በዝቋላ ገዳም ደን ላይ ለደረሰው የእሳት አደጋ የገንዘብና የቁሳቁስ ድጋፍ ተደረገ፡፡

መጋቢት 18/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን አብርሃም አንዳርጌ

•    እሳቱ መጥፋቱ የተገለጠ ሲሆን የእሳት አደጋን ለመከላከል የሚያስችል ቋሚ ጥናትም ተጀምሯል፡፡


በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት የሚገኘው የዝቋላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ደን ምሥራቃዊ ክፍል መቃጠሉን ተከትሎ ከሀገር ውስጥ እና ከውጭ የሚገኙ ምእመናን የገንዘብና የቁሳቁስ ድጋፍ መደረጉ ተገለጸ፡፡

 

ቃጠሎውን ተከትሎ ከአካባቢው በአቅራቢያው ከሚገኙ ከተማዎች ምእመናን ወደ ቦታው በመሔድ እሳቱን ለማጥፋት ጥረት አድርገዋል፡፡ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ በቦታው በመገኘት ቡራኬ ሰጥተው ምእመናን የሚያከናውኑትን ሥራ አበረታተዋል፡፡ እንዲሁም በማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ በቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ሥዩም የተመራ ልዑክ ሰኞ ቃጠሎው እንደተሰማ አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት በቦታው በመገኘት ጊዜያዊ የውኃ፣ የዳቦና የገንዘብ ድጋፍ ለገዳሙ እንዲደረግ በማስተባበር እሳቱን የማጥፋቱን ሥራ ለማከናወን ተችሏል፡፡

 

ባጠቃላይ በገዳሙ ላይ ለደረሰው ጉዳትና ለዘለቄታው መፍትሔ ጥናት ለማድረግ ከ171,860 ብር በላይ የሚጠጋ ገንዘብና ቁሳቁስ በማኅበረ ቅዱሳን አማካይነት ከአሜሪካ ማዕከል፣ ከአሜሪካ ማኅበረ ባለወልድ ከሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነትና ከሀገር ውስጥ የተሰበሰበ ሲሆን ከ85 ሺ ብር በላይ ወጪ በማድረግ ጊዜያዊ የምግብና የመጠጥ ውኃ አቅርቦት ሥራ ተከናውኗል፡፡ በቀረውና ወደፊትም ለቋሚ ፕሮጀክቶች ጥናት በሚሰበሰበው ገቢ በዝቋላና በአሰቦት ገዳማት ዘላቂ የመከላከልና የልማት ሥራ ለማከናወን የጥናት ሥራዎቹ መጀመራቸው ታውቋል፡፡

 

በወቅቱ ለተፈጠረው ችግር በሶ፣ ስኳር፣ ከ2000 ሊትር በላይ ውኃ፣ 16 ገጀራና 15 ዶማ ጨምሮ ሌሎች እርዳታዎችን በመሰብሰብ እንዲሁም ከ20 ኩንታል ጤፍ ጋር ለገዳሙ ገቢ ተደርጓል፡፡ ይህም በገዳሙ ውስጥ ለተፈጠረው የምግብ እጥረት መፍትሔ እንደሚሰጠው ታምኖበታል፡፡

 

እሳቱን ለማጥፋት በተደረገው ጥረት የማኅበረ ቅዱሳን አባላትን ጨምሮ በናዝሬት ማአከል አስተባባሪነት ሰባት አውቶብስ የአዳማ ዩንቨርሲቲ ተማሪዎች፣ የደብረ ዘይት አየር ኀይል አባላት የኦሮሚያ ፖሊስ፣ የፌደራል ልዩ ኀይል፣ የአዲስ አበባ፣ አድማ፣ ደብረ ዘይት፣ ሞጆና አካባቢው ምእመናን ቦታው ድረስ በመገኘት ሰፊ እንቅስቃሴ አድርገዋል፡፡

 

በዚህም እሳቱን በቁጥጥር ሥር ማዋል የተቻለ ሲሆን ባጠቃላይ በገዳሙ ላይ ዘላቂ ልማት እንደሚከናወን ለማወቅ ተችሏል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ዘላቂ የመከላከልና የልማት ሥራዎችን ለመጀመር በትናንትናው ዕለት አምስት ባለሙያዎች የያዘ የጥናት ቡድን ወደ ዝቋላ ገዳም የላከ ሲሆን ከገዳማውኑ ጋር በመወያየት በሚወሰነው አቅጣጫ መሠረት ሥራው ይጀመራል፡

 

በዚሁ አጋጣሚ ዘላቂ አደጋን የመከላከልና የልማት ሥራዎችን ለመደገፍ የምትፈልጉ ሁሉ የማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናትና አብነት ትምህርት ቤቶች መርጃና ማቋቋሚያ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አራት ኪሎ ቅርንጫፍ፣ የአካውንት ቁጥር 01730604664000፣ በመጠቀም የምትችሉ መሆኑነ ማኅበሩ አስታውቋል፡፡