baba shenouda

‹‹ትእዛዝህ ከጠላቶቼ ይልቅ አስተዋይ አደረገኝ›› መዝ 118፥98 ፤ በእንተ ቅዱስነታቸው አቡነ ሲኖዳ

መጋቢት 25/2004 ዓ.ም.

በአያሌው ዘኢየሱስ


/ይህ ጽሑፍ ካይሮ በሚገኘው የአሜሪካ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ ፕሮፌሰር የሆኑት ዶክተር አቶ ሜናርደስ “የግብጽ የሁለት ሺህ ዓመት ክርስትና” በሚል ርዕስ ካዘጋጁት መጽሐፍ የተወሰደ ሲሆን የጽሑፍን የአርትኦት ሥራ ያከናወኑት አባ አውጉስጢኖስ ሐና ናቸው፡፡ የዘመን አቆጣጠሩ እንደ አውሮፓውያን ቀመር ነው፡፡/


baba shenoudaየግብጽ ቤተ ክርስቲያን ወደ ሃያኛው መቶ ክፍለ ዘመን ሁለተኛ አጋማሽ ለመዝለቅ ያሳየችው ያልተጠበቀ መነቃቃት በዓለም የክርስትና እምነት ውስጥ ታላላቅ ከሚባሉት ታሪኮች መካከል አንዱ ነበር፡፡ በአብዛኛው የዓለም ክፍል ውስጥ ወንዶቹና ሴቶቹ የግብጽ ልጆች /ፈርዖኖች/Pharaohs/ በቤተ ክርስቲያናቸው አማካይነት የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመመሥረትና ወንጌልን ለማስፋፋት ያሳዩት ትጋት ተሰምቶ የማይታወቅ ነበር፡፡

ይህ መንፈሳዊ መንሠራራት ጅምሩን ያደረገው ግን ከግማሽ ምእተ ዓመት በፊት ሲሆን ይህም በአሥራ ዘጠኝ አርባዎቹና በአሥራ ዘጠኝ ሀምሳዎቹ በካይሮ፣ በጊዛና በአሲዩት በሚገኙ የቅብጥ/coptic/ የሰንበት ትምህርት ቤቶች እንቅስቃሴ ውስጥ ነበር፡፡ በሰንበት ትምህርት ቤቶች ውስጥ በሚደረጉ ትምህርታዊ ውድድሮች የተነሣሱት ወጣት ወንዶች ሕይወታቸውን ለእግዚአብሔር በመቀደስ፥ በበረሀ የሚኖሩ አባቶቻቸውን ለመከተል ወደዚያው ወጥተዋል፡፡ እነዚህ ወጣቶች በተለይም በሶርያውያን ገዳም ውስጥ በሚገኙት በአባ ቴዎፍሎስ /Bishop Theophilus/ ብቃት ያለው አመራር አማካይነት ለቤተ ክርስቲያናቸው የማነቃቃት ሥራ ለመሥራት ራሳቸውን አዘጋጁ፡፡

 

በ1959 ዓ.ም. አቡነ ቄርሎስ 6ኛ ፓትርያርክ ሆነው ከተሾሙ በኋላ የቀድሞዎቹ የሰንበት ትምህርት ቤት አገልጋዮች ከነበሩት መምህራን፣ መነኮሳትና ባሕታውያን መካከል ጥቂቶቹ ወደ መንበረ ፓትርያርክ ተጠርተው በቤተ ክርስቲያኒቱ ሕይወትና አደረጃጀት ውስጥ ቁልፍ የሓላፊነት ሥልጣን እንዲጨብጡ ተደረገ፡፡ ከእነዚህ ወጣቶች መካከል አቡነ እንጦንስ አል ሱሪያኒ /1954-2012//Fr. Antonyos (Anthony) El-Souryani/፣ በኋላም ሲኖዳ ተብለው የቅብጥ ቤተ ክርስቲያን የሥነ መለኮትና የትምህርት ተቋማት ጳጳስ /1962-71/ የተባሉትና በመጨረሻም አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ በሚል ስም የተሾሙት የአሁኑ ጳጳስና ፓትርያርክ የቀድሞው ናዚር ጋዪድ (Nazir Gayyid) ናቸው፡፡ የአቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ የጵጵስና ሕይወት በታላቅ ጥረትና ጥልቀት ባለው መንፈሳዊነት የተቃኘ ስለ ነበር ሕይወቱን ለማጣት ተቃርቦ ለነበረው የስብከት ተቋም አዲስ ራእይና ሕይወት በመስጠት ስኬታማ ሊሆን ችሏል፡፡ ይህ በመሆኑም ከፍተኛ ወግ ተሰጥቶአቸው የነበሩትና ከተመሠረቱ ረዥም ጊዜያት ያስቆጠሩትን የቤተ ክርስቲያን ሥርዓቶችን ያዝ በማድረግ በአዲስ መንፈሳዊ ስሜት እንዲሞሉ አድርጓል፡፡

 

የአቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ መንፈሳዊና ትምህርታዊ መነሻ አሁን ያለውን የቤተ ክርስቲያኒቷን የእንቅስቃሴ አቅጣጫ በስፋት የወሰነ ነው፡፡ ናዚር ጋዪድ /የአቡነ ሲኖዳ የመጀመሪያ የቤተሰብ ስማቸው ነው/ ሹብራ(Shubra) በሚገኘው የቅዱስ እንጦንስ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሰንበት ትምህርት ቤት አባል የሆኑት ገና በ16 ዓመታቸው ነበር፡፡ በኋላ ግን የዚሁ ሰንበት ትምህርት አስተማሪ በመሆን በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣት ግብጻውያንን በኢየሱስ ክርስቶስ እንዲያምኑ አድርገዋል፡፡

 

ናዚር ጋዪድ በብዙ መንገድ በላይ በቅብጥ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ለተቋቋመው አዲስ የወጣቶች አገልግሎት አጠቃላይ መሪ ሆነዋል፡፡ በ1947 ዓ.ም. በካይሮ ዩኒቨርሲቲ በእንግሊዝኛና በታሪክ የቢ.ኤ. (B.A.) ዲግሪያቸውን ተቀብለዋል፡፡ እስከ አሁን ድረስ ንግግራቸው፣ ስብከታቸውና መጻሕፍቶቻቸው እንከን የማይወጣላቸው የእንግሊኛ ቋንቋ ተጠቃሚ መሆናቸውን ያንጸባርቃሉ፡፡ በሥነ መለኮት ኮሌጅ ውስጥ የተሰጡትን ጥናቶች ብሩህ በሆነ የትምህርት ብቃት ስለ ፈጸሙ በዚያው ኮሌጅ ውስጥ የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መምህር ሆነው ለመሾም በቅተዋል፡፡ ከዚህ በኋላ 1953 ዓ.ም. ሄልዋን (Helwan) በሚገኘው የምንኩስና ኮሌጅ ውስጥ የሙሉ ሰዓት አስተማሪ ሆነው ተመድበዋል፡፡

 

ሐምሌ 19 ቀን 1954 ዓ.ም. በሶሪያውያን ገዳም ውስጥ በሚገኙት በጳጳስ ቴዎፍሎስ (Bishop Tawfilus) አማካይነት ምንኩስናን ተቀብለዋል፡፡ በዚህ ዕለት ናዚር ጋዪድ የሚከተለውን ቃል ኪዳን ፈጽመዋል፡-

 

ምንኩስና ማለት ሀብትና ንብረትን፤ ዘመዶችንና ጓደኞችን፤ ሹመትንና ሥልጣንን አስመልክቶ ለዓለም ሙሉ ለሙሉ መሞት መሆኑን አረጋግጣለሁ፡፡ ምንኩስና የአምልኮና ራስን ለእግዚአብሔር የመስጠት ሕይወት መሆኑን አረጋግጣለሁ፡፡ የንስሓ፣ራስን የመተው፣ ፍጹም የመታዘዝ፣ የብቸኝነትና የድህነት ሕይወት መሆኑንም አረጋግጣለሁ፡፡ በእግዚአብሔር በመላእክቱና በቅዱስ መሠዊያው ፊት እንዲሁም ቅዱስ አባቴ በሆኑት በጳጳሱ ፊት፤ በተሰበሰቡ አባቶች ፊት፤ በመነኮሳት ፊት እና በዚህ ቅዱስ ጉባኤ ፊት ከዓለም ተለይቼ በድንግልና እና በንጽሕና እኖር ዘንድ ሕይወቴን ለእግዚአብሔር አቀርባለሁ፡፡ እውነተኛውን የምንኩስና ሥርዓት ለመቀበልና ቅዱሳን አባቶቻችን ለእኛ ያስቀመጡልንን ይህን መላእክታዊ የሕይወት ጠባይ ለመከተል ቃል እገባለሁ፡፡ ይህ ከሆነ ከአንድ ዓመት በኋላ ክህነትን ተቀብለዋል፡፡ ካህን፣ ጳጳስና ፓትርያርክ ሆነው በኖሩበት የሕይወት ዘመናቸው በሶሪያውያን ገዳም ውስጥ በምትገኘው የድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን የገቡትን ቃል ኪዳን እስከ አሁን ድረስ በታማኝነት ጠብቀዋል፡፡

 

በገዳሙ ውስጥ የቤተ መጻሕፍቱ ሓላፊ ሆኖ አገልግለዋል፡፡ እነዚህ ሥራዎች ጥናታቸውን በቤተ ክርስቲያን አባቶችና ሐኪሞች ላይ እንዲያደርጉ አስችለውታል፡፡ ይህ ይሁን እንጂ እርሳቸው ይናፍቁ የነበረው የብቸኝነትን ሕይወት ነበር፡፡ በመሆኑም በመጀመሪያ የመረጡት ከገዳሙ በሦስት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የሚገኘውን ዋሻ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ይህንን የባሕታዊ መኖሪያ ከገዳሙ አሥር ኪ.ሜ. ርቀት ላይ በሚገኘው ባኸር አል ፋራይ (Bahr al-Farigh) ዋሻ እንዲለውጡ ሆነዋል፡፡ በ1984 ዓ.ም. መግቢያ ላይ “ባሕታዊው” በሚል ርዕስ የጻፉት ግጥም በ1954 ዓ.ም. በሰንበት ትምህርት ቤቱ መጽሔት ላይ ታትሞ ወቷል፡፡

 

ከመጽሔቱ የተወሰደ፡-

ብቻዬን በበረሀ ውስጥ የራሴን ነገር እየሰላሰልሁ፤

በተራራው ጫፍ  ባለ ዋሻ ገብቼ ተከልያለሁ፤

እና አንድ ቀን ትቼው እሔዳለሁ፤

የምኖርበትን ወደማላውቀው፡፡


በ1959 ዓ.ም. ፓትርያርኩ ቄርሎስ 6ኛ የግል ጸሐፊያቸው አድርገው ቢሾሟቸውም አባ እንጦንዮስ የመረጡት የብቸኝነት ሕይወት ነበር፡፡ አባ እንጦንስ ለብዙ ዓመታት የጵጵስና ማዕረግ እንዲቀበሉ የተለያዩ ጫናዎች ቢደረጉባቸውም ሁሉንም በተሳካ ሁኔታ ሊከላከሉ ችለዋል፡፡ ይሁን እንጂ በመስከረም ወር 1962 ዓ.ም. ፓትርያርኩ አቡነ ቄርሎስ በገዳሙ ውስጥ አለመግባባት ስለ ፈጠሩት ጥቂት የአስተዳደር ነክ ጉዳዮች ከባሕታዊው ከአባ እንጦንስ ጋር ለመወያየት በሚል ካይሮ ወደሚገኘው መንበረ ፓትርያርክ እንዲመጡ ያስጠሯቸዋል፡፡ አባ እንጦንስ በፓትርያርኩ ፊት ተንበርክከው ይቅርታ በመጠየቅና ከአስተዳደር ሥራ እንዲለዩ በማሳሰብ ለጥያቄያቸው መልስ በመጠባበቅ ላይ ሳሉ ፓትርያርኩ ቄርሎስ እጆቻቸውን በባሕታዊው ራስ ላይ በመጫን የቅብጥ ቤተ ክርስቲያን የሥነ መለኮት እና የትምህርት ተቋማት ጳጳስ አድርገው ይሾሟቸዋል፡፡

 

ይህ ሹመት በመንበረ ፓትርያርኩ መስከረም 30 ቀን 1962 ዓ.ም. ተሰጠ፡፡ ከዚህ በኋላ እኔ ራሴ /የዚህ ጽሑፍ ጸሐፊ/ “እንኳን ደስ አልዎ” በማለት ለአቡነ ሲኖዳ ለጻፍኩላቸው ደብዳቤ የጻፉልኝ የመልስ ደብዳቤ ከዚህ የሚከተለው ነው፡-

 

“ከአምላካችንና ከመድኀኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የሆነ ጸጋና ሰላም ለአንተ ይሁን፡፡ ወደ እኔ ስለላክሃቸው የ”እንኳን ደስ አልዎ” መልካም ቃላት አመሰግንሃለሁ፡፡ ወዳጅነትህንና ፍቅርህን በጭራሽ ልዘነጋ አልችልም፡፡ እውነቱን ለመናገር ግን አሁን ለገጠመኝ ሁኔታ የሚገባኝ የማጽናኛ ደብዳቤ እንጂ የእንኳን ደስ ያለህ ደብዳቤ አልነበረም፡፡ አንድ መነኩሴ የበረሀውን ፀጥታ ትቶ በከተማ ሁከት ለመታጀብ በመሔዱ እንዴት እንኳን ደስ ያለህ ሊባል ይችላል? ማርያም ከክርስቶስ እግር አጠገብ ያለ ቦታዋን ትታ ከማርታ ጋር በኩሽና ለመገኘት በመሔዷ እንኳን ደስ አለሽ የሚላት ማነው? በእርግጥም ይህ ለእኔ በጣም የሚያሳፍር ነገር ነው፡፡ ለጵጵስና የተመረጥሁባትን ያቺን ቀን የማስታውሳት በዕንባና በሰቆቃ ነው፡፡ እውነቱን ለመናገር ግን የብቸኝነትና የተመስጦ ክብር ከመናገር በላይ ነው፡፡ ከኤጲስ ቆጶስነትና ከጳጳስነት ጋር አይነጻጸርም፡፡ ውድ ወዳጄ ሆይ፤ እውነተኛው መቀደስ ልብን ለእግዚአብሔር ቅዱስ ቤተ መቅደስ አድርጎ መቀደስ ነው፤ እርሱ በመጨረሻው ቀን የሚጠይቀን የእረኝነት ማዕረጋችንን ሳይሆን የልባችንን ንጽሕና ነውና፡፡ ይህን ደብዳቤ የጻፍሁልህ ከምወደውና ዋዲ አል-ንጥራን (Wadi al-Natrun) ውስጥ ከሚገኘው ከባሕር አል ፋራይ (Bahr al-Farigh) ዋሻ ሆኜ ነው፡፡ ወደ ካይሮ ከመመለሴ በፊት የምቆየውና የጥምቀትን በዓል የማከብረው በዚህ ዋሻ ውስጥ ነው፡፡››

 

ይሁን እንጂ በተገኘው አመቺ ጊዜ ሁሉ ጳጳሱ አባ ሲኖዳ የሚሔዱት ወደዚህ ገዳም ነው፡፡ በክርስቲያን የትምህርት መስክ ውስጥ የአቡነ ሲኖዳ አመራር ዋጋውን ያገኘው በ1969 ዓ.ም. የመካከለኛው ምሥራቅ የሥነ መለኮት ኮሌጆች ኅብረት ፕሬዝዳንት (President of the Association of Middle East Theological Colleges) ሆነው ሲመረጡ ነው፡፡ የአቡነ ሲኖዳ እጅግ ጠቃሚ የአገልግሎት ዘርፍ በየሳምንቱ የሚያቀርቧቸው ስብከቶች አቀራረብ ሲሆን በዚህም ለሥነ መለኮታዊና ለማኅበረሰባዊ ጥያቄዎች መልስ ሰጥተዋል፡፡ በሺዎች የሚቆጠሩ ወጣቶችም የዚህ አገልግሎት ተሳታፊዎች ሆነዋል፡፡ አቡነ ሲኖዳ የሳምንቱን እኩሌታ በካይሮና በእስክንድርያ በማስተማርና በመስበክ ከቆዩ በኋላ የሳምንቱን እኩሌታ የሚያሳልፉት በዚህ ገዳም ውስጥ ነው፡፡

 

በእነዚህ ዓመታት ውስጥ ከቅብጥ ቤተ ክርስቲያን ዓላማዎች አንዱ ለመቶ ዓመታት አብሯት ከቆየው የሥነ መለኮት ልዩነት ራስዋን ነጻ ማውጣት ነበር፡፡ አቡነ ሲኖዳ ቤተ ክርስቲያናቸውን በመወከል ብዛት ባላቸው የአብያተ ክርስቲያናት ኅብረት ጉባኤዎች ላይ ተሳትፈዋል፡፡ የትምህርት ጳጳስ ሳሉ ለመጨረሻ ጊዜ የተሳተፉበት ጉባኤ በ1971 ዓ.ም. ቪየና ውስጥ በምሥራቃውያን ኦርቶዶክስና በካቶሊካውያን አብያተ ክርስቲያናት መካከል የተደረገው የመጀመሪያው ጠቃሚ የምክክር ጉባኤ ነው፡፡ ይህ የሆነው የእስክንድርያ ፓትርያርክ ሆነው ሊሾሙ ልክ አንድ ወር ሲቀራቸው ነበር፡፡ በዚህ ጉባኤ ላይ አቡነ ሲኖዳ የእስክንድርያው ቅዱስ ቄርሎስ ያዘጋጀውን የክርስቶስ ትምህርት ተቀባይነት እንዲያገኝ አድርገዋል፡፡ ይህ አንቀጽ ኋላ ላይ በሮማው ጳጳስ በዮሐንስ ጳውሎስ አራተኛና በአቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ በይፋ ተቀባይነትን አግኝቷል፡፡

 

ተቀባይነት ያገኘውና የእስክንድርያው ቅዱስ ቄርሎስ ስለ ክርስቶስ ያስተማረው ትምህርት አንቀጽ የሚከተለው ነው፡-

“እኛ ሁላችን አምላካችን እግዚአብሔር መሆኑንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋ የለበሰው ቃል መሆኑን እናምናለን፡፡ እርሱ በመለኮቱና ሰው በመሆኑ ፍጹም እንደሆነ እናምናለን፡፡ አምላክነቱ ከሰውነቱ ለቅጽበት እንኳ እንዳልተለየም እናምናለን፡፡ ሰው መሆኑ ከመለኮቱ ጋር ያለ መቀላቀለ፣ ያለ መለወጥ፣ ያለ መከፋፈልና ያለ መለያየት የሆነ ነው፡፡”


ፓትርያርኩ አቡነ ቄርሎስ አራተኛ መጋቢት 9 ቀን 1971 ዓ.ም. በሞተ ሥጋ ሲለዩ ቅዱስ ሲኖዶሱ ማርች 22 ቀን 1971 ዓ.ም. ተከታዩን ፓትርያርክ ለመምረጥ ዝግጅት ማድረግ እንዳለበት ወሰነ፡፡ ጥቅምት 29 ቀን 1971 ዓ.ም. ይፋ የነበረው ምርጫ ከአምስት ወደ ሦስት እጩዎች ዝቅ አለ፡፡ ከዚህ በኋላ አይማን ሙኒር ካሚል የተባለና ዐይኖቹ በጨርቅ የታሰሩ አንድ ልጅ የዕጩዎቹ ጳጳሳት ስሞች ተጽፈውባቸው ከተጠቀለሉት ቁርጥራጭ ወረቀቶች መካከል አንዱን በማንሣት ለከተማዋ ጳጳስ ለእንጦኒዮስ ሰጠ፡፡ እርሳቸውም ለቅብጥ ቤተ ክርስቲያን እረኛ ይሆን ዘንድ የተመረጠው ጳጳሱ ሲኖዳ መሆኑን በይፋ አስታወቁ፡፡ ከሁለት ሳምንታት በኋላ ኅዳር 14 ቀን 1971 ዓ.ም. ጳጳሱ ሲኖዳ “ቅዱስነታቸው አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ በማርቆስ መንበር 117ኛው ፓትርያርክ” ተብለው በይፋ ተሰየሙ፡፡

 

ምንም እንኳን ጳጳስና ፓትርያርክ ቢሆኑም በሥነ መለኮት ኮሌጅና በቅብጥ ጥናት ከፍተኛ ተቋም ውስጥ ማስተማራቸውን አላቋረጡም፡፡ በመሆኑም በታሕታይ ግብጽና በላዕላይ ግብጽ ውስጥ ቅርንጫፍ የሆኑ ስድስት ተጨማሪ የሥነ መለኮት ኮሌጆች ሲከፈቱ ሌሎች ተጨማሪ ሦስት ኮሌጆች በዩናይትድ ስቴትስ አሜሪካና በአውስትራሊያ ተመሠረቱ፡፡

 

እንደ ሊቅነታቸው አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ በቅብጥ ላይ የሚደረጉ የተለያዩ ጥናቶችን አበረታተዋል፤ በዚህም ታላቁ የቅብጥ ኢንሳይክሎፒዲያ እንዲታተም አድርገዋል፡፡ በሚያዝያ ወር 1988 ዓ.ም. በመንበረ ፓትርያርኩ ውስጥ ያለው የቅብጥ መዝገብ ቤት በማይክሮ ፊልም እንዲነሣ አል አህራም (Al-Ahram) ከተባለ የዜና ድርጅት ጋር ኮንትራት ተፈራርመዋል፡፡

 

የቤተ ክርስቲያኗ የበላይ ጠባቂ በመሆናቸው ከ80 የሚበልጡ ጳጳሳትንና ከ500 የሚበልጡ ካህናትን ግብጽ ውስጥ ለምትገኘው ለቅብጥ ቤተ ክርስቲያንና በውጪ ለሚኖሩ የቅብጥ አብያተ ክርስቲያናት አማኞች ሾመዋል፡፡ በየጊዜው ከካህናቱ አባላት ጋር የሚያደርጓቸው ሴሚናሮች የካህናቱንና የጳጳሳቱን የእረኝነቱን፣ የመንፈሳዊነቱንና የትምህርቱን ሕይወት አበረታትዋል፡፡ እርሳቸው ለወጣቱ ትውልድ ልዩ ትኩረት ስለሰጡ በአቡነ ሙሳ የበላይ ሓላፊነት በጣም ድንቅ የሆነ የወጣቶች የአገልግሎት ዘርፍ እንዲቋቋም አድርገዋል፡፡ ታይቶ የማይታወቅ የአብያተ ክርስቲያናት ቁጥር በተለይም በውጪ ሀገራት እየጨመረ ስለመጣ አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ መጠኑ የበዛ ቅዱስ ሜሮን ወይም የምሥጢር ዘይት በ1981፣ በ1983፣ በ1993 እና በ1995 ዓ.ም. በቅዱስ ቢሶይ ገዳም ውስጥ ባርከዋል፡፡ የክርስቲያኖች አንድነት እንዲኖር ጥልቅ ፍላጎት ስለነበራቸው የተሻለ የምክክር መግባባት ይፈጠር ዘንድ ሰፊ ጊዜና ጥረት አድርገዋል፡፡ በክርስቲያኖች አንድነት ላይ ምንጊዜም አጽንዖት ሰጥተው የሚናገሩት የክርስቲያኖች አንድነት ሊመሠረት የሚገባው በእምነት ላይ እንጂ በሥልጣን ላይ አለመሆኑን ነው፡፡ እስከ ዛሬ ድረስ በምሥራቅ ኦርቶዶክስ፣ በሮማ ካቶሊክ፣ በአንጀሊካን፣ በፕሬስባይቴሪያን፣ በስዊድን ሉተራን እና በተሐድሶ አብያተ ክርስቲያናት መካከል የሥነ መለኮት ውይይት እንዲደረግ አነሣሥተዋል፡፡

 

ይህ በመሆኑም በግንቦት ወር 1973 ዓ.ም. አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ በሮማው ጳጳስ በጳውሎስ 6ኛ ጥሪ ሮምን እንዲጎበኙ ተጋብዘው ነበር፡፡ ከ451 ዓ.ም. በኋላ በአንድ እስክንድርያዊና በአንድ ሮማዊ ጳጳስ መካከል እንዲህ ያለው ግንኙነት ሲደረግ ይህ የመጀመሪያው ነው፡፡ በዚህ ግንኙነት ሁለቱም በክርስቶስ ላይ ያላቸውን የጋራ እምነት በፊርማቸው አጽድቀዋል፡፡ በ1979፣ በ1987 እና በ1995 ዓ.ም. አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ ከካንተርበሪ ሊቀ ጳጳስ (Archbishop of Canterbury) ጋር ተገናኝተው በቅዱሳት መጻሕፍት ላይ ያላቸውን የጋራ ግንዛቤ ተወያይተዋል፡፡ በኖቬምበር ወር 1988 ዓ.ም. ደግሞ በቅብጥና በፕሬስባይቴሪያን አብያተ ክርስቲያናት መካከል የሥነ መለኮት ክርክር እንዲካሔድ አበረታተዋል፡፡ ይህ ክርክር በመካከለኛው ምሥራቅ በሚገኙ ኦርቶዶክሶችና ፕሮቴስታንቶች መካከል ተፈጥረው የነበሩትን አንዳንድ የሥነ መለኮት የአመለካከት ችግሮት ለማስታረቅ መንገዱን ጠርጓል፡፡

 

ከሌሎች የኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት ጋር ያለውን ግንኙነት በተመለከተ አቡነ ሲኖዳ ሳልሳዊ በደማስቆ፣ በኢስታንቡል፣ በሞስኮ፣ በቡካሬስትና በሶፊያ ያሉትን የኦርቶዶክስ መንበረ ፓትርያርኮች ጎብኝተዋል፡፡ በመካከለኛው ምሥራቅ ታላቅ በአፍሪካም ጥንታዊት የሆነችው ቤተ ክርስቲያን መሪ እንደመሆናቸው መጠን ቤተ ክርስቲያናቸው በመካከለኛው ምሥራቅ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት እና ከመላው አፍሪቃ አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ጋር ላላት ተሳትፎ ልዩ ትኩረት ሰጥተዋል፡፡

 

በየካቲት ወር 1991 ዓ.ም. በካንቤራ አውስትራሊያ በተካሔደው በ7ኛው የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ጉባኤ ላይ ለመገኘት አሥራ አንድ የቅብጥ አባላትን ያካተተውን የልዑካን ቡድን መርተዋል፡፡ በስብሰባው ማብቂያ ላይ ከዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዘዳንቶች መካከል አንዲ ሆነው ተመርጠዋል፡፡ በኅዳር ወር 1994 ዓ.ም. ቆጵሮስ (Cyprus) ውስጥ በተካሔደው ስብሰባ ላይ ደግሞ የመካከለኛው ምሥራቅ አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት አራት ፕሬዘዳንቶች መካከል አንዱ ሆነው ተመርጠዋል፡፡ ምንም እንኳ የዓለም የክርስትና እምነትን ለማገልገል ሰፊ ጊዜያቸውን መሥዋዕት አድርገው ቢያቀርቡም ሲኖዳ ሳልሳዊ በልባቸው መነኩሴ መሆናቸው አልቀረም ነበር፡፡

 

ከዚህ ሌላ በመካከለኛው መቶ ክፍለ ዘመን ከሰው የተራቆቱ ብዛት ያላቸው ገዳማት እንዲታደሱና ተመልሰው እንዲገነቡ መሣሪያ ሆነው ቆይተዋል፡፡ የጵጵስና መኖሪያቸው የተመሠረተው ቅዱስ ቢሶይ ገዳም ውስጥ ነው፡፡ ይህ መኖሪያቸው በውስጡ የጸሎት ቤት፣ የስብሰባና የስብከት አዳራሾችን እና እንግዳ መቀበያ ክፍሎች ያካተተ ነው፡፡ አቡነ ሲኖዳ ሳልሳዊ የእያንዳንዱን ሳምንት እኩሌታ በተመስጦና በአርምሞ የሚያሳልፉት በዚህ ገዳም ውስጥ ነው፡፡

 

በ1971 ዓ.ም. ከግብጽ ውጪ ለሚኖሩ ግብጻውያን የነበሩት የቅብጥ አብያተ ክርስቲያናት ሰባት ብቻ ነበሩ፡፡ ዛሬ ግን በዩናይትድ ስቴትስና በካናዳ ብቻ አንድ መቶ፣ በአውስትራሊያ ሃያ ስድስት በአውሮፓ ደግሞ ከሠላሳ የሚበልጡ አብያተ ክርስቲያናት አሉ፡፡ በውጪ ሀገራት በሚገኙ በእነዚህ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ የሚያገለግሉ አሥራ አምስት የቅብጥ ጳጳሳትም አሉ፡፡

 

በ1994 ዓ.ም. በእንግሊዝ ደሴቶች (British Isles) ላይ የሚኖሩና አሥራ ዘጠኝ የሚደርሱ የእንግሊዝ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሀገረ ስብከቶች ከቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጋር ሙሉ ኅብረት ፈጥረዋል፡፡ በ1994 ዓ.ም. በተከበረው የበዓለ አምሳ ላይ አባ ሱሪፌል የግላስተንበሪ (Glastonbury) ጳጳስ ሆነው ተሾመዋል፡፡ ኤርትራ የራስዋን መንግሥት ካቋቋመችና አቶ ኢሳይያስ አፈወርቂ የኤርትራ ፕሬዝዳንት ሆነው ከተመረጡ በኋላ በመንበረ ማርቆስ የስብከት አሰጣጥ ደንብ የሚመራ ነጻ የኤርትራ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን እንዲቋቋምላቸው አቡነ ሲኖዳ ሳልሳዊን ጠይቀዋል፡፡ ከዚህ በኋላ የቅብጥ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ቅዲስ ሲኖዶስ መስከረም 28 ቀን 1993 ዓ.ም. ባካሔደው ስብሰባ የኤርትራውያን ክርስቲያኖችን ጥያቄ ለመቀበል ተስማምቷል፡፡ በዚህ መሠረት 1994 ዓ.ም. በዋለው በዓለ ሀምሳ አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ አምስት ኤርትራውያን ጳጳሳትን በመሾም የኤርትራውያንን የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ነጻ ሲኖዶስ ለመመሥረት መሠረት አስቀመጡ፡፡ ግንቦት 7 ቀን 1998 ዓ.ም. ቅዱስነታቸው አቡነ ሲኖዳ የ93 ዓመቱን ጳጳስ አቡነ ፊልጶስን የኤርትራ የመጀመሪያው ፓትርያርክ በማድረግ ሾሙ፡፡ ካይሮ በሚገኘው የቅዱስ ማርቆስ ካቴድራል ውስጥ በዓለ ሲመቱ ሲከናወን ከሀምሳ የሚበልጡ የቅብጥ ጳጳሳትና ሰባት የኤርትራ ጳጳሳት ተገኝተው ነበር፡፡

 

አስቀድመን ካነሳነው ተጋድሎአቸው መካከል፥ ፕሬዝዳንት አንዋር አል ሳዳት አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊን በትክክል ባለመረዳት በተደጋጋሚ ከሰዋቸው እንደነበር ነው፡፡ በተለይም አቡነ ሲኖዳ ግንቦት 14 ቀን 1980 ዓ.ም. በፓርላማው ፊት ያሰሙት ንግግር በቅብጥ ቤተ ክርስቲያንና በግብጽ መንግሥት መካከል ያለውን የፖለቲካ አየር ክፉኛ በከለው ተባለ፡፡ ይህ አሳዛኝ ሁኔታ ተደማምሮ መስከረም 3 ቀን 1981 ዓ.ም. ፕሬዝዳንት ሳዳት ከቤተ መንግሥት ባስተላለፉት ትእዛዝ መሠረት አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ በቅዱስ ቢሾይ ገዳም በግዞት እንዲቀመጡ አደረጉ፡፡ ከዚህ በተመሳሳይ ጊዜ ስምንት ጳጳሳት፣ ሃያ አራት ቀሳውስትና ሌሎች እውቅና ያላቸው ብዙ የቅብጥ ቤተ ክርስቲያን አባላት ታሠሩ፡፡ ሳዳት ይህን ካደረጉ በኋላ አምስት ጳጳሳትን ያቀፈ አንድ የቅብጥ ቤተ ክርስቲያን የአስተዳደር ኮሚቴ አዘጋጁ፡፡ ቅዱስ ሲኖዶሱ ግን የቅብጥ ቤተ ክርስቲያን መሪ አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ መሆናቸውን በአጽንዖት አረጋገጠ፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ፕሬዝዳንት ሳዳት አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊን ይጠሩ የነበረው “የቀድሞው ፓትርያርክ” እያሉ ነበር፡፡

 

አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ በቅዱስ ቢሶይ ገዳም በግዞት ሳሉ ዓለም አቀፉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች አምነስቲ ኢንተርናሽናል (Amnesty International) “የኅሊና እስረኛ” (‘Prisoner of Conscience’) በማለት ነሐሴ 26 ቀን 1983 ዓ.ም. በይፋ ሰይሟቸዋል፡፡ በዓለም ዙሪያ የሚኖሩ ብዛት ያላቸው ክርስቲያኖች ጥልቅ ሃዘናቸውን ገልጠዋል፡፡ ይፈቱ ዘንድ በሰኔ ወር 1982 ዓ.ም. እና በኅዳር ወር 1984 ዓ.ም. ልዩ የጸሎት መርሐ ግብር ተደርጎላቸዋል፡፡ የጊዛው ጳጳስ ዱማዴዎስ የቀድሞ ባልንጀራቸውን በየሳምንቱ ይጠይቋቸው ነበር፡፡ ፕሬዝዳንት ሳዳት ነሐሴ 3 ቀን 1981 ዓ.ም. ያስተላለፉትን የግዞት ትእዛዝ ፕሬዝዳንት ሙባረክ ታኅሣሥ 2 ቀን 1985 ዓ.ም. ሻሩት፡፡ አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ ከስደት ዓመት ከአራት ወራት ግዞት በኋላ ታኅሣሥ 4 ቀን 1985 ዓ.ም. በአሥራ አራት ጳጳሳት ታጅበው ወጡ፡፡ በሚቀጥለው ቀን የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን የልደት በዓል በቅዱስ ማርቆስ ካቴድራል ሲያከብሩ ከአሥር ሺህ የሚበልጥ ሕዝብ ተገኝቶ ፓትርያርኩን ተቀብሏል፡፡

 

ከዚህ በኋላ በመንግሥትና በቤተ ክርስቲያን መካከል ያለው ግንኙነት አመርቂ በሆነ መልኩ ተሻሻለ፡፡ ከብዙኀኑ የእስልምና እምነት ተከታዮች ጋር ስለ ተፈጠረው መልካም ግንኙነት ምስክር የሚሆነው በረመዳን የጾም ወር ውስጥ ቅዱስነታቸው አቡነ ሲኖዳ ሣልሳዊ በፖለቲካውና በሃይማኖቱ ውስጥ የሚገኙትን የሀገሪቱን የበላይ አመራር አባላት በየዓመቱ የአፍጥር መጋበዛቸው ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ከ1986 ዓ.ም. ጀምሮ የአል አዛር ሼህ፤ ታላቁ ሙፍቲ እና የውጪ ጉዳይ ሚኒስትሩ ከሌሎች ሰዎች ጋር በመሆን ትርጉም ባለው የመልካም ፈቃድ ሰላማዊ ሰልፍ ላይ እየተሳተፉ ነው፡፡ ይህ ይሁን እንጂ አቡነ ሺኖዳ ሣልሳዊ የአናሳ ክርስቲያኖች መሪ ተብለው ሊጠሩ እንደማይፈቅዱ በተደጋጋሚ ገልጸዋል፡፡ በመሆኑም “ቅብጥ እንደ መሆናችን በግብጽ ክፍል የምንኖር ግብጻውያን ነን፡፡” በማለት አዘውትረው ይናገራሉ፡፡

 

ምንጭ፡-

  • ST.JOHN-NOVEMBER 2004
  • አዘጋጅ፡- ኦክተር አቶ ሜናርደስ
  • ተርጓሜ፡- አያሌው ዘኢየሱስ