የማኅበረ ቅዱሳን 10ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ ተጠናቀቀ

ጳጉሜን 5 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

ነሐሴ 30 ቀን 2004 ዓ.ም. የተጀመረው የማኅበረ ቅዱሳን መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ በታቀደለትና በወጣለት መርሐ ግብር መሰረት በማካሔድ ጳጉሜን 2 ቀን 2004 ዓ.ም. ከለሊቱ 9፡00 ስዓት በድምቀት ተጠናቀቀ፡፡

 

ጳጉሜን 2 ቀን 2004 ዓ.ም.  ለሊት በተካሔደው  የጠቅላላ ጉባኤው ቀጣይ ውይይት በቀኑ መርሐ ግብር የአራት ዓመት ስልታዊ እቅድ ረቂቅ ላይ የተካሔደውን የቡድን ውይይት ውጤት በየቡድኖቹ ሰብሳቢዎችና ጸሐፊዎች አማካይነት እንዲቀርቡ በማድረግ በጠቅላላ ጉባኤው ውይይት ተካሒዶበት ጸድቋል፡፡ በቀጣይነትም የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ዋና የአገልግሎት ክፍሎች ስለክፍሎቻቸው እንቅስቃሴ ለጠቅላላ ጉባኤው ግንዛቤ የማስጨበጥና አሁን ያሉበትን ደረጃ አቅርበዋል፡፡

 

የ10ኛው መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ አዘጋጅ አብይ ኮሚቴ የተሠጣቸውን ኀላፊነት ለመወጣት ያደረጉት ጥረት፤ ያጋጠሟቸው ችግሮችና ችግሮቹን ለመፍታት ያደረጉት ጥረት ያቀረቡ ሲሆን ዝግጅቱን ለማሳካት የገንዘብ ፤ የቁሳቁስና የሃሳብ ድጋፍ ላደረጉ ድርጅቶችና ግለሰቦች ከፍተኛ ምስጋና በማቅረብ የምስክር ወረቀት ተሰጥቷቸዋል፡፡

 

በመጨረሻም በማኅበሩ መተዳደሪያ ደንብ መሠረት ማኅበሩ በማንኛውም የፖለቲካ  እንቅስቃሴ ጣልቃ የማይገባና የማኅበሩ የሥራ አመራር፤ የሥራ አስፈጻሚ፤ የየማእከላት ሰብሳቢዎች፤ የኤዲቶርያል ቦርድ ጽ/ቤት፤ የኦዲትና ኢንስፔክሽን አገልግሎት ጽ/ቤት፤  መምህራን የማኅበሩ ጋዜጠኖችና የማንኛውም ፖለቲካ ድርጅት አባል እንዳይሆኑ የሚያግደውን መመሪያ በማብራራት ውይይት ተደርጓል፡፡ በአሉባልታ ላይ የተመሰረተውን ውዥንብር ለማጥራት ይመለከታቸዋል የተባሉ የማኅበሩ አባላት ሃሳባቸውንና አቋማቸውን እንዲገልጹ በማድረግ የተፈጠረውን ውዥንብር ለማጥራት ተችሏል፡፡ በዚህም መሠረት ማኅበሩ በመተዳደሪያ ደንቡ ላይ ያጸደቀውን ከፖለቲካና ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር በተያያዘ ያለውን አቋም ቀድሞ እንደነበረው እንዲቀጥል አጽንቷል፡፡ በመጨረሻም መርሐ ግብሩ እንደዛሬው ለከርሞው ያድርሰን በሚል ዝማሬ ታጅቦ 10ኛው ጠቅላላ ጉባኤ በድምቀት እንደ ተጀመረ በድምቀት ከለሊቱ 9፡00 ስዓት ተጠናቋል፡፡

የሐዋሳ ማእከል በአፍ መፍቻ ቋንቋ ያሠለጠናቸውን ሰባኪያነ ወንጌል አስመረቀ

ጳጉሜን 5 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዳዊት ደስታ


የማኅበረ ቅዱሳን ሐዋሳ ማእከል ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት የገጠር ስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ንዑስ ክፍል በአፍ መፍቻ ቋንቋ ለአንድ ወር ያሠለጠናቸውን ሠልጣኞች ነሐሴ 1 ቀን 2004 ዓ.ም. አስመረቀ፡፡

 

የሲዳማና ቦረና ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ብፁዕ አቡነ ገብርኤል “በሕዝቡ ቋንቋ ባለማስተማራችን በማኅሌት ብቻ በመወሰናችን ቤተ ክርስቲያን የተሰወረች ሆና በዚህ በደቡብ ክፍለ ሀገር ትታያለች፡፡ ይህ ትልቅ ጉድለት ነው፡፡ ለቤተ ክርስቲያናችን የቆመ ማኅበር ማኅበረ ቅዱሳን በየትኛው በኩል ጉድለት እንዳለብን የተገነዘቡ ልጆቻችን ይህንን የሥልጠና መርሐ ግብር መጀመራቸው ያለብንን ጉድለት ይሞላል” በማለት በምረቃው ዕለት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የሥልጠናውን ዓላማ አስመልክቶ የሐዋሳ ማእከል የደቡብ ማእከላት ማስተባበሪያ ዋና ሓላፊ አቶ ዘሪሁን ከበደ እንደገለጹት ሥልጠናው በሲዳማ፣ ጌዴኦ፣ አማሮና ቡርጂ ዞኖችና ወረዳዎች ሀገረ ስብከት ሥር ለሚገኙ የገጠር አብያተ ክርስቲያናት በአፍ መፍቻ ቋንቋ የሚሰብኩ ሰባኪያነ ወንጌልን በማሠልጠን በገጠር የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን ለማጠናከር እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

 

አያይዘውም ከዚህ ሥልጠና በኋላ ሠልጣኞች የአካባቢውን ቋንቋ በመጠቀም የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን ለማጠናከር፣ የቤተ ክርስቲያን ዶግማ፣ ሥርዓትና ትውፊትን እንዲያስተምሩ፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን በመመሥረት በመምራት በማስተማርና በማጠናከር በአጠቃላይ የጠፉ የቤተ ክርስቲያን ልጆችን አስተምርው የመመለስ ሥራ መሥራት እንዲቻል ለማድረግ እንደሆነ ሓላፊው ገልጸዋል፡፡

 

ሠልጣኞቹ ከሲዳማ፣ ጌዲኦ፣ አማሮና ቡርጂ፣ ጉጂና ቦረና ሀገረ ስብከት የመጡ ሲሆን በስድስት ቋንቋ በተለያዩ ርዕሶች ዙሪያ የሰለጠኑና ቁጥራቸውም 26 እንደሆኑ ተገልጿል፡፡ በዚህ ዓመት ሠልጥነው የተመረቁትን ጨምሮ ማእከሉ ከ1999 ዓ.ም. ጀምሮ ያሠለጠናቸው 201 ሠልጣኖች መድረሳቸውንም ለማወቅ ተችሏል፡፡

ብፁዕነታቸው አዲሱን ዓመት አስመልክቶ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ፡፡

ጳጉሜን 5 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ለመላው ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት ባስተላለፉት መልእክት፡- “የዘመናት ጌታ እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ከዘመነ ዮሐንስ 2004 ዓ.ም. ወደ ዘመነ ማቴዎስ 2005 ዓ.ም. በሰላም አደረሳችሁ፤ ለሚቀጥለውም ዘመን በቸርነቱ ጠብቆ በሰላምና በጤና እንዲያደርሳችሁ ቤተ ክርስቲያናችን ዘወትር ያለ ማቋረጥ ጸሎቷን ወደ ፈጣሪ ታቀርባለች” ካሉ በኋላ ሁሉም ኅብረተሰብ መልካም ታሪክን ለማስመዝገብ በተሰለፈበት ዓላማ የሚጠበቅበትን ድርሻ ማበርከት እንደሚገባው አሳስበዋል፡፡

የመግለጫውን ሙሉ ቃል ከዚህ በታች ያንብቡ፡፡

 

New year

ማኅበረ ቅዱሳን የሥራ አመራር ጉባኤ ምርጫ አካሄደ

ጳጉሜን 2 ቀን 2004 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

ከነሐሴ 30 ቀን 2004 ዓ.ም. ጀምሮ እየተካሄደ የሚገኘው የማኅበረ ቅዱሳን 10ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ በመጠናቀቅ ላይ ነው፡፡

1-2004

ጳጉሜን 1 ቀን 2004 ዓ.ም. ጠዋት በተካሄደው የጠቅላላ ጉባኤው ስብሰባ “በማኅበረ ቅዱሳን የአገልግሎት ጉዞ የአባላት ተሳትፎና የወደፊት ሁኔታ” በተመለከተ ጥናት የቀረበ ሲሆን በአባላት ሰፋ ያለ ውይይት ተካሂዷል፡፡ ከሰዓት በኋላ በቀጠለው ስብሰባም “ስልታዊ ለውጥ ለሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን እድገት ከማኅበረ ቅዱሳን ተልእኮና አቅም አንጻር” በሚል በዲ/ን ያረጋል አበጋዝና ዲ/ን ብርሃኑ አድማስ ጥናታዊ ጽሑፍ ቀርቦ በአባላት ውይይት ተደርጎበታል፡፡ በመጨረሻም የጽ/ቤት ግንባታ ሪፓርት ቀርቦ የመርሐ ግብሩ ፍጸሜ ሆኗል፡፡

 

ምሽት ላይ ጠቅላላ ጉባኤው በዋነኛነት ሁለት ጉዳዮች ላይ ትኩረት በማድረግ የተወያየ ሲሆን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል እያከናወነ ያለውን ዘርፈ ብዙ ተግባራት የተገለጸ ሲሆን ክፍሉም በገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ጋር በተያያዘ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱ ማእከላት የማበረታቻ ሽልማት ከ19500 ብር በላይ አበርክቷል፡፡

3-2004

በቀጣይነት በጠቅላላ ጉባኤው የተሰየመውና ማኅበሩን ለአራት ዓመታት ሊመሩ የሚችሉ የሥራ አመራር አባላትን እንዲያቀርብ የተሰየመው አስመራጭ ኮሚቴ ማኅበሩን ሊመሩ ይችላሉ ያላቸውን አባላት ለጠቅላላ ጉባኤው አቅርቦ በአባላቱ ሰፊ ውይይትና ግምገማ በማድረግ ከ39 እጩዎች መካከል 20 እጩዎችን ለጳጉሜን 2 ቀን 2004 ዓ.ም. ምርጫ እንዲቀርቡ አጽድቋል፡፡ ከ20ዎቹ አጩዎች መካከል የማኅበረ ቅዱሳን የጠቅላላ ጉባኤ የምርጫ ሥነ ሥርዓት ደንብ  አንቀጽ 8 ቁጥር 3 ንዑስ ፊደል ለ በሚያዘው መሠረት ከ20ዎቹ እጩዎች ጸሎት ተደርጎ በእጣ በመለየት 17ቱ የሚመረጡ ይሆናሉ፡፡

 

ጳጉሜን 2 ቀን 2004 ዓ.ም. ጠዋት በተያዘው መርሐ ግብር መሠረት “የማኅበረ ቅዱሳን የአራት ዓመት ስልታዊ እቅድ ረቂቅ ለጠቅላላ ጉባኤው ቀርቧል፡፡ ኮሚቴው በዋነኛነት የማኅበሩ ርዕይ፣ ተልእኮና የማኅበሩ እሴቶች ፤የማኅበሩ ጥንካሬና ድክመቶች፣ መልካም አጋጣሚዎችና ስጋቶች እንዲሁም የማኅበሩ የውስጥ ጉዳዮችና ስትራቴጂያዊ ግቦችን በማካተት አቅርቧል፡፡

 

በተጨማሪም የማኅበሩ ቀጣይ አራት ዓመታት ወሳኝ ጉዳዮችና ግቦች ያሏቸውን የማኅበሩ ተቋማዊ አቅም ማሳደግ፣ የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊ አገልግሎት እንዲያድግ ማድረግ፣ የግቢ ጉባኤያት ተደራሽነትና ብቃት ማሳደግ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ዝግጁ ማድረግ፣ የአብነት ት/ቤቶችና ገዳማት ድጋፍ ቀጣይ የቤተ ክርስቲያን ችግር በሚፈታ መልኩ ማድረግ፣ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ለሁሉም ተደራሽ ማድረግ ዘላቂነቱን ማረጋገጥ በሚሉ ወሳኝ ጉዳዮች ላይ ሰፋ ያሉ ነጥቦች ቀርበዋል፡፡ በእያንዳንዳቸው ዋና ዋና ጉዳዮችም የአፈጻጸም ስልቶችን አስቀምጧል፡፡

 

ኮሚቴው የአራት ዓመት ስልታዊ እቅዱን ካቀረበ በኋላ ለአባላት በስልታዊ እቅድ ረቂቅ ላይ መካተት ነበረባቸው ያሏቸውን እንዲያቀርቡ በተጠየቀው መሠረት ማየትና መስማት የተሳናቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆችን ተጠቃሚ እንዲሆኑ በስልታዊ ረቂቅ አቅዱ ውስጥ እንዲካተት ጥያቄ ቀርቧል፡፡ በመቀጠልም አባላት በቡድን በመከፋፈል ውይይት አድርገዋል፡፡

 

ከሰዓት በኋላ በነበረው መርሐ ግብርም የመተዳደሪያ ደንብ ማሻሻያው ለጠቅላላ ጉባኤው ቀርቧል፡፡ ኮሚቴው ባቀረበው የማሻሻያ ረቂቅ መሠረት በመተዳደሪያ ደንቡ ሊሻሻሉ የሚገባቸው ያላቸውን በማሻሻል፣ መውጣት ያለባቸውን በማስወጣትና አዲስ መግባት አለባቸው ብሎ ያመነባቸውን በማካተት ያቀረበ ሲሆን የጠቅላላ ጉባኤው አባላት ያላቸውን አስተያየትና ማሻሻያ    በጽሑፍ ለኮሚቴው እንዲያቀርቡ ተደርጓል፡፡

2-2004

በመጨረሻም ማኅበሩን ለቀጣይ አራት ዓመታት  የሚመሩ የሥራ አመራር ጉባኤ ምርጫ ተካሒዷል፡፡ በዚህም መሠረት በእጩነት ከቀረቡት 20 እጩዎች መካከል በብፁዐን አባቶች ፀሎት ከተደረገ በኋላ በእጣ 17ቱ ተመርጠዋል፡፡ 3ቱ ደግሞ በተጠባባቂነት ተሰይመዋል፡፡

በዚህም መሠረት ፡

ቀሲስ ዶ/ር ሰሙ ምትኩ ሰብሳቢ

ወ/ሪት ዳግማዊት ኃይሌ ምክትል ሰብሳቢ

ዲ/ን ሙሉዓለም ካሳ ፀሐፊ ሆነው ተመርጠዋል፡፡

 

በተጨማሪም የኤዲቶሪያል ቦርድ፤ ኦዲትና ኢንስፔክሽን በኀላፊነት የሚመሩ አባላት የተመረጡ ሲሆን አዲሱ የሥራ አመራር ኮሚቴ የሥራ አስፈጻሚ አባላትን ለጠቅላላ ጉባኤ አቅርበው አጸድቀዋል፡፡

 

ጉባኤው ምሽቱን እንደሚቀጥልና ሌሎች ማኅበሩን የሚጠቅሙ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ በማሳለፍ እንደሚጠናቀቅ ይጠበቃል፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን 10ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ ተጀመረ

ጳጉሜ 1 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

gubaye 2የማኅበረ ቅዱሳን 10ኛ ጠቅላላ ጉባኤ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነት፤ የመምሪያ ሓላፊዎች፤ ቀሳውስትና ካህናት፤ በሬዴራል ጉዳዮች የሃይማኖት ተወካዮች ነሐሴ 30 ቀን 2004 ዓ.ም. ተጀምሯል፡፡

 

በዋዜማው ነሐሴ 29 ቀን 2004 ዓ.ም. ከተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የመጡ የማኅበሩ አባላት ከምሽቱ 12፤00 ስዓት ጀምሮ የጠቅላላ ጉባኤው አስተባባሪ ኮሚቴ ባዘጋጀው ትራንስፖርት ከማኅበሩ ዋናው ማእከል አቧሬ ወደሚገኘው አቡነ ጎርጎርዮስ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል በመጓዝ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልእክት፤ የመርሐ ግብር ትውውቅ፤  ሕጽበተ እግርና የእራት መርሐ ግብር ተከናውኗል፡፡

 

gubaye 6ነሐሴ 30 ቀን 2004 ዓ.ም. ጠዋት የማኅበረ ቅዱሳን 10ኛ ጠቅላላ ጉባኤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረስብከት ሊቀ ጳጳስ በመመራት በመንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስ ቤተክርስቲያን በተጋበዙ ቀሳውስትና ካህናት ጸሎተ ወንጌል የተካሄደ ሲሆን በብፁዕነታቸው ጸሎትና ቡራኬ ተከፍቷል፡፡

 

የማኅበረ ቅዱሳን የሁለት ዓመት የአገልግሎት ክንውን ሪፖርት በማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩምgubaye 7 አማካይነት የቀረበ ሲሆን ሪፖርቱም በሚዲያ አገልግሎት በግቢ ጉባኤያት፤ በስብከተ ወንጌል አገልግሎት፤ በቅዱሳት መካናትና የአብነት ትምህርት ቤቶች ላይ የተሠሩ ከፍተኛና አነስተኛ ፕሮጀክቶች፤ ስለ ቤተ ክርስቲያናችን የተደረጉ የጥናትና ምርምር ሥራዎች፤ የቤተ ክርስቲያንና የምእመናን ማኅበራዊ አገልግሎት፤ አጽራረ ቤተ ክርስቲያን በቤተ ክርስቲያን ላይ የሚያደርሱትን ጥቃትና የተወሰዱ እርምጃዎች፤ ወዘተ የተከናወኑ ተግባራት በዝርዝር ቀርቧል፡፡

 

በተያዘው መርሐ ግብር የኦዲት ሪፖርት ቀርበዋል፡፡ የማኅበሩ ሒሳብ የ2003 ሪፓርት የውጪ ኦዲተር ሀብተ ወልድ መንክርና ጓደኞቹ በቻርተር የተመሰከረላቸው የሂሳብ አዋቂዎች የኦዲት ሪፖርቶች ቀርበዋል፡፡ በዚህም ሂሳቡ ትክክለኛ እና የማኅበሩን ገጽታ የሚያሳይ መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡

 

በቀረበው የማኅበሩ የሁለት ዓመታት ክንውን እንዲሁም አጠቃላይ አስተያየት እንዲሰጡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል መልካም ፈቃድ ከብፁዐን ሊቃ ነጳጳሳት ተጋብዘዋል፡፡ በተጨማሪም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችም ከበጎ አድራጊ ምእመናን፤ ከነገረ መለኮት ምሩቃን ማኅበር፤ ከፀረ ተሐድሶ ጥምረት የተወከሉ እንግዶች በማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት ዙሪያ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

 

አስተያየታቸውን ከሰጡ ብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት መካከል ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ሣልሳዊ የምስራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ “በገሊላ አውራጃ ጌታ አሥራሁለት ሐዋርያትን እንደ መረጠ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስም በምሳሌነት ይህች ቤተ ክርስቲያን የተማረ የሰው ኀይል ያስፈልጋታል በማለት 12 የዩኒቨርስቲ ተማሪዎችን ይዘው ነው በዝዋይ ሥራ የጀመሩት፡፡ ማኅበሩ ማኅበራችን ነው” በማለት የማኅበረ ቅዱሳንን አመሠራረት አስታውሰዋል፡፡

 

ብፁዕ አቡነ ማትያስ የካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት አስተያት “ማኅበረ ቅዱሳን ብዙ ምሁራንና አዋቂዎች የተሰባሰቡበት ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን የቅዱስ ሲኖዶስ ቋሚ ተጠሪ ነው” በማለት ነበር የገለጹት፡፡

 

ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ “ማኅበረ ቅዱሳን በ20 ዓመት ውስጥ ያከናወነው አገልግሎት እኛ የማኅበረ ቅዱሳን ደጋፊዎች ብቻ ሳንሆን ተቃራኒዎችም የሚመሰክሩት ነው” በማለት ተናግረዋል፡፡

 

ሊቀ ካህናት ኃ/ሥላሴ ዓለማየሁ የዴንቨር ደብረ ሰላም መድኀኔዓለም አስተዳዳሪና የካሊፎርኒያ  አካባቢ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ በሰጡትgubaye 11 አስተያየት ”ከማኅበሩ ጋር በግጭትም፤ በፍቅርም ተገናኝተናል፡፡ ማኅበሩን ከማወቄ በፊት የተቀበልኩት በበጎ መንፈስ አልነበረም፡፡ ነገር ግን በሚያስደንቅ ሁኔታ እኔን የሚያሳምኑ ነገሮች የተፈጠሩት ውስጣችን ገብተህ አገልግሎታችንን ተመልክተህ ፍረድ የሚል ጥያቄ አቀረቡልኝ፡፡ አላቅማማሁም ገባሁ፡፡ የማኅበሩን ማንነት ውስጡን ሕይወቱን ለማየት በምሞክርበት ጊዜ በትክክል የቤተ ክርስቲያኒቱ የጀርባ አጥንት ሆኖ እያገለገለ መሆኑን ለማወቅ እድል አገኘሁ” በማለት ከማኅበሩ ጋር ያላቸውን ቅርበት ገልጸዋል፡፡

 

የጠዋቱ መርሐ ግብር በዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና በአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ናትናኤል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ተጠናቋል፡፡

 

ከስዓት በኋላ በነበረው መርሐ ግብር የማኅበሩ ኦዲትና ኢንስፔክሽን አገልግሎት ሓላፊ ዲ/ን ንጋቱ ባልቻ ሪፖርት የቀረበ ሲሆን በሪፖርቱም የማኅበሩ ስልታዊ ዕቅድ አፈጻጸም፤ የማኅበሩ ሥራ አመራር አፈጻጸም፤ የጠቅላላ ጉባኤያት ውሳኔ በተመለከተ ያልተተገበሩ፤ የሂሳብ ሪፖርት ላይ ታይተዋል ያሏቸውን ክፍተቶች አቅርበዋል፡፡በተጨማሪም የጠቅላላ ጉበኤ ውሳኔ ወይም አቅጣጫ የሚሹ ጉዳዮች ተለይተው ጠቅላላ ጉባኤው ቀጣዩን ስልታዊ እቅድ እና የማኅበሩ መተዳደሪያ ደንብ ሲከለስ እንዲካተቱ ትኩረት እንዲሰጣቸው አሳስበዋል፡፡ በኦዲትና ኢንስፔክሽን በቀረበው ሪፖርት ላይና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች እንዲሁም ከአባላት በተነሱ ጥያቄዎችና አስተያየቶች ማኅበሩን ወደ ፊት ሊጠቅሙ በሚችሉ ጉዳዮች ላይ ሰፊ ውይይት ተደርጓል፡፡

 

በመጨረሻም የሚቀጥሉትን አራት ዓመታት ማኅበሩን የሚመሩ የሥራ አመራር አባላትን የሚያስመርጥ 5 አባላትን ያቀፈ አስመራጭ ኮሚቴ ለመምረጥ አስተያየት ከተሰጠባቸው በኋላ በብፁዕ አቡነ ዮናስ የአፋር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ መሪነት ጸሎተ እግዝእትነ ማርያምና አቡነ ዘበሰማያትን በማድረስ አምስቱን አስመራጭ ኮሚቴ አባላትን በእጣ እንዲለዩ ተደርጓል፡፡ በዚሁ መሠረት የዕለቱ መርሐ ግብር በብፁዕ አቡነ ዮናስ ቡራኬ ተጠናቋል፡፡

 

የጠቅላላ ጉባኤው እስከ አርብ ጳጉሜ 2 ቀን የሚቀጥል ሲሆን የተለያዩ ጥናታዊ ጽሑፎች የሚቀርቡበትና ለቀጣዩ አራት ዓመት ማኅበሩን የሚመለከት ስልታዊ ዕቅድ ላይ እንደሚወያዩ ይጠበቃል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ ጸሎተ ምህላ እንዲደረግ ወሰነ

kidusSinodos

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ነሐሴ 30/2004 ዓ.ም. ለመገናኛ ብዙኅን በሰጠው መግለጫ ከጳጉሜ 1 ቀን 2004 ዓ.ም. እስከ መስከረም 10/2005 ዓ.ም. ድረስ ምእመናን ለሁለት ሱባኤያት በመላዋ ኢትዮጵያና በውጭ ሀገር በሚገኙ አህጉረ ስብከቶች በሚገኙ ገዳማት፣ አድባራትና አብያተ ክርስቲያናት  ጸሎተ ምህላ እንዲደረግ ወስኗል፡፡

 

ቅዱስ ሲኖዶስ ጸሎተ ምኅላውን ያወጀበት ምክንያት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በነበሩበት ዘመን በሃይማኖታዊና ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ  ሰፊ ሥራ የሠሩ አባት እንደነበሩ ጠቅሶ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ሁለንተናዊ ዕድገት ፤ ለሀገሪቱ ሰላምና አንድነት የሚበጅ ተተኪ አባት(ፓትርያርክ) እግዚአብሔር ባወቀ መርጦ እንዲያስቀምጥ ካህናትና ምእመናን  በጸሎተ ምኅላው እንዲሳተፉ አሳስቧል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በዝዋይ ተተኪ ሰባክያንን አስመረቀ

ነሐሴ 28 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዳዊት ደስታ

Zewaye 2 (2)በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ክፍል ከሐምሌ 24 እስከ ነሐሴ 24 ቀን 2004 ዓ.ም. በዝዋይ ሐመረ ኖኅ ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ያሠለጠናቸውን ተተኪ ሰባክያነ ወንጌል አስመረቀ፡፡

 

ሠልጣኞች በቆይታቸው የጥናትና ምርምር፣ የቅዱሳት መጻሕፍት ጥናት፣ ነገረ አበው፣ የተመረጡ ነገረ ሃይማኖት ርእሰ ጉዳዮች፣ የመማር ማስተማር ዘዴ፣ የታሪክ አጠናን ሂደት፣ የተግባቦት ሥልጠና፣ ሥርዓተ ጾታ፣ ወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ተግዳሮት በሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ሥልጠና ወስደዋል፡፡

 

የሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም አስተዳዳሪ የኔታ ሐረገ ወይን ለተመራቂ ተማሪዎች ቃለ ምእዳን አስተላልፈዋል፡፡

 

የተማሪዎቹ ተወካይ ወጣት ግርማ አብደታ ማኅበረ ቅዱሳን ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት የሚያደርገው እንደዚህ ዓይነት ሥልጠናZewaye 2 (1) ለመንፈሳዊ አገልግሎታችን ብቻ ሳይሆን ለዓለማዊም ትምህርታችን ጠቅሞናል በማለት ገልጸዋል፡፡

 

አያይዘውም ከወሰድናቸው የሥልጠና ርዕሶች አንዱ ነገረ አበው ትምህርት አባቶችን ለዚህች ሃይማኖት የከፈሉትን መሥዋእት በአጠቃላይ የሰዓት አጠቃቀምን የሥራ ፍቅርንና የጸሎት ሕይወትን የተረዳንበት ነው በማለት ገልጸዋል፡፡

 

በምርቃት መርሐ ግብሩ ላይ የገዳሙ አስተዳዳሪ የኔታ ሐረገ ወይንና የገዳሙ ርዕሰ መምህር አባ ገ/ሕይወት አባቶች መነኮሳት የማኅበረ ቅዱሳን ተወካዮችና መዘምራን ተገኝተዋል፡፡

ሊቀ መዘምራን ላእከ ማርያም ወልደ ኢየሱስ ዐረፉ

ነሐሴ 28 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

Leke mezemeraneስንክሳርንና ግብረ ሕማማትን እንዲሁም ሌሎችን መጻሕፍት ከግእዝ ወደ አማርኛ የተረጎሙት ታላቁ የመጻሕፍት ሊቅ ሊቀ መዘምራን ላእከ ማርያም ወልደ ኢየሱስ በተወለዱ በ90 ዓመታቸው ነሐሴ 1 ቀን 2004 ዓ.ም. በሞተ ስጋ ከዚህ ዓለም ተለዩ፡፡

 

ሊቀ መዘምራን ላእከ ማርያም ወልደ ኢየሱስ በአርሲ ክፍለ ሀገር በጢዮ ወረዳ ልዩ ስሙ ጨቢ አቦ በተባለ አካባቢ ከአባታቸው መምህር ወልደ ኢየሱስ ዘነበ እና ከእናታቸው ከወ/ሮ ወለተ ሩፋኤል ብስራት ነሐሴ 16 ቀን 1915 ዓ. ም. ተወለዱ፡፡

 

ከአባታቸው ከመምህር ወልደ ኢየሱስ ዘነበ ንባብ፤ ውዳሴ ማርያም ንባብና ዜማ ፤መዝሙረ ዳዊትና ግብረ ዲቁና በመማር ለስልጣነ ክህነት ከበቁ በኋላ በአካባቢያቸው በሚገኘው ዱግዳ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን በዲቁና ሲያገለግሉ ቆይተዋል፡፡

 

ገና በለጋ እድሜያቸው ትምህርትን ፍለጋ ወደ ወሎ ክፍለ ሀገር ላስታ ገረገራ ቅዱስ ጊዮርጊስ በመሔድ ከመምህር ሰይፉ የመጻሕፍተ ሐዲሳትን ትርጓሜ ፤ ከሌሎችም ታዋቂ መምህራን ድጓንና ጾመ ድጓን ተምረዋል፡፡ ወደ ጎንደር በማቅናት ዙር አምባ ገዳም ከታላቁ መምህር ቀለመወርቅ ዝማሬ መዋሥዕት በመማር አጠናቀዋል፡፡ ወደ ደብረ ታቦር በመሔድም የተክሌ አቋቋም ሊቅ ከሆኑት መምህር ቀለመወርቅ ዘንድ ገብተው አስመስክረዋል፡፡ ጎንደር አደባባይ ኢየሱስ ከታዋቂው የቅኔ መምህር በቅጽል ስማቸው የቅኔው ማዕበል መምህር ፈንቴ ቅኔ አስመስክረዋል፡፡ በዋሸራ ከሚገኙት የቅዳሴ መምህር አባ አላምረው ዘንድ የደብረ ዓባይ የመዝገብ ቅዳሴ ተምረዋል፡፡ ሞጣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን በመሄድ ደግሞ  ከመልአከ ገነት ጥሩነህ ለተማሪዎቻቸው ዝማሬ መዋሥዕትን እያስቀጸሉ  ከእሳቸው የአቋቋም ስልቶችን በሚገባ አጣርተው ለማስመስከር በቅተዋል፡፡

 

ወደ መምህርነት ከገቡ በኋላ ብዛት ያላቸው ደቀመዛሙርትን ያፈሩ ሲሆን የተክሌ የአቋቋም በቀላሉ ለመማር የሚያስችል ምልክት ፈጥረው ለደቀ መዛሙርቶቻቸው አስተምረዋል፡፡

 

በአዲስ አበባ በተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት በመምህርነት ያገለገሉ ሲሆን፤ በታእካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም፤ በደብረ ኀይል ቅዱስ ራጉኤል ፤ በብርሃናተ ዓለም ጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተ ክርስቲያናት እየተዘዋወሩ በርካታ ደቀመዛሙርትን አፍርተዋል፡፡

 

ወደ ትውልድ ሀገራቸው አሰላ በመመለስም በአሰላ መንበረ ጵጵስና ደ/ም/ቅ/ማርያም ቤተ ክርስቲያን በመሪ ጌትነት ሲያገለግሉ የቆዩ ሲሆን፤ ከ1971 ዓ.ም.  እስከ 1998 ዓ.ም. በአሰላ ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን በአስተዳዳሪነት አገልግለዋል፡፡

 

በጎንደርና ጎጃም የትምህርትና የመምህርነት ዘመናቸው ላበረከቱት አገልግሎት ከደብረ ወርቅ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን በቅሎ ከነኮርቻው ተሸልመዋል፡፡

 

ባበረከቱት ፍጹም ቅንነት የተሞላበት አገልግሎታቸው የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከነበሩት ከቀድሞው ብፁዕ አቡነ ሉቃስ ቀሚስና ጥንግ ድርብ ከነካባው አልብሰዋቸው፤ የእጅ የወርቅ መስቀል በመሸለም ሊቀ መዘምራን የሚል የክብር ስምም ሰጥተዋቸዋል፡፡

 

መጻሕፍትን በማንበብና በመተርጎም ለቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ ውለታ የዋሉ አባት ሲሆኑ የዓመቱን መጽሐፈ ስንክሳር ከግእዝ ወደ አማርኛ ለመተርጎም ሰባት ዓመታትን ፈጅቶባቸው አስመራ ለሕትመት በተላከበት ወቅት ጠፍቷል፡፡ ተስፋ ሳይቆርጡ በድጋሚ በሁለት ዓመታት ውስጥ በድጋሚ ተርጉመው ለሕትመት አብቅተዋል፡፡ እንዲሁም ግብረ ሕማማትንና ገድለ ዜና ማርቆስን ከግእዝ ወደ አማርኛ በመተርጎም ለሕትመት አብቅተው ቤተ ክርስቲያን እየተጠቀመችባቸው ትገኛለች፡፡ በተጨማሪም ገድለ ሓዋርያት፤ ተአምረ ኢየሱስ፤ ገድለ ቂርቆስ ፤ ገድለ ነአኩቶ ለአብ ፤ ገድለ ሊባኖስ፤ ገድለ ማርያም መግደላዊት፤ ድርሳነ ሐና ፤ ገድለ ዮሐንስ መጥምቅና ሌሎችም በርካታ መጻሕፍት ከግእዝ ወደ አማርኛ በመተርጎም ለቤተ ክርስቲያን አበርክተዋል፡፡

 

ሊቀ መዘምራን ላዕከ ማርያም ወልደ ኢየሱስ በአንድ ወቅት መጻሕፍትን ለመተርጎም የተነሳሱበትን ምክንያት ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ “በመኪና አደጋ እግሬ ተሰብሮ በነበረበት ወቅት ቁጭ ከምል ለምን መጻሕፍትን አልተረጉምም በሚል እግዚአብሔር አሳስቦኝ ተነሳሳሁ፡፡ ስንክሳርንና ሌሎችን አሥራ ሦስት መጻሕፍትን የተረጎምኩት ያኔ ነው፡፡ እግዚአብሔር ታላቅ ችሮታ ነው ያደረገልኝ፡፡ እግሬ ባይሰበር ኖሮ እነዚህን መጻሕፍት መተርጎም አልችልም ነበር፡፡ እግዚአብሔር የጎዳ መስሎ ይጠቅማል፡፡ የእግሬ መሰበር ትልቅ ጥቅም ለኔም ለቤተ ክርስቲያንም አስገኝቶልኛል፡፡” ብለው ነበር፡፡

 

በቅርቡም በጠና ታመው ሕመማቸው ፋታ በሰጣቸው ስዓት ለደብረ ሊባኖስ ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ገዳም ይተረጉሙት የነበረው ዜና ሥላሴ የተሰኘው መጽሐፍ አብዛኛውን ክፍል ተርጉመው ያገባደዱት ሲሆን ሳይፈጽሙት ሞት ቀድሟቸዋል፡፡

 

በእርግና ምክንያት ጡረታ ከወጡ በኋላ ለቤተ ክርስቲያን ባበረከቱት ከፍተኛ ትጋትና አገልግሎት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ሙሉ ደሞዛቸው እንዲከፈላቸው አድርገዋል፡፡

 

ሊቀ መዘምራን ላእከ ማርያም ወልደ ኢየሱስ በ1946 ዓ.ም. ከወ/ሮ ምሕረት በትዕዛዙ ጋር በስርዓተ ተክሊል ጋብቻ የፈጸሙ ሲሆን ስድስት ወንዶችና ስድስት ሴቶች ልጆችን አፍርተው ሠላሳ አንድ የልጅ ልጆችን ለማየት በቅተዋል፡፡ ዝግጅት ክፍላችን ለቤተሰቦቻቸውና ለዘመድ ወዳጆቻቸው መጽናናትን ይመኛል፡፡ የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር ነፍሳቸውን በገነት ያኑርልን፡፡

 

 

የሆሳዕና ደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የንባብና የቅዳሴ ትምህርት ቤት ተመረቀ

ነሐሴ 28 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

PIC_0322የከምባታ፣ ሀዲያ፣ ስልጤና ጉራጌ አህጉረ ስብከት በሆሳዕና ከተማ በደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ቀደም ሲል አገልግሎት ሲሰጥ የነበረው የንባብና የቅዳሴ የአብነት ትምህርት ቤት የጥገና እና የግንባታ እንዲሁም የውስጥ ቁሳቁስ የማሟላት ሥራ ተጠናቆ እሑድ ነሐሴ 20 ቀን 2004 ዓ.ም ተመረቀ፡፡

 

የአብነት ትምህርት ቤቱን በማጠናከር በሀገረ ስብከቱ ለሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት አገልጋይ ካህናትና ዲያቆናት ማፍራት የሚቻልበት ሁኔታ ለማመቻቸት በማኅበረ ቅዱሳን ሆሳዕና ማእከል ፕሮጀክቱ ተቀርጾ በማኅበረ ቅዱሳን ከአሜሪካ ማእከል በተገኘ የገንዘብ ድጋፍ፣ በዋናው ማእከል በቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አስተባባሪነት ተሠርቶ ለመመረቅ በቅቷል፡፡

 

“በተደረገው ጥገናና ግንባታ የሰባት ክፍሎች የውኃ ልክ፤ የወለል ሊሾ፤ የግድግዳ ግርፍ ሥራ፤ የኮርኒስና ቀለም ቅብ የተሠራ ሲሆን ከእነዚህPIC_0314 ክፍሎች ውስጥ  አምስቱ ለተማሪዎች ማደሪያ፣ አንድ ክፍል ለመምህራን፣ አንድ ክፍል ለተማሪዎች መማሪያ፣ አንድ መመገቢያ አዳራሽ ታድሰዋል፡፡ አንድ ክፍል ሙሉ ለሙሉ በመፍረሱ በአዲስ መልክ ተገንብቷል፡፡ በተጨማሪም አንድ መቀጸያ ክፍል፣ አራት መጸዳጃ ቤቶች፣ ሁለት ገላ መታጠቢያ ቤቶች፣ አንድ ምግብ ማብሰያ ክፍል አዲስ ግንባታ መከናወኑንና ሙሉ የውስጥ መገልገያ ቁሳቁስ አልጋ፣ ፍራሽ፣ የመማሪያ ወንበር፣ ጠረጴዛ፣ የምግብ ማብሰያና መመገቢያ ቁሳቁስ ተሟልቶለታል፡፡” በማለት ዲ/ን አእምሮ ይሔይስ የቅዱሳት መካናት የልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ዳይሬክተር በምረቃው ላይ ባሰሙት ሪፖርት ገልጸዋል፡፡

 

በማኅበሩ ተቀርጾ ተግባራዊ እየተደረገ ያለው መርሐ ግብር ለተማሪዎችና ለመምህራን በያሉበት ሀገረ ስብከት የምግብ፣ የአልባሳት፣ የመጸሐፍት ድጋፍ በማቅረብ ጉባኤ ቤት፣ የተማሪዎች ማደሪያ ቤቶችን በመሥራት፣ በመጠገን፣ ልዩ ልዩ ሥልጠናዎችን በማካተት ለዘመናት የሚገባ አገልግሎት እንዲያበረክቱ ማድረግ ነው ያሉት ዲ/ን አእምሮ ይሔይስ “የሆሳዕና ደብረ ገነት ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን የአብነት ትምህርት ቤት 40 ተማሪዎችን በአዳሪነት በመቀበል ሙሉ የማደሪና የመመገቢያ አገልግሎት ለመስጠት እንዲችል ተደርጎ ተገንብቷል፡፡ ፕሮጀክቱም የአስተዳደርን ወጪ ጨምሮ በአጠቃላይ ብር 553,779.20 (አምስት መቶ ሃምሳ ሦስት ሺህ ሰባት መቶ ሰባ ዘጠኝ ብር ከሃያ ሣንቲም) ፈጅቷል” ብለዋል፡፡ ሥራውንም በተቀላጠፈ ሁኔታ ለመሥራት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስና ሥራ አስኪያጅ ላደረጉት ከፍተኛ ትብብር ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

 

ከሀገረ ስብከቱ በተገኘው  መረጃ መሠረት በጉራጌ፤ ሀዲያና ስልጤ ሀገረ ስብከት ውስጥ ካሉት 121 አብያተ ክርስቲያናት መካከል ከ60 የማያንሱት መንፈሳዊ አገልግሎት በአግባቡ ለመስጠት የማይችሉ ናቸው፡፡ የአብነት ትምህርት ቤቱ ጥገናና እድሳት በማግኘቱ በቀጣይ ካህናትንና ዲያቆናትን ተቀብሎ ለማስተማር የሚያስችለው ሲሆን በሀገረ ስብከቱ የተዘጉ አብያተ ክርስቲናት ተከፍተው ምእመናን መንፈሳዊ አገልግሎት የሚገኙበትንና ስብከተ ወንጌል የሚጠናከርበት ምቹ ሁኔታን ይፈጥራል፡፡

 

በምረቃው መርሐ ግብር ላይ የሀገረ ስብከቱ ተወካዮች፤ የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳደርና አገልጋዮች፤ የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራር አባላትና አገልጋዮች፤ እንዲሁም ተማሪዎችና ምእመናን ተገኝተዋል፡፡

 

PIC_0039በተያያዘም ከማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ባገኘነው መረጃ መሠረት ማኅበረ ቅዱሳን በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍሎች ከፍተኛ ችግር ላጋጠማቸው ገዳማትና አድባራት እንዲሁም የአብነት ትምህርት ቤቶች ድጋፍ እያደረገ ሲሆን ግንባታቸው የተጠናቀቁና በመጠናቀቅ ላይ ያሉ ፕሮጀክቶች ይገኛሉ፡፡ ከእነዚህም ውስጥ፡

 

  • የጎንደር የደብረ ኀይል ወደብረ ጥበባት በኣታ ለማርያም ደብር የአቋቋም ምስክር ጉባኤ ቤት በብር 5,981,321.30 (አምስት ሚሊዮን ዘጠኝ መቶ ሰማንያ አንድ ሺህ ሦስት መቶ ሃያ አንድ ብር ከሠላሳ ሳንቲም) ባለ ሁለት ፎቅ የተማሪዎች መኖሪያ የመጀመሪያው ምዕራፍ በመሥራት ላይ ይገኛል፡፡

  • የደብረ ባሕሪይ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ እና አባ በጸሎተ ሚካኤል ገዳም ባለ 3 ፎቅ ሁለገብ ሕንፃ  በብር 2,300,057.00 (ሁለት ሚሊዮን ሦስት መቶ ሺህ ሃምሳ ሰባት ብር) እየተሠራ ይገኛል፡፡

  • ሞጣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን የተማሪዎች መማሪያ፣ ማደሪያና ቤተ መጸሐፍት ግንባታ የመጀመሪያው ምዕራፍ በብር 1,344,144.15 (አንድ ሚሊዮን ሦስት መቶ አርባ አራት ሺህ አንድ መቶ አርባ አራት ብር ከአሥራ አምስት ሳንቲም) እየተከናወነ ይገኛል፡፡

  • የጎንደር ቅድሰት ቤተልሔም ጉባኤ ቤትና የቤተ መጸሐፍት ግንባታ በ787,318.26 (ሰባት መቶ ሰማንያ ሰባት ሺህ ሦስት መቶ አሥራ ስምንት ብር ከሃያ ስድስት ሳንቲም) በመሥራት ተጠናቋል፡፡

  • ደብረ ጽጌ ቅድስት ማርያም ገዳም የአብነት ትምህርት ቤት የሁለተኛው ምእራፍ የመጸዳጃ ቤት፣ ምግብ ማብሰያና መማሪያ ክፍሎች በመገንባት ላይ ሲሆኑ ብር 717,368.98 (ሰባት መቶ አሥራ ሰባት ሺህ ሦስት ስልሳ ስምንት ብር ከዘጠና ስምንት ሳንቲም) ተመድቦለታል፡፡ በመጀመሪያው ምዕራፍ የተማሪዎች ማደሪያ፣ አልጋ፣ ጠጴዛና ወንበሮች አንዲሁም የተለያዩ መገልገያ ቁሳቁስ ተሟልቶለታል፡፡

  • የምድረ ከብድ የመጠጥ ውኃ ፕሮጀክት 100,000 (አንድ መቶ ሺህ) ሊትር ውኃ የሚይዝ በኮንክሪት የተገነባ ማጠራቀሚያ ታንከር በ329,606.19 (ሦስት መቶ ሃያ ዘጠኝ ሺህ ስድስት መቶ ስድስት ብር ከአሥራ ዘጠኝ ሳንቲም) ተገንብቶ ርክክቡ ተፈጽሟል፡፡ በተጨማሪም የአብነት ትምህርት ቤቱን ጣሪያ ቆርቆሮ እንዲለብስ ተደርጓል፡፡

  • የአምባ ማርያም የመጠጥ ውኃ ፕሮጀክት በብር 157,600.00 ( አንድ መቶ ሃምሳ ሰባት ሺህ ስድስት መቶ ብር) ተሠርቶ ተጠናቋል፡፡

  • የበልበሊት ኢየሱስ ገዳም የመስኖ ልማት ፕሮጀክት በብር 72,472.58 (ሰባ ሁለት ሺህ አራት መቶ ሰባ ሁለት ብር ከሃምሳ ስምንት ሳንቲም) ለመሥራት በጅምር ላይ ይገኛል፡፡

 

ማኅበሩ በቀጣይነት የሚያከናውናቸው ሥራዎች እንዳሉና በእንቅስቃሴ ላይ እንደሚገኝ ከቅዱሳት መካናት የልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡

አሥረኛው ጠቅላላ ጉባኤ ተራዘመ

ነሐሴ 24 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደጀኔ

ከነሐሴ 26-28 ቀን 2004 ዓ.ም. ሊካሄድ የነበረው የማኅበረ ቅዱሳን አሥረኛ ጠቅላላ ጉባኤ ወደ ነሐሴ 30 ቀን 2004 ዓ.ም. ተራዘመ፡፡

 

በኢፌዲሪ ጠቅላይ ሚኒስትር ክቡር አቶ መለስ ዜናዊ ኅልፈተ ሕይወት ምክንያት ብሔራዊ የሃዘን ቀን በመሆኑ ጉባኤው እንዲራዘም መደረጉን የጠቅላላ ጉባኤው አዘጋጅ አብይ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ የሺዋስ ማሞ ገልጸዋል፡፡

 

ዘንድሮ የሚካሄደው ጠቅላላ ጉባኤ 1 ሺህ ተሳታፊዎች የሚታደሙበት ሲሆን ለቀጣዩ 4 ዓመታት ማኅበሩን የሚመራ አዲስ አመራር እንደሚመረጥም አቶ የሺዋስ ማሞ ጨምረው ገልጸዋል፡፡

 

ጠቅላላ ጉባኤው እስከ ጳጉሜ 2 ቀን 2004 ዓ.ም. ይቀጥላል፡፡