በወቅታዊ ጉዳዮች ዙሪያ የአዲስ አበባ ሰንበት ት/ቤቶች የአቋም መግለጫ አወጡ።
«የኢትዮጵያ ሀገራችን የአፍሪካ ኩራትነት፥ ለመላው ጥቁር ሕዝብ አለኝታና መመኪያ መሆኗን፥ በዚህም ሠይጣናዊ ቅናት ያደረባቸው ጠብ ያለሽ በዳቦ የሚሉ ምዕራባዊያን ይህችን ለሀገራችን ታላቅ የታሪክ አሻራ ያስቀመጠች ቤተ ክርስቲያን ለማጥፋት የማይፈነቅሉት ድንጋይና የማይቆፍሩት ጉድጓድ የለም።» በማለት የሚያወሳው ደብዳቤው «በየዘመኑ በነበሩና ረድኤተ እግዚአብሔር ባልተለያቸው ቆራጥ ልጆቿ ተጋድሎ ፈተናዎችን በጽናት በማለፍ እስከ ዘመናቸን ደርሳለች» ይላል።
«ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የወላድ መካን አይደለችምና፥ ‘ዛሬም ከቤተ ክርስቲያን በፊት እኛን ያስቀድመን፣ የቤተ ክርስቲያንን ጥፋት አያሳየን’ የሚሉ እስከ ሰማዕትነት ራሳቸውን ያዘጋጁ እንደሚኖሩ ማሰቡ ሳይበጅ አይቀርም» በማለት እምነቱን ይገልጻል።
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያና አዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፥ ሕገ ወጥ ሰባክያንንና ዘማርያንን ለማስቆም ደረጃውን ጠብቆ የጻፉትን ደብዳቤና የሰንበት ትምህርት ቤቶችን አንድነት ለማጠናከር የሚያደርጉትን ጥረት የሚያመሰግነው መግለጫው፤ ከተሾሙ ጊዜ አንስቶ እስከ ዛሬ ድረስ አንዳች የሚጠቀስና የሚጠቅም ሥራ አላበረክቱም ያላቸውን የሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ኃላፊ አባ ሠረቀ ብርሃን ግንቦት 23 ቀን 2003 ዓ.ም የሰጡትን መግለጫ አስደንጋጭና አሳዛኝ እንደሆነበት ያወሳል።
የአባ ሠረቀ መግለጫ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን የማይወክል ከመሆኑም በላይ፥ በአሁኑ ወቅት በየአድባራቱና በየገዳማቱ ተፋፍሞ የቤተ ክርስቲያኗን ሰላምና አንድነት በመፈታተን ላይ የሚገኘውን የመናፍቃን ሴራ ጆሮ ዳባ ልበስ እንደማለት አለዚያም እንደመደገፍ ይቆጠራል፤ በዚህም በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ኃላፊ ላይ የነበረን እምነትም እንዲጠፋ ሆኗል ይላል።
ለዚህ የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ እየሰጡት ያለው ሽፋን ምእመናንን በከፍተኛ ሁኔታ በማስቆጣቱ በየቦታው ሁከት እየተፈጠረ ይገኛል በማለት የሚጠቁመው መግለጫው፥ በተለያዩ አካባቢዎች ለተከሰተው ችግር ተዋንያን በመሆን የሚታወቁ ግለሰቦችን በተለያዩ የጠቅላይ ቤተ ክህነት መምሪያዎች ላይ በኃላፊነት የማስቀመጥ ሂደት እየተካሄደ መሆኑን መረጃዎች እንደሚያመለክቱ ጠቅሶ፥ የከፋ ችግር ሊያመጣ እንደሚችልና ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ ያስገነዝባል።
በአሁኑ ሰዓት የተሐድሶ መናፍቃንን እንቅስቃሴ ለመግታት ብሎም ከቤተ ክርስቲያን ለማጽዳት ባለድርሻ አካላትና ሰንበት ትምህርት ቤቶች እያደረጉ ያለውን ጥረት የሚያደናቅፉት የማደራጃ መምሪያው ኃላፊ የቤተ ክርስቲያንን መዋቅር/የእዝ ሰንሰለት/ ሳይጥብቁ ለአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት የሚሰጡት አደናጋሪ መመሪያዎች፥ ሰ/ት/ቤቶች የተሃድሶ መናፍቃንን ዘመቻ ለመግታት የሚያደርጉትን እንቅስቃሴ አስቸጋሪ እንዳደረገባቸው ይገልጻል።
የተሐድሶ መናፍቃን የዘመቻ ምልክቶች የሆኑት የቤተ ክርስቲያናችንን ሥርዓት ያልጠበቁ ስብከቶችና ዝማሬዎች በተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት በከፍተኛ ሁኔታ በመስፋፋት ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንንና የሰ/ት/ቤቶችን ህልዉና በመፈታተን ላይ ይገኛል እንደሚገኝ የሚያሳስበው መግለጫው፥ ችግሩን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት የአቋም መግለጫ አውጥተናል በማለት ይገልጻል።
ሰ/ት/ቤቶቹ ባወጡት ባለ 6 ነጥብ መግለጫ፥ ቅዱስ ሲኖዶስ በተለያዩ ጉባኤያት ያስተላለፈውና የሚያስተላልፋቸው ውሳኔዎች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲከበሩና እንዲተገበሩ፥ በሰ/ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ኃላፊ በልዩ ልዩ የመገናኛ ብዙኃን ከመምሪያው ሊቀ ጳጳስ እውቅና ውጭ «ተሐድሶ የሚባል ነገር የለም» በሚል የተሰጠው መግለጫ ሰ/ት/ቤቶች የማይቀበሉት መሆኑን እያሳወቅን ተገቢው እርማት በመገናኛ ብዙኃን እንዲሰጥበት፥ አውቀውም ሆነ ሳያውቁ የተሐድሶ መናፍቃንን ጉዳይ በማስፈጸም ላይ የሚገኙ ሕገ-ወጥ ሰባክያንና ዘማርያን በየትናውም የቤተ ክርስቲያናችን ዓውደ ምሕረት ላይ እንዳይቆሙ ለተመሳሳይ ዓላማ በሚንቀሳቀሱትም ተጣርቶ የማያዳግም እርምጃ እንዲወሰድ፥ የተሐድሶ መናፍቃንን ሴራ የማጋለጥ የምእመኑን በቅድስት ተዋሕዶ እምነቱ የማጽናት ሥራ ተጠናክሮ እንዲሠራ፥ ከቤተ ክርስቲያን እውቅና ውጭ በቤተ ክርስቲያኗ ስም የሚተላልፉ የቴሌቪዥን ፕሮግራም፣ የቤተ ክርስቲያንን አስተምሮ የሚያፋልሱና በኑፋቄ የታጀቡ መጻሕፍት ጋዜጦች፣ ካሴቶችና ቪሲዲዎች እንዲሁም መካነ-ድሮች የቤተ ክርስቲያንን ስም እንዳይጠቀሙ፣ ተጠቅመው ከተገኙ በሕግ እንዲጠየቁ የሚሉና ሌሎች ነጥቦችንም አካትቷል።
መግለጫው በማጠቃለያው እነዚህን ችግሮች ጊዜውን የጠበቀ መፍትሔ ሳይሰጣቸው ቢቀርና ተዳፍነው ቢቆዩ የምእመናንና የሰ/ት/ቤቶች አባላት ቁጣ ውስጥ ውስጡን ሲቀጣጠል ቆይቶ ድንገት ከፈነዳ አደጋው በቤተ ክርስቲያንና በሀገር ላይ የከፋ ጉዳት ስለሚያደርስ ሳይቃጠል በቅጠል እንዲሉ ዛሬ ነገ ሳይባል የእርምት እርምጃ መውሰድ ይበጃል በማለት ይገልጻል።
ለሐመር መጽሔት መካነ ድር /website/ ተሠራለት፡፡
በቀደመው ጊዜ ብዙ የተደከመባቸውና ዋጋ የተከፈለባቸው የኅትመት ውጤቶች ምዕመናን እንዲጠቀሙበት ታስቦ እንደተሠራ በማኅበረ ቅዱሳን የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ ሓላፊ ዲ/ን ዘላለም ቻላቸው ተናግረዋል፡፡
ለወደፊቱም የሚወጡትን የመጽሔቷን ዝግጅቶች በሽፋን /cover/ ገጽ በማስተዋወቅ ሥርጭቷን ከፍ የማድረግና በዚህም ስብከተ ወንጌልን የማስፋፋት ተልዕኮን የበለጠ ማሳለጥን ዓላማ ያደረገ እንደሆነ የገለጹት ዲ/ን ዘላለም ቤተ ክርስቲያን በየዘመናቱ የጽሕፈትና የመገናኛ ቴክኖሎጂውን በቀዳሚነት ስትጠቀም ቆይታለች፡፡ አሁን ደግሞ የሰዎች ኢንተርኔትን የመጠቀም እውነታ ቤተ ክርስቲያንን ተወዳዳሪ ሊያደርጋት ይገባል በማለት አያይዘው አስረድተዋል፡፡
በአንዳንድ አቻ መካነ ድሮች ከጥንት አባቶች እስከ ቅርብ ጊዜ ያሉት ጽሑፎችና ሥራዎችን ማግኘት ይቻላል፡፡ በአገራችንም አንዳንድ የኅትመት ውጤቶች የቀጥታ የኢንተርኔት/Online Journalism/ ዘገባ እየጀመሩ እንደሆነ ሌሎችም የቆዩ ሕትመቶቻቸውን የሚያስነብቡበት መካነ ድር እንዳላቸው ይታወቃል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን የስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት ቅድሚያ እንደሚሰጥ የሚገልጹት ዲ/ን ዘላለም በብዙ ሀገሮች መድረስ የሚችል መካነ ድር በአሁኑ ጊዜ ተመራጭ ሚዲያ እንደሆነ ነው፡፡
ለወደፊቱም ለስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ፣ ለጥናትና ምርምር ማእከል፣ ለቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት እንዲሁም ለሌሎች ዋና ክፍሎች ድረ ገጾችን የመሥራት ሐሳብ እንዳለ ሓላፊው አስታውቀዋል፡፡
መካነ ድሩን ያዘጋጁት አቶ ደመላሽ ጋሻው በኤሌክትሮኒክስ ሚድያ ክፍል የቴክኖሎጂ ንዑስ ክፍል አባል ሲሆኑ በዚህ ወቅት መካነ ድሩ ከ45 እትሞች የሚበልጡ ከ1985 እስከ 2001 ዓ.ም የሚገኙ እትሞችን /ከጠቅላላው እትም ከ45-50% የሚሆን /እንዳካተተ ተናግረዋል፡፡ በሰው ኃይል እጥረት፣ በአንዳንድ እትሞች አለመገኘት ወይም ተጠርዘው መቀመጣቸው ስካን /Scan/ ለማድረግ አለመመቸቱ ሁሉንም የቀድሞ እትም መልቀቅ አልተቻለም በማለት አስረድተዋል፡፡ያልተሟሉ ቀሪ ሕትመቶችም በየጊዜው ስካን እየተደረጉ እንደሚጨመሩ አክለው ገልጸዋል።
መካነ ድሩ በአሁኑ ጊዜ ለመጠቀም ምቹና ቀላል ሲሆን እትሞቹንም በዓመት ማግኘት ይቻላል፡፡ በተጨማሪም ምን እንደተለወጠ የሚገልጽ አካል አካቷል፡፡ ለወደፊትም የሕትመት ውጤቶችን በደራሲ፣ በእትም ቁጥር፣ በውስጡ ይዘት /content/፣ የመጽሔቱን ዓምዶች መሠረት ባደረገ ክፍፍል የፍለጋ /Search/ ሥርዓትን ያካትታል፡፡ ከዚህም በላይ የቀጥታ ሽያጭ /Online selling/ እና የቀጥታ ምዝገባ /Online Registration/ እንደ ቴክኖሎጂው ተጨባጭ ሁኔታ ይይዛል በማለት አቶ ደመላሽ አስታውቀዋል፡፡
መካነ ድሩን ለመስራት የሚያስፈልገው ወጪ ከ10,000-15,000 ብር የሚገመት ሲሆን ሥራውም ከዓመት በፊት እንደተጀመረ ታውቋል፡፡ ሐመር መጽሔት በ20ኛው ክፍለ ዘመን መጨረሻና በ21ኛው ክፍለ ዘመን መጀመሪያ ስብከተ ወንጌልን በማስፋፋት፣ በእቅበተ ቤተ ክርስቲያን /Apology/፣ ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን እንዲጠበቅ በማሳሰብ /በማስተማር/ ታዋቂነት ያላት መጽሔት ናት።
መጽሔቷም በስርጭት ስፋትና በሽያጭ የመጀመሪያ ስትሆን ላለፉት ተከታታይ 18 ዓመታትም ያለ ማቋረጥ በማገልገል ታሪካዊ ናት፡፡
የመዝሙር ዐውደ ርዕይ ተከፈተ
ዐውደ ርዕዩ አባቶቻችን ያቆዩልንን የቤተ ክርስቲያን አሻራ የሆነውን ዜማችንን የሚያሳውቅ፣ የሰንበት ት/ቤቶች መዝሙር አሁን ያለበትን ደረጃ የሚያሳይ እንዲሁም በመዝሙር ዙሪያ ላሉ ችግሮች የመፍትሔ ሐሳብ የሚወሰድበት ነው፡፡
በዕለቱ አንዳንድ እንግዶች አስተያየት የሰጡ ሲሆን ከነዚህ መሀል መዝገበ ጥበባት ጌትነት እንዳሉት ‹‹ያየሁት ለሰሚ ድንቅ ነው፡፡ ብዙዎች ቢያዩት መልካም ነው›› ሲሉ ሊቀ መዘምራን ኪነጥበብ ወልደ ቂርቆስ በበኩላቸው ‹‹ያለው የነበረው የቀረበበት›› ዐውደ ርዕይ ነው ብለዋል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን በመዝሙር ዙሪያ ዐውደ ርዕይ ሲያዘጋጅ ይህ የመጀመሪያው ነው፡፡
የወልደ ነጎድጓድ ልጆች እንቅስቃሴ
ሥርዓተ ትምህርት በመቅረጽ ለምዕመናን ጥሪ በማድረግ የሚያስተምረው ሰንበት ትምህርት ቤቱ በዓመት ሁለት መርሐ ግብሮች አሉት፣ በበጋና በክረምት የሚከናወኑ፡፡ ከሰኞ እስከ አርብ በማታው መርሐ ግብር እንዲሁም ቅዳሜና እሑድ ደግሞ በቀን መርሐ ግብር ለምእመናን የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ያስተምራል፡፡ የተማሪዎችንም የክረምት እረፍት ተከትሎ ተጠናክሮ ይካሄዳል፡፡
በእድሜ ክልል በመክፈል ቀዳማይ፣ ካልዓይና ሣልሳይ በማለት የአንድ ዓመት ኮርሶችን ያስተምራል፡፡ ትምህርተ ሃይማኖት፣ ክርቲያናዊ ሥነ ምግባር፣ ታሪክ በመጽሐፍ ቅዱስ፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት፣ የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ለዓለም መድረክና በኢትዮጵያ፣ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን እንዲሁም የዮሐንስ ወንጌል አንድምታ ከሚሰጡት ውስጥ ይጠቀሳሉ፡፡
ከጥሩ ተሞክሮዎቹ
ይህን ያህል የገነነ ተሞክሮ የለንም በማለት በትሕትና የሚገልጡት የሰንበት ትምህርት ቤቱ ሰብሳቢ አቶ አበበ ሥዩም ጥቂቶቹን ይገልጻሉ፡፡
ከአዲስ አበባ ወጣ ካሉ ሰንበት ትምህርት ቤት ጋር ጥሩ ግንኙነት እንደመሠረቱ የሚገልጡት አቶ አበበ ኪናዊ የሆነ ሥራዎችን በማዋስ፣ ልምድ ለማካፈል እንደሚያግዟቸው ይናገራሉ፡፡
በቤተ ክርስቲያንና በሰንበት ትምህርት ቤቱ ላይ ፈተና ሲመጣ መባ ይዞ በመሄድ ወይም በመላክ በጸሎት እንዲያስቡ ያደርጋሉ ሰንበት ትምህርት ቤቱ በራሱም የጸሎትና የጉባኤ መርሐ ግብር በማዘጋጀት በቂ ግንዛቤ ያስጨብጣል፡፡ አብዛኛው ምእመን ሱባኤ በመያዝ በየገዳማቱና የገጠር አብያተ ክርስቲያናት በሚያሳልፍበት በጳጉሜን ወር ትምህርት ጸሎትና ምክረ አበው በማዘጋጀት እንዲያሳልፍ ያደርጋል፡፡ ይሄም የሚናፈቅ እንደሆነ የሰንበት ትምህርት ቤቱ አባላት ይገልጻሉ፡፡
የአብነት ትምህርትን በማስተማር በኩል ሊጠቀስ የሚችል ሥራ ሠርቷል፣ ሰንበት ትምህርት ቤቱ እንደ ዲያቆን ወሳኙ ገለጻ ሰንበት ትምህርት ቤቱ የአብነት ትምህርት ማስተማር ከጀመረ ወደ ሰባት ዓመት አስቶጥሯል፡፡ በእነዚህ ጊዜያት ወደ 20 የሚጠጉ ዲያቆናት አፍርቷል፡፡ በአሁኑ ጊዜ በደብሩም ውስጥ የሚያገለግሉ አሉ፡፡ ቢሆንም የሚጠበቅበትን ያህል እየሄደ እንዳልሆነ የሚገልጹት ዲያቆን ወሳኙ ከዚህ በፊት የነበሩት አንድ መምህር ብቻ መሆናቸውና እርሳቸውም ደጅ ጠኚ ሆነው በትራንስፖርት /በመጓጓዣ/ አበል ብቻ ያስተምሩ እንደነበር ነው፡፡ ትምህርቱም ሥርዓተ ትምህርት ተቀርጾለት አለመሰጠቱ ሌላው ችግር ነው፡፡ ይህም የተፈለገውን ያህል ለማስፋፋት እንዳላስቻለ ይገልጻሉ ዲ/ን ወሳኙ፡፡
ሰንበት ትምህርት ቤቱ ለአብነት ትምህርቱ ምእመናን እንዲሳተፉ ቅስቀሳ የሚካሄደው የደብረ ታቦር ዕለት ነው፡፡ የቆሎ ትምህርት ቤትን ገጽታ የሚያሳይ ኪናዊ ሥራ በማሳየት አውደ ምሕረት ላይ ቅስቀሳ ይደረጋል፡፡ ምንም እንኳን በርካታ ወጣቶች ቢመዘገቡም፤ ጥቂቶች ብቻ ለውጤት እንደሚበቁ ይገልጻሉ ዲ/ን ወሳኙ፡፡ አሁን ግን ቤተ ክርስቲያኗ የአብነት መምህር በመቅጠሯ የተሻለ የመማር እድል አለ፡፡
የወደፊት እቅድ
በጅምር ላይ ያለው የሰንበት ትምህርት ቤቱ አዳራሽ ሲያልቅ በውስጡ የእደ ጥበብ ሥራዎችን በማምረት ያከፋፍላል፣ ይሸጣል፣ ከሌሎች ሰንበት ትምህርት ቤቶችና ማኅበራት ጋር በመቀናጀት ሙያዊ ሥልጠናዎችን፣ ተሞክሮዎችንና ድጋፍ ካገኘ በኋላ የልማት ሥራዎችን ይሠራል፡፡
በመጪዎቹ አሥር ዓመታት ውስጥ የአብነት ትምህርት ቤቱን በማጠናከር አብነት መር የሆነ ሰንበት ትምህርት ቤት ለመፍጠር እቅድ አለ፡፡ ይህንንም ለመፈጸም ጥናቱን አጠናቆ ተግባራዊ ይደረጋል ብለዋል ዲ/ን ወሳኙ፡፡
ሁሉም ሰንበት ትምህርት ቤቶች እጅ ለእጅ ተያይዘን አንዲት ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ቆርጠን መነሣት አለብን በማለት የሚያሳስቡት የሰንበት ትምህርት ቤቱ አቶ አበበ ስዩም በአሁኑ ጊዜ ቤተ ክርስቲያን የገጠማትን ከበድ ያለ ወቅታዊ ፈተና ያነሣሉ፡፡
በቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን ምድር ቤት ፊት ለፊት ደረጃው ሥር ባሉ ክፍሎች በመሰባሰብ የተጀመረው ሰንበት ትምህርት ቤቱ፣ ቀጥሎም በክርስትና ቤት፤ የአባላት ቁጥር ሲጨምርም ትልቅ የቆርቆሮ ቤት በመሥራት እንዲቀጥል ሆኗል፡፡ በእግዚአብሔር ፈቃድ የያኔው ተክል እያበበ እያፈራ 43 ዓመቱን ያከበረው ባለፈው ከግንቦት 19 እስከ 21 ቀን 2003 ዓ.ም ለሦስት ቀናት በተዘጋጀ መርሐ ግብር ነበር፡፡ የሰንበት ትምህርት ቤቱ የኪነ ጥበብ ክፍል ከላሊበላ አርቲስቶች ጋር በመተባበር “ተዋሕዶ” በሚል ርዕስ ያዘጋጁትን ድራማ ለምእመናን አቅርበዋል፡፡ በሦስቱ ቀን መርሐ ግብር የልማትና የጸሎት ክፍል የጸሎት መርሐ ግብር አዘጋጅቶ ነበር፡፡ የቤተ ክርስቲያንን ወቅታዊ ጉዳይና አጽራረ ቤተ ክርስቲያንን በተመለከተም በጉባኤው ላይ ለታደሙት ምእመናንና ተጋባዥ እንግዶች መረጃ እንደደረሰ ዲ/ን ወሳኙ ዘውዴና አቶ አበበ ስዩም ገልጸዋል፡፡
“የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሚና በአየር ንብረት ለውጥ” በሚል መሪ ቃል ጥናታዊ የውይይት መድረክ ተካሄደ
በመቀጠል በአቶ ወንድወሰን ሚቻጎ “የአየር ንብረት ለውጥና ሃይማኖታዊ እሳቤ” በሚል ጥናታዊ ጽሑፍ ቀርቧል፡፡ አቶ ወንድወሰን በጥናታቸው የኢትዮጵያ ኦርቶዶከስ ቤተ ክርስቲያን በአየር ለውጥ ላይ ምን ዓይነት ሚና አላት? ዕውቀት በአየር ንብረት ለውጥ ላይ ያለው አስተዋጽኦና የሃይማኖት እሳቤ በአየር ንብረት ለውጥ ላይ አስተዋጽኦ የሚያመጣው ምንድን ነው? በሚል ሰፋ ያለ የጥናታዊ ጽሑፍ መነሻቸውን አቅርበው ጥያቄዎችና አስተያየቶች ከተሰጡ በኋላ የጠዋቱ ክፍለ ጊዜ ተጠናቋል፡፡
ከሰዓት በኋላ በነበረው ክፍለ ጊዜ ሦስት ጥናታዊ ጽሑፎች የቀረቡ ሲሆን በመጀመሪያው ክፍለ ጊዜ “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን አስተዋጽኦ የካርቦን ልቀትን ለመከላከል “በሚል በዲያቆን ቱሉ ቶላ ቀርቧል፡፡ ዲያቆን ቱሉ በአዲስ አበባ በሚገኙ ሰባት ቀደምት አድባራትና ገዳማት ላይ ተመርኩዘው የሠሩትን ጥናት አቅርበዋል፤ በመቀጠል በአቶ ተስፋዬ አራጌ “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሚና ለተፈጥሮ ደን ጥበቃና እንክብካቤ” በሚል በደቡብ ጎንደር በሚገኝ ሦስት በተመረጡ ወረዳዎች ባሉ አስር አብያተ ክርስቲያናት ስለ ደንና አጠባበቅ የተደረገ ጥናት አቅርበዋል፣ በመጨረሻም በአቶ ብርሃኑ በላይ “የቅብዓ ሜሮን ዕፅዋት የዳሰሳ ጥናት” በሚል ጥናት፣ ሜሮንን ለማዘጋጀት የምንጠቀምባቸው ዕፅዋት እነማን ናቸው? በቀጣይስ እነዚህ ዕፅዋቶች እንዴት ነው? ማሳደግና መንከባከብ የምንችለው? በሚል መነሻ ጥናታቸውን አቅርበዋል፡፡
ከጥናታዊ ጽሑፎች ጋር ተያያዥነት ካላቸው ከአዲስ አባባ ዩኒቨርሲቲ፣ መንግሥታዊና መንግሥታዊ ካልሆኑ ተቋማት እንዲሁም በግል የተጋበዙ ከ300 በላይ እንግዶች የተገኘበት ሲሆን፣ በመጨረሻም የጥናትና ምርምር ማዕከሉ አማካሪ፣ የሰቲት ሁመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ሉቃስ “ጊዜ ገቢር ለእግዚአብሔር” በሚል ርዕስ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ተሰጥቶ የመርሐ ግብሩ ፍጻሜ ሆኗል፡፡
የማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማዕከል ከተመሠረተ ጀምሮ በርካታ ጥናታዊ የውይይት መድረኮችን ያካሄደ ሲሆን ባለፈው ዓመትም የመጀመሪያውን የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጥናት መጽሔት አሳትሞ አበርክቷል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን 20ኛውን ሐዋርያዊ ጉዞ በሰሜን ምሥራቅ ኢትዮጵያ በተሳካ ሁኔታ አደረገ
ሰኔ 20 ቀን 2003ዓ.ም
ማኅበረ ቅዱሳን በትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ከግንቦት 19 – ሰኔ 1 ቀን 2003 ዓ.ም ድረስ በሰሜን ወሎ እና ደቡብ ትግራይ አህጉረ ስብከቶች ሃያ ሰባት ልዑካንን በመያዝ ሐዋርያዊ ጉዞ ማድረጉን በትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዋና ክፍል መደበኛ መምህርና የሐዋርያዊው ጉዞ አስተባባሪ ቀሲስ ለማ በሱ ፍቃድ አስታወቁ፡፡
ቀሲስ ለማ በሱ ፍቃድ እንዳሉት ሐዋረያዊ ጉዞው ከሁለት አህጉረ ስብከቶች በተመረጡ ሰባት ዋና ዋና ከተሞች ማለትም ከደቡብ ወሎ /መርሳ ወልዲያ፣ ፍላቂትና ቆቦ/ እንዲሁም ከደቡብ ትግራይ /አላማጣ፣ ኮረምና ማይጨው/ ማኅበሩ በእነዚህ ሁለት የተመረጡ አህጉረ ስብከቶች ሐዋርያዊ ጉዞ ያካሄደበትን ዓላማ ቀሲስ ለማ እንዲህ በማለት አብራርተዋል፤ ሕዝቡና ካህኑ እንዳለ ተከባብሮ የሚኖርበት ቦታ በመሆኑ፥ አህጉረ ስብከቶቹ የብዙ ሊቃውንት መፍለቂያ፣ የታላላቅ አድባራትና ገዳማት ባለቤት እንዲሁም ብዙ ቅርሶች ያሉባቸው በመሆናቸውና የሕዝቡ ባህል ሃይማኖታዊ ስለሆነ እነዚህ እንዳሉ ተጠብቀው እንዲቆዩ ሕዝቡን ለማጽናት ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ በዚህ አካባቢ ከወቅታዊ የተሃድሶ እንቅስቃሴ ጋር ተያይዞ ብዙ ፈተናዎች ይበዛሉ፤ ይህንንም በማስገንዘብ ምእመናን ራሳቸውንና ቤተ ክርስቲያናቸውን እንዲጠብቁ ነው ብለዋል፡፡
1600 ኪሎ ሜትር በሸፈነው ሐዋርያዊ ጉዞ የቀረቡት ትምህርቶችና መዝሙሮች በወቅታዊ የቤተ ክርሰቲያን ችግሮች ዙሪያ ያጠነጠኑ፥ ምእመኑ በሚረዳው ቋንቋ የቀረቡና ምእመኑ ለለውጥ የተነሳሳበት፣ ልዑካኑም ከምእመኑ የተማረበት ነበር ያሉት ቀሲስ ለማ በየጉባኤዎቹ መጨረሻ "ሕያው እውነት" መንፈሳዊ ፊልም መታየቱም የራሱ የሆነ ልዩ አስተዋጽኦ እንዳበረከተ ተናግረዋል፡፡
ምንም እንኳን ጉዞው በብዙው ስኬታማ ቢሆንም፥ ምእመናን የሰሟቸውን መዝሙሮች ለመገዛት ቢፈልጉም አለመመቻቸቱ፣ የጋዜጠኛ አብሮ አለመጓዝ፣ የካሜራ ባለሙያ አንድ መሆንና የመሳሰሉት ችግሮችን እንዳአስተዋሉ ቀሲስ አስታውቀው ለወደፊቱ መፍትሔ ሊበጅላቸው ይገባል ብለዋል፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን በዋና ክፍሉ ለሐዋርያዊ ጉዞ የሚያስፈልጉ ወጪዎችን በፕሮጀክት እየቀረጸ ለባለሀብቶች፣ በጎ አድራጊዎችና ለመንፈሳዊ ማኅበራት ያቀርባል፡፡ በእነዚህ አካላት ድጋፍ ሐዋርያዊ ጉዞ ያደርጋል፡፡ ለዚህኛውም ሐዋርያዊ ጉዞ 33,000 ያህል የወጣ ሲሆን በኢትዮጵያ አየር መንገድ ሠራተኞች መንፈሳዊ ጉባኤ 25,000 ብር ሲለግሱ ቀሪውን ወጪ ደግሞ ማኅበሩን መሸፈኑ ታውቋል፡፡
ለሐዋርያዊ ጉዞው መሳካት ከፍተኛውን ድርሻ የሚወስዱት አህጉረ ስብከቶቹ ናቸው ያሉት ቀሲስ ለማ የአህጉረ ስብከቶቹ ሊቃነ ጳጳሳት ከፍተኛ ቅስቀሳና መመሪያ በመስጠት፤ ሥራ አስኪያጆች፣ ልዩ ልዩ የመምሪያ ኃላፊዎችና የወረዳ ቤተ ክህነት ሊቃነ ካህናት በጉባኤ በመገኘት፣ የሚያስፈልገውን ሁሉ በማድረግ፣ ሕዝቡን በመቀስቀስ ከፍተኛ ቦታ መያዛቸውን ተናግረዋል፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑም ከጠዋቱ 11፡00 እስከ ሥራ ሰዓት መግቢያና ከሥራ መልስ በሰዓቱ በመገኘት ሥራውን ሳይፈታ ከትምህርቱም ሳይለይ የሚማር፣ ካህናቱም ሕዝቡን በመቀስቀስና የራሳቸውን አስተዋጽኦ በወረብና ቅኔ በማበርከት የተሳተፉበት ጉባኤ ነበር ብለዋል፡፡
ቀሲስ ለማ በጉባኤው ወቅት በማይጨው መካነ ሰማዕት ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ባለው የሰማዕታት አፅም የሰማዕታት መታሰቢያ በዓል ለማክበር የመጡት ባለሥልጣናት ታዳሚ የሆኑበት፣ እኛም ለጊዜው ጉባኤውን አቁመን የአከበርንበት ሁኔታ ነበር ብለዋል፡፡
የሃገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ፣ የክልሉ ትምህርት ቢሮ ኃላፊ፣ የከተማው ከንቲባ፣ የአርበኞች ፕሬዝዳንት በአደረጉት ንግግር፣ ቤተ ክርስቲያን በሀገሪቱ የምታደርገውን እንቅስቃሴ አድንቀው ይሄ ዓይነቱ ጉባኤ የከተማውን መንፈሳዊና ኢኮኖሚያዊ ዕድገት ከሚያፋጥኑት ነገሮች አንዱ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
ሐዋርያዊ ጉዞ ለቤተ ክርስቲያንዋም ሆነ ለሀገር ከፍተኛ አስተዋዕኦ የሚያበረክት ምዕመናንን በእምነታቸው እንዲጸኑ፣ ባህላቸውንና ቅርሳቸውን እንዲጠብቁ የሚያደርግ መንፈሳዊና ትውፊታዊ የጉዞ ጉባኤ ነው፡፡
በክለሳ ላይ ያለው የግቢ ጉባኤያት ሥርዓተ ትምህርት ትግበራው በ2004 ዓ.ም ይጀመራል ተባለ፡፡
ይህንን ሥርዓተ ትምህርት ከግብ ለማድረስ የግቢ ጉባኤያትና የማዕከላት ሥራ አስፈጻሚ አካላትን ግንዛቤ ማስጨበጥ እንዲሁም በቂ መምህራንን ለማፍራት ሥራ እየተሠራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ከ 3000 በላይ ምዕመናን ይሳተፉበታል ተብሎ የሚጠበቅ መንፈሳዊ ጉዞ ተዘጋጀ
በተ/ሥላሴ ፀጋ ኪሮስ
ሰኔ 15 ቀን 2003 ዓ.ም
ከ6 ወራት በፊት ተዘጋጅቶ እንደነበረው በርካታ ምእመናን የሚሳተፉበት መንፈሳዊ ጉዞ ተዘጋጀ፡፡ ሐዊረ ሕይወት ቁጥር 2 የሚል ስያሜ ያለው ይህ ጉዞ ሰኔ 19 ቀን 2003 ዓ.ም ይከናወናል፡፡
ከአዲስ አበባ 108 ኪ.ሜ ርቆ ፍቼ ከተማ ወደ ሚገኘው መካነ ሰማዕት አቡነ ጴጥሮስ ገዳም የሚደረገው ይህ ጉዞ መንፈሳዊ ሕይወታችን የምናጠነክርበት ይህም ከሆነ ዘንድ በቤተ ክርስቲያን የእኛ ድርሻ ምንድን ነው? ብለን ራሳችንን እንድንጠይቅና ኃላፊነታችንን እንድንወጣ የሚያስችል እንደሆነ የጉዞው አስተባባሪ ቀሲስ አንተነህ ጌጡ ተናግረዋል፡፡
ሐዊረ ሕይወት ምእመናን ከመኖሪያና ከሥራ ቦታቸው ራቅ ብለው በተሰበሰበ ልቡና የቅዱሳን ሰማዕታትና የጻድቃን በረከት በሚገኝበት ቦታ ተረጋግቶ ራስን እንዲያዩ የሚያስችል፣ የአበውን ተጋድሎ በመመልከትና በማስታወስ ከፍ ወደ አለ ሥነ ልቡና የሚያደርስና የቤተ ክርስቲያንን ጣዕም የሚያሳይ መንፈሳዊ ጉዞ እንዲሆን ታስቦ እየተዘጋጀ እንደሆነ በአስተባባሪዎቹ ተያይዞ ተገልጿል፡፡
በኢትዮጵያ አንድና ብቸኛ ወደ ሆነው የአቡነ ጴጥሮስ ገዳም በሚደረገው ጉዞ በሐዊረ ሕይወት ቁጥር አንድ ጉዞ ወቅት ተነስተው ላልተመለሱና አሁንም ለሚነሱ ጥያቄዎች ሰፋ ባለ ሁኔታ በአበው ሊቃውንት መልስ የሚሰጥበት የምክረ አበውን ዝግጅት በድጋሚ አካቷል፡፡ ባለፈው ከነበሩ መምህራንና ሊቃውንት በተጨማሪም ሌሎች በርካታ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን የሚገኙበት እንደሆነ ተገልጿል፡፡ በተለይም ይህ ጉዞ የቤተ ክርስቲያንን ችግር ተረድተን መፍትሔ ፍለጋ ለመሄድ አቅጣጫ የሚሰጥ እንደሆነ አጽንኦት ተሰጥቶበታል፡፡
“ገዳሙ አንድና ብቸኛ መሆኑና ከአካባቢው ምእመናን በስተቀር በብዙው ኅብረተሰብ ዘንድ አይታወቅም በአሁኑ ጉዞ ወደ 3000 ምእመናን ይዘን እንጓዛለን ብለን እናስባለን” ያሉት ቀሲስ አንተነህ የሄዱት ምእመናን ለሌሎች ስለሚያስተላልፉ ገዳሙን በቀላሉ ማስተዋወቅ ይቻላል፡፡ በዚህም ምዕመናን የራሳቸውን አስተዋጽኦ ለገዳሙ እንዲያበረክቱ ያደርጋል ሲሉ ሌላኛውን አላማ ተናግረዋል፡፡
ሰማዕቱ ብፁዕ አቡነ ጴጥሮስ ሊቀ ጳጳስ ዘምሥራቅ ኢትዮጵያ የኢጣሊያ ጦር ሀገራችን ኢትዮጵያን በወረረበት ወቅት አርበኞችን በማስተባበር በጀግንነት ያዋጉ ሲሆን በጦርነቱ መሃል ተይዘው ስለሃይማኖታቸው በመመስከር የሀገራቸውን መሬትም ለፋሽስት እንዳትገዛ በመገዘት ሐምሌ 22 ቀን 1928 በሰማዕትነት ያረፉ አባት ናቸው፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በ2001 ዓ.ም በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ የቅድስና ማዕረግ ሰጥታ ጽላት ተቀርጾላቸው እንዲሁም በስማቸው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን በትውልድ ሀገራቸው ሰርታ ሰማዕተ ጽድቅ ዘኢትዮጵያ እያለች ታከብራቸዋልች፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን ለምዕመናን መንፈሳዊ ሕይወት መጠንከር ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን የጠበቁ የተለያዩ መንፈስዊ ጉዞዎችን እንደሚያዘጋጁ የገለፁት ቀሲስ አንተነህ በቅርብ ጊዜ የአዲስ አበባ ማዕከል ባዘጋጀው መንፈሳዊ ጉዞ ከ3000 በላይ ምእመናንን የማኅበረሩን አባላት ሌሎች ማኅበራችንና ሰንበት ትምህርት ቤቶችን ይዞ ወደ ደብር ቅዱስ ደብር ጽጌ ማርያም ገዳም ያደረገውን የሐዊረ ሕይወት ቁጥር አንድ ጉዞን ተጠቃሽ አድርገዋል፡፡
የግቢ ጉባኤያትን ተማሪዎች መንፈሳዊ ሕይወት ለማሳደግ የሚያስችል የንሰሐ አባቶች ሴሚናር ተካሔደ
በእንዳለ ደጀኔ
ሰኔ 10 ቀን 2003 ዓ.ም
ለመጀመሪያ ጊዜ በተዘጋጀው በዚህ የግቢ ጉባኤያት የንስሐ አባቶች ሴሚናር ቁጥራቸው 50 የሚደርሱ አባቶች መሳተፋቸው ታውቋል፡፡
በካህናቱ አቀባበል ላይ የተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩም «እናንተን አባቶች እዚህ ድረስ እንድትመጡ ያስቸገርነው በግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች አገልግሎት ያላችሁ ድርሻ ታላቅ በመሆኑ ነው» ብለዋል፡፡
በሴሚናሩ ላይም ብፁዕ አቡነ ዮናስ የአፋር ሀገረ ስብከት ሊቀጳጳስ እና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ተገኝተው ቡራኬና ቃል ምዕዳን የሰጡ ሲሆን «ማኅበሩ የሚያደርገው የልጅነት ድርሻውን በማገዝ እናንተ ካህናት ትልቁን ድርሻ ትይዛላችሁ» ብለዋል፡፡
ለ3 ቀናት በተካሔደው በዚህ ሴሚናር «እጅግ በጣም ተደስተናል» ያሉት ተሳታፊ ካህናቱ «ቀጣዩን ትውልዱ በመቅረጽና ለሀገርና ለቤተክርስቲያን ብቁና በሥነ-ምግባር የታነፁ ለማድረግ የምንችልበትን ግንዛቤ አግኝተናል። ይህም ካህናት ባገኘነው ግንዛቤና ልምድ ተነሳስተን ውጤታማ ሥራዎችን እንሰራለን» ብለዋል፡፡
ሴሚናሩም ሊቃውንቱን እርስ በእርስ ያስተዋወቀና በመረጃም ረገድ ልምድ ለመለዋወጥ መነሳሳትን እንደፈጠረላቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡