የቅድስት ቤተልሔም የመጻሕፍት ቤትና የጉባኤ ቤት ተመረቀ

የካቲት 12/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን አብርሃም አንዳርጌ

{gallery count=1 width=275 height=225 counter=1 links=0 alignment=right animation=3000}Beteleheme{/gallery}በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ፕሮጀክት የተገነባው በደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት በታች ጋይንት ወረዳ የምትገኘው የድጓ ማስመስከሪያ ቅድስት ቤተልሔም ቤተ ክርስቲያን የመጻሕፍት ቤትና የጉባኤ ቤት ተመረቀ፡፡

የካቲት 4 ቀን 2004 ዓ.ም በደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ እንድርያስ የተመረቀው ይኸው መጻሕፍት ቤትና ጉባኤ ቤት ሙሉ ወጪውን የላስ ቬጋስ ምእመናን በዋናነት መሸፈናቸው ታውቋል፡፡

 

ኅዳር 26 ቀን 2003 ዓ.ም. የመሠረት ድንጋይ ተጥሎ በአንድ ዓመት ውስጥ የተጠናቀቀውን ግንባታ አስመልክቶ ብፁዕ አቡነ እንድርያስ ሲናገሩ የአብነት ትምህርት ቤቶች ለቤተ ክርስቲያናችን ህልውና ከፍተኛ ጠቀሜታ ያላቸው ናቸው፡፡ በመሆኑም ማኅበረ ቅዱሳን በዚህ ረገድ እያደረገ ያለው አስተዋጽዖ ቀላል የሚባል አይደለም” በማለት አመስግነዋል፡፡

 

በዕለቱ አጠቃላይ የሥራ ሒደቱን ዝርዝር ሪፖርት ያቀረቡት የድጓ ምስክር መምህር የሆኑት ሊቀምሁራን ይትባረክ ካሳዬ እንዳሉት “በግንባታው ምክንያት በተፈቀደልን ቦታ ላይ ፕሮጀክት ተቀርጾ የደብሩ ማኅበረ ካህናት፣ የድጓ አድራሾቹ ሁላችን ልማት እያለማን እራሳችንን የምንችልበት መንገድ ይፈልግልን፤ እስከ አሁን ለጉባኤ ቤታችን ለተደረገልን ሁሉ ማኅበረ ቅዱሳንን በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም እናመሰግናለን” ብለዋል፡፡

 

በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት የቅስቀሳና ገቢ አሰባሳቢ ክፍል ሓላፊ ዲያቆን ደረጀ ግርማ በበኩሉ ማኅበሩ በቀጣይም ከቅድስት ቤተልሔም የድጓ ማስመስከሪያ ጎን በመሆን በጋራ ችግሮቹን በመፍታት እንደሚሠራ ጠቁሞ የገንዘብ ድጋፍ ያደረጉ የላስቬጋስ ምእመናንንና የአካባባውን ማኅበረሰብ ስለቀና ትብብራቸው አመስግኗል፡፡

 

በዕለቱም በድጓ ያስመሰከሩ የተወሰኑ አድራሾችና በግንባታው በጎ እንቅስቃሴ የነበራቸው ምእመናን ከብፁዕ አቡነ እንድርያስ እጅ የምስክር ወረቀት ተቀብለዋል፡፡ በቅድስት ቤተልሔም የድጓ ማስመስከሪያ በሀገራችን ብቸኛው ማስመስከሪያ መሆኑ ይታወሳል፡፡