abune abusade

ብፁዕ አቡነ አብሳዲ አረፉ

የካቲት 13/2004 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

abune abusadeብፁዕ አቡነ አብሳዲ በተወለዱ በ92 ዓመታቸው ቅዳሜ የካቲት 10/2004 ዓ.ም. ለእሑድ አጥቢያ በቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም ከዚህ ዓለም በሞት ተለዩ፡፡ ብፁዕነታቸው በትግራይ ክፍለ ሀገር ሽሬ በ1912 ዓ.ም ተወለዱ፡፡ በ1926 ዓ.ም ከሽሬ ወደ ኤርትራ በመሔድና ደብረ ማርያም ገዳም በመግባት የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በመከታተል ዲቁናን ከብፁዕ አቡነ ይስሐቅ፣ ቅስናን ደግሞ ከአቡነ ማርቆስ ተቀብለዋል፡፡ በደብረ ማርያም ገዳም ውስጥ በቆዩባቸው ዐሥር ዓመታት ውስጥ ከአንድ መቶ በላይ ዲያቆናትንና ካህናትን በማስተማር አፍርተዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ አብሳዲ በ1943 ዓ.ም በሱዳን በኩል ወደ ኢየሩሳሌም በእግራቸው የሔዱ ሲሆን፤ በግብጽ ለሁለት ዓመታት ለመቆየት ችለዋል፡፡ ከ1959 ዓ.ም. ጀምሮ ከ60 ዓመታት በላይ በኢየሩሳሌም የኖሩ ሲሆን ጥር 30 ቀን 1983 ዓ.ም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በኤጲስ ቆጶስነት ከተሾሙት ጳጳሳት መካከል አንዱ ናቸው፡፡ በኤጲስ ቆጶስነት እንደተሾሙ በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ ረዳት ኤጲስ ቆጶስ ሆነው እስከ ዕለተ እረፍታቸው ድረስ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በማገልገል ላይ ይገኙ ነበር፡፡

በቆይታቸውም በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ይዞታ የሆኑትን አብያተ ክርስቲያናትና ገዳማትን ለማስከበር ከፍተኛ ጥረት ያደረጉና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሟገት የተጣለባቸውን ሓላፊነት በመወጣት ሰፊ ሥራ ሠርተዋል፡፡ ብፁዕ አቡነ አብሳዲ ዕብራይስጥንና አረብኛ ቋንቋዎችን አቀላጥፈው ይናገሩም ነበር፡፡