ነቢዩ ዮናስ (ክፍል ሁለት) /ለሕፃናት/

የካቲት 14 ቀን 2005 ዓ.ም.

በወልደ ኢየሱስ /ቤካ ፋንታ/


እግዚአብሔር በጣም የሚወዳችሁ እናንተም እግዚአብሔርን በጣም የምትወዱት ሕፃናት እንደምን ሰነበታችሁልን?

 

ልጆችዬ ባለፈው በክፍል አንድ ጽሑፍ ስለ ደጉ ልጅ ስለ ዮናስ የተማርነውን ታስታውሳላችሁ? ዮናስ ለእግዚአብሔር ባለመታዘዙ ምክንያት በባሕር ላይ የሚሄድባት መርከብ ከባድ ችግር ደርሶባት ነበር፡፡ መጨረሻ ላይ ዮናስን ወደ ባሕር ውስጥ ሲጥሉት ንፋሱ ቆመ፡፡ መርከቧም በሰላም መሄድ ቻለች፡፡ ዮናስ ግን ወደ ስምጡ ባሕር እንደገባ አይተን ነበረ ያቆምነው፡፡ ዛሬ ካቆምንበት እንቀጥላለን፡፡

 

በመጀመሪያ ግን አንድ ጥያቄ እጠይቃችኋለሁ፡-

  • ትልቁ በጣም ትልቁ በባሕር ውስጥ ከሚኖሩት ዓሣዎች ሁሉ የሚበልጠው ትልቁ ዓሣ ስሙ ምን ይባላል?

 

ደጉ ዮናስ የመርከቧ ሠራተኞች ከመርከቧ ላይ ወርውረው ወደ ሰፊው ባሕር ሲጥሉት ውኃው ውስጥ ሰመጠ፡፡ ከዚያ ወደ ስምጡ ባሕር ሲገባ በውኃ ስለተከበበ ዮናስ መተንፈስ አቃተው እግዚአብሔርም ለዮናስ አዘነለት እንዳይሞትም አስቦለት በባሕር ውስጥ ካሉት ዓሣዎች ሁሉ በጣም ትልቁን ዓሣ ላከለት፡፡ ትልቁ ዓሣ ስሙ ዓሣ አንበሪ ይባላል፡፡ እግዚአብሔርም ዓሣውን እንዲህ ብሎ አዘዘው “የምወደው ደጉ ዮናስ ውኃው እንዳያፍነውና እንዳይሞት ሂድና ዋጠው፡፡ በሆድህ ውስጥም ለሦስት ቀን እና ለሦስት ሌሊት ይኖራል፡፡” ሲለው ዓሣ አንብሪው ካለበት ቦታ ፈጥኖ እግዚአብሔር እንዳዘዘው ወዶ ዮናስ ደረሰና ዋጠው፡፡ ከዚያ ወደ ስምጡ ባሕር ውስጥ እየዋኘ ሄደ፡፡

 

ልጆችዬ የሚገርማችሁ ነገር ትልቁ ዓሣ ዮናስን ሲውጠው ዮናስ አልሞተም፡፡ በዓሣው አፍ ገብቶ፣ በጉሮሮው አልፎ መጨረሻ ላይ ሆዱ ውስጥ ሲደርስ ዮናስ ደነገጠ፡፡ ወዲያውም ቆሞ ሲመለከት ያለው ትልቁ ዓሣ ሆድ ውስጥ ነው፡፡ በሆድ ውስጥ ሆኖ መተንፈስ ይችላል፣ ማየት ይችላል፣ መቆም ይችላል፣ መናገርም ይችላል፡፡

 

ዮናስ እግዚአብሔር ዓሣ አንበሪውን ልኮት ከሞት እንዳዳነው ሲያውቅ በዓሣ አንበሪው ሆድ ውስጥ ሆኖ በጉልበቱ ተንበረከከና አንገቱን ቀና አድርጎ ወደ ላይ ወደ ሰማይ እያየ “እግዚአብሔር ሆይ ስለምንህ ጸሎቴን ሰምተህ ከሞት ስላዳንከኝ አመሰግንሃለሁ፡፡ በዚህ በዓሣ ውስጥም የዓሣው ጨጓራ እንዳይፈጨኝ ስለጠበቅኸኝ አመሰግንሃለሁ….” እያለ ሦስት ቀንና ሦስት ሌሊት ሙሉ ሳያቋርጥ ደስ ብሎት እግዚአብሔርን ሲያመሰግነው፣ እያጨበጨበ መዝሙር ሲዘምር እግዚአብሔር የዮናስን ጸሎት ሰማ፡፡ እግዚአብሔርም ዓሣውን “ልጄ ዮናስን ወደ ደረቅ መሬት ሄደህ ትፋው” ብሎ አዘዘው፡፡ ዓሣውም ዮናስን በባሕርl ዳር አጠገብ ወዳለች ነነዌ ወደምትባል ሀገር ተፋው፡፡

 

ዮናስ ከዓሣ አንበሪው ሆድ ውስጥ ሲወጣ ቶሎ ብሎ የሄደው እግዚአብሔር ወደ ላከው ሀገር ወደ ነነዌ ነው፡፡ ዮናስ ከባሕሩ ሲወጣ አንድ ነገርን ተምሮዋል፤ ለእግዚአብሔር አለመታዘዝ ብዚ ችግር እንደሚያመጣ አውቆዋል፡፡ ስለዚህም እግዚአብሔር ወደ ላከው ነነዌ ወደምትባል ሀገር ሄደ፡፡ የነነዌ ሕዝብ ሆይ እግዚአብሔር እንዲህ ብሎዋችኋል፡- ክፉ ሥራ መሥራት ትታችሁ ጥሩ ሥራ እኔ እግዚአብሔር የምወደውን መልካም ሥራ ካልሠራችሁ እቆጣችኋለሁ፡፡ ክፉ ሥራ መሥራት ካልተዋችሁ የምትኖሩበትን ከተማ እሳት ከሰማይ አውርጄ አቃጥላታለሁ፡፡” እያለ እየዞረ ለሕዝቡ ሁሉ ነገራቸው፡፡

 

የነነዌ ሕዝቦች የነቢዩ ዮናስን ቃል ሲሰሙ በጣም ደነገጡ፡፡ እግዚአብሔርም ከተማቸውን እንዳያጠፋባቸው እነርሱንም ይቅር እንዲላቸው ሁሉም ተሰበሰቡና ተማከሩ “እግዚአብሔር በክፉ ሥራችን ምክንያት ተቆጥቶ ሀገራችንን እንዳያጠፋ እንጹም፤ እግዚአብሔር እኮ እየጾምን ከለመንነው ይቅር ይለናል፡፡ ስለዚህ ከአሁን ሰዓት ጀምረን ሁላችንም ምግብ ሳንበላ ውኃ ሳንጠጣ ክፉ ሥራ መሥራት ትተን በጾም ለሦስት ቀን እግዚአብሔርን እንለምነው፡፡” ተባባሉና ሕፃናትም፣ ወጣቶችም፣ እናቶችም፣ አባቶችም፣ እንስሳቶችም ሁሉም “እግዚአብሔር ሆይ ይቅር በለን፣ ከአሁን በኋላ ክፉ ሥራ አንሠራም፣ ጥሩ ሥራ እየሠራን አንተ ያዘዝከንን እንፈጽማለን፡፡” እያሉ ለሦስት ቀን ውኃ ሳይጠጡ፣ ምግብ ሳይበሉ በጾም እግዚአብሔርን ለመኑት፡፡

 

እግዚአብሔርም ወደ ነነዌ ሕዝብ ሲመለከት ሁሉም እየጾሙ አየ፡፡ ሁሉም “ይቅር በለን” ይላሉ፡ የነነዌ ሕዝቦች ክፉ ሥራ መሥራት ትተው እየጾሙ እየጸለዩ ሲለምኑት እግዚአብሔር ከሰማይ ከተማዋን ሊያጠፋ እየፈጠነ የሚወርደውን እሳት እሳት እንዳይወርድባቸው ከለከለው እየወረደ የነበረውም እሳት ጠፋ፡፡

 

ልጆችዬ እግዚአብሔር የሚጾም ልጅን በጣም ነው የሚወደው፡፡ እግዚአብሔርን እየጾምን እየጸለይን ከለመነው በእኛ ላይ ክፉ ነገር አይመጣብንም፣ ቤተሰቦቻችንንም እግዚአብሔር ይጠብቅልናል፡፡ ጾመ ነነዌ የሚባለውን ለሦስት ቀን የሚጾመውን ጾም በሚመጣው ሰኞ ጀምረን እስከ ዕረቡ ለሦስት ቀን እንጾመዋለን፡፡ ታዲያ ልጆች ስንጾም ሳንዋሽ፣ ሳንሳደብ ክፉ ሥራ ሳንሠራ፣ ለእግዚአብሔርም ለቤተሰቦቻችንም እየታዘዝን መጾም ይኖርብናል፡፡ መልካም የጾም ቀናት ይሁንላችሁ፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን ከነቢዩ ዮናስ በረከትን ያድለን፡፡ አሜን፡፡

ነቢዩ ዮናስ (ክፍል አንድ) /ለሕፃናት/

የካቲት 8 ቀን 2005 ዓ.ም.

በቤካ ፋንታ /ወልደ ኢየሱስ/

 

ልጆችዬ እንደምን ሰነበታችሁልኝ? እግዚአብሔር ይመስገን አላችሁኝ? ጎበዞች፡፡ ዛሬ ይዤላችሁ የመጣሁት በጣም ደስ የሚል ታሪክ ነው፡፡ ስለዚህ በደንብ ተከታተሉኝ እሺ፡፡

 

በድሮ ጊዜ ነው፣ በጣም በጣም በድሮ ጊዜ አንድ እግዚአብሔርን በጣም የሚወድ ልጅ ነበረ፡፡ ስሙ ዮናስ ይባላል፡፡ ታዲያ ዮናስ ደግ፣ የዋህ፣ ለሰዎች ሁሉ ታዛዥ እና ክፉ ነገርን የማያደርግ ነው፡፡ በዚህ ጥሩ ጸባዩ የተነሣ እግዚአብሔር ዮናስን በጣም ይወደዋል፣ ስሙንም ጠርቶ ያናግረዋል፡፡

 

አንድ ቀን እግዚአብሔር ዮናስን እንዲህ ብሎ አዘዘው፡- “ወዳጄ ዮናስ ሆይ ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ተነሥና ሂድ፡፡ ለነነዌ ሕዝብም እንዲህ በላቸው፡- ክፉ ሥራ መሥራት ትታችሁ ጥሩ እግዚአብሔር የሚወደውን መልካም ሥራ ካልሠራችሁ እግዚአብሔር ይቆጣችኋል፣ ከክፉ ሥራችሁ ካልተመሳችሁ ከተማችሁን ያጠፋባችኋል፡፡” ብለህ ተናገር ብሎ አዘዘው፡፡ ዮናስ ግን እግዚአብሔር ወደ ላከው ወደ ነነዌ መሄድ ትቶ ወደ ሌላ ሀገር ተርሴስ ወደምትባል ሀገር ሊሄድ ወደ ባሕር ዳርቻ ሄደና በመርከብ ላይ ተሳፈረ /ወጣ/፡፡ ከዚያም መርከብ ውስጥ ሆኖ በባሕሩ ላይ መጓዝ ጀመረ፡፡ ግን የሚሄደው እግዚአብሔር ወደ ላከው ሀገር ሳይሆን ወደ ሌላ ሀገር ነበረ፡፡

 

እግዚአብሔርም ዮናስ እንዳልታዘዘው ባየ ጊዜ ነፋሱን አዘዘው፡፡ ነፋሱም እግዚአብሔር እንዳዘዘው ባሕሩን በጣም ያነቃንቀው ያወዛውዘው ጀመረ ከዚያ ከባድ ማዕበል ሆነ፡፡ የባሕሩም ውኃ መርከቧን ሊያሰጥማት አወዛወዛት፡፡ አንዴ ወደ ቀኝ አንዴ ወደ ግራ ልትወድቅ፣ ልትገለበጥ መርከቧ ተወዛወዘች፡፡ ያን ጊዜ በውስጧ ያሉ የመርከቧ ሠራተኞች መርከቧ እንዳትገለበጥና እንዳይሞቱ በጣም ቢደክሙም ነፋሱ ግን ውኃውን እያነሳ መርከቧ ላይ ይጥልባቸዋል፡፡

 

ልጆችዬ በጣም የሚገርማችሁ ነገር ግን ይህ ሁሉ ነፋስ ሲነፍስ መርከቧም ወዲህና ወዲያ ስትወዛወዝ ዮናስ በመርከቧ ውስጥ ሆኖ አልሰማም ነበር፡፡ ለምን መሰላችሁ? በመርከቧ ውስጠኛ ክፍል ገብቶ ኀይለኛ እንቅልፍ ተኝቶ ስለነበረ ነው፡፡ የመርከቧ ሠራተኞ ወደ ዮናስ መጣና ኧረ መርከባችን በባሕር ውስጥ ልትሰጥምብን ነው፣ ኧረ ልንገለበጥ ነው፤ ከተኛህበት ንቃ ብሎ ከእንቅልፉ ቀሰቀሰው፡፡ ዮናስ ተነሥቶ ሲያይ ነፋሱ በጣም ይጮኻል፣ የባሕሩም ውኃ መርከቧን ሊገለብጣት ወደ ላይ እየተነሣ መርከቧን ይመታታል፡፡ የመርከቡ ሠራተኞችም ሁሉም በጣም ተደናግጠውና ፈርተዋል፡፡ ነፋሱን እንዲያቆምላቸውና በሰላም እንዲሄዱ ሁሉም እግዚአብሔርን “አድነን፣ ነፋሱን አቁምልን፣ በሰላም አገራችን አድርሰን፡፡” እያሉ መጸለይ ጀመሩ፡፡

 

ዮናስም ይሄ ሁሉ ችግር የመጣው እርሱ ለእግዚአብሔር ባለመታዘዙና ሂድ ወደ ተባለበት አገር ባለመሄዱ ምክንያት የመጣ እንደሆነ አወቀ፡፡ እግዚአብሔርም በዮናስ ተቆጥቶ እንዲህ ማድረጉን በተረዳ ጊዜ የመርከቧን ሠራተኞች “ይሄ ሁሉ ችግር የደረሰባችሁ በእኔ ጥፋት ስለሆነ ወደ ባሕሩ ውስጥ ጣሉኝ፡፡ ከዚያ ነፋሱ ይቆምላችሁና በባሕር ውስጥ ከመገልበጥ እና ከመሞት ትድናላችሁ፡፡ ስለዚህ ወደ ባሕሩ ውስጥ እኔን ጣሉኝ፡፡” አላቸው፡፡ በዚህ ጊዜ የመርከቧ ሠራተኞች ዮናስን ወደ ባሕር ውስጥ ወረወሩት፡፡ ወዲያውኑ የሚነፍሰው ኀይለኛ ነፋስ ቆመ፡፡ መርከቧም በሰላም ተጓዘች፡፡

 

ደጉና የዋሁ ዮናስ ወደ ሰፊው ባሕር ውስጥ ተጣለ፡፡ ወደ ባሕሩ ጥልቅ ውስጥም ገባ፡፡ በዙሪያውም በውኃ ተከበበ፡፡ ልጆችዬ ውኃ ውስጥ ደግሞ የሰው ልጆች መተንፈስ አንችልም፣ ማንም ሰው ደግሞ መተንፈስ ካልቻለ ይሞታል፡፡ ዮናስ ግን ጥልቁ ባሕር ውስጥ ተጥሎም አልሞተም፡፡ ዮናስ ለምን እንዳልሞተ፣ በባሕር ውስጥ ሲገባ ምን እንዳገኘው በሚቀጥለው ክፍል ይዤላችሁ እመጣለሁ፡፡

 

አሁን ከመሰናበቴ በፊት ሦስት ጥያቄ እጠይቃችኂለሁ፡-

  1. እግዚአብሔር ዮናስን በጣም የሚወደውና የሚያነጋግረው ዮናስ ምን ዓይነት ጸባይ ስላለው ነው?

  2. ዮናስ የተሳፈረባት መርከብ በነፋስ ብዙ ችግር የደረሰባት በማን ስህተት ነው?

  3. እግዚአብሔር ዮናስን የላከው ምን ወደ ተባለ ሀገር ነው?

ይቀጥላል

የጥምቀት በዓል በዮርዳኖስ ወንዝ /ለሕፃናት/

ጥር 9 ቀን 2005 ዓ.ም.
ከወልደ ኢየሱስ /ቤካ ፋንታ/

 

ልጆችዬ እንኳን ለጥምቀት በዓል በሰላም አደረሳችሁ! ዛሬ ስለ ታላቁ በዓል ስለ ጥምቀት ብዙ የምነግራችሁ ነገር አለኝ፡፡ በደንብ ተከታተሉኝ እሺ፡፡

 

በገዳም ውስጥ ለሠላሳ ዓመት ለብቻው ሆኖ እግዚአብሔርን እያመሰገነ የሚኖር የእግዚአብሔር አገልጋይ ነበር፡፡ ስሙም ቅዱስ ዮሐንስ ይባላል፡፡ ልጆችዬ የቅዱስ ዮሐንስ ልብስ ምንድር መሰላችሁ የግመል ቆዳ ነበረ፣ የሚበላው ደግሞ በበረሃ የሚገኝ ማር ነው፡፡ በገዳም ሲኖር ሁል ጊዜ እግዚአብሔርን በደስታ እየዘመረ ያመሰግነው ነበር፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን ከሚኖርበት ገዳም ተነሥቶ ዮርዳኖስ ወደሚባል ወንዝ እያስተማረ መጣ፡፡ ትምህርቱም “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ፡፡” የሚል ነው፡፡ ያን ጊዜ ይህንን ትምህርት የሰሙ በጣም ብዙ ሕፃናት፣ ወጣቶች እና ትልልቅ ሰዎች ወደ ቅዱስ ዮሐንስ ተሰብስበው መጡና ያጠፉትን ጥፋት፣ የበደሉትን በደል፣ የሠሩትን ኃጢአት ሁሉ እየነገሩት /እየተናዘዙ/ በጸበል አጥምቀን አሉት፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም የዮርዳኖስን ወንዝ በእግዚአብሔር ስም ሲባርከው ጸበል ሆነ፡፡ ከዚያም የተሰበሰቡትን ሁሉ ወንዶችን ሴቶችን እና ሕፃናትን በጸበሉ አጠመቃቸው፡፡

 

ልጆችዬ ከዚያም ምን ሆነ መሰላችሁ? ፈጣሪያችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ ሊጠመቅ መጣ፡፡ አጥማቂው ቅዱስ ዮሐንስም ኢየሱስ ክርስቶስን ሲያየው ፈጣሪዬ ሆይ አጥምቀኝ አለው፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ግን አይሆንም አንተ አጥምቀኝ ብሎት በጥር 11 በቅዱስ ዮሐንስ እጅ በዮርዳኖስ ወንዝ ተጠመቀ፡፡ ስለዚህም አምላካችን በዚህች ቀን ስለተጠመቀ ዛሬ የምናከብረው የጥምቀት በዓላችን የተባረከ ሆነ፡፡

 

ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ ከውኃ ሲወጣ  በጣም የሚያስደንቅ ተአምር ታየ፡፡ ሰማያት ተከፈቱ፤ ከሰማዩ ውስጥም መንፈስ ቅዱስ በነጭ ርግብ ተመስሎ መጣና በጌታችንነ በመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ  በራሱ ላይ ተቀመጠ፡፡ ከዚያም አንድ ታላቅ ድምፅ ከሰማይ ውስጥ ተሰማ፡፡ እንዲህ የሚል “በእርሱ ደስ የሚለኝ የምወደው ልጄ ይህ ነው፡፡”

 

ልጆችዬ ዛሬም እኛ ክርስቲያኖች ከጥር ዐሥር ጀምረን ነጭ የሀገር ልብስ ለብሰን ቅዱሱን ታቦት አጅበን እየዘመርን፣ እልል እያልን የምንዘምረውና በጸበል የምንጠመቀው በመስቀልም በአባቶቻችን ካህናት የምንባረከው አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተጠመቀበት ቀን ስለሆነ ነው፡፡

 

አገራችን ኢትዮጵያ ደግሞ በሁሉም ቤተ ክርስቲያን ያሉት ታቦታት ጥር አሥር ቀን ከየቤተ ክርስቲያኑ ወጥተው ወደ ጥምቀተ ባሕር /ጸበሉ ቦታ/ ሄደው እየተዘመረ፣ እየተጸለየ በምስጋና ይታደራል፡፡ በነጋታው ጥር 11 በጠዋት ውኃው ተባርኮ ጸበል ይሆናል፡፡ በሥፍራው የተሰበሰቡትን ክርስቲያኖች ሁሉንም በጸበሉ እየረጩ ያጠምቋቸዋል፡፡ በመጨረሻም የእግዚአብሔር ማደሪያ ቅዱስ ታቦቱ በካህናቱ ዝማሬ በምእመናን እልልታ ታጅቦ ወደ ቤተ ክርስቲያን ይመለሳል፡፡

አሁን ደግሞ ጥያቄ ልጠይቃችሁ፡-

  1. ቅዱስ ዮሐንስ የሚኖረው በየት ነበር?

  2. ጌታችን መድኃኒጻችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተጠመቀው የት ነው?

  3. ኢየሱስ ክርስቶስን ያጠመቀው ማን ነው?

  4. ቅዱስ ዮሐንስ ያጠመቃቸው  ወገኖች እነማን ናቸው?

ልጆችዬ ከመሰናበቴ በፊት ለዛሬ የምታነቡትን የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍል ልንገራችሁ፡፡ ይኸውም የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ ሦስት ነው፡፡ ስለተከታተላችሁኝ የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር ይስጥልኝ፡፡ እመቤታችን ድንግል ማርያም ታሳድግልኝ፡፡ መልካም የጥምቀት በዓል ይሁንላችሁ፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር
christmas 1

የሕፃኑ የኢየሱስ ልደት /ለሕፃናት/

ታኅሣሥ 26 ቀን 2005 ዓ.ም.

ከወልደ ኢየሱስ /ቤካ ፋንታ/

  • “እነሆ ድንግል ትፀንሳለች ልጅም ትወልዳለች ስሙንም አማኑኤል ትለዋለች” ማቴ.1፥23

 

ልጆችዬ እንደምን ሰነበታችሁ? ዛሬ ስለ ታላቁ ሕፃን ልደት የምነግራችሁ ነገር አለና በማስተዋል ተከታተሉኝ እሺ፡፡ ጎበዞች!

christmas 1

የዛሬ ሁለት ሺ ዓመት ገደማ ነው፡፡ በኢየሩሳሌም ሀገር ንጉሡ ሄሮድስ ሕዝቡን ሁሉ ቤተልሄም ወደምትባል ከተማ ጠራቸው፡፡ እመቤታችንም በዚያ ጊዜ የአሥራ አምስት/15/ ዓመት ልጅ ሆኖ በሚጠብቃት በአረጋዊው /በሽማግሌው/ ዮሴፍ ቤት ትኖር ነበር፡፡ እመቤታችን ድንግል ማርያም ሕፃኑን ኢየሱስ ክርስቶስን ፀንሳ ልትወልድ ደርሳ ሳለ ወደ ቤተልሄም ከተማ ከአረጋዊው ጠባቂዋ ዮሴፍና ከቅድስት ሰሎሜ ጋር ሄደች፡፡

 

በዚያ ሲደርሱ ምን ሆነ መሰላችሁ? እናታችን ማርያም ቅድስት ሰሎሜና አረጋዊው ዮሴፍ ማደሪያ ፈልገው በየቤቱ እየሄዱ “የእግዚአብሔር እንግዶች ነን ማደሪያ ስጡን፣ እባካችሁ አሳድሩን…” ብለው ቢጠይቋቸው ሁሉም “ቦታ የለንም፣ አናሳድርም፣ አናስገባም ሂዱ፡፡” እያሉ መለሷቸው፡፡ በጣም መሽቶ ስለነበረ ጨለማው ያስፈራ ነበረ፣ ብርዱ ደግሞ በጣም ከባድ ነበረ፡፡ ማደሪያ አጥተው የት እንሂድ እያሉ ሲያስቡ በድንገት አረጋዊ ዮሴፍ “ኑ ተከተሉኝ” ብሎ በመንደሩ ውስጥ ወዳለ አንድ የከብቶች ማደሪያ ቤት ወሰዳቸው፡፡

 

ከከብቶቹ ቤት ሲደርሱ በዚያ አህዮች፣ በሬዎች፣ በጎች፣…. ብዙ እንስሳት ተኝተው አገኙዋቸው፡፡ የበረቱ ሽታ በጣም ያስቸግር ነበረ፡፡ ነገር ግን ማደሪያ ስላልነበረ በዚያ ሊያድሩ ተስማሙ፡፡

 

ወደ በረቱ ሲገቡ እንስሶቹ ከተኙበት ተነሥተው በደስታ እየዘለሉ ተቀበሏቸው፡፡ በዚያም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ሕፃኑን ኢየሱስ ክርስቶስን ወለደችው፡፡ ይህም ታላቅ ሕፃን የሁላችንም አምላክ ነው፡፡ ወዲያውኑ የከብቶቹ ቤት በታላቅ ብርሃን ተሞላ፡፡ ቅዱሳን መላእክት ተገለጡ፤ በእመቤታችንም ፊት ሆነው በደስታ ከበሮ እየመቱ፣ እያጨበጨቡ መዘመር ጀመሩ፡፡ መዝሙሩም እንዲህ የሚል ነበር፡-

 

“ለእግዚአብሔር ክብርና ምስጋና በሰማያት ይሁን፣ በምድርም ሰላም ለሰውም በጎ ፈቃድ”


ልጆችዬ አሁን አንድ ጥያቄ ልጠይቃችሁ ነው፡፡ ተዘጋጃችሁ? መልካም፡-

  • የገናን በዓል እንዴት ነው የምታከብሩት? ለሕፃኑ ለኢየሱስ ክርስቶስ የልደት መዝሙር እየዘመርን ነው አላችሁኝ? ጎበዞች! የገናን በዓል ከወላጆቻችሁ ጋር በቤተ ክርስቲያን ተገኝታችሁ እንደ ቅዱሳን መላእክት በደስታ መዝሙር በመዘመር አክብሩት እሺ፡፡

መልካም የገና በዓል ይሁንላችሁ፡፡

የአብርሃም የይስሐቅ የያዕቆብ አምላክ /ለሕፃናት/

ኅዳር 7 ቀን 2005 ዓ.ም.

በኪዳነማርያም


አባታችን አብርሃም እግዚአብሔርን በማያውቁ፣ ጣዖት በሚያመልኩ መንደር ውስጥ ይኖር ነበር፡፡ አባቱ ጣዖት እየቀረጸ የሚሸጥ ነበር፡፡ አንድ ቀን አባቱ ሸጠህ ና! ያለውን ጣዖት ከረሀቡ ያስታግሰው ዘንድ አብላኝ ብሎ ቢጠይቀው አልሰማህ አለው፡፡ የጠየቀውን አልመልስልህ ሲለው ሰባብሮ ጣለው፡፡ ወደ ሰማይ አንጋጦ ጨረቃን ጠየቃት አልመለሰችም፣ ፀሐይን ጠየቀ አልመለሰችም፡፡ ተስፋው ሲሟጠጥ አምላከ ፀሐይ ተናበበኒ (የፀሐይ አምላክ አናገረኝ) አለ፡፡ እግዚአብሔርም ሰማው ከዘመዶችህ ተለይተህ እኔ ወደ ማሳይህ ስፍራ ውጣ አለው፡፡ አባታችን አብርሃምም እንደታዘዘው በመፈጸሙ እግዚአብሔር ቃልኪዳን ገባለት፡፡ ዘርህን እንደ ምድር አሸዋ አበዛዋለሁ የምድርም አሕዛብ ሁሉ በዘርህ ይባረካሉ አለው፡፡ አብርሃምም ከሣራ ይስሐቅን ወለደ፣ ይስሐቅም ታዛዥ ነበር፡፡ እግዚአብሔር አብርሃምን አንድያ ልጅህን ሠዋልኝ ባለው ጊዜ አብርሃም ታዘዘ፡፡ ልጁ ይስሐቅም አባቱን ታዘዘ፡፡ አምላክህን ከምታሳዝነው እኔንም ዓይን ዓይኔን እያየህ ከምትራራ በጀርባዬ ሠዋኝ ብሎ አባቱን አበረታው፡፡ እግዚአብሔርም የአብርሃምን እምነት የልጁን ታዛዥነት ዓይቶ በይስሐቅ ፋንታ ነጭ በግ በዕፀ ሳቤቅ አዘጋጅቶ እንዲሠዋ አደረገ፡፡ የበጉም ምሳሌ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡

 

ይስሐቅም ለእግዚአብሔር ታማኝ ነበር ካደገ በኋላ ርብቃን አግብቶ መንታ ልጆችን ወለደ፡፡ የልጆቹ ስም ዔሳው እና ያዕቆብ ይባላሉ፡፡ እነዚህ ልጆች ገና በእናታቸው ማኅፀን እያሉ ይገፋፉ ነበር፡፡ ነገር ግን የበኩር (የመጀመሪያ) ልጅ ሆኖ የተወለደው ኤሳው ነበር፡፡ በሀገራቸው ልማድ የበኩር ልጅ መሆን የአባትን በረከት ምርቃት የሚያሰጥ ነበር፡፡ እነዚህ ልጆች ካደጉ በኋላ ዝንባሌአቸው የተለያየ ነበር፡፡ ዔሳው አደን የሚወድ ያዕቆብም በቤት ውስጥ እናቱን የሚላላክ ሆነው አደጉ፡፡ አንድ ቀን ኤሳው ከአደን ሲመለስ ምንም አልቀናውም ነበር፡፡ በጣም ተርቦ ወንድሙ ያዕቆብን ከሠራኸው የምስር ወጥ አብላኝ አለው፡፡ ያዕቆብም ብኩርናህን ስጠኝና ከሠራሁት አበላሀለው ብሎ ነፈገው፡፡ ዔሳውም ብኲርናዬ ረኀቤን ካላስታገሰችልኝ ለችግሬ ካልሆነችኝ ለኔ ምኔ ናት ብሎ አቃለላት፣ በምስር ወጥ ሸጣት፡፡ አባታቸው ይስሐቅ ስላረጀ ምርቃቱን፣ በረከቱን ሊያስተላልፍ የበኩር ልጁ ዔሳውን ጠርቶ እነሆ እኔ አረጀሁ የምሞትበትንም ቀን አላውቅም፤ ሳልሞት ነፍሴ እንድትባርክህ የምወደውን ምግብ ሠርተህ አብላኝ አለው፡፡ ይህን ሁሉ እናታቸው ርብቃ ተደብቃ ትሰማ ነበር፡፡  አብልጣ የምትወደው ያዕቆብን ነበርና የአባቱ ምርቃት እንዳያመልጠው የሰማችውን ሁሉ ነገረችው፡፡ አባትህ የሚወደውን ምግብ እኔ አዘጋጅልሀለው አለችው፤ አባቱ እርሱ ዔሳው እንዳልሆነ ቢያውቅበት በበረከት ፈንታ መርገም እንዳይደርስበት ያዕቆብ ፈራ፡፡ አባታችሁ በእርጅና ምክንያት ዓይኑ ስለተያዘ አንተንም በመዳበስ እንዳይለይህ እንደወንድምህ ሰውነት ጠጉራም እንድትመስል በበግ ለምድ ሸፍኜ መልካሙን የዔሳው ልብስ አለብስሀለው መርገሙም በእኔ ላይ ይሁን ብላ መከረችው፣  አደፋፈረችው፡፡ ያዕቆብ እናቱ ያዘጋጀችውን ምግብ ይዞ ገባ አባዬ ያልከኝን አዘጋጅቻለሁ፤ ብላ ነፍስህም ትባርከኝ አለው፡፡ አባቱም አንተ ማነህ? ብሎ ጠየቀ፡፡ እኔ የበኩር ልጅህ ዔሳው ነኝ ብሎ ዋሸ፡፡ እንዴት ፈጥነህ አገኘህ? አለው፡፡እርሱም እግዚአብሔር አምላክህ ወደ እኔ ስላቀረበው ነው፤ አለው፡፡

 

እጁንም ዳሰሰና ድምፅህ የያዕቆብን ጠረንህ ደግሞ የዔሳውን ይመስላል ብሎ ልጁ ያዕቆብ ካቀረበለት መአድ ተመግቦ ሲጨርስ የልጁን ጠረን አሸተተ፣ እግዚአብሔር ፈቅዷልና  “እግዚአብሔርም ከሰማይ ጠል ከምድርም ስብ የእህልንም የወይንንም ብዛት ይስጥኽ፤ አሕዛብ ይገዙልህ ሕዝብም ይስገዱልህ፤ ለወንድሞችህ ጌታ ኹን የእናትህም ልጆች ይስገዱልህ፤ የሚረግምህ እርሱ ርጉም ይሁን የሚባርክህም ቡሩክ ይሁን፡፡” ብሎባረከው፡፡ ዔሳው ከአደን ደክሞ ውሎ ለአባቱ የሚሆን ምግብ አዘጋጅቶ አባዬ ያልከኝን አዘጋጅቻለሁ፤ ብላ ነፍስህም ትባርከኝ ብሎ አገባለት፡፡ አባቱም አንተ ማነህ? አለው፡፡ እኔ የበኩር ልጅህ ዔሳው ነኝ አለ፡፡ አባቱም አሁን በረከቱን የወሰደው ዔሳው አይደለምን? ወይስ ምርቃትህን ታናሽህ ያዕቆብ አታሎ ወሰደብህ? አለው፡፡ በዚህ ጊዜ ዔሳው በኀይል ጮኸ! መጀመሪያ ብኩርናዬን ቀጥሎ በረከቴን አታሎ ወሰደብኝ እያለ በጣም አዘነ፡፡ አባቱንም እንዲህ ብሎ ጠየቀው በረከትህ አንዲት ብቻ ናት? አባቱ ይሥሐቅም “እንሆ መኖሪያኽ ከምድር ስብ ከላይ ከሚገኝ ከሰማይም ጠል ይሆናል፤ በሰይፍህም ትኖራለህ ለወንድምህም ትገዛለህ፤  ነገር ግን በተቃወምኸው ጊዜ ቀንበሩን ከአንገትህ ትጥላለኽ።” አለው ዔሳውም ለእርሱ የተረፈችውን በረከት ተቀበለ፡፡ በያዕቆብም ቂም ይዞ በልቡ “ለአባቴ የልቅሶ ቀን ቀርቧል፣ ከዚያም በኋላ ወንድሜን ያዕቆብን እገድለዋለሁ!” አለ፡፡  ዔሳው የያዕቆብን ሕይወት ለማጥፋት እንደተነሳሳ እናታቸው ርብቃ በማወቋ ያዕቆብን ካደገበት ከኖረበት ቤት ወደ ካራን ምድር ወደ አጎቱ ላባ እንዲሰደድ መክራ ሸኘችው፡፡

 

በመጽሐፍ ቅዱስ በኦሪት ዘፍጥረት ላይ እንደምናነበው ያዕቆብም በእርጅናው ጊዜ ከዐሥራ ሁለቱ ልጆቹ አብልጦ ይወደው የነበረውን ዮሴፍን ወንድሞቹ ሸጠውት ሳለ ነገር ግን ክፉ አውሬ በልቶታል ብለው ዋሹት፤ በዚህም ምክንያት ለልጁ ብዙ ቀን አለቀሰ፡፡ ነገር ግን ዮሴፍ በተሰደደበት ቦታ ሁሉ እግዚአብሔር አብሮት ነበርና ኋላ ላይ ቤተሰቡ በረሀብ ምክንያት ተሰደው ወደ እርሱ በመጡ ጊዜ ለቤተሰቡ መልካም አድርጓል፡፡

 

ልጆች ከዚህ ሁሉ የምንማረው፡-

  1. ለቤተሰቦቻችን በመታዘዛችን የበለጠ እንደሚወዱን፤

  2. እናትና አባትን ማክበር እንዳለብን፤

  3. የእግዚአብሔርን በረከት ለማግኘት መጣር እንዳለብን፤

  4. የተሰጠንን ብኩርና(ሃይማኖት) ማቃለል መናቅ እንደሌለብን፤

  5. መዋሸት የሚያመጣብን መከራ ሥጋ መከራ ነፍስ እንዳለ፤

  6. እግዚአብሔር የገባውን ቃል ኪዳን እንደማያጥፍ እንደማያስቀርብን፤

  7. እግዚአብሔር የአብርሃም የይስሐቅ የያዕቆብ አምላክ ተብሎ እንዲጠራ አላፈረባቸውምና በእነዚህ ደጋግ ቅዱሳን አባቶች ምልጃ መጠቀም እንዳለብን እንማራለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን፡፡

meskel 1

መስቀል (ለሕፃናት)

መስከረም 22 ቀን 2005 ዓ.ም


ቢኒያም ፍቅረ ማርያም


meskel 1እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? እግዚአብሔር ይመስገን፡፡ እንኳን ከዘመነ ዮሐንስ ወደ ዘመነ ማቴዎስ በሰላም አሸጋገራችሁ፡፡ ትምህርት ቤት ተከፍቶ በአዲስ ደብተር፣ በአዲስ እስክርቢቶ፣ በአዲስ ልብስ … ስትማሩ ምን ተሰማችሁ? በጣም ያስደስታል አይደል? ይህ ሁሉ የሆነው እግዚአብሔር አዲስ ዘመን አዲስ ዓመት ስለሰጠን ነው፡፡ መስከረም 17 የሚከበረው የመስቀል በዓልም የእግዚአብሔር ሥጦታ ነው፡፡

 

የዘወትር ጸሎት በሚጸለይበት ጊዜ ስለመስቀል እንዲህ የሚል አልሰማችሁም “…መስቀል ኀይላችን ነው፤ ኀይላችን መስቀል ነው፤ የሚያጸናን መስቀል ነው፤ መስቀል ቤዛችን ነው፤ መስቀል የነፍሳችን መዳኛ ነው፡፡ አይሁድ ይክዱታል እኛ ግን እናምነዋለን፡፡ ያመንነው እኛ በመስቀሉ እንድናለን፡፡ ድነናልም፡፡ …” እያልን የምንጸልየው እኛ በጉልበታችን፣ በእውቀታችን ባለን ነገር ሁሉ እንዳንመካ፤ ነገር ግን በመስቀሉ እንድንመካ ነው፡፡

 

በመስቀል እንመካለን ምክንያቱም መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከጥንት ጀምሮ ማለትም ከአባታችን አዳም ከእናታችን ሔዋን ጀምሮ እስከ አሁን ጠላታችን የሆነው ዲያብሎስን እንደ ደካማ በመስቀል ተሰቅሎ /ተቸንክሮ/ ድል ስላደረገው፤ አዳምና ሔዋንን ከሲዖል እስራት ነፃ ስላደረጋቸው ነው፡፡ ለእኛም መስቀሉ መመኪያችን ሆኖ ዲያብሎስ መስቀሉን ሲያይ ይሸሸናልና ነው፡፡

 

ልጆች መስከረም 17 የምናከብረው የመስቀል ደመራ በዓል ምክንያት አይሁድ መስቀሉ የታመሙትን እንደሚፈውስ፣ የሞቱትን እንደሚያስነሣ ባወቁ ጊዜ በክፉ ቅናት ተነሣሥተው በመስቀሉ ክብር እንዳይገኝ ቆፍረው ቀብረውት፣ ቆሻሻ መጣያም አድርገውት ስለነበር እግዚአብሔርም መስቀሉ ተቀብሮ እንዲቀር ስላልፈለገ ንግሥት እሌኒን አስነሥቶ አባ መቃርስ እና አባ ኪራኮስ በሚባሉ አባቶች መሪነት በቦታው በደረሱ ጊዜ ቦታው ከቆሻሻው ክምር የተነሣ ተራራ ሆኖ ስለነበር ትክክለኛው ቦታ የት እንደሆነ ማወቅ አልቻሉም፡፡

 

ንግሥት እሌኒም ወደ እግዚአብሔር በመጸለይዋ የእግዚአብሔር መልአክ ተገልጦላት ደመራ እንድትደምር በዚያም ላይ እጣን እንድትጨምር ስለነገራት አገልጋዮቿን ወታደሮቿን ጠርታ በአካባቢው ደመራ እንዲተክሉ፣ እንዲያቀጣጥሉ፣ እጣንም እንዲጨምሩበት ነገረቻቸው፡፡ በተባሉትም መሠረት አድርገው ጢሱ  ወደሰማይ ከወጣ በኋላ በእግዚአብሔር ኀይል ተመልሶ መስቀሉ ወደ ተቀበረበት ተራራ አመለከተ፡፡ በዚህ ጊዜ ንግሥት እሌኒ እና አገልጋዮቿ ደስ አላቸው፡፡

 

ከስድስት ወራት ቁፋሮ በኋላ ሦስት መስቀሎች ተገኙ፡፡ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀልም የታመሙትን ሲፈውስ ሙት ሲያስነሣ በማየታቸው ከሁለቱ መስቀሎች ለመለየት ችለዋል፡፡ ዲያብሎስ በአይሁድ ላይ አድሮ መስቀሉን ቢደብቅም በእግዚአብሔር ኀይል ሊገኝ ችሏል፡፡ ልጆች መስቀላችሁን አትደብቁ እሺ! ቸር ሰንብቱ፡፡

የአባ ማሩ ተረት /ለሕፃናት/

ግንቦት 7/2004 ዓ.ም.

በልያ አበበ

እንደምን አላችሁ ልጆች! እግዚአብሔር ይመስገን ደኅና ነን እንደምትሉ አልጠራጠርም፡፡ ዛሬ የምነግራችሁ ተረት ስለ አንበሳ፣ ጥንቸልና አሳማ ነው እሺ በጣም ጥሩ ልጆች ተረቱን ልንገራችሁ?  ግን እኮ ስለራሴ አላስተዋወኳችሁም፡፡ ስሜ አባ ማሩ ዘነበ ይባላል፡፡ ቁመቴ በጣም አጭር ነው፡፡ ፊቴ ደግሞ ልክ እንደ ብርቱካን ክብ ሆኖ ዓይኖቼ ትናንሽ ናቸው፡፡ ሁል ጊዜ የምለብሰው ነጭ ሱሪና ነጭ ሸሚዝ ነው፡፡ ከእጄ ነጭ ጭራ አይለይም፡፡ ለምን ነጭ ጭራ እንደምይዝ ታውቃላችሁ? በሰፈሬ የሚኖሩ እንደ እናንተ ያሉ ሕፃናት ወደ 12፡00 ሰዓት አካባቢ ፀሐይ ስትገባ ተሰብስበው ይመጡና “አባ ማሩ ዘነበ ተረት ይንገሩን?” እያሉ በዙሪያዬ ስብስብ ይላሉ፡፡ እኔም ልጆችን በጣም ስለምወዳቸው ትንሸን ወንበሬን ይዤ ከቤቴ እወጣና ከግቢያችን ካለው ሰፊ ሜዳ ቁጭ እላለሁ፡፡ ልጆችም በዙሪያዬ ይሰበሰባሉ እሳት እየሞቅን ተረቱን አጫውታቸዋለሁ ታዲያ ያን ጊዜ ትንኞች በአፌ ውስጥ እንዳይገቡ በነጩ ጭራዬ እከላከላቸዋለሁ፡፡ ስለራሴ ይኸን ያኽል ከነገርኳችሁ ወደ ተረቴ ልመለስ፡፡ ዝግጁ ናችሁ ልጆች? ጎበዞች፡፡

 

ተረት ተረት፤ “የመሠረት” አላችሁ፤ በአንድ ሰፊ ደን ውስጥ አንበሳ፣ ጥንቸልና አሳማ ይኖሩ ነበር፡፡ ከዕለታት በአንደኛው ቀን አንበሳው በጣም ስለራበው ምግብ ፍለጋ ከዋሻዋ ሲወጣ “እግዚአብሔር ሆይ ዛሬ በጣም ስለራበኝ እባክህን ምግብ ስጠኝ?” ብሎ ጸለየ፡፡ ጸሎቱን እንደጨረሰ ከፊት ለፊቱ ጥንቸልን ተመለከታት አንበሳውም “አምላኬ ሆይ ጸሎቴን ሰምተህ ምግብ እንድትሆነኝ ጥንቸልን ስላዘጋጀህልኝ አመሰግንሃለሁ” ብሎ አፉን ከፍቶ ዐይኑን አፍጥጦ ቆመ… ጥንቸልም አንበሳውን ስታይ በጣም ደነገጠችና “ወይኔ አምላኬ ይኼ አንበሳ በጣም ያስፈራል እባክህን የዛሬን ብቻ ከዚህ አንበሳ አፍ አውጣኝ” ብላ ጸለየች፡፡

 

አንበሳው፡- “እግዚአብሔር ሆይ አብላኝ” በማለት እየ ጸለየ ጥንቸሏም “እግዚአብሔር ሆይ ከዚህ አንበሳ አድነኝ” እያለች እየጸለየች ሁለቱም መሮጥ ጀመሩ፡፡ አንበሳው ከኋላ ሲያባርራት ጥንቸሏም ስትሮጥ አንድ ወንዝ አገኘች፡፡ ወንዙን ዘላ ስትሔድ ከወንዙ አጠገብ አንድ አሳማ በልቶ ጠጥቶ ጸሎት ሳያደርግ ተኝቶ ነበር፡፡ አንበሳውም ዞር ሲል የተኛ አሳማ ተመለከተ ወዲያው አንበሳው የተኛ አሳማ ከአጠገቤ እያለ ከጥንቸል ጋር ምን አሯሯጠኝ አለና ጥንቸሏን ትቶ አሳማውን በላ፡፡ ከዚያ በኋላ የጥንቸሏን መዳን የአንበሳውን መብላት የአሳማውን መበላት ያዩ አንድ ሽማግሌ

 

“ልብላም ያለ በላ፤ ልውጣም ያለ ወጣ ከመሐል የተኛ አሳማ ተበላ” ብለው ግጥም ገጠሙ ይባላል፡፡

 

ልጆች ከዚህ ታሪክ ምን ተማራችሁ? ጸሎት ከመጥፎ ነገር ያድናል ካላችሁ ትክክል ናችሁ፡፡ ስለዚህ እናንተም ምግብ ስትበሉ ማታ ስትተኙ ጠዋት ስትነሡ አባታችን ሆይ የሚለውን ጸሎት ከጸለያችሁ ከመጥፎ ነገር ትድናላችሁ እሺ፡፡

 

ለዛሬው ተረቴን ከዚህ አቆማለሁ በሌላ ጊዜ በሌላ ተረት እስክንገናኝ ድረስ ደኅና ሁኑ ልጆች፡፡

የደጉዋ እናት ልደት/ለሕፃናት/

ግንቦት 3/2004 ዓ.ም.

በሊያ አበበ

በኢየሩሳሌም አገር የሚኖሩ ኢያቄምና ሃና የተባሉ በጣም ደጋግ ሰዎች ነበሩ፡፡ ኢያቄምና ሃና ለእግዚአብሔር የታዘዘ  በተቀደሰ ጋብቻ ውስጥ በብዙ ዘመናት አብረው ቢኖሩም በነዚያ ጊዜያት ወስጥ አንድ ልጅ እንኳ ስላልነበራቸው እጅግ ያዝኑ ነበር፡፡ ወደ ቤተ መቅደስ እየሄዱ እግዚአብሔር ልጅ ይሰጣቸው ዘንድ አጥብቀው ይለምኑት ነበር፡፡

ከእለታት አንድ ቀን ኢያቄምና ሃና እርግቦች ጫጩቶቻቸውን ሲያጫውቱ ተመልክተው “ለነዚኽ ወፎች እንኳ ልጆችን የሰጠህ አምላክ ለእኛስ መች ይሆን ልጅ የምትሰጠን?” ብለው እጅግ አምርረው አለቀሱ፡፡ ከሐዘናቸውም ጽናት የተነሳ እንቅልፍ ያዛቸውና ተኙ፡፡

 

በተኙ ግዜም ለሁለቱም እግዚአብሔር መልካም ፈቃዱን በህልም ገለጠላቸው፡፡ ኢያቄም በህልሙ ሃና በእቅፍ ውስጥ ከፍሬዎች ሁሉ የምትበልጥ መልካም ጣፋጭ ፍሬ ይዛ ተመለከተ፡፡ ሃና የኢያቄም በትር ለምልማ፣ አብባና አፍርታ ተመለከተች፡፡ ከእንቅልፋቸውም ነቅተው ስለ ህልማቸው ተነጋገሩ፡፡ የእግዚአብሔር ፈቃድ እንዲሆንላቸው በጸሎት ጠየቁ፡፡ እግዚአብሔር ወንድም ሆነ ሴት ልጅ ቢሰጣቸው አድጎ እኛን ያገልግለን ይታዘዘን ሳይሉ ለቤተ እግዚአብሔር አገልጋይ እንዲሆን እንደሚሰጡት ቃል ገቡ፡፡

 

ከዚህ በኋላ ነሐሴ 7 ቀን ሃና ፀነሰች፡፡ ሃና በእርጅናዋ ጊዜ መፅነሷ የተመለከቱ ዘመዶቿና ያገሯ ሰዎች ተገርመው እየመጡ ይጠይቋት ነበር፡፡ ከነዚህም ሰዎች መካከል አንዱ ዐይነ ስውር የነበረችው የአርሳባን ልጅ ናት፡፡ የአርሳባን ልጅ ወደ ሃና መጥታ እውነትም ሃና መጽነሷን ለማረጋገጥ ሆዷን ዳሰሰቻት፡፡ በአድናቆትም ሳታስበው ዐይኗን ስትነካ ዐይኗ በራላት፡፡ በሌላ ግዜም የአጎቷ ልጅ በህመም ምክንያት ይሞትና ሃና ትወደው ስለነበር ልታለቅስ ወደአረፈበት ቤት ትሔዳለች፡፡ እንደደረሰችም አስክሬኑ በተቀመጠበት መካከል አልጋ ዙሪያ ስታለቅስ ሳለ ድንገት ጥላዋ ቢያርፍበት የሞተው ሰው ተነስቶ ሃና የአምላክ እናት የምትሆን እመቤታችንን እንደምልድና በዚህም ሃና እጅግ የከበረችና ምስጋና የሚገባት መሆኗን መሰከረ፡፡

 

ሃና በፀነሰች ግዜ የተደረጉ ብዙ ተአምራትን አይሁድ አይተው ገና በፅንስ ግዜ ይህን ያክል ተአምራት ያደረገ ሲወለድማ ብዙ ነገር ያደርጋል ብለው በምቀኝነት ተነሳስተው ኢያቅምና ሃናን ሊገድሏቸው ተነሱ፡፡ እግዚአብሔር ግን መልአኩን ልኮ ኢያቄምና ሃና ወደ ሊባኖስ ተራራ እንዲሸሹ አደረጋቸው፡፡ በዚያም ሆነው ግንቦት 1 ቀን ከንጋት ኮከብ ይልቅ የምታበራ እጅግ ያማረች የተቀደሰች የምትሆን ልጅን ወለዱ፡፡ ስሟንም ማርያም አሏት፡፡ ልጆች እኳን ለእመቤታችን ለቅድስት ድንግል ማርያም የልደት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፡፡

st.Tomas

ዳግም ትንሣኤ (ለሕፃናት)

ሚያዝያ 12/2004 ዓ.ም.

በእኅተ ፍሬስብሐት

st.Tomasጌታችን በተነሣበት ዕለት የክርስቶስ ደቀመዛሙርት ተሰብስበው ሳለ ጌታችን በመካከላቸው ቆመና “ሰላም ለእናንተ ይሁን “አላቸው፡፡ የነበሩበት ቤት በሩም መስኮቱም ተቆልፎ ስለነበር ደቀ መዛሙርቱም በጣም ደነገጡ፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም  “አትፍሩ እኔ አምላካችሁ ነኝ” ብሎ የተወጋ ጎኑን እና የተቸነከሩ እጆቹን አሳያቸው፡፡ እነርሱም ጌታ ከሞት መነሣቱን አመኑ፡፡ ደቀመዛሙርቱንም(ተማሪዎቹንም) ሕዝቡን እንዲያስተምሩ ላካቸው፡፡

በዚህ ዕለት ከ12ቱ ደቀመዛሙርት አንዱ የሆነው ቶማስ ከእነርሱ ጋር አልነበረም፡፡ ደቀመዛሙርቱ የጌታን መነሣት እና እነርሱም እነዳዩት ነገሩት፡፡ እርሱ ግን በዓይኔ ካላየሁ አላምንም አለ፡፡

 

ከስምነት ቀን በኃላ እንደገና ቶማስ አብሯቸው ሳለ በሩ እንደተዘጋ ጌታችን መጣ፣  በመካከላቸውም ቆሞ “ሰላም ለእናንተ ይሁን” አላቸው፡፡ ቶማስ ትንሣኤውን እነደተጠራጠረ ስላወቀ  እጅህን አምጣና የተወጋ ጎኔን እና የተቸነከሩ እጆቼን ዳስስ አለው፡፡ ቶማስም በዳሰሰው ጊዜ አምላክ መሆኑን ዐወቀ፡፡ ይኽ ዕለት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሁለተኛ ጊዜ ቶማስ ባለበት  ለደቀመዛሙርቱ የተገለጠበት ዕለት በመሆኑ ዳግም ትንሣኤ ተብሎ ተሰየመ፡፡ ዳግም ማለት ሁለተኛ ማለት ነው እሽ ልጆች፡፡ በሚቀጥለው ሳምንት በሌላ ታሪክ እሰክንገናኝ ደኅና ሁኑ!

ትንሣኤ /ለሕፃናት/

ሚያዝያ 6/2004 ዓ.ም.

በልያ አበበ

ልጆች መግደላዊት ማርያምን ታውቋታላችሁ? መግደላዊት ማርያም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከፈወሳቸው ሕመምተኛ የነበሩ ሰዎች አንዷ ናት፡፡ ከነበረባት በሽታ ከዳነች ጊዜ ጀምሮ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሚያስተምረውን ትምህርት በሙሉ የምትከታተል እና እርሱንም የምታገለግል ነበረች፡፡
መግደላዊት ማርያም ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአይሁድ እጅ ተገርፎ ሲሰቀል ከሌሎች ከገሊላ ከመጡ ብዙ ሴቶች ጋር ሆና በጣም አዝና በሩቅ ስትመለከት ነበር፡፡
ዮሴፍና ኒቆዲሞስ የተባሉት እግዚአብሔር የባረካቸው ደጋግ ሰዎች የጌታችንን ቅዱስ ሥጋ ከጲላጦስ ተቀብለው እያመሰገኑ በንጹሕ በፍታ ወይም የመግነዝ ጨርቅ ሲከፍኑት፤ በአዲስ መቃብርም አኑረው የመቃብሩን ደጃፍ ሲዘጉ መግደላዊት ማርያም በመቃብሩ አንጻር ተቀምጣ ትመለከት ነበር፡፡
አይሁድ የጌታችን መቃብርን እንዲጠብቁ ጠባቂ ወታደሮችን አዝዘው ነበር፡፡ መግደላዊት ማርያም እሑድ ዕለት በጠዋት የጌታችንን ቅዱስ ሥጋ ለመቀባት ያዘጋጀችውን ሽቱ ይዛ ሌሎቹንም ሴቶች አስከትላ ወደ መቃብሩ ወጣች፡፡ ወደመቃብሩ ስትደርስ የመቃብሩ ድንጋይ ተንከባሎ ነበር፡፡ በድንጋጤ ወደ ውስጥ ስትገባም የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ሥጋ አላገኘችውም፡፡ የጌታችንን ሥጋ ማን እንደወሰደው ልታውቅ አልቻለችም፡፡
እየሮጠችም ወደ ሐዋርያት መጥታ “ጌታን ከመቃብር ወስደውታል ወዴትም እንዳኖሩት አናውቅም” አለቻቸው፡፡ ጴጥሮስና ዮሐንስ ይህን በሰሙ ጊዜ ወጥተው ወደ መቃብሩ ሮጡ፡፡ ወደ መቃብሩ ውስጥ ሲመለከቱም የተከፈነበትን ጨርቅ ብቻ ተመለከቱ፡፡ ስለዚህም ወደ ቤታቸው ተመለሱ፡፡ መግደላዊት ማርያም ግን እያለቀሰች ከመቃብሩ ውጭ ቆማ ቆየች፡፡ ድንገት ወደ መቃብሩ ዝቅ ብላ ብትመለከት ሁለት መላእክት የጌታችን ሥጋ በነበረበት ቦታ ላይ ተቀምጠው አየች፡፡
እነርሱም ለምን እንደምታለቅስ ጠየቋት፡፡ እርስዋም “ጌታዬን ወስደውታል ወዴትም እንዳኖሩት አላውቅም” አለቻቸው፡፡ ይህንንም ብላ ወደ ኋላ ዘወር ስትል አንድ ሰው ቆሞ አየች፡፡ የአትክልት ቦታው ጠባቂ መስሏት፡፡ ሰውየው “ለምን ታለቅሻለሽ? ማንንስ ትፈልጊያለሽ?” አላት እርሷም የጌታዬን ሥጋ አንተ ወስደኸው ከሆነ ወዴት እንዳኖርኸው ንገረኝ” አለችው፡፡
ልጆች ያነጋግራት የነበረው ሰው ግን የአትክልት ቦታ ጠባቂው አልነበረም፡፡ ማን እንደሆነ አወቃችሁ? አዎ፡፡ የሚወደን ስለ እኛ የሞተልን ከሙታንም መካከል ተለይቶ በሦስተኛው ቀን የተነሣው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነበር፡፡ በመጨረሻም በስሟ ማርያም ብሎ ሲጠራት አወቀችው፡፡ ከሙታን ተለይቶ እንደተነሣ ለሐዋርያት በሙሉ እንድትነግር ላካት፡፡ እርሷም በደስታ ወደ ሐዋርያት ተመልሳ ነገረቻቸው፡፡ ልጆች ጌታችን ከሙታን ከተነሣ በኋላ በመጀመሪያ ያየችው መግደላዊት ማርያም ነበረች፡፡
ልጆች በጌታችን ትንሣኤ ደስ አልተሰኛችሁም? ክርስቲያኖች በሙሉ በትንሣኤ በዓል በደስታ እንዘምራለን አምላካችንን እናመሰግናለን፡፡ መልካም የትንሣኤ በዓል ይሁንላችሁ፡፡
ልጆች ይህን ታሪክ የምታገኙት ከመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 20 ቁጥር 1 ላይ ነው፡፡