ሰሙነ ሕማማት(ለህጻናት)

ሚያዚያ 1/2004 ዓ.ም.

በአዜብ ገብሩ

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ደህና ናችሁ? እንኳን ለሰሙነ ሕማማት በሰላም አደረሳችሁ፡፡ ልጆች ሰሙነ ሕማማት ምን ማለት እንደሆነ ታውቃላች? ሰሙነ ሕማማት ከትንሣኤ በፊት ያለውን ሳምንት ሲሆን በዚህ ሳምንት ጌታችን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛን የሰው ልጆች ለማዳን ሲል የተቀበለውን መከራ ከሌላ ጊዜ በተለየ መልኩ የምናስብበት ሳምንት ነው፡፡ ጌታችን በዚህ ሳምንት ውስጥ ባሉት ቀናት ውስጥ የተለያዩ ተግባራት አከናውኗል፡፡ እስኪ ልጆች ቀናቱንና በቀናቱ ውስጥ የተፈጸሙትን ተግባራት በዝርዝር እንመልከት፡-

1. እሑድ /ሆሣዕና/፡- በዚህ ዕለት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአህያ ጀርቦ ተቀምጦ ወደpalmsunday.jpg ኢየሩሳሌም ሲገባ ይከተሉት የነበሩት ሰዎች በተለይም ሕፃናት ሆሣዕና ለዳዊት ልጅ በጌታ ስም የሚመጣ የተባረከ ነው ብለው እየዘመሩ ጌታችንን አመስግነውታል፡፡

2. ሰኞ፡- ይህ ዕለት የሆሣዕና ማግስት ሲሆን በዚህ ዕለት ጌታችን ሁለት ዋና ዋና ተግባራትን አከናውኗል፡፡

  • ጌታችን እርቦት ስለነበር ወደ አንዲት በለስ ሄደ፡፡ በለሷ ግን ቅጠል ብቻ ሆና ፍሬ አላገኘባትም ነበር፡፡ ያቺ በለስም ዳግመኛ ፍሬ እንዳታፈራ ረገማት፡፡
  • ወደ ቤተ መቅደስ ገብቶ የሚሸጡትንና የሚለውጡትን ሰዎች አስወጣቸው፡፡

– ልጆች በዚህ ዕለት ማር.11÷12-19 እና ሉቃ.19÷45-46 ላይ የሚገኘውን የወንጌል ክፍል አንብቡ፡፡

3. ማክሰኞ፡- በዚህ ዕለት ጌታችን ስለሥልጣኑ ተጠይቋል፡፡ የጠየቁትም የካህናት አለቆች ነበሩ፡፡ ጌታችን በዚህ ምድር በነበረበት ወቅት ብዙ ተአምራትን አከናውኗል፡፡ የታመሙትን ፈውሷል፣ የተራቡትን መግቧል፣ …፡፡ እናም የካህናት አለቆች ይህን ሁሉ ተአምር በምን ሥልጣን እንደሚያደርግ ነበር የጠየቁት፡፡ ልጆች በዚህ ጥያቄ መሠረት ጌታችን ቀኑን ሙሉ በቤተ መቅደስ ውስጥ ረጅም ትምህርት አስተምሯል፡፡
– በዚህ ዕለት ማቴ.21÷23፣ ማር.11÷27፣ ሉቃ.20÷1 ላይ የሚገኘውን የወንጌል ክፍል አንብቡ እሺ፡፡
4. ረቡዕ፡- በዚህ ዕለት ሦስት ነገሮች ተደርገዋል፡-

  • የካህናት አለቆች ጌታን ሊሰቅሉት ተማክረዋል
  • ጌታ በስምዖን ቤት ተገኝቶ ሳለ አንዲት ሴት ሽቶ ቀብታዋለች፡፡
  • ይሁዳ የተባለው ሐዋርያ ጌታን ለካህናት አለቃ አሳልፎ ለመስጠት በ30 ብር ተስማምቷል፡፡
– በዚህ ዕለት ማቴ.26÷3-16፣ ማር.14÷1-11፣ አና ሉቃ.22÷1-6 ላይ የሚገኘውን የወንጌል ክፍል አንብቡ እሺ፡፡
5. ሐሙስ፡- በዚህ ዕለት ጌታችን ለእኛ ያለውን ፍቅር የሚያሳዩ ተግባራትን አከናውኗል፡፡

  • ጌታ የሐዋርያትን እግር አጠበ
  • የቊርባንን ሥርዓት ሠራ
  • በዮሐንስ ወንጌል ምራፍ 17 ላይ ያለውን ረጅም ጸሎት በጌቴ ሴማኒ ጸለየ፡፡
  • በዚህ ዕለት ሌሊት ይሁዳ ጌታን አሳልፎ ለካህናት አለቆች ሰጠው፤ ወታደሮችም ያዙት፡፡

– በዚህ ዕለት ዮሐ.18÷1-12፣ ሉቃ.22÷7-53፣ ማቴ.26÷17 ላይ የሚገኘውን የወንጌል ክፍል አንብቡ፡፡

6. ዐርብ፡- ይህ ዕለት “ስቅለተ ዐርብ” በመባል ይታወቃል፡፡ በዚህ ዕለት የተለያዩ ድርጊቶች በጌታችን ላይ ተፈጽመዋል፡፡
  • የእግዚአብሔር ልጅ ነኝ በማለቱ በጲላጦስ ፊት በሐሰት ከሰሱት፡፡ በዚህ ዕለት ጌታችን ስለ እኛ ሲል ተሰቀለ፡፡ በሰዎች ፈንታ ሞትን ተቀበለ፡፡
– በዚህ ዕለት ማቴ.27÷1-60 ላይ የሚገኘውን የወንጌል ክፍል አንበቡ፡፡
እንግዲህ ልጆች በሰሙነ ሕማማት በእያንዳንዱ ዕለት የተፈጸሙትን ተግባራት በደንብ ተረድታችሁ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሂዱ፡፡ የሰሙነ ሕማማት ጸሎት ያለበት መጽሐፍ ይዛችሁ ሥርዓቱን በደንብ ተከታተሉ፡፡ በየዕለቱ የሚነበበውን የወንጌል ክፍል አንብቡና ያልገባችሁን ታላላቆቻችሁን ጠይቁ፡፡ አቅማችሁ የቻለውን ያህል ስግደት ስገዱ፡፡ በሉ እንግዲህ ልጆች መልካም የሰሙነ ሕማማት ሳምንት ይሁንላችሁ እሺ፡፡ ደህና ሁኑ ልጆች፡፡

ድንቅ ቀን /ለሕፃናት/

መጋቢት 28/2004 ዓ.ም.

በልያ አበበ


ልጆች የዕረፍት ጊዜያችሁ ወይም የጨዋታ ሰዓት ሲደርስ በጣም ትደሰታላችሁ አይደል? እኔና ዘመዶቼ ደግሞ ዓመቱን ሙሉ ሰዎችን በማገልገል እነርሱንና ዕቃዎቻቸው ከቦታ ቦታ ለማጓጓዝ ስንለፋ እና ስንደክም የምንኖር ቢሆንም በዓመቱ ውስጥ ግን ልክ እንደሰዎች እጅግ ተደስተንባቸው የምናሳለፋቸው በዓላት አሉ፡፡

 

Hosaena

 

አንደኛው በዓል የሁላችን ፈጣሪ የሆነው ኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ነው ለዚያ ቀን እርሱ ቤተልሔም በሚገኝ የዘመዶቻችን ቤት /በሰዎች አጠራር በረት/ ውስጥ ሲወለድ አንደኛ በትሕትና በእንስሳት ቤት ለመወለድ በመምረጡ ሁለተኛ እጅግ ብርዳማ በነበረው የልደቱ ዕለት የእኛ ዘመዶች የሰው ልጆች እንኳን ያላደረጉትን በትንፋሻቸው እንዲሞቀው ስላደረጉ በጣም ደስተኞች ነን፡፡

ስሜ ደስተኛዋ አህይት ነው፡፡ አሁን የምነግራችሁ በሕይወቴ እጅግ የተደሰትኩበትና እኔና ዘመዶቼ እስካሁን የምንወደውን ሌላኛውን ቀን ነው፡፡ ቀደም ብዬ የነገርኳችሁን የቤተልሔሙን ልደት የነገረችኝ አንደኛዋ አክስቴ አህያ ናት፡፡ ሁል ጊዜም ያንን ታሪክ እንደ አክስቴ እኔም በቤተልሔም በረት ውስጥ በነበርኩ እል ነበር፡፡

 

ያ ቤተልሔም በሚኖሩ ዘመዶቻችን ቤት የተወለደው የዓለም ሁሉ ፈጣሪ እኛ እንኖርበት በነበረው ሀገር ለ30 ዓመት ከኖረ በኋላ የሀገራችን ሰዎች ሁሉ ማስተማር ጀመረ፡፡

 

እኔና እናቴ የምንኖረው ደብረ ዘይት ቤተ ፋጌ ከሚባለው ቦታ ጥቂት እንደተሔደ በምትገኘው ትንሽ መንደር ነበር፡፡ የእኛ ባለቤት የሆነው ሰው ፈጣሪያችን በትንሽዬዋ የእንስሳት ቤት ሲወለድ የተደረጉትን ነገሮች ማለቴ የእረኞችና የመላእክትን ዝማሬ የሦስቱ ነገሥታት ስጦታን ማምጣት ሰምቶ ስለነበር ኢየሱስ ክርስቶስ በሚያስተምርበት ቦታ ሁሉ እየሔደ ይማር እጅግም ይወደው ነበር፡፡

 

ታዲያ አንድ ቀን ምን ሆነ መሰላችሁ፡፡ እናቴ ባለቤታችን አንድ ሁል ጊዜው ለብርቱ ሥራ ሊፈልገን ስለሚችል ብላ በጠዋት ቀሰቀሰችኝ፡፡ በሚያስገርም ሁኔታ ሌላ ቀን ስትቀሰቅሰኝ ተኝቼ ማርፈድ የሚያምረኝ ቢሆንም የዚያን ቀን ወዲያውኑ ነበር የተነሣሁት፡፡ ፊቴን ከታጠብኩ እና ሰውነቴ ላይ ያለውን አቧራ ካራገፍኩ በኋላ ከእናቴ ጋር ሆነን ለዛ ቀን ያደረሰንን እና ጣፋጯን የጠዋት ፀሐይ እንድንሞቅ ላደረገው ፈጣሪያችን ጮክ ብለን እየጮህን ምስጋና አቀረብን፡፡

 

አሳዳሪያችን ከበረታችን አውጥቶ የቤቱ በር ላይ ባለ የእንጨት ምሰሶ ላይ አሰረንና ወደ ሌሎች ሥራዎች ተሰማራ፡፡ አሳዳሪያችን እንዲህ የሚያደርገው እርሱ ወደገበያ የማይወጣ እኛንም የሚያሥረን ሥራ ከሌለው ነው፡፡ እኔም እናቴም ቀኑን በሙሉ በማናውቀው ምክንያት ደስ ሲለን ዋለ፡፡

 

የሆነ ሰዓት ላይ ከሩቅ ሁለት ሰዎች ወደ እኛ መንደር ሲመጡ አየናቸው፡፡ ሰዎቹ እየቀረቡ መጡና እኛ ጋር ሲደርሱ አጎንብሰው የታሠርንበትን ገመድ ፈቱልን፡፡ ሰዎቹ ለጌታችን ፈጣሪያችን እንደሚፈልገን ነገሩን፡፡ እኛም በደስታ አብረናቸው ሔድን፡፡

 

ፈጣሪያችን ወደነበረበት ስንደርስ ምን እንደተደረገ ልንገራችሁ? ፈጣሪያችን በእኔ ላይ ልብስ ተነጥፎለት ተቀመጠና ወደ ኢየሩሳሌም ጉዞ ጀመርን፡፡ ምን ያህል እንደተደሰትኩ ልነግራችሁ አልችልም፡፡ በመንገድ የምናገኛቸው ሰዎች በሙሉ ሆሣዕና በአርያም እያሉ እየዘመሩ ልብሶቻቸውና የዘንባባ ዝንጣፊ በምናልፍበት መንገድ ላይ ያነጥፉ ነበር፡፡ ትንንሽ ሕፃናትም በእግዚአብሔር ስም የሚመጣ የተባረከ ነው እያሉ ዘመሩ፡፡ ትልልቆቹ መምህራን ግን ልጆቹን ተቆጥተው ዝም በሉ አሏአቸው፡፡ ነገር ግን አንድ ተአምራዊ ነገር ተከሰተ፡፡ በመንገድ ላይ የነበሩ ድንጋዮች ሁሉ ልክ እንደ ሰው መዘመርና ፈጣሪያችንን ማመስገን ጀመሩ፡፡

 

ልጆች በዚያን ቀን ፈጣሪዬን በጀርባዬ ተሸክሜ 16 ምዕራፍ ያክል ወደ ኢየሩሳሌም ቤተ መቅደስ ወሰድኩት ታዲያ ይህንን ቀን እኛ አህዮችና ሌሎችም እንስሳት በታላቅ ደስታ እናከብረዋለን፡፡ ሆሣዕና ሕፃናት ፈጣሪያችንን ያመሰገኑበት ቀን ስለሆነ በቤተ ክርስቲያን ተገኝታችሁ አክብሩት እሺ ልጆች፡፡

niqodimos_

ኒቆዲሞስ/ለሕፃናት/

መጋቢት 21 2004ዓ.ም

በቴዎድሮስ እሸቱ

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ደህና ናችሁ? መልካም ይኸው ዘወረደ ብለን በመጀመሪያው ሳምንት የጀመርነው ጾም ዛሬ ኒቆዲሞስ ላይ ደርሷል፡፡ ኒቆዲሞስ የ7ኛው ሳምንት መጠሪያ ነው፡፡

niqodimos_

ልጆች የአይሁድ መምህር የሆነ አንድ ኒቆዲሞስ የሚባል ሰው ነበር፡፡ ይህ የአይሁድ መምህር ማታ ማታ እየመጣ ከክርስቶስ እግር ስር ቁጭ ብሎ ትምህርት ይማር ነበር፡፡ ልጆች ማታ ማታ እየመጣ የሚማረው ለምን መሰላችሁ፡፡

 

አንደኛ የአይሁድ መምህር ስለሆነ ሲማር እንዳያዩት ነው፡፡ ሲማር ካዩት ገና ሳይማር ነው እንዴ የሚያስተምረን እንዳይሉት፡፡ ሁለተኛ አይሁድ ክርስቶስን ያመነና የተከተለ ከሀገራችን /ከምኲራባችን/ ይባረራል ብለው ስለነበር እንዳይባረር ፈርቶ ሦስተኛ ደግሞ ሌሊት ሲማሩ ምንም የሚረብሽና ዐሳብን የሚሰርቅ ነገር ስለሌለ ትምህርት በደንብ ይበገባል ብሎ በማሰብ ነው፡፡ እናንተስ በሌሊት ትምህርታችሁን የምታጠኑት እንዲገባችሁ አይደል ልጆች? በሌሊት ዐሳባችሁ አይበተንም፡፡

ታዲያ አንድ ቀን ማታ ክርስቶስ ለኒቆዲሞስ ስለ ጥምቀት አስተማረው፡፡ “ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በስተቀር የእግዚአብሔር መንግሥት ሊወርስ አይችልም” አለው፡፡ ኒቆዲሞስም “ሰው ከሸመገለ ካረጀ በኋላ እንዴት ድጋሚ ሊወለድ ይችላል” ብሎ ጠየቀ ክርስቶስ ዳግም ልደት ማለት ሰው በጥምቀት የሚያገኘው የእግዚአብሔር ልጅነት እንደሆነ ሰው ተጠምቆ የእግዚአብሔር ልጅ ካልሆነ መንግሥተ ሰማያትን እንደማይወርስ አስተማረው፡፡ ኒቆዲሞስም ስለ ጥምቀት በሚገባ ተረዳ፡፡

አያችሁ ልጆች እንግዲህ በዚህ ሳምንት ከሚነገረው ታሪክ በርካታ ቁም ነገሮችን እናገኛለን ለምሳሌ እኛ ልጆች የእግዚአብሔርን ቃል ቀን ከሌሊት ሳንል ሁል ጊዜ መማር እንዳለብን፤ ያልገባን ነገር ካለ የቤተ ክርስቲያን አባቶችን ጠይቀን መረዳት እንዳለብን ነው፡፡ እንደዚህ በማድረግ ስለ እምነታችን በቂ እውቀት ልንጨብጥ ይገባናል ማለት ነው፡፡ ለዛሬ አበቃሁ ደህና ሰንብቱ፡፡

12

ገብርኄር /ለሕፃናት/

መጋቢት 14/2004 ዓ.ም.

በቴዎድሮስ እሸቱ

 

ደህ12ና ሰነበታችሁ ልጆች? እንዴት ናችሁ? በጾሙ እየበረታችሁ ነው አይደል? ጎበዞች፡፡ ዛሬ ስድስተኛው ሳምንት ላይ ደርሰናል፡፡ ይህ ሳምንት ገብርኄር ይባላል፡፡ ገብርኄር ማለት ልጆች መልካም አገልጋይ ማለት ነው፡፡ በዚህ ሳምንት በቤተ ክርስቲያናችን ክርስቶስ ስለመልካም አገልጋይ ያስተማረው ትምህርት ይነገራል፡፡ ይህን የተመለከተ ምስጋናም ይቀርባል፡፡

 

አንድ ባለጸጋ አገልጋዮቹን ያስጠራቸውና ለአንኛው 5 መክሊት ለሁለተኛው 2 መክሊት ለሦስተኛው ደግሞ 1 መክሊት ወርቅ ይሰጣቸዋል፡፡ ከዚያም እኔ እስክመጣ በዚህ ወርቅ በመነገድ ተጠቀሙ ብሏቸው ወደሩቅ ሀገር ይሔዳል፡፡ ልጆች መክሊት የወርቅ መለኪያ /መስፈሪያ/ ነው፡፡

ይህም ባለጸጋ ከሔደበት ሀገረ ብዙ ከቆየ በኋላ ወደ ሀገሩ ይመለስና ወርቅ የሰጣቸውን ሰዎች በመጥራት ስለንግዳቸው1212 ይጠይቃቸዋል፡፡ አምስት የተሰጠው አገልጋይ ሌላ አምስት መክሊት አትርፌአለሁ አለው፡፡ ጌታውም አንተ መልካም አገልጋይ ነህ ወርቁን ከነትርፉ ውሰድ ወደጌታህም ደስታ ግባ አለው፡፡ ሁለት መክሊት የተሰጠውም ሌላ ሁለት መክሊት እንዳተረፈ ተናገረ ጌታው እሱንም አንተም መልካም አገልጋይ ነህ በጥቂቱ ታምነሃልና በብዙ እሾምሀለሁ ወደጌታህ ደስታ ግባ አለው፡፡ በመጨረሻም አንድ መክሊት የተሰጠው አገልጋይ መጣ እንዲህም አለ “ጌታዬ አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ ያልበተንከውን የምትሰበስብ ክፉ ጌታ መሆንህን አውቃለሁ ስለዚህ ሌቦች እንዳይሠርቁኝ አታላዮች እንዳይቀሙኝ ብዬ መክሊትህን ቀብሬ እስክትመጣ አስቀምጨዋለሁ አሁንም እንካ ይኸው አንድ መክሊትህ” ብሎ ሰጠው፡፡ ጌታውም “አንተ ክፉ አገልጋይ መቼ ነው እኔ ያልዘራሁትን ያጨድኩት፣ ያልበተንኩትን የሰበሰብኩት አሁን ወርቁን ተቀበሉትና ለባለ አምስት መክሊቱ ስጡት እሱን ደግሞ ወደ ዘለዓለም ሃዘንና መከራ ወዳለብት ወደጭለማው አውጥታችሁ ጣሉት” አላቸው፡፡ አገልጋዮችም ይህንን ክፉ አገልጋይ ወደ ጭለማው አውጥተው ጣሉት፡፡

 

ልጆች እንግዲህ በዚህ ሳምንት የሚነገረው ታሪክ ይህ ነው፡፡ እናንተ ክፉ አገልጋይ እንዳትባሉ ተግታችሁ ሥሩ በሃይማኖት ጠንክሩ እሺ! መልካም ደህና ሰንብቱ፡፡

5debrezeit

ደብረ ዘይት(ለሕጻናት)

መጋቢት 06/2004ዓ.ም

በቴዎድሮስ እሸቱ

 

5debrezeit

ልጆች እንኳን ለጾመ እኩሌታው /ለደብረ ዘይት/ በሰላም አደረሳችሁ፡፡ ይህ አምስተኛው ሳምንት ደብረ ዘይት ይባላል፡፡ የጾሙ እኩሌታ በመሆኑ በቤተ ክርስቲያናችን ታላቅ በዓል ነው፡፡ ልጆች በዚህ ቀን ጌታ በደብረ ዘይት ስለዳግም ምጽአቱ ያስተማረው ትምህርት ይነገራል፡፡ ጌታ ይህን ዓለም ለማሳለፍ ለሁሉም እንደየሥራው ለመክፈል፣ በግርማ መንግሥቱ ይመጣል፡፡

 

በዚህ ዓለም ሰው ከአባት ከእናቱ ተወልዶ ሲወርድ ሲወጣ ኖሮ ይሞታል ሞቶ ግን አይቀርም በዳግም ምፅአት ጊዜ መቃብር ክፈቱልኝ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል ደጉ ደግነቱ ክፉውም ክፋቱን ይዞ ይነሣል፡፡ ወንዱ የሰላሳ ዓመት ጎልማሳ፣ ሴቷ የአሥራ አምስት ዓመት ኮረዳ ሆነው ጻድቃን ብርሃን ለብሰው ከፀሐይ 7 እጅ አብርተው፣ ኀጥአን ጨለማ ለብሰው ፍጹም ዲያብሎስን መስለው ይነሣሉ፡፡

 

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ጻድቃንን “ብራብ አብልታችሁኛል ብጠማ አጠጥታችሁኛል ኑ እናንተ የአባቴ ብሩካን ዓለም ሳይፈጠር ያዘጋጀሁላችሁን መንግሥቴን ውረሱ” ብሎ መንግሥተ ሰማያትን ያወርሳቸዋል፡፡ ኀጥአንን ደግሞ “ሒዱ ከእኔ ለሰይጣንና ለመልእክተኞቹ ወደተዘጋጀው ዘለዓለማዊ እሳት ግቡ” ብሎ ገሀነምን ያወርሳቸዋል፡፡ ጻድቃን ደስ ይላቸዋል፤ ኀጥአን ግን ያዝናሉ ዋይ ዋይ እያሉ ያለቅሳሉ፤ እንባቸውን ያፈሳሉ ግን አይጠቅማቸውም፡፡

 

ልጆች እናንተም በዳግም ምጽአት ኑ እናንተ የአባቴ ብሩካን ከሚላቸው ከጻድቃን ወገን እንድትሆኑ ለተራበ አብሉ፤ አጠጡ፤ ደግ ደግ ሥራ ሥሩ፡፡ ሁላችንንም “ኑ እናንተ የአባቴ ብሩካን ብሎ ከሚጠራቸው ተርታ ያቁመን!

መፃጒዕ /ለሕፃናት/

መጋቢት1/2004 ዓ.ም.

በቴዎድሮስ አሸቱ

እንደምን ሰነበታችሁ? ልጆች ደህና ናችሁ? መልካም እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ አሁን የአብይ ጾም አራተኛው ሳምንት ላይ ደርሰናል፡፡ ለቤተ ክርስቲያናችን ይህ ሳምንት መፃጒዕ ይባላል፡፡ በዚህ ሳንምንት በቤተ ክርስቲያን የሚቀርቡ ምስጋናዎች ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያደረጋችውን ድንቅ ድንቅ ተአምራት /ህሙም መፈወሱን፤ ሙት ማስነሣቱን/ የሚያዘክሩ ናቸው፡፡

መፃጒዕ ማለት ልጆች ድውይ፣ ሕመምተኛ ማለት ነው፡፡ በኢየሩሳሌም አንዲት ቤተሳይዳ ተብላ የምትጠራ የመጠመቂያ ቦታ ነበረች፡፡ ይህቺ የመጠመቂያ ቦታ ጠዋት ጠዋት የእግዚአብሔር መልአክ በክንፉ ያማታታል፣ ያናውጣታል፡፡ በዚህ ሰዓት ወዲያውኑ ገብቶ የተጠመቀ ካለበት በሽታ ሁሉ ይድናል፤ ይፈወሳል፡፡

በዚህች የመጠመቂያ ቦታ 38 ዓመት ሙሉ የተኛ በሽተኛ ነበር ከአልጋው መነሣት ስለማይችል መልአኩ ውኃውን ሲያማታው ቀድሞ መግባትና መጠመቅ አልቻለም ከዕለታት አንድ ቀን ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚያ ሲያልፍ ይህንን መፃጒዕ /ድውይ/ አየውና “ልትድን ትወዳለህን?” አለው ያም መፃጒዕ “ጌታ ሆይ ውኃው በተናወጠ ጊዜ በመጠመቂያይቱ ውስጥ የሚያኖረኝ ሰው የለኝም ሌላው ቀድሞኝ እየገባ ይፈወሳል፡፡ “አለው ጌታችንም ተነሣና አልጋህን ተሸክመህ ሒድ አለው ያም መፃጒዕ ዳነና 38 ዓመት ሙሉ ተኝቶባት የነበረችውን አልጋ ተሸክሞ ወደ ቤቱ ሔደ ዮሐ.5፥1-9

በሉ ልጆች በሚቀጥለው ሳምንት ስለተከታዩ የአብይ ጾም ሳምንት ይዤላችሁ እመጣለሁ እስከዚያው መልካም የጾም ሳምንት ደህና ሰንብቱ፡፡

333 (2)

ስትተባበሩ ሁሉንም ታሸንፋላችሁ /ለሕፃናት/

የካቲት 8/2004 ዓ.ም.

በቴዎድሮስ እሸቱ

ልጆች እንደምን ሰነበታችሁ ከዚህ በታች ያለውን ተረት በደንብ አንብቡ በርካታ ቁም ነገሮችን ታገኙበታላችሁ መልካም ንባብ፡፡
ከእለታት አንድ ቀን በአንድ ሀገር የሚኖር ሰው ነበር ይህ ሰው ዘጠኝ ልጆች ሲኖሩት ሁሉም እርስ በራሳቸው የማይዋደዱ የማይስማሙ ነበሩ333 (2) ሁሉም አባታቸው የሚያወርሳቸውን የራሳቸውን ድርሻ ይዘው ለብቻቸው መኖር ይፈልጉ ነበር፡፡ ከዚያም አንድ ቀን አባታቸው በጠና ታሞ አልጋ ላይ ተኛ ልጆቹንም ጠራቸውና አንድ ትእዛዝ አዘዛቸው ትእዛዙም “ሁላችሁም ሒዱና ለየራሳችሁ አንድ አንድ ጭራሮ ይዛችሁ ኑ” የሚል ነበር፡፡ ከዚያም ልጆቹ ወደውጪ ሔደው ለየራሳቸው አንድ አንድ ጭራሮ ይዘው ተመለሱ፡፡

 

አባታቸውም ታላቁን ልጅ ጠርቶ የያዝከውን ጭራሮ ስበረው አለው ታላቁ ልጅም ጭራሮዋን ቀሽ አድርጎ ሰበራት እንዲህ እንዲህ እያሉ ሁሉም ልጆች የየራሳቸውን ጭራሮዎች ሰበሯቸው፡፡ ከዚያም አባትየው ትልቁን ልጅ ጠራውና የሁሉንም ወንድሞችህን ጭራሮ ሰብስብ አለው፡፡ታላቁ ልጅም የሁሉንም ጭራሮ ተቀብሎ ሰብስቦ ያዘ አባትየውም በል አሁን የያዝካቸውን ጭራሮ አንድ ላይ ስበራቸው አለው፡፡

22ታላቁ ልጅም ቢሞክር ቢሞክር ቢታገል ጭራሮዎቹን ሊሰብራቸው አልቻለም ሁሉም ልጆች ቢሞክሩ አንድ ላይ የተሰበሰቡትን ጭራሮዎች ሊሰብሯቸው አልቻሉም ከዚያም አባትየው ልጆቹ ወደእርሱ እንዲጠጉ በምልክት ጠራቸውና እንዲህ ብሎ ነገራቸው፡፡

ልጆቼ በመጀመሪያ ሁላችሁም የያዛችኋቸውን ጭራሮዎች በቀላል ሰበራችኋቸው በኋላ ግን333 (1) አንድ ላይ ሲሰበሰቡ ከእናንተ ውስጥ ማናችሁም ልትሰብሩ አልቻላችሁም፡፡ እናንተም የምትለያዩ ከሆነ አንድ ላይ የማትሆኑ ከሆነ ጠላት በቀላሉ ያጠፋችኋል ሌባ ይዘርፋችኋል፤ ጠንካራና ጎበዝ ልትሆኑ አትችሉም፡፡ አንድ ላይ ከሆናችሁ ግን ማንም አይደፍራችሁም፡፡ አሁን እኔ ልሞት ነው የማወርሳችሁን ሀብት በጋራ ተጠቀሙበት በመካከላችሁ መለያየት እንዳይኖር አደራ አላቸው፡፡ ከዚያም ትንሽ ቆይቶ ሞተ እነሱም ከዚያች ዕለት በኋላ ሳይጣሉ እርስ በእርስ በመዋደድ በፍቅር አንድ ላይ መኖር ጀመሩ ተባብረው ስለሚሠሩም ሀብታምና ጠንካሮች መሆን ቻሉ፡፡

ልጆቼ እነዚህ ወንድማማቾች ባይተባበሩ ኖሮ ጠንካሮች መሆን አይችሉም ጠላትም በቀላሉ ያጠቃቸዋል፡፡ እናንተም ከጓደኞቻችሁ በመጠየቅ ለጓደኞቻችሁ የምታውቁትን በማስረዳት ልትተባበሩ ይገባል በትብብር ስታጠኑ የሚከብዳችሁ ሁሉ ይቀላችኋል፡፡

በርናባስ ረድእ /ለሕፃናት/

የካቲት 3/2004 ዓ.ም.
በቴዎድሮስ እሸቱ

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች ዛሬ ከ12ቱ አርድእት አንዱ ስለሆነው ስለ ቅዱስ በርናባስ ታሪክ በአጭሩ እጽፍላችኋለሁ፡፡

በርናባስ ማለት የስሙ ትርጉም ወልደ ፍስሐ የደስታ ልጅ ማለት ነው የተወለደው ቆጵሮስ በሚባል አገር ነው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከአረገ በኋላ ሀብት ንብረቱን በመሸጥ ለሐዋርያት ሰጥቶአቸዋል፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ ወደ ክርስትና ዓለም ሲጠራ ከሐዋርያት ጋር ያስተዋወቀው እርሱ ነው፡፡ ከቅዱስ ጳውሎስም ጋር በመሆን በልጥራን ያስተምሩ በነበረበት ወቅት አንድ ሕመምተኛ ፈወሱ፡፡ በዚህ ጊዜ የአካባቢው ነዋሪ አማልክት በሰው አምሳል ወደ እኛ ወረዱ ኑ መስዋእት እንሠዋላቸው ብለው ላም ይጎትቱ ጀመር፡፡ እነ ቅዱስ በርናባስም እኛ እንደ እናንተ የምንምት ሰዎች ነን ተው ብለው ከለከሏቸው የዚያ ሀገር ሰዎችም ስማቸውን ቀይረው ቅዱስ በርናባስን ድያ ጳውሎስን ሄርሜን ብለው ሰይመዋቸዋል፡፡

ቅዱስ በርናባስም እንዲህ ከሀገር ሀገር እየተዘዋወረ ሲያስተምር ኖሮ ሕዝበ ክርስቲያኑን ለመጎብኘት ቅዱስ ማርቆስን አስከትሎ ወደ ቆጵሮስ በመመለስ ማስተማር ጀመረ፡፡ ከቆጵሮስ በተጨማሪም ሶርያንና ዲልቅያን ጨምሮ ሲያስተምር አሕዛብ /የማያምኑ/ ጠልተው፤ ተመቅኝተው በድንጋይ በመውገር ነፍሱን ከሥጋው ከለዩ በኋላ ከእሳት ጣሉት፡፡ እሳቱ ግን ሥጋውን ሳያቃጥለው ቅዱስ ማርቆስ አንሥቶ ቀብሮታል፡፡

የነነዌ ጦም (ለሕፃናት)

ጥር 29/2004 ዓ.ም

በእኅተ ፍሬስብሐት

አንድ ቀን እግዚአብሔር ዮናስ ወደ ተባለ ሰው መጥቶ “ተነሥተህ ወደ ነነዌ ከተማ ሒድ፤  ሕዝቡ ኀጢአት ስለሠሩ ልቀጣቸው ነው፡፡ ነገር ግን አንተ ሔደህ ካስተማርካቸው እና እነሱም ከጥፋታቸው ከተመለሱ እምራቸዋለሁ፡፡” አለው ዮናስ ግን ወደ እነርሱ ሔዶ እግዚአብሔር የነገረውን ቢነግራቸው ይጎዱኛል ብሎ አሰበ፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔር ያዘዘውን መልእክት ላይናገር ወስኖ ተርሴስ ወደምትባል ሀገር ለመሸሽ ፈለገ፡፡  እግዚአብሔር እርሱን ፈልጎ እንደማያገኘውም አሰበ፡፡ ነገር ግን ማንም ከእግዚአብሔር መሸሽ አይችልም፡፡ ዮናስ ግን ይህን አላወቀም ነበር፡፡

ዮናስ በመርከቧ ላይ ሳለ ከባድ አውሎ ነፋስ ተነሣ፡፡ የመርከቧ ተሳፋሪዎች በሙሉ ተጨነቁ  መርከቧ ከተገለበጠች እንዳይሞቱ አሰቡና እግዚአብሔር እንዲረዳቸው ጸለዩ፡፡ ዮናስ ግን ከእግዚአብሔር ሸሽቶ መምጣቱን አሰበ እሱን ወደ ውኃው ቢወረውሩት አውሎ ንፋሱ እንደሚቆም ነገራቸው፡፡ ሰዎቹ በጣም አዘኑ ነገር ግን መርከቧ እንዳትሰምጥባቸው ዮናስን ወደ ባሕሩ ወረወሩት፡፡ ዮናስ በውኃው ውስጥ እንዲሞት ግን እግዚአብሔር አልተወውም፡፡ ዮናስን ሳይጎዳው እንዲውጠው ዓሣ አንበሪ ላከ፡፡ ከሦስት ቀን በኋላ ዓሣ አንበሪው እየዋኘ ወደ ባሕሩ ዳርቻ ወጥቶ ዮናስን ተፋው፡፡ ከተፋው በኋላ እግዚአብሔር ዮናስ ወደ ነነዌ ሔዶ እንዲያስተምራቸው በድጋሚ ነገረው፡፡ ዮናስም ወደ ነነዌ ሔደ እግዚአብሔር የነገረውን ነገራቸው፡፡ ሰዎቹም ሰሙት፡፡ በነነዌ የነገሠው ንጉሥ የዮናስን ትምህርት በሰማ ጊዜ ሕዝቡን ሁሉ ሰበሰበ፡፡ ሕፃን፣ ሽማግሌ ሳይሉ እንስሳትም ሳይቀሩ ለሦስት ቀን እንዲጦሙ እና እንዲጸልዩ አዘዘ፡፡ ሕዝቡም ሁሉም ሦስት ቀን ጦሙ ጸለዩ፡፡ እግዚአብሔርም ሕዝቡ በጥፋታቸው ስለተጸጸቱ እና ስለጦሙ ከጥፋት አዳናቸው፡፡

ከታሪኩ የምንረዳው፡-

  1. ጦም እና ጸሎት ሊደርስብን ከሚችለው መከራ እና ችግር እንደሚያድን
  2. እግዚአብሔር በሁሉም ቦታ እንዳለ እና በየትም ቦታ ብንሆን የምንሠራውን ሉ እንደሚመለከተን ያስረዳል፡፡

 

ቃና ዘገሊላ(ለሕፃናት)

ጥር 17/2004 ዓ.ም

በአቤል ገ/ኪዳን
አንድ ቀን በገሊላ አውራጃ ቃና በሚባል ቦታ የሚኖር አንድ ዶኪማስ የሚባል ሰው ሰርግ ደግሶ እመቤትችን ቅድስት ድንግል ማርያምን እና ሌሎች ብዙ ሰዎችን ጋበዘ፡፡ እመቤታችንም በግብዣው ላይ ከልጇ ከጌታችን ከመድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጋር፣ ከሐዋርያት ጋር ተገኘች፡፡
ምግቡና መጠጡ ቀረበ፡፡ ትንሽ ቆይቶ ግን የወይን ጠጁ አለቀ፡፡ በዚህ ጊዜ የሰርጉ አስተናጋጆች በጣም መጨነቅ ጀመሩ፡፡ ለእመቤታችንም የወይን ጠጅ ማለቁን  አማከሯት እመቤታችንም የሰርጉን ቤት አስተናጋጆች በተለይም ዶኪማስን ተጨንቆ ስታየው በጣም አዘነች፡፡ ለልጇ ለጌታችን ለመድኃኒታችን ለኢየሱስ ክርስቶስ የወይን ጠጁ እንዳለቀባቸውና አስተናጋጆቹ እንደተጨነቁ ነገረችው፡፡
ጌታም ባዶ የሆኑት የወይን ጋኖች ላይ ውኃ እንዲሞሉ አዘዛቸው፡፡ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምም ጌታችን የሚለውን እንዲያደርጉ ነገረቻቸው፡፡ አስተናጋጆቹም ጋኖቹ ላይ ውኃውን ሞሉ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ውኃውን ወደ ወይን ለወጠው፡፡ ዶኪማስም በጣም ደስ አለው፡፡ በሰርጉ ላይ የተጋበዙት እንግዶችም አዲሱን የወይን ጠጅ ሲጠጡ በጣዕሙ እጅግ ተደነቁ፡፡ ዶኪማስንም ጠርተው ሌሎች ሰዎች ጥሩውን መጠጥ አስቀድመው ይሰጡና በኋላ ደግሞ ብዙም የማይጥመውን ያቅርባሉ፡፡ አንተ ግን  የማይጥመውን አስቀድመህ አቅርበህ ጣፋጩን ወይን ከኋላ አመጣህ በማለት አሞገሱት፡፡
ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አምላክ መሆኑን ከሚያሳዩት ተአምራት አንዱን በዚያ ዕለት በሰርጉ ቤት አደረገ፡፡ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነትም በዚያን ዕለት ታወቀ፡፡ ይህ ተአምር የተፈጸመው በጥር 12 ቀን በመሆኑ ሁል ጊዜ ጥር 12 ቀን “የቃና ዘገሊላ” በዓል በመባል ይከበራል፡፡