ጸሎት በቤተ ክርስቲያን

ቀሲስ ዘክርስቶስ ፀጋዬ
ጥቅምት ፴ ቀን ፳፻፲፬ ዓ.ም

የተወዳዳችሁ የእግዚአብሔር ልጆች! እንደምን ሰነበታችሁ? እግዚአብሔር ይመስገን አላችሁ? መልካም፤ እግዚአብሔር አምላካችን የተመሰገነ ይሁን፡፡ በቤታችሁ ሆናችሁ ትምህርታችሁን በጥሞና ተከታተሉ!

ልጆች ባለፈው ትምህርታችን ላይ ጸሎት በቤታችን መጸለይ እንዳለብን አስተምረናችኋል፤ አሁን ደግሞ ጸሎት በቤተ ክርስቲያን ስንጸልይ ምን ማድረግ እንዳለብን እንመለከታለን፡፡
የሰው ልጆች ከእግዚአብሔር ጋር የሚገናኙበት መንገድ መካከል አንዱ ጸሎት ስለሆነ በየትኛውም ቦታ ሆነን የምንጸልየውን ጸሎት እግዚአብሔር አምላክ ይሰማል፤ ይሁን እንጂ የተመረጡ የተቀደሱ ቦታዎች አሉ፡፡ ይኸውም በቤታችን ውስጥ የተለየ የጸሎት ቦታ በማዘጋጀት መጸለይ እና በቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመገኘት ከካህናት አባቶች እና ከምእመናን ጋራ በኅብረት የሚጸለይባቸው ናቸው፡፡

ልጆች ጸሎት በቤተክርስቲያን በዘፈቀደ/ያለ ሥርዓት/ የሚከናወን ሳይሆን ራሱን የቻለ ሥርዓት ያለው ነው፡፡ ይህም ከመጸለያችን በፊት በቂ ዝግጅት ማድረግ ይጠበቅብናል፡፡ ማድረግ የሚገባንን ዝግጅት ለመረዳት ያስችለን ዘንድ በሁለት ወገን ከፍለን እንመለከተዋለን፡፡ ከእነዚህም አንዱ ውጫዊ /አፍአዊ ዝግጅት/ ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ ውስጣዊ ዝግጅት ነው፡፡

በዛሬው ትምህርታችን ውጫዊ /አፍአዊ ዝግጅቶች/ ውስጥ የሚጠቃለሉትና ማድረግ የሚገባንን እንመለከታለን፡፡

ሀ. መታጠብና አለባበስን ማስተካከል
ከመኝታ ተነስተን ወደ ጸሎት ከመሄዳችን በፊት እጅንና ፊትን መታጠብ ያስፈልጋል
ነጠላችንን መስቀለኛ ማጣፋት ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲኬድ ሴቶች ረዥም ልብስ መልበስ /ሴቶች / በጸሎት ጊዜ ጸጉርን መከናነብ ቀሚስ መልበስ ይገባል፡፡

ለ. መብራት ማብራት
‹‹መልካሙን ሥራችሁን አይተው፥ በሰማያት ያለውን አባታችሁን ያመሰግኑት ዘንድ እንዲሁ ብርሃናችሁ በሰው ፊት ይብራ›› እንደተባለው ጧፍ ወይም ሻማ አብርተን ስንጸልይ የሚበራውም መብራት የእግዚአብሔርና የቅዱሳኑን ብርሃንነት ያስታውሰናል፡፡ ቅዱሳን መላእክት/ጻድቃን ፣ሰማዕታት፣…/ በዙሪያችን እንዳሉም ያሳስበናል፡፡ (ማቴ. ፭፥፲፮)

ሐ. አቋቋም /ቀዊም/

ለጸሎትና ለምስጋና በምንቆምበት ጊዜ በቅዱሳን ሥዕላት ፊት በመቆም እንደ ሥዕሉ ባለቤት የሥላሴ /የእግዚአብሔር ወልድ ከሆነ የአምልኮት፣ የእመቤታችንና የቅዱሳን ከሆነ የጸጋ የአክብሮት ስግደት በመስገድና በመሳለም ለሥዕሉ ባለቤት ያለንን ፍቅር አንገልጥባቸዋለን፡፡
ዓምድ /ቋሚ/ ሳይደገፉ፣ መቋሚያ ሳይዙ በሁለት እግር ቀጥ ብሎ መቆም ይገባል፡፡ ‹‹በማለዳ በፊትህ እቆማለሁ›› በማለት ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ እንደገለጸው እግርን አጣምሮ መቆም አይገባም፡፡ ካልታመሙ ለመቆም የማያስችል ችግር ከሌለ ተቀምጦ/ ተኝቶ/ መጸለይ አይገባም፡፡ (መዝ. ፭፥፫)

ቅዱሳን ሥዕላት ከሌሉ ፊትን ወደ ምሥራቅ አድርጎ ወደ ግራና ቀኝ ሳያዩ መቆም እጆቻችንን ከሰውነታችን መስቀለኛ አድርጎ በመዘርጋት /መጸለይ ይገባል/፡፡ በቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ ‹‹በሌሊት በቤተ መቅደስ እጆቻችሁን አንሱ እግዚአብሔርንም አመስግኑ›› በማለት ተናግሯል፡፡ (መዝ.፻፴፫፥፪)

መ. ዓይንን ወደ ሰማይ ማንሳት
ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረን ዓይንን ገልጦ ወደ ሰማይ አቅንቶ መጸለይን ነው፡፡ ለዚህም አልዓዛርን ባስነሳው ጊዜ/ ዓይኑን ወደ ላይ በማቅናት ጸልዪል፤ እንደዚሁም አምስት እንጀራና ሁለቱን ዓሳ /ኅብስቱን/ አበርክቶ ሲያበላ ያደረገውን /ምሳሌ በማድረግ እኛም ዓይናችንን ወደ ሰማይ ወደ ቅዱሳት ስዕላት በማቅናት በመመልከት መጸለይ ይገባናል፡፡ (ዮሐ.፲፩፥፵፩፣ ፲፯፥፩)

መ. ማማተብ
ጸሎት ሲጀመርና ሲፈጸም አመልካችን ጣትን ከሌሎች ጣቶች ጋር አመሳቅሎ በትእምርተ መስቀል አምሳል ከላይ ወደ ታች ከግራ ወደ ቀኝ በማድረግ ሳይፈጥኑና እጅን ሳያወራጩ ረጋ ብሎ ማማተብ ይገባል፡፡
በጸሎት ላይ መስቀልን የሚያነሳ ቃል ስንጣራም ማማተብ ያስፈልጋል፡፡
ስናማትብ ‹‹በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፤ አአትብ ገጽየ ወኩለንታየ በትእምርተ መስቀል በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ ፊቴንና መላ ሰውነቴን አማትባለው በማለት በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን›› እያልን ነው፡፡ ስናማትብም የዲያብሎስ ሠራዊትን እናርቅበታለን የጠላትን ኃይል ድል እንነሳበታለን፡፡

ሠ. አስተብርኮ \ስግደት\
ለጸሎትና ለምስጋና በምንቆምበት ጊዜ በቅዱሳን ሥዕላት ፊት በመቆም እንደ ሥዕሉ ባለቤት የሥላሴ ከሆነ የአምልኮት፣ የእመቤታችንና የቅዱሳን ከሆነ የጸጋ የአክብሮት ስግደት በመስገድና በመሳለም ለሥዕሉ ባለቤት ያለንን ፍቅር አንገጥላቸዋለን፡፡
በጸሎት መጀመሪያና መጨረሻ ጉልበትን በማስተብረክ በመስገድ መጸለይ ይገባል፡፡ ስግደትን የሚያነሣ አንቀጽ ሲደርሱም ለእግዚአብሔር መስገድ ያስፈልጋል፡፡ በዕለተ ሰንበት (ቅዳሜ እና እሑድ)፣ በበዓለ ሃምሳ በበዓለ ወልድ በሀያ ዘጠኝ፣ በእመቤታችን በሀያ አንድ፣ በቅዱስ ሚካኤል በዐሥራ ሁለት፣ ሥጋና ደሙን ከተቀበሉ በኋላ በእነዚህ ቀናት ጉልበት ምድር አስነክቶ መስገድ አይገባል/ም/፡፡ የዚህም ምክንያት ዕለታቱ በዓል በመሆናቸው በአንደበታችን ማመስገንና መዘመር እንጂ በጉልበታችን ስግደት አይፈቀድም፤ ቁርባን ከጠቀበልን በኋላም የጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሥጋና ደም በውስጣችን ስለሚኖር በሰውነታችን ክቡር ስለሚሆን መሬት መንካት የለብንም፡፡

ሰ. ጸሎት አለማቋረጥ
ጸሎትን አቋርጦ ከማንም ሰው ጋር ፈጽሞ በቃልም ሆነ በምልክት መነጋገር አይገባም፡፡
ጸሎቱን የሚያቋርጥ ችግር ከገጠመን አባታችን ሆይ ብለን በማሳረግ ጸልየን ንግግራችንን ስንፈጽም ወደ ጸሎት ስንመለስ በድጋሚ አባታችን ሆይ ብለን ያቋረጥነውን መቀጠል ይኖርብናል፡፡

ጸሎት መጸለይ ከጀመርን ጀምሮ አንድ ቀን መተው በሌላ ቀን መጸለይ ሳይሆን ከጀመሩ አለማቋረጥ ተገቢ ነው፡፡

እንግዲህ ልጆች ጸሎት ንጹሕ ቅዱስ የሆነውን እግዚአብሔርን የምንነጋገርበት እንዲሁም አምላካችን እግዚአብሔር ያከበራቸውን ቅዱሳንን የምናናግርበት እንዲያማልዱን የምንማጸንበት መሆኑን አውቃችሁ በንጽሕናና በሥርዓት መጸለይ፣ ከመጸለያችሁ በፊትና በጸሎት ጊዜ መደረግ ያለበትን ዝግጅት በተማራችሁት መሠረት በሚገባ መፈጸም ይጠበቅባችኋል፡፡

ልጆች እስከ ዛሬ ጸሎት ያልጀመራችሁ ካላችሁ ጀምሩ፤ የጀመራችሁ ደግሞ ሳታቋርጡ አጠናክራችሁ ቀጥሉበት፡፡ ይህንን ስታደርጉ አምላካችን እግዚአብሔር ይወዳችኋል፡፡

በመጨረሻም በሚቀጥለው ትምህርት እስክንገናኝ መልካሙንና የተወደደውን ነገር ሁሉ እንመኝላችኋለን፤ ደኅና ሰንብቱ!