አሥሩ ትእዛዛት

  እመቤት ፈለገ
እግዚአብሔር አምላካችን እጅግ በጣም የሚወደን እና የሚያስብልን አባታችን ነው፡፡ እርሱ ደግሞ ሁሉንም የሚያውቅ ስለሆነ ለእኛ ምን እንደሚጠቅመን፤ምን እንደሚያስፈልገን፤ምን እንደሚጎዳን ሰለሚያውቅ አሥሩን ትእዛዛት ሰጠን፡፡

 እነዚህም፡-
          1.ከኔ በቀር ሌሎችን አማልክት አታምልክ
          2.የእግዚአብሔር አምላክህን ስም በከንቱ አትጥራ
          3.የሰንበትን ቀን አክብር
          4.አባትና እናትህን አክብር
          5.አትግደል
          6.አታመንዝር
          7.አትስረቅ
          8.በሐሰት አትመስክር
          9.የባልንጀራህን ቤት አትመኝ
         10.ባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ የሚሉት ናቸው፡፡

 

እነዚህ ትዕዛዞች ሁሉም ሰው እንዲያደርጋቸው ርህሩህ አባታችን እግዚአብሔር አዞናል፡፡ እነዚህ ትዕዛዞችን ከፈጸምን እግዚአብሔር ይወደናል፤በረከትም ይሰጠናል፡፡
ልጆች እግዚአብሄርን እንወደዋለን አይደል? እግዚአብሄርን መውደዳችን የሚታወቀው ደግሞ አድርጉ ያለንን ስናደርግ፤ አታድርጉ ያለንን ደግሞ የማናደርግ ከሆነ ነው፡፡ይህን ካደረግን እግዚአብሔር በእኛ ደስ ይለዋል፤ ይባርከናል፤የሚያስፈልገንን ሁሉ ይሰጠናል፡፡ እነዚህ ትዕዛዛት ካልፈጸምን  ግን እግዚአብሔር ያዝንብናል፤ ከደጉ አምላካችንም እንለያያለን፡፡ ከአምላካችን ከተለየን ደግሞ ጥሩ ነገር አይኖረንም፡፡ ስለዚህ ልጆች እነዚህን ትእዛዛት ልንፈጽማቸው ስለሚገባ እያንዳዳቸውን በዝርዝር በሌላ ቀን እናያቸዋለን፡፡

በሌላ ቀን አሥሩን ትዛዛት በዝርዝር እስከምናያቸው ድረስ እናንተ በቃላችሁ ይዛችሁ ለእማማ፤ ለአባባ እና ለጓደኞቻችሁ ንገሯቸው፡፡
                                                                                  

Silestu Dekik.jpg

ሠለስቱ ደቂቅ

በአዜብ ገብሩ
እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች?ደህና ናችሁ ልጆች? ዛሬ ስለ ሦስቱ ህጻናት ታሪክ እንነግራችኋለሁን በደንብ ተከታተሉን እሺ፡፡
 

በአንድ ወቅት በባቢሎን ከተማ የሚኖር ናቡከደነፆር የሚባል ንጉሥ ነበር፡፡ይህም ንጉሥ ከወርቅ የተሰራ ትልቅ ጣኦት አሠርቶ አቆመ፡፡ ሕዝቡንም ሁሉ ሰበሰበና ለጣኦቱ እንዲሰግዱ አዘዘ፡፡ ለጣኦት ያልሰገደ ግን በእሳት ውስጥ ይጣላል ብሎ አዋጅ አስነገረ፡፡

Silestu Dekik.jpg
 
ከሕዝቡም መካከል ሚሳቅ፤ሲድራቅ እና አብደናጎም የተባሉት ህፃናት ግን ለጣኦቱ አንሰግድም አሉ፡፡ምክንያቱም እግዚአብሔርን ስለሚወዱ ለእርሱ ስለሚገዙ ነው፡፡ንጉሡ እነዚህን ህጻናት ለጣኦቱ አንሰግድም በማለታቸው በጣም ተቆጣ፡፡ካልሰገዱም ወደ እሳት እንደሚጣሉ ነገራቸው፡፡ህጻናቱም የሚያመልኩት አምላክ በሰማይ እንዳለና እርሱም ከእሳቱ እንደሚያድናቸው ነገሩት፡፡እንዲህም ሲሉ ወደ እግዚአብሔር ጸለዩ ‹‹አንተ ከእኛ ጋር ነህና ክፉውን አንፈራም››። ንጉሡም በመለሱለት መልስ ይበልጥ ተቆጣ፡፡ እሳቱንም ይነድ ከነበርው ሰባት እጥፍ እንዲያነዱትና ወደ እሳቱ ውስጥ እንዲጥሏቸው አዘዘ፡፡
ሲድራቅ ሚሳቅና አብደናጎም ግን እሳቱ አላቃጠላቸውም ነበር፡፡ በእሳት ውስጥ ሆነው እግዚአሔርን በመዝሙር እያመሰግኑ ነበር፡፡ከእነርሱም ጋር ሌላ አራተኛ ሰው ይታይ ነበር፡፡ እርሱም ከእሳቱ ሊያድናቸው  ከእግዚአብሔር ዘንድ የተላከው መልአክ  ቅዱስ ገብርኤል ነበር፡፡ በእሳቱ ውስጥ ሆነው መዝሙር ሲዘምሩ ንጉሡ በጣም ተገረመ ከእሳቱ እንዲያወጧቸው አዘዘ። ከፀጉራቸው አንዲቷ እንኳን ሳትቃጠል በሰላም ከእሳቱ ወጡ፡፡ንጉሡም ባየው ተዓምር ተደንቆ የእነርሱን አምላክ አመለከ በፊታቸውም ለእግዚአብሔር ሰገደ።
አያችሁ ልጆች እነዚህ ሦስቱ ህጻናት  ጎበዞች ናቸው፤ አምላካቸው እንደሚያድናቸው በሁሉም ቦታ ቢሄዱ ከእነርሱ ጋር እንደሆነ ስለሚያምኑ እሳቱን አልፈሩም፡፡እግዚአባሔርም ስለእምነታቸው እሳቱን አቀዘቀዘው፡፡በሰላም ከእሳቱም አወጣቸው፡፡

ክፉ ለሚያደርጉባችሁ ሰዎች መልካምን አድርጉ::

በአዜብ ገብሩ

በአንድ ወቅት ሳኦል የሚባል የእስራኤላውያን ንጉሥ ነበር፡፡ ይህ ንጉስ በዳዊት ላይ እጅግ ይቀናበት ነበር፡፡ ምክንያቱም ዳዊት ፍልስጤማዊው ጎልያድን ስላሸነፈ እስራኤላውያን በጣም ወደውት ነበር፡፡ ታዋቂም ሆኖ ነበር፡፡ ሳኦልም እግዚአብሔር እርሱን ትቶ ከዳዊት ጋር እንደሆነ ማሰብ ጀመረ፡፡ ስለዚህ በተለያየ ጊዜ ዳዊትን ለመግደል ሙከራ ያደርግ ነበር፡፡

 

አንድ ጊዜ ሳኦል የጦር ሰራዊቱን አስከትሎ ዳዊትን ለመግደል ፍለጋ ጀመረ ሳኦል ሳያውቅ ዳዊት ከሰራዊቶቹ ጋር የሚተኛበትና የሚሸሸግበት ዋሻ ስር ተኛ፡፡ ዳዊት ግን በዋሻው ውስጥ ተደብቆ ነበር፡፡ ሳኦልንም አየው፤ ልጆች እናንተ ዳዊትን ብትሆኑ ምን ታደርጉ ነበር? ዳዊት ግን ሳኦልን ሳይገድለው በተኛበት የልብሱን ጫፍ ቆርጦ ወሰደ፡፡ ሳኦልም ከእንቅልፉ ሲነቃ በተኛበት ጊዜ የተፈጠረውን ነገር ምንም አላወቀም፡፡ ዳዊትም ከኋላው ልብሱን እንደቆረጠበት ነገረው፡፡ ሳኦልም አለቀሰ፤ እጅግም አዘነ፡፡ ምክንያቱም ዳዊት እርሱን መግደል ሲችል ስላልገደለው ነው፡፡ ለዳዊትም እንዲህ አለው ‹‹ከእኔ ይልቅ አንተ ፃድቅ ነህ፤ እኔ ክፉ ሳደርግብህ አንተ ግን ክፉ አላደረግህብኝም፤ ስለዚህ ለእኔ ስላደረግኸው ቸርነት እግዚአብሔር መልካሙን ይመልስልህ’’ አለው:: ከዚህም በኋላ ሳኦልና ዳዊት ይቅር ተባባሉ፡፡

አያችሁ ልጆች እኛም ልክ እንደ ዳዊት የእግዚአብሔር ልጆች ስለሆንን ሁሉንም ሰው መውደድ አለብን፡፡ ክፉ ያደረጉብንን፣ የማይወዱንንና ሊጎዱን ያሰቡ ሰዎች ይቅር ማለት አለብን አንድ ሰው ክፉ ሲያደርግብንም እኛ ግን ያንን ሰው ይቅር ልንለውና ልንወደው ይገባል፡፡ የእግዚአብሔር ልጆች ከሆንን ሰዎችን የምንወድና ለሰዎች የምንራራ መሆን አለብን፡፡

ለቅዱስ ቁርባን ስለ መዘጋጀት

                                                                                   በአዜብ ገብሩ
ልጆች ዛሬ ቅዳሴ ስናስቀድስ ወደ ቤተክርስቲያን ስንመጣ ምን ማድረግ እንዳለብን እነግራችኋለሁ፡፡
በቤተክርስቲያን ጸሎት እናደርጋለን፣ እንቆርባለን፣ ትምህርት እንማራለን፡ስናስቀድስ ከእግዚአብሔር፣ከመላእክት እና ከቅዱሳን ጋር ሰለምንገናኝ ማስቀደስ በጣም ደስ ይላል፡፡

ልጆች ልንቆርብ ስንል ምን ማድረግ እንዳለብን ታውቃላችሁ? የሠራነው ኃጢአት ካለ ለእግዚአብሔር እና ለንስሐ አባታችን መናገር አለብን፡፡ የተጣላነው ሰው ካለ ይቅርታ መጠየቅ፣ ውሸት አለመዋሸት አለብን፡፡ ሌላው ልጆች ገላችንን መታጠብና ንጹሕ የሆነ ልብስ መልበስ አለብን፡፡

ምክንያቱም ከሁሉም በላይ የሆነውን የአምላክ ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም ልንቀበል ስለሆነ ነው፡፡ ንጹሕ የሆነውን ልብሳችሁን ከለበሳችሁ በኋላ ቅዳሴ ከመጀመሩ በፊት በቤተክርስቲያን መገኘት አለባችሁ፡፡ ይህንንም ለወላጆቻችሁ ነግራችሁ በጊዜ ይዘዋችሁ እንዲመጡ አድርጉ፡፡ በቅዳሴ ጊዜም እግዚአብሔር የማይወደውን ወሬ ማውራት ስለማይፈቀድ ይህን ማድረግ የለባችሁም ዝም ብላችሁ ቅዳሴውን መከታተል አለባችሁ፡፡ ከጎናችሁ የቆሙ ሕፃናትም ሲያወሩ ካያችሁ ክቡር በሆነው በእግዚአብሔር ቤት እንዳሉ ልትነግሯቸው ይገባል፡፡

የቅዳሴ ሥርዓት እና ምንባብ ያለበት መጽሐፍ ይዛችሁ ጸሎቱን በደንብ መከታተል አለባችሁ፡፡ልትቆርቡም ስትሉ ከጎናችሁ ካለው ልጅ ጋር መጋፋት መሰዳደብና መጣላት አይገባም፤ ተራችሁን በትህትና ቆማችሁ መጠበቅ አለባችሁ፡፡ ከቆረባችሁ በኋላ የቅዳሴ ጸበል ጠጡ፡፡ ቆሻሻ የሆነ ነገር ወደ አፋችሁ እንዳይገባ፣ከአፋችሁ እና ከአፍንጫችሁም ምንም ዓይነት ነገር እንዳይወጣ አፋችሁን በነጠላችሁ ሸፍኑ፡፡ ቅዳሴው አልቆ ዲያቆኑ በሰላም ወደየቤታችሁ ግቡ ብሎ እስኪያሰናብት ድረስ በቤተክርስቲያን ቆዩ፤ቅዳሴው ሲጠናቀቅም እግዚአብሔርን አመስግናችሁ በመንገድ እንቅፋት እንዳይመታችሁ እየተጠነቀቃችሁ ከወላጆቻችሁ ጋር ወደየቤታችሁ ሂዱ፡፡

እኛ ቤተ ክርስቲያን ሄደን ስንቆርብ ጌታችንም ከእኛ ጋር ወደ ቤታችን ይመጣል፤በዚህም ምክንያት ቤታችን ይገባል፤ቤታችንንም ይባርክልናል፡፡

ስለ እመቤታችን ቤተመቅደስ መግባት

እህተ ፍሬስብሃት

 

ኢያቄምና ሐና የሚባሉ በተቀደሰ ትዳር የሚኖሩ የእግዚአብሔር ሰዎች ነበሩ፡፡ ሁለቱም እግዚአብሔርን የሚወዱ ደግ ሰዎች ነበሩ፡፡ ነገር ግን ሐና ልጅ መውለድ አትችልም ነበር፡፡ ልጅም ስለሌላቸው በጣም አዝነው ይኖሩ ነበር፡፡ ሁልጊዜ ወደ ቤተ እግዚአብሔር እየሄዱ ልጅ እንዲሰጣቸው ልመና ያቀርቡ ነበር፡፡ ለእግዚአብሔርም ልጅ ከሰጠኸን ለአንተ ብጽአት (ስጦታ) አድርገን እንሰጣለን ብለው ተሳሉ፡፡

 

እግዚአብሔርም ልጅ ሰጣቸው፡፡ ሐናም በግንቦት አንድ ቀን ከፀሐይ የምታበራ ሴት ልጅ ወለደች፡፡ ሕፃኗንም ማርያም ብለው ስም አወጡላት፡፡ ልጃቸው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በንጽህና ሲያሳድጉ 3 ዓመት ከሆናት በኋላ በተሳሉት ስእለት መሠረት ወደ ቤተ እግዚአብሔር መውሰድ እንዳለባቸው ተነጋገሩ፡፡ ለመንገድ የሚሆን ስንቅና ለቤተ እግዚአብሔር የሚሆን ስጦታ ሁሉ አዘጋጁ፡፡ 
 

ከዚያም ልጃቸውን ድንግል ማርያምን ይዘው ወደ ቤተመቅደስ ሄዱ፡፡በቤተ መቅደስ የካህናት አለቃ የነበረው ካህኑ ዘካርያስ ተቀበላቸው፡፡ሐና እና ኢያቄም ለእግዚአብሔር የገቡትን ቃል የተደረገላቸውንም ድንቅ ተአምር ነገሩት፡፡
 
ካህኑ ዘካርያስም ለእግዚአብሔር የገቡትን ቃል ባለመርሳታቸው እጅግ ተደሰተ፡፡ ነገር ግን ወዲያው አንድ ነገር አሳሰበው፡፡ምን መሰላችሁ ልጆች እመቤታችንን በዚያ በቤተመቅደስ ስትኖር ማን ይመግባታል ብሎ ነበር የተጨነቀው፡፡ 
 
ወዲያው ከሰማይ ቅዱስ ፋኑኤለ የተባለው መልአክ መጣ መልአኩ እመቤታችን አቅፎ በአንድ ክንፉ ከልሎአት ከሰማይ ያመጣውን ኅብስት እና መጠጥ መግቦአት እንደመጣው ሁሉ ወደ ሰማይ አረገ፡፡ካህኑ ዘካርያስና ህዝቡም እግዚአብሔር ምግቧን እና መጠጧን እንዳዘጋጀላት ተመለከቱ፡፡ካህኑ ዘካርያስ በፍፁም ደስታ እመቤታችንን ተቀብሎ ወደ ቤተ መቅደስ አሥገባት ይህ ዕለት ታኅሳስ 3 ቀን ሲሆን በዓታ ለማርያም ተብሎ በታላቅ ድምቀት ይከበራል፡፡

 

ልጆች እኛም በዓሉን በማክበር ከእመቤታችን በረከትን ማግኘት አለብን፡፡

ታቦት

እህተ ፍሬስብሐት

 ልጆች ታቦት ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ?

ልጆች ታቦት ማለት የእግዚአብሔር ትዕዛዝ የተፃፈበት ቅዱስ ሰሌዳ ማለት ነው፡፡ በመጀመሪያ ታቦትን ከእግዚአብሔር እጅ የተቀበለው ሙሴ ነበር።

እስራኤላውያን በግብፅ በስደት ከኖሩ በኋላ በሙሴ መሪነት ወደ ሀገራቸው ወደ እስራኤል ጉዞ ጀመሩ፡፡ ብዙ ቀናቶችን ከተጓዙ በኋላ እረፍት አድርገው እግዚአብሔር ሙሴን ሲና  ወደተባለው ተራራ እንዲወጣ አዘው፡፡ ሙሴም ወንድሙ አሮን ህዝቡን እንዲጠብቅ አድርጎ ወደ ተራራው ወጣ፡፡ በተራራውም ላይ 40 ቀንና 40 ሌሊት ከፆመ በኋላ ከእግዚአብሔር እጅ ሁለቱን ታቦቶች ተቀበለ፡፡ በታቦቱ ላይም አስር የእግዚአብሔር ትዕዛዞች ተፅፈውበታል፡፡ እግዚአብሔር ታቦትን የሰጠበት ምክንያት ሌሎች ህዝቦች ጣኦትን ያመልኩ ስለነበር እስራኤላውያን ግን እግዚአብሔርን ስለሚያምኑ ሌሎች ህዝቦችን አይተው ጣኦት እንዳያመልኩ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበትን ታቦት እንዲያመልኩ ታቦትን ለሙሴ ሰጠው፡፡

ሙሴ ከሲና ተራራ ታቦታቱን ይዞ እስከሚመለስ እስራኤላውያኑ 40 ቀን መታገስ አቅቷቸው አሮንን አስገድደው ጣዖት ሠርተው ሲሰግዱ አገኛቸው። በዚህ ጊዜ ሙሴ ህዝቡ እግዚአብሔርን ትተው ጣኦትን በማምለካቸው በጣም ስለተናደደ ታቦቶቹን በጣኦቱ ላይ ጣላቸው እና ታቦቱም ጣኦቱም ተሰባበሩ፡፡ ሙሴ ታቦቶች በመሰባበራቸው በጣም አዘነ፡፡ እግዚአብሔርም የሙሴን ማዘን ተመልክቶ “የሰበርካቸውን አስመስለህ አንተ ራስህ ስራ እኔም እባርክልሃሁ” አለው፡፡ ሙሴም እንደታዘዘው ቅርፁን ከሰራ በኋላ እግዚአብሔርም እንደገና አስሩ ትዕዛዞችን በጣቶቹ ፃፈበት እና ባረከለት፡፡

ልጆች በሌላ ቀን ደግሞ የእግዚአብሔር አስሩ ትዕዛዞች ምን እንደሆነ እንነግራቹሀለን፡፡

አሥራ ሦስቱ ሕማማተ መስቀል

በሰሙነ ሕማማት ጠቅለል ባለ መልኩ የምናስባቸው የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ሕማማት አሥራ ሦስት ናቸው፡፡ እነርሱም አሥራ ሦስቱ ሕማማተ መስቀል ይባላሉ፡፡ ለክርስቲያኖች እነዚህን ሕማማተ መስቀል ማወቅና ዘወትር ማሰብ ተገቢ በመሆኑ እንደሚከተለው ቀርበዋል፡፡

1.     ተኰርዖተ ርእስ (ራስና በዘንግ መመታት)

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱን በዘንግ መመታቱንና መቀጥቀጡን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ተኰርዖት›› የሚለው ቃል ኩርዐ – መታ ከሚለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ ርእስ ደግሞ ራስ ማለት ነው፡፡ አገረ ገዥው ጲላጦስ ‹‹እኔ ከዚህ ጻድቅ ሰው ደም ንጹሕ ነኝ›› ብሎ እጁን ከታጠበ በኋላ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ገርፎ ለካህናት አለቆችና ለሽማግሎች አሳልፎ ሰጥቶት ነበር፡፡ በአይሁድ ሕግ የተገረፈ አይሰቀልም፤ የሚሰቀል ደግሞ አይገረፍም፡፡ እርሱ ጲላጦስ ግን ከገረፈው በኋላ፣ የበደል በደል፣ እንዲሰቅሉት አሳልፎ ሰጣቸው (ማቴ 27-24፤ ማር 15-15፤ ሉቃ 23-25፤ ዮሐ 18-39)፡፡
 
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተላልፎ ከተሰጠ በኋላ የእሾህ አክሊል ጐንጉነው ራሱ ላይ ደፍተውበታል፡፡ ራሱንም በዘንግ መትተውታል (ማር 15-19)፡፡ የሰው ዘር ከአዳም ጀምሮ በጠላቱ በዲያብሎስ በተጐነጐነ የኃጢአት እሾህ ራሱ ተይዞ ነበርና ይህንኑ ለማስወገድ ከሰማይ የወረደ ሰማያዊ የሆነ ዳግማዊ አዳም ክርስቶስ በጠላቶቹ በአይሁድ ተንኮል የተጐነጐነ አክሊለ ሦክ እንደ ዘውድ ደፋ፡፡ በሲኦል ወድቆ በዲያብሎስ ተረግጦ ራሱ የሚቀጠቀጠውን የሰውን ልጅ ለማዳን መድኃኔዓለም ክርስቶስ ራሱን በመቃ ተቀጠቀጠ፡፡ ከራሱ ላይ በሚወርደው ደም ፊቱ ተሸፈነ፡፡
 
2.     ተፀፍዖ መልታሕት (በጥፊ መመታት)

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ እጃቸው በደም፣ ጣቶቻቸው በበደል በረከሰ በአይሁድ እጅ በጥፊ መመታቱን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ተፀፍዖ›› የሚለው ቃል ፀፍዐ በጥፊ መታ ከሚለው የግእዝ ግሥ የወጣ ነው፡፡ መልታሕት ደግሞ ፊት ጉንጭ ማለት ነው፡፡
 
ጌታችን ለሊቀ ካህናት ቀያፋ እውነትን መናገር እንደ ስድብ ተቆጥሮበት መላልሰው ፊቱን በጥፊ መትተውታል፡፡ ፊቱንም በጨርቅ ሸፍነው ‹‹ክርስቶስ ሆይ በጥፊ የመታህ ማነው? ትንቢት ተናገርልን›› እያሉ ዘብተውበታል፡፡ በጠላት ዲያብሎስ እጅ ወድቆ በነፍሱ ይቀለድበትና ይንገላታ የነበረውን የሰውን ልጅ ለማዳን ብሎ በጠላቶቹ በአይሁድ እጅ ወድቆ ተጐሰመ፤ ተንገላታ፤ በጥፊም ተመታ (ማቴ 27-27)፡፡ ጲላጦስ አሳልፎ ከሰጠው በኋላም አክሊለ ሦክ በራሱ ላይ አኑረው ቀይ ልብስ አልብሰው ‹‹የአይሁድ ንጉሥ ሆይ፣ ሰላም ለአንተ ይሁን›› እያሉ እየተሳለቁበት በጥፊ መትተውታል (ዮሐ 19-2-4)፡፡ አላወቁትም እንጂ እርሱ በመንግሥቱ ሽረት፣ በባሕርዩ ሞት የሌለበት የዘለዓለም አምላክ ነው፡፡
 
3.     ወሪቀ ምራቅ (ምራቅ መተፋት)

ርኩሳን አይሁድ በብርሃናዊው የክርስቶስ ፊት ላይ በሚያስጸይፍ ሁኔታ ምራቃቸውን እንደተፉበት የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ወሪቅ›› የሚለው ቃል ወረቀ ካለው ግእዛዊ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ ትርጉሙም እንትፍ አለ፣ (ተፋ) ማለት ነው፡፡ በነቢዩ በኢሳይያስ መጽሐፍ (ምዕራፍ 5ዐ-6) ‹‹ፊቴንም ከውርደትና ከትፋት አልመለስኩም›› ተብሎ እንደተነገረ እየዘበቱበት ምራቃቸውን ተፉበት (ማቴ 27-29-3ዐ፤ ማር 15-19)፡፡ በኃጢአት የቆሸሸውን የሰውን ሕይወት ለማጥራት የመጣው ንጹሐ ባሕርይ አምላክ ተተፋበት፡፡ በሥራው ከገነት ተተፍቶ፤ ተንቆ፤ ተዋርዶ የነበረውን የሰውን ልጅ ለማዳን ኃጢአትን ይቅር የሚል እርሱ ጌታችን ያለ ኃጢአቱ ተተፋበት፤ ተናቀ፤ ተዋረደ፡፡ እንኳን በአምላክ ፊት በሰው ፊት እንኳን መትፋት እጅግ ያስነውራል፡፡ እርሱ ግን የኃጢአታችንን ነውር ከእኛ ሊያጠፋ ነውር የሆነውን ምራቅ ተቀበለ፡፡
 
4.     ሰትየ ሐሞት (መራራ ሐሞት መጠጣት)

ጌታችንና አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመልዕልተ መስቀል ሳለ ተጠማሁ ባለ ጊዜ መራራ ሐሞት መጠጣቱን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ሰተየ›› ማለት ጠጣ ማለት ነው፡፡ ሐሞት የሚለውም አሞት ተብሎ በቁሙ ይተረጐማል፡፡ በመዝሙር 68 ቁጥር 21 ላይ ‹‹ለመብሌ ሐሞት ሰጡኝ፣ ለጥማቴም ሆምጣጤ አጠጡኝ›› ብሎ ነቢዩ ዳዊትን ትንቢት ያናገረ የነቢያት አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ የመጽሐፉ ቃል ይፈጸም ዘንድ ‹‹ተጠማሁ›› ባለ ጊዜ ሆምጣጤ ተሞልቶበት ተቀምጦ ከነበረው ዕቃ ሆምጣጤውን በሰፍነግ ሞልተው ወደ አፉ አቀረቡለት፡፡ ውኃ አጠጡኝ ቢላቸው በሐሞት የተደባለቀ የወይን ጠጅ ሊጠጣ አቀረቡለት፡፡ ቀምሶም ሊጠጣው አልወደደም (ማቴ 27-34)፡፡ ጌታችንም ሆምጣጤውን ከተቀበለ በኋላ ‹‹ተፈጸመ›› አለ፡፡ ራሱንም አዘንብሎ ነፍሱን አሳልፎ ሰጠ (ማቴ 27-48፤ ማር 15-36፤ ሉቃ 23-36፤ ዮሐ 19-29)፡፡
 
ቢጠጡት ለዘለዓለም የማያስጠማ ውኃ የሚሰጥ አምላክ፤ የተጠማችውን ነፍስ የሚያረካ ጌታ፤ ለዘለዓለም የሚፈልቅ የሕይወት ውኃ ምንጭ የሚያድል ፈጣሪ በተጠማ ጊዜ የፈጠረውን ውኃ እንኳን የሚያጠጣው የሚያቀምሰውም አላገኘም (ኢሳ 55-1)፡፡ አርባ ዓመት ሙሉ በቃዴስ በረሃ ኳትነው ለነበሩ አባቶቻቸው ከሰማይ መና አውርዶ የመገባቸው፤ ከአለት ላይ ውኃ አመንጭቶ ያጠጣቸው ክርስቶስ በተጠማ ጊዜ ቀዝቃዛ ውኃ ነፈጉት (ዘዳ 16-1-2ዐ፤ 1ቆሮ 1ዐ-3)፡፡ የዝናማት፤ የባሕርና የውቅያኖስ ጌታ በውኃ ጥም ተቃጠለ፡፡
 
መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሲኦል በረሃ ወድቀው በሕይወት ውሃ ጥም የተቃጠሉትን ነፍሳት ለማርካት ሲል እርሱ ተጠማ፡፡ በኃጢአት ወድቀው፣ በበደል ረክሰው፣ በነፍሳቸው ተጐሳቁለው፣ መራራ መከራን የሚቀበሉትንና ምረረ ገሃነም አፉን ከፍቶ ሆዱን አስፍቶ የሚጠብቃቸውን ሁሉ ለማዳን መራራ ሐሞትን ቀመሰ፤ ሆምጣጣውንም ጠጣ፡፡ የመረረውን የሰው ልጆችን ሕይወት ለማጣፈጥ የመረረውን መጠጥ ተቀበለ፡፡

5.     ተቀሥፎ ዘባን (ጀርባን መገረፍ)

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጀርባው እስኪላጥ ያለ ርኅራኄ የመገረፉን ነገር የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ተቀሥፎ›› የሚለው ቃል ቀሠፈ- ገረፈ ካለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ ‹‹ዘባን›› ደግሞ ጫንቃ፣ ትከሻ፣ ጀርባ ማለት ነው፡፡ ከላይ እንደተገለጠው የተገረፈ አይሰቀልም፡፡ የሚሰቀል ደግሞ አይገረፍም ነበር፡፡ ጲላጣስ ግን ኢየሱስ ክርስቶስን አስገረፈው፡፡ ከደሙ ንጹሕ ነኝ ብሎ ከታጠበ በኋላ ክርስቶስን ያለ ኃጢአቱ በመግረፍ ለአይሁድም አሳልፎ በመስጠት ‹‹ታጥቦ ጭቃ›› እንዲሉ የታጠበ እጁን መልሶ አቆሸሸው (ማቴ 27-28፤ ማር 15-15፤ ዮሐ19-1)፡፡
 
መድኃኒታችን መንፀፈ ደይን ወድቆ በእግረ አጋንንት ተጠቅጥቆ በእሳት አለንጋ የሚገረፈውን የሰው ልጅ ለማዳን ሲል ጀርባውን ለግርፋት ሰጠ፡፡ ሥጋው አልቆ አጥንቱ እስኪቆጠር ተገረፈ፡፡ አይሁድ አገረ ገዥያቸው ጲላጣስ ላቀረበላቸው ምርጫ ይፈታላቸው ዘንድ ነፍሳትን ከሲኦል የሚያወጣውን ክርስቶስን ሳይሆን ራሱን እንኳን ከምድራዊ ወህኒ ማውጣት ያልቻለውን ወንበዴውን በርባንን መረጡ፡፡ መገረፍ ይገባው የነበረ በርባን ተለቀቀ፡፡ በነቢዩ በኢሳይያስ ‹‹ጀርባዬን ለገራፊዎች፣ ጉንጬንም ለጠጉር ነጪዎች ሰጠሁ›› (በኢሳ 5ዐ-6) ተብሎ እንደተነገረ ጀርባውን ለገራፊዎች አሳልፎ ሰጠ፤ ጽሕሙንም ተነጨ፡፡ ይህ ሁሉ የሆነው የሰው ልጅ ከሚያድነው አምላክ ይልቅ የሚገርፈውንና የሚዘርፈውን ወንበዴ መርጦ ስለተገኘ ነው፡፡
 
6.     ተዐርቆተ ልብስ (ከልብስ መራቆት)

አምላካችን ኢየሱስ ክርስስቶስ ልብሱን መራቆቱን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ተዐርቆተ›› ማለት ታረዘ፤ ተራቆተ ማለት ነው፡፡ ፀሐይና ከዋክብትን ብርሃን አልብሶ የፈጠረ አምላክ ተራቆተ፡፡ ጸጋውን ለዕሩቃን የሚያለብስ አምላክ ልብሱን ተገፍፎ ዕራቁቱን ቆመ፡፡ ጨለማን ለብሶ ጨለማን ተንተርሶ ይኖር የነበረውን ሰው መልሶ ብርሃን ያለብሰው ዘንድ የብርሃናት ጌታ፣ የጸጋ ሁሉ አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ተገፈፈ፤ ተራቆተ፡፡
 
የሲኦል ወታደሮች የሆኑት አጋንንት የሰውን ልጅ ጸጋ ገፍፈውት ነበርና ጲላጦስ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አሳልፎ በሰጣቸው ሰዓት ወታደሮች ልብሱን ገፍፈውታል (ማቴ 27-27)፡፡ የሰው ልጅ ለቀረበለት ምርጫ የሰው ምላሽ ዘራፊው፤ ገራፊው ወንበዴ በርባን እንዲፈታለት ነበር፡፡ ‹‹አቅረብኩ ለከ እሳተ ወማየ፣ ደይ እዴከ ኅበ ዘፈቀድከ! እነሆ እሳትና ውኃን አቅርቤልሃለሁ፣ እጅህን ወደ ፈቀድከው ስደድ›› ሲባል የሰው ልጅ እጁን ወደ እሳት ሰደደ፡፡
 
7.     ርግዘተ ገቦ (ጎንን መወጋት)

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነፍሱን ለሞት አሳልፎ ከሰጠ በኋላ ጎኑን በስለታም ጦር መወጋቱን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ርግዘት›› የሚለው ቃል ረገዘ- ወጋ ከተሰኘ የግእዝ ግሥ የወጣ ነው፡፡ ገቦ ማለት ደግሞ ጎን ማለት ነው፡፡ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ አጠገብ፣ በግራና በቀኙ ሁለት ወንበዴዎች ተሰቅለው ነበር፡፡ ሥጋቸው በሰንበት በመስቀል ላይ እንዳይኖር ጭናቸው ተሰብሮ እንዲወርዱ አይሁድ ጲላጦስን በለመኑት መሠረት ጭፍሮቹ የሁለቱን ወንበዴዎች ጭን ጭናቸውን ከሰበሩ በኋላ ወደ ጌታችን ወደ ኢየሱስ ሲመጡ ፈጽሞ እንደሞተ አይተው ጭኑን አልሰበሩም፡፡ ነገር ግን ከጭፍሮቹ አንዱ ጎኑን በጦር ስለወጋው ወዲያው ከጎኑ ደምና ውኃ ፈሰሰ (ዮሐ 19-33)፡፡
 
አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሞትን ድል ያደርገው ዘንድ ሞተ፤ የሰው ልጅ በዘለዓለማዊ ሞት ተይዞ ነበርና፡፡ ትልቁ ሞት በኃጢአት ምክንያት ከእግዚአብሔር መለየት ነው፡፡ በጌታችን ሞት ግን ሞት ራሱ ድል ተነሣ፡፡ የሞት መውጊያ በሆነ ኃጢአት የሞተውን ሰው ለማዳን ጎኑን በጦር ተወጋ፡፡ በሰው ልቡና ተተክሎ የነበረውን ኃጢአት ከነሥሩ ነቅሎ ስለጣለው ‹‹ሞት ሆይ መውጊያህ የት አለ?›› ተባለ፡፡ የሞት መውጊያው ኃጢአት ነበርና (1ቆሮ 15-54-55፤ ኢሳ 25-8፤ ሆሴ 13-14)፡፡
 
ከተወጋው የጌታችን ጎን ደምና ውኃ መፍሰሱም የእግዚአብሔርን ልጅነትና የዘለዓለምን ሕይወት አጥቶ የነበረው ሰው ልጅነቱና ሕይወቱ እንደተመለሰለት የሚያረጋግጥ ነው፡፡ ምክንያቱም ከጎኑ በፈሰሰው ውኃ ተጠምቆ ልጅነትን፣ ደሙንም ጠጥቶ የዘለዓለም ሕይወትን ያገኛልና (ዮሐ 3-5፤ ዮሐ 6-54)፡፡
 
8.     ተአሥሮተ ድኅሪት (ወደ ኋላ መታሠር)

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሁለት እጆቹን ወደኋላ የፊጥኝ መታሠሩን የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ተአሥሮት›› የሚለው ቃል አሠረ (ሲነበብ ይላላል) ከሚለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ሲሆን ትርጉሙም አሠረ ማለት ነው፡፡ ‹‹ድኅሪት›› የሚለው ቃል ደግሞ ተድኅረ- ወደኋላ አለ ከሚለው ግሥ የወጣ ነው፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጊዜው በደረሰ ሰዓት ራሱን ለአይሁድ አሳልፎ በሰጠባት በዚያች ዕለትና ሰዓት ሻለቃውና ጭፍሮቹ የአይሁድም ሎሌዎች እጁን የኋሊት አሥረው መሬት ለመሬት ጎትተውታል፡፡ አፍገምግመውታል (ዮሐ 18-12)፡፡
 
በኃጢአት ሰንሰለት የኋሊት ታሥሮ ጠላት ዲያብሎስ የሚያፍገመግመውን የሰው ልጅ ለማዳን፣ ሰውንም ከኃጢአት እሥራት ይፈታ ዘንድ ሲል መድኃኔዓለም ክርስቶስ በጠላቶቹ በአይሁድ እጅ የኋሊት ታሠረ፡፡
 
9.     አምሥቱ ቅንዋተ መስቀል

መድኃኒታችን በመስቀል ላይ የተቸነከረባቸውን ጠንካራ የብረት ችንካሮች (ምስማሮች) የሚገልጥ ነው፡፡ ‹‹ቅንዋት›› የሚለው ቃል ቀነወ- ቸነከረ ከሚለው የግእዝ ግሥ የተገኘ ነው፡፡ መስቀል ማለት ደግሞ ዝም ብሎ የቆመ ግንድ ሳይሆን አሁን በየሥፍራው እንደምናየው ምልክት የተመሳቀለ እንጨት ነው፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተቸነከረባቸው አምስቱ ችንካሮች ሳዶር፣ አላዶር፣ ዳናት፣ አዴራ፤ ሮዳስ ይባላሉ፡፡ እነዚህም የአምሥቱ አዕማደ ምሥጢራት ምሳሌዎች መሆናቸውን አበው ያስተምራሉ፡፡
 
ሐዋርያው ቶማስ ከትንሣኤ በኋላ ወንድሞቹ ሐዋርያት ስለ ትንሣኤው በነገሩት ጊዜ ‹‹የችንካሩን ምልክት በዓይኖቼ ካላየእንኳን ብንሆን እግዚአብሔር ከኛ ጋር ከሆነ ማንም አያሸንፈንም፡፡ 

Melakit_Yemegebuat_Blatena.jpg

መላእክት የመገቧት ብላቴና

መ/ር መንግሥተአብ አበጋዝ

  Melakit_Yemegebuat_Blatena.jpg

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? መላእክት በሰማይ የሚኖሩ የእግዚአብሔር አገልጋዮች መሆናቸውን ታውቃላችሁ አይደል? በመጽሐፍ ቅዱስ የሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ መልእክት ወደ ዕብራውያን ሰዎች ምዕራፍ 1 ቁጥር 7 ላይ ይገኛል፡፡

 

በጣም ጥሩ ልጆች ከዚህ በተጨማሪ መላእክት በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ 18 ቁጥር 10 ላይ እንደተገለጸው፤ እኛን የሰው ልጆችን ሁሉ ከክፉ የሚጠብቁ እና በእግዚአብሔር ፊት የሚጸልዩልን ናቸው፡፡

ዛሬ የምንነግራችሁ ከቅዱሳን መላእክት አንዱ የሆነው ቅዱስ ፋኑኤል የተባለው መልአክ የፈጸመውን ተግባር ነው፡፡

ኢያቄምና ሐና የተባሉ የእግዚአብሔር ሰዎች በስዕለት ያገኟትን ልጃቸውን ለእግዚአብሔር ቤት ሊሰጧት በሦስት ዓመቷ ወደ ቤተ መቅደስ ይዘዋት መጡ፡፡
የቤተ መቅደሱም አገልጋዮች /ካህናት/ በኢያቄምና ሐና አሳብ ተገርመው ሕጿኗን ምን እንመግባታለን እያሉም ተጨነቁ፡፡

በዚህ ወቅት ነበር አንድ አስደናቂ ነገር በቤተ መቅደሱ ዙሪያ የታየው፡፡ ስሙ ፋኑኤል የተባለው መልአክ በእጁ ሕብስትና ወይን ይዞ መጥቶ ነበርና የቤተ መቅደሱ አካባቢ በብርሃን ተሞላ፡፡

የቤተ መቅደሱ ሓላፊ ካህኑ ዘካርያስ ለእርሱ መልእክት ሊያደርስ የመጣ መስሎት ወደ መልአኩ ተጠጋ፡፡ መልአኩ ግን ከእርሱ ራቀ፡፡ ደግሞም በየተራ ሕዝቡም ካህናቱም ወደ መልአኩ ቀረቡ መልአኩ ግን ከሁሉም እየራቀ ከፍ አለ፡፡

ከዚህ በኋላ ካህናቱ የእግዚአብሔር ጥበብ አይታወቅምና መልአኩ የመጣው ለብላቴናዋ /ለሕጻኗ/ ይሆናልና፤ ሐና ሆይ እስኪ ትተሻት እልፍ በይ አሏት፡፡ ሐናም ሕጻን ልጇን ትታት ራቅ አለች፡፡ በዚህ ጊዜ መልአኩ ብላቴናይቱን አንድ ክንፉን አንጥፎ አንድ ክንፉን ጋርዶ የሰው ቁመት ያህል ከመሬት ከፍ አደረጋትና መግቧት ወደ ሰማይ ተመለሰ፡፡

በእግዚአብሔር ሥራ ሕዝቡ ሁሉ ተደነቁ፡፡ ምን እንመግባታለን? እያሉ ይጨነቁ የነበሩት ካህናትም የምግቧን ነገር መልአኩ ከያዘልንማ ብለው ቤተ መቅደስ እንድትገባ አደረጓት፡፡ ብላቴናይቱም መላእክት እየመገቧት እስከ አሥራ አምስት ዓመቷ በቤተ መቅደስ ኖረች፡፡

ልጆች ይህች ብላቴና ማን ናት?

እናትና አባቷ ማን ይባላሉ? 

ይመግባት የነበረው መልአክ ስሙ ማን ነው? በሉ ደህና ሁኑ!
ወላጆች:- ለሕጻናት ተጨማሪ ጥያቄ በማቅረብ ታሪኩን በቃል እንዲያጠኑና እንዲነግሯችሁ አድርጉ፡፡

ጸሎትና ጥቅሙ

             

ልጆች ትምህርት ጥሩ ነው?ቤተ ክርስቲያን እሑድ እሑድ ትሔዳላችሁ ? በጣም ጥሩ ልጆች ! ዛሬ የምንማማረው ስለ ጸሎት ጥቅም ነው፡፡ ጸሎት ማለት ከእግዚአብሔር የምንገናኝበት እግዚአብሔርን የምናመሰግንበት ትልቅ ኃይል ማለት ነው፡፡

በጸሎት የእግዚአብሔርን ሩህሩህነት፣ ቸርነት ኃያልነት እንገልጻለን፡፡ በጸሎት እግዚአብሔር ያደረገልንን ሁሉ አስታውሰን ምስጋና እናቀርባለን፡፡  በጸሎት በደላችንን ለእግዚአብሔር እንናዘዛለን፡፡ ይቅርታውንም እንጠይቃለን፡፡ በጸሎት ከእግዚአብሔር የፈለግነውንና የጐደለንን ለማግኘት እንለምናለን፡፡ ጸሎት ይቅርታ መጠየቂያ በመሆኗ ከቅጣትና ከመከራ የምታድን ናት፡፡ እንግዲህ ልጆች በአጠቃላይ የጸሎት ጥቅም ተነግሮ የሚያልቅ አይደለም፡፡ ልጆች እናንተስ ጠዋት ከመኝታችሁ ስትነሡ ማታ ስትተኙ ትጸልያላችሁ ?
ወይንስ ዝም ብላችሁ ትተኛላችሁ፡፡ ትነሣላችሁ? ማታ ስትተኙ እግዚአብሔርን አመስግናችሁ ጠዋት ስትነሡ እግዚአብሔርን አመስግናችሁ ጸልያችሁ መዋል አለባችሁ፡፡ ልጆች ምግብም ስትመገቡ ጸሎት አድርሳችሁ መመገብ አለባችሁ፡፡ ልጆች ጸሎት ትምህርታችሁን ይገልጽላችኋል፡፡ ከብዙ ክፉ ነገር እግዚአብሔር ይጠብቃችኋል፡፡
እንግዲህ ልጆች ጸሎት ብዙ ዓይነት ነው፡፡ 1ኛ የግል ጸሎት፣ 2ኛ. የማኅበር ጸሎት 3ኛ. የቤተሰብ ጸሎት አለ፡፡ ስትጸልዩ በጸጥታና ካለወሬ መጸለይ ያስፈልጋችኋል፡፡ በአጠቃላይ የጸሎትን ጥቅም ማወቅ ይገባናል፡፡ እሺ ልጆች! ከብዙ በጥቂቱ የጸሎትን ጥቅም እንዳወቃችሁ ተስፋ እናደርጋለን፡፡

ሥነ ፍጥረት

ልጆች የምንነግራችሁ ስለ ሥነ ፍጥረት ነው፡፡ እግዚአብሔር የሚታየውን ዓለም የፈጠረው በስድስት ቀናት ውስጥ ነው፡፡ ይህም በአንድ ቀን ለመፍጠር አቅም አጥቶ አይደለም፡፡ እርሱ ባወቀ ሁሉን በሥርዐትና በአግባቡ ለማድረግ ብሎ ነው እንጂ፡፡ ደግሞም ፈቃዱና ጊዜውም ስለሆነ ፍጥረታትን በስድስት ቀናት ውስጥ አከናወነ፡፡ 

 
የዕለታት መጀመሪያ እሑድ ናት፡፡ እግዚአብሔር በዕለተ እሑድ በመጀመሪያው ቀን አራቱ ባሕርያት የተባሉትን መሬት፣ ውኃ፣ ነፋስ፣ እሳትን ፈጠረ፡፡ በሁለተኛዋ ዕለተ ሰኞ እግዚአብሔር ጠፈርን ፈጠረ፡፡
በሦስተኛው ቀን በዕለተ ማክሰኞ ልዑል እግዚአብሔር ምድርን፣ ዘርን የሚሰጥ ሣርንና ቡቃያን በምድርም ላይ እንደ ወገኑ ዘር ያለበትን ፍሬን የሚያፈራ ዛፍን ታብቅል ብሎ በዚያ መሬት፣ አትክልትን፣ አዝርዕትን፣ ዕፅዋትን አስገኘች /ዘፍ. 1፡12/ እነዚህ ከአራቱ ባሕርያት መካከል ከመሬት፣ ከውኃ፣ ከነፋስ ተፈጠሩ፡፡
ዓርብ በመጀመሪያው ሰዓት በመዓልት ልዑል እግዚአብሔር አዳምን ፈጠረው፡፡ ከአዳም በፊት የተፈጠሩት ፍጥረታት በሀልዮና በነቢብ የተፈጠሩ ሲሆን፤ እግዚአብሔር አዳምን የፈጠረው በእጆቹ በማበጃጀት ነው፡፡ እግዚአብሔር ሰውን ለመፍጠር ሰውን በመልካችንና በአርአያችን እንፍጠር አለ /ዘፍ. 1፡26/
በአራተኛው ቀን የረቡዕ ፍጥረት የሆኑት በሰማይ ጠፈር ብርሃን ይሁን ብሎ በቃል በማዘዝ ሦስቱን ፍጥረታት ፀሐይን፣ ጨረቃንና ከዋክብትን ፈጠራቸው፡፡ /ዘፍ.1፡14/ ሐሙስ ማለት አምስተኛ ዕለት ማለት ነው፡፡ በዕለተ ሐሙስ የተፈጠሩት ሦስቱ ፍጥረታት ዘመደ እንስሳ የሚባሉት ዓሣዎች ዘመደ አራዊት የሚባሉት አዞ፣ ጉማሬ፣ እንቁራሪት፣ ዘመደ አዕዋፍ የሚባሉት ዳክዬዎች ዝዬዎች ናቸው፡፡
በዕለተ ዓርብ እግዚአብሔር የፈጠራቸው ፍጥረታት በልብ የሚሳቡ በእግር የሚራመዱ በክንፍ የሚበሩ ናቸው፡፡ ሁሉንም የፈጠራቸው ሴትና ወንድ አድርጎ ነው፡፡ለምሳሌ የቤት እንስሳት ላም፣ በሬ፣ ፈረስ፣ በቅሎ፣ ፍየል፣ በግ ውሻ እና ድመት ናቸው፡፡
አዕዋፍ ዶሮ፣ ድንቢጥ፣ እርግብ ሌሎችም ናቸው፡፡ እንስሳት ለምሳሌ አጋዘን፣ ፊቆ፣ ሚዳቋ፣ ጎሽ፣ ዝሆን፣ ዋልያ የመሳሰሉት ናቸው፡፡
ቀዳሚት ሰንበት ማለት ቅዳሜ ማለት ነው፡፡ በዚች ዕለት ልዑል እግዚአብሔር ሊፈጥረው የወደደውን ሃያ ሁለቱን ሥነ ፍጥረት ፈጥሮ አከናውኖ አረፈባት፡፡ /ዘፍ.2፡2/ በመሆኑም እግዚአብሔር ባርኮ  የቀደሳትን ዕለት ማክበር ይገባል፡፡
ልጆች እስኪ ጥያቄ እንጠይቃችሁ
1ኛ. ሀልዮና ነቢብ ማለት ምን ማለት ነው?
2ኛ. ሔዋን እንዴት ተፈጠረች?
ልጆች በመጠኑም ቢሆን ሥነ ፍጥረትን እንዳወቃችሁ ተስፋ እናደር 
ጋለን፡፡ በተረፈ ሰንበት ትምህርት ቤት ሔዳችሁ ተማሩ እሺ ጎበዞች፡፡