እንግዳ ተቀባዩ አባ ቢሾይ(ለሕፃናት)

ሐምሌ23፣2003 ዓ.ም
                                                                               አዜብ ገብሩ

እግዚአብሔርን ከሚፈሩ ጻድቅ ከሆኑ ሰዎች የተወለደ አባ ቢሾይ የሚባል አባት ነበረ፡፡ ይህ አባት ለቤተሰቦቹ ሰባተኛ እና የመጨረሻ ልጅ ነው፡፡ አንድ ሌሊት ምን ሆነ መሰላችሁ ልጆች የአባ ቢሾይ እናት ሕልም አየች የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጸ፡፡ ጌታ እንዲህ ብሏል፤ “ያገለግለኝ ዘንድ ከልጆችሽ አንዱን ስጭኝ” እናቱም እንዲህ አለች “ሰባቱም ልጆቼ አሉ፤ የፈለግኸውን መርጠህ እንዲያገለግልህ ውሰድ”
መልአኩም አባ ቢሾይን ነካው፤ እናቱ ግን እንዲህ አለች “ከልጆቼ ሁሉ እርሱ ደካማ ነው፤ እግዚአብሔርን የበለጠ እንዲያገለግሉት ከሌሎቹ ልጆቼ ምረጥ” መልአኩም እንዲህ አላት “እግዚአብሔር ያገለግለው ዘንድ የመረጠው እርሱን ነው” ከዚያም አባ ቢሾይ ሃያ ዓመት ሲሆነው ወደ ገዳም ገባ፡፡ አባ ቢሾይ ለእግዚአብሔር ታማኝ የሆነ ሰው ነበረ፡፡ ሁሌም ይጸልያል፣ ለረዥም ሰዓት ይጾማል፣ ቅዱሳት መጻሕፍን ይማራል፣ በቤቱ እንግዳ ተቀብሎ ያስተናግዳል፡፡ እግዚአብሔርን የሚያስደስት  ብዙ መልካም ሥራ ይሠራል፡፡

 

ከዕለታት አንድ ቀን አባ ቢሾይ ከበአቱ በር ላይ ተቀምጦ ሳለ በጣም የደከመው ሰው ወደ እርሱ ሲመጣ ተመለከተ፡፡ ከተቀመጠበት ተነሣና ያን ሰው ወደ በአቱ እንዲገባና እንዲያርፍ ጠየቀው፡፡ ከዚያም ያን በጣም የደከመው ሰው ውሃ አቅርቦ እግሩን ማጠብ ጀመረ፡፡ እግሩን እያጠበው ሳለም የእግዚአብሔር ድምጽ እንዲህ ሲል ሰማ “የተወደድክ ልጄ ቢሾይ ሆይ አንተ የተከበርክ ሰው ነህ” ወዲያውም የአምላካችንን እግር እያጠበ እንደነበር አስተዋለ፡፡ ተንሥቶም ተንበረከከ እግዚአብሔርን አመሰገነ፡፡ እግዚአብሔርም ሰላምን ሰጠው፡፡
 
አያችሁ ልጆች አባ ቢሾይ እግዚአብሔርን አየው ምክንያቱም ትሑት ስለነበረና ዝቅ ብሎ የሌሎችን ሰዎች እግር ያጥብ ስለነበረ ነው፡፡ እኛም እንደ አባ ቢሾይ ትሑት መሆንና ወደቤታችን ለሚመጡት ሰዎች ሁሉ ደግ መሆን አለብን ይህን ካደረግን እግዚአብሔር ለእኛ መልካምን ነገር ያደርግልናል፡፡ በመንግሥተ ሰማይም ስለ ሠራነው መልካም ነገር ሽልማትን ይሸልመናል፡፡

                                                          ወስብሐት ለእግዚአብሔር