አትዋሹ(ለሕፃናት)

 

በአዜብ ገብሩ

በድሮ ጊዜ ክርስቲያኖች በአንድነት ይኖሩ ነበር፡፡ በመካከላቸውም የሁሉ ገንዘብ በአንድነት ነበር አንጂ “ይህ የእኔ ገንዘብ ነው” የሚል አልነበረም ከእነርሱም አንድም ችግረኛ አልነበረም፤ ቤትና መሬት ያላቸው ሁሉ እየሸጡ ገንዘቡን ያመጡ ነበር፡፡

 

 

አምጥተውም በሐዋርያት እግር ስር ያስቀምጡ ነበር፡፡ ሐዋርያትም ለእያንዳንዱ እንደፍላጎቱ ይሰጡ ነበር፡፡ ሐዋርያት ስሙን ዮሴፍ እያሉ የሚጠሩት በርናባስ የተባለ ሰው ነበር፡፡ የእርሻ መሬትም ነበረው፡፡መሬቱንም ሸጦ ገንዘቡን በሐዋርያት እግር ስር አስቀመጠው ከሐዋርያትም ማኅበር ተቀላቀለ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ልጆች ሐናንያና ሰጲራ የተባሉ ባልና ሚስቶች ነበሩ፡፡ እነዚህ ባልና ሚስቶች መሬታቸውን ሸጡ፡፡ እርስ በርሳቸውም ተማከሩና ከሸጡት ዋጋ ግማሹን ለራሳቸው ወሰዱና የሸጥነው በዚህ ዋጋ ነው ብለው ግማሹን በሐዋርያት እግር ስር አስቀምጠው ከማኅበሩ ለማቀላቀል ይዘው ሄዱ፡፡ ያደረጉትን ማንም የሚያውቅባቸው አልመሰላቸውም ነበር፡፡ ነገር ግን ይህን ሁሉ ነገር እግዚአብሔር ያውቃል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም መንፈስ ቅዱስ በእርሱ ውስጥ ነበርና ያደረጉትን ነገር ያውቅ ነበር፡፡

 

ቅዱስ ጴጥሮስም ለሐናንያ እንዲህ አለው “ሰውን ሳይሆን መንፈስ ቅዱስን ለምን ታታልላለህ መጀመሪያም ሳትሸጠው ያንተ አልነበረምን አሁንስ ከሸጥነው በኋላ ያንተ አይደለምን ይህንን ነገር ለምን በልብህ አሰብሀ” አለው ሐናንያም ይህን በሰማ ጊዜ ወድቆ ሞተ፤ ሰዎችም ተሸክመው ወስደው ቀበሩት፡፡ ይህ ከሆነ ከሦስት ሰዓት በኋላም ሚስቱ ሰጲራ መጣች፡፡ ባልዋ የሆነውን ሳታውቅ ገባች፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም “እስኪ ንገሪኝ መሬታችሁን የሸጣችሁት በዚህ ዋጋ ነውን” አላት፡፡ እርሷም “አዎ” አለች፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስም “የእግዚአብሔርን መንፈስ ትፈታተኑት ዘንድ እንዴት ተባበራችሁ አነሆ ባልሽን የቀበሩት ሰዎች በበር ናቸው አንቺንም ይወስዱሻል” አላት፡፡ ወዲያውም ወድቃ ሞተች፤ ሰዎቹም ወስደው ቀበሩአት፡፡

 

ልጆች እኛም ውሸት ስንናገር እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ሥራ እየሰራን እና የሌሎች ሰዎችን እምነት እያጣን መሆኑን ልናውቅ ይገባል፡፡ የምንዋሽ ከሆነ እግዚአብሔር በጣም ስለሚወደን ከውሸታችን እንድንመለስ ይታገሰናል፡፡ ካልተመለስን ግን በረከቱን ከእኛ ይወስድብናል፡፡ ስለዚህ ይህን ማስወገድ ይገባናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር