ጥር 30/2004 ዓ.ም
በዲ/ን ኅሩይ ባየ
“በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ብዙ ጊዜ ድርሳንና ገድል ሲባል እሰማለሁ፡፡ እኔም የድርሳንና የገድል ልዩነት ብዙ ጊዜ አይገባኝም፤ እባካችሁ የድርሳንና የገድልን አንድነትና ልዩነት አስረዱኝ”
ገብረ እግዚአብሔር
ከዲላ
ውድ ጠያቂያችን በእርግጥ እርስዎ እንዳሉት ድርሳንና ገድል በቤተ ክርስቲያን የማይነሡበት ጊዜ የለም፡፡ “የኑሮአቸውን ፍሬ እየተመለከታችሁ በእምነት ምሰሏቸው” ዕብ.13፥7 እንደተባለው በሃይማኖትና በምግባር ለመጠንከር ገድለ ቅዱሳንን የያዙ መጻሕፍትን እናነባለን፤ እንጸልይባቸዋለን፡፡ የቅዱሳን መላእክትንም ጠባቂነት፣ የሊቃውንትን ተግሣጽ ትርጓሜና ምክር የዕለተ ሰንበትን ክብር እና የኢየሱስ ክርስቶስን የቤዛነት ሥራ የሚናገሩ ድርሳናትን ሁል ጊዜ እናነባለን እናደርሳለን፡፡
አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ መጽሐፈ ሰዋሰው ወግሥ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ በተባለው መጽሐፋቸው “ድርሳን” የሚለውን ቃል እንዲህ ብለው ይፈቱታል “ድርሳን በቁሙ “የተደረሰ፣ የተጣፈ፣ ቃለ ነገር፣ ሰፊ ንባብ፣ ረዥም ስብከት፣ ትርጓሜ፣ አፈታት፣ ጉሥዐተ ልብ፣ መዝሙር፣ ምሥጢሩ የሚያጠግብ፣ ቃሉ የተሳካ፣ ጣዕመ ቃሉና ኃይለ ቃሉ ደስ የሚያሰኝ ልብ የሚነካ” ማለት ነው፡፡