ስትተባበሩ ሁሉንም ታሸንፋላችሁ /ለሕፃናት/

የካቲት 8/2004 ዓ.ም.

በቴዎድሮስ እሸቱ

ልጆች እንደምን ሰነበታችሁ ከዚህ በታች ያለውን ተረት በደንብ አንብቡ በርካታ ቁም ነገሮችን ታገኙበታላችሁ መልካም ንባብ፡፡
ከእለታት አንድ ቀን በአንድ ሀገር የሚኖር ሰው ነበር ይህ ሰው ዘጠኝ ልጆች ሲኖሩት ሁሉም እርስ በራሳቸው የማይዋደዱ የማይስማሙ ነበሩ333 (2) ሁሉም አባታቸው የሚያወርሳቸውን የራሳቸውን ድርሻ ይዘው ለብቻቸው መኖር ይፈልጉ ነበር፡፡ ከዚያም አንድ ቀን አባታቸው በጠና ታሞ አልጋ ላይ ተኛ ልጆቹንም ጠራቸውና አንድ ትእዛዝ አዘዛቸው ትእዛዙም “ሁላችሁም ሒዱና ለየራሳችሁ አንድ አንድ ጭራሮ ይዛችሁ ኑ” የሚል ነበር፡፡ ከዚያም ልጆቹ ወደውጪ ሔደው ለየራሳቸው አንድ አንድ ጭራሮ ይዘው ተመለሱ፡፡

 

አባታቸውም ታላቁን ልጅ ጠርቶ የያዝከውን ጭራሮ ስበረው አለው ታላቁ ልጅም ጭራሮዋን ቀሽ አድርጎ ሰበራት እንዲህ እንዲህ እያሉ ሁሉም ልጆች የየራሳቸውን ጭራሮዎች ሰበሯቸው፡፡ ከዚያም አባትየው ትልቁን ልጅ ጠራውና የሁሉንም ወንድሞችህን ጭራሮ ሰብስብ አለው፡፡ታላቁ ልጅም የሁሉንም ጭራሮ ተቀብሎ ሰብስቦ ያዘ አባትየውም በል አሁን የያዝካቸውን ጭራሮ አንድ ላይ ስበራቸው አለው፡፡

22ታላቁ ልጅም ቢሞክር ቢሞክር ቢታገል ጭራሮዎቹን ሊሰብራቸው አልቻለም ሁሉም ልጆች ቢሞክሩ አንድ ላይ የተሰበሰቡትን ጭራሮዎች ሊሰብሯቸው አልቻሉም ከዚያም አባትየው ልጆቹ ወደእርሱ እንዲጠጉ በምልክት ጠራቸውና እንዲህ ብሎ ነገራቸው፡፡

ልጆቼ በመጀመሪያ ሁላችሁም የያዛችኋቸውን ጭራሮዎች በቀላል ሰበራችኋቸው በኋላ ግን333 (1) አንድ ላይ ሲሰበሰቡ ከእናንተ ውስጥ ማናችሁም ልትሰብሩ አልቻላችሁም፡፡ እናንተም የምትለያዩ ከሆነ አንድ ላይ የማትሆኑ ከሆነ ጠላት በቀላሉ ያጠፋችኋል ሌባ ይዘርፋችኋል፤ ጠንካራና ጎበዝ ልትሆኑ አትችሉም፡፡ አንድ ላይ ከሆናችሁ ግን ማንም አይደፍራችሁም፡፡ አሁን እኔ ልሞት ነው የማወርሳችሁን ሀብት በጋራ ተጠቀሙበት በመካከላችሁ መለያየት እንዳይኖር አደራ አላቸው፡፡ ከዚያም ትንሽ ቆይቶ ሞተ እነሱም ከዚያች ዕለት በኋላ ሳይጣሉ እርስ በእርስ በመዋደድ በፍቅር አንድ ላይ መኖር ጀመሩ ተባብረው ስለሚሠሩም ሀብታምና ጠንካሮች መሆን ቻሉ፡፡

ልጆቼ እነዚህ ወንድማማቾች ባይተባበሩ ኖሮ ጠንካሮች መሆን አይችሉም ጠላትም በቀላሉ ያጠቃቸዋል፡፡ እናንተም ከጓደኞቻችሁ በመጠየቅ ለጓደኞቻችሁ የምታውቁትን በማስረዳት ልትተባበሩ ይገባል በትብብር ስታጠኑ የሚከብዳችሁ ሁሉ ይቀላችኋል፡፡