የካቲት 9/2004 ዓ.ም.
በእንዳለ ደጀኔ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ምእመናን መታሰቢያ ድርጅት ለኢየሩሳሌም የካቲት 4 ቀን 2004ዓ.ም የተመሠረተበት 49ኛ ዓመት በዓል ለድርጅቱን መሥራች ክብር አቶ መኮንን ዘውዴ የመታሰቢያ ሐውልት ቦሌ ሩዋንዳ በሚገኘው መሰብሰቢያ አዳራሽ በር ላይ በማቆም ጭምር ተከብሯል፡፡
በ1955 ዓ.ም. ሚያዝያ 3 ቀን ከሠላሳ በማይበልጡ ኢትዮጵያውያን ወገኖች እንደተመሠረተ የሚነገረው መታሰቢያ ድርጅቱ በክብር አቶ መኮንን ዘውዴ ጠንሳሽነትና አሰባሳቢነት እንደሆነ ይነገራል፡፡ በወቅቱ ቅዱሳን መካናትን ለመሳለም ወደ ቅድስት ሀገር ኢየሩሳሌም የሔደው የምእመናን ቡድን በዚያ ያለውን ችግርና በገዳማቱ የሚኖሩ አባቶችና እናቶችን በደልና ስቃይ ተመልክቶ የነበረ ሲሆን በተለይ የዴር ሱልጣን ገዳማችን ወደ ጥንቱ ይዞታ ለመመለስ ካልተቻለበት ምክንያቶች አንዱ ከኢትዮጵያ ገዳማውያንን ለመጎብኘት የሚመጣ ሰው የለም የሚል ምክንያት እንደሚሰጥ መረዳታቸው ለድርጅቱ መመሥረት ምክንያት እንደሆነ ተገልጿል፡፡