በርናባስ ረድእ /ለሕፃናት/

የካቲት 3/2004 ዓ.ም.
በቴዎድሮስ እሸቱ

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች ዛሬ ከ12ቱ አርድእት አንዱ ስለሆነው ስለ ቅዱስ በርናባስ ታሪክ በአጭሩ እጽፍላችኋለሁ፡፡

በርናባስ ማለት የስሙ ትርጉም ወልደ ፍስሐ የደስታ ልጅ ማለት ነው የተወለደው ቆጵሮስ በሚባል አገር ነው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከአረገ በኋላ ሀብት ንብረቱን በመሸጥ ለሐዋርያት ሰጥቶአቸዋል፡፡

ቅዱስ ጴጥሮስ ወደ ክርስትና ዓለም ሲጠራ ከሐዋርያት ጋር ያስተዋወቀው እርሱ ነው፡፡ ከቅዱስ ጳውሎስም ጋር በመሆን በልጥራን ያስተምሩ በነበረበት ወቅት አንድ ሕመምተኛ ፈወሱ፡፡ በዚህ ጊዜ የአካባቢው ነዋሪ አማልክት በሰው አምሳል ወደ እኛ ወረዱ ኑ መስዋእት እንሠዋላቸው ብለው ላም ይጎትቱ ጀመር፡፡ እነ ቅዱስ በርናባስም እኛ እንደ እናንተ የምንምት ሰዎች ነን ተው ብለው ከለከሏቸው የዚያ ሀገር ሰዎችም ስማቸውን ቀይረው ቅዱስ በርናባስን ድያ ጳውሎስን ሄርሜን ብለው ሰይመዋቸዋል፡፡

ቅዱስ በርናባስም እንዲህ ከሀገር ሀገር እየተዘዋወረ ሲያስተምር ኖሮ ሕዝበ ክርስቲያኑን ለመጎብኘት ቅዱስ ማርቆስን አስከትሎ ወደ ቆጵሮስ በመመለስ ማስተማር ጀመረ፡፡ ከቆጵሮስ በተጨማሪም ሶርያንና ዲልቅያን ጨምሮ ሲያስተምር አሕዛብ /የማያምኑ/ ጠልተው፤ ተመቅኝተው በድንጋይ በመውገር ነፍሱን ከሥጋው ከለዩ በኋላ ከእሳት ጣሉት፡፡ እሳቱ ግን ሥጋውን ሳያቃጥለው ቅዱስ ማርቆስ አንሥቶ ቀብሮታል፡፡