ጌታችን ከተወለደ ፴፫ የምሕረት ዘመናት ተቆጠሩ። ዕለቱ እሑድ፣ ቀኑ መጋቢት ፳፪ ነበር። በምድር የሚመላለስበትን ዘመን ሊጨርስ ጥቂት ቀናት ሲቀሩት ወደ ኢየሩሳሌም ለመግባት ለደብረ ዘይት ትራራ ቅርብ ወደ ሆነችው ቤተ ፋጌና ቢታንያ መንደር ገሰገሰ፡፡ ከደቀ መዛሙርቱም ጴጥሮስና ዮሐንስን እንዲህ አላቸው፤ ‘‘በፊታችሁ ወዳለችው መንደር ሂዱ፤ ወደ መንደርም በገባችሁ ጊዜ ሰው በላዩ ያልተቀመጠበት የአህያ ውርንጫ ታስሮ ታገኛላችሁ፤ ፍቱና አምጡልኝ፤ ምን ታደርጋላችሁ የሚላችሁ ሰው ቢኖርም ጌታው ይሻዋል በሉ’’ አላቸው፤ (ማር.፲፩፥፪) ሁለቱ ደቀ መዛሙርትም እንደታዘዙት አደርጉ፡፡
የታሰሩትን ሊፈታ መጥቱዋልና የታሰርውን ፍቱልኝ አለ፤ ሰውን ሁሉ ከማዕሰረ ኃጢአት የሚፈታበት ጊዜ እንደደረሰ ሲያጠይቅ ነው። በአህያ ላይ ሁኖ ሲገባም የሚበዙት ሕዝብ ለጌታችን ክብር ለአህያዋ ልብሳቸውን ጎዘጎዙ፤ ልብስ ገላን ይሸፍናልና ከባቴ አበሳ ነህ ሲሉ። በፊት በኋላ ሁነው ‘‘ለወልደ ዳዊት መድኃኒት መባል ይገባዋል’’ እያሉ አመሰገኑ፤ ሆሣዕና ማለት መድኃኒት ማለት ነውና “ሆሣዕና በአርያም” ሲሉ ቀኑን ዋሉ፡፡ በፊቱ ያሉት የሐዋርያት በኋላው ያሉት የነቢያት ምሳሌዎች ናቸው፡፡ በሌላም ትርጉም የብሉያትና የሐዲሳት ምሳሌዎች ሁነዋል። በዚህም የፊተኛውም የኋኛውም ዘመን ጌታ መሆኑ ተገልጧል፡፡