ከውኃና ከመንፈስ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት አያይም

በአያሌው ዘኢየሱስ

መጋቢት ፳፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹እውነት እውነት እልሃለሁ፤ ሰው ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት አያይም፤›› (ዮሐ.፫፥፫)፡፡

ይህ ቃል ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለኒቆዲሞስ ካስተማረው ትምህርት የተወሰደ ኃይለ ቃል ነው፡፡ ኒቆዲሞስ ብዙ የተማረ፤ ብዙ ያወቀ የሃይማኖት ሊቅ ነው፡፡ ከዚህም የተነሣ ሊቅ፣ ምሁር፣ አለቃ ተብሎ ተጠርቶአል፡፡ በጊዜው ከነበሩ ሰዎች ከፍ ያለና የላቀ ዕውቀት የነበረው ሰው ነበር፡፡ በሌሊት ወደ ጌታ እየመጣ ይማር ነበር፡፡ የማታ ተማሪ ነበር፡፡ ቀን፣ ቀን የምኵራብ አስተማሪ ኾኖ ብዙ ሰዎችን ያስተምር ስለ ነበረና እርሱ የሚያስተምራቸው አይሁድ ጌታችንን ስላልተቀበሉ በቀን ለመማር አመቺ ጊዜ አልነበረውም፡፡

በአይሁድ ሕግ ጌታን የሚከተልና የሚቀበል ሰው ከምኵራብ ይባረር ስለ ነበረ እነርሱን ላላማስቀየም ኒቆዲሞስ ማታ፣ ማታ ነበር የሚማረው፡፡ ኒቆዲሞስ፡- ‹‹ከሰው ችሎታ በላይ የኾኑ ተአምራትን ስለምትሠራ እኛን ለማስተማርና ለመምከር ከእግዚአብሔር ዘንድ ተልከህ የመጣህ ነህ›› ብሎ ለጌታችን መስክሮለታል፡፡ ጌታችንም፡- ‹‹እናንተን ለማስተማር እንደ መጣሁ ከተረዳህ ሰው ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት አይገባም›› አለው፡፡

ኒቆዲሞስ ስላልገባው ‹‹እኔ አርጅቼአለሁ፤ እንዴት ነው ወደ እናቴ ማኅፀን ተመልሼ የምገባውና ዳግም የምወለደው?›› ብሎ ኢየሱስ ክርስቶስን ጠየቀው፡፡ ጌታችንም፡- ‹‹ሰው ከሰው ከተወለደ ሥጋዊ ነው፤ የሰው ልጅ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ልጅ ለመኾን በመንፈስ መወለድ አለበት፡፡ ከእግዚአብሔር መወለድ ነፋስ ከየት ተነሥቶ ወዴት እንደሚነፍስ እንደማይታወቅ ያለ ረቂቅ ምሥጢር ነው›› አለው፡፡ አሁንም ያ ሊቅ፤ ያ አዋቂ ‹‹አልገባኝም›› አለ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስም፡- ‹‹አንተ የእስራኤል መምህር እና ሊቅ ኾነህ እንዴት ይህን አታውቅም?›› አለው፡፡ ከሰማይ ከወረደው በቀር ወደ ሰማይ የሚወጣ የለም፤ የምናውቀውንም እንናገራለን ካለው በኋላ ጥያቄውን በዚህ ገታ፡፡

ኒቆዲሞስ  ወደ ጌታችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ መጥቶ መማሩ የሚያስመሰግነው ተግባር ነው፡፡ አይሁድ ወገኖቹ ጌታን ሳይከተሉት እርሱ ግን ጌታን መውደዱ የሚያስደንቅ ነው፡፡ ኒቆዲሞስ የሚያመሸው ከጌታ ጋር ነበር፡፡ ባለችው ትርፍ ጊዜው ዅሉ ወደ ፈጣሪው ይሔድ ነበር፡፡ ይህ ታላቅ ዕድል ነው፡፡ ቀን ሲያስተምርና ሲደክም ስለሚውል ማታ፣ ማታ ማረፍ ይገባው ነበር፡፡ ኒቆዲሞስ ግን ቤቴ ገብቼ ልረፍ አላለም፡፡ ባለ ሥልጣንና ባለጠጋ ስለ ነበር ደጅ የሚጠናው ሕዝብና መሰል ባልንጀሮቹ ይፈልጉት ነበር፡፡ ይኹን እንጂ ከእነርሱ ጋር አላመሸም፡፡

ከዚህ አባት ታላቅ ትምህርት ልንማር ያስፈልጋል፡፡ እኛ ዛሬ የምናመሸው የት ነው? የምናመሸውስ ከማን ጋር ነው? ምን ስናደርግ ነው የምናመሸው? ኒቆዲሞስ ቤቱ አልነበረም የሚያመሸው፤  ከእውነተኛው መምህር ጋር እንጂ፡፡ ኒቆዲሞስ ጽድቁንና በረከቱን እየያዘ ነበር ወደ ቤቱ ይገባ የነበረው፡፡ እኛ ወደ ቤታችን የምንገባው እየከበርን ነው ወይ? ጸድቀን ነው የምንገባው ወይስ ጐስቁለን?

የዛሬ ዘመን ሰው እየሰከረ፣ እየጨፈረ፣ እየደማ፣ እየቆሰለ አእምሮውን ስቶ ነው ወደ ቤቱ የሚመለሰው፡፡ የሚሞትም አለ፡፡ በቤት ያሉት ወገኖቹም ‹‹እንቅፋት ያገኘው ይኾን? ይሞት ይኾን?›› እያሉ እየተሳቀቁ ነው የሚያመሹት፡፡ ማምሸት እንደ ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር ነው እንጂ! ኒቆዲሞስ ከጌታ ጋር በማምሸቱ ፈጣሪውን አወቀ፡፡ ጌታን ማወቅ ብቻ ደግሞ አይበቃም፡፡ ማወቅማ አጋንንትም ያውቁታል፡፡ ከመንፈስ መወለድ ያስፈልጋል፡፡

የሰው ልጅ ዕፀ በለስን በበላ ጊዜ የእግዚአብሔር ልጅነቱን ተነጥቆ ነበር፡፡ ጌታችን መጥቶ ዳግም ሰው እስከሚያደርገን ድረስ የሰይጣን ልጆች ኾነን ነበር፡፡ ከዚያም በዐርባና በሰማንያ ቀን ከአብራከ መንፈስ ቅዱስና ከማኅፀነ ዮርዳኖስ ተወልደናል፡፡ እግዚአብሔርን አባታችን የምንለውም ስለዚህ ነው፡፡ ከእርሱ ከተወለድንና ልጅነትን ካገኘን፣ እንደ ገና ልጅነታችንን እንዳናጣ አክብረን እንያዘው፡፡ መጀመሪያም አላወቅንበትም ነበር፡፡ አዳም ከገነት የሚወጣ አልመሰለውም ነበር፡፡ ሰይጣን አታሎታል፡፡ እኛም እንደ ገና እንዳንታለል ልጅነታችን እንዳይሰረዝ እንጠንቀቅ፡፡

የብዙዎቻችን ልጅነት ዛሬ እየተወሰደ ነው፡፡ ልጅነታችንን እያስነጠቅነው ነው፡፡ እነኤሳው እየነጠቁን ነው፡፡ ብዙዎች እንደ ያዕቆብ ልጅነታችንን ሊወስዱብን አሰፍስፈዋል፡፡ ሰይጣን እንደ አዳም ሊነጥቀን አሰፍስፏል፡፡ ኒቆዲሞስ አርጅቶ ነበር፡፡ በጥምቀትና በንስሐ ግን አዲስ ሕይወትን አግኝቶአል፤ ታድሷል፡፡ ያረጀው ሕይወቱ ለምልሟል፡፡ እኛም ዛሬ በጣም አርጅተናል፡፡ ያረጀው ሰውነታችንን በሥጋውና በደሙ በንስሐ እናድሰው፡፡ ይህ ከኾነ ነው የእግዚአብሔርን መንግሥት የምንወርሰው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

  • ብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ የከምባታ፣ ሀድያ፣ ጉራጌና ሥልጤ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ በአዲስ አበባ የደብረ ብሥራት ቅዱስ ገብርኤል ደብር የበላይ ሓላፊ፤ በዚሁ ደብር በአስተዳዳሪነት ባገለገሉባቸው ዓመታት ካስተማሩት ትምህርተ ወንጌል የተወሰደ (መጋቢት ፳፩ ቀን ፲፱፻፹፭ .ም)፡፡

የ፲፪ኛው ሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በፎቶ

መጋቢት ፳፬ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ማኅበረ ቅዱሳን ለ፲፪ኛ ጊዜ ያዘጋጀው የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር በደቡብ ምዕራብ ሸዋ ሀገረ ስብከት በቾ ወረዳ ቤተ ክህነት ከአዲስ አበባ ከተማ በሰባ ሁለት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘው ቱሉ ጉጂ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን በዛሬው ዕለት ተካሒዷል፡፡ በመርሐ ግብሩ ላይም ከዐሥራ ሦስት ሺሕ ሁለት መቶ አምሳ በላይ ምእመናን መሳተፋቸው ታውቋል፡፡ መርሐ ግብሩ ከሰዓታት በፊት በጸሎት የተፈጸመ ሲኾን፣ የጉባኤውን አጠቃላይ ኹኔታም በሚከተሉት ፎቶዎች ትመለከቱ ዘንድ ጋበዝናችሁ፤

img_0137

ቱሉ ጉጂ ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን

img_0275

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እና የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

img_0348

ብፁዕ አቡነ ሳዊሮስ ቃለ ምዕዳን ሲሰጡ

img_0317

ብፁዕ አቡነ ዳንኤል ቃለ ምዕዳን ሲሰጡ

img_0092

img_0097

መርሐ ግብሩ በጸሎተ ወንጌል ሲከፈት

img_0103

img_0098

የጉባኤው ተሳታፊዎች ቆመው ጸሎተ ወንጌል ሲያስደርሱ

img_0290

የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

img_0237

ምክረ አበው አቅራቢ መምህራን

img_0243

img_0227

img_0271

የማኅበረ ቅዱሳን ዘማርያን የበገና ዝማሬ ሲያቀርቡ

img_0113

የመርካቶ ደብረ ኃይል ቅዱስ ራጉኤል ሰ/ት/ቤት የጎልማሶች መዘምራን መዝሙር ሲያቀርቡ

img_0213

መጋቤ ስብሐት ዓለሙ አጋ የበገና ዝማሬ ሲያቀርቡ

img_0121

የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

img_0110

img_0160

img_0326

img_0329

img_0153

img_0180

img_0169

የጉባኤው ተሳታፊዎች በከፊል

img_0216

በጉባኤው የተገኙ የቱሉ ጉጂና የአካባቢው ምእመናን በከፊል

img_0005

የጉዞው ቅድመ ዝግጅት

img_0018

img_0021

img_0012

img_0047

ጉዞ ወደ ቱሉ ጉጂ

img_0076

የቱሉ ጉጂ አካባቢ ወጣቶች መንገድ ሲያስተካክሉ

img_0078

img_0081

የመኪኖች መቆሚያ እና የጉባኤው ቦታ በከፊል ከርቀት ሲታይ

img_0122

img_0087

ምእመናን ከመኪና ወርደው ወደ ጉባኤው ሲያመሩ

img_0083

img_0132

የጉባኤው ሥፍራ በከፊል

img_0350

ጉባኤው በጸሎት ከተፈጸመ በኋላ ምእመናን ወደ ተዘጋጁላቸው መኪኖች ሲመለሱ

img_0355

img_0352

img_0353

img_0360

ኒቆዲሞስ

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

መጋቢት ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹ጾምን ቀድሱ፤ ጉባኤውንም ዐውጁ፡፡ ሽማግሌዎችንና በምድር የሚኖሩትን ዅሉ ወደ አምላካችሁ ወደ እግዚአብሔር ሰብስቡ፤ ወደ እግዚአብሔርም ጩኹ፡፡ በጽዮን መለከት ንፉጾምንም ቀድሱ፤›› በማለት የዐዋጅ አጽዋማትን እንድንጾም እግዚአብሔር አምላካችን በነቢዩ ኢዩኤል ላይ አድሮ ነግሮናል (ኢዩ. ፩፥፲፬፤ ፪፥፲፭)፡፡ ከእነዚህ አጽዋማት መካከልም ዐቢይ ጾም አንዱ ነው፡፡

ይህ ጾም የጠፋውን የሰውን ልጅ ለመፈለግ፣ የሞተውን አዳምን ለማስነሣት ሰው ኾኖ ወደዚህ ዓለም የመጣው፣ ወልደ አብ ወልደ ማርያም ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመብል የተጀመረውን የሞት መንገድ ለማጥፋት ሲል የጾመው ጾም ነው፡፡ እኛም አባቶቻችን በሠሩልን ሥርዓት መሠረት በዐቢይ ጾም ወራት ‹ዘወረደ› ብለን ጀምረን በዓለ ትንሣኤን እስከምናከብርበት ዕለት ድረስ ያሉትን ሰንበታት በልዩ ልዩ ስያሜ በመጥራት የተከፈለልንን ዋጋ እያሰብን ቃለ እግዚአብሔር እንማራለን፤ እንዘምራለን፤ እንጸልያለን፡፡ ከእነዚህ ሰንበታት መካከል በሰባተኛው ሳምንት የሚገኘው ወቅት ‹ኒቆዲሞስ› ይባላል፡፡

ኒቆዲሞስ ከፈሪሳውያን ወገን የአይሁድ አለቃ የነበረው ሰው ነው፡፡ የአይሁድ አለቆች አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስን ‹‹ምልክት አሳየን›› እያሉ ይፈታተኑት ነበር፡፡ ጌታችን ስለ ሞቱና ትንሣኤው በምሳሌ እያስረዳ ቢያስተምራቸውም እነርሱ ግን አልገባቸውም ነበር፡፡ ከዚህም አልፎ ጌታችን በተአምራቱ የታመሙትን ሲፈውስ ‹‹ሕጋችን ተሻረ›› ይሉ ነበር፡፡ በዚህ ዅሉ ተአምራትና ትምህርት የአይሁድ አለቆች ክርስቶስን ለመክሰስ በሚፈልጉበት ወቅት ከአይሁድ አለቆች አንዱ ኒቆዲሞስ በቀን እንዳያደርገው አይሁድን ቢፈራ፣ አንድም ጊዜ ባያደርሰው እንደ ባልንጀሮቹ ክርስቶስን ሳይቃወም በሌሊት ወደ ጌታችን ዘንድ እየሔደ ወንጌልን ይማር ነበር፡፡

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በነፍስ የታመሙትን በቃሉ፣ በሥጋ የታመሙትን በተአምራቱ ሲፈውስ ኒቆዲሞስ ሰምቶ፣ ተመልክቶ በመምህርነቱ ሳይኮራ አለቅነቱን መመኪያ ሳያደርግ በልቦናው የተሳለውን እውነትን የመፈለግ ስሜት አንግቦ ከጌታው፣ ከመምህሩ ከክርስቶስ ዘንድ በሌሊት ይገሰግስ ነበር (ዮሐ. ፫፥፩)፡፡ ምስክርነቱንም እንዲህ ሲል መስጠት ጀመረ፤ ‹‹መምህር ልታስተምር ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደ መጣህ እናውቃለን፡፡ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከኾነ በቀር አንተ የምታደርገውን ተአምራት ሊያደርግ የሚችል የለምና፤›› (ዮሐ. ፱፥፳፬፤ ሐዋ. ፲፥፴፰)፡፡

ይህን ምስክርነቱን በሚሰጥበት ጊዜም ጎዶሎን የሚሞላ፤ አላዋቂነት በአዋቂነት የሚለውጥ፤ ከምድራዊ ዕውቀት ወደ ሰማያዊው ምሥጢር የሚያሸጋግር አምላክ ‹‹ዳግመኛ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማየት አይችልም፤›› በማለት የአይሁድ መምህር ለኾነው ኒቆዲሞስ ቢያስተምረው ምሥጢሩ አልተገለጠለትም ነበርና ‹‹ሰው ከሸመገለ በኋላ ዳግመኛ መወለድ እንደምን ይቻላል? ዳግመኛ ይወለድ ዘንድ ወደ እናቱ ማኅፀን ተመልሶ መግባት ይችላልን?›› በማለት ጥያቄ አቅርቧል (ዮሐ. ፫፥፮፤ ፩ኛጴጥ. ፩፥፳፫)፡፡ ‹‹እውነት እውነት እልሃለሁ፤ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡ ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፡፡ ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነውና፤›› (ኤፌ. ፭፥፳፮) በማለት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለኒቆዲሞስ ቢያስረዳውም ምሥጢሩ ከአቅሙ በላይ ስለ ኾነበት እንደምን ይቻላል? በማለት ጠይቋል፡፡

አበ ብዙኃን አብርሃም ከአምላኩ ሞገስን አግኝቶ የሰዶምና ገሞራ ጥፋት እንዳይደርስ ለመማለድ ከእግዚአብሔር ጋር ሲነጋገር እንደ ነበረ፤ ኒቆዲሞስም አላዋቂነቱን አምኖ ያልገባውን ምሥጢር ከአምላኩ በጠየቀ ጊዜ ኢየሱስ ክርስቶስም፡- ‹‹አንተ የእስራኤል መምህራቸው ኾነህ ሳለ ይህን ነገር አታውቅምን? በምድር ያለውን ስንነግራችሁ ካላመናችሁ በሰማይ ያለውን ብንነግራችሁ እንደምን ታምናላችሁ? ከሰማይ ከወረደው ከሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለምሙሴምድረ በዳ እባቡን እንደ ሰቀለ የሰው ልጅ እንዲሁ ይሰቀላል፡፡ ያመነበት ዅሉ ለዘለዓለም ሕያው እንዲኖር እንጂ እንዲጠፋ አይደለም ...፤›› እያለ ሰው በመብል ምክንያት የአምላኩን ትእዛዝ አፍርሶ ከእግዚአብሔር ቢለይም የሰው ልጅ ያጣውን ልጅነት ለመመለስ፣ ስመ ክርስትናን፣ ሀብተ ወልድን ለመስጠት ጌታችን መምጣቱን አስረዳው (ዮሐ. ፫፥፲፬)፡፡ ይህን የክርስቶስን የማዳን ሥራና በሥጋ መገለጥም ‹‹ሐወጽከኒ ሌሊተ ወፈተንኮ ለልብየ አመከርከኒ ወኢተረከ ዐመፃ በላዕሌየ ከመ ኢይንብብ አፉየ ግብረ እጓለ እመሕያው፤ ልቤን ፈተንኸው፡፡ በሌሊትም ጐበኘኸኝ፤ ፈተንከኝም፡፡ ምንም አላገኘህብኝም፡፡ የሰውን ሥራ አፌ እንዳይናገር ፈቃዴ ነው፤›› (መዝ. ፲፮፥፫) በማለት ቅዱስ ዳዊት ከኒቆዲሞስ ሕይወት ጋር በማዛመድ አመሥጥሮታል፡፡

በሌሊት ከአምላኩ ተምሮ ምሥጢሩ የተገለጸለት ኒቆዲሞስ ቀድሞ በአደባባይ ሔዶ መማርን ይፈራ እንዳልነበረ ምሥጢሩ ሲገለጽለት ግን አይሁድ ጌታችንን በሰቀሉት ዕለት ፍርኃት ርቆለት ከአርማትያሱ ዮሴፍ ጋር ቅዱስ ሥጋውን ገንዞ ለመቅበር በቃ፡፡ ‹‹ወአልቦ ፍርኃት ውስተ ተፋቅሮትነ፤ ፍጹም ፍቅር ፍርኃትን አውጥቶ ይጥላል›› ተብሎ እንደ ተጻፈ (ማቴ. ፳፯፥፶፰፤ ፩ኛዮሐ. ፬፥፲፰)፡፡ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ያመነየተጠመቀ ይድናል፡፡ ያላመነ፣ ያልተጠመቀ ግን ይፈረድበታል›› (ማር. ፲፮፥፮) በማለት በሰጠን ቃል ኪዳን መሠረት በአምላክነቱ አምነን የመንግሥቱ ወራሾች እንኾን ዘንድ ለኒቆዲሞስ ምሥጢሩን እንደ ገለጸ ለእኛም ይግለጽልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የዐቢይ ጾም ሳምንታት (ለሕፃናት) – ክፍል አምስት  

በቴዎድሮስ እሸቱ

መጋቢት ፳፫ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

፯. ኒቆዲሞስ

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች? ደኅና ናችሁ? መልካም! ይኸው ዘወረደ ብለን በመጀመሪያው ሳምንት የጀመርነው ጾም ዛሬ ኒቆዲሞስ ላይ ደርሷል፡፡ ኒቆዲሞስ የሰባተኛው ሳምንት መጠሪያ ነው፡፡ ልጆች! የአይሁድ መምህር የኾነ አንድ ኒቆዲሞስ የሚባል ሰው ነበር፡፡ ይህ የአይሁድ መምህር ማታ ማታ እየመጣ ከጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እግር ሥር ቁጭ ብሎ ትምህርት ይማር ነበር፡፡ ኒቆዲሞስ ማታ ማታ የሚማረው ለምን መሰላችሁ ልጆች?

አንደኛ የአይሁድ መምህር ስለ ኾነ አይሁድ ሲማር እንዳያዩት ነው፡፡ እነርሱ ሲማር ካዩት ገና ሳይማር ነው እንዴ እኛን የሚያስተምረን እንዳይሉት፤ ሁለተኛ አይሁድ በክርስቶስ የሚያምኑ ሰዎችን ከአገራቸው ያባርሩ ስለ ነበር እንዳይባረር በመፍራቱ፤ ሦስተኛ ሌሊት ምንም የሚረብሽና ዐሳብን የሚሰርቅ ጫጫታ ስለሌለ ትምህርቱ እንዲገባው ነበር፡፡ እናንተስ በሌሊት ትምህርታችሁን የምታጠኑት እንዲገባችሁ አይደል ልጆች? በሌሊት ዐሳባችሁ አይበተንም፡፡

ታዲያ አንድ ቀን ማታ ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ሰው ከውኃና ከመንፈስ ካልተወለደ በስተቀር የእግዚአብሔር መንግሥት ሊወርስ አይችልም›› ብሎ ለኒቆዲሞስ ስለ ጥምቀት አስተማረው፡፡ ኒቆዲሞስም ‹‹ሰው ከሸመገለ ካረጀ በኋላ እንዴት ድጋሜ ሊወለድ ይችላል?›› ብሎ ጠየቀው፡፡ ጌታችንም ዳግም ልደት ማለት ሰው በጥምቀት የሚያገኘው የእግዚአብሔር ልጅነት እንደ ኾነ፣ ሰው ተጠምቆ የእግዚአብሔር ልጅ ካልኾነ መንግሥተ ሰማያትን እንደማይወርስ አስተማረው፡፡ ኒቆዲሞስም ስለ ጥምቀት በሚገባ ተረዳ፡፡

ልጆች! በዚህ ሳምንት ከሚነገረው ከዚህ ታሪክ ዅል ጊዜ የእግዚአብሔርን ቃል መማር እንዳለብን፤ ያልገባን ነገር ካለ የቤተ ክርስቲያን አባቶችን ጠይቀን መረዳት እንደሚገባን እንማራለን፡፡ እናንተም እንደ ኒቆዲሞስ ቃለ እግዚአብሔር በመማር እና ስለ እምነታችሁ ያልገባሁን በመጠየቅ በቂ ዕውቀት ልትቀስሙ ይገባችኋል፡፡ ልጆች! ለዛሬ በዚህ ይበቃናል፤ ደኅና ሰንብቱ፡፡

የትሩፋት ሥራ በቆጠር ገድራ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መጋቢት ፳፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

አሁን የምንገኝበት የዐቢይ ጾም ሳምንት ስለ ገብር ኄር (ታማኝ አገልጋይ) እና ገብር ሐካይ (ሰነፍ አገልጋይ) የሚነገርበት ወቅት ነው፡፡ ይኸውም ስለ አገልግሎት ትርፋማነትና ዋጋ የምንማርበት ሳምንት ነው፡፡ በተሰጣቸው መክሊት እጥፍ አትርፈው እንደ ተወደሱት ታማኝ አገልጋዮች እኛ ምእመናንም በሃይማኖት ጸንተን፣ በክርስቲያናዊ ምግባር ጎልምሰን እግዚአብሔር እንደየአቅማችን በሰጠን ልዩ ልዩ ጸጋ ተጠቅመን መንፈሳዊ ትርፍ ካስመዘገብን ከአምላካችን ዘንድ ዋጋ እናገኛለን፡፡ በአንጻሩ በሃይማኖታችን ካልጸናን፣ በክርስቲያዊ ምግባር ካልበረታን፣ ጸጋችንን እንደ ሰነፉ ባርያ ደብቀን መንፈሳዊ ትርፍ ካላስመዘገብን እጣ ፋንታችን ቅጣት ይኾናል፡፡

በምድራዊው ሕይወታችን የተሰጠንን ጸጋ ደብቀን ያለ ምግባር የምንኖር ምእመናን ብዙ የመኾናችንን ያህል፣ ከዚህ በተቃራኒ ደግሞ ከሚበሉት ቈርሰው፣ ከሚጠጡት ቀንሰው፣ ከሚለብሱት ከፍለው ለችግረኞች የሚደርሱ፤ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መፋጠን የሚሽቀዳደሙ፤ በሚጠፋ ገንዘባቸው የማያልፈውን የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ የሚተጉ በጎ አድራጊ ምእመናንም አይታጡም፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን እግዚአብሔር አምላክ በሰጣቸው ልዩ ልዩ ጸጋ ለማትረፍ የተነሡ፣ እንደ ልጅነታቸው ቤተ ክርስቲያን የምትጠብቅባቸውን ክርስቲያናዊ ሓላፊነት ለመወጣት የወሰኑ በጎ አድራጊ ምእመናን በቆጠር ገድራ መካነ ቅዱሳን ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳም በማከናወን ላይ የሚገኙትን አርአያነት ያለው የትሩፋት ሥራ ልናስታውሳችሁ ወደድን፡፡ በመጀመርያም የገዳሙን ታሪክ በአጭሩ እናቀርባለን፤

‹ቆጠር› የሚለው ቃል ቦታውን የመሠረቱት ግለሰብ ስም ሲኾን፣ በጊዜ ሒደት ቃሉ የጎሣ መጠርያ ኾኖ ቀጥሏል፡፡ ‹ገድራ› በአካባቢው ቋንቋ የዛፍ ዓይነትን የሚያመለክት ቃል ነው፡፡ አካባቢው ‹ገድራ› የተሰኘው ዛፍ የሚበዛበት በመኾኑ ቦታው ‹ቆጠር ገድራ› ተብሎ ይጠራል፡፡ አካባቢው በተፈጥሮ ደን የተከበበ ሥፍራ ሲኾን፣ ነዋሪዎቹ ከዚህ ደን ውስጥ ዕፀዋትን እንዳይቆርጡ ቃል ኪዳን ገብተዋል፡፡ ስለዚህም የደኑ ህልውና ተጠብቆ ይኖራል፡፡ የቆጠር ገድራ መካነ ቅዱሳን ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳምም በዚህ ቦታ የተመሠረተ ጥንታዊ ገዳም ነው፡፡ ገዳሙ ከጉራጌ ሀገረ ስብከት መንበረ ጵጵስና ወልቂጤ ከተማ በአምሳ ሁለት ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ ይገኛል፡፡

በዳግማዊ ምኒልክ ዘመነ መንግሥት የነበሩ የአካባቢው ምእመናን ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን ሊያስገነቡ ቦታዎችን መርጠው ዕጣ ሲጥሉ ዕጣው በተደጋጋሚ ‹ይነኹራ› ለተባለው ቦታ ወጣ፡፡ በዚያ ሥፍራም በመድኃኔ ዓለም ስም ቤተ ክርስቲያን አነጹ፡፡ ይህ ቤተ ክርስቲያን በዕድሜ ብዛት በመጎዳቱ በየጊዜው ዕድሳት እየተደረገለት እስከዛሬ ቆይቷል፡፡ በአሁኑ ሰዓትም ለበርካታ ሕዝበ ክርስቲያን አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡ በወቅቱ የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ የነበሩት ብፁዕ አቡነ መልከ ጼዴቅ የዚህን ሕንጻ የመሠረት ድንጋይ ለማስቀመጥ በ፳፻፪ ዓ.ም ወደ ቦታው በሔዱ ጊዜ ‹ቆጠር ገድራ› ከሚባለው ደናማ ሥፍራ ሲደርሱ በቦታው በመማረካቸው ከደኑ ውስጥ ገብተው ‹‹ገዳም ገዳም ሸተተኝ፤ ከዚህ ቦታ አልወጣም›› አሉ፡፡ ከጥቂት ሰዓታት ቆይታ በኋላ ጉዟቸውን ቀጥለው ይነኹራ መድኃኔ ዓለም ደርሰው ትምህርተ ወንጌልና ቃለ ቡራኬ ሰጥተው ‹‹ዛሬ ከዚህ ቦታ ላይ የመሠረት ድንጋይ እንዳኖር እግዚአብሔር አልፈቀደልኝም›› ብለው የመሠረት ድንጋዩን ሳያስቀምጡ ወደ አዲስ አበባ ከተማ ተመለሱ፡፡

በሌላ ጊዜ ከሕዝበ ክርስቲያኑ ጋር ውይይት አካሒደው በዕድሳት መልክ በድጋሜ ከሚታነጸው ይነኹራ መድኃኔ ዓለም በተጨማሪ በቆጠር ገድራም በኪዳነ ምሕረት ስም ቤተ ክርስቲያን እንዲታነጽ አዘዙ፡፡ ብፁዕነታቸው ፍጻሜውን ሳያዩ ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ ቢያርፉም በጥቅምት ወር ፳፻፫ ዓ.ም እርሳቸው በመረጡት ቦታ የመሠረት ድንጋይ ተቀምጦ ነሐሴ ፲፮ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም የቤተ ክርስቲያኑ ቅዳሴ ቤት ከበረ፡፡ በቆጠር ገድራ በአንድ ወቅት በተደረገ ቁፋሮ ሰባት ጥንታውያን የዋሻ ቤተ መቅደሶች፣ ሦስት የሱባዔ መያዣ ቦታዎችና ልዩ ልዩ ንዋያተ ቅድሳት ተገኝተዋል፡፡ ይህም በዚያ ሥፍራ ቀደም ሲል ቤተ ክርስቲያን ታንጾ እንደ ነበር የሚጠቁም ማስረጃ ነው፡፡ በቁፋሮ የተገኙ ሰባቱ የዋሻ ቤተ መቅደሶችም፡- የደብረ ቢዘን ቤተ መቅደስ፣ ቤተ ጎልጎታ፣ ቤተ መድኅን፣ ቤተ ጠበብት፣ ቤተ ኤፍራታ፣ ቤተ ደብረ ብርሃን እና ቤተ ደናግል ይባላሉ፡፡

ከእነዚህ ቤተ መቅደሶች መካከል በቤተ ጎልጎታ የኦሪት መሥዋዕት ይቀርብበት እንደ ነበረ፤ በውስጡም ከወርቅ የተሠራ መሠዊያ እንደ ተገኘና ይህን መሠዊያም በስድስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን በሥፍራው ሲያገለግሉ የነበሩ አባ ማትያስ የተባሉ አባት እንዳይዘረፍ ብለው ቆፈረው እንደ ቀበሩት የአካባቢውን ታሪክ የሚያውቁ አባቶች ይናገራሉ፡፡ የቦታው ታሪክና የንዋያተ ቅድሳቱ ዝርዝርም በቁፋሮው በወጣው ‹ዝንቱ መጽሐፍ ዘአቡነ ማትያስ› በተባለው የብራና መጽሐፍ ተመዝግቦ ይገኛል፡፡ በቁፋሮ የወጡት የወርቅ መሠዊያ፣ የብራና መጻሕፍት፣ ቅዱሳት ሥዕላት፣ እርፈ መስቀል እና ሌሎች ጥንታውያን ንዋያተ ቅድሳት ቤተ መዘክር እስከሚሠራላቸው ድረስ እንዳይጠፉ በምሥጢር እንዲጠበቁ ተደርገዋል፡፡ በዚህ ሥፍራ ከአሁን በፊት ያልወጡና ወደ ፊት በቁፋሮ የሚገኙ ንዋያተ ቅድሳት እንዳሉም ይታመናል፡፡ ከዚሁ ዅሉ ጋርም በገዳሙ የፈለቁት፣ በአምስት ቅዱሳን ማለትም በኪዳነ ምሕረት፣ መጥምቀ መለኮት ዮሐንስ፣ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ እና አባ ማትያስ ስም የተሰየሙት ጠበሎች ለበርካታ ሕሙማን ፈውስ እየሰጡ ተአምራትን እያሳዩ ነው፡፡ በቍጥር ወደ ፳፪ የሚደርሱ የሌላ እምነት ተከታዮችም በገዳሙ ጠበሎች ከሕመማቸው ተፈውሰው፣ የክርስትና ጥምቀትን ተጠምቀው የሥላሴን ልጅነት አግኝተዋል፡፡

ምንጭ፡

  • የማኅበረ ቅዱሳን ኅትመትና ኤሌክትሮኒክስ ሚድያ ዋና ክፍል፤
  • የገዳሙ ሕንጻ አሠሪ ኰሚቴ ያሳተመው በራሪ ወረቀት፤
  • የጉራጌ ዞን ባህል ቱሪዝም እና መንግሥት ኮሚኒኬሽን፡፡
img_0748

መርሐ ግብሩ በጸሎተ ወንጌል ሲከፈት

የዚህ ዅሉ ታሪክ ባለቤት ለኾነችው ቆጠር ገድራ መካነ ቅዱሳን ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳም ደረጃውን የጠበቀ ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን፣ የአብነት ት/ቤት፣ የካህናት ማሠልጠኛ ተቋም እና ቤተ መዘክር ለመሥራት እግዚአብሔር ያስነሣቸው የአካባቢው ተወላጆች ከሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ፈቃድ አግኝተው በመፋጠን ላይ ይገኛሉ፡፡ እነዚህ በጎ አድራጊ ምእመናን ከሀገረ ስብከቱና ወረዳ ቤተ ክህነቱ ጋር በመተባበር ገዳሙን የትምህርትና የልማት ማእከል ለማድረግ እንቅስቃሴ ላይ ናቸው፡፡ የገዳሙን ታሪክ ለትውልድ ለማስተላለፍ ያመች ዘንድ ሰባክያነ ወንጌልንና አስጐብኚዎችን ለመመደብም ታቅዷል፡፡

003

በአጠቃላይ ገዳሙን ወደ ጥንት ስሙና ታሪኩ ለመመለስ የሚደረገው ጥረት ተጠናክሮ ቀጥሏል፡፡ በዚህ መልካም የትሩፋት ሥራም የሕንጻዎቹን ዲዛይን በነጻ በመሥራትና ኰሚቴውን በማስተባበር፣ እንደዚሁም ዓላማውን በማስተዋወቅ ማኅበረ ቅዱሳን ድጋፍ በማድረግ ላይ ሲኾን፣ ማኅበረ ጽዮንም ሌላው አጋር አካል ነው፡፡ ለዚህ መልካም ተግባር የተቋቋመው ሕንጻ አሠሪ ኰሚቴም ለታቀዱት ዘርፈ ብዙ የልማት ሥራዎች ገቢ በማሰባሰብ መንፈሳዊ ተልእኮውን በአግባቡ እየተወጣ ነው፡፡ ኰሚቴው ካከናወናቸው የግንዛቤ ማስጨበጫ እና የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብራት መካከልም የካቲት ፳፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ቦሌ አየር ማረፊያ አካባቢ በሚገኘው ዮድ አቢሲንያ የባህል ምግብ አምባሳደር ያደረገው ልዩ መርሐ ግብር አንዱ ነው፡፡

img_0795

የመርሐ ግብሩ ታዳሚዎች በከፊል

በጸሎተ ወንጌል በተከፈተው በዚህ መርሐ ግብር በካህኑ የተነበበው፣ በዓለ ደብረ ታቦርን የሚመለከተው፣ ‹‹… ሦስት ዳስ እንሥራ …›› የሚለው ኃይለ ቃል የሚገኝበት የወንጌል ክፍል ከገዳሙ የልማት ሥራ ጋር የሚተባበር ምሥጢር አለው (ማቴ. ፲፯፥፩-፬)፡፡

img_0809

መምህር አባ ኤልሳዕ ከደቀ መዛሙርታቸው ጋር ኾነው የአብነት ሥርዓተ ትምህርትን በተግባር ሲያሳዩ

በዕለቱ የገዳሙ አስተዳዳሪ መምህር አባ ኤልሳዕ ከደቀ መዛሙርታቸው ጋር ተገኝተው ንባብ፣ ዜማ፣ ቅኔ፣ የመጻሕፍት ትርጓሜ እና የአቋቋም ሥርዓተ ትምህርትን ለመርሐ ግብሩ ታዳሚዎች በተግባር አሳይተዋል፡፡

img_0757

ዲያቆን ብርሃኑ አድማስ ትምህርተ ወንጌል ሲሰጡ

ዲ/ን ብርሃኑ አድማስም ‹‹የመስጠትና የመቀበል ስሌት›› (ፊልጵ. ፬፥፲-፳) በሚል ኃይለ ቃል ገንዘብንም ኾነ ሌላ ንብረትን ለመንፈሳዊ ዓላማ ማዋል ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚያሰጠውን ልዩ ጸጋና የሚያስገኘውን ጥቅም ቅዱሳት መጻሕፍትን ዋቢ በማድረግ አስተምረዋል፡፡

ቀሲስ ምንዳዬ ብርሃኑ እና መጋቤ ስብሐት ዓለሙ አጋ ደግሞ መዝሙር አቅርበዋል፡፡

img_0753

ቀሲስ ምንዳዬ ብርሃኑ መዝሙር ሲያቀርቡ

img_0779

መጋቤ ስብሐት ዓለሙ አጋ በገና ሲደረድሩ

የመርሐ ግብሩ መሪ ዲ/ን ደረጀ ግርማ በበኩላቸው በበጎ አድራጊ ምእመናን የተጀመረው ይህ ገዳሙን የማሳደግ ሥራ ዓላማው በየጊዜው እየቀዘቀዘ የመጣውን የአብነት ትምህርት ለማስፋፋት፣ ጥንታውያን ቅርሶችን በመጠበቅ ለትውልድ ለማስተላለፍ፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ለማሳደግ እና ስብከተ ወንጌልን በስፋት ለማዳረስ መኾኑን አስገንዝበዋል፡፡

img_0815

የሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ ዲዛይን ተመርቆ ሲከፈት

የገዳሙን ታሪክ የሚያስቃኝ ዘጋቢ ፊልምም ሌላው የመርሐ ግብሩ አካል የነበረ ሲኾን የኰሚቴው ሰብሳቢ እና የዮድ አቢሲንያ የባህል ምግብ አምባሳደር ባለቤት አቶ ትእዛዙ ኮሬ ‹‹የሰማይ አምላክ ያከናውንልናል፤ እኛ በርያዎቹም ተነሥተን እንሠራለን›› በሚል ርእስ በዘገባ መልክ የኰሚቴውን እንቅስቃሴ ለጉባኤው አስረድተዋል፡፡ በዚህ መርሐ ግብር በገዳሙ ሊሠራ የታቀደው ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን፣ ዘመናዊ የአብነት ት/ት ቤት እና የቤተ መዘክር ዲዛይን በአባቶች ቡራኬ ተመርቋል፡፡ በመርሐ ግብሩ የታደሙ ምእመናንም ለዚህ መልካም ሥራ በመሽቀዳደም የሚችሉትን ዅሉ ለማድረግ ቃል ከመግባታቸው ባለፈ በዕለቱ በሚሊዮን የሚቈጠር ገንዘብ ገቢ አድርገዋል፡፡ የሕንጻ ቤተ ክርስቲያኑ ዲዛይን በከፍተኛ መንፈሳዊ ፉክክር በአንድ መቶ ሃያ ሺሕ ብር ጨረታ መሸጡም ብዙዎችን አስደንቋል፡፡ ይህም ሕዝበ ክርስቲያኑ ገንዘቡን ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ለማዋል ያለውን ቍርጠኝነት ያሳያል፡፡

001-copy

ይህን የትሩፋት ሥራ በመደገፍና በማስተባበር የተሳተፉ አካላትን ዅሉ የኰሚቴው ሰብሳቢ አቶ ትእዛዙ ኮሬ በእግዚአብሔር ስም አመስግነው የአካባቢው ተወላጆች ሥራውን ቢጀምሩትም ሓላፊነቱ ግን ለዅላችንም ነውና እያንዳንዱ ምእመን እግዚአብሔር ከሰጠው ገንዘብ ላይ ዐሥራት በማውጣት የገዳሙን ልማት መደገፍ እንደሚገባው አሳስበዋል፡፡ በመቀጠል በዕለቱ የተሰበሰበውን ገንዘብ ያበረከቱ ምእመናንን ሰብሳቢው ካመሰገኑ በኋላ ይህ ገቢ ለታቀደው ልዩ ልዩ ተግባር በቂ ስለማይኾን መላው ሕዝበ ክርስቲያን በያሉበት ርብርብ እንዲያደርጉና የገዳሙን ልማት በጋራ እንዲደግፉ በኰሚቴው አባላት ስም ጥሪ አቅርበዋል፡፡ መርሐ ግብሩም በአባቶች ጸሎት ተፈጽሟል፡፡

img_0774

አቶ ትእዛዙ ኮሬ የኰሚቴውን የሥራ እንቅስቃሴ ሪፖርት ሲያደርጉ

በቆጠር ገድራ መካነ ቅዱሳን ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ገዳም ሊሠራ የታቀደውን መንፈሳዊ ተግባር በገንዘብ፣ በጉልበት፣ በቁሳቁስ ወይም በሐሳብ ለመደገፍ የምትፈልጉ ምእመናን በስልክ ቍጥር፡- 09 11 72 27 93 ወይም 09 21 06 23 82 በመደወል ተጨማሪ መረጃ መጠየቅና ድጋፍ ማድረግ የምትችሉ መኾኑን ኰሜቴው ያሳስባል፡፡ እኛም እንደ ዝግጅት ክፍል የኰሜቴው ሥራና የምእመናኑ ተሳትፎ አርአያነት ያለው፣ ሊበረታታ የሚገባው ተግባር በመኾኑ ይህን መንፈሳዊ እንቅስቃሴ በዚህ መልኩ አስታወስናችሁ፡፡ በመጨረሻም ይህን የትሩፋት ሥራ በመደገፍ የሚጠበቅብንን የልጅነት ድርሻ እንወጣ በማለት መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

በበልበሊት ኢየሱስ ገዳም ዙርያ የተነሣው የእሳት ቃጠሎ ጠፋ

የምዕራፈ ቅዱሳን በልበሊት ኢየሱስ ገዳም ሕንጻ ቤተ ክርስቲያን

በዝግጅት ክፍሉ

መጋቢት ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት በእንሳሮ ወረዳ ቤተ ክህነት በምዕራፈ ቅዱሳን በልበሊት ኢየሱስ አንድነት ገዳም ዙርያ የተነሣው የእሳት ቃጠሎ መጥፋቱን የገዳሙ አበምኔት ገለጹ፡፡

መጋቢት ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከምሽቱ ፲፩ ሰዓት ገደማ በግልጽ ባልታወቀ ምክንያት የተነሣው ይህ የእሳት ቃጠሎ በገዳሙ መነኮሳት፣ በአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን እና በወረዳው የመንግሥት አካላት ጥረት ከሌሊቱ ፭ ሰዓት ገደማ ጠፍቷል፡፡

01

የአካባቢው መልክዐ ምድር

ቃጠሎው በቤተ ክርስቲያኑ ላይ ምንም ዓይነት ጉዳት ባያደርስም በግምት አምስት ሄክታር የደን ሽፋንና ሦስት ሄክታር የአትክልት ቦታ በድምሩ ስምንት ሄክታር የሚኾነውን የገዳሙ መነኮሳት ያለሙትን የገዳሙን ይዞታ ማውደሙን የገዳሙ አበምኔት በኵረ ትጉሃን ቆሞስ አባ ሐረገ ወይን አድማሱ አስታውቀዋል፡፡

ከሥፍራው ያገኘነው መረጃ እንደሚያመለክተው የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ፣ በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አገልጋዮች መጋቢት ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም በገዳሙ ተገኝተው ማኅበረ መነኮሳቱን ያጽናኑ ሲኾን፣ ማኅበረ መነኮሳቱም ተረጋግተው ወደ ቀደመ የጸሎት ተግባራቸው ተመልሰዋል፡፡

?

ገዳሙ ከሁለት መቶ አምሳ በላይ መነኮሳት እና መነኮሳይያት፤ እንደዚሁም ወደ ሁለት መቶ የሚደርሱ የቅኔ፣ የድጓ እና የቅዳሴ ደቀ መዛሙርት የሚገኙበት ሲኾን፣ ገዳሙ የሚተዳደርበት በቂ ገቢ የሌለው ከመኾኑ ባሻገር የአብነት ተማሪዎቹም በመጠለያ እና በምግብ እጥረት ምክንያት ትምህርታቸውን በአግባቡ ለመከታተል ተቸግረዋል፡፡ ‹‹ስለዚህም የገዳሙን ህልውና ለመጠበቅ እና የአብነት ተማሪዎችን ከስደት ለመታደግ መላው ሕዝበ ክርስቲያን ድጋፋችሁ አይለየን›› ሲሉ የገዳሙ አበምኔት በገዳሙና በማኅበረ መነኮሳቱ ስም ጥሪያቸውን አቅርበዋል፡፡

02

ቃጠሎው ያደረሰው ጉዳት በከፊል

ምዕራፈ ቅዱሳን በልበሊት ኢየሱስ አንድነት ገዳም መልክዐ ምድራዊ አቀማመጡ ለጎርፍ አደጋ ተጋላጭ በመኾኑ በየጊዜው በግምት ስድሳ ሄክታር የሚደርስ የገዳሙ ይዞታ በጎርፍ መወሰዱን፤ በአሁኑ ሰዓትም በክልሉ መንግሥት በጀት በገዳሙ ዙርያ የአፈር ጥበቃ ሥራ እየተከናወነ መኾኑን ከገዳሙ ጽ/ቤት ለመረዳት ተችሏል፡፡

መረጃውን ያደረሰን በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ነው፡፡

የተወደዳችሁ ምእመናን! በየጊዜው በገዳሞቻችን ላይ የሚደርሰውን የእሳት ቃጠሎ እና መሰል አደጋ ከፍተኛ ጉዳት ከማድረሱ በፊት ዅላችንም ተግተን፣ ነቅተን ቤተ ክርስቲያናችንን እንጠብቅ ስንል መልእክታችንን እናስተላልፋለን፡፡

እርማት

በዚህ ዜና ሦስተኛው አንቀጽ ላይ ‹… ስምንት ሺሕ ሄክታር …› በሚል የተገለጸው በስሕተት ስለ ኾነ ስምንት ሄክታር› ተብሎ መስተካከሉን ከይቅርታ ጋር ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡

ክርስቲያናዊ ምግባርን ከገብር ኄር እንማር

በዲያቆን አባተ አሰፋ

መጋቢት ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ታላቁን የጌታችንን ጾም ከጀመርን ስድስተኛው ሳምንት ላይ ደርሰናል፡፡ ይህን ሳምንት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ‹ገብር ኄር› የሚል ስያሜ ሰጥታዋለች፡፡ ትርጕሙም ‹በጎ አገልጋይ› ማለት ሲኾን የስያሜውን መነሻ የምናገኘው በዕለቱ ሥርዓተ ቅዳሴ ከሚነበበው የወንጌል ክፍል ነው (ማቴ.፳፭፥፲፬-፴)፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምሳሌ መስሎ ካስተማራቸው ትምህርቶች መካከል አንዱ የኾነው ይህ የወንጌል ክፍል በርካታ መልእክትታን በውስጡ ይዟል፡፡ በቤተ ክርስቲያን በልዩ ልዩ ሓላፊነት ላይ የሚገኙ ሰዎች ትኩረት ሰጡባቸው የሚገቡ ነጥቦችን ይጠቁማል፡፡ ይህን ለመረዳት ያመቸን ዘንድ ከታሪኩ የመጀመርያ ክፍል በመነሣት ዋና ዋና ነጥቦችን መመርመር ጠቃሚ ነው፤

በዚህ ምሳሌያዊው ታሪክ አንድ ጌታ አገልጋዮቹን ጠርቶ ለእያንዳንዳቸው እንደ ችሎታቸው መጠን ለአንዱ አምስት ለአንዱ ሁለት እንዲሁም ለሌላኛው አንድ መክሊት ነግደው ያተርፉበት ዘንድ እንደ ሰጣቸው ተጠቅሷል፡፡ ከታሪኩ እንደምንረዳው የአገልጋዮቹ ጌታ ለመንገድ ቢዘጋጅም ሀብቱ ግን በተዘጋ ቤት ውስጥ ተቆልፎበት እንዲቀመጥ አልፈለገም፡፡ እንዲያተርፉበት ገንዘቡን ለአገልጋዮቹ ሰጥቷቸዋል፡፡ ሰውዬው ማትረፍ በመፈለጉ ብቻም ገንዘቡን ያለ አግባብ አልበተነም፡፡ ለእርሱ ቀረቤታ የነበራቸውን አገልጋዮቹን ጠርቶ እንደየችሎታቸው መጠን እንዲሠሩበት አከፋፈላቸው እንጂ፡፡

ይህ ጌታ ቅንነትና ርኅራኄ የበዛለት እንደ ኾነ የሚያመላክተን ነገር አለ፡፡ ይኸውም ለአገልጋዮቹ ሓላፊነትን ቢሰጥም እንኳን ከእነርሱ ጋር በነበረው ቀረቤታ ማን ምን መሥራት ይችላል የሚለውን ከግምት ውስጥ በማስገባት ለእያንዳንዳቸው እንደ ሓላፊነት የመሸከም አቅማቸው አምስት፣ ሁለት፣ አንድ እያደረገ መስጠቱ ነው፡፡ የዚህ ጌታ መክሊት አሰጣጥ አድልዎ ያለበት ሊመስለን ይችላል፡፡ ታሪኩን እስከ መጨረሻው ብንከታተለው ግን የባለ መክሊቱን ቅንነት እናስተውላለን፡፡

ይህ ጌታ ለአገልጋዮቹ አትርፉበት ብሎ መክሊቱን ሰጥቷቸው በሔደበት አገር አልቀረም፡፡ ይልቁንም እያንዳንዱ በተሰጣቸው መክሊት ምን እንደ ሠሩበት ሊቆጣጠራቸው ተመልሷል፡፡ ስለዚህ አገልጋዮቹ በሰጣቸው መክሊት ምን እንደ ሠሩ እንደሚጠይቃቸው እያወቀ ከአቅማቸው በላይ የኾነ መክሊትን በመስጠት እንዲጨነቁ አልፈለገም፡፡ በተቃራኒው የምናስተውለው ከአእምሯቸው በላይ ሳይኾን ባላቸው ኃይል ተጠቅመው መሥራትና ማትረፍ የሚችሉትን ያህል መክሊት እንደ ሰጣቸው ነው፡፡

ከብዙ ጊዜም በኋላ የእነዚያ አገልጋዮች ጌታ ሊቆጣጠራቸው ሲመጣ አምስት መክሊት ተቀብሎ የነበረው ሌላ አምስት፣ እንደዚሁም ሁለት መክሊት ተቀብሎ የነበረው ሌላ ሁለት መክሊት አትርፈው ከጌታቸው ፊት እንደ ቆሙ፤ ያ ጌታም በእነዚህ አገልጋዮቹ ታማኝነት ተደስቶ ወደ ደስታ ቦታ እንዳስገባቸው እናያለን፡፡ በተቃራኒው ደግሞ ያ አንድ መክሊት ተቀብሎ የነበረው አገልጋይ ያተርፍባት ዘንድ የተሰጠችውን መክሊት ምድርን ቆፍሮ እንደ ቀበረ፤ ከዚህም አልፎ ‹‹ምን አደረግህባት?›› ተብሎ ሲጠየቅ የዐመፅ ንግግር እንደ ተናገረ፤ በዚህ ያዘነው ጌታውም ያን ክፉ አገልጋይ እንዲቀጣ እንዳደረገው እንረዳለን፡፡ በዚህኛው ክፍል ከተጠቀሰው ታሪክ ሦስቱን አካላት ማለት የመክሊቱን ሰጪ ጌታ፣ በጎ የተባሉ አገልጋዮችን፣ ክፉ እና ሰነፍ የተባለውን አገልጋይ በተናጠል እንመልከታቸው፤

የአገልጋዮቹ ጌታ

ይህ ሰው ለገንዘቡ ጠንቃቃ ከመኾኑ ባሻገር በአገልጋዮቹ ላይ ሙሉ ሥልጣን አለው፡፡ ባለ መታዘዙ ምክንያት በክፉው አገልጋይ ላይ የፈረደበትን ፍርድ (ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት፣ በውጪ ወዳለ ጨለማ አውጡት የሚለው) የጌታው ሙሉ ሥልጣን ያሳያል፡፡ ይህ ጌታ ፍርዱ በእውነት ላይ የተመረኮዘ መኾኑንም በተሰጣቸው መክሊት ላተረፉት ሁለቱ አገልጋዮቹ ከሰጣቸውን ክብር መረዳት ይቻላል፡፡

በጎ እና ታማኝ አገልጋዮች

በአገልጋዮቹ ጌታ በጎ አገልጋዮች የተባሉት አምስት መክሊት የተቀበለውና ሁለት መክሊት የተቀበለው ናቸው፡፡ እነዚህ አገልጋዮች በጎ ለመባል ያበቃቸው አስቀድመው ብዙ ቍጥር ያለው መክሊት በመቀበላቸው አይደለም፡፡ ጉዳዩ የመክሊቱ ብዛት ሳይኾን በተሰጣቸው መክሊት መጠን የሚገባቸውን ያህል ደክመው ማትረፍ መቻላቸው ነው፡፡

ክፉና ሰነፍ አገልጋይ

አንድ መክሊት የተቀበለውን አገልጋይ ከሁለቱ አገልጋዮች ያሳነሰውም ከአንድ በላይ መክሊት አለመቀበሉ ሳይኾን በዚያችው በአንዷ መክሊት እንኳን መሥራት አለመቻሉ ነው፡፡ በአጠቃላይ ይህ አገልጋይ ሦስት መሠረታዊ ስሕተት ፈጽሟል፤

የጌታውን ትእዛዝ በቸልተኝነት መመልከቱ የመጀመርያው ስሕተቱ ነው፡፡ ጌታው ለእያንዳንዳቸው እንደ ችሎታቸው ገንዘቡን ሲሰጣቸው አትርፈው እንዲቆዩት ነው፡፡ እንደ አቅማቸው መስጠቱም አቅማቸው በሚፈቅደው የሥራ ደረጃ እንዲሰማሩ በማሰብ ነበር፡፡ ይህ ሰነፍ አገልጋይ ግን ያደረገው ከታዘዘበት ዓላማ በተቃራኒው መልኩ ነው፡፡ ሊሠራበት የሚገባውን መክሊት ቀበረው፡፡ ይህም ለጌታው ትእዛዝ ያለውን ቸልተኝነት ያሳያል፡፡

ሁለተኛው ስሕተቱ ጌታው መክሊቱን በተቆጣጠረው ጊዜ የዐመፅ ቃል መናገሩ ነው፡፡ ጌታው ከሔደበት ቦታ ተመልሶ በተሰጠው መክሊት ምን እንዳደረገ ይህን አገልጋይ ሲጠይቀው፡- «አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፣ ካልበተንህበትም የምትሰበሰብ ጨካኝ ሰው እንደንህ አውቃለሁ፡፡ ስለ ፈራሁም ሔድሁና መክሊትህን በምድር ውስጥ ቀበርሁ፤» ሲል ነበር የመለሰለት፡፡ ይህ ምላሽ ከዐመፃ ባሻገር የሐሰት ቃልም አለበት፡፡ ምክንያቱም እርሱ እንዳለው ጌታው ካልዘራበት የሚያጭድ ካልበተነበት የሚሰበሰብ ጨካኝ ሰው ቢኾን ኖሮ ምንም መክሊት ሳይሰጠው ከነትርፉ ሁለት መክሊቶችን ይጠይቀው ነበር፡፡ ነገር ግን ተጽፎ የምናነበው ትርፉን ከመጠየቅ በፊት አንድ መክሊት ሰጥቶት እንደ ነበረ ነው፡፡ ይህ ማለት ደግሞ አስቀድሞ ገንዘቡን ዘርቶ ነበር ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ይህ ጌታ ዘርቷልና ማጨድ ይገባዋል፤ በትኗልና መሰብሰብም መብቱ ነው፡፡

ሦስተኛው ስሕተቱ ደግሞ ዕድሉን ለሌሎች አለመስጠቱ ሲኾን፣ ይህ አገልጋይ በተሰጠው መክሊት ነግዶ ማትረፍ ቢሳነው እንኳን ዕድሉን ለሌሎች መስጠት ሲገባው መክሊቱን ቆፍሮ ቀብሮታል፡፡ ይህ ሰው የተሰጠው መክሊት በትርፍ ሊመለስ እንደሚገባው ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ ምክንያቱም ገና ሲቀበል ከጌታው የተቀበለው ትእዛዝ ነውና፡፡ ስለዚህ እርሱ መውጣት መውረዱ ቢከብደውም ወጥተው ወርደው ማትረፍ ለሚችሉ ሰዎች አለመስጠቱ ተጨማሪ ጥፋቱ ነው፡፡ ይህን እንዳያደርግ ያሰረው ደግሞ በውስጡ የተቀረፀው የዐመፅ መንፈስ ለመኾኑ ለጌታው የሰጠው ረብ የሌለው ምላሽ ማስረጃችን ነው፡፡

የአገልጋዮቹ ጌታ የእግዚአብሔር ምሳሌ እንደ ኾነ፤ ሦስቱ አገልጋዮች ደግሞ በተለያየ ደረጃ ያሉ ምእመናንን እንደሚወክሉ የቤተ ክርስቲያን መተርጕማን ያስተምራሉ፡፡ ከተጠቀሰው ታሪክ ከምንማራቸው ቁም ነገሮች መካከልም ሁለቱን እንመልከታለን፤

ለእያንዳንዳችን ከእግዚአብሔር የተሰጠን ጸጋ እንዳለ እንረዳበታለን

እግዚአብሔር አምላካችን እያንዳንዳችን በሃይማኖታችን ፍሬ እንድናፈራ ይፈልጋል፡፡ ፍሬ ማፍራት የምንችልበትን ኃይልና ጸጋ ደግሞ እርሱ ይሰጠናል፡፡ ከእግዚአብሔር ዘንድ የተቀበልናቸው ስጦታዎች በቍጥር እጅግ ብዙ ቢኾኑም በዓይነታቸው ግን በሁለት መክፈል እንችላለን፡፡ የመጀመሪያው እያንዳንዱ ክርስቲያን ዳግመኛ በመወለድ ምሥጢር ያገኘው የእግዚአብሔር ልጅነት ጸጋና ከልጅነት ጋር በተያያዘ የሚሰጠን ስጦታ ነው (ዮሐ.፫፥፫)፡፡ ሁለተኛው ደግሞ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድና እንደየአቅማችን ለመንፈሳዊ አገልግሎታችን ማስፈጸሚያ ይኾነን ዘንድ የሚሰጠን ስጦታ ነው፡፡ ለምሳሌ ትንቢት መናገር፣ በልዩ ልዩ ልሳናት መናገር፣ አጋንንትን ማስወጣት፣ ወዘተ. የመሳሰሉት ጸጋዎች (ስጦታዎች) ከዚህኛው ዓይነት ስጦታ የሚመደቡ ናቸው (፩ኛቆሮ.፲፪፥፬)፡፡

በመጀመሪያውም ይኹን በሁለተኛው ዓይነት ስጦታ በእኛ በተቀባዮች ዘንድ ብዙ የሚያሳዝኑ ችግሮች አሉ፡፡ ዳግመኛ በመወለድ ምሥጢር (በጥምቀት የሥላሴን ልጅ መኾን) ስላገኘው የልጅነት ጸጋ የሚያስብና በዚህም የሚደሰት ክርስቲያን ማግኘት አዳጋች ነው፡፡ ለዓመት በዓላት (ለመስቀል ደመራ፣ ለጥምቀት፣ ለፋሲካ፣ ወዘተ) ካልኾነ በስተቀር ክርስትናችን ትዝ የማይለን ክርስቲያኖች ጥቂቶች አይደለንም፡፡ እንደዚሁም ዘመዶቻችን ወይም ራሳችን ከዚህ ዓለም በሞት ስንለይ ካልኾነ በስተቀር በሕይወት ዘመናችን ወደ ቤተ ክርስቲያን ደጅ የማንደርስ ብዙዎች ነን፡፡ እግዚአብሔር ለእኛ የልጅነትን ጸጋ በመስጠቱ ለእኛ ያለውን ጥልቅ ፍቅሩን አሳይቶናል፡፡ ምክንያቱም ልጅነታችን ዋጋ ተከፍሎበታልና፡፡ እንዲሁ በቀላሉ አይደለም ልጆች የተባልነው፡፡

እኛ ልጅነትን እንድንቀበል አምላክ መከራን ተቀብሏል፡፡ የጥምቀታችን ውኃ የፈሰሰውም በጦር ከተወጋው ከጌታች ጎን ነው (ዮሐ.፲፱፥፳፬)፡፡ ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ይኼንን ዅሉ ምሥጢር ሲያመለክት ‹‹የእግዚአብሔር ልጆች ተብለን ልንጠራ አብ እንዴት ያለውን ፍቅር እንደ ሰጠን እዩ፤›› በማለት ያደንቃል (፩ኛ ዮሐ.፫፥፩)፡፡ እኛ ልጆቹ እንኾን ዘንድ እግዚአብሔር ካሳየን የአባትነት ፍቅሩ ባሻገር ልጆቹ በመኾናችን መንግሥቱን እንድንወርስ መፍቀዱም ከአእምሮ በላይ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለገላትያ ምእመናን በላከው መልእክቱ ‹‹እንኪያስ እናንተ ልጆች ናችሁ እንጂ ባሮች አይደላችሁም፡፡ ልጆች ከኾናችሁ በኢየሱስ ክርስቶስ የእግዚአብሔር ወራሾች ናችሁ፤›› በማለት የሚነግረንም ይህንኑ ተስፋ ነው (ገላ.፬፥፯)፡፡

ትልቁ ችግር ተጠማቂው ሰው ይህን የልጅነት ክብር አለመረዳቱ ነው፡፡ የልጅነቴን ክብር ተረድቻለሁ እያለ የሚያወራውም ቢኾን የልጅነቱን መክሊት በልቡናው ውስጥ ቀብሮ አንድም ፍሬ ሳያፈራ ስለ ማንነቱ ለማውራት ቃላት ሲመርጥ ጊዜውን ያባክናል፡፡ አብዛኞቻችን ክርስቲያን የክርስትና እምነት ደጋፊዎች እንጂ ተከታዮች አይደለንም፡፡ የእግዚአብሔር ልጅነት ሊገለጥ የሚገባው ግን በምናሳየው የደጋፊነት (የቲፎዞነት) ስሜት አይደለም፡፡ ደጋፊነት የሚያስፈልገው በጊዜ እና በቦታ ለተወሰነ ያውም ኃላፊ ለኾነ ድርጊት ነው፡፡ ክርስትና ግን በማንኛውም ቦታና ጊዜ ልንኖርበት የሚገባ ዘለዓለማዊ የሕይወት መስመር ነው፡፡ ስለዚህ የመጀመሪያው መክሊታችን ልጅነታችን መኾኑን በሚገባ መረዳት ያስፈልገናል፡፡ በዚህ መክሊታችንም የታዘዝናቸውን ምግባራት ፈጽመን የሚጠበቅብንን ፍሬ ማፍራት አለብን፡፡ ካለዚያ መክሊቱን እንደ ቀበረው ሰው መኾናችን ነው፡፡

እያንዳንዱ ስጦታ እንደሚያስጠይቅ እንገነዘብበታለን

እግዚአብሔር ያለ አንድ ዓላማ በሓላፊነት ለሰዎች ስጦታን አልሰጠም፤ አይሰጥምም፡፡ ማንም ከእግዚአብሔር የተቀበለ ሰው የተሰጠው ስጦታ ለዓላማ ነውና ጥያቄ አለበት፡፡ ጠያቂው ደግሞ የስጦታው ባለቤት ራሱ እግዚአብሔር ነው፡፡ መንጋውን እንዲጠብቁለት ልዩ ልዩ የአገልግሎት ሰጦታዎችን እግዚአብሔር የሰጣቸው አሉ (ዮሐ. ፳፩፥፲፭፤ ገላ. ፩፥፲፭-፲፮)፡፡ ኾኖም ግን የተሰጣቸው ሓላፊነት የሚያስጨንቃቸው፤ ከልባቸው በትሕትና የሚተጉ ክርስቲያኖች የመኖራቸውን ያህል የሚያገለግሉበትን ስጦታ ከእግዚአብሔር መቀበላቸውን፣ ጸጋቸው የሚያስጠይቃቸው መኾኑን የዘነጉና መንገዳቸውን የሳቱም በርካታ ናቸው፡፡

በእግዚአብሔርና በሰዎች መካከል እንደ ድልድይ ኾነው ያገለግሉበት ዘንድ በተሰጣቸው ሥልጣን እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ተግባር የሚፈጽሙ አገልጋዮች ለዚህ ጥሩ ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑን ወደ እግዚአብሔር ከመምራት ይልቅ የነሱ ደጋፊ፣ ስለ ክብራቸው ተሟጋች እንዲኾን፤ እርስበርስ ጎራ እንዲፈጥርና ‹‹የጳውሎስ ነኝ፤ የአጵሎስ ነኝ›› በሚል ከንቱና የማይጠቅም ሐሳብ እንዲከፋፈል የሚያደርጉ ሰባኪዎችም አይታጡም፡፡ በአጠቃላይ ዅላችንም በተሰጠን መክሊት ባለቤቱ ከፊቱ አቁሞ ስለሚጠይቀን ከገብር ኄር ታሪክ በጎ አገልጋይነትን ተምረን፣ በክርስቲያናዊ ምግባር ጸንተን፣ እንደየአቅማችን መልካም ፍሬን ማፍራት ይጠበቅብናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

እንደ ገብር ኄር ታማኝ አገልጋዮች እንኹን

በአያሌው ዘኢየሱስ 

መጋቢት ፲፰ ቀን ፳፻፱ .

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው ለሕዝቡና ለደቀ መዛሙርቱ ትምህርቱን ቃል በቃል ወይም በሰምና ወርቅ ወይም በምሳሌ አስተምሮአቸዋል፡፡ ሲያስተምርም በተለያዩ የሙያ ዘርፎች ላይ የተለያዩ ምሳሌዎችን በማቅረብና ምሥጢሩን በማስረዳት ነበር፡፡ ስለዚህም ቃሉን ለገበሬዎች በዘርና በእንክርዳድ፤ እንደዚሁም በሰናፍጭ ቅንጣት፤ ለእናቶች በእርሾ፤ ለነጋዴዎች በመዝገብና በዕንቍ፤ ለዓሣ አጥማጆች በመረብ፤ ወዘተ. እየሰመሰለ ያስተምራቸው ነበር፡፡ በተመሳሳይ መልኩ በዐሥሩ ቆነጃጅት፤ በሰርግ ቤት፤ በበግና በፍየል፤ ወዘተ. እየመሰለ ስለ መንግሥቱ በስፋት አስተምሯል፡፡ ጌታ ትምህርቱን በምሳሌ ያስተምር የነበረው አስቀድሞ፡- «አፌን በምሳሌ እከፍታለሁ፤ ከቀድሞ ጀምሮ ያለውንም ተምሳሌት እናገራለሁ፤» ተብሎ በነቢዩ ዳዊት እንደ ተነገረ (መዝ.፸፯፥፪)፣ ቃሉን የሚሰሙት ዅሉ ትምህርቱ ሳይገባቸው እየተጠራጠሩ ወደ ቤታቸው እንዳይመለሱና ምሥጢሩ ግልጽ እንዲኾንላቸው ለማድረግ ነበር፡፡

በዐቢይ ጾም ስድስተኛ ሳምንት በቤተ ክርስቲያን የሚቀርበው ንባብ፣ ስብከትና መዝሙር የሚያስረዳን ምሥጢርም ስለ አንድ በጎ እና ታማኝ አገልጋይ በምሳሌ የተነገረውን ትምህርት ነው፡፡ በዚህ የወንጌል ንባብ ውስጥ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመጨረሻው የፍርድ ቀን ሰዎች እንደ ሥራቸው መጠን እንደሚዳኙ በምሳሌ አስተምሯል፡፡ በዚህ ምሳሌ አንድ ጌታ ለሦስት አገልጋዮቹ ለአንዱ አምስት፤ ለአንዱ ሁለት እና ለሌላው ደግሞ አንድ መክሊት ከሰጣቸው በኋላ ነግዱና አትርፉ በማለት እርሱ ወደ ሌላ አገር መሔዱ ተገልጦአል፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለው የመጀመሪያው አገልጋይ በተሰጠው አምስት መክሊት ቆላ ወርዶ፣ ደጋ ወጥቶ ከነገደ በኋላ አምስት ተጨማሪ መክሊቶችን በማትረፍ ዐሥር መክሊት አኖረ፡፡ ሁለተኛውም በተሰጡት አምስት መክሊቶች ከነገደ በኋላ ሌሎች ተጨማሪ ሁለት መክሊቶችን አትርፎ አስቀመጠ፡፡ ሦስተኛው ግን እንደ ሁለቱ አገልጋዮች ሳይወጣና ሳይወርድ፣ ሳይደክምና ሳያተርፍ በአቅሙ መጠን በተሰጠው አንድ መክሊት ሥራ ሳይሠራ መክሊቱን በጉድጓድ ቀበረው፡፡

ይህ ዅሉ ከኾነ በኋላ ለእነዚህ ሦስት ባሪያዎች በመጠን የተለያዩ መክሊቶችን ሰጥቶ ወደ ሩቅ አገር ሔዶ የነበረው ጌታቸው ወደ እነርሱ ተመልሶ መጣ፡፡ ከዚያም እያንዳንዳቸውን በየተራ እየጠራ በተሰጧቸው መክሊቶች ምን እንደ ሠሩ ጠየቃቸው፤ ተቆጣጠራቸው፡፡ በዚህ መሠረት አምስት መክሊቶችን የተቀበለው የመጀመሪያው አገልጋይ በጌታው ፊት ቀርቦ በተሰጡት አምስት መክሊቶች አምስት በማትረፍ ዐሥር መክሊቶችን ለጌታው አስረከበ፡፡ ሁለተኛውም እንዲሁ ሌሎች ሁለት መክሊቶችን አትርፎ አራት መክሊቶች ለጌታው አስረከበ፡፡ በዚህ ጊዜ የእነዚህ ሁለት አገልጋዮች ጌታ በእነርሱ ደስ በመሰኘቱ፡- ‹‹አንተ መልካም፣ በጎ እና ታማኝ ባርያ! በጥቂቱ ታምሃልና በብዙ ስለምሾምህ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› በማለት ሁለቱንም ወደ መንግሥቱ አስገባቸው፡፡

የተሰጠውን አንድ መክሊት ምንም ሥራ ሳይሠራና ሳያተርፍበት ጉድጓድ ውስጥ የቀበረው ሦስተኛው አገልጋይ ግን፡- ‹‹ጌታ ሆይ፣ ካልዘራህበት የምታጭድ፤ ካልበተንህበት የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መኾንህን ስለማውቅና ስለ ፈራሁ መክሊትህን ጉድጓድ ቆፍሬ በመቅበር አቆይቼልሃለሁና እነሆ ተረከበኝ!›› አለው፡፡ በዚህ ጊዜ ንጉሡ እጅግ ተቆጥቶ፡- ‹‹አንተ ክፉና ሐኬተኛ ባርያ! በእርግጥ እንዲህ ዓይነት ሰው መኾኔን ካወቅህ ገንዘቤን ለሚነግዱበት ወይም ለሚለውጡ ሰዎች በመስጠት እንዲያተርፉበት ማድረግና ተመልሼ ስመጣ ከነትርፉ ከእነርሱ መቀበል እችል ነበር፡፡ አንተ ይህን ሳታደርግ ጭራሹኑ በድፍረት እነዚህን በእውነት ላይ ያልተመሠረቱ ክፉ ቃላትን ስለ ተናገርህ ቅጣት ይገባሃል!›› ሲል መለሰለት፡፡ ከዚያም፡– ‹‹ያለውን መክሊት ውሰዱና ዐሥር መክሊት ላተረፈው ጨምሩለት፤ላለው ይሰጠዋል፤ ይበዛለትማል፡፡ ከሌለው ግን ያው ያለው እንኳ ይወሰድበታል፡፡ ስለዚህ የማይጠቅመውን ባሪያ ወደ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ወደ ውጪ አውጡት!›› ብሎ ለወታደሮቹ አሳልፎ ሰጠው፡፡

በዚህ የወንጌል ቃል «ወደ ሌላ አገር የሚሔድ ሰው» ተብሎ የተጠቀሰው ባለጠጋ ቅን ፈራጅ የኾነው የጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምሳሌ ነው፡፡ በምሳሌው ውስጥ የተጠቀሱት አገልጋዮች የሚወክሉት ምእመናንን ወይም እኛን ነው፡፡ መክሊት የተባለው ደግሞ በጎ የሚያሰኘው መልካም ሥራ ነው፡፡ የመጀመሪያዎቹ ሁለት ባሪያዎች ወይም አገልጋዮች ምግባርን ከሃይማኖት ጋር አስተባብረው በያዙ ጻድቃን ይመሰላሉ፤ መክሊቱን ጉድጓድ በመቆፈር የቀበረው ክፉና ሐኬተኛ አገልጋይ ደግሞ ምግባርና ሃይማኖት የሌላቸው ኃጥአን ምሳሌ ነው፡፡

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በአጭር ቁመት፣ በጠባብ ደረት ተወስኖ፣ በመካከላችን ተገኝቶ ወንጌለ መንግሥቱን ከሰበከልን በኋላ ለእያንዳንዳችን አንድ፣ ሁለትና አምስት መክሊቶችን በመስጠት ‹‹ለፍርድ እስከምመጣ ደረስ ነግዳችሁና አትርፋችሁ ጠብቁኝ›› ብሎን በዕርገቱ ወደ ቀደመ ክብሩ ተመልሶ  ሔዷል፡፡ ዅላችንም ከእግዚአብሔር የተለያዩ መክሊቶችን ተቀብለናል፤ እንድንነግድባቸውና እንድናተርፍባቸው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ይህን አስመልክቶ ቃሉን ባስተማረበት መልእክቱ እንዲህ ብሏል፤ ‹‹ለአንዱ ጥበብን መናገር በመንፈስ ይሰጠዋልና፤ ለአንዱም በዚያው መንፈስ ዕውቀትን መናገር ይሰጠዋል፡፡ ለአንዱም በዚያው መንፈስ እምነት፤ ለአንዱም በአንዱ መንፈስ የመፈወስ ስጦታ፤ ለአንዱም ትንቢትን መናገር፤ ለአንዱም መናፍስትን መለየት፤ ለአንዱም በልዩ ዓይነት ልሳን መናገር፤ ለአንዱም በልሳኖች የተነገረውን መተርጐም ይሰጠዋል፡፡ ይህን ዅሉ ግን ያ፣ አንዱ መንፈስ እንደሚፈቅድ ለእያንዳንዱ ለብቻው እያካፈለ ያደርጋል፤» (፩ኛ ቆሮ.፲፪፥፰-፲፩)፡፡

እግዚአብሔር ለልጆቹ የሰጣቸው መክሊት ብዙ ነው፤ ለአንዱ የመስበክ፣ ለሌላው የማስተማር፣ ለሌላው የመቀደስ፣ ለሌላው የመዘመርመ ለሌላው የመባረክ፣ ለሌላው የማገልገል፣ ወዘተ. መክሊቶችን ወይም ልዩ ልዩ ጸጋን ሰጥቶአል፡፡ አንድ ሰው የሚሰጠው አንድ መክሊት ብቻ አይደለም፡፡ ሁለት ወይም ሦስት ወይም ከዚያ በላይ መክሊቶች ሊሰጡት ይችላል፡፡ በፍርድ ቀን ዅሉም ሰው የሚፈረድበትም በተሰጠው መክሊት ትርፍ መሠረት ነው፡፡ በተቀበለው መክሊት የሚያተርፍ ሰው በፍርድ ቀን በኢየሱስ ክርስቶስ፡- ‹‹መልካም፤ አንተ በጎ፣ ታማኝም ባርያ! በጥቂቱ ታምነሃል፤ በብዙም እሾምሃለሁ፡፡ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› የሚል ቃል ይሰማል፡፡ መክሊቱን መሬት ቆፍሮ የሚቀብር አገልጋይ ግን በውጪ ባለው ጨለማ ውስጥ ተጥሎ በዚያ በልቅሶና ጥርስ በማፋጨት እንዲቆይ ይደረጋል፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ተናገረው ዅሉም ከእግዚአብሔር ዘንድ የተለያዩ ስጦታዎችን ወይም መክሊቶችን ተቀብሏል፡፡ ይኹን እንጂ ዅሉም መክሊቱን ቆፍሮ ስለ ቀበረ ለእግዚአብሔር ምንም ሊያተርፍ አልቻለም፡፡ በወንጌል ላይ የተጠቀሰው ክፉና ሐኬተኛ አገልጋይ የተሰጠውን መክሊት ምንም ዓይነት ሥራ ሳይሠራበት ወይም ሳይነግድበት ወይም ሳያተርፍበት በመሬት ውስጥ ቆፍሮ በማስቀመጡና ጌታው ሲመጣ ያለ ትርፍ በማስረከቡ በዚህ ዘመን ከምንገኝ ሰዎች እጅጉን ይሻላል፡፡ ምክንያቱም እኛ መክሊቶቻችንን ጠብቀን በማቆየት ለእግዚአብሔር ማስረከብ እንኳ አልቻልንምና፡፡ ዛሬ መክሊት የተቀበለ ዅሉ መክሊቱን ቀብሯል ወይም ጥሏል ለማለት ያስደፍራል፡፡ አንድ የእግዚአብሔር አገልጋይ በተሰጠው የመቀደስ መክሊት መቀደስ ሲገባው የሚዘፍን ከኾነ መክሊቱን ጥሏል፡፡

አንድ የመዘመር መክሊት የተሰጠው አገልጋይ ለእግዚአብሔር መዘመር ሲገባው የሚዘፍን ወይም ሰዎችን የሚያማ ወይም የሚሳደብ ከኾነ መክሊቱን ጥሏል፡፡ ትክክለኛውን የወንጌል ትምህርት እንዲያስተምርና ሰዎችን በንስሐ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት እንዲያስገባ የማስተማር መክሊት ከኢየሱስ ክርስቶስ የተቀበለ ሰባኬ ወንጌል የኑፋቄ ትምህርት በማስተማር የዋሃንን ወደ ሲኦል የሚመራ ከኾነ መክሊቱን ጥሎታል ወይም አጥፍቶታል እንጂ አልቀበረውም፡፡ በተሰጠው የመባረክ መክሊት ወይም ሥልጣን ምእመናንን መባረክና ኃጢአታቸውን መናዘዝ ሲገባው ለጥንቆላ ሥራ ተቀምጦ እፈርዳለሁ የሚል ከኾነ መክሊት የተባለ ክህነቱን አቃሎአታል፤ አጥፍቷታል እንጂ አልቀበራትም፡፡ በእግዚአብሔር ዐውደ ምሕረት ላይ ወንጌልን መናገር ሲገባው ተራ ወሬ ወይም ፖለቲካ የሚደሰኩር ከኾነ ይህ ሰው መክሊቱን ጥሏል፡፡ ሌሎቹም እንደዚሁ፡፡ ለዚህ ነው በዚህ ዘመን ያለን ሰዎች መክሊቱን ከቀበረው ሰው ያነስን፤ ክፉዎች እና ሐኬተኞች ነን የምንለው፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን በወንጌል እንደ ተነገረለት ለጻድቃን ሊፈርድላቸውና በኃጥአን ሊፈርድባቸው ዳግመኛ ወደ ምድር ይመጣል፡፡ ከፍርዱ በፊት ዅላችንንም በሰጠን መክሊቶች መጠን ይቆጣጠረናል፡፡ ስለዚህም አንድ መክሊት የተሰጠን ሁለትና ከዚያ በላይ፤ ሁለት የተሰጠን ሁለት ወይም ከዚያ በላይ፤ አምስት የተቀበልነውም አምስትና ከዚያም የሚበልጡ መክሊቶችን ማትረፍ ይጠበቅብናል፡፡ ለመኾኑ በተሰጠን መክሊት እኛ ያተረፍነው ምንድር ነው? በዕርቅ ፋንታ ጠብን የምናባብስ ከኾንን በመክሊታችን ሰዎችን አጉድለናል እንጂ ማትረፍ አልቻልንም፡፡ በመመረቅ ፋንታ የምንራገም ከኾንን መክሊታችንን ጥለናል፡፡ በመጸለይ ፋንታ ለመደባደብ የምንጋበዝ ከኾነም የተሰጠንን መክሊት አጥፍተናል፡፡ የገብር ኄርን ሰንበት ዛሬ ስናከብር አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ተገልጦ እያንዳንዳችንን፡- ‹‹ታተርፉበት ዘንድ የሰጠኋችሁን መክሊት እስከነትርፉ አስረክቡኝ!› ቢለን ምንድር ነው የምናስረክበው? ለጥያቄው የምንሰጠውስ ምላሽ ምን የሚል ይኾን?

በወንጌል የተጠቀሰው ያ፣ ሰነፍ አገልጋይ መክሊቱን መቅበሩ ሳያንሰው ለጌታው የሰጠው ክፉ መልስ ለከፍተኛ ቅጣት ዳርጎታል፡፡ ለጌታው፡- «ካልዘራህበት የምታጭድ፤ ካልበተንህበትም የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መኾንህን አውቃለሁ፤» የሚል ምላሽ ነበር የሰጠው፡፡ በዘመናችን ያሉ አንዳንድ ሰዎችም ከዚህ ሰው ጋር የሚመሳሰል ጠባይ አላቸው፤ እነርሱ ስለ እግዚአብሔር ባሕርይ ምንም ነገር ሳያውቁ የእግዚአብሔርን ጠባይና ዕውቀት በእነርሱ የዕውቀት ሚዛን ለመመዘን ይሞክራሉና፡፡ አንድ ክርስቲያን በጠና ሕመም ሲታመም ወይም ከልጆቹ አንዱ በሞት ሲለይበት ወይም ንብረቱ በእሳት ቃጠሎ ሲወድም ይህን አደጋ ያደረሰበት እግዚአብሔር እንደ ኾነ አድርጎ በማሰብ የማይገቡ ቃላትን በእግዚአብሔር ላይ የሚሰነዝሩ ሰዎች አሉ፡፡ እንደ እነዚህ ዓይነት ሰዎች በእግዚአብሔር ህልውና ላይ በመምጣት «እግዚአብሔር ቢኖር ኖሮ ይህ ሕመም ወይም አደጋ በእኔ ላይ አይደርስም ነበር፤» ይላሉ፡፡ ከዚህ በተጨማሪ «እግዚአብሔር እንደዚህ የጨከነብኝ ምን አድርጌው ነው እያሉ እግዚአብሔርን እንደ ሐኬተኛው አገልጋይ ጨካኝ አምላክ የሚያደርጉት ሰዎችም አሉ፡፡

የጻድቁ የኢዮብ ሚስት በእግዚአብሔር ላይ በልቧ ስትሰነዝራቸው የነበሩ ቃላትን ይደግማቸው ዘንድ «እግዚአብሔርን ስደበውና ሙት» በማለት በእርሱ ላይ ልታነሣሣው ሞክራ ነበር፡፡ ነገር ግን «የለም» ወይም «ጨካኝ ነው» ብሎ በድፍረት እግዚአብሔርን መናገር ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ጨለማ የሚያስገባ ክፉ ቃል መኾኑን እናስተውል፡፡ በመሠረቱ ሊነቀፍ ወይም ሊወገዝ ወይም ሊኮነን የሚገባው ሰይጣን እንጂ እግዚአብሔር አይደለም፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ቸር፣ ርኅሩኅ፣ ታጋሽ፣ ይቅር ባይ፣ መዓቱ የራቀ፤ ምሕረቱ የበዛ አምላክ ነው፡፡ እርሱ በዚህ ምድር ላይ ስንኖር ያልዘራነውን የጽድቅ ፍሬ እንድንዘራና እንድናጭድ፤ ያልበተንነውንም መልካም ዘር በመበተን በፍርድ ቀን ምርቱን እንድንሰበስብ የሚፈልግ ጌታ ነው፡፡ እኛ ሠላሳ፣ ስድሳና መቶ ፍሬ በማፍራት የእነዚህ ፍሬዎችን ምርት በመሰብሰብ ሰማያዊ መንግሥቱን እንድንወርስ ይፈልጋል፡፡ እርሱ ለሚያምኑትና ለሚታመኑት ዅሉ ታማኝ ነው፤ የሚያምኑትን የሚክድ ጨካኝ ፈጣሪ አይደለም፡፡ ካልዘራበት የሚያጭድና ካልበተነበት የሚሰበስብ ሰው እንጂ እግዚአብሔር አይደለም፤ ጨካኝ፣ ከሀዲና የማይታመንም ሰው ነው፡፡

ዛሬ እግዚአብሔር በጎ እና ታማኝ አገልጋይ አጥቶአል፡፡ ዛሬ ቤተ ክርስቲያን የሚታመን አገልጋይ አጥታለች፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ፡- «ዅሉ ዐመፁ፤ በአንድነትም ረከሱ፡፡ በጎ ነገርን የሚሠራ የለም፤ አንድም ስንኳ፤» (መዝ ፲፫፥፫) ተብሎ የተነገረው ለዚህ ዘመን አገልጋዮች ነው፡፡ የሰው ልጅ ለእግዚአብሔርና ለቤተ ክርስቲያን ታማኝ አገልጋይ ሊኾን አልቻለም፡፡ ቤተ ክርስቲያን በቃሉ የሚገኝ ሰው ለማግኘት ተቸግራለች፡፡ በጥቂቱ ታምኖ በብዙ ላይ ሊሾም የሚችል ሰው ስለ ጠፋ ቤተ ክርስቲያን ‹‹የሰው ያለህ!›› እያለች ነው፡፡ ለምእመናን መዳንና ወደ እግዚአብሔር መንግሥት መግባት የሚተጉ አገልጋዮች ቍጥር እየቀነሰ ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ አገልጋዮችን በቤተ ክርስቲያን ላይ የሾማቸውና የሚሾማቸው ግን ራሳቸውን፣ ቤተ ክርስቲያንንና መንጋውን ከጥፋት እንዲጠብቁ ነበር (ሐዋ. ፳፥፳፰)፡፡ ሕዝቡን ለመጠበቅ ተሹሞ የሚያጠፋ ጠባቂ ዕድል ፈንታውና ዕጣ ተርታው ትሉ በማያንቀላፋበትና እሳቱ በማይጠፋበት ዘላለማዊ ሲኦል ውስጥ ነው፡፡ ይህን የሚያደርግ አገልጋይ ቅጣቱ ዘላለማዊ መኾኑን ከወዲሁ ሊያውቅ ይገባዋል፡፡

አምላካችን በዳግም ምጽአቱ እስከሚገለጥ ድረስ መንጋውን በመመገብ፣ ውኃ በማጠጣትና በማሳረፍ ፋንታ ለራሱ ብቻ የሚበላና የሚጠግብ፤ የሚጠጣና የሚሰክር፤ የሚያርፍና የሚዝናና ከኾነ እግዚአብሔር ዕድሉን ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ባለበት ጨለማ ውስጥ ያደርግበታል (ማቴ. ፳፬፥፵፭-፶፩)፡፡ ቤተ ክርስቲያንን በተለያያ መልኩ የሚዘርፍና እግዚአብሔርን የሚያሳዝን አገልጋይም ኾነ ተገልጋይ ከዚህ ጠባዩ ሊቆጠብ ይገባዋል፡፡  የቤተ ክርስቲያን አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ መከራ የተቀበለው ለዚህች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ነው፡፡ በጥፊ የተመታው፤ ርኩስ ምራቅ የተተፋበት፤ የእሾኽ አክሊል የተቀዳጀው፤ በአጠቃላይ የተንገላታውና የሞተው ለዚህች ቤተ ክርስቲያንና ለምእመናን ነው፡፡ ስለ ኾነም ካህናትም ምእመናንም በጎ እና ታማኝ አገልጋዮች ልንኾን ይገባናል፡፡

የአምላካችን የእግዚአብሔር አብ ፍቅር፣ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ጸጋ እና የመንፈስ ቅዱስ ኅብረት ከእኛ ጋር ይኹን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ገብር ኄር (ለሕፃናት)

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

መጋቢት ፲፮ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

እንደምን ሰነበታችሁ የተወደዳችሁ ሕፃናት? መልካም! እስከ ዛሬ ድረስ የጠበቀን፣ ለወደፊትም የሚጠብቀን አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር ይመስገን! ልጆች! ስድስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ‹ገብር ኄር› የሚል ስያሜ አለው፡፡ ‹ገብር ኄር› ማለት ‹በጎ፣ ታማኝ አገልጋይ› ማለት ነው፡፡

በዚህ ሳምንት ጸጋን (ተሰጥዎን) በአግባቡ ስለ መጠቀም እና ስለ መንፈሳዊ አገልግሎት የሚያስተምር ቃለ እግዚአብሔር በቤተ ክርስቲያን ይነገራል፡፡ በተጨማሪም ስለ ‹ገብር ሐካይ› ጠባይ የሚያስረዳ ትምህርት ይቀርባል፡፡ ‹ገብር ሐካይ› ማለት ‹ሰነፍ አገልጋይ› ማለት ነው፡፡ የእነዚህን ሰዎች ታሪክም በአጭሩ እናስታውሳችኋለን፤ በማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ ፳፭ ከቍጥር ፲፬ ጀምሮ እንደ ተጻፈው አንድ ሰው አገልጋዮቹን ጠራና ለአንዱ አምስት፤ ለአንዱ ሁለት፤ ለአንዱ ደግሞ አንድ መክሊት ሰጣቸው፡፡ ልጆች! ‹መክሊት› – ብር፣ ዶላር፣ እንደሚባለው ያለ የገንዘብ ዓይነት ነው፡፡

አምስት መክሊት የተቀበለው አገልጋይ ነግዶ፣ ሌላ አምስት መክሊት አትርፎ ዐሥር አድርጎ ለጌታው አቀረበ፡፡ ጌታውም፡- ‹‹አንተ ጎበዝ እና ታማኝ አገልጋይ! በጥቂቱ ታምነሃልና በብዙ እሾምሃለሁ፤ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› አለው፡፡ ሁለት መክሊት የተቀበለውም አትርፎ አራት አድርጎ አቀረበ፡፡ እርሱንም ጌታው፡- ‹‹አንተ ታማኝ አገልጋይ በጥቂቱ ታምነሃልና ወደ ጌታህ ደስታ ግባ!›› አለው፡፡ እርሱ ግን መክሊቱን ቀብሮ አቆየና ጌታው እንዲያስረክብ በጠየቀው ጊዜ፡- ‹‹እነሆ መክሊትህ!›› ብሎ ምንም ሳያተርፍበት መለሰለት፡፡ ጌታውም፡- ‹‹ይህን ክፉና ሰነፍ አገልጋይ እጅ እግሩን አስራችሁ ጨለማና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ሥፍራ ውሰዱት! መክሊቱን ቀሙና ለባለ ዐሥሩ ጨምሩለት!›› ብሎ አዘዘ፡፡ ‹ገብር ሐካይ› የተባለው ይህ መክሊቱን የቀበረው አገልጋይ ነው፡፡

ልጆች! ከእግዚአብሔር ዘንድ የተሰጠንን ጸጋ በአግባቡ ከተጠቀምን ትልቅ ዋጋ እንደምናገኝ፤ ጸጋችንን በአግባቡ ካልተጠቀምን ደግሞ ቅጣት እንደምንቀበል ከዚህ ታሪክ እንማራለን፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን ለእናንተም ስታድጉ በመንፈሳዊው ሕይወታችሁ የጵጵስና፣ የቅስና፣ የዲቁና፣ የሰባኪነት፣ የዘማሪነት፣ ወዘተ. የመሳሰሉ ጸጋዎችን እንደየአቅማችሁ ይሰጣችኋል፡፡ በዓለማዊው ሕይወታችሁ ደግሞ የፓይለትነት፣ የመሐንዲስነት፣ የዶክተርነት፣ የመምህርነት፣ የመንግሥት ሠራተኛነት፣ ወዘተ. ሌላም ዓይነት የሥራ ጸጋ ያድላችኋል፡፡

መንፈሳዊውን ወይም ዓለማዊውን ትምህርታችሁን በርትታችሁ በመማር ካጠናቀቃችሁ በኋላ ከእናንተ ብዙ ሥራ ይጠበቃል፡፡ ስለዚህ ልጆች! በምድር ሕይወታችሁ እንዲባረክ፤ በሰማይም የእግዚአብሔርን መንግሥት እንድትወርሱ እንደ ገብር ኄር የተሰጣችሁን ጸጋ በመጠቀም ቤተሰባችሁን፣ አገራችሁንና ቤተ ክርስቲያናችሁን በቅንነት ማገልገል አለባችሁ፡፡ በጣም ጥሩ ልጆች! ለዛሬው በዚህ ይበቃናል፤ በሌላ ዝግጅት እስከምንገናኝ ድረስ ሰላመ እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር ይኹን! ሳምንቱ መልካም የትምህርት ጊዜ ይኹንላችሁ!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የዐቢይ ጾም ሳምንታት (ለሕፃናት) – ክፍል አራት

፮. ገብር ኄር

በልደት አስፋው

መጋቢት ፲፮ ቀን ፳፻፱ .

ሰላም ናችሁ ልጆች? ባለፈው ዝግጅት ስለ ደብረ ዘይት ተምረናል፡፡ ዛሬ ደግሞ ስለ ‹ገብር ኄር› እንማራለን፡፡ ስድስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት (እሑድ) ‹ገብር ኄር› ይባላል፡፡ ትርጕሙ ‹ታማኝ፣ በጎ፣ ደግ አገልጋይ› ማለት ነው፡፡ ልጆች! አንድ ባለጠጋ አገልጋዮቹ ነግደው እንዲያተርፉበት ለአንዱ አምስት፤ ለሁለተኛው ሁለት፤ ለሦስተኛው አንድ መክሊት ሰጣቸው፡፡ ልጆች! ‹መክሊት› የገንዘብ ስም ነው፡፡

ከዚያ በኋላ አምስት እና ሁለት መክሊት የተቀበሉት ሁለቱ አገልጋዮች በተሰጣቸው መክሊት ነግደው እጥፍ አትርፈው ለባለ ጌታው አስረከቡ፡፡ ስለዚህም ገብር ኄር (ታማኝ አገልጋይ) ተብለው ተመሰገኑ፤ ልዩ ክብርን አገኙ፡፡ አንድ መክሊት የተቀበለው አገልጋይ ግን የተቀበለውን መክሊት ቀብሮ ካቆየ በኋላ ምንም ሳያተርፍበት ለጌታው አስረከበ፡፡ ይህ አገልጋይ ‹ገብር ሐካይ› ይባላል፡፡ ‹ሰነፍ አገልጋይ› ማለት ነው፡፡ በመክሊቱ ባለማትረፉ የተነሣ ቅጣት ተፈርዶበታል፡፡

የማቴዎስ ወንጌል ምዕራፍ ፳፭ ቍጥር ፲፬-፵፮ ያለውን የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ብታነቡት ሙሉ ታሪኩን ታገኙታላችሁ፡፡ ልጆች! ስድስተኛው የዐቢይ ጾም እሑድ ስለ እነዚህ አገልጋዮች እና ስለ መንፈሳዊ አገልግሎት ጥቅም ትምህርት የሚቀርብት ሳምንት በመኾኑ ‹ገብር ኄር› ተብሏል፡፡ እናንተም በተሰጣችሁ ጸጋ ብዙ ምግባር መሥራት አለባችሁ እሺ? መልካም ልጆች! ለዛሬው በዚህ ይበቃናል፡፡ በቀጣይ ደግሞ ስለ ኒቆዲሞስ እንማማራለን፡፡ ሰላመ እግዚአብሔር ከዅላችን ጋር ይኹን!