የማኅበረ ቅዱሳን 10ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ ተጠናቀቀ

ጳጉሜን 5 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

ነሐሴ 30 ቀን 2004 ዓ.ም. የተጀመረው የማኅበረ ቅዱሳን መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ በታቀደለትና በወጣለት መርሐ ግብር መሰረት በማካሔድ ጳጉሜን 2 ቀን 2004 ዓ.ም. ከለሊቱ 9፡00 ስዓት በድምቀት ተጠናቀቀ፡፡

 

ጳጉሜን 2 ቀን 2004 ዓ.ም.  ለሊት በተካሔደው  የጠቅላላ ጉባኤው ቀጣይ ውይይት በቀኑ መርሐ ግብር የአራት ዓመት ስልታዊ እቅድ ረቂቅ ላይ የተካሔደውን የቡድን ውይይት ውጤት በየቡድኖቹ ሰብሳቢዎችና ጸሐፊዎች አማካይነት እንዲቀርቡ በማድረግ በጠቅላላ ጉባኤው ውይይት ተካሒዶበት ጸድቋል፡፡ በቀጣይነትም የማኅበረ ቅዱሳን ዋና ዋና የአገልግሎት ክፍሎች ስለክፍሎቻቸው እንቅስቃሴ ለጠቅላላ ጉባኤው ግንዛቤ የማስጨበጥና አሁን ያሉበትን ደረጃ አቅርበዋል፡፡

 

የ10ኛው መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ አዘጋጅ አብይ ኮሚቴ የተሠጣቸውን ኀላፊነት ለመወጣት ያደረጉት ጥረት፤ ያጋጠሟቸው ችግሮችና ችግሮቹን ለመፍታት ያደረጉት ጥረት ያቀረቡ ሲሆን ዝግጅቱን ለማሳካት የገንዘብ ፤ የቁሳቁስና የሃሳብ ድጋፍ ላደረጉ ድርጅቶችና ግለሰቦች ከፍተኛ ምስጋና በማቅረብ የምስክር ወረቀት ተሰጥቷቸዋል፡፡

 

በመጨረሻም በማኅበሩ መተዳደሪያ ደንብ መሠረት ማኅበሩ በማንኛውም የፖለቲካ  እንቅስቃሴ ጣልቃ የማይገባና የማኅበሩ የሥራ አመራር፤ የሥራ አስፈጻሚ፤ የየማእከላት ሰብሳቢዎች፤ የኤዲቶርያል ቦርድ ጽ/ቤት፤ የኦዲትና ኢንስፔክሽን አገልግሎት ጽ/ቤት፤  መምህራን የማኅበሩ ጋዜጠኖችና የማንኛውም ፖለቲካ ድርጅት አባል እንዳይሆኑ የሚያግደውን መመሪያ በማብራራት ውይይት ተደርጓል፡፡ በአሉባልታ ላይ የተመሰረተውን ውዥንብር ለማጥራት ይመለከታቸዋል የተባሉ የማኅበሩ አባላት ሃሳባቸውንና አቋማቸውን እንዲገልጹ በማድረግ የተፈጠረውን ውዥንብር ለማጥራት ተችሏል፡፡ በዚህም መሠረት ማኅበሩ በመተዳደሪያ ደንቡ ላይ ያጸደቀውን ከፖለቲካና ከፖለቲካ ፓርቲዎች ጋር በተያያዘ ያለውን አቋም ቀድሞ እንደነበረው እንዲቀጥል አጽንቷል፡፡ በመጨረሻም መርሐ ግብሩ እንደዛሬው ለከርሞው ያድርሰን በሚል ዝማሬ ታጅቦ 10ኛው ጠቅላላ ጉባኤ በድምቀት እንደ ተጀመረ በድምቀት ከለሊቱ 9፡00 ስዓት ተጠናቋል፡፡

የሐዋሳ ማእከል በአፍ መፍቻ ቋንቋ ያሠለጠናቸውን ሰባኪያነ ወንጌል አስመረቀ

ጳጉሜን 5 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዳዊት ደስታ


የማኅበረ ቅዱሳን ሐዋሳ ማእከል ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት የገጠር ስብከተ ወንጌል ማስፋፊያ ንዑስ ክፍል በአፍ መፍቻ ቋንቋ ለአንድ ወር ያሠለጠናቸውን ሠልጣኞች ነሐሴ 1 ቀን 2004 ዓ.ም. አስመረቀ፡፡

 

የሲዳማና ቦረና ሊቀ ጳጳስና የቅዱስ ሲኖዶስ አባል ብፁዕ አቡነ ገብርኤል “በሕዝቡ ቋንቋ ባለማስተማራችን በማኅሌት ብቻ በመወሰናችን ቤተ ክርስቲያን የተሰወረች ሆና በዚህ በደቡብ ክፍለ ሀገር ትታያለች፡፡ ይህ ትልቅ ጉድለት ነው፡፡ ለቤተ ክርስቲያናችን የቆመ ማኅበር ማኅበረ ቅዱሳን በየትኛው በኩል ጉድለት እንዳለብን የተገነዘቡ ልጆቻችን ይህንን የሥልጠና መርሐ ግብር መጀመራቸው ያለብንን ጉድለት ይሞላል” በማለት በምረቃው ዕለት መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

የሥልጠናውን ዓላማ አስመልክቶ የሐዋሳ ማእከል የደቡብ ማእከላት ማስተባበሪያ ዋና ሓላፊ አቶ ዘሪሁን ከበደ እንደገለጹት ሥልጠናው በሲዳማ፣ ጌዴኦ፣ አማሮና ቡርጂ ዞኖችና ወረዳዎች ሀገረ ስብከት ሥር ለሚገኙ የገጠር አብያተ ክርስቲያናት በአፍ መፍቻ ቋንቋ የሚሰብኩ ሰባኪያነ ወንጌልን በማሠልጠን በገጠር የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን ለማጠናከር እንደሆነ ገልጸዋል፡፡

 

አያይዘውም ከዚህ ሥልጠና በኋላ ሠልጣኞች የአካባቢውን ቋንቋ በመጠቀም የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን ለማጠናከር፣ የቤተ ክርስቲያን ዶግማ፣ ሥርዓትና ትውፊትን እንዲያስተምሩ፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን በመመሥረት በመምራት በማስተማርና በማጠናከር በአጠቃላይ የጠፉ የቤተ ክርስቲያን ልጆችን አስተምርው የመመለስ ሥራ መሥራት እንዲቻል ለማድረግ እንደሆነ ሓላፊው ገልጸዋል፡፡

 

ሠልጣኞቹ ከሲዳማ፣ ጌዲኦ፣ አማሮና ቡርጂ፣ ጉጂና ቦረና ሀገረ ስብከት የመጡ ሲሆን በስድስት ቋንቋ በተለያዩ ርዕሶች ዙሪያ የሰለጠኑና ቁጥራቸውም 26 እንደሆኑ ተገልጿል፡፡ በዚህ ዓመት ሠልጥነው የተመረቁትን ጨምሮ ማእከሉ ከ1999 ዓ.ም. ጀምሮ ያሠለጠናቸው 201 ሠልጣኖች መድረሳቸውንም ለማወቅ ተችሏል፡፡

ብፁዕነታቸው አዲሱን ዓመት አስመልክቶ ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ሰጡ፡፡

ጳጉሜን 5 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ለመላው ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት ባስተላለፉት መልእክት፡- “የዘመናት ጌታ እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ከዘመነ ዮሐንስ 2004 ዓ.ም. ወደ ዘመነ ማቴዎስ 2005 ዓ.ም. በሰላም አደረሳችሁ፤ ለሚቀጥለውም ዘመን በቸርነቱ ጠብቆ በሰላምና በጤና እንዲያደርሳችሁ ቤተ ክርስቲያናችን ዘወትር ያለ ማቋረጥ ጸሎቷን ወደ ፈጣሪ ታቀርባለች” ካሉ በኋላ ሁሉም ኅብረተሰብ መልካም ታሪክን ለማስመዝገብ በተሰለፈበት ዓላማ የሚጠበቅበትን ድርሻ ማበርከት እንደሚገባው አሳስበዋል፡፡

የመግለጫውን ሙሉ ቃል ከዚህ በታች ያንብቡ፡፡

 

New year

አዲስ ዓመት

ጳጉሜን 5 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዳዊት ደስታ

ኢትዮጵያ የወራት ሁሉ መጀመሪያ መስከረም ነው፡፡ ይህ ወር ዘመን መለወጫ፣ ዕንቁጣጣሽ፣ ቅዱስ ዮሐንስ እየተባለ ይጠራል፡፡ ስለ አዲስ ዓመት በተለያየ ስም የመጠራቱ ታሪካዊ አመጣጥና ስያሜ መነሻ አሳቡ ምን እንደሆነ እንደሚከተለው እንመለከታለን፡፡

 

ዘመን መለወጫ

ዘመን መለወጫ መስከረም ወር የሆነበት ምክንያት “ብርሃናት /ፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ከዋክብት/ የዓመት ዑደታቸውን በጳጉሜ ወር ጨርሰው በመስከረም ወር ስለሚጀምሩ ነው፡፡ ሌሊቱ ከቀኑ ጋር ይተካከላል፡፡ ዓመቱን ጠንቅቀው ቢቆጥሩ 364 ቀናት ይሆናል፡፡ “ሌሊቱም ከቀኑ ጋራ ይተካከላል፡፡ ዓመቱም ጠንቅቆ ቢቆጥሩት ሦስት መቶ ስልሳ አራት ቀን ይሆናል፡፡ /ሄኖክ.26፥44/ “ዘመናችንን እንደ ቀድሞ አድሱ” /ሰ.ኤር.5፥21/ እንዲል፡፡

በዘመነ ኖኅ ዓለምን ንፍር ውኃ አጥለቅልቆት ከቆየ በኋላ ዳግመኛ ውኃው የጎደለበት በመሆኑ /ኩፋሌ 7፥1/ “በመጀመሪያው ወር መባቻም ምድር ታየች” እንዲል፡፡

 

ዕንቁጣጣሽ

ዕንቁጣጣሽ የተባለበት ምክንያት አንደኛ “ዕንቁ – ዕፅ አመጣሽ” ብሎ የአበባውን መፈንዳት ያመለክታል፡፡ ሁለተኛ ኖኅ ለሦስቱ ልጆቹ አህጉራትን በእጣ ሲያካፍላቸው አፍሪካ ለካም ደረሰችው፡፡ በአፍሪካ ምድርም ሲገባ በመጀመሪያ ያረፈው በኢትዮጵያ ነበር፡፡ ሀገሪቱም በአደይ አበባ አሸብርቃ ነበር፡፡ ወሩ ወርኀ መስከረም በመሆኑ ደስ ብሎት ዕንቁ ዕጣ ወጣሽልኝ ይህችን ወቅት እንቁጣጣሽ ብሏታል፡፡ ሦስተኛው /1ነገ.10፥1-10/ ኢትዮጵያዊቷ ንግሥት ሣባ /አዜብ የንጉሡን ጥበብ ከመስማት ማየትን መርጣ ወደ ንጉሥ ሰሎሞን ከብዙ ሠራዊቶቿ ጋር የእጅ መንሻ በመያዝ ሄደች፡፡ ንጉሡም በደስታ ተቀብሎ እርሱም “እንቁ ለጣትሽ ጌጥ ይሁንሽ” በማለት አራት አይነት ቀለም የሚታይበት በቀንና በሌሊት የምታበራ ቀለበት ሰጥቷታል፡፡ ወሩም ወርኀ መስከረም ነበር፡፡ ከዚህ በመነሣት እንቁጣጣሽ የሚለው ስያሜ ወጥቷል፡፡

 

ቅዱስ ዮሐንስ

ሦስተኛው የአዲስ ዘመን ስያሜ ቅዱስ ዮሐንስ ነው፡፡ የመጥምቁ ዮሐንስ ተግባር ለዘመነ ወንጌል በር ወይም መነሻ እንዲሆን ለኢትዮጵያ ዐውደ ዓመት መስከረም አንድ ቀን እንዲከበር አባቶች ወስነዋል፡፡ /ድርሳነ ዮሐንስ አፈወርቅ ገጽ 1-3/ መጽሐፈ ስንክሳር “የመስከረም ወር የተባረከ ነው፡፡ እርሱም የግብጽና የኢትዮጵያ ዓመቶች መጀመሪያ ነው፡፡ የዚህ ወር ቀኑና ሌሊቱ እኩል 12 ሰዓት ነው፡፡ ከዚህ በኋላ ቀኑ እየጎደለ ይሄዳል” እንዲል፡፡

 

በአጠቃላይ ዘመን መለወጫ ከላይ ባየናቸው የተለያየ ስያሜ ይጠራ እንጂ ዘመኑ አዲስ እየተባለ ቢጠራም አዲስ መሆን ያለበት ወርና ወቅቱ ብቻ ሳይሆን የእኛ የክርስቲያኖች ሥርዓት ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰውነታችሁን አታርክሱ የእግዚአብሔር ማደሪያ ነውና እያለ በመዋዕለ ሥጋዌው ያስተምር ነበር፡፡ አዲስ ዓመት ሲመጣ በኀጥያት፣ በተንኮል፣ በክፋት የቆሸሸው ሰውነታችን በንስሓ፣ በቅዱስ ቊርባን፣ በመልካም ተግባር አዲስ ልናደርገው ይገባናል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን የሥራ አመራር ጉባኤ ምርጫ አካሄደ

ጳጉሜን 2 ቀን 2004 ዓ.ም

በእንዳለ ደምስስ

ከነሐሴ 30 ቀን 2004 ዓ.ም. ጀምሮ እየተካሄደ የሚገኘው የማኅበረ ቅዱሳን 10ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ በመጠናቀቅ ላይ ነው፡፡

1-2004

ጳጉሜን 1 ቀን 2004 ዓ.ም. ጠዋት በተካሄደው የጠቅላላ ጉባኤው ስብሰባ “በማኅበረ ቅዱሳን የአገልግሎት ጉዞ የአባላት ተሳትፎና የወደፊት ሁኔታ” በተመለከተ ጥናት የቀረበ ሲሆን በአባላት ሰፋ ያለ ውይይት ተካሂዷል፡፡ ከሰዓት በኋላ በቀጠለው ስብሰባም “ስልታዊ ለውጥ ለሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን እድገት ከማኅበረ ቅዱሳን ተልእኮና አቅም አንጻር” በሚል በዲ/ን ያረጋል አበጋዝና ዲ/ን ብርሃኑ አድማስ ጥናታዊ ጽሑፍ ቀርቦ በአባላት ውይይት ተደርጎበታል፡፡ በመጨረሻም የጽ/ቤት ግንባታ ሪፓርት ቀርቦ የመርሐ ግብሩ ፍጸሜ ሆኗል፡፡

 

ምሽት ላይ ጠቅላላ ጉባኤው በዋነኛነት ሁለት ጉዳዮች ላይ ትኩረት በማድረግ የተወያየ ሲሆን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል እያከናወነ ያለውን ዘርፈ ብዙ ተግባራት የተገለጸ ሲሆን ክፍሉም በገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች ጋር በተያያዘ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ላበረከቱ ማእከላት የማበረታቻ ሽልማት ከ19500 ብር በላይ አበርክቷል፡፡

3-2004

በቀጣይነት በጠቅላላ ጉባኤው የተሰየመውና ማኅበሩን ለአራት ዓመታት ሊመሩ የሚችሉ የሥራ አመራር አባላትን እንዲያቀርብ የተሰየመው አስመራጭ ኮሚቴ ማኅበሩን ሊመሩ ይችላሉ ያላቸውን አባላት ለጠቅላላ ጉባኤው አቅርቦ በአባላቱ ሰፊ ውይይትና ግምገማ በማድረግ ከ39 እጩዎች መካከል 20 እጩዎችን ለጳጉሜን 2 ቀን 2004 ዓ.ም. ምርጫ እንዲቀርቡ አጽድቋል፡፡ ከ20ዎቹ አጩዎች መካከል የማኅበረ ቅዱሳን የጠቅላላ ጉባኤ የምርጫ ሥነ ሥርዓት ደንብ  አንቀጽ 8 ቁጥር 3 ንዑስ ፊደል ለ በሚያዘው መሠረት ከ20ዎቹ እጩዎች ጸሎት ተደርጎ በእጣ በመለየት 17ቱ የሚመረጡ ይሆናሉ፡፡

 

ጳጉሜን 2 ቀን 2004 ዓ.ም. ጠዋት በተያዘው መርሐ ግብር መሠረት “የማኅበረ ቅዱሳን የአራት ዓመት ስልታዊ እቅድ ረቂቅ ለጠቅላላ ጉባኤው ቀርቧል፡፡ ኮሚቴው በዋነኛነት የማኅበሩ ርዕይ፣ ተልእኮና የማኅበሩ እሴቶች ፤የማኅበሩ ጥንካሬና ድክመቶች፣ መልካም አጋጣሚዎችና ስጋቶች እንዲሁም የማኅበሩ የውስጥ ጉዳዮችና ስትራቴጂያዊ ግቦችን በማካተት አቅርቧል፡፡

 

በተጨማሪም የማኅበሩ ቀጣይ አራት ዓመታት ወሳኝ ጉዳዮችና ግቦች ያሏቸውን የማኅበሩ ተቋማዊ አቅም ማሳደግ፣ የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊ አገልግሎት እንዲያድግ ማድረግ፣ የግቢ ጉባኤያት ተደራሽነትና ብቃት ማሳደግ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ዝግጁ ማድረግ፣ የአብነት ት/ቤቶችና ገዳማት ድጋፍ ቀጣይ የቤተ ክርስቲያን ችግር በሚፈታ መልኩ ማድረግ፣ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ለሁሉም ተደራሽ ማድረግ ዘላቂነቱን ማረጋገጥ በሚሉ ወሳኝ ጉዳዮች ላይ ሰፋ ያሉ ነጥቦች ቀርበዋል፡፡ በእያንዳንዳቸው ዋና ዋና ጉዳዮችም የአፈጻጸም ስልቶችን አስቀምጧል፡፡

 

ኮሚቴው የአራት ዓመት ስልታዊ እቅዱን ካቀረበ በኋላ ለአባላት በስልታዊ እቅድ ረቂቅ ላይ መካተት ነበረባቸው ያሏቸውን እንዲያቀርቡ በተጠየቀው መሠረት ማየትና መስማት የተሳናቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆችን ተጠቃሚ እንዲሆኑ በስልታዊ ረቂቅ አቅዱ ውስጥ እንዲካተት ጥያቄ ቀርቧል፡፡ በመቀጠልም አባላት በቡድን በመከፋፈል ውይይት አድርገዋል፡፡

 

ከሰዓት በኋላ በነበረው መርሐ ግብርም የመተዳደሪያ ደንብ ማሻሻያው ለጠቅላላ ጉባኤው ቀርቧል፡፡ ኮሚቴው ባቀረበው የማሻሻያ ረቂቅ መሠረት በመተዳደሪያ ደንቡ ሊሻሻሉ የሚገባቸው ያላቸውን በማሻሻል፣ መውጣት ያለባቸውን በማስወጣትና አዲስ መግባት አለባቸው ብሎ ያመነባቸውን በማካተት ያቀረበ ሲሆን የጠቅላላ ጉባኤው አባላት ያላቸውን አስተያየትና ማሻሻያ    በጽሑፍ ለኮሚቴው እንዲያቀርቡ ተደርጓል፡፡

2-2004

በመጨረሻም ማኅበሩን ለቀጣይ አራት ዓመታት  የሚመሩ የሥራ አመራር ጉባኤ ምርጫ ተካሒዷል፡፡ በዚህም መሠረት በእጩነት ከቀረቡት 20 እጩዎች መካከል በብፁዐን አባቶች ፀሎት ከተደረገ በኋላ በእጣ 17ቱ ተመርጠዋል፡፡ 3ቱ ደግሞ በተጠባባቂነት ተሰይመዋል፡፡

በዚህም መሠረት ፡

ቀሲስ ዶ/ር ሰሙ ምትኩ ሰብሳቢ

ወ/ሪት ዳግማዊት ኃይሌ ምክትል ሰብሳቢ

ዲ/ን ሙሉዓለም ካሳ ፀሐፊ ሆነው ተመርጠዋል፡፡

 

በተጨማሪም የኤዲቶሪያል ቦርድ፤ ኦዲትና ኢንስፔክሽን በኀላፊነት የሚመሩ አባላት የተመረጡ ሲሆን አዲሱ የሥራ አመራር ኮሚቴ የሥራ አስፈጻሚ አባላትን ለጠቅላላ ጉባኤ አቅርበው አጸድቀዋል፡፡

 

ጉባኤው ምሽቱን እንደሚቀጥልና ሌሎች ማኅበሩን የሚጠቅሙ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ በማሳለፍ እንደሚጠናቀቅ ይጠበቃል፡፡

መልአከ ሰላም ወጥኢና

ጳጉሜን 2 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

Kiduse Rufyele

ጳጉሜን፡- “ጭማሪ፣ ተወሳክ፣ አምስት ቀን ተሩብ” የሚል ትርጉም አለው፡፡ ጳጉሜን 13ኛ ወር ትባል እንጂ በውስጧ የያዘቻቸው ቀናት ቁጥር በአንድ ሳምንት ካሉ ቀናት ያነሱ ናቸው፡፡ እንደዚያም ሆኖ ኢትዮጵያን ብቸኛዋ የዓለማችን ባለ 13 ወራት ሀገር እንድትሆን ያስቻለች ልዩ ወር ናት፡- ወርኀ ጳጉሜን፡፡

 

ጳጉሜን ገዝፋና ጎልታ የምትታየው በመንፈሳዊ  ዓለም ነው ማለት ይቻላል፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የዓለም ፍጻሜ መታሰቢያ ተደርጋ ትታሰባለች፡፡ በዚህ የተነሣ በርካታ የቤተ ክርስቲያኒቱ ተከታዮች ወርኀ ጳጉሜን በጾምና በጸሎት /በሱባኤ/ ያሳልፏታል፡፡ በተለይም እንደ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ በቅዱስ ሩፋኤል ዕለት ሰማያት የሚከፈቱበት /ተርኅዎ ሰማይ/ መሆኑን በማመን ምእመናን ወደ ፈፍላጋት በመሄድ እንዲሁም በጳጉሜን ቀናት በሚዘንበው ዝናብ በመጠመቅና በረከትን ይሻሉ፡፡ ጸሎታቸውንም ከምንገባም በበለጠ ያቀርባሉ፡፡

 

ወርኀ ጳጉሜን የጌታችን ምጽአት የሚታሰብባት በመሆኗ የሚዘመረው መዝሙር፣ የሚነበቡ ምንባባትና ቅዱስ ወንጌሉ እንዲሁም የሚሰበከው ምስባክ ይህንኑ የሚያሳዩ ናቸው፡፡ ከነዚህም ውስጥ፡-

 

“ከመ ንተ መብረቅ ዘይወፅእ እምጽባሕ ወያስተርኢ እስከ አረብ ከማሁ ምጽአቱ ለወልደ እግዚአብሔር ምስለ ኀይለ ሰማያት በንጥረ መባርቅት/ከ/ ምስለ አላፍ መላእክት /ከ/ ወኲሎሙ ሊቃነ መላእክት /ከ/ አክሊለ አክሊላት ዲበ ርእሶሙ” ይህም ማለት፡-


“መብረቅ ከምሥራቅ ወጥቶ እስከ ምዕራብ እንዲታይ በመባርቅት ፍጥነት፡ – ሰማያውያን ኀይላት ከብዙ መላእክትና የመላእክት አለቆች ጋር በካህናት ራስ ላይ ያሉት አክሊሎች መገኛ የሆነው የሾህ አክሊል ደፍቶ የእግዚአብሔር ልጅ እንዲሁ ይመጣል” ማለት ነው፡፡

 

በየዓመቱ ጳጉሜን ሦስት ቀን የሊቀ መላእክት የቅዱስ ሩፋኤል ዓመታዊ ክብረ በዓልም በመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት፣ በልዩ ልዩ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ይከበራል፡፡ ይህም ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል ከከበሩት ቅዱሳን መላእክት ሦስተኛው ነው፡፡ መጽሐፍ፡-  “ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ” እንዲል፡፡ /ጦቢት 12፥15/

 

መላእክት ሲፈጠሩ የማይሞቱ፣ የማይራቡ፣ ጾታ የሌላቸው ዝንተ ዓለም በቅድስና ጸንተው እንዲያገለግሉና ፈጻምያነ ፈቃድ እንዲሆኑ ነው፡፡ በዚሁ መሠረት ከአንዱ ዲያብሎስና ከተከታዮቹ አጋንንት በቀር ቅዱሳን መላእክት ሁሉ በተፈጠሩበት ዓላማ ጸንተው ያሉና የሚኖሩ ናቸው፡፡ በዚሁ አገልግሎታቸውም የእግዚአብሔርንና የሰውን በጎ ፈቃድ ሲፈጽሙ ይኖራሉ፡፡ ያለማቋረጥ ፈጣሪያቸውን ልዑል እግዚአብሔርን ከሚያመሰግኑ ቅዱሳን መላእክት አንዱ መልአከ ጥኢና ወሰላም /የሰላምና የጤና መልአክ/ የሚባለው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡

 

“ሩፋኤል” የሚለው የስሙ ትርጓሜ ደስ የሚያሰኝ፣ ቸር፣ መሐሪ፣ ቅን የዋህ ማለት ነው፡፡

በሰውነታችን ላይ የሚወጣውን ደዌም ሆነ ቁስል ይፈወስ ዘንድ ከልዑል እግዚአብሔር ሥልጣን ተሰጥቶታል፡፡ “በሰው ቁስል ላይ የተሾመ ከከበሩ መላእክት አንዱ ቅዱስ ሩፋኤል ነው” መጽሐፈ ሄኖክ 6፥3 ይላል፡፡ ለቆሰሉ ፈውስን የሚያሰጣቸው ለማሕጸን ችግር ሁሉ ለሴቶች እረዳታቸው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡ ሴት በፀነሰችበት ወቅት ቅዱስ ሩፋኤል አይለያትም ሕፃኑ አርባ ቀን ሞልቶት፣ በማሕፀን እያለ “ተስእሎተ መልክዕ” /በሥላሴ አርአያ መልኩ መሳል ከጀመረበት ቀን አንሥቶ እስከሚወለድበት ቀን ድረስ/ ቅዱስ ሩፋኤል አይለየውም፡፡ በወሊዳቸው ቀን ሴቶች ከሚደርስባቸው ጭንቀትና ሕመም ስሙን ጠርተው ይማጸኑታል፡፡ ፈታሔ ማሕፀን ነውና ቅዱስ ሩፋኤልም ጭንቀታቸውን ያቀላል፡፡

 

ቅዱስ ሩፋኤል በሰውነት ያለን ረቂቅ ርኩስ መንፈስ ያውቃል፡፡ አስማንድዮስ የተባለ ጋኔን በወለተ ራጉኤል ጭን ላይ አድሮ ባሎቿን እየገደለ ቢያሰቃያት ቅዱስ ሩፋኤል ጋኔኑን አስጨንቆ አስወጥቶላታል፡፡ /ጦቢት.3፥8-17/

 

“ዳግመኛም እግዚአብሔር ሩፋኤልን፣ አዛዝኤልን እጁን እግሩን አስረህ በጨለማ ውስጥ ጣለው አለው” /ሄኖክ 3፥5-7/ በዚህ መሠረት ለቃየን ልጆች ሰይፍና ሾተል መሥራትን፣ የምንዝር ጌጥ ማጌጥን፣ መቀንደብን ያስተማረ አዛዝኤል የተባለውን ጋኔን በእሳት ሰይፍ እየቀጣ በረቂቅ አስሮ ወደ ጥልቁ የጣለው ይኸው መልአክ ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡ /ሄኖክ፤2፥18/ የሰው ልጆች ከተያዙበት የኀጢአት ቁስል ይፈወሱ ዘንድ በአማላጅነቱና በጸሎቱ የማይለይ መልአክ ነው፡፡ “በበሽታ ሁሉ ላይ በሰው ልጆችም ቁስል ላይ የተሾመው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡” በማለት ሄኖክ ከእግዚአብሔር መልአክ ያገኘውን የምስክርነት ቃል ጽፏል፡፡ /ሄኖክ.10፥13/

 

የጦቢትን ልጁ ጦቢያን በሰው አምሳል ተገልጦ ከተራዳው በኋላ ወደ ሰማይ በሚያርግበት ጊዜ ራሱን ሲገልጥ “የቅዱሳንን ጸሎት ከሚያሳርጉ ወደ ከበረ ወደገነነ ወደ እግዚአብሔር ጌትነትም ከሚያገቡ ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ አላቸው” /ጦቢት.12፥15/

 

የቅዱስ ሩፋኤል በዓሉ የሚከበርባቸው ምክንያቶችም ሁለት ናቸው፡፡ እነርሱም አንደኛው በዓለ ሢመቱን ምክንያት በማድረግ ሲሆን ሁለተኛው የቅዳሴ ቤቱ የተከበረበት ስለሆነ ነው፡፡ ይኸውም በመጽሐፈ ስንክሳር እንዲህ ተመዝግቧል፡፡ ከእስክንድርያ አቅራቢያ በምትገኝ በደሴት የታነጸች ቤተ ክርስቲያኑ በከበረ ሊቀ ጳጳሳት ቴዎፍሎስ ዘመን በውስጧ ተአምር የተገለጸባት የከበረችበት ነው፡፡

 

ይህም እንዲህ ነው፤ ሀብትም ሴት ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ቴዎፍሎስ መጥታ ሳለ ከእርሷ ጋርም ብዙ ሰው ነበረ፡፡ ከባሏም የወረሰችው ብዙ ገንዘብ አላት፡፡ በሊቀ ጳጳሳቱ ቤት አንጻር ያለውን ኮረብታ አስቆፈረችው በዚያም የወርቅ መዝገብ ተገለጠ፡፡ በዚያም ወርቅ ብዙዎች አብያተ ክርስቲያናትን አነፀ፤ ከእርሳቸውም አንዲቱ የመላአክት አለቃ በሆነ በከበረ መልአክ ቅዱስ ሩፋኤል በስሙ የታነፀች ይህች ናት፡፡ ሥራዋንም በፈጸመ ጊዜ እንደዛሬው በዚች ቀን አከበራት፡፡ ብዙ ምእመናንም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እያሉ ቤተ ክርስቲያኒቱ ፈጽማ ተናወጸች፤ ያቺ ደሴት በታላቅ አንበሪ ጀርባ ላይ የቆመች ናትና፡፡ የሰዎች ብዛትም በከበደው ጊዜ ቤተ ክርስቲያኒቱን ያፈርሳት ዘንድ ሰይጣን አነሣሣው፡፡ ወደ ክብር ባለቤት እግዚአብሔርም በከበረ መልአክ ሩፋኤል ስም ጮሁ፡፡ ያን ጊዜ ይህ የከበረ ሩፋኤል ያንን አንበሪ በጦሩ ወግቶ እንዲህ አለው “እግዚአብሔር አዝዞሃልና ከቦታህ ሳትናወጽ ጸጥ ብለህ ቁም!” አንበሪውም ጸጥ ብሎ ቆመ፡፡ አልታወከም፡፡ በውስጧም ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ ለሕሙማንም ፈውስ ሆነ” ይላል፡፡

 

በቀኖና ቤተ ክርስቲያን በወርኀ ጳጉሜን ከሚታሰቡት እና ከሚከበሩት በዓላት መካከል ጳጉሜን 2 ቀን የሐዋርያው ቅዱስ ቲቶ በዓለ ዕረፍቱ፣ እንዲሁም ጳጉሜን 5 ቀን የነቢዩ አሞጽ ዕረፍት ይጠቀሳሉ፡፡

 

ፈጣሪያችን ከሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል እና ከቅዱሳኑ በረከት ረድኤት ያሳትፈን፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን 10ኛ መደበኛ ጠቅላላ ጉባኤ ተጀመረ

ጳጉሜ 1 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

gubaye 2የማኅበረ ቅዱሳን 10ኛ ጠቅላላ ጉባኤ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሽ ብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነት፤ የመምሪያ ሓላፊዎች፤ ቀሳውስትና ካህናት፤ በሬዴራል ጉዳዮች የሃይማኖት ተወካዮች ነሐሴ 30 ቀን 2004 ዓ.ም. ተጀምሯል፡፡

 

በዋዜማው ነሐሴ 29 ቀን 2004 ዓ.ም. ከተለያዩ የሀገሪቱ አካባቢዎች የመጡ የማኅበሩ አባላት ከምሽቱ 12፤00 ስዓት ጀምሮ የጠቅላላ ጉባኤው አስተባባሪ ኮሚቴ ባዘጋጀው ትራንስፖርት ከማኅበሩ ዋናው ማእከል አቧሬ ወደሚገኘው አቡነ ጎርጎርዮስ የትምህርትና ሥልጠና ማእከል በመጓዝ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልእክት፤ የመርሐ ግብር ትውውቅ፤  ሕጽበተ እግርና የእራት መርሐ ግብር ተከናውኗል፡፡

 

gubaye 6ነሐሴ 30 ቀን 2004 ዓ.ም. ጠዋት የማኅበረ ቅዱሳን 10ኛ ጠቅላላ ጉባኤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረስብከት ሊቀ ጳጳስ በመመራት በመንበረ ልዑል ቅዱስ ማርቆስ ቤተክርስቲያን በተጋበዙ ቀሳውስትና ካህናት ጸሎተ ወንጌል የተካሄደ ሲሆን በብፁዕነታቸው ጸሎትና ቡራኬ ተከፍቷል፡፡

 

የማኅበረ ቅዱሳን የሁለት ዓመት የአገልግሎት ክንውን ሪፖርት በማኅበሩ ሰብሳቢ ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ ስዩምgubaye 7 አማካይነት የቀረበ ሲሆን ሪፖርቱም በሚዲያ አገልግሎት በግቢ ጉባኤያት፤ በስብከተ ወንጌል አገልግሎት፤ በቅዱሳት መካናትና የአብነት ትምህርት ቤቶች ላይ የተሠሩ ከፍተኛና አነስተኛ ፕሮጀክቶች፤ ስለ ቤተ ክርስቲያናችን የተደረጉ የጥናትና ምርምር ሥራዎች፤ የቤተ ክርስቲያንና የምእመናን ማኅበራዊ አገልግሎት፤ አጽራረ ቤተ ክርስቲያን በቤተ ክርስቲያን ላይ የሚያደርሱትን ጥቃትና የተወሰዱ እርምጃዎች፤ ወዘተ የተከናወኑ ተግባራት በዝርዝር ቀርቧል፡፡

 

በተያዘው መርሐ ግብር የኦዲት ሪፖርት ቀርበዋል፡፡ የማኅበሩ ሒሳብ የ2003 ሪፓርት የውጪ ኦዲተር ሀብተ ወልድ መንክርና ጓደኞቹ በቻርተር የተመሰከረላቸው የሂሳብ አዋቂዎች የኦዲት ሪፖርቶች ቀርበዋል፡፡ በዚህም ሂሳቡ ትክክለኛ እና የማኅበሩን ገጽታ የሚያሳይ መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡

 

በቀረበው የማኅበሩ የሁለት ዓመታት ክንውን እንዲሁም አጠቃላይ አስተያየት እንዲሰጡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል መልካም ፈቃድ ከብፁዐን ሊቃ ነጳጳሳት ተጋብዘዋል፡፡ በተጨማሪም ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶችም ከበጎ አድራጊ ምእመናን፤ ከነገረ መለኮት ምሩቃን ማኅበር፤ ከፀረ ተሐድሶ ጥምረት የተወከሉ እንግዶች በማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት ዙሪያ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡

 

አስተያየታቸውን ከሰጡ ብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት መካከል ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ሣልሳዊ የምስራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ “በገሊላ አውራጃ ጌታ አሥራሁለት ሐዋርያትን እንደ መረጠ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስም በምሳሌነት ይህች ቤተ ክርስቲያን የተማረ የሰው ኀይል ያስፈልጋታል በማለት 12 የዩኒቨርስቲ ተማሪዎችን ይዘው ነው በዝዋይ ሥራ የጀመሩት፡፡ ማኅበሩ ማኅበራችን ነው” በማለት የማኅበረ ቅዱሳንን አመሠራረት አስታውሰዋል፡፡

 

ብፁዕ አቡነ ማትያስ የካናዳ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት አስተያት “ማኅበረ ቅዱሳን ብዙ ምሁራንና አዋቂዎች የተሰባሰቡበት ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን የቅዱስ ሲኖዶስ ቋሚ ተጠሪ ነው” በማለት ነበር የገለጹት፡፡

 

ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ የሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ “ማኅበረ ቅዱሳን በ20 ዓመት ውስጥ ያከናወነው አገልግሎት እኛ የማኅበረ ቅዱሳን ደጋፊዎች ብቻ ሳንሆን ተቃራኒዎችም የሚመሰክሩት ነው” በማለት ተናግረዋል፡፡

 

ሊቀ ካህናት ኃ/ሥላሴ ዓለማየሁ የዴንቨር ደብረ ሰላም መድኀኔዓለም አስተዳዳሪና የካሊፎርኒያ  አካባቢ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ በሰጡትgubaye 11 አስተያየት ”ከማኅበሩ ጋር በግጭትም፤ በፍቅርም ተገናኝተናል፡፡ ማኅበሩን ከማወቄ በፊት የተቀበልኩት በበጎ መንፈስ አልነበረም፡፡ ነገር ግን በሚያስደንቅ ሁኔታ እኔን የሚያሳምኑ ነገሮች የተፈጠሩት ውስጣችን ገብተህ አገልግሎታችንን ተመልክተህ ፍረድ የሚል ጥያቄ አቀረቡልኝ፡፡ አላቅማማሁም ገባሁ፡፡ የማኅበሩን ማንነት ውስጡን ሕይወቱን ለማየት በምሞክርበት ጊዜ በትክክል የቤተ ክርስቲያኒቱ የጀርባ አጥንት ሆኖ እያገለገለ መሆኑን ለማወቅ እድል አገኘሁ” በማለት ከማኅበሩ ጋር ያላቸውን ቅርበት ገልጸዋል፡፡

 

የጠዋቱ መርሐ ግብር በዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክና በአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በብፁዕ አቡነ ናትናኤል ቃለ ምዕዳንና ቡራኬ ተጠናቋል፡፡

 

ከስዓት በኋላ በነበረው መርሐ ግብር የማኅበሩ ኦዲትና ኢንስፔክሽን አገልግሎት ሓላፊ ዲ/ን ንጋቱ ባልቻ ሪፖርት የቀረበ ሲሆን በሪፖርቱም የማኅበሩ ስልታዊ ዕቅድ አፈጻጸም፤ የማኅበሩ ሥራ አመራር አፈጻጸም፤ የጠቅላላ ጉባኤያት ውሳኔ በተመለከተ ያልተተገበሩ፤ የሂሳብ ሪፖርት ላይ ታይተዋል ያሏቸውን ክፍተቶች አቅርበዋል፡፡በተጨማሪም የጠቅላላ ጉበኤ ውሳኔ ወይም አቅጣጫ የሚሹ ጉዳዮች ተለይተው ጠቅላላ ጉባኤው ቀጣዩን ስልታዊ እቅድ እና የማኅበሩ መተዳደሪያ ደንብ ሲከለስ እንዲካተቱ ትኩረት እንዲሰጣቸው አሳስበዋል፡፡ በኦዲትና ኢንስፔክሽን በቀረበው ሪፖርት ላይና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች እንዲሁም ከአባላት በተነሱ ጥያቄዎችና አስተያየቶች ማኅበሩን ወደ ፊት ሊጠቅሙ በሚችሉ ጉዳዮች ላይ ሰፊ ውይይት ተደርጓል፡፡

 

በመጨረሻም የሚቀጥሉትን አራት ዓመታት ማኅበሩን የሚመሩ የሥራ አመራር አባላትን የሚያስመርጥ 5 አባላትን ያቀፈ አስመራጭ ኮሚቴ ለመምረጥ አስተያየት ከተሰጠባቸው በኋላ በብፁዕ አቡነ ዮናስ የአፋር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ መሪነት ጸሎተ እግዝእትነ ማርያምና አቡነ ዘበሰማያትን በማድረስ አምስቱን አስመራጭ ኮሚቴ አባላትን በእጣ እንዲለዩ ተደርጓል፡፡ በዚሁ መሠረት የዕለቱ መርሐ ግብር በብፁዕ አቡነ ዮናስ ቡራኬ ተጠናቋል፡፡

 

የጠቅላላ ጉባኤው እስከ አርብ ጳጉሜ 2 ቀን የሚቀጥል ሲሆን የተለያዩ ጥናታዊ ጽሑፎች የሚቀርቡበትና ለቀጣዩ አራት ዓመት ማኅበሩን የሚመለከት ስልታዊ ዕቅድ ላይ እንደሚወያዩ ይጠበቃል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ ጸሎተ ምህላ እንዲደረግ ወሰነ

kidusSinodos

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ጽ/ቤት ነሐሴ 30/2004 ዓ.ም. ለመገናኛ ብዙኅን በሰጠው መግለጫ ከጳጉሜ 1 ቀን 2004 ዓ.ም. እስከ መስከረም 10/2005 ዓ.ም. ድረስ ምእመናን ለሁለት ሱባኤያት በመላዋ ኢትዮጵያና በውጭ ሀገር በሚገኙ አህጉረ ስብከቶች በሚገኙ ገዳማት፣ አድባራትና አብያተ ክርስቲያናት  ጸሎተ ምህላ እንዲደረግ ወስኗል፡፡

 

ቅዱስ ሲኖዶስ ጸሎተ ምኅላውን ያወጀበት ምክንያት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በነበሩበት ዘመን በሃይማኖታዊና ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ  ሰፊ ሥራ የሠሩ አባት እንደነበሩ ጠቅሶ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ሁለንተናዊ ዕድገት ፤ ለሀገሪቱ ሰላምና አንድነት የሚበጅ ተተኪ አባት(ፓትርያርክ) እግዚአብሔር ባወቀ መርጦ እንዲያስቀምጥ ካህናትና ምእመናን  በጸሎተ ምኅላው እንዲሳተፉ አሳስቧል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን በዝዋይ ተተኪ ሰባክያንን አስመረቀ

ነሐሴ 28 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዳዊት ደስታ

Zewaye 2 (2)በማኅበረ ቅዱሳን የአዲስ አበባ ማእከል ትምህርትና ሐዋርያዊ አገልግሎት ክፍል ከሐምሌ 24 እስከ ነሐሴ 24 ቀን 2004 ዓ.ም. በዝዋይ ሐመረ ኖኅ ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ያሠለጠናቸውን ተተኪ ሰባክያነ ወንጌል አስመረቀ፡፡

 

ሠልጣኞች በቆይታቸው የጥናትና ምርምር፣ የቅዱሳት መጻሕፍት ጥናት፣ ነገረ አበው፣ የተመረጡ ነገረ ሃይማኖት ርእሰ ጉዳዮች፣ የመማር ማስተማር ዘዴ፣ የታሪክ አጠናን ሂደት፣ የተግባቦት ሥልጠና፣ ሥርዓተ ጾታ፣ ወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ተግዳሮት በሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ሥልጠና ወስደዋል፡፡

 

የሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም አስተዳዳሪ የኔታ ሐረገ ወይን ለተመራቂ ተማሪዎች ቃለ ምእዳን አስተላልፈዋል፡፡

 

የተማሪዎቹ ተወካይ ወጣት ግርማ አብደታ ማኅበረ ቅዱሳን ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት የሚያደርገው እንደዚህ ዓይነት ሥልጠናZewaye 2 (1) ለመንፈሳዊ አገልግሎታችን ብቻ ሳይሆን ለዓለማዊም ትምህርታችን ጠቅሞናል በማለት ገልጸዋል፡፡

 

አያይዘውም ከወሰድናቸው የሥልጠና ርዕሶች አንዱ ነገረ አበው ትምህርት አባቶችን ለዚህች ሃይማኖት የከፈሉትን መሥዋእት በአጠቃላይ የሰዓት አጠቃቀምን የሥራ ፍቅርንና የጸሎት ሕይወትን የተረዳንበት ነው በማለት ገልጸዋል፡፡

 

በምርቃት መርሐ ግብሩ ላይ የገዳሙ አስተዳዳሪ የኔታ ሐረገ ወይንና የገዳሙ ርዕሰ መምህር አባ ገ/ሕይወት አባቶች መነኮሳት የማኅበረ ቅዱሳን ተወካዮችና መዘምራን ተገኝተዋል፡፡

ሊቀ መዘምራን ላእከ ማርያም ወልደ ኢየሱስ ዐረፉ

ነሐሴ 28 ቀን 2004 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

Leke mezemeraneስንክሳርንና ግብረ ሕማማትን እንዲሁም ሌሎችን መጻሕፍት ከግእዝ ወደ አማርኛ የተረጎሙት ታላቁ የመጻሕፍት ሊቅ ሊቀ መዘምራን ላእከ ማርያም ወልደ ኢየሱስ በተወለዱ በ90 ዓመታቸው ነሐሴ 1 ቀን 2004 ዓ.ም. በሞተ ስጋ ከዚህ ዓለም ተለዩ፡፡

 

ሊቀ መዘምራን ላእከ ማርያም ወልደ ኢየሱስ በአርሲ ክፍለ ሀገር በጢዮ ወረዳ ልዩ ስሙ ጨቢ አቦ በተባለ አካባቢ ከአባታቸው መምህር ወልደ ኢየሱስ ዘነበ እና ከእናታቸው ከወ/ሮ ወለተ ሩፋኤል ብስራት ነሐሴ 16 ቀን 1915 ዓ. ም. ተወለዱ፡፡

 

ከአባታቸው ከመምህር ወልደ ኢየሱስ ዘነበ ንባብ፤ ውዳሴ ማርያም ንባብና ዜማ ፤መዝሙረ ዳዊትና ግብረ ዲቁና በመማር ለስልጣነ ክህነት ከበቁ በኋላ በአካባቢያቸው በሚገኘው ዱግዳ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን በዲቁና ሲያገለግሉ ቆይተዋል፡፡

 

ገና በለጋ እድሜያቸው ትምህርትን ፍለጋ ወደ ወሎ ክፍለ ሀገር ላስታ ገረገራ ቅዱስ ጊዮርጊስ በመሔድ ከመምህር ሰይፉ የመጻሕፍተ ሐዲሳትን ትርጓሜ ፤ ከሌሎችም ታዋቂ መምህራን ድጓንና ጾመ ድጓን ተምረዋል፡፡ ወደ ጎንደር በማቅናት ዙር አምባ ገዳም ከታላቁ መምህር ቀለመወርቅ ዝማሬ መዋሥዕት በመማር አጠናቀዋል፡፡ ወደ ደብረ ታቦር በመሔድም የተክሌ አቋቋም ሊቅ ከሆኑት መምህር ቀለመወርቅ ዘንድ ገብተው አስመስክረዋል፡፡ ጎንደር አደባባይ ኢየሱስ ከታዋቂው የቅኔ መምህር በቅጽል ስማቸው የቅኔው ማዕበል መምህር ፈንቴ ቅኔ አስመስክረዋል፡፡ በዋሸራ ከሚገኙት የቅዳሴ መምህር አባ አላምረው ዘንድ የደብረ ዓባይ የመዝገብ ቅዳሴ ተምረዋል፡፡ ሞጣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን በመሄድ ደግሞ  ከመልአከ ገነት ጥሩነህ ለተማሪዎቻቸው ዝማሬ መዋሥዕትን እያስቀጸሉ  ከእሳቸው የአቋቋም ስልቶችን በሚገባ አጣርተው ለማስመስከር በቅተዋል፡፡

 

ወደ መምህርነት ከገቡ በኋላ ብዛት ያላቸው ደቀመዛሙርትን ያፈሩ ሲሆን የተክሌ የአቋቋም በቀላሉ ለመማር የሚያስችል ምልክት ፈጥረው ለደቀ መዛሙርቶቻቸው አስተምረዋል፡፡

 

በአዲስ አበባ በተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት በመምህርነት ያገለገሉ ሲሆን፤ በታእካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም፤ በደብረ ኀይል ቅዱስ ራጉኤል ፤ በብርሃናተ ዓለም ጴጥሮስ ወጳውሎስ ቤተ ክርስቲያናት እየተዘዋወሩ በርካታ ደቀመዛሙርትን አፍርተዋል፡፡

 

ወደ ትውልድ ሀገራቸው አሰላ በመመለስም በአሰላ መንበረ ጵጵስና ደ/ም/ቅ/ማርያም ቤተ ክርስቲያን በመሪ ጌትነት ሲያገለግሉ የቆዩ ሲሆን፤ ከ1971 ዓ.ም.  እስከ 1998 ዓ.ም. በአሰላ ደብረ መድኃኒት መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን በአስተዳዳሪነት አገልግለዋል፡፡

 

በጎንደርና ጎጃም የትምህርትና የመምህርነት ዘመናቸው ላበረከቱት አገልግሎት ከደብረ ወርቅ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን በቅሎ ከነኮርቻው ተሸልመዋል፡፡

 

ባበረከቱት ፍጹም ቅንነት የተሞላበት አገልግሎታቸው የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከነበሩት ከቀድሞው ብፁዕ አቡነ ሉቃስ ቀሚስና ጥንግ ድርብ ከነካባው አልብሰዋቸው፤ የእጅ የወርቅ መስቀል በመሸለም ሊቀ መዘምራን የሚል የክብር ስምም ሰጥተዋቸዋል፡፡

 

መጻሕፍትን በማንበብና በመተርጎም ለቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ ውለታ የዋሉ አባት ሲሆኑ የዓመቱን መጽሐፈ ስንክሳር ከግእዝ ወደ አማርኛ ለመተርጎም ሰባት ዓመታትን ፈጅቶባቸው አስመራ ለሕትመት በተላከበት ወቅት ጠፍቷል፡፡ ተስፋ ሳይቆርጡ በድጋሚ በሁለት ዓመታት ውስጥ በድጋሚ ተርጉመው ለሕትመት አብቅተዋል፡፡ እንዲሁም ግብረ ሕማማትንና ገድለ ዜና ማርቆስን ከግእዝ ወደ አማርኛ በመተርጎም ለሕትመት አብቅተው ቤተ ክርስቲያን እየተጠቀመችባቸው ትገኛለች፡፡ በተጨማሪም ገድለ ሓዋርያት፤ ተአምረ ኢየሱስ፤ ገድለ ቂርቆስ ፤ ገድለ ነአኩቶ ለአብ ፤ ገድለ ሊባኖስ፤ ገድለ ማርያም መግደላዊት፤ ድርሳነ ሐና ፤ ገድለ ዮሐንስ መጥምቅና ሌሎችም በርካታ መጻሕፍት ከግእዝ ወደ አማርኛ በመተርጎም ለቤተ ክርስቲያን አበርክተዋል፡፡

 

ሊቀ መዘምራን ላዕከ ማርያም ወልደ ኢየሱስ በአንድ ወቅት መጻሕፍትን ለመተርጎም የተነሳሱበትን ምክንያት ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ “በመኪና አደጋ እግሬ ተሰብሮ በነበረበት ወቅት ቁጭ ከምል ለምን መጻሕፍትን አልተረጉምም በሚል እግዚአብሔር አሳስቦኝ ተነሳሳሁ፡፡ ስንክሳርንና ሌሎችን አሥራ ሦስት መጻሕፍትን የተረጎምኩት ያኔ ነው፡፡ እግዚአብሔር ታላቅ ችሮታ ነው ያደረገልኝ፡፡ እግሬ ባይሰበር ኖሮ እነዚህን መጻሕፍት መተርጎም አልችልም ነበር፡፡ እግዚአብሔር የጎዳ መስሎ ይጠቅማል፡፡ የእግሬ መሰበር ትልቅ ጥቅም ለኔም ለቤተ ክርስቲያንም አስገኝቶልኛል፡፡” ብለው ነበር፡፡

 

በቅርቡም በጠና ታመው ሕመማቸው ፋታ በሰጣቸው ስዓት ለደብረ ሊባኖስ ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ገዳም ይተረጉሙት የነበረው ዜና ሥላሴ የተሰኘው መጽሐፍ አብዛኛውን ክፍል ተርጉመው ያገባደዱት ሲሆን ሳይፈጽሙት ሞት ቀድሟቸዋል፡፡

 

በእርግና ምክንያት ጡረታ ከወጡ በኋላ ለቤተ ክርስቲያን ባበረከቱት ከፍተኛ ትጋትና አገልግሎት የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ናትናኤል ሙሉ ደሞዛቸው እንዲከፈላቸው አድርገዋል፡፡

 

ሊቀ መዘምራን ላእከ ማርያም ወልደ ኢየሱስ በ1946 ዓ.ም. ከወ/ሮ ምሕረት በትዕዛዙ ጋር በስርዓተ ተክሊል ጋብቻ የፈጸሙ ሲሆን ስድስት ወንዶችና ስድስት ሴቶች ልጆችን አፍርተው ሠላሳ አንድ የልጅ ልጆችን ለማየት በቅተዋል፡፡ ዝግጅት ክፍላችን ለቤተሰቦቻቸውና ለዘመድ ወዳጆቻቸው መጽናናትን ይመኛል፡፡ የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር ነፍሳቸውን በገነት ያኑርልን፡፡