አዲስ ዓመት

ጳጉሜን 5 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዳዊት ደስታ

ኢትዮጵያ የወራት ሁሉ መጀመሪያ መስከረም ነው፡፡ ይህ ወር ዘመን መለወጫ፣ ዕንቁጣጣሽ፣ ቅዱስ ዮሐንስ እየተባለ ይጠራል፡፡ ስለ አዲስ ዓመት በተለያየ ስም የመጠራቱ ታሪካዊ አመጣጥና ስያሜ መነሻ አሳቡ ምን እንደሆነ እንደሚከተለው እንመለከታለን፡፡

 

ዘመን መለወጫ

ዘመን መለወጫ መስከረም ወር የሆነበት ምክንያት “ብርሃናት /ፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ከዋክብት/ የዓመት ዑደታቸውን በጳጉሜ ወር ጨርሰው በመስከረም ወር ስለሚጀምሩ ነው፡፡ ሌሊቱ ከቀኑ ጋር ይተካከላል፡፡ ዓመቱን ጠንቅቀው ቢቆጥሩ 364 ቀናት ይሆናል፡፡ “ሌሊቱም ከቀኑ ጋራ ይተካከላል፡፡ ዓመቱም ጠንቅቆ ቢቆጥሩት ሦስት መቶ ስልሳ አራት ቀን ይሆናል፡፡ /ሄኖክ.26፥44/ “ዘመናችንን እንደ ቀድሞ አድሱ” /ሰ.ኤር.5፥21/ እንዲል፡፡

በዘመነ ኖኅ ዓለምን ንፍር ውኃ አጥለቅልቆት ከቆየ በኋላ ዳግመኛ ውኃው የጎደለበት በመሆኑ /ኩፋሌ 7፥1/ “በመጀመሪያው ወር መባቻም ምድር ታየች” እንዲል፡፡

 

ዕንቁጣጣሽ

ዕንቁጣጣሽ የተባለበት ምክንያት አንደኛ “ዕንቁ – ዕፅ አመጣሽ” ብሎ የአበባውን መፈንዳት ያመለክታል፡፡ ሁለተኛ ኖኅ ለሦስቱ ልጆቹ አህጉራትን በእጣ ሲያካፍላቸው አፍሪካ ለካም ደረሰችው፡፡ በአፍሪካ ምድርም ሲገባ በመጀመሪያ ያረፈው በኢትዮጵያ ነበር፡፡ ሀገሪቱም በአደይ አበባ አሸብርቃ ነበር፡፡ ወሩ ወርኀ መስከረም በመሆኑ ደስ ብሎት ዕንቁ ዕጣ ወጣሽልኝ ይህችን ወቅት እንቁጣጣሽ ብሏታል፡፡ ሦስተኛው /1ነገ.10፥1-10/ ኢትዮጵያዊቷ ንግሥት ሣባ /አዜብ የንጉሡን ጥበብ ከመስማት ማየትን መርጣ ወደ ንጉሥ ሰሎሞን ከብዙ ሠራዊቶቿ ጋር የእጅ መንሻ በመያዝ ሄደች፡፡ ንጉሡም በደስታ ተቀብሎ እርሱም “እንቁ ለጣትሽ ጌጥ ይሁንሽ” በማለት አራት አይነት ቀለም የሚታይበት በቀንና በሌሊት የምታበራ ቀለበት ሰጥቷታል፡፡ ወሩም ወርኀ መስከረም ነበር፡፡ ከዚህ በመነሣት እንቁጣጣሽ የሚለው ስያሜ ወጥቷል፡፡

 

ቅዱስ ዮሐንስ

ሦስተኛው የአዲስ ዘመን ስያሜ ቅዱስ ዮሐንስ ነው፡፡ የመጥምቁ ዮሐንስ ተግባር ለዘመነ ወንጌል በር ወይም መነሻ እንዲሆን ለኢትዮጵያ ዐውደ ዓመት መስከረም አንድ ቀን እንዲከበር አባቶች ወስነዋል፡፡ /ድርሳነ ዮሐንስ አፈወርቅ ገጽ 1-3/ መጽሐፈ ስንክሳር “የመስከረም ወር የተባረከ ነው፡፡ እርሱም የግብጽና የኢትዮጵያ ዓመቶች መጀመሪያ ነው፡፡ የዚህ ወር ቀኑና ሌሊቱ እኩል 12 ሰዓት ነው፡፡ ከዚህ በኋላ ቀኑ እየጎደለ ይሄዳል” እንዲል፡፡

 

በአጠቃላይ ዘመን መለወጫ ከላይ ባየናቸው የተለያየ ስያሜ ይጠራ እንጂ ዘመኑ አዲስ እየተባለ ቢጠራም አዲስ መሆን ያለበት ወርና ወቅቱ ብቻ ሳይሆን የእኛ የክርስቲያኖች ሥርዓት ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰውነታችሁን አታርክሱ የእግዚአብሔር ማደሪያ ነውና እያለ በመዋዕለ ሥጋዌው ያስተምር ነበር፡፡ አዲስ ዓመት ሲመጣ በኀጥያት፣ በተንኮል፣ በክፋት የቆሸሸው ሰውነታችን በንስሓ፣ በቅዱስ ቊርባን፣ በመልካም ተግባር አዲስ ልናደርገው ይገባናል፡፡