hawassakidusgebriel.jpg

በሐዋሳ ያለው ችግር እንደ ቀጠለ ነው፡፡

ሰኞ፣ የካቲት 14/2003 ዓ.ም                                                                    በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ
 
hawassakidusgebriel.jpgትናንት እሑድ የካቲት 13/2003 ዓ.ም በሐዋሳ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ከቅዳሴ በኋላ በብፁዕ አቡነ ገብርኤል ሊሰጥ የነበረው ትምህርተ ወንጌል በተወሰኑ የሰ/ት/ቤት ወጣቶች አመጽ ተስተጓጉሏል፡፡ ከሥፍራው የደረሰንን ሪፖርት እንደሚከተለው አቅርበናል፡፡
 
ብፁዕነታቸው ጸሎተ ቅዳሴውን ከመሩ በኋላ ለማስተማር ዐውደ ምሕረት ላይ ወጥተው ከካህናቱ ጋር ተቀመጡ፡፡ ወጣቶቹም የሰንበት ትምህርት ቤት ዩኒፎርም ለብሰው ዝማሬ ማቅረብ ጀመሩ፡፡ በተለምዶ ሁለት መዝሙር ቀርቦ ስብከተ ወንጌል የሚጀመር ቢሆንም ትናንት ግን “እመቤቴ ማርያም እለምንሻለሁ” እና “የኢቲሳ አንበሳ ተክልዬ ተነሳ” የሚሉ መዝሙሮች ከተዘመሩ በኋላም ዝማሬው አልቆመም፡፡ 
 
ወጣቶቹ ከኪሳቸው ይዘውት የነበረውን ጥቁር ጨርቅ አውጥተው እያውለበለቡ “መዘመራቸውን” ቀጠሉ፡፡ ይህንን የተመለከቱት ብፁዕ አቡነ ገብርኤል ትምህርት መስጠቱን ትተው ወደ ቤተ ክርስቲያን በመግባት ቅድስቱ ላይ በመሆን የማሰናበቻ ጸሎቱን አድርሰዋል፡፡

ከጸሎቱ በኋላ ብፁዕ አቡነ ገብርኤል “ጥቂት ወጣቶች የቤተ ክርስቲያንን ሰላም አያደፈርሱም፣ …. የቤተ ክርስቲያን ዐውደ ምሕረት ተከብሮ ይኖራል፣ … ከአሁን በኋላ እንድንጨክን እያደረጋችሁን ነው…” በማለት ጠንከር ያለ ወቀሳና ተግሣጽ አስተላልፈዋል፡፡ ምእመናን ስለ ቤተ ክርስቲያን ሰላም እንዲጸልዩም በአጽንዖት አሳስበዋል፡፡ ለምነዋል፡፡

ብፁዕነታቸው ይህንን መልእክት ሲያስተላልፉ ወጣቶቹ በከፍተኛ ድምፅ እየዘመሩና ከበሮ እየመቱ እንዳይሰሙ ለማድረግ ጥረት ሲያደርጉ ነበር፡፡

እነዚሁ ወጣቶች እና ሌሎች ከ60 – 100 ያህል የሚሆኑ “ምእመናን” ብፁዕ አቡነ ገብርኤል ከቅዳሴ በኋላ ወደሚወጡበት የቤተ ክርስቲያኑ የምሥራቅ በር ጥቁር ጨርቃቸውን እያውለበለቡና “አንፈራም አንሰጋም…” እያሉ እየዘመሩ በመሄዳቸው በቤተ ክርስቲያኑ ግቢ ውስጥ የነበሩት ምእመናን ግልብጥ ብለው ወደዚያው በመሄድ ብፁዕ አቡነ ገብርኤልን አጅበው እስከ መንበረ ጵጵስናቸው /መኖሪያቸው/ አድርሰዋቸዋል፡፡ ሰዎቹ ለምን ዓላማ ጥቁር ጨርቅ እያውለበለቡና እንደዚያ እያሉ እየዘመሩ ወደ ብፁዕነታቸው እንደሄዱ ግልጽ ባይሆንም በኋላ ተመልሰው ወደ ሰንበት ትምህርት ቤት አዳራሽ ገብተዋል፡፡

ብፁዕ አቡነ ገብርኤልን አጅበው ወደ ቤታቸው ያደረሱት ምእመናን “አይዝዎት አባታችን፣  ሰላማችንን እያጠፋውና እየበጠበጠን ያለው ዲያብሎስ በመሆኑ ልንታገሥ ይገባል፣ እኛም ከጎንዎት ነን…” በማለት ብፁዕነታቸውን አጽናንተዋል፡፡ ብፁዕነታቸውም ለዚህ ሁሉ ዋናው መፍትሔ ጸሎት በመሆኑ ሁሉም ስለቤተ ክርስቲያን ሰላም በመጸለይ እንዲተጋ በድጋሚ በማሳሰብ ሕዝቡን በቡራኬ አሰናብተዋል፡፡

ትናንት ይህንን ሁከት ያደረሱት ወጣቶች በቀድሞው የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ አማካኝነት በተፈጸመው ቃለ ዐዋዲውን ያልጠበቀ ምርጫ በተመረጠው የሰንበት ትምህርት ቤት አመራር የሚመሩ ሲሆኑ፣ ይህ ሁኔታ ከመፈጸሙ ከአንድ ቀን በፊትም /ቅዳሜ የካቲት 12/2003 ዓ.ም/  በሰንበት ትምህርት ቤቱ አዳራሽ ተገኝተው እንደተወያዩ ለማወቅ ተችሏል፡፡ ከዚህ በፊት ብፁዕነታቸው ወደ ሀገረ ስብከቱ ለመጀመሪያ ጊዜ ሲሄዱ በተመሳሳይ መልኩ ጥቁር ጨርቅ እያውለበለቡ እንደተቀበሏቸውም ይታወሳል፡፡

ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተባባሰ የመጣውንና የታቀደና የተቀናጀ የሚመስለውን እንቅስቃሴ በማየት፥ እነዚህ አካላት ሆን ብለው የቤተ ክርስቲያንን ገጽታ የማጉደፍና አገልግሎቷን የማደናቀፍ ብሎም ምእመናንን አስመርሮ ከቤተ  ክርስቲያን የማስወጣት ሥውር ተልእኮ ባላቸው የውስጥ አርበኞች የሚነዱ እንዳይሆኑ ስጋት እንዳላቸው የሚገልጹ ምዕመናንንም ቁጥር በርካታ ነው፡፡

የደቡብ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ክቡር አቶ ሽፈራው ሽጉጤ በቤተ ክርስቲያን ምንም ዓይነት ሁከት መፈጠር እንደሌለበትና ተቃውሞም ቢኖር ሰላማዊ በሆነ መንገድ ብቻ መቅረብ እንዳለበት ያሳሰቡ መሆኑ ይታወሳል፡፡

The first sheep.JPG

ሻሼ(ለህጻናት)

በእመቤት ፈለገ 

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች ? ዛሬ የምንነግራችሁ በጣም ደስ ስለሚለው ነጭ የበግ ግልገል ነው፡፡
በአንድ ወቅት አብረው ይኖሩ የነበሩ መቶ በጎች ነበሩ፡፡ ከነዚህ በጎች መካከል ሻሼ የተባለ በጣም ደስ የሚል እና ከጓደኞቹ በጎች ጋር መጫወት የሚወድ ነበር፡፡ በጣም የሚወዳቸው እናት እና አባት ነበሩት፡፡ ሌሎቹም እንደራሱ ወንድም እና እህት ነበር የሚያያቸው፡፡

እነዚህ መቶ በጎችን እጅግ በጣም የሚወዳቸው፤ ሌሎች እንስሳት ጉዳት እንዳያደርሱባቸው የሚጠብቃቸው እና ጥሩ ምግብ እና መጠጥ ሊያገኙበት ወደሚችሉት ቦታ የሚወስዳቸው ጎበዝ እረኛ ነበር፡፡ በእየለቱም ከመካከላቸው የጎደለ በግ እንዳይኖር 1፣2፣3፣ …. 1ዐዐ እያለ ይቆጥራቸው ነበር፡፡The first sheep.JPG

       

        

           

ከእለታት አንድ ቀን ጎበዙ እረኛ በጎቹን ይዞ በጣም ደስ ወደሚል ቦታ ወሰዳቸው፡፡ በጎቹም ወዲያው ቦታውን ሲያዩት እጅግ በጣም አስደሰታቸው፡፡ እየበሉ እና እየጠጡ መጫወት ጀመሩ፡፡ እነ ሻሼ በመጫወት ላይ እያሉ ከሌላ ቦታ የመጣ አስቸጋሪ በግ ወደ እነሱ ተቀላቀለ፡፡The 2 sheeps.JPG ወደ ሻሼም ጠጋ ብሎ  «ሌላ ከዚህ በጣም የሚያምር ቦታ አለ፡፡ ብዙ ምግብ፤ መጠጥ እና እየዘለልን ለመጫወት የሚያመች ተራራ አለ» አለው፡፡ 

ሻሼም ከእረኛው ከእናት እና ከአባቱ ተለይቶ ጠፋ፡፡ ቦታው ላይ እንደደረሱም መዝለል መጫወት ቀጠሉ፡፡ ሻሼም “ብዙ ምግብ እና መጠጥ የት ነው ያለው?” ብሎ ጠየቀው፡፡ አስቸጋሪው በግም «እዚህ ቦታ ምንም አይነት ምግብ እና መጠጥ የለም ነገር ግን እኛ እዚህ የመጣነው ለመጫወት ነው» አለው፡፡ ብዙ ከመጫወታቸው የተነሣ በጣም ደከማቸው፡፡ አስቸጋሪውም በግ ሻሼን ለብቻው ትቶት ወደ ቤቱ ሄደ፡፡ ሻሼም ወደ ቤት ለመሔድ ሲነሳ መንገዱ ጠፋበት እየመሸ ስለነበር እጅግ በጣም ፈራ እዚያው ካደረ ደግሞ ሌላ የዱር አራዊት መጥቶ ይበላዋል፡፡ ሰውነቱ እየተንቀጠቀጠ ማልቀስ ጀመረ፡፡

ሰአቱ ሲመሽ በጎቹ ከጠባቂያቸው ጋር ሆነው ወደቤታቸው ሄዱ፡፡ ጠባቂያቸውም እየጠራ መቁጠር ጀመረ 1፣2፣3፣ ……. 99 «ሻሼ የት ሄደ?» ብሎ ጠየቀ ማንም ሊመልስለት አልቻለም ሻሼ እያለ እየጮኸ ተጣራ ነገር ግን ማንም አቤት ሊለው አልቻለም፡፡

ቤት ውስጥም እንደሌለ ሲያውቅ ሌሎቹን በጎች የትም እንዳይሔዱ ነግሮ ሻሼን ለመፈለግ ወጣ፡፡The man and the sheep.JPG የተለያየ ቦታ መፈለግም ጀመረ በመጨረሻም ሻሼን እያለቀሰ እና እየተንቀጠቀጠ አየው፡፡

ሻሼ የእረኛውን መምጣት ሲያይ እጅግ በጣም ደስ አለው፡፡ ፍርሀቱም ለቀቀው፡፡

 የበጎቹ እረኛ ሻሼን እንዳገኘው በትከሻው ተሸከመው እና ወደ ቤታቸው ተመለሱ፡፡99ኙ በጎች ተሰብስበው የሻሼን እና የእረኛቸውን መምጣት ሲመለከቱ በጣም ተደስተው ዘለሉ፡፡ The last Sheep.JPG

ልጆች ሁል ጊዜ ቤተሰቦቻችን እና ታላላቆቻችን የሚሉንን መስማት አለብን፡፡ አትሒዱ ያሉን ቦታ መሔድ የለብንም ቤተሰቦቻችንን እና ታላላቆቻችን የሚሉንን ከሰማን እግዚአብሔር ይባርከናል፡፡

ልጆች ይህ ምሳሌ የጌታችን ምሳሌ ነው፡፡ መላእክትን ሲፈጥር መቶ ነገድ አድርጎ ነው፡፡ ከእነዚህ መካከል የሳጥናኤል ነገድ በትዕቢት ምክንያት ከእግዚአብሔር መንግስት ተባረረ፡፡ በምትኩ የአዳምን ዘር አንድ ነገድ አድርጎ ፈጠረው፡፡ አዳም በሰይጣን ምክር ተታለለ፡፡ ጌታውም አትብላ ያለውን ዕፅ በላና ሞት ተፈረደበት፡፡ ይህ እንደሆነ ባየ ጊዜ ጌታችን ዘጠና ዘጠኙን ነገደ መላእክትን በሰማይ ትቶ የጠፋውን አዳምን ለመፈለግ ከድንግል ማርያም ተወለደ፡፡ ሰላሳ ሦስት ዓመትም በምድር ላይ ተመላለሰ፡፡ ሞቶ፤ ተነስቶ፣ አርጎ፤ የአዳምን ዘር ከወጣበት ቤት መለሰው፡፡ ልጆች አያችሁ የጌታን ቸርነት?

                                                                                        

                                                                                             ደህና ሰንብቱ

 

Picture.jpg

‹እንግዲህ አንተና ዘርህ በሕይወት ትኖሩ ዘንድ ሕይወትን ምረጥ› ዘዳ 30፥19

በዲ/ን ሄኖክ ኃይሌ
 
Picture.jpgአምላካችን እግዚአብሔር በሥልጣኑ ገደብ የሌለበት ሁሉን ማድረግ የሚችል አምላክ ነው፡፡ ከሥልጣኑ ማምለጥ የሚችልም የለም፤ ሁሉ በእርሱ መግቦት፣ ጥበቃና እይታ ሥር ነው፡፡ በምድር ላይ ያሉ ባለሥልጣናት ሥልጣናቸው በድንበር፤ በጊዜ፤ በሕግ የተገደበ ነው፡፡ እንዲህም ሆኖ በቦታና በጊዜ የተገደበ ሥልጣናቸውን ያለገደብ ለመጠቀም ይሞክራሉ፡፡ ሥልጣናቸውና ኃይላቸው የፈቀደላቸውን ያህል ኅብረተሰቡን እንደ ሰም አቅልጠው፤ እንደገል ቀጥቅጠው በግርፋት፣ በቅጣት፣ እየተጠቀሙ ልክ ሊያስገቡት ያም ባይሆን ሊያዳክሙት መሞከራቸው የምድራዊ ገዢዎች ጠባይ እንደሆነ በመጽሐፍ ቅዱስና በታሪክ የምንረዳው ሀቅ ነው፡፡ እግዚአብሔር ግን ገደብ የሌለው ሥልጣኑን በራሱ መግቦት ቸርነት፣ ምሕረት ገድቦ ሁሉን የሚያኖር አምላክ ነው፡፡
የሰው ልጅን ታሪክ ስንመረምርም ይህን እውነት መረዳት እንችላለን፡፡ አዳም የእግዚአብሔርን ሥልጣን (አምላክነትን) ሽቶ በዲያብሎስ ምክር ሕገ እግዚአብሔርን በጣሰ ጊዜ እግዚአብሔር ‹ሥልጣኔን ልትጋፋ አሰብህን? ብሎ በአዳም የፈረደበትን ፍርድ በራሱ ላይ አድርጎ ለመቀበል የፈጠረውን ሥጋ ተዋሕዶ በመከራው፣ በሞቱ አድኖታል፡፡ ይህም እግዚአብሔር የሰውን ልጅ በግድ ሳይሆን በነፃነት የሚገዛ አምላክ መሆኑን ያስረዳል፡፡ ከአዳምም በኋላ የሰው ልጆች እርሱን ከማምለክ ወደኋላ ሲሉና ለፍቅር አገዛዙ ሊመለስ የማይገባ ያለመታዘዝና የአመጽ አጸፋን ሲመልሱ የነጻነት እርምጃውን አልተወም። ሰውን ሁሉ እርሱን ወደ ማምለክና ለእርሱ ብቻ መገዛት የሚችልበት ችሎታ ሲኖረው ‹እሳትና ውኃን አቀረብኩልህ ወደ ወደድኸው እጅህን ስደድ› የሚል የነፃነት ጥሪን ከማቅረብ በቀር ምንም አላደረገም፡፡ ዛሬም ድረስ “እግዚአብሔር የለም” እስከማለት፤ በእርሱ ላይ እስከማፌዝና እስከመዘበት የሚደርሱ ብዙዎችን እየተመለከተ ዝም ማለቱ ማንም ሰው በፍላጎቱ ብቻ እርሱን እንዲመርጥ ስለሚፈልግ ነው፡፡ ‹ወደ እኔ ኑ! ወደ እኔ ቅረቡ› እያለ መጣራቱን ወደንና መርጠን በፈቃደኝነት ወደ እርሱ እንድንሄድ፤ ነፃነታችን ላለመንፈግ እንጂ እኛን ወደ እርሱ ማቅረብ ተስኖት የሚያደርገው የልምምጥ ጥሪ አይደለም፡፡ ይህን ሁኔታም አሁን ከምንረዳው በላይ በእግዚአብሔር ፊት በሞት እጅ ተይዘን በምንቀርብበት ጊዜ በይበልጥ የምንረዳው ነው፡፡
አንባብያን ሆይ! እግዚአብሔር አባታችን አዳምን በገነት ሳለ ዕፀ በለስን እንዳይበላ መከልከሉ ከሞላ ዛፍና ፍሬ አንዲት ዕፅ ተበልታ እርሱ የሚጎድልበት ሆኖ ነው? ወይስ ዲያቢሎስ ለሔዋን እንደነገራት አምላክ እንዳይሆን ነው? እንዲህ እንዳንል ደግሞ አዳም ዕፅዋን ሲበላ እንኳን አምላክነት ሊጨመርለት የነበረው ፀጋ ተገፍፎ ዕርቃኑን ቀርቶአል፡፡ ታዲያ ለእግዚአብሔር አንዲት ቅጠል ምን ልትረባው ነው አትብላ ብሎ የከለከለው? በንባብና በትምህርት ከምንደርስባቸው በርካታ ምክንያቶች በተጨማሪ የአዳም ነጻ ፈቃድ እንዲታወቅ ነው፡፡
እግዚአብሔር ለአዳም ያለውን ፍቅር በመፍጠር፤ ሁሉን በመስጠት ከገለጠ አዳም ለእግዚአብሔር ያለውን ፍቅርስ በምን መለካት ይቻላል? አዳም ለእግዚአብሔር ሊሰጠው የሚችለው እግዚአብሔር ከሰጠው ነገር ሌላ አዲስ ነገር ምን አለ? ምንም የለም! አዳም ለአምላኩ ያለውን ፍቅር የሚገልጠው በምንም ቁስ አይደለም የመታዘዝና ያለመታዘዝ ነጻ ፈቃዱን ለእግዚአብሔር በመስጠት (በመታዘዝ) ብቻ ነበር፡፡ ዕፀ በለስም የዚህ ነጻ ፈቃድ መመዘኛ ነበረች፡፡ አዳም ግን ነጻ ፈቃዱን ለእግዚአብሔር ሊሰጥ አልፈቀደም። በነጻነት ከሚገዛው ፈጣሪ ይልቅ ረግጦ የሚገዛውን የዲያብሎስን አገዛዝ መረጠ፡፡
አንዳንዶች ‹ፈጣሪ የሰው ልጅ ኃጢአተኛ እንደሚሆነ እያወቀ፤ እያየ ለምን ኃጢአት እንዳይሠራ አላደረገውም? ይላሉ፡፡ ይሁንና እግዚአብሔር የሰውን ልጅ ነጻ ፈቃድ የማይነካ የነጻነት ገዢ ነው፡፡ ደግሞም ሰው በበጎው መንገድ ብቻ እንዲሔድ ቢያስገድደው ኖሮ ‹ነጻነቴን ተነፈግሁ› ባለ ነበር፡፡ እንኳን ዕድሜያችንን ሙሉ በመንፈሳዊው አኗኗር ለመኖር በዕለተ ሰንበት በቤተ ክርስቲያን መጥተን ሥርዓተ ቅዳሴ እስከሚጠናቀቅ ለመታገስ ፈቃደኛ ያልሆንን ብዙዎች ነን፡፡
ወደ ሲኦል ወይንም ወደ ገነት መግባታችን የነጻነት አገዛዙ አካል ነው፡፡ አንዳንዴ ‹እግዚአብሔር እንዴት ሰው ወደ ሲኦል እንዲገባ ያደርጋል? ለምን ይጨክናል?› ብለን ባላወቅነው ልንፈርድ እንችላለን፡፡ እግዚአብሔር  በምድር ሳለን ‹ይህን ብትፈጽሙና ብታደርጉ ገነትን ትወርሳላችሁ፤ ይህንን ብታደርጉ ደግሞ ሲኦል ትገባላችሁ ብሎ ሁለት አማራጮችን ሰጥቶናል፡፡ የምንመርጠው መንገድ የምንወርሰው ርስት ምን እንደሆነ ይወስነዋል፡፡ እግዚአብሔር ሁሉም ሰው ቢድን (ወደ ገነት ቢገባ) የሚወድ አምላክ መሆኑን ራሱ በቃሉ ተናግሯል፡፡ ይሁንና በምድር ሳሉ ሲኦል ለመግባት የሚያበቃቸውን መንገድ የመረጡ ሰዎችን ግን ከምርጫቸው ለይቶ ወደ ገነት መውሰድን የነጻነት አገዛዙ አይፈቅድም፡፡ ስለዚህም ማንንም ማስገደድ የማይወድ አምላክ የሰው ልጅ በተሰጠው ነጻ ፈቃድ በምድር ሳለ የመረጠውን ርስት እንዲወርስ ያደርገዋል፡፡
የዚህ ጽሑፍ መሪ ጥቅስ የሆነው ቃልም ከላይ ለጠቀስነው ሀሳብ ምሳሌ የሚሆን የነጻነት ጥሪ ነው፡፡ ‹በፊታችሁ ሕይወትና ሞትን፤ በረከትና መርገምን እንዳስቀመጥኩ እኔ ዛሬ ሰማይና ምድርን ባንተ ላይ አስመሰክራለሁ፡፡ እንግዲህ ‹አንተና ዘርህ በሕይወት ትኖሩ ዘንድ ሕይወትን ምረጥ› ዘዳ 30፥19
እግዚአብሔር ሕይወት የተባለች ሃይማኖትንና ምግባርን በእርስዋ ከሚገኘው በረከት ጋር፤ ሞት የተባለች ኃጢአትንና ርኩሰትን በእርስዋ ከሚመጣው መርገም ጋር በፊታችን አስቀምጧል፡፡ የምንወደውን የምንመርጥበት ነጻ ፈቃድ አለንና፡፡
choose.jpg
የዚህ ምርጫ ታዛቢዎች ሰማይና ምድር ናቸው፡፡ ሰማይና ምድር ደግሞ በየትኛውም ዘዴ የማይታለሉና ንቁ ታዛቢዎች ናቸው፡፡ ወደ ሞት መንገድ እየሄድን የመረጥኩት ሕይወትን ነው ብሎ ማታለል አይቻልም፤ ሰማይና ምድር ይመለከታሉና፡፡ ኃጢአትን አብዝተን እየፈጸምን በመላ ሰውነታችን ርኩሰትን እየመረጥን የመረጥኩት ሕይወት ነው ብንል ከሰማይና ከምድር ዕይታ ውጪ የሰራነው ኃጢአት ስለሌለ እግዚአብሔር እነርሱን ምስክር ያደርግብናል፡፡ ብሎም በምድር በሰው ልጆች በሰማይ በመላእክት ያስመሰክርብናል፡፡ መላእክቱም ጠባቂዎቻችን ፤ የሰው ልጆችም አብረውን የሚኖሩ ናቸውና ሥራችንና ምርጫችን ምን እንደሆነ ለመታዘብ አይቸገሩም። እግዚአብሔር ታዛቢዎች አቁሞ ምረጡ ሲለን ምንም ነጻ ፈቃዳችንን ባይነካም፤ ብንሰማውም ባንሰማውን እንደ አባትነቱ የቱን ብንመርጥ እንደሚሻለን ይመክረናል ‹እንግዲህ አንተና ዘርህ በሕይወት ትኖሩ ዘንድ ሕይወትን ምረጥ› በማለት፡፡
 
ሕይወትን ምረጡ ሲል ወደ ሞት የምትወስደውን የኃጢአት መንገድ ትታችሁ ወደ ዘላለማዊ ሕይወት የምትወስደውን የሃይማኖትና የጽድቅን መንገድ ተከተሉ ማለት ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ቤት መራቅና ዓለማዊ ተድላ ደስታን ብቻ ማሳደድ ሕይወትን አለመፈለግ ነው፡፡ ወደዚህች ቅድስት ስፍራ የሚመጣ ሁሉ ሕይወት የሆነ አምላክን ከእርሱም የሚገኘውን መንፈሳዊ ስጦታ ሁሉ ያገኛል፡፡ እግዚአብሔር ሕይወትን ምረጡ ማለቱ በሌላው ምርጫችን የሚደርስብንን ክፉ ነገር ሁሉ እንዳናይ በማሰብ ነው፡፡
ውድ አንባብያን! ቀጣዩን አንቀፅ ከማንበባችን በፊት እስቲ ቆም ብለን ‹ባለፈው የሕይወት ዘመናችን መርጠን የነበረው መንገድ የሕይወት ነው? ወይስ የሞት?› በማለት ራሳችንን እንጠይቅ የብዙዎቻችን ሕሊና የሚነግረን ምርጫችን የጥፋት መንገድ እንደነበረ ነው፡፡ ከነፍሳችን ይልቅ ለሥጋችን፤ ከሕይወታችን ይልቅ ለሞታችን፤ከልማታችን ይልቅ ለጥፋታችን ስንደክም መኖራችን ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ የደጋግ ቅዱሳን አባቶች መፍለቂያ የሃይማኖትና የምግባር መነኻሪያ በነበረችው ቅድስት ሀገራችን ያለአንዳች እፍረትና ፍርሃት  ተከፍሎ የሚያልቅ፤ የማይመስል የኃጢአት ዕዳ ሲከማች እንደዋዛ መታየቱ ምንም እንኳን መጽሐፍ ቅዱስ ‹ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች› ቢል የብዙ ኢትዮጵያውያን እጅ ግን ወደ ሌላ አቅጣጫ መዘርጋቱን የሚያመለክት ነው፡፡ ለመንፈሳዊ አገልግሎትና ለሥራ ዳተኛ የሆነ ሁሉ ለዝሙትና ለዳንኪራ ያለስስት ገንዘቡን፣ ጊዜውንና ጉልበቱን ሲሰጥ በመንፈሳዊ ዓይን ለሚመለከተው ሰው እጅግ የሚያሳዝን ነበር፡፡
ክርስቲያኖች፣ በዚህ ዲያብሎስና የዓለም ጠባይ ሰውን ሁሉ ከሃይማኖትና ከምግባር ለማውጣት፤ የተቀደሰ ኢትዮጵያዊ ባሕሉን፤ ማንነቱንና ሥርዓቱን ለማጥፋት ታጥቀው በተነሱበት ጊዜ ‹ሕይወት ምረጡ› የሚለው አዋጅ እጅግ ተገቢ አይደለም ትላላችሁ? ስለዚህ ነው ፈጣሪ እያንዳንዱ ክርስቲያን ‹ወደ ሌላው ሰው በደል መጠቆምና ማመካኘት ትተህ አንተና ዘርህ በሕይወት ትኖሩ ዘንድ ሕይወትን ምረጥ› በሚለው ቃል ራስን ለመመርመር ወደ ቤተ ክርስቲያን መቅረብ ነው፡፡
ቤተ ክርስቲያን ሕይወትን የሚመርጡ ሁሉ የሚገቡባት በር ናት፡፡ ምንም እንኳን በቤተ ክርስቲያን ስላሉ ሰዎች መጥፎ ወሬን ቢሰሙ እንኳን እንደ ተራ እንቅፋት ቆጥረው በጽናት መቀጠል ለክርስቲያኖች ይገባቸዋል፡፡ ያለፉት የኃጢአትና የርኩሰት ዓመታት በንስሐ በማጠብ ወደ ሥጋ ወደሙ መቅረብ ፤ ሕይወትን መምረጥ ፤ብሎም በሕይወት መኖር ነው፡፡
የእግዚአብሔርን ጥሪ ተቀብሎ ይህንን የሕይወትና የሞት ምርጫ ለመምረጥ ልዩ መሥፈርት የለውም ክርስቲያንነት ብቻ በቂ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም መንፈሳዊውን መንገድ መርጠን መኖር ጀምረን በድክመታችን ያቋረጥነው ሰዎችም አሁን ዳግመኛ ሕይወትን መርጠን በሕይወት ከመኖር አንከለከልም፡፡ አውራጣታችንን ይዞ ቀለም እየቀባ ‹እናንተ ከዚህ በፊት መርጣችኋል ድጋሚ መምረጥ አትችሉም!..›የሚል ከልካይ በቤተ ክርስቲያን የለም፡፡ ዲያብሎስ ግን «ጠፍቼ ጠፍቼ እመለሳለሁ?» እንድንል ወደ ኋላ ሊስበን ይሞክራልና ሕይወትን በመምረጥ የክርስቶስን መንገድ በመያዝ እናሳፍረው፡፡
 
የእግዚአብሔር ሁሉን የመቀበል፣ ይቅር የማለት ባህርይ የእኛን ድኅነት ከመሻቱ ነውና የተዘረጋልንን የምሕረት እጅ ቸል ብንል እንቀጣለን። ነገሩም እንዲህ ያለውን መዳን ቸል ብንል የሚብስ ቅጣት የሚገጥመን አይመስላችሁም? እንዳለው ነው። እርሱ ይቅር ማለት ሳይታክተውና እኛ ይቅር መባልና ይቅር በለኝ ማለትን ልንጠላ አይገባንም።
እግዚአብሔር መጪውን ጊዜ የንስሐ፤ የስምምነት፣ የፍቅርና መደማመጥ የሞላበት የአገልግሎትና የመንፈሳዊነት ዘመን ያድርግልን! አሜን!
 
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የደቡብ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ከምእመናን ጋር ተወያዩ።

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ

በሐዋሳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የተነሳው አለመግባባት አሁንም ቀጥሎ ማክሰኞ በ08/06/03 ዓ.ም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በተፈጠረው ግጭት ወጣቶችና ምእመናን ጉዳት ደርሶባቸዋል። እርሱን ተከትሎ ያለመግባባቱን ተዋናዮች ሰብስበው ያናገሩት የደቡብ ክልል ርዕሰ መስተዳድር ክቡር አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ተቃውሞን ሰላማዊ በሆነ መልኩ ብቻ መግለጥ እንደሚቻል አሳስበዋል።
 
በግጭቱ ወቅት በስፍራው እንደተገኙ የተናገሩ የዐይን ምስክር “በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በሁለት ጎራ ተለይቶ ጉባኤ ከተጀመረ ቆይቷል።” ብለው፤ ስለ ዕለቱ ክስተት ሲናገሩ “በአንደኛው ወገን የተወሰኑ ሰዎች ለጸሎት ተሰብስበው እያሉ ከቀኑ 9፡30 ሲሆን፥ ከሌላኛው ወገን በትር ይዘው በመምጣት ሁለት ልጆችን በተደጋጋሚ ሲደበድቧቸው፤ ሌላ አንዲት ምእመን ግንባሯ ላይ ተፈንክታ እንደተመለከቱ ገልጸዋል።

ከዚህ አለመግባባትና ግጭት በኋላ ከሁለቱም ወገን የተወከሉ ሃምሳ ሃምሳ ሰዎችና የሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ገብርኤል በተገኙበት ከክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ክቡር አቶ ሽፈራው ሽጉጤ ጋር ውይይት ተካሂዷል። በውይይቱ ወቅት ሁለቱም ያላቸው ሃሳብና ቅሬታ አቅርበዋል።

በአንደኛው ወገን የአለመግባባቶቹ መነሻና ሂደቶቹ የቀረቡ ሲሆን፥ በሌላኛው በኩል በአብዛኛው ሲነገሩ የነበሩት የማኅበረ ቅዱሳንን ጣልቃ ገብነት፥ እንዲሁም ማኅበሩን የመክሰስ ሁኔታዎች እንደነበር ምንጮቻችን ገልጸዋል።

ክቡር ርዕሰ መስተዳድሩ በውይይቱ ወቅት አጽንኦት ሠጥተው የገለጹት ነገር፥ ከእንግዲህ አንዲት ጠጠር በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንደማትወረወርና ማንኛውንም ተቃውሞ ሰላማዊ በሆነ መልኩ መግለጥ እንደሚቻል ነው።

አቶ ሽፈራው አያይዘውም “ሊቀ ጳጳሱ እዚህ ቦታ እስከተቀመጡ ድረስ በሀገረ ስብከታቸው የሊቀ ጳጳሱ ወሳኔ የቤተ ክርስቲያኒቱ የመጨረሻ ውሳኔ ነው፤ እርሱን ተቀብለን እንሄዳለን” በማለት አብራርተዋል።  

መነሻው ከ9 ወር በፊት አካባቢ እንደሆነ የሚነገርለት አለመግባባት፥ ቀኖና ቤተ ክርስቲያን ይጠበቅ፣ የቃለ ዓዋዲው መመሪያ ይከበር፣ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ተግባራዊ ሊሆን ይገባል፤ በሚሉና ይህንን በሚቃወሙ መካከል እንደሆነ የሲዳማ፣ አማሮና ቡርጅ ልዩ ዞኖችና ወረዳዎች ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ኅሩያን ዓለም እሸት ገ/ጻድቅ ከማኅበረ ቅዱሳን የአማርኛ መካነ ድር ጋር ባደረጉት ቆይታ መግለጻቸው ይታወሳል።

በአንድ እጅ ማጨብጨብ እንዳይሆን

ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት እና ከየአህጉረ ስብከቱ ሊቃነ ጳጳሳት የስብከተ ወንጌል ፍቃድ ሳይኖራቸው በየቤተ ክርስቲያኑ ዐውደ ምሕረት በሕዝበ ክርስቲያኑ መካከል እየተገኙ እንሰብካለን እናስተምራለን በማለት የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሥርዓትና መመሪያ በሚጥሱ  ሕገወጥ ሰባክያን፤ ከቤተ ክርስቲያን ዕውቅናና ፈቃድ ውጪ በጉባኤ ሊቃውንት ያልታዩና ያልተመረመሩ የተለያዩ የኅትመት ውጤቶች፤ መጻሕፍት፣ የስብከት የመዝሙር የምስል ወድምፅ /ኦዲዮ ቪዲዮ/ ካሴቶች እየተሠራጩ፤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን መሠረተ እምነት፣ ሥርዓትና ትውፊት የሚጥሱ ተግባራት ሲፈጸሙ ይታያል፡፡

ይህንኑ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ሥርዓትና አሠራር ውጪ የሆነ ሕገወጥ ተግባር የተገነዘበው ቅዱስ ሲኖዶስ፤ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነትና ሥርዓት አካሔድ አቅጣጫውን ሳይስት ተጠብቆ እንደቆየ ሁሉ ወደፊትም መቀጠል ስላለበት፤ የካቲት 12 ቀን 2001 ዓ. ም. ባደረገው ስብሰባ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ በቁጥር ል/ጽ/382/2001 የካቲት 16 ቀን 2001 ዓ.ም በተጻፈ ደብዳቤ፤

1ኛ. በዚህ ውሳኔ መሠረት፤ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤትና ከየአህጉረ ስብከቱ ሊቃነ ጳጳሳት የስብከተ ወንጌል ፈቃድ ሳይኖራቸው እንዳይሰብኩ በቅዱስ ሲኖዶስ የተከለከለ ስለሆነ፤ የቅዱስ ሲኖዶስ መመሪያ ከሀገረ ስብከት እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን በየደረጃው ባለው መዋቅር ተግባራዊ እንዲሆን፤

2ኛ. የእያንዳንዱ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ የተጣለበትን ሓላፊነት ተገንዝቦ የመቆጣጠሩን ተግባር በማጠናከር የቤተ ክርስቲያኒቱን ህልውና ከሚፈታተን ተግባር    እንዲጠብቅ፤

3ኛ. በጉባኤ ሊቃውንት ተመርምረው ዕውቅና ሳይሰጣቸው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰም የሚሠራጩ የኅትመት ውጤቶች፤ መጻሕፍት፣ በምስል ወድምፅ /ኦዲዮ ቪዲዮ/ የተዘጋጁ ስብከቶች መዝሙሮች ጥብቅ ቁጥጥር እንዲደረግባቸው፤

4ኛ. በስብከተ ወንጌል ትምህርት አሰጣጡና በሥርጭቱ ረገድ በቁጥጥሩ የሥራ ሒደት አፈጻጸም ወቅት ከቤተ ክርስቲያኒቱ ዕውቅናና ፈቃድ ውጪ የሆነ ከአቅም በላይ ችግር ሲያጋጥም ለሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ጭምር በመግለጽ ችግሩ ሕጋዊ መፍትሔ እንዲያገኝ፤ በማለት መመሪያ ማስተላለፉ ይታወቃል፡፡

ይህንኑ ተከትሎ በአሁኑ ወቅት ጐልተው የሚታዩትን የስብከተ ወንጌል ችግሮች ለመፍታት የሚያስችል ሴሚናር፤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ አዘጋጅነት መስከረም 11 እና 12 ቀን 2003 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሽ መካሔዱም ይታወሳል፡፡

በዚህ ቅዱስ ፓትርያሪኩ በተገኙበትና መመሪያ ባስተላለፉበት፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ በየአህጉረ ስብከቱ፣ አድባራትና ገዳማቱ ስብከተ ወንጌልን በማሰፋፋት ረገድ ዐቢይ ሚና ያላቸው ሓላፊዎች፣ ሰባክያንና ዘማርያን በተሳተፉበት ውይይት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓትና አሠራር ተጠብቆ መንፈሳዊ አገልግሎቷም በአግባቡ እንዲፈጸም የሚረዱ ውሳኔዎችም ተወስነዋል፡፡

የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሥርዓትና አሠራር ለማስጠበቅ የተላለፉትን መመሪያዎች በማስፈጸም ረገድ በጠቅላይ ቤተክህነት የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ በርካታ ሥራዎችን አከናውኗል፡፡

በየአህጉረ ስብከቱ ስምሪት በማድረግ ከሚመለከታቸው ሓላፊዎች፣ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት አስተባባሪዎችና መምህራነ ወንጌል በአጠቃላይ ከደቀ መዛሙርት አገልጋዮች ጋር በተካሔዱ ተከታታይ ውይይቶች የተደረሰበት የጋራ ግንዛቤ ለአፈጻጸሙ አጋዥ ኃይል ሆኗል፡፡ በመምሪያው ሥር በሚያገለግሉ ሊቃነ ካህናት አማካኝነት በየአህጉረ ስብከቱ በርካታ የስብከተ ወንጌል ጉባኤያት ተካሒደዋል፡፡

ማእከላዊነቱን የጠበቀ የቤተ ክርስቲያኒቱ አንድ ድምፅ ወጥ ለሆነው የስብከተ ወንጌል አገልግሎት መስፋፋት መሠረት ነው፡፡ ስለዚህ ከቀደሙት አባቶች የተረከብነው የቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅራዊ ቅብብሎሽ እንደተጠበቀ ዶግማዋ፣ ቀኖናዋና ትውፊቷ ወደፊትም ለትውልድ እንዲተላለፍ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያው ከፍተኛ እንቅሰቃሴ እያደረገ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱ መምህራነ ወንጌልም ሥርዓትና መመሪያውን ጠብቀው መንፈሳዊ ተልእኮአቸውን እየፈጸሙ ሲሆን፤ መምሪያው ስብከተ ወንጌልን በማስፋፋት ረገድ ከሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያን አካላት ጋር አብሮ በመሥራት ላይ ይገኛል፡፡

በስብከተ ወንጌሉ አገልግሎት ረገድ አበረታች ጥረት እየተደረገ ቢታይም፤ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት መሠረት፤ የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔና መመሪያ በተሟላ ሁኔታ ተግባራዊ ለማድረግ በአንዳንድ አህጉረ ስብከት ችግሮች እያጋጠሙ ነው፡፡ ለምሳሌ በቅርቡ በሐዋሳ ከተማ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ከጥር 20-22 ቀን 2003 ዓ.ም እንዲካሔድ ለተዘጋጀ ጉባኤ የሲዳማ ጌዲኦ፣ አማሮና ቡርጂ አህጉረ ስብከት ለጠቅላይ ቤተክህነት ስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ መምህራነ ወንጌል እንዲላኩለት ባቀረበው ጥያቄ መሠረት የተላኩት ሦስት መምህራን በተከሠተው ችግር ምክንያት የተላኩበትን የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ሳይፈጽሙ ለመመለስ ተገደዋል፡፡ ይህ ሁኔታ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተቃና መንፈሳዊ አገልግሎት አካሔድ ላይ እንቅፋት የሚፈጥር አሳዛኝ ድርጊት ነው፡፡

ለችግሩ ምክንያት የሆኑትም የራሳቸውን ዓላማና ፍላጐት ለማስፈጸም የሚያስቡና የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ዓላማ ያልተረዱ የተወሰኑ አካላት እንደሆኑ ከስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያው እና ከሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መግለጫ ለመረዳት ይቻላል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ከቤተ ክርስቲያን ዕውቅናና ፈቃድ ውጪ ስለሚሠራጩ የኅትመት ውጤቶች፤ መጻሕፍት፣ የስብከትና መዝሙር የምስል እና ድምፅ ካሴቶች የተላለፈው መመሪያ በአግባቡ ተፈጻሚ አለመሆኑን ከመምሪያው ሓላፊ ገለጻ እንገነዘባለን፡፡

በእርግጥ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቅድሚያ ትኩረቷ በማስተማርና በመምከር ወደ መልካም መንገድ መመለስ እንደመሆኑ ይህንኑ ተግባሯን ትፈጽማለች፡፡ ሆኖም የቅድስት ቤተ ክርስቲያን እውነተኛ ልጆች አገልጋዮቿና ምእመናን ሁሉ ትምህርቷን ሰምተው፣ ሥርዓቷን   ጠብቀውና መመሪያዋን አክብረው የሚጠበቅባቸውን ሁሉ በአግባቡ መፈጸም ደግሞ ሃይማኖታዊ ግዴታቸው እንደሆነም የሚታወቅ ጉዳይ ነው፡፡

ከዚህ ቀደም በጠቅላይ ቤተክህነት ደረጃ በመምሪያው የተዘጋጀው ሴሚናርና፤ በየአህጉረ ስብከቱ በተደረገው ስምሪት የተካሔደው ውይይት በየደረጃው በሚገኙ ሓላፊዎች፣ ሊቃውንትና ሰባክያነ ወንጌል ዘንድ የጋራ ግንዛቤ እንዲኖር አስችሏል፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔና መመሪያዎች እንዲሁም የስብከተ ወንጌሉን አሠራርና ሥርዓቱን የጠበቀ አፈጻጸም በማስተዋወቅ ረገድ ጠቀሜታው እጅግ የጐላ ነው፡፡

እንዲህ ዓይነቱ በየደረጃው የሚካሔደው ውይይትና ተከታታይነት ያለው ተግባራዊ እንቅስቃሴ በየአህጉረ ስብከቱ እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን የሚገኙ አባቶች መምህራነ ወንጌልና አገልጋዮች ዘንድ የጋራ ግንዛቤና የተቀናጀ አሠራር ለማምጣት ከፍተኛ ጠቀሜታ ስላለው ወደፊትም ይህ ጥረት ተጠናክሮ መቀጠል ይኖርበታል፡፡

የቤተ ክርስቲያኒቷን ሐዋርያዊ ተልእኮ ለማሳካት ሥርዓቷን፣ መዋቅርና አሠራሯን አክብረውና ጠብቀው በየዘርፉ ለተሰማሩ አገልጋዮቿ ሁሉ ስለአገልግሎታቸው ሪፖርት ማቅረብ፤ ያከናወኑትን ተግባር አፈጻጸማቸውንና የአገልግሎታቸውን ውጤት መገምገም፤ በአጋጠሙ ችግሮች ላይ መወያየትና መፍትሔ መፈለግ፤ የወደፊቱን የአገልግሎት አቅጣጫ መተለም እና ማቀድ አስፈላጊ ነው፡፡ ይህ ሲሆን የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሥርዓትና መዋቅር ማስጠበቅ፣ መመሪያና አሠራሯ የበለጠ ውጤታማ እንዲሆን ለማድረግ ይቻላል፡፡ ከቤተ ክርስቲያኒቷ ሥርዓትና አሠራር ውጪ የሚሆኑትንም በአግባቡ ተከታትሎ በወቅቱ ለማረምና ለማስተካከል አመቺ ይሆናል፡፡

ሁላችንም የምንፈልገው ትክክለኛ አሠራርና መልካም ውጤት እንዲመጣ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔና መመሪያ እንዲሁም የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ጥረት ብቻውን በቂ እንደማይሆን እንገነዘባለን፡፡

ለውሳኔዎቹና ለሚተላለፉት መመሪያዎች ተግባራዊ አፈጻጸም መሟላት የሚገባቸው አስፈላጊ ነገሮች ካልተሟሉ ውሳኔውም ሆነ መመሪያው በወረቀት፤ ዕቅዱም በሐሳብ ብቻ ተወስነው ይቀራሉ፡፡

የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሥርዓትና አሠራር አክብሮና ተከትሎ ስብከተ ወንጌልን ማስፋፋት ሌሎች ዘርፈ ብዙ መንፈሳዊ አገልግሎቷን ማስፈጸምም ሆነ መፈጸም ከጠቅላይ ቤተክህነት ጀምሮ እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን በተለያዩ ደረጃዎች የሚገኙ ሓላፊዎች፣ አባቶችና አገልጋዮች ሁሉ ቀዳሚ የሓላፊነት ግዴታቻው መሆኑ ይታወቃል፡፡ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት አክብረው የሚሠሩ ለሐዋርያዊ ተልእኮዋ መሳካት የበኩላቸውን ድርሻ የሚያበረክቱ፤ የተለያዩ ኅትመት ውጤቶች መጻሕፍት፣ የስብከተ ወንጌልና መዝሙር አዘጋጆች፣ ሰባክያነ፣ ዘማርያን፣ አሳታሚና አከፋፋዮች የአገልግሎቱ አካላት እንደመሆናቸው፤ የስብከተ ወንጌል መምሪያው በቤተ ክርስቲያን አሠሪርና መመሪያዎች ላይ በማወያየት የጋራ ግንዛቤ እንዲኖር መሥራት አለበት፡፡ እነሱም የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት እንዲጠበቅ የበኩላቸውን ክርስቲያናዊ ሓላፊነት ይወጡ ዘንድ ይገባልና፡፡ ምእመናንም እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነታቸው የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሥርዓትና መመሪያ በሚገባ የመፈጸም የልጅነት ድርሻና ሃይማኖታዊ ግዴታ አለባቸው፡፡

እያንዳንዱ የአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ፤ በአጥቢያው የቤተ ክርስቲያኒቷን ዘርፈ ብዙ መንፈሳዊ አገልግሎት በተሳካ ሁኔታ እንዲፈጸም፣ ምእመናን በቤተ ክርስቲያናቸው ላይ ያላቸው እምነትና ተስፋ እንዲጠነክር፣ በሰላምና በፍቅር በተረጋጋ ሁኔታ የአገልገሎቷ ተጠቃሚዎች እንዲሆኑና ለዘለዓለማዊ ሕይወት እንዲበቁ፣ እንዲሁም የልጅነት ድርሻቸውን እንዲወጡ በማድረግ ረገድ፤ በመምራት፣ በማስተባበር፣ በቅርብ ሆኖ በመከታተል የተቃና እንዲሆን የተጣለበት አባታዊና መንፈሳዊ ሓላፊነት እጅግ ታላቅ ነው፡፡ ይህ ታላቅ መንፈሳዊ ሓላፊነት ከግል አሳብና አመለካከት ይልቅ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ዓላማ ቅድሚያ ሰጥተው እንዲያስፈጽሙ የሚያስገድዳቸው እንደሆነ እንገነዘባለን፡፡

ስለዚህ በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔና መመሪያ ላይ እንደተገለጸው፤ የአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪዎች የተጣለባቸውን ሓላፊነት ተገንዝበው በሚገባ የመምራትና የማስተባበር እንዲሁም የመቆጣጠሩን ተግባር በማጠናከር የቤተ ክርስቲያኒቱን ህልውና ከሚፈታተን ተግባር መጠበቅ አለባቸው፡፡

ምእመናንም ትክክለኛውን የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በመቀበል፣ ሥርዓትና መመሪያዋን በአግባቡ በመፈጸም በሰላምና በፍቅር ሃይማኖታዊ የልጅነት ድርሻቸውን መወጣት ይገባቸዋል፡፡

አሁን ባለንበት ዘመን የቴክኖሎጂው እድገትና ተደራሽነት አመቺ በሆነበት እና የሕዝቡም ፍላጐትና ጥያቄ በዚያው መጠን በጨመረበት ወቅት፤ እጅግ በርካታ የኅትመት ውጤቶች፤ መጻሕፍት፣ የስብከትና የመዝሙር የምስል እና የድምፅ ካሴቶች /ኦዲዮ ቪዲዮ/ እየተዘጋጁ መቅረባቸው አስፈላጊነቱ አያጠያይቅም፡፡

ስለዚህ የቤተ ክርስቲያኒቱን አሠራር ዘመናዊና ቀልጣፋ በማድረግ፤ ሊቃውንቱንና በሙያው የተዘጋጁ ብቁ ባለሙያ የሰው ኃይል ማሠማራት፣ አስፈላጊውን የአገልግሎት መሣሪያ ማሟላትና በቂ በጀት መመደብ ያስፈልጋል፡፡ ይህ ሲሆን የቤተ ክርስቲያኒቱን ሥርዓት ጠብቀው ለተዘጋጁ የኅትመት ውጤቶች መጻሕፍት፣ የስብከትና መዝሙር ካሴቶች የዕውቅናና ፍቃድ ጥያቄ አፋጣኝ ምላሽና የተቀላጠፈ አገልግሎት ለመስጠት ይቻላል፡፡

ይህንን ለማስፈጸም የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያው ብቸኛ ጥረት ብቻ በቂ እንደማይሆን ይታመናል፡፡

ስለዚህ ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ የጠቅላይ ቤተክህነት ሓላፊዎችና በየደረጃው ያሉ የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ ትኩረትና ተግባራዊ ተሳትፎ ያስፈልጋል፡፡ መምሪያው    የተሰጠውን ተግባርና ሓላፊነት በብቃት እንዲያከናውን የቅርብ ክትትል ማድረግ፣ አፈጻጸሙን እየተከታተሉ በመገምገም አስፈላጊውን ሁሉ ማሟላት ይገባል፡፡ ምክንያቱም የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዶግማ፣ ሥርዓት እና አስተምህሮ እንዲሁም ወጥ የሆነው መዋቅራዊ አሠራሯ     ባልተከበረና በተጣሰ ቁጥር የቤተ ክርስቲያኗ ህልውና አጠያያቂ ሊሆን ይችላል፡፡ ለመናፍቃን ሥውር ተልእኮ ምእመናንን ሊያጋልጣቸው ይችላል፡፡ የግል ፍላጐትና ጥቅማቸውን ለማስጠበቅ የሚንቀሳቀሱ ጥቂት ግለሰቦችም የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን የምሕረት ዐደባባይ ያለአግባቡ እንዲጠቀሙበት ዕድል ይሰጣል፡፡ ስለዚህ የመምሪያው ጥረት ብቻውን በአንድ እጅ ማጨብጨብ እንዳይሆን  ትኩረት ሊሰጠው ይገባል እንላለን፡፡

ምንጭ፡ስምዐ ጽድቅ ከየካቲት 1-15/2003 ዓ.ም.

ወስብሐት ለእግዚአብሔር
hawassakidusgebrieltiks.jpg

“የእኛ ግዴታ ሲኖዶስ ያወጣውን ሕግ ማስከበር ነው” ሊቀ ኅሩያን ዓለም እሸት ገ/ጻድቅ

በተ/ሥላሴ ጸጋ ኪሮስ   

hawassakidusgebrieltiks.jpgባለፈው ጊዜ በሐዋሳ ከተማ በተለይም ደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የተፈጠሩትን ጉዳዮች አስመልክቶ ከሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ኅሩያን ዓለም እሸት ገ/ጻድቅ ጋር ያደረግነውን ውይይት የመጀመሪያ ክፍል የሐዋሳ ጉዳይ 1 በሚል ርዕስ አቅርበንላችሁ ነበር። የውይይታችን ቀጣይ ክፍል ደግሞ እነሆ፤ መልካም ንባብ። (ፎቶ፦ ሐዋሳ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ግቢ ውስጥ ከሚገኙት ጥቅሶች መካከል)

•    በብፁዕነታቸው መልካም ፈቃድና በሀገረ ስብከቱ ጥረት እርቅ እንደተካሄደ ይታወቃል። የእርቁ ሂደት እንዴት ነው? ከእርቁ በኋላ አለመግባባቶች እንዴት ሊፈጠሩ ቻሉ?

እንግዲህ በኛ በኩል እርቁ አልፈረሰም እንደተጠበቀና እንዳለ ነው፡፡ የዕርቅ ስምምነት የተባለው፤ የተጣላ ኖሮ አንተ ይህን አድርገሀል አንተ ይህን አድርገሀል ተብሎ እርስ በእርሱ የተጣላ ኖሮ አይደለም። ዋናው የቤተ ክርስቲያኒቱ መመሪያና ደንብ አልተከበረም ነው፡፡ ይህንን በሚመለከት በመንግሥት አካላት በኩልም የቤተ ክርስቲያኒቱን ደንብና መመሪያ እንዲያውቁት፥ ግንዛቤ እንዲኖር፥ በታዛቢነትም ተገኘተው ደግሞ የራሳቸውን ሀሳብና አስተያየት እንዲለግሱን አድርገናል። ይህን ከማድረግ አኳያ ከሁሉም የኅብረተሰብ ክፍል ማለትም ከአገር ሽማግሌዎች፣ ከሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች፣ ከሰበካው ጉባኤውና ከልማት ኮሚቴ ከሚመለከታቸው ክፍሎች ሁሉ የተውጣጡ አካላት ባሉበት፥ ከመንግሥት አካላትም በታዛቢነት አድርገን ባለ ሰባት ነጥብ የያዘ የእርቅ ሰነድ ወይም ውሳኔ የሚባለውን ያዘጋጀነው፡፡

ውሳኔውና የእርቅ ሰነዱ ብዙ ነገሮች ሲኖሩት ሌላው ሁሉ እንዳለ ሆኖ፥ ጠቅለል ባለ መልክ ሁሉም ነገር በቃለ አዋዲው እና በቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግና መመሪያ መሠረት እንዲሠራ የሚል ነው፡፡ በተለይ ደግሞ በእርቅ ሰነዱ ሰባተኛው እና የመጨረሻው ተራ ቁጥር ላይ ሰባክያንና ዘማርያንን የተመለከተ ነው፤ አብዛኛውን ጊዜ ችግር የሚያመጣውና አለመግባባት የሚያስከትለው ጉዳይ እሱ ነው፡፡ ምክንያቱም ሰዎች ይነሳሱና እነ እከሌ መስበክ አለባቸው ይላሉ፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳደርና አካሄድ ደግሞ ይህን አይፈልግም፥ ስለዚህ አሁን እገሌ ይስበክ እገሌ አይስበክ ሳይሆን፥ የሚሰብክ ሰው በቤተ ክህነቱ ሕጋዊ እውቅና ኖሮት ይስበክ የሚል ነው፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ ምሳሌው አይሄድም እንጂ ፈቃድ ሲባል እንደ ንግድ ፈቃድ ወይም እንደ ቀበሌ መታወቂያ አንድ ጊዜ የሚሰጥ አይደለም። አንድ ጉባኤ፣ ክብረ በዓል ሲኖር ወይም ወደ አንድ ቦታ ላይ ተጉዞ የወንጌል ማስተማር ጉባኤም ካለ፥ ለዚያ ጉባኤ እገሌ የተባለ ሰባኬ ወንጌል ወይም መምህር እንዲያስተምር የሚል ደብደቤ መኖር አለበት ነው፡፡ ያን ደብዳቤ የሚጽፈው ደግሞ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል እና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ ወይም ደግሞ የሀገረ ስብከቱ ጽሕፈት ቤቱ ሊሆን ይችላል። በዚህ መልኩ ነው ሥራው መሠራት ያለበት፡፡ እነዚህን የመሳሰሉት ውሳኔዎች በእርቅ ሰነዱ ላይ ተካተው ከክልሉ መስተዳድር ጀምሮ ለሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ተላልፏል፤ የመንግሥት አካላትም በታዛቢነት በተገኙበት ሕጉን አስረግጠን ነግረን በግልጽ በጉባኤ ተነቧል። በተለይም ሰባክያንን፣ ዘማርያንን፣ ባሕታውያንንና የመሳሰሉትን በሚመለከት ቅድም እንዳልኩት በብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ ፊርማ ለመላው አህጉረ ስብከት የተላለፈው መመሪያ በሚገባ ተነብቦ፣ ተገለጾ፣ ታይቶ መመሪያው ተጠብቆ በሲኖዶስ ውሳኔ መሠረት እንዲሠራ፤ እንዲሁም በተለይ በሀገረ ስብከቱ ክልል ባሉ አብያተ ክርስቲያናት ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ወይም ከሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ያልተፈቀደለት አካል በቤተ ክርስቲያኒቱ አውደ ምሕረት ሲቆም ሀገረ ስብከቱ ጥብቅ ቁጥጥር እንዲያደርግ የሚል ሰፍሯል። ስለዚህ የእኛ ትግል የሲኖዶስን መመሪያ ተግባራዊ ለማድረግ ነው ማለት ነው። በዚያ መሠረት ነው የምንሠራው። የእርቅ ሰነዱ ውሳኔ ከተላለፈ በኋላም ምንም ዓይነት ጭቅጭቅም ሁከትም አልነበረም።

ከጊዜ በኋላ እንግዲህ አሁንም ሰዎች እነ እገሌ የሚባሉት ሰባክያን ይምጡ፣ ዘማርያን ይምጡ፣ እነ እገሌ ይምጡ ማለት ጀመሩ። ቤተ ክህነቱ ደግሞ በሕጋዊ መንገድ ፈቅዶ የሚልካቸው መምህራንና ሰባኪያን አሉ፡፡ ሰዎችን ይምጡልን ቢሉም ቤተ  ክህነቱ ደግሞ እኔ እነዚህን ነው የማሰማራው ብሎ ልኳል፡፡ ሀገረ ስብከቱ እንደ ተዋረድ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት የሚተላለፍለትን መመሪያ የመፈፀምና የማስፈጸም ግዴታ አለበት፡፡ ይሄ ለምን ሆነ? ይሄ አይሆንም ማለት ሕጉም ሥርዓቱም አያስኬድም። በዚህ ምክንያት እንግዲህ እነ እገሌ ካልሰበኩ ወይም እኛ ካልሰበክን በሚል አንዳንድ ሰዎች ተነሥተዋል፡፡ ያው እነዚያ በግል ማለት ነው፡፡ አሁንም ግን የመላው ምእመንና ካህናቱ አመለካከት የውሳኔ ሰነዱ፣ ቃለ ዐዋዲው ይከበር፤ ለሀገረ ስብከቱ አቅርቦ ሲፈቀድለት ይሰማራ ነው፡፡ ይሄንን ሳያቀርቡ ደግሞ እራሳችንን እናሰማራ የሚሉ ክፍሎች ሲነሱ፤ ይሄ አይሆንም፥ ይሄ መደረግ የለበትም በሚል ነው አለመግባባቱ የተፈጠረው፡፡ ከዚህ አንጻር ነው እንጂ እርቅ የፈረሰ ነገር የለም እርቁም ደግሞ የቤተክርስቲያኒቱን መመሪያ ጠብቀን እንሂድ፤ ሁላችንም ለቤተ ክርስቲያንቱ መመሪያ ተገዥ እንሁን የሚል ውሳኔ ነው እንጂ እገሌና እገሌ ተጣልተው የሚል የግል ጥላቻ በዚህ ላይ የለውም፡፡ የቤተ ክርስቲያንኒቱን መመሪያ ግን በጋራ እናክብር፡፡ መንግሥትም መመሪያውንም ውሳኔውንም አውቆታል፤ ይሄ ውሳኔ ለብፁዕ ቅዱስ ፓትርያርክ ልዩ ጽ/ቤት፣ ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌልና ሐዋሪያዊ ተልእኮ መምሪያ በግልባጭ ደርሷል። በቃ ያንኑ የነበረውን መመሪያና ሕጉን የሚያጸና እንጂ የተለያየ ነገር የለውም። ይሄ ከተባለ በኋላ ግን አሁንም ሰዎች እንደግል ፍላጎታቸው እንዲህ ካልሆነ የሚሉ ሲነሱ አይ ይሄማ ከሕግ ውጪ ነው የሚል ነው ያለው ማለት ነው እንጂ የእርቅ መፍረስ አይደለም።

•    ታዲያ ከዚህ ውሳኔ በኋላ አለመግባባቶችና ግጭቶች አልተነሱም ብለው ያስባሉ?

እንግዲህ አንዳንድ ሰባክያን እኛ እንሰብካለን፣ እኛ እንዲህ እናደርጋለን ብለው የሚሉት አብዛኛውን ወሬው የሚወራው በውጪ ነው፡፡ አንዳንዴ ግን ያልተፈቀደላቸው ሰዎች ወይም ያልተመደቡ ሰባክያን ወይም ቤተ ክህነቱ ያላሰማራቸው ዘማርያን ሆኑ ሰባክያን ወደ ዐውደ ምሕረቱ ሲመጡ፥ የለም፤ ይሄ አይደለም፤ ይላል ምእመኑ። ምእመኑ ነው መመሪያውን የሚያስከብረው። ይሄ ሰባኪ አይደለም የተመደበው ይላል። በዚህ ጊዜ የግድ አለመግባባቶች ይመጣሉ።

ሕጉ፣ መመሪያው፣ የሲኖዶሱ ደንብ፣ ቃለ አዋዲውና ሕገ ቤተ ክርስቲያኑ በአግባቡ በሥራ ላይ ይዋል ሲባል፥ የለም እኛ በፈቀድነው መሆን አለበት የሚሉ ክፍሎች ደግሞ ከተነሱ፥ ይኼማ የቤተ ክርስቲያናችን መመሪያዋ አይደለም የሚሉ ክፍሎች ይነሳሉ። በዚህ ጊዜ መቼም የሀሳብ አለመጣጣም አለመግባባት ግድ ይከሰታል። ያን ሲሆን ደግሞ ችግር ሊፈጠር ይችላል። ነገር ግን ያው ዞሮ ዞሮ ችግሮች ሲፈጠሩ በመንፈሳዊነት ሚዛን ይታያል። እንደ ሕግ የሚታየው ደግሞ በሕግ ይታያል። በዚህ ዓይነት ታይቶ እልባት እንዲያገኝ ይደረጋል፡፡

•    በሀገረ ስብከቱ በኩል የወደፊት ዕቅዳችሁ ምንድን ነው?

እንግዲህ ለወደፊቱ እግዚአብሔር ፈቃዱ ቢሆን ከፍተኛው ሥራ ያለው ከታች ስለሆነ ያለው 13ቱንም የወረዳ ቤተ ክህነቶች በተሻለ መልኩ በተሟላ የሰው ኃይል የማጠናከር፥ ባለፈው ለወረዳ ሊቃነ ካህናት፣ ለርእሰ ከተማው አድባራት አስተዳዳሪዎችና ሰበካ ጉበኤያት በተቻለ መልኩ ትምህርታዊ ሴሚናር ለመስጠት ተሞክሯል። በቀጣይነት ደግሞ በሂደት ለእያንዳንዱ ወረዳ ቤተክህነት መርሐ ግብር ወጥቶ፥ በወረዳው ሥር ያሉ አብያተ ክርስትያናትን፣ የአብያተ ክርስቲያናት አስተዳዳሪዎችን፣ የሰበካ ጉባኤ አባላትን፣ ሰባክያነ ወንጌልና ካህናትን አሳታፊ ያደረገ፥ የቃለ ዐዋዲውን መመሪያና ሕገ ደንብ በተመለከተ፣ የቃለ ዐዋዲውን ሕግና ደንብ በማይነካ መልኩ ቤተ ክርስቲያኒቱ በልማትና ሁለንተናዊ ሥራዎች ላይ ማከናወን ያለባትና ዘመኑን የተከተለ ዘመናዊ አስተዳደርና የሥራ ሁኔታዎችን በሚመለከት፥ እንደዚሁም ደግሞ የበጀትና የሂሳብ አያያዝ፣ የንብረት ጥበቃና አመዘጋገብን፣ የቅርሶች ምዝገባንና የመሳሰሉትን ሁሉ በየጊዜው ተከታታይ ስብሰባዎችን በማድረግ ሴሚናሮችን መስጠት አስበናል።

በወረዳ ደረጃ የተሰጠው ሴሚናር በአጠቢያው ሥር ላሉ ደግሞ ካልተሰጠ ሥራው ሁለት ዓይነት ስለሚሆን በየወረዳው ሥር ያሉትን አጥቢያ ቤተ ክርስቲያናትን በየወረዳው ርእሰ ከተማ አቅም በፈቀደ መጠን ሴሚናሩ እዚያ ደርሶ ይህንን ሥልጠና መስጠት የመጀመሪያ እቅዳችን ነው፡፡

ከዚሁ ጋር ደግሞ ያው በሀገረ ስብከቱ ሥር በሚተዳደረው የደ/ታ/ቅ/ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን አጠገብ የካህናት ማሠልጠኛ ትምህርት ቤት አለን። በዚህ የካህናት ማሰለጠኛ ትምህርት ቤት ያለንን በጀት በመጠቀም ካህናትን እናሠለጥናለን። የሠለጠኑት ካህናትም ወደ ነበሩበት አጥቢያ ቤተ ክርስቲያናት እየተመለሱ ምእመናኑን በስብከተ ወንጌልና በመሳሰለው ሁሉ እንዲያገለግሉ የማድረጉን ሥራ አጠናክረን እንቀጥላለን።

እንግዲህ ደቡብ ክልል ወደ 56 የሚጠጉ ብሔር ብሔረሰቦችን ያቀፈ ክልል ነው። የተለያዩ ብሔር ብሔረሰቦች ተወላጅ የሆኑ እና የየብሔረሰቡን ቋንቋ የሚናገሩ የተወሰኑ ሕፃናትን በማሰባሰብ ለማስተማር ጥረት እያደረግን ነው። ለምሳሌ አሁን 12 ያህል ህፃናት አሉን። ሀገረ ስብከቱ ከኛ ቀደም ብሎ ወደዚሁ ማሠልጠኛ አምጥቶ ትምህርት ቤት ከፍቶ፥ መንፈሳዊውን ትምህርት ማለትም ከፊደል ቆጠራ ጀመሮ እስከ ሥርዓተ ቅዳሴ ሌላም ሌላም የመሳሰሉትን መንፈሳዊ ትምህርት እያስተማረ አሁን ለዲቁና የሚያበቃ ትመህርት ተምረው የሚገኙና በቅዳሴ አገለግሎት ላይ የሚገኙ አሉ። እነዚህ ልጆች ለጊዜው ቁጥራቸው 12 ቢሆንም ይሄ 12 የሆነው ቁጥር ወደ 24 ወደ 36 ብሎም ወደ 72 እንዲያድግ ቁጥሩ እየጨመረ የሚሄድበትን መንገድ ለመፍጠር ጥረት ይደረጋል።

እነዚህ ልጆች ደግሞ ከየብሔረሰቡ የተወጣጡና የየብሔረሰቡን ቋንቋ የሚችሉ እንደ መሆናቸው መጠን ወንጌልን በየቋንቋቸው ለማስተማር ይረዳቸዋል። ኅብረተሰቡም ይቀበላቸዋል። ከመንፈሳዊው ትምህርት ጎን ለጎን ዘመናዊ ትምህርትም እየተማሩ ነው። ይሄን በሚማሩ ጊዜ አንዳንድ በጎ አድራጊዎች ከሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት ጋር በመተባበር የሚቻለውን ድጋፍ በማድረግ ቀለባቸውን፣ ልብሳቸውን የትምህርት ቁሳቁስና የመሳሰሉትን ወጪ አድርጎ ዘመናዊውን ትምህርት ያስተምራቸዋል፡፡ ከመንፈሳዊውና አለማዊው ትምህርታቸው በተጨማሪ በቅዱስ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን ደግሞ በዲቁና ያገለግላሉ። ሥርዓተ ቤተክርስቲያንን፣ እንዲሁ አገለግሎትንም በኪዳንና በመሳሰለው እየተለማመዱትም ይገኛሉ ማለት ነው።

የነዚህ ልጆች ወደዚህ ማሠልጠኛ ገብቶ የማደግና የመማሩ ጉዳይ በብፁዕነታቸው ትኩረት ተሰጥቶበታል። እንግዲህ ይህን ሥልጠና ለማድረግ ቁጥራቸውንም ለመጨመር በጀት ያስፈልጋል፤ ሥራዎች ሁሌም የሚሠሩት በበጀት ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን በጀቷ ምእመናን ናቸው፡፡ በዚሁ በሐዋሳ ያሉ አንዳንድ ምእመናን ለልጆቹ የተቻላቸውን ያህል  የሚያደርጉ አሉ። ወደፊት ደግሞ ፕሮፖዛል ቀርፀን፣ እቅድ አውጥተን፣ በጎ አድራጊዎችንም በማስተባበር፣ እርዳታ ሰጪ ክፍሎችንም በማፈላለግ ለመንቀሳቀስ አስበናል። ማኅበረ ቅዱሳንም በዚህ በኩል ይረዳናል የሚል ተስፋ አለን። እንዲሁም  ማሠልጠኛው ራሱን ችሎ እንዲንቀሳቀስ የልማት ሥራዎችን በፕሮጀክት ቀርፀን ለመሥራት አስበናል። እንዲህ ዓይነት ሥራዎችን የምናከናውነው የሀገረ ስብከቱ ጽ/ቤት እስከ ገጠሪቱ ቤተ ክርስቲያን ያለው በቃለ አዋዲው ድንጋጌ የሠፈረው የሥራ እንቅስቃሴ እንዳለና እንደተጠበቀ ሆኖ ማለት ነው፡፡ ያኛው እንዳለና እንደ ተጠበቀ ሆኖ ሌላው እቅዳችን ደግሞ በተለይ በቤተ ክርስትያኒቱ ተተኪ ትውልድ የመፍጠርና የመተካት፥ የዛሬው ትውልድ የነገይቱ የቤተ ክርስቲያን ተረካቢ እንዲሆን የማስቻል፥ የቤተ ክርስቲያኒቱ አገልግሉት በጥንካሬና በስፋት ቀጣይነት እንዲኖረው የማድረግ፥ ለነገይቱ ቤተ ክርስቲያን በትምህርት ሰዎችን የማዘጋጀት እና ተተኪዎችን የማፍራቱን ጉዳይ ከምንግዜውም የበለጠ አቅም በፈቀደ መጠን አጠንክረን ለመሥራት ነው፡፡

•    በመጨረሻ የሚያስተላለፋት መልእክት ካለ?

እንግዲህ በሲዳማ አማሮና ቡርጂ ልዩ ዞኖች እና ወረዳዎች ሀገረ ስብከት ለሚገኙ ለመላው ካህናትና ምእመናን በሀገረ ስብከታችን ጽ/ቤት ስም የማስተላልፈው መልእክት፤ አሁንም የቤተ ክርስትያኒቱን ሁለንተናዊ መንፈሳዊ፣ የልማት እና የሥራ እንቅስቃሴ ተባብረን ሁሉንም ለማከናወን እንድንችል መላው ምእመናን እና ካህናት የቅዱስ ሲኖዶሱን ውሳኔ እና መመሪያ፥ የቃለ አዋዲውን ድንጋጌ እና ደንብ ጠብቀን ቤተ ክርስቲያኒቱ በቅዱስ ሲኖዶስ አማካኝነት በተዋረድ በምታስተላለፍልን መሠረት ሕጓን ጠብቀን አክብረን ተባብረን እንድናገለግልና እንድናስገለግል ነው። ወደ ፊት ስብከተ ወንጌል እንዲስፋፋ፥ ሰንበት ትምህርት ቤቶች እንዲጠናከሩና ቤተ ክርስቲያናችን በልማት ልትጠናከር ያስፈልጋል።

ምእመናን ደግሞ በዕውቀታቸው በገንዘባቸውና በጉልበታቸው አብያተ ክርስቲያናትን በማስፋፋት፣ በማሳነጽና በማሠራት እንዲተጉ አሳስባለሁ። ሀገረ ስብከቱም ጠቅላላ ሥራውን የሚያከናውነው  ከካህናትና ምእመናን ጋር ነውና፥ ካህናቱም ስብከተ ወንጌልን በማስፋፋት፥ መንፈሳዊ አገለግሎትን አጠናክሮ በመቀጠልና ልማትም በቤተ ክርስቲያን እንዲስፋፋ በማድረግ ሊተጉ ይገባል። ምእመናኑ እውነት በመንገር ማሳሰብ ብቻ ነው የሚፈለጉት። በእውነት ይሄ ቀረ የማይባል ከፍተኛ ሥራ የሚሠሩ በርካታ ምእመናን አሉ። በእውነት ከተነገረና ካሳሰቡአቸው፥ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናን ለቤተ ክርስቲያናቸው ወደኋላ የሚሉበት አንድም ነገር የለም። ስለዚህ ከኛ የሚጠበቀው መንገርና ማስረዳት ብቻ ነው። እኛም የሚቻለንን ያህል እግዚአብሔር እንደፈቀደ ለማስረዳት ለመንገር እንሞክራለን። አሁንም እየነገርን እያሳሰብን ነው፤ ምዕመናኑም እየሰሙን ነው፡፡ ስለዚህ መላው ምእመናንና ካህናት ተባብረን ስብከተ ወንጌሉንም እንድናስፋፋ አብያተ ክርስቲያናቱንም በልማት እንድናጠናክር እላለሁ። የሁሉም ምእመናንና ካህናት ከሀገረ ስብከቱ ጋር መተባበር አስፈላጊ ስለሆነ እስከ አሁን ያለውን ቀና ትብብራቸውን አጠናክረው አንዲቀጥሉ በሀገረ ስብከቱ ጽ/ ቤት ስም መልእክቴን አስተላልፋለሁ፡፡

•    በእውነት ጊዜዎን ሰውተው ለሰጡን ቃለመጠይቅ በእግዚአብሔር ስም እናመሰግናለን፡፡

እንግዲህ ከመጣን አጭር ጊዜ ቢሆንም ከሞላ ጎደል ያለውንና እንዲሁም ለወደፊት ያለውንና ለመሥራት የታቀዱትን እኔ የሚቻለኝን ያህል ብያለሁ፤ ብፁዕ አባታችን አቡነ ገብርኤል ደግሞ በአባትነታቸው በሀገረ ስብከቱ ያለውን ሁኔታ አስፍተው አምልተው ከኔ የበለጠ አድርገው፥ እኔ ምናልባት ያተረፍኩትም ያጎደልኩትም ካለ የበለጠ ብፁዕነታቸው አርመው አስተካክለው አስፍተው በጥሩ ቋንቋ በጥሩ ሁኔታ ለትውልዱ በሚመች መልኩ ይገለፁታል። እኔም በሀገረ ስብከቱ ስም ምስጋናዬን አቀርባለሁ፥ እግዚአብሔር ይስጥልኝ።

ማሳሰቢያ፦ይህ ቃለ መጠይቅ የተደረገው በ30/05/2003 ዓ.ም. ነው።

የነነዌ ህዝቦች (ለህጻናት)

        በአንድ ወቅት ስሙ ዮናስ የተባለ ሰው ነበር፡፡ ከእለታት አንድ ቀን እግዚአብሔር አምላክ ለዮናስ እንዲህ አለው፡፡ «ወደ ነነዌ ከተማ ሂድ ለሕዝቡም በምትሰሩት የኃጢዓት ሥራ በጣም አዘኜባችኋለሁ፡፡ ይኼንን የምትሠሩትን ሥራ ካላቆማችሁ ከተማዋን አጠፋታለሁ» ብለህ ንገራቸው አለው፡፡ ነገር ግን ዮናስ እግዚአብሔር ያዘዘውን ማድረግ አልፈለገም፤ እየሮጠ ማምለጥ እና ከእግዚአብሔር መደበቅ ፈለገ ስለዚህም ዮናስ ከነነዌ ከተማ በተቃራኒው ወደ ምትገኘው አገር በመርከብ መሔድ ጀመረ፡፡
      እግዚአብሔርም በባሕሩ ላይ ኃይለኛ ነፋስን አመጣ መርከቧም ከአንድ ጎን ወደ ሌላ ጎን፤ ከላይ ወደ ታች እያለች አቅጣጫዋን ጠብቃ መሔድ አቃታት፤ ውኃውም ወደ መርከቧ ውስጥ መግባት ጀመረ፡፡

      በመርከቧ ውስጥ የነበሩ ሰዎች ሁሉ በጣም ፈሩ፤ መርከቧም ትሰጥማለች ብለው በጣም ተጨነቁ ሁሉም ሰዎች በከባድ ጭንቀት ላይ ሆነው እግዚአብሔር አምላክ ይኸንን ታላቅ ንፋስ የላከብን ምን መጥፎ ነገር ሰርተን ነው ብለው መጨነቅ ጀመሩ፡፡

       ይኼ ሁሉ ነገር ሲሆን ግን ዮናስ እንቅልፍ ወስዶት ነበር፡፡ የመርከቧም አለቃ ወደ ዮናስ ሔዶ ቀሰቀሰው፡፡ «ይህን ከባድ የሆነ ንፋስ ያቆምልን ዘንድ ለአምላክህ ፀልይልን» አለው፡፡

        ዮናስም ይህን ሲሠማ ለመርከቧ አለቃ ይህ ነገር የመጣው በእኔ ይሆናል ከአምላክ ለመደበቅ እየሞከርኩ ነበር እኔን አንስታችሁ ወደ ውኃው ብትጥሉኝ ንፋሱ እና የመርከቧ መናወጥ ሊያቆም ይችላል አላቸው፡፡ በመርከቧም የነበሩ ሰዎች ዮናስ እንደነገራቸው አደረጉ፡፡ ወደ ባህሩ ወረወሩት፡፡ ወዲያውም ባህሩ ፀጥ አለ፡፡ ንፋሱም ቆመ፡፡

        እግዚአብሔር አምላክም ዮናስን የሚውጠው ትልቅ አሳን አዘጋጀ፡፡ ዮናስም በአሳው ሆድ ውስጥ ሦስት ቀን ቆየ፡፡ በአሣ ነባሪ ሆድ ውስጥ ሆኖ ፀለየ እግዚአብሔርን እንዲረዳው ለመነ፡፡ እግዚአብሔርም የለመኑትን መልካም ነገር ቶሎ የሚሰማ ስለሆነ ፀሎቱን ሰማውና አሳውን ደረቅ መሬት ላይ እንዲተፋው አዘዘው፡፡ ትልቁም አሣ በፍጥነት ትዕዛዙን ተቀብሎ በመሬት ላይ ተፋው፡፡

        ዮናስም ምንም ሳይሆን ከትልቁ አሳ ውስጥ ስለወጣ አምላኩን አመሠገነ ወደ ተላከበትም አገር ወደ ነነዌ ወዲያውኑ ሄደ፡፡ ወደከተማዋ እንደገባ ድመፁን ከፍ አድርጎ ለህዝቡ «እግዚአብሔር በናንተ በጣም ተከፈቶባችኋል ምክንያቱም ከክፋ ሥራችሁ የተነሣ ነው፡፡» የነነዌ ህዝቦች ይዋሻሉ፣ ይምላሉ፣ ይሰርቃሉ፣ ሌላም ብዙ መጥፎ ነገር ያደርጉ ነበር፡፡ ዮናስም ከዚህ መጥፎ ሥራችሁ ካልተመለሳችሁ አገራችሁ ይጠፋል ብሏል እግዚአብሔር ብሎ ነገራቸው፡፡ የነነዌ ሰዎችም ይህንን ሲሰሙ በጣም ተጨነቁ፤ የሚሠሩትንም ክፋ ሥራ ትተው እግዚአብሔርን የሚያስደስት ነገር በመስራት ጥሩ ሰው መሆን ፈለጉ፡፡ ስለዚህም ምንም ምግብ ሳይበሉ እና ሳይጠጡ ለሦስት ቀናት ያህል ፆሙ፡፡ ሁሉንም መጥፎ ነገር መሥራት አቆሙ፡፡ መጥፎ ሥራቸውንም ሰውን በመውደድ፣ ታዛዥ በመሆን በመልካም ሥራ ቀየሩት፡፡ እግዚአብሔር አምላክም ጥሩ ሰዎች መሆናቸውን ሲያይ እጅግ በጣም ተደሰተባቸው ከተማቸውንም አላጠፋባቸውም ብሎ ወሰነ፡፡

       አያችሁ ልጆች እግዚአብሔር አድርጉ ያለንን ሁሉ ማድረግ አለብን በአደጋና በአስቸጋሪ ቦታ ላይ ስንሆንም ፀሎት ማድረግ አለብን ይሔን ካደረግን እግዚአብሔር ይጠብቀናል፡፡

       ልጆች እግዚአብሔር አምላካችን እኛ ከመጥፎ ሥራችን ተቀይረን ጥሩ ሰዎች እንድንሆን ሁል ጊዜ ይፈልጋል እና ጥሩ ሰዎች ለመሆን ጥረት እናድርግ እሺ ልጆች፡፡

                                                                         ደህና ሰንብቱ!!

hawassakidusgebriel.jpg

የሐዋሳ ጉዳይ 1

hawassakidusgebriel.jpgባለፉት ጥቂት ወራት በሐዋሳ ከተማ፥ በተለይም ደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በርካታ ችግሮች ሲከሰቱ ቆይተዋል። ያለውን ሁኔታ በተመለከተ ወደ ሐዋሳ የተጓዘው ሪፖርተራችን ተሥፋሥላሴ የሀገረ ስብከቱን ሥራ አስኪያጅ፥ የዋሳ ደብረ ምሕረት ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪንና ምእመናንን አናግሮ ዘገባ አጠናቅሯል።
በመጀመሪያ ከሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ከሊቀ ኅሩያን ዓለም እሸት ገ/ጻድቅ ጋር የተደረገውን ቃለ መጠይቅ በሁለት ክፍል እናቀርባለን። በቀጣይነት በቦታው ያለውን ዝርዝር ሁኔታ የሚመለከት ሐተታዊ ጽሑፍ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ለማስነበብ እንሞክራለን።
  • ብፁዕ አቡነ ገብርኤልም ሆነ እርስዎ ከመጣችሁ ጥቂት ጊዜያት ቢሆንም፥ በሀገረ ስብከቱ ያሉ እንቅስቃሴዎች፣ በጎ ነገሮችና ፈተናዎች ካሉ ቢገልጹልን?

እኔም ሆንኩ የሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ብፁዕ አቡነ ገብርኤል ተመድበን ከመጣን ወደ 3 ወር የሚጠጋ ጊዜ ብቻ አስቆጥረናል፡፡ እኛ ከመምጣታችን በፊት በቦታው ላይ አንዳንድ አለመግባባቶችና ችግሮች ነበሩ፡፡ እነዚህ ችግሮች እንዳሉ ነው እኛ የመጣነው፡፡ ቢሆንም ከመጣንበት ጊዜ ጀምሮ አብዛኛውን የማረጋጋት፣ የመምከር፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን ደንብ፣ መመሪያ፣ ሥርዓትና ሕጉን የማሳወቅ፣ ሰዎች ሁሉ ወደ በጎና ወደ ቀና አስተሳሰብ እንዲመጡ የመመለስ፣ ያልተረዱት ነገር ካለ እንዲረዱ ያላወቁት ካለ እንዲያውቁ፤ አጠቃላይ የቤተክርስቲያኒቱን ሥርዓትና ሕግ በተከተለ መልኩ መንገዶችን የማሳየት፣ የማስተካከል፣ ይሄኛው ያስኬዳል፣ ይሄኛው አያስኬድም በማለት  እየነገርንና እያስተካከልን ነው የቆየነው። ችግሮቹ ምን እንደሆኑ፥ አነሣሣቸው ምን አንደሆነ በውል ባናውቀውም ከኛ በፊት አለመግባባቶች ነበሩ፡፡ አሁን ደግሞ ከመጣንበት ጊዜ ጀምሮ ሽማግሌዎችን ካህናትን፣ ማኅበረ ምዕመናንንና፣ የሰንበት ትምህርት ቤቶች ወጣቶችንና የሚመለከታቸውን አካላት በማነጋገር በተቻለ መልኩ ችግሮች በሰላም፥ በውይይትና በመግባባት የሚፈቱበትን የተቻለውን ያህል ብዙ ጥረት አድርገናል። ከዚህም በኋላ የሀገር ሽማግሌዎችም እንዲሁ ሃሳቡን እንዲያግዙንና ድጋፍ እንዲያደርጉልን አድርገን፤ እነርሱም የሚቻላቸውን በትብብር መልክ ሰርተዋል፡፡ የመንግሥት አካላትም ጭምር በእውነት ለቤተ ክርስቲያናችን በሚያስፈልገው በማንኛውም መልኩ ከክልሉ ርዕሰ መስተዳድር ጀምሮ በተለያዩ በፀጥታ፣ በፖሊስ፣ በደህንነት በቀበሌም በማንኛውም ሕዝባውያንና መንግስታውያን ድርጅቶች የሚገኙ፥ ቤተክርስቲያኒቷ ሕጓ፣ ሥርዓቷ፣ ደንቧ ተጠብቆ በአግባቡ ሥራዋን እንድታከናውን፤ ከቅዱስ ሲኖዶስ በሚተላለፈው መመሪያና ውሳኔ መሠረት፥ ማንኛውም ሥራ መመሪያና ደምቡ ተጠብቆ እንዲሠራ፣ ሁሉም የሚቻላቸውን ከፍተኛ ድጋፍን እገዛ እያደረጉልን ይገኛሉ፡፡ በዚህ አይነት ነው ሥራዎችን እየሠራንም እያስተካከልን የቆየነው፡፡ እንግዲህ ከቆየታው ማነስ የተነሣ /ከመጣን አጭር ጊዜ ቢሆንም/ በተቻለ መልኩ ችግሩን ከማስወገድ አንፃር ሥራዎችን በተዋረድ እያከናወንን ነው፡፡ ከዚሁ ጎን ለጎን ደግሞ ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር በመተባበር ወደየ ወረዳዎቹ እንቅስቄሴ በማድረግ ለየወረዳዎቹ ሊቃነ ካህናትና ለየወረዳዎቹ ቤተክህነት ኃላፊዎች እንደሁም ለርዕሰ ከተማዋ /ሐዋሳ/ አድባራት አስተዳዳሪዎች ሰባክያነ ወንጌል፣ የሰበካ ጉባኤ ሊቃነ መናብርት፣ ምክትል ሊቃነ መናብርት እንዲሁም ጸሐፊዎች በሁለቱም የብፁዕነታችን ሀገረ ስብከቶች ለሚገኙት፣ ሰበካ ጉባኤን ለማጠናከር፤ ሰንበት ትምህርት ቤትን ለማደራጀት፣ ስብከተ ወንጌልን ለማስፋፋት፣ የአሥራት በኩራትና የሰበካ ጉባኤ ክፍያዎችን ለማጠናከር በብፁዕነታቸው መሪነት የ3 ቀናት ሴሚናር አካሂደናል፡፡

  • ከመጣችሁ በኋላ ችግሮችን በመፍታት እንዳሳለፋችሁ ገልጸዋል፡፡ የችግሮቹ አካሄድ አፈጣጠር ምን እንደሆነ ሊነግሩን ይችላሉ?
በሀገረ ስብከታችን ከርዕሰ ከተማው በስተቀር ቢያንስ ከ125 በላይ አብያተ liquehiruyan.jpgክርስትያናትና 13 የወረዳ ቤተ ክህነቶች ይገኛሉ፡፡ በሌሎቹ አብያት ክርስቲያናት ምንም ዓይነት የተለየ ችግር አላጋጠመንም አልፎ አልፎ አንዳንድ ቦታዎች ቢታዩም ይሄን ያህል አይደሉም፡፡ ትልቁና ከፍተኛው ችግር አልፎ አልፎ እየተነሣ ያለው በመንበረ ጵጵስናው ርዕሰ ከተማ በሚገኘው ደብረ ምህረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም ነው፡፡ ውሳኔዎች፣ መመሪያዎች፣ ሰርኩላሮች ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ወደ ሃገረ ስብከቱ በተዋረድ ይመጣሉ፤ ተወረዱንም ጠብቆ ወደ አድባራትና ገዳማት ይወርዳሉ፡፡ በደብረ ምህረት ቅዱስ ገብርኤል ገዳም አስተዳዳሪና ሰበካ ጉባኤ በኩል ግን መመሪያን የመፈጸምና የማስፈጸም፥ የቃለ አዋዲውን ሕግ የመጠበቅና የማስጠበቅ፤ በአጠቃላይ ግቢውን ከሁከትና አላስፈላጊ ከሆነ ነገሮች ሁሉ የመጠበቅና የማስጠበቅ ጉዳይ የሰበካ ጉባኤ ጉዳይ ሆኖ ሳለ አባላቱና የደብሩ አስተዳዳሪ ኃላፊነታቸውን ባለመወጣታቸው ምክንያት ነው ይሄ ሁሉ ችግር እየተፈጠረ ያለው። ይሄንንም ችግር እንዲፈቱ ለአስተዳዳሪው በብጹዕነታቸው ከአንድም ሁለት ሦስቴ መመሪያ ተሰጥቷል፡፡ የሰበካ ጉባኤውንም በጋራ አሰባስበን የአቅማቸውን ቃለ ዐዋዲውን ጠብቀው እንዲሠሩ፥ ከአቅም በላይ የሆነ ነገር ሲገኝ ደግሞ ለሃገረ ስብከቱና ለመንግሥት አካላት አቅርበው እንዲያስከብሩ፣ ግቢውን እንዲያስጠብቁ፤ ተደጋጋሚ ውይይቶች የጽሑፍም ሆነ የቃል መመሪያዎች ተሰጥተዋል፤ ነገር ግን ተፈጻሚነት ሳያገኙ እየቀሩ፥ በቸልታ እየታለፈ ችግሩ ወደ አለመወገድና መድረኩ በተለያየ ጊዜ የጭቅጭቅ መድረክ እንዲሆን አድርጎታል፡፡

ከፍተኛው ይሄ ችግር የሚታየው የገዳሙ ሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ነን በሚሉት በኩል ነው፡፡ በካህናቱም፣ በማኅበረ ምዕመናኑንም በመላው ሐዋሳ ከተማ በሚገኙ ምዕመናን በእውነት ለቤተ ክርስቲያናቸው የሚያስፈለገውን የሚያደርጉ፣ የሚታዘዙትን የሚፈጽሙ፣ ቅንነት የዋህነት ያላቸው፣ ሃይማኖታቸውን ጠብቀው ይዘው ለቤተ ክርስቲያናቸው አስፈላጊውን ሁሉ የሚፈጽሙ ናቸው፡፡ እንደ ቃለ ዓዋዲው በሰንበት ትምህርት ቤት የሚታቀፉት ከ4 ዓመት እስከ 3ዐ ዓመት ያሉ ናቸው። ነገር ግን በቅዱስ ገብርኤል ሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ የ4ዐ ዓመት የ5ዐ ዓመት ትልልቅ ሰዎች ሁሉ አሉ የእድሜ ገደቡም የሚመለከታቸው አይደለም። ይሄ የሚያሳየው ድርሻቸውን ለይተው አለማወቃቸው ነው ከ3ዐ ዓመት በኋላ ወደ ማኅበረ ምዕመናን ነው መቀላቀል ያለባቸው፡፡ ይህን ማድረግም የሰበካ ጉባኤው የሥራ ድርሻ ነበር፡፡ ሰንበት ትምህርት ቤት በቤተ ክርስቲያን ሊቋቋሙ ከሚገባቸው ከ13 ንዑሳን ክፍሎች ውስጥ አንድ ነው ይሄንን መፈጸም የሰበካ ጉባኤው ድርሻ ነው እኛ ከመምጣታችን በፊት እኛ ከመጣንም በኋላ ተቀላቅለው አንድ ዓይነት ትምህርት ነበር የሚሰጣቸው፡፡ ስለዚህ ድርሻዎችን የመለየት፣ መመሪያዎችን የማወቅና ነገሮችን በቅንነት የመመልከት ሁኔታው የለም፡፡

በሌላ በኩል በቅዱስ ሲኖዶስ ተወስኖ በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደሪጃ መምሪያ በኩል የሚፈጸም መመሪያ አለ፡፡ ያንን ተከትሎ መሄድ ቢቻል ምንም ዓይነት ችግር አይኖርም፡፡ ነገር ግን ሰንበት ትምህርት ቤት ነን ይላሉ ዕድሜአቸው ከጣሪያ በላይ የሆኑ በውስጣቸው አሉ፡፡ እነዚያው ክፍሎች ደግሞ የገዳሙን አውደ ምህረት ይዘን እኛ ነን መስበክ ያለብን ይላሉ፡፡ ለመስበክ ደግሞ የቤተ ክርስቲያን ዶግማ ሥርዓት ቀኖና መማር ከሊቃውንት እግር ሥር ቁጭ ብሎ መጻሕፍትን መመርመር ይገባል፤ ይህ ባልሆነበት ሁኔታ እናስተምራለን እንሰብካለን ማለቱ ደግሞ ወደ ስህተት ትምህርት ይወስዳል፡፡ በአሁኑ ወቅት ደግሞ ሰባክያነ ወንጌል ነን፣ ዘማርያን ነን፣ ባሕታውያን ነን፣ እናጠምቃለን እንዲህ እናደርጋለን የሚሉትንና የመሳሰሉትን በሚመለከት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በ2001ዓ.ም የካቲት ወር ያሳለፈውና ለመላው ስብከት ያስተላለፈው ሰርኩላር አለ፡፡ በዚያ ሰርኩላር ላይ ከመንበረ ፓትርያሪኩ ጠቅላይ ጽ/ቤት ወይም ከሀገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ ፈቃድ ያልተሰጠው ማንም ሰው መስበክ አይችልም፡፡ ቤተ ክርስቲያኒቱ በቅዱስ ሲኖዶስ የምትመራና ከቅዱስ ሲኖዶስ እስከ አጥቢያ ቤተክርስቲያን ድረስ የራሷ የሆነ አስተዳደራዊ መዋቅር ያላት በመሆኗ፥ በዚያው በመዋቅር ውስጥ ተካቶ ሕጋዊ እውቅና ኖሮት፥ በየሃገረ ስብከቱ ያለውም የየሃገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስና የሃገረ ስብከቱ ጽ/ቤት አሊያም ጠቅላይ ቤተ ክህነትም የስብከተ ወንጌል ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያው አውቆት በዚህ አይነት ነው መስበክ ያለበት ይላል መመሪያው። ይሄ መመሪያ የተላለፈው በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቃነ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ፕሬዚዳንትና የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዚዳንት ክቡር ፊርማ ተፈርሞ ነው፡፡ እኛ ደግሞ እንደ ሀገረ ስብከት በቅዱስ ሲኖዶስና ከብፁዕ ወቅዱስ አባታችን የሚሰጠውን መመሪያ የመፈፀም የማስፈጸም ኃላፊነት፣ የቤተክርስቲያን ልጅነትና አደራ አለብን፡፡

እንደ ሀገረ ስብከት ግን እገሌ ይስበክ እገሌ አይሰበክ የሚል አመለካከት የለንም፡፡ በአንዳንድ አካላት ግን እንደዚህ አይነት ሰባክያን ካልመጡልን እንደዚህ ዓይነት መምህራን ካልመጡልን የሚል የግል ጥያቃቄዎች ይነሳሉ፤ ሃሳቦቹ ለምን ኖሩ አንልም፡፡ ነገር ግን ጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የሚያሰማራቸው፣ የሚቆጣጠራቸው፣ አንድ ጥፋት  ቢያጠፉ ሊጠይቃቸው የሚችል ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ጀምሮ እስከ ገጠሪቱ ቤተ ክርስቲያን ድረስ በቤተ ክርስቲያኒቱ የአስተዳደርን የሥራ መዋቅር ውስጥ የተካተቱ ሊሆን ይገባል፡፡ ደግሞም በርካታ ሠራተኞችና ሊቃውንት አሏት፡፡

እናስተምራለን ለሚሉ ግን ለጠቅላይ ቤተ ክህነት ወይም ለሃገረ ስብከቱ ሊቀ ጳጳስ መጠየቂያ ቀርቦ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልዕኮ መምሪያ ጉዳዩን መርምሮና አጣርቶ፥ ይህ ሰው ብቁ ነው ብቁ አይደለም፥ ለማስተማር አስፈላጊውን የትምህርት ሆኔታ ይዟል አልያዘም፥ የሚለውን ሁሉ አይቶ ሲያሰማራ /ሲፈቀድ/ ሊሆን ይችላል፡፡

ለምሳሌ አንድ ሰው በራሱ ተነሳሽነት ተነስቶ ወይ ባሕታዊ ነኝ ወይም ሰባኪ ነኝ ብሎ አንድ አጥቢያ ቤተክርስቲያን ላይ እሰብካለሁ ቢል፡-
1.    የደብሩ አስተዳዳሪ ወይም ሰበካ ጉባኤ አያውቁም፣ የወረዳው ቤተ ክህነት፣ ሀገረ ስብከትና ጠቅላይ ቤተክህነቱም አያውቁም
2.    እዚያ ቦታ በአጋጣሚ ሆኖ /እግዚአብሔር አያድርስና/ ችግር ቢፈጠር፡፡ ጠቅላይ ቤተክህነቱም ሀገረ ስብከቱን መጠየቁ አይቀርም ሀገረ ስብከቱም የደብሩን ተጠሪ መጠየቁ አይቀርም፡፡ ስለዚህ እንደኃላፊነት ሀገረ ስብከቱ እያወቀው መሆን አለበት፡፡ ምዕመናንም ምን አልባት የስሕተት ትምህርት እየተላለፈ እንደሆነ፣ ቃለ ዐዋዲውም እየተከበረ እንደሆነ፣ አበው ያቆዩት ሥርዓት እየተጠበቀ እንደሆነ ሊከታተሉ ሊያውቁ ይገባል፡፡

ስለዚህ በአጠቃላይ ችግሮቹ የተፈጠሩት በመጀመሪያ ያለ እድሜያቸው በሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ ተካተው ድርሻቸውን ሳያውቁ የሚኖሩ ስላሉ፣ ቀጥሎም በተናጠልም ሆነ በቡድን ተሰባስበው እኛ መስበክ አለብን ወይም እገሌ ካልሰበከ አይሆንም በማለት እንደግል አመለካከት በመያዝ የሚንቀሳቀሱ ስላሉ ነው፡፡ ይሄንን ደግሞ ሰበካ ጉባኤው ባለው ሥልጣን ማስተካከል ይችላል፡፡

•    በአለመግባባቱ ውስጥ ሁለት ዋና ቡድኖች እንደተፈጠሩ ይነገራል፤ የቅዱስ ገብርኤል ወርሃዊ በዓል ማግስትም ግጭቶች እንደተፈጠሩ ይታወቃል፡፡ እነዚህ ቡድኖች ምንድን ነው አካሄዳቸው? ወይም ምክንያታቸው?

ሰዎች በራሳቸው እይታ ሁለት ቡድን አለ ሊሉ ይችላሉ፡፡ እንደ ሀገረ ስብከት ግን እኛ ሁለት ቡድን አለ የምንለው ነገር የለም፡፡ በመሠረቱ ቤተክርስቲያን ዓላማዋ ሰውና እግዚአብሔርን ማገናኘት ነው፡፡ በዚህ ሕይወት ደግሞ ወንጌልን፣ ፍቅርን ትህትናን እርስ በእርስ መከባበርን መተሳሰብን እንዲይዙ ማድረግ ነው፡፡ እንደ ጌታችን መድኅኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትምህርትም የቡድን አካሄድ የመከፋፈል አካሄድ፣ የመለያየት አካሄድ አነ ዘአጵሎስ ወአነ ዘኬፋ የሚለው አነጋገር በቅዱስ ወንጌልም የተደገፈ አይደለም፡፡ እኛ ከመጣን ጀምሮ የምናየው ቅድም እንዳልኩት ነው፡፡ ከችግሮቹ ምንጮች እንደገለጽኩት ከሰንበት ትምህርት ቤት የተውጣጡ የተወሰኑ የእድሜ ገደብ ያለፋባቸውና እኛ ብቻ ነን መስበክ ማስተማር ያለብን የሚሉና ወጣቶችንም ወደ ስሜት ወደ መገፋፋት የሚያመጡና፣ የቤተክርስቲያኗ ደንብ ሥርዓትና መመሪያ ያለመቀበል ሁኔታ የሚያሳዩና እንደ ራሳቸው ሃሳብ የመሄድ ጉዳይ ይታያል በሌላ በኩል መላው ምዕመናን ማለት ይቻላል፤ ሕጉ ሥርዓቱ የሲኖዶሱ መመሪያ ተከብሮ ቤተክርስቲያን ሥራዋን በአግባቡ ታከናውን የሚል ብቻ ነው ያለው፡፡ እንግዲህ አሁን የመለያየትና የቡድን ስሜት የለውም፡፡ ሕጉና መመሪያው ሲነገር ሁሉም ይሰማል፣ ሁሉም ያከብራል እዚህ ቅዱስ ገብርኤል ሰንበት ትምህርት ቤት ያሉ ጥቂት ወጣቶች ግን የልጅነትም ሊሆን ይችላል ከረር የማለትና መድረኩን እኛ ካልያዝነው፣ ስብከቱንም እኛ ካልሰበክነው የሚል የግል አካሄድ ያሳያሉ እንጂ ከሁለት የተከፈለ ቡድን የለም፡፡

የአገር ሽማግሌዎችን አባቶች፣ እባካችሁ ይሄንን መመሪያ እንዲያከብሩ አድርጓቸው፣ ትንሽ እኛን አልሰማ አሉ የሚቻለውን ነግረናል ብለን ስናስረዳ፤ እግዚአብሔር ይስጣችሁ፥ ሸክሙን እንድናግዛችሁ ወደ እኛ ማምጣታችሁ ጥሩ ነው ብለው ብዙ ደክመዋል በዚህ ጉዳይ፡፡ የተቀበሉ አሉ፥ ልክ ነው ያሉ አሉ፡፡ አንዳንዶቹ ግን የለም አይሆንም ያሉ አሉ፡፡ እንደዚህ እንደዚህ አይነት አካሄዶች ናቸው እንጂ እንደ ሰው አባባል ሁለት ቡድን የለም፡፡

•    በቤተ ክርስቲያን ታሪክ እንደዚህ አይነት አለመግባባቶች ምንጫቸው ምንድን ነው? እንዲያው ዝም ብሎ ቃለ ዐዋዲን ብቻ ባለ ማክበር የሚፈጠሩ ናቸው ብለው ያስባሉ?

ሰው ምን ጊዜም ችግር የሚገጥመው ከሕግ፣ ከሥርዓትና ከመመሪያ ሲወጣ መሆኑ ግለፅ ነው። ያለን ቆይታ አጭር በመሆኑ እስከ አሁን ያየነው ሁኔታ ከላይ የገለፅኩትን ነው የሚመስለው። ከበስተኋላው ምንድን ነው ይሄ ነገር? ምንስ አይነት እንቅስቄሴ አለው? ወይስ የተለየ ዓላማ አለው? ወይስ ሕጉን ያለማወቅ ብቻ ነው? ወይስ ደግሞ ቃለ ዐዋዲውን ያለመቀበል ነው? እስከ አሁን እንደምናየው መመሪያው እየተነገረ እያዩ እየሰሙ ያለመቀበል ነው ያለው? ግን ከበስተኋላ ምን አለው? ተጨማሪ ነገር አለው ወይ? የሚለው ግን ትንሽ ጥናት ይፈልጋል፡፡ ሲነገራቸው ተስተካክለው በመስመር መጓዝ የጀመሩና የሄዱ አሉ፡፡ ሌሎች ደግሞ የለም እንዲህ ነው እያሉ ክርር የሚሉ አሉ፡፡ ሰው ሕሊናው እያየ አእምሮው ያስባል፡፡ ማንኛውም በአርአያ እግዚአብሔር የተፈጠረ ሰው ሲነገረው ይሰማል፤ ሲያይ ያነባል፥ ግን አንብቦ፣ ተነግሮት ሰምቶ፣ ተረድቶ፣ እውነቱን አውቆ ግን ይሄ ነው ማለት መቻል አለበት፡፡ ይሄንን ካልቻለ ችግሩ ምን እንደሆነ የሰውየው ሁኔታ ነው አላማውን የሚያውቀው፡፡

የቅዱስ ገብርኤል ሰንበት ትምህርት ቤት የራሱ የሆነ መምህር የለውም፡፡ ከዚህም የተነሳ ከብፁዕ የሀገረ ስብከቱ ሊቀጳጳስ ጋር ጉዳዩን በመመካከርና በመነጋገር፣ እንደብፁዕነታቸውም መመሪያ በመቀበል አሁን የሰበካ ጉባኤ ምርጫ ከተካሄደ በኋላ በሂደት ሰንበት ትምህርት ቤቱ በአግባቡ መምህር እንዲኖረው፣ ልጆች ተኮትኩተው የቤተክርስቲያኒቱን ሥርዓትና ደንብ ጠንቅቀው አውቀው እየተገበሩ እንዲያድጉ ለማድረግ፣ ይሄ በእቅድ ደረጃ ተይዟል፡፡ ትምህርትም ሲሰጥ እንደ እድሜ ደረጃቸው ነው። ወጣቶች አሉ፣ ህፃናት አሉ፣ አዋቂዎች አሉ፣ እንደወንጌሉም ግልገሎች፤ ጠቦቶች በጎች፣ ብሎ ይለየዋልና። እዚያ ሰንበት ትምህርት ቤት ደግሞ ተቀላቅለው ነው የሚማሩት ይህ ችግር ይፈጥራል፡፡

የትምህርት አሰጣጡ ይስተካከል ሲባል ደግሞ በአንዳንድ ሰዎች ይሄ የተለመደ ነው ይላሉ፡፡ ግን ልማድ ሲጋነን ባሕል ይሆናል ይባላልና ልማድን ትተው ሊስተካከሉና መስመር ይዘው ሊጓዙ ቃለ ዐዋዲውንም ሊያከብሩ ይገባል ማለት ነው፡፡

ሌላው ቤተክርስቲያኒቱ ውስጥ ምንም አይነት የሥራ ድርሻ የሌላቸው ያልተቀጠሩ፣ የሥራ ውል የሌላቸው ወይ ዲያቆን፣ ቄስ፣ መነኩሴ፣ መሪጌታ፣ አወዳሽ ቀዳሽ ያልሆኑ፣ እንደ አንድ ምዕመን ጸልየው ወይም ትምህርት ሰምተው መሄድ ብቻ የሚገባቸው ሆነው ሳለ በማይገባቸው አንዳንድ አስተዳደራዊ ጉዳዮች ውስጥ ጣለቃ የመግባት ነገር ይታያል፡፡ በሰንበት ትምህርት ቤትም፣ በስብከተ ወንጌልም፣ በአውደ ምህረትም ጣልቃ የሚገቡ ሰዎች ናቸው ነገሩንም እንዲባባስ እያደረጉት የሚገኙት፡፡

•    የቅዱስ ገብርኤል ገዳም አስተዳደርና ሰበካ ጉባኤ ችግሮቹን ለመፍታት ከእናንተ ጋር ያላቸው ተግባቦት ምን ይመስላል?
 

በእርግጥ አሁን ያለው ሰበካ ጉባኤ እኛ ከመምጣታችን በፊት ጊዜያዊ ተብሎ የተመረጠ ነው፡፡ በዚህ የተነሣ ብዙ ጊዜ፥ አንዳንድ ሥራዎችን ለመሥራት ሲቸገሩ እናያለን፡፡ ጠርተን በጋራ አወያይተናል፥ ተመካክረናል ጊዜያዊ ሆነው እንዴት እንደተመረጡ ለእኛም ግለፅ አይደለም፤ ምክንያቱም ባልነበርንበት ጊዜ ስለነበር፤ አንዳንድ ምዕመናንም አልመረጥንም፤ ጊዜያዊ ናቸው፤ የማለት ያለመተባበር ችግር ይታያል፡፡

እኛ ከመጣን ግን የገዳሙን አስተዳዳሪና ሰበካ ጉባኤውንም በጋራ ቁጭ አድርገን አወያይተናል፥ ማደሪያ ጉዳዩንም አገላብጠን ተመልክተን ጊዜአዊ ሰበካ ጉባኤ መሆናቸውን እነርሱም አውቀውት፥ እነርሱም ባሉበት ሆነው፣ ከወጣቱም፣ ከአገር ሽማግሌዎችም፣ ከልማት ኮሚቴም፣ ከሚመለከታቸው አካላት የተወሰኑ ይዘን የመንግሥት አካላትም በታዛቢነት እንዲገኙልን አድርገን የቃለ ዐዋዲውን ሕግና መመሪያ በጠበቀ መልኩ ተገቢውን ቅስቀሳና ትምህርት ተሰጥቶ የቤተክርስቲያኒቱን አስተዳደራዊ ሥራ በአግባቡ ሊመራና ግቢውን ሊያስከብር ሊጠብቅ የሚችል ሰበካ ጉባኤ ምርጫ እንዲካሄድ የሚል ውሳኔም ስምምነት አድርገናል፡፡
 
አሁንም ቅድመ ሁኔታዎችን በማመቻቸት ላይ እንገኛለን፡፡ እስከዚያው ድረስ ግን አሁን ያለው ሰበካ ጉባኤ ያለውን ኃላፊነት እንዲወጣና ለአንድ ቀንም ቢሆን ኃላፊነት ስላለው ግቢውን እንዲያስከብር፣ እንዲጠብቅ በተደጋጋሚ ጊዜ ተወያይተናል መመሪያ ተሰጥቷል ብፁዕ አባታችንም በሰፊው ደክመውበታል፡፡ ተፈፃሚነቱ ግን እምብዛም አይታይም፡፡ የአቅም ማደስም፣ ኃላፊነትን በአግባቡ አለመወጣት ሊሆን ይችላል እንግዲህ ምክንያቱ፡፡

በግቢው ያለው ማንኛውም እንቅስቃሴ ሰበካ ጉባኤውንም አስተዳዳሪውን በመጀመሪያ ደረጃ ይመለከታል፡፡ ስለዚህ አዛው አጥቢያው ላይ እንደ ቃለ ዐዋዲው የማስኬድ ፣ መመሪያውን የመጠበቅና የማስጠበቅ፣ መስመሮችን እንዳይለቁ የመከታተልና ቁርጥ ያለ ውሳኔና ፍትሕ የመስጠት አስተዳደራዊ ሥራ ቢሠራ ምንም አይነት ችግር አይኖርም፡፡

                                                                                    ይቆየን

ትንሣኤ ግዕዝ

 

/ርት ፀደቀ ወርቅ አስራት

የጥንቱ ውበቱ

ጭራሽ ተዘንግቶ፣

ለብዙ ዘመናት

የሚያስታውስ አጥቶ፣

ተዳክሞ ቢያገኙት

ግዕዝ አንቀላፍቶ፣ 

«ሞተ ሞተ» ብለው

አዋጅ አስነገሩ፣

በርቀት እያዩ

ቀርበው ሳያጣሩ፡፡

ታዲያ ይሄን ጊዜ…..

አዋጁን የሰሙት

ቀርበው ወገኖቹ፣

ፍፁም እያነቡ

ግዕዝ….. ግዕዝ ቢሉ

አብዝተው ቢጣሩ፣

በቅፅበት ተነሣ፣

ትንሣኤን አግኝቶ

ለወዳጆቹ ጥሪ

ምላሽ ሊሰጥ ሽቶ፡፡


ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እና የ«ተሐድሶዎች» ቅሰጣ

                                    በእደማርያም ንርአዩ

ምድራችን እስከ ዕለተ ምጽአት ከመልካም ስንዴው ጋር እንክርዳዱን ማብቀሏ፤ ከየዋሁ በግ ጋር ተኩላውን ማሰለፏ፤ ከንጹሐን ሐዋርያት መካከል ይሁዳን ማስገኘቷ አይቀርም፡፡ እንክርዳዱ እንዳይነቀል ከስንዴው ጋር አብሮ በቅሎ፣ ተኩላው እንዳይጋለጥ በግ ይመስል ዘንድ ለምድ ለብሶ ከስንዴው ጋር ልዘናፈል፣ ከበጉም ጋር ልመሳሰል ብለው ያልሆኑትን ለመሆን እየታገሉ ለዓላማቸው መስለው የሚሠሩ ተቆርቋሪም ሆነው የሚቀርቡ በማባበል ቃል የሚጎዱ ከፍጥረት ጅማሬ እስከ ዘመን ፍጻሜ፤ ከመላእክት ከተማ እስከ ደብረ ዘይት ተራራ ጌታችን እስከሚገለጥበት ቦታ ከገነት እስከ ዛሬዋ መቅደስ ስተው እያሳቱ ክደው እያስካዱ ከዚህ ዘመን ደርሰዋል፡፡

ለዚህም ነው ሄሬኔዎስ /ከ 130-200 ዓ.ም/ የተባለ ሊቅ «በእውነቱ የስኅተት ትምህርት ወዲያው ታይቶና ታውቆ እንዳይገለጥ እርቃኑን ከቶ አይቆምም፡፡ ነገር ግን መስሕብነት ያለውን ልብስ በብልሃት ለብሶ በውጭ አምሮ ይገኛል፡፡ የሚሞኝ ሰው ካገኘ ለማታለል ከእውነትም የበለጠ እውነት መስሎ ይታያል፡፡» በማለት የገለጸው፡፡

ቅድስት ቤተክርስቲያን ከምሥረታዋ ጀምሮ ጠላት ዲያብሎስ በግብር የወለዳቸውን በመጠቀም እውነቱን ሐሰት በማለት ማሩን በማምረር ወተቱን በማጥቆር የዋሃንን በረቀቀ ስልቱ ተመሳስሎ የጸኑትን ደግሞ እርቃኑን ገልጦ      ጭንብሉን አውልቆ፤ ሲሆን ኃይለ ቃል አጣምሞ ሳይሆንለት ደግሞ ሰይፍ ስሎ ስንዴውን ለማጥፋት እንክርዳዱን    ለማብዛት ያለማቋረጥ ይሠራል፡፡ ያለ ድካም ይተጋል፡፡

ሰማዕታቱም ሞት በእጅጉ በሚፈራበት ዘመን ሞትን እየናቁ ወደ መገደያቸው በዝማሬ ሲሄዱ ያዩ      ሃይማኖታቸው ምንኛ እውነት ቢሆን ነው በማለት ብዙዎችን በሞታቸው ወለዱ የካርታጎው ጠርጠሉስ «አሠቃዩን፣ ስቀሉን፣ ንቀፉን፣ ኮንኑን፣ አቃጥሉን የእናንተ ክፋት ግፍና ጭካኔ የእኛ ንጽሕና ማረጋገጫ ነው፡፡ እናንተ በወገራችሁንና በቆረጣችሁን ልክ ቁጥራችን እልፍ ይሆናል፤ ደመ ሰማዕታት የክርስቲያኖች ዘር ነው፡፡» እንዳለው እንደ ሐሰተኛ ተቆጠሩ እንደ አበደ ውሻ ተወገሩ፤ እንደ ጥራጊ ቆሻሻ ተቃጠሉ፡፡ ስንዴ ስትርስ እንደምታፈራ ሁሉ ሲሞቱ ሌሎችን እያፈሩ ስብከተ ወንጌል ካጸናቸው መከራው የሳባቸው እየበዙ «ሞት ምንም አይደለም ክርስቶስ ተነሥቶአልና» እያሉ በሰማዕትነት ቀናቸው ለዘላለማዊ ሕይወት እየተወለዱ ያረፉበት ዕለትም እንደ ልደት ቀናቸው የሚከበር ሆነ፡፡

መከራ መገለጫቸው ስደት ኑሯቸው ቢሆንም እንኳን በትንሣኤ ተስፋ እየ ተጽናኑ መከራውን እንደ ኢምንት እየቆጠሩ ሳይጠራጠሩ ንግግር የማያውቁ ሲሆኑ ንግግር አዋቂዎችን በክርክር እየረቱ የተረቱትንም ሞትን እንዲንቁ ዘላለማዊ ሕይወትን እንዲናፍቁ አደረጉ፡፡

ገንዘው ሊቀብሯት ስም አጠራሯንም ሊያጠፏት መስሏቸው ለጊዜውም ቢሆን ላይ ታች ቢሉ «እኔ ዓለምን    አሸንፌአለሁ» ያለ አምላክ እንዴት ይሸነፋል ? ቀላያት ተነድለው፣ ምድርንና በውስጧ ያለው ሁሉ በውኃ በጠፋበት በኖኅ ዘመን ኖኅና ቤተሰቦቹን የያዛቸውን መርከብ ይሰብራትና ያጠፋት ዘንድ ውኃው መች ተቻለው ? መጽሐፍ «ውኃውም በምድር ላይ አሸነፈ» ቢልም የኖኅን መርከብ ያሸንፋት ዘንድ ግን አልቻልም፤ እግዚአብሔር ደጆቿንና መስኮቶቿን ራሱ ዘግቷቸዋልና፡፡ እግዚአብሔር የዘጋውንስ ማን ሊከፍተው ይችላል ? ውኃው ሌላውን ሁሉ ሲያሰጥምም መርከቢቷን ግን ከፍ ከፍ እያደረጋት ወደ ተራራው ጫፍ አደረሳት እንጂ መቼ አሰጠማት ?

ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን በዚህ ሁሉ መከራ የምትሰጥም ለሚመስላቸው ደጆቿን ለመስበር ለሚታገሉ በዙሪያዋ እንደ አንበሳ ለሚዞሩ «ከሠሪው ጋር ለሚታገል ወዮለት» /ኢሳ. 45/ ከማለትስ ሌላ ምን እንላለን ? መሠረቷ ዐለት ነውና ብትወድቁበት ትሰበራላችሁ ቢወድቅባችሁ ትፈጫላችሁ ከማለት ሌላስ ምን እንናገራለን ? / ኢሳ 8/፡፡

ቤተክርስቲያንን በመከራ እየገፏት ወደ ተራራው ጫፍ ወደ ዘላለማዊ ዕረፍት ወደ ፍጹም ጽናት ያደርሷታል እንጂ መቼ ከአምላኳ ይለይዋታል ?

በዚህ ሁሉ ግን ስለ ጥርጥር ጥያቄአቸው ስለ ክህደት አቋማቸው ስለ ነቀፋና ትችታቸው በብርቱ ያለ ዕረፍት ቢዘበዝቡንም ነገር ሁሉ ለበጎ በሆነ በአምላካችን ፊት ወደ በለጠ ጽናት ወደ በለጠ ምርምር ወደ ጥልቅ ንባብ ወደ ታላቅ የሥራ በር መርተውናልና አናማርራቸው፡፡ ቅዱስ አውግስጢን «መናፍቃንን ስለ ጥርጥር         ጥያቄዎቻቸው ሁሉ እናመሰግናቸዋለን፤ የበለጠ እንድናጠና፣ በጥልቀትም እንድንመራመር አድርገውናልና» እንዳለው፡፡ የመናፍቃን መነሣት ለቤተክርስቲያን ትልቅ ጥቅም ነው፡፡ ታላቁ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስም «ሥራ የሞላበት ታላቅ በር ተከፍቶልኛል ተቃዋሚዎች ግን ብዙ ናቸው» ብሏል፡፡

በዚህ ጽሑፍ «ተቃዋሚዎች» በከፈቱልን የሥራ በር ጥቂት መቆየት ፈለግን፤ በሩ… እነሆ

ከአባቶች ትምህርት የራቀው ማን ነው ?

ራሱን እንደ «ለውጥ» አራማጅ እንደ «ተሐድሶ» ፋና ወጊ አንዳንዴም እንደ «ተሳዳጅ» አንዳንዴም እንደ «ሰማዕት» የሚቆጥረው ቡድን «ዛሬ ያለችው ቤተ ክርስቲያን ከጥንቶቹ አባቶች ትምህርት የራቀች ናት» በማለት ራሱን ከአባቶቿ የሚያገናኛት ሐዋርያ አድርጎ አስቀምጧል፡፡ ለእግሮቹ ማረፊያ ፍለጋ ማነህ ለሚለው ጥግ መያዣ ሲሻው የጥንታዊያን አበውን ትምህርት ይጠቅሳል ስማቸውን በማንሣት የትምህርታቸውን ጫፍ በመጠንቆል በስማቸው ይሸፈናል፡፡ ክንብንብ ጭንብሉን ሲያወልቁበት ደግሞ «አባቶቼ» እንዳላላቸው ዞር ብሎ ደግሞ ይሰድባቸዋል፡፡ በቅዱሳን ሐዋርያት፣ በሐዋርያውያን አበው በሊቃውንት ትምህርት ተስቦ ሳያምን ትምህርታቸውን እየሳበ ወደ ራሱ ሃሳብ ሊያገባቸው እየሞከረ በስማቸው እንድንቀበለው ይፈልጋል፡፡

መጽሐፍ ቅዱስ አንድ ወይም ጥቂት ጥቅሶች ብቻ እስኪመስል እንዳደረጉት ፕሮቴስታንት ወላጆቻቸው አንዲት መሥመር ትምህርታቸውን ብቻ፣ አንዲት ቃላቸውን ብቻ ይዘው ብዙውን ከራሳቸው ጨምረው የአበው ልጆች መስለው እንደተማሩ፣ የእነርሱ ወራሽ መስለው እንደተረከቡ ብዙዎችን ያደናግራሉ፡፡ ልባቸው ሰፊ አይደለምና ታግሰው አይመረምሩም፣ ጥቂት እንኳን ዝቅ ብለው አያነቡም፤ ብቻ «የአይሁድ ንጉሥ» የምትለዋን ቃል ከሰብአ ሰገል ሲሰማ ብዙ የማይመለስ ጥፋት እንዳጠፋ ሄሮድስ «ሊቀ ካህናት» «አስታራቂ» የሚለውን ቃለ ሲሰሙ ይደናበሩና ራሳቸውን ሌሎችንም ይዘው ለጥፋት ይፋጠናሉ፡፡ የአበውን ሙሉ ቃል የድምጻቸውንም ለዛ እየሰሙ እንደመከተል የተገላቢጦሽ እየመሩ ሊወስዱአቸው ይከጅላሉ፡፡ ታዲያ እንዴት «አባቶቼ» ይሏቸዋል? «አባቴ» ለማለት «ልጅ» ሆኖ መገኘት ግድ ይላል፡፡ እውነተኛ ልጅ ለመሆን ደግሞ በአባቱ ትምህርት ፍጹም መወለድን ይጠይቃል፡፡   

ይህ ቡድን «አባት» ብሎ ትምህርቱን እንደወረሰ ቃሉን እንደታጠቀ የሚናገርለት ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን ደጋግሞ ከአፉ አይለየውም ከብዕሩ አይነጥለውም፡፡ እውነት ይህ ቡድን «አባቴ» የሚለው ይህ ታላቅ     የቤተክርስቲያን አባት የዚህ ቡድን አባት ነው ? እስኪ ልጅ ነኝ የሚለውን ቡድን አባቴ ከሚለው ታላቅ አባት ትምህርት ጋር እያነጻጸርን «ልጅ» አይደለህምና፤ እርሱም አባትህ አይደለም፤ ሌላ አባትህን ፈልግ እንበለው፡፡

መናፍቃን በሚያሳትሙት መጽሔት ላይ ቃለ መጠይቅ የሰጠው የዚሁ ቡድን አባል መሪጌታ ጽጌ ስጦታው     በተለመደው የአበውን ትምህርት ድጋፍ ለማድረግ በሚያደርጉት ጉድፈራ አንዲት መሥመር እንኳን የማትሞላ ቃል በመምዘዝ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን «ክርስቶስ አማላጅ ነው» ? ለሚለው ፕሮቴስታንታዊ ትምህርቱ ታኮ ለማድረግ ይፈልጋል፤ እንዲህ በማለት «ዮሐንስ አፈወርቅ ደግሞ በክርስቶስ በተገኘው እርቅ ካልሆነ በቀር በሌላ በማንም በኩል ጸሎትና ምልጃን ማቅረብ አልተቻለም…፡፡» /ትሪኒቲ ቁ.4 ገጽ 3/ የሚል ቃል በመጥቀስ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ጌታችንን «አማላጅ» ብሎታል በማለት ሊቁን  የስሕተት ትምህርታቸው ተባባሪ ሊያደርጉት ይፈልጋሉ፡፡ በዚህም ፍጹም የአበውን ፈለግ የተከተሉ የእነርሱን ሃይማኖት ያነገቡ መስለው ለመታየት ይከጅላሉ፡፡ እውነቱን ለመናገር ግን በዚህ በፕሮቴስታንት መጽሔት ቃለ መጠይቅ የሰጠው ግለሰብ የሊቁን ትምህርት ቆንጽሎ ለስኅተቱ መደገፊያ ያድርገው እንጂ የሊቁን ሙሉ ጭብጥ ትምህርት ያላገናዘበ አንዲት መስመርን እንኳ ያልፈተሸ መሆኑ ይገልጽበታል፡፡

ቆንጽሎ የጠቀሰውን ቃል ብቻ እንኳን ብናየው አንድም ጌታችንን «አማላጅ» የሚል ትምህርት ከሊቁ አናገኝም፡፡

በክርስቶስ በተገኘው እርቅ ካልሆነ በቀር…

ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ «እግዚአብሔርም አየ ፍርድም ስለሌለ ተከፋ፡፡ ሰውም እንደ ሌለ አየ፤ ወደ እርሱ    የሚማልድ እንደሌለ ተረዳ፤ ተደነቀም፤ ስለዚህ የገዛ ክንዱ መድኃኒት አመጣለት ጽድቁም አገዘው፡፡» /ኢሳ. 59÷16/ የሚለውን መሠረት አድርጎ ሰው ሁሉ በአንዱ በአዳም በደል ተጠያቂ ሆኖ፣ ባሕርይው ጎስቁሎ፣ ሕያውነትን አጥቶ፣ ባለ ዕዳ ሆኖ በኖረበት ዘመን የካህናቱ ጸሎት፣ የነቢያቱ ምልጃ፣ የቅዱሳኑ ልመና የሰውን ልጅ ከሲኦል ማውጣት፤ ገነትን መክፈት፤ ጎስቋላ ባሕርይውን ማደስ፤ የሰውን ጥንተ ተፈጥሮ ሳይወድቅ በፊት ወደ ነበረበት ንጽሕና መመለስ አልቻለምና ነቢዩ ኢሳይያስ እንዳለው ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ «በክርስቶስ በተገኘው እርቅ ካልሆነ በቀር» አለ፡፡

ጌታችን መገለጥ ያስፈለገበት መንገድ እንደ ነቢያቱና ካህናቱ ምልጃና ጸሎት አይደለም፡፡ ዕርቁ ኃጢአት የተዋሐደውን የሰው ልጅ ከኃጢአት ነጻ ማውጣት የተፈረደበትን የሞት ፍርድ በደሙ መፍሰስ፣ በሥጋው መቆረስ ማስወገድ፣ ገነትን መክፈትን ባሕርይውን ማደስ ነው፡፡ ለዚህም ደግሞ ከሰው ወገን ይህንን ሊፈጽም የሚችል አልተገኘምና «ሰው እንደሌለ አየ» ተባለ፤ ራሱ የሰው ልጅ ገነትን መክፈት አልቻለም፤ ገነት ተዘግታበታለችና፡፡ ሞትን ማስወገድ አልቻለም፤ ሕያውነትን አጥቷልና፡፡ ከኃጢአት ነጻ አይደለም፤ ባለዕዳ ነውና፡፡ ታዲያ ለዚህ የሚያስፈልገው ሰው ሆኖ የሚክስለት ሰው የሆነ በሐዲስ ተፈጥሮ ይቅር ብሎ የሚታረቀውም አምላክ መሆን አለበትና ይህንን የሚያሟላ ቢጠፋ «የሚማልድ እንደሌለ ተረዳ» አለ፡፡ ስለሆነም «የገዛ ክንዱ መድኃኒት አመጣለት» እንዲል ክንዱ የተባለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተለየ አካሉ ተገልጦ እንደ ነቢያቱ «እግዚአብሔር እንዲህ ይላል» እያለ ሳይሆን « እኔ ግን እላችኋለሁ» በማለት ተገለጠ፡፡ ነቢያት ምሳሌውን እየመሰሉት ትንቢት እየተናገሩለት ሱባኤ እየቆጠሩለት ኖሩ ጌታችን ግን እርሱ መሆኑን ስለ እርሱ መነገሩን… እንደ ተፈጸመ እየነገረን መጣ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስም «በአምላካቸው በእግዚአብሔር አድናቸዋለሁ» ይላል፡፡ /ሆሴ 1÷3/ የተገለጠው እግዚአብሔር  ነው፤ ያለ እግዚአብሔር ይህ ሁሉ ሊሆን አይችልምና፡፡ በትምህርታቸው እየገሠጹ በኃይለ ቃላቸው እየመከሩ መጻኢያቱን እየተናገሩ በጸሎትና በምልጃ ሕዝቡን እየተራዱ የኖሩት ነቢያት /ቅዱሳን/ ይህን ፍጹም እርቅ ማምጣት አልተቻላቸውምና ነው ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ «በክርስቶስ በተገኘ እርቅ ካልሆነ በቀር» ያለው እንጂ ሊቁ ክርስቶስን «አማላጅ» የሚል አሳብ የለውም፡፡

በሌላ በማንም በኩል ጸሎትና ምልጃን ማቅረብ አልተቻለም

ይህ ከላይ የዘረዘርነው የጌታችን ሥራ አገልግሎት በራሱ በእግዚአብሔር ካልሆነ የሚሠራ ባለመሆኑ በፍጡር ሳይሆን በፈጣሪ ብቻ የሚሠራ በመሆኑ ፍጡራን በሆኑ በማናቸውም ይህን እርቅ ማምጣት አልተቻለምና «..በሌላ በማንም በኩል ጸሎትንና ምልጃን ማቅረብ አልተቻለም፡፡» በማለት ገለጸው፡፡ በአዳም የሞት ፍርድ የፈረደው እግዚአብሔር ነውና እግዚአብሔር የፈረደውን እንዴት ፍጡራን ያነሣሉ? ስለዚህ «በክርስቶስ በተገኘው እርቅ ካልሆነ በቀር» አለ፡፡ እግዚአብሔርም ያስወጣውን ፍጡራን /ነቢያት፣ መላእክት፣ ካህናት/ ሊያስገቡት አይችሉምና «በሌላ በማንም በኩል» አለ እንጂ ሊቁ «ጸሎትንና ምልጃን» ሲያቀርብ የሚኖር «አማላጅ» አላለውም፡፡

ጽድቃችን ፍሬ፣ ጸሎታችን ተሰሚ፣ ደጅ ጥናታችን ግዳጅ ፈጻሚ እንዲሆን ዳግመኛ ሕይወት እንድናገኝ ለማድረግ ኃጢአትን አስወግዶልን ወደ ጥንት ክብራችን መልሶን አንድ ጊዜ ክሶ ያስታረቀንን እና የታረቀንን አምላክ ሁሌ «አማላጅ» በማለት ደጋግሞ እንደሚሠራ አድርጎ ማቅረብ የቃለ መጠይቅ ሰጪው የ«ጽጌ ስጦታው» እንጂ የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ትምህርት አይደለም፡፡ ደጋግሞ መሥራት ከፍጡራን የሚጠበቅም እንጂ ከፈጣሪ የሚጠበቅም አይደለም፡፡

የነቢያት፣ የካህናት፣ የቅዱሳኑ ጸሎትና ምልጃ ፍጹምን ዕርቅ አምጥቶ ሰውንም አድኖ ከሲኦል ወደ ገነት ማግባት የማይቻለው በመሆኑ ለሰው ልጅ ደጋግመው መጸለይ ዘወትር መሥዋዕት መሠዋት ሲያገለግሉ መኖርን ጠይቋቸው ነበር፡፡ ደጋግመው በማድረጋቸውም ድካም ስላለባቸው ፍጹም መፈወስ /ማዳን/ አለመቻላቸው ይታወቃል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ድካም የሌለበት የባሕርይ አምላክ በመሆኑ አንዴ ሠርቶ የሚያድን አንዴ ተናግሮ የሚያጸና በመሆኑ እንደ እነርሱ ዘወትር ምልጃን ሲያቀርብ አይኖርም፡፡ ሊቁ ዮሐንስ አፈወርቅ «..በክርስቶስ በተገኘው እርቅ» አለ እርቁን አንዴ አስገኝቷልና «በተገኘው» አለ የሚያስገኝልን እርቅ የለምና፤ «በተገኘው» የሚለው ቃል ጌታችን በመስቀል ላይ የሰጠንን ፍጹም እርቅ የሚያመለክት እንጂ «ሲያስታርቅ» ስለመኖሩ በማስታረቅ ሥራን እየደጋገመ ስለመፈጸሙ የሚያሳይ አይደለም፡፡ ሊቁ ይህንን ቃል ከሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ትምህርት አግኝቶታል፤ «ነገር ግን አሁን መታረቁን ባገኘንበት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በእግዚአብሔር እንመካለን፡፡» ከሚለው /ሮሜ. 5÷11/ መታረቁን አንድ ጊዜ በመስቀል ላይ አግኝተናልና «..በልጁ ሞት ታረቀን» እንዲል፡፡ /ሮሜ. 5÷10/

ዳግመኛም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ «ብርቱ መድኃኒት አንድ ጊዜ በመደረጉ ጽኑውን ደዌ ያድናል፡፡ ብዙ ጊዜ የሚደረግ መድኃኒት ደካማ እንደሆነ ይታወቃልና፡፡» እንዳለው /ድርሳ 17 ቁ 96 -97/ የቀደሙት /የነቢያቱ ጸሎት የካህናቱ መስዋዕት /ደካማ ነበሩና/ በኃጢአት በባለዕዳነት/ ብዙ ጊዜ መሥዋዕት እየሰሠዉ ምልጃ እያቀረቡ ኖሩ፡፡ ጌታችንን ግን «ብርቱ መድኃኒት» ነውና አንድ ጊዜ ባደረገው የመስቀል ዕርቅ ጽኑ ደዌአችንን አስወገደልን፡፡ አሁን /መታረቁን ካገኘን በኋላ/ «አማላጅ ነው» «ሁልጊዜም በማያቋርጥ ሁኔታ… የምልጃ ተግባሩን ይፈጽማል፡፡» ማለት /በንስሐ የመታደስ አገልግሎት በጎ ፈቃደኛ ገጽ 69 ቁ.1 2002 ዓ.ም/ በየትኛውም አቀራረብ ጌታችንን ያለ ጥርጥር «ደካማ መድኃኒት ማድረግ» ነው፡፡ እንደ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ትምህርት፡፡      «ሁልጊዜም ሳያቋርጥ» ይፈጽማል ማለት አንዴ ማዳን የማይችል ነው ማለት ነው፡፡ ይህም በቅዱሳት መጻሕፍት ተደጋግመው ከተጠቀሱት «አንድ ጊዜ»  ከሚሉት ኃይለ ቃላት ጋር መላተም ነው፡፡

ይቆየን
ምንጭ፡ ሐመር ጥር 2003 ዓ.ም.

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር