“በሰላም ማሠሪያ፣ የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ትጉ» (ኤፌ 4፡3)

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡
“በሰላም ማሠሪያ፣ የመንፈስን አንድነት ለመጠበቅ ትጉ» (ኤፌ 4፡3)
እርስ በርሳችሁ በአንድ አሳብ ተስማሙ፣ የትዕቢትን ነገር አታስቡ፣ ነገር ግን የትሕትናን ነገር ለመሥራት ትጉ፡፡ ልባሞች የሆናችሁ አይምሰላችሁ፡፡ (ሮሜ.12፡16) ተብሎ እንደተጻፈ፡- የቅድስት ቤተክርስቲያን አገልግሎት፣ ምእመናንን ከማጠንከርና ከማብዛት አንፃር፣ ዘመኑን በዋጀ ሁኔታ መመራት ያለበት በመሆኑ፣ በዘፈቀደ ሳይሆን፣ እግዚአብሔርን አጋዥ አድርጐ በመግባባት፣ በፍቅር፣ በስልትና በዕቅድ የሚፈጸም ነው፡፡
«መከሩ ብዙ ሠራተኛው ግን ትንሽ ነው» (ማቴ. 9÷37) ተብሎ በቅዱስ መጽሐፍ እንደተጻፈው በዘመናችን ብዙ የሰው ኃይልና ዐቅም የሚጠይቁ የቅድስት ቤተክርስቲያን አገልግሎቶች ያሉ ሲሆን፤ ቅድሚያ የሚሰጠውን እየመረጡ ሥምሪት ማድረግ፣ ከቅዱሳን ሐዋርያት የምንማረው ትምህርት ነው፡፡ ለዚህም ቅድስት ቤተክርስቲያን በየዓመቱ በምታደርጋቸው የቅዱስ ሲኖዶስና የጠቅላይ ቤተ ክህነት አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ከፍተኛ ጉባኤያት፣የትኩረት አቅጣጫዎች ይያዛሉ፡፡ ለእነዚህ አቅጣጫዎች ተፈፃሚነትም፣ በመዋቅሯ ውስጥ ያሉ አካላትና ልጆቿ የሆኑት ምእመናን እርስ በርሳቸው በመናበብ ሐዋርያዊ አገልግሎቱን ይደግፋሉ፡፡
ይህ ሆኖ ሲታይ ግን፡- ያለው ውሱን ዐቅምና ሀብት በአግባቡ ሥራ ላይ እንዲውል ይደረጋል፤ ባለቤት እና ድጋፍ ያጣው አገልግሎት ተከታታይ እንዲኖረው፣ ሥርዓት ያልወጣለት አገልግሎት ሥርዓት እንዲወጣለት ይደረጋል እንጂ፣ «ልባሞች የሆን እየመሰለን» አስታዋሽ ያጣውን ሳናስታውስ ከግል ፍላጐት አንፃር በተጀመረ ነገር ላይ፣ እንደ ምድራዊ ሀብትና ሥልጣን ክርክር የምንፈጥርበት አይደለም፡፡
የ2010 ዓ.ም የቅዱስ ሲኖዶስ ርክበ ካህናት ምልአተ ጉባኤ ከሚያዝያ 24-29 ቀን 2010 ዓ.ም ሲካሄድ ቆይቶ ለቅድስት ቤተክርስቲያን ተልእኮ መሳካት በሚጠቅሙ የተለያዩ አጀንዳዎች ላይ ተነጋግሮ ውሳኔ አሳልፏል፡፡ በቅዱስ ሲኖዶስ አጀንዳነት ተይዘው ውይይት ከተደረገባቸው ነጥቦች መካከል፡አንዱ በኦሮሚያ ክልል በሚገኙ አንዳንድ ዩኒቨርሲቲዎች ውስጥ የሚማሩ ጥቂት የአፋን ኦሮሞ ተናጋሪ የግቢ ጉባኤያት ተሳታፊ ነበርን የሚሉ ተማሪዎች፣ ‹‹ከማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤ መዋቅር ተለይተን ለብቻችን እንማር›› በሚል ያቀረቡት ጥያቄ ይገኝበታል፡፡
የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤም ጉዳዩን በጥልቀት ከተወያየበት በኋላ ለቤተ ክርስቲያን አንድነት በሚጠቅም መልኩ‹‹ጥያቄዎቹ የተነሱባቸው ዩኒቨርሲቲዎች የሚገኙባቸው አህጉረ ስብከት ኃላፊነትን ወስደው፣ ጥያቄ ያቀረቡ ተማሪዎችን በሰንበት ት/ቤት ውስጥ ለብቻቸው እንዲማሩ ይደረግ››ሲል ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ ይህ ውሳኔ የማያሻማና ግልጽ ሆኖ ሳለ ቀድሞውኑ ሃይማኖታቸውን በስፋት በመማር በመንፈሳዊነታቸው ከመበልጸግ ይልቅ ማኅበሩን በሐሰት በመክሰስ ጉዳዩን አጀንዳ እንዲሆን ያደረጉት ጥቂት ግለሰቦች የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ውሳኔ በዚህ መልኩ መሆኑ አላስደሰታቸውም፡፡ በመሆኑም ውሳኔውን በማዛባት እና የተለያየ መልክ በመስጠት በተለያዩ ሚዲያዎች የተሳሳተ መረጃ ማናፈስ በመጀመራቸው የውሳኔውን ትክክለኛ ጭብጥ ማብራራት አስፈላጊ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ በዚህም መሠረት፡-
1ኛ) ምንም እንኳን ተማሪዎቹ ሁሉንም የአፋን ኦሮሞ ተናጋሪ የግቢ ጉባኤያት አባላትን የማይወክሉ ጥቂቶች ቢሆኑም፤ ቅዱስ ሲኖዶስ ‹‹አንዲት ነፍስም ብትሆን እንዳትጠፋ›› በሚል የቤተክርስቲያንን መርህ መሠረት በማድረግ፣ ጉዳዩን አጀንዳ አድርጎ መወያየቱን ማኅበራችን ማኅበረ ቅዱሳን ተቀብሎታል፡፡
2ኛ) ማኅበረ ቅዱሳን በአፋን ኦሮሞም ሆነ በሌሎች አገልግሎት በሚሰጥባቸው ቋንቋዎች የፈጸመው አገልግሎት በቂ እንዳልሆነ አበክሮ ይረዳል፡፡ በመሆኑም ተማሪዎቹ ‹‹ማኅበሩ በአፋን ኦሮሞ በብቃት አገልግሎት አልሰጠንም›› ሲሉ ያቀረቡት ቅሬታ አገልግሎቱ የበለጠ ሊጠናከርና ሊሰፋ ይገባል በሚለው መልኩ ከታየ አግባብነት ያለው ነው ብሎ መቀበል ይቻላል፡፡ነገር ግን በአንጻሩ የማኅበሩን ማንነት እና ዓላማ በማይወክሉ ክሶች፣ ለምሳሌ ‹‹በቋንቋችን እንዳንማር በደል አድርሶብናል፤ ዐሥራት በኲራት ይሰበስባል፤ በፀጥታ ኃይሎች አማካኝነት ያስፈራራናል ወዘተ›› (ለብፁዓን አበው የቀረበ ክስ) በማለት መወቀሱን አጥብቆ ይቃወማል፡፡ እነዚህንና መሰል አሉባልታዎችን በማስወራት ማኅበሩን ለቅዱስ ሲኖዶስ አባለት በከሰሱበት ወቅት ማኅበሩም ለቀረቡበት ክሶች ምላሹን እንዲሰጥ ዕድል መሰጠት የነበረበት ቢሆንም፣ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት አባቶቻችን ይህንን ያላደረጉት ማኅበሩ በእነዚህ መሰል ጉዳዮች ውስጥ እጁን እንደማያስገባ ስለሚያውቁ እና በማኅበሩ አሠራርና መርሖች ላይ ያላቸው እምነት ከፍተኛ በመሆኑ፣ ለብቻቸው መማር የፈለጉ ተማሪዎች በሀገረ ስብከት አማካኝነት ይማሩ በማለት ወስነዋል፡፡
3ኛ) የቅዱስ ሲኖዶሱን ውሳኔ በማጣመም ወይንም በተሳሳተ መንገድ ባለማወቅ በመተርጎም በአፈጻጸም ሂደት ውስጥ ችግር እንዳያጋጥም ከዚህ በታች የተገለጹት ነጥቦች በአንክሮ ሊታዮ ይገባቸዋል ብለን እናምናለን፡፡
ሀ) የግንቦቱ ርክበ ካህናት ውሳኔ ‹‹በሲኖዶስ ደረጃ›› ከመሆኑ በቀር ቀድሞውንም ቢሆን በአንዳንድ አህጉረ ስብከት ተመሳሳይ ውሳኔዎች እና ተሞክሮዎች ነበሩ፡፡ ለምሳሌ፡- በጅማ፣ በወለጋ እና በቡሌ ሆራ ከየአህጉረ ስብከቱ ሊቃነ ጳጳሳት ጋር በተደረጉ ውይይቶች፣ ቋንቋን መሠረት በማድረግ ‹‹በማኅበረ ቅዱሳን ሥር መሆን አንፈልግም›› ያሉትን በጣም ጥቂት የአፋን ኦሮሞ ተናጋሪ ተማሪዎች ‹‹የግድ ማኅበረ ቅዱሳን ሥር ካልሆናችሁ ከቤተ ክርስቲያን ውጡ›› ሊባል እንደማይገባ ግልጽ ስለሆነና የቅድስት ቤተክርስቲያን ጠባይ ባለመሆኑ ለጠያቂዎቹ የተሰጠው ምላሽ ‹‹በአህጉረ ስብከቱ ቀጥተኛ ክትትል ለጊዜው በአጥቢያዎቹ ሥር ሆናችሁ ተማሩ›› የሚል ውሳኔ ነበር፤ ምንም እንኳን አፈጻጸሙ ላይ ግጭቶች ቢስተዋሉም በዚያው አግባብ ለጥቂት ወራት ለማስኬድ ተሞክሯል፡፡ እናም ይህ ውሳኔና የቀደሙ ልምዶች ‹‹የማኅበረ ቅዱሳንን የቤተክርስቲያን አገልግሎት የጎዳ አዲስ ውሳኔ›› ተደርጎ መታየት ስለማይገባ የአህጉረ ስብከት መዋቅራት፣ የግቢ ጉባኤ አገልጋዮችና የማዕከላት አስተባባሪዎች አገልግሎታቸውን አጠናክረውና የጎደለውን ሞልተው ሊቀጥሉበት ይገባል፡፡
ለ) የግንቦቱ ርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ደግሞ ‹‹ዩኒቨርስቲዎቹ ያሉበት አህጉረ ስብከት ወጣቶቹን ተረክበው፣ መርሐ ግብር አዘጋጅተው፣ መምህራንን መድበው እንዲማሩ እንዲያደርጉ›› የሚል መሠረታዊ ነጥብ አስቀምጧል፡፡ (የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ) ይህም የሚያመለክተው ከዚህ በኋላ ‹‹በማኅበሩ መዋቅር ውስጥ መገልገል አንፈልግም›› ያሉት የተወሰኑ ተማሪዎች ለሚያደርጓቸው ማናቸውም እንቅስቃሴዎች ከአጥቢያም በላይ ሀገረ ስብከት ቀጥተኛ ኃላፊነት እንዳለበት አጽንዖት የሰጠ ውሳኔ ነው፡፡ አህጉረ ስብከቶቹ ስንቸገርበት የቆየነውን የተማሪዎቹን እንቅስቃሴ በቀጥታ መከታተላቸው ደግሞ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን የግቢ ጉባኤ ሐዋርያዊ አገልግሎት መቀላጠፍ ምቹ አጋጣሚን የፈጠረ ከመሆኑም በተጨማሪ ከዚህ በተሻለ ትጋት እንድናገለግል ክፍተቶቻችንን ለመለየት ረድቶናል፡፡ በተጨማሪም ‹‹አህጉረ ስብከቱ ይረከቧቸው፣ መምህራንን መድበው ያስተምሯቸው›› ተባለ እንጂ ‹‹ሌላ ግቢ ጉባኤ ይመስርቱ›› ስላልተባለ ይህ ውሳኔ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነትም ሆነ ለማኅበረ ቅዱሳን የግቢ ጉባኤ ክርስቲያናዊ አንድነትና የፍቅር አገልግሎት ትልቅ ፋይዳ ያለው ውሳኔ መሆኑ ሊታወቅ ይገባል፡፡
ሐ) ውሳኔው የፈጠረው መልካም ዕድል ፍሬ እንዳያፈራ ለማድረግ ከዚህ ቀደም ከልምድ እንደታየው መንፈሳዊ ሥነ ምግባራት ከጎደላቸው ጥቂት ወጣቶች በአፈጻጸም ላይ ችግር በመፍጠር አገልግሎቱን ሊያውኩ እንደሚችሉ ታሳቢ ሊደረግ ይገባል፡፡ እነዚህ ተማሪዎች በአጥቢያ ሥር የሚገኙትን የግቢ ጉባኤ ቦታዎች እና ንብረቶች ‹‹ይገባኛል›› ሊሉ ስለሚችሉ፤ አላስፈላጊ ግጭቶች ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡ እስካሁን በነበረው አካሄድ ‹‹በመንፈሳዊ መንገድ ለመፍታት፣ ቅዱስ ሲኖዶስም የመጨረሻውን ውሳኔ እስኪሰጥ›› በሚል ሁሉንም ነገር ለእነዚያ ወጣቶች ተውላቸው እያልን ግቢ ጉባኤያቱን ስንጫን ቆይተናል፡፡ ከዚህ በኋላ ግን ሁለቱም በየመዋቅሮቻቸው ሥር ሆነው እንዲማሩ ተወስኗልና የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች መብታቸው እየተገፈፈ እንዲቀጥል ዕድል መስጠት እንደማይገባ ማኅበሩ ያምናል፡፡
በመሆኑም በማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት መሳተፍ ‹‹አንፈልግም›› ብለው ከወጡ እና በሀገረ ስብከቱ እንዲማሩ በቅዱስ ሲኖስ ከተወሰነ በኋላ ከግቢ ጉባኤው ጋር የማይስማሙ ከሆነ ግን በየደረጃው ላሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ አካላት እንዲሁም ለክልሉ መንግሥትና የጸጥታ አካላት ማሳወቁ ተገቢ ይሆናል፡፡ ለሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያን እና የመንግሥት አካላት አሳውቀን ጉዳዩ ሳይፈታ በቸልታ ከታለፈ በተለያዩ የአስተደዳር ደረጃዎች ለሚገኙ አካላት ሁሉ ከወዲሁ አጥብቆ ማሳሰብ ይገባል፡፡ በየደረጃው የሚገኙ የማኅበረ ቅዱሳን መዋቅራትም ይህንኑ አቋም በየአካባቢያቸው ለሚገኙ የቤተ ክርስቲያንና የመንግሥት አካላት በአጽንዖት በማሳወቅ አገልግሎቱን ከማይገባ ሥነ ምግባር ከጎደለው ነገር የመጠበቅ ኃላፊነት ይኖርባቸዋል፡፡
መ) ከዚሁ ጋር ተያይዞ ከላይ የተገለጸው ለብቻችን የሚል የመለየት አጀንዳ ይዘው ለሚገኙ በጣት ለሚቆጠሩ ወጣት ያሉባቸው አህጉረ ስብከት ወረዳ ቤተ ክህነት እና የማኅበሩ ማእከላት ትልቅ የቤት ሥራ እንዳለባቸውም መዘንጋት የለባቸውም፡- በማኅበሩ የግቢ ጉባኤ መዋቅር ሥር በአፋን ኦሮሞ ለሚማሩት ተማሪዎች በልዩ ሁኔታ ትኩረት ሰጥቶ ማስተማር እና መከታተል፤ ከሃይማኖታቸው የበለጠ ሌላ አጀንዳ የሚበልጥባቸውን ወጣቶች አግባብነት ባለው የትምህርት መልእክትና ፍቅር በመስጠት ወደ እውነተኛ ክርስቲያናዊ አመለካከት እንዲመለሱ ማድረግ፣ በቋንቋው የምንሰጠውን አገልግሎት ከበፊቱም ይልቅ አጠናክረን በመቀጠል በተሳሳተ የአሉባልታ መረጃ፣ በክርስትና ትምህርት ባለመብሰል በሚፈጠር የመረጃ ትንታኔና ስሜታዊነት፣ በአንዲት ቅድስት ቤተክርስቲያን ወንድሞችና እኅቶች መካከል የሚዘራውን የጥላቻ ቅስቀሳ ተከትለው ከግቢ ጉባኤ መዋቅር የሚወጡ ተማሪዎችን ለመመለስ አትኩሮ መሥራት ተገቢ ነው፡፡ ማእከላቱ በልዩ ሁኔታ ሊሰጧቸው የሚያስቧቸውን አገልግሎቶች ለማሳካት የሚያስፈልጓቸውን ግብዓቶች እና አቅጣጫዎች በተመለከተ ከዋናው ማዕከል የግቢ ጉባኤያት አገልግሎት ማስተባበሪያ ጋር በቀጥታ እየተገናኙ፣ ችግሮችንና ጥያቄዎችን በፍጥነት በመወያየት መፍትሔ የመስጠት እና የማሰጠት ኃላፊነት አለባቸው፡፡
ሠ) እነዚህንና መሰል ተግባራትን ስናከናውን ደግሞ፣ ከየአህጉረ ስብከቶቹ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጋር መወያየትና መመሪያ እየተቀበሉ መተግበር፣ የቅዱስ ሰኖዶሱን ውሳኔ በተለያየ መንገድ በመተርጎም ወይም ዋጋ ባለመስጠት የራሳቸውን አቅጣጫ የሚከተሉትን ለሚመለከታቸው ሁሉ በፍጥነት ማሳወቅ፤ ከሚመለከታቸው ሌሎች የቤተ ክርስቲያን አካላትም ጋር ተቀራርቦ መመካከር፣ በአከባቢው ተሰሚነት ካላቸው ኦርቶዶክሳውያን የሀገር ሽማግሌዎች ጋር ጭምር እየተመካከሩ መሥራት በፍጹም ሊረሳ የማይገባው ነው፡፡ ይህ ሲሆን የግቢ ጉባኤያት ጉዳይ፣ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚካሄዱ ማናቸውም እንቅስቃሴዎች የማኅበረ ቅዱሳን ብቻ ሳይሆኑ የሁሉም የቤተ ክርስቲያኗ አካላት፣ ምእመናንና ለቅድስት ቤተክርስቲያን ሁለንተናዊ እድገት ለሚያስቡ፣ ለሚመኙና ለሚቆሙ ሁሉ ነውና፣ አስተማማኝ እና ቀጣይነት ያለው ክርስቲያናዊ የሆነ፣ ከቡድንና ከስሜት፣ ከድብቅ አጀንዳና ፍላጎቶች የጸዳ እውነተኛ መፍትሔ ያመጣል ብለን እናምናለን፡፡
በአጠቃላይም የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ዘመኑን የዋጀ ሆኖ በጐቿን የሚጠብቅ እንዲሆን ስንሻና፣ በእያንዳንዳችን ፍላጐትና ጥበብ ሳይሆን፣ በፍጹም መንፈሳዊነት መሆን ያለበት ስለሆነ፤ የሚፈጸሙ ተግባራት ሁሉ «ሰላምን ማሠሪያ የሚያደርጉ፣ የመንፈስ አንድነትን ለመጠበቅ የሚረዱ እንጂ፣ ተቃራኒ የሆነ ውጤት ለማምጣት ምክንያትና ምቹ ሁኔታ የማይሆኑ መሆናቸውን ማረጋገጥ ይገባናል፡፡» ኤፌ. 4÷3 ለዚህም የቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ትእዛዛተ እግዚአብሔርንና ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን በጠበቀ ሁኔታ ይፈጸም ዘንድ፣ የተጣመመውን እያቀኑ፣ የጐደለውን እየሞሉ መሄድ ይገባል፡፡ በመሆኑም ሁላችንም እንደ ባለቤት ሆነን በትጋት መከታተል፤ ከቅድስት ቤተክርስቲያን መዋቅር ማለትም ከአህጉረ ስብከት፣ ወረዳ ቤተ ክህነት፣ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት፣ አባቶች፣ ምእመናን፣ ሰንበት ት/ቤቶች እና ግቢ ጉባኤያት እንዲሁም ከሚመለከታቸው አካላት ሁሉ የሚጠበቅ ነውና፤ በሰላም ማሠሪያነት በቅድስት ቤተክርስቲያን ውስጥ የመንፈስ አንድነትን ለመጠበቅ የሚያግዙና የሚረዱ ነገሮችን ትኩረት ሰጥተን እንሥራ በማለት ማኅበሩ መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡
ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን!
ምንጭ ፤ሐመር መጽሔት 26ኛ ዓመት ቊጥር ግንቦት 2010ዓ.ም ቁጥር1

የማኅበረ ቅዱሳን ወቅታዊ የአዘክሮ መልእክት

ጥቅምት ፭ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

‹‹ወንድሜ ሆይ፥ በጎ አድራጊ እንጂ ክፉ አድራጊ አትኹን፤›› (፫ኛ ዮሐ. ቍ. ፲፩)::

በጌታችን ላይ በአይሁድ የተፈጸመውን ዂሉ ለድኅነተ ሰብእ እንደ ተፈጸመ ተቀብለን ሐተታ ላለማብዛት ብንተወው እንኳን መልካም የሚሠሩትን ክፉ ስም እየሰጡ ቤተ ክርስቲያንን የሚከፋፍል ሥራ መሥራት የተጀመረው በዚያው በሐዋርያት ዘመን እንደ ኾነ ቅዱስ መጽሐፍ ይመሰክራል፡፡ ‹‹ከእነርሱ አንዳንዶች በቅናታቸውና በክርክራቸው፥ ሌሎችም በበጎ ፈቃድ ስለ ክርስቶስ ሊሰብኩና ሊያስተምሩ የወደዱ አሉ፡፡ በፍቅር የሚያስተምሩም አሉ፤ ወንጌልን ለማስተማር እንደ ተሾምኹ ያውቃሉና፡፡ በኵራት ስለ ክርስቶስ የሚያስተምሩ ግን፥ ይህን አደርገው በእስራቴ ላይ መከራ ሊጨምሩብኝ መስሏቸው ነው እንጂ በእውነት አይደለም፤ በቅንነትም አይደለም፡፡ ነገር ግን ምን አለ? በየምክንያቱ በእውነትም ቢኾን፥ በሐሰትም ቢኾን ስለ ክርስቶስ ይናገራሉ፤ ሰዉን ዂሉ ወደ እርሱ ይጠራሉ፡፡ በዚህም ደስ ብሎኛል፤ ወደ ፊትም ደስ ይለኛል፤› (ፊልጵ. ፩፥፲፭-፲፰) በማለት የክርስትና ተቃዋሚዎች ቅዱስ ጳውሎስን ለማሳሰርና በእርሱ ላይ ከባድ መከራ ለማምጣት ሲሉ ራሱ የሚሰብከውን ቅዱስ ወንጌል ለመጠቀም መጣራቸውን ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ ገልጾልናል፡፡ ከመልእክቱ እንደምንረዳው ታላቁ ሐዋርያ በቅንዓትና በክፋትም ቢኾን ‹‹እሰይ! እንኳን ወንጌል ተሰበከ!›› ሲል ለበጎ አድርጎ ይወስደዋል፡፡ ድርጊታቸው ለበጎ ባይኾንም ሰማዕያንን ስለሚያዘጋጅለትና የበለጠ እንዲረዱ ስለሚጋብዝለት እንደ መልካም ዕድል ወስዶታል፤ ኾኖለታልም፡፡

እጅግ የሚያስደንቀው ደግሞ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እንቅፋት ይገጥመው የነበረው ቤተ ክርስቲያንን በሓላፊነት ሊያገለግሉ በተለያየ መዓርግ ከተሾሙት ወገኖች ጭምር መኾኑ ነበር፡፡ ይህም የተከሠተው ልክ እንደ ቀደመው ዂሉ ራሳቸው ሐዋርያት በነበሩበትና ከራሱ ከመድኃኔ ዓለም ክርስቶስ የሰሙትን የድኅነት ወንጌል በሚመሰክሩበት ዘመን ነበር፡፡ ከዚህም የተነሣ እንደ ፍቁረ እግዚእ ቅዱስ ዮሐንስ ያሉ ሐዋርያት ይሰሙናል ብለው ለሚያስቧቸው አገልጋዮች የሁለቱንም ዓይነት አገልጋዮች ጠቅሰው በጎውን እንዲመስሉና ክፉውን ግን እንዳይከተሉት ያሳስቡ እንደ ነበረ ለርእስነት ከተጠቀምንበት ኃይለ ቃል ለመረዳት ይቻላል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ ይህችን ሦስተኛዪቱን መልእክቱን የላካት ለደቀ መዝሙሩ ለጋይዮስ ሲኾን መልእክቱንና አደራውን የሚሰጠው በዘመኑ የነበሩትን ሁለቱንም ዓይነት አገልጋዮች በንጽጽር ካቀረበለት በኋላ ነበር፡፡ አንድ ምዕራፍ ብቻ ባላት፣ በይዘት አነስተኛ በኾነች፣ በጭብጥና በፍሬ ነገር ግን ከሌሎቹ መልእክታተ ሐዋርያት በማታንሰው በዚህች መልእክቱ ያነጻጸራቸው ሁለቱ አገልጋዮች ደግሞ ዲዮጥራጢስ እና ድሜጥሮስ ነበሩ፡፡

ሐዋርያው በዚህ መልእክቱ ቍጥር ዘጠኝ ላይ እንደ ገለጸው ዲዮጥራጢስ ፍቁረ እግዚእ የተባለ ቅዱስ ዮሐንስ ለቤተ ክርስቲያን የላከውን መልእክት እንኳን የማይቀበል፤ እንዲያገለግሉ የተፈቀደላቸውን አገልጋዮች የሚያንገላታና የሚቀበሏቸውን ሳይቀር ከቤተ ክርስቲያን ለማባረር ጥረት የሚያደርግ ክፉ አገልጋይ ነበረ፡፡ በአንጻሩ ድሜጥሮስ ደግሞ የቤተ ክርስቲያኒቱ የኾኑትን፣ ለዕድገቷና ለጥንካሬዋ የሚላላኩትን ዂሉ የሚቀበል፤ በመልካም የሚያስተናግድና ከበጎዎቹ ጋር ዂሉ አብሮ የሚሠራ፤ የልቡናውን ሳይኾን የቤተ ክርስቲያንን፤ የራሱን ብቻ ሳይኾን የአባቶቹን ድምፅ፣ ምክርና ዐሳብ ተቀብሎ የሚያስተናግድ ቅን አገልጋይ ነበር፡፡ ይህንንም ቅዱስ ዮሐንስ ‹‹ስለ ድሜጥሮስ ዂሉ ይመሰክሩለታል፤ እውነት ራሷም ትመሰክርለታለች፤ እኛም መስክረንለታል፤ ምስክርነታችንም እውነት እንደ ኾነች ታውቃላችሁ፤›› ሲል ይመሰክርታል (ቍ. ፲፪)፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ እነዚህን ሁለቱን አገልግዮች ያነጻጸረውም መልእክቱን የሚልክለት ሌላው ረድዕ ቅዱስ ጋይዮስ አብነት ሊያደርገው የሚገባው ዲዮጥራጢስን ሳይኾን ድሜጥሮስን መኾን እንዳለበት ለማሳየት ነው፡፡ ‹‹ወንድሜ ሆይ፥ በጎ አድራጊ እንጂ ክፉ አድራጊ አትኹን፤›› ማለቱም ስለዚህ ነው (ቍ. ፲፩)፡፡

በዘመናችን ያለው የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት የገጠመው ኹኔታም ከዚህ ኹኔታ ጋር በእጅጉ እንደሚመሳሰል ስለምናምን፤ ማኅበሩም ለአባላቱና ለወዳጆቹ ብቻ ሳይኾን በቤተ ክርስቲያን ላሉ አገልጋዮች ዂሉ የሚያቀርበው ወቅታዊ የአዘክሮ መልእክት ይኼው ‹‹ወንድሜ ሆይ፥ በጎ አድራጊ እንጂ ክፉ አድራጊ አትኹን፤›› የሚለው የቅዱስ ዮሐንስን ምክር ነው፡፡ የሐዋርያት ዘመን አገልግሎት በሁለቱ ዓይነት ሰዎች የተያዘ ከነበር የእኛ ዘመን አገልግሎት ከዚያ የተሻለ ነገር እንዴት ሊገጥመው ይችላል? ፍቁረ እግዚእ (ጌታ የሚወደው) የተባለው፤ በክርስቶስ ዕለተ ስቅለት እንኳን ከእግረ መስቀሉ ሳይርቅ ከመከራ መስቀሉ ያልሸሸው፤ እስከ ዕለተ ሞቱ ድረስም ሞተ ወልደ እግዚአብሔርን እያሰበ ፊቱን ለቅጽበትም ሳይፈታና ፈገግ ሳይል በፍጹም ዂለንተናው ያገለገለው፤ እኔ እስክመጣ ቢኖርስ ብሎ ጌታችን በቅርብ ሞትን እንደማያይ ቃል ኪዳን የገባለት፤ ንጽሕት ቅድስት ድንግል ማርያምን ‹‹እነኋት እናትህ›› ተብሎ ከእግረ መስቀል የተቀበለው ቅዱስ ዮሐንስ እስኪቸገር ድረስ ቤተ ክርስቲያንን ለፍላጎታቸው ብቻ የሚጠቀሙባት አገልጋዮች በዚያ ዘመን ከነበሩ ‹‹በእኛ ዘመን ለምን እንዲህ ያለ ነገር ኾነ?›› ብለን ልንደነቅበት የማይገባ እንደ ኾነ ለመረዳት የሚያስቸግር አይኾንም፡፡ በዚያው አንጻር ደግሞ እንደ ድሜጥሮስ እውነት ራሷ የምትመሰክርላቸው አገልጋዮች መኖራቸውን መዘንጋት ተገቢ አይደለም፡፡ ይልቁንስ ዋናውና ለእኛ ለዂላችን የሚያስፈልገው ነገር ‹‹እኛ ልንመስለውና አብነት ልናደርገው የሚገባው የትኛውን ነው?›› የሚለው ሊኾን ይገባል፡፡

የቍጥር መለያየትና የፍሬ ነገሩ መለዋወጥ ካልኾነ በቀር ዛሬም እንደ ጥንቱ ወይም በየዘመናቱ ዂሉ በታሪክ እንደ ተመዘገበው በቤተ ክርስቲያን ሁለቱም ዓይነት አገልጋዮች ይኖራሉ፡፡ ጌታችንም በወንጌል ‹‹ያን ጊዜ ሁለት ሰዎች በአንድ እርሻ ላይ ይኖራሉ፤ አንዱን ይወስዳሉ፤ ሁለተኛዉንም ይተዋሉ፡፡ ሁለት ሴቶች በአንድ ወፍጮ ይፈጫሉ፤ አንዲቱን ይወስዳሉ፤ ሁለተኛዪቱንም ይተዋሉ፡፡ ሁለት ሰዎች በአንድ አልጋ ላይ ይተኛሉ፤ አንዱን ይወስዳሉ፤ ሁለተኛዉንም ይተዋሉ፡፡ እንግዲህ ትጉ፤ ጌታችሁ በምን ሰዓት እንደሚመጣ አታውቁምና፤›› (ማቴ. ፳፬፥፵-፵፪) በማለት እስከ ዕለተ ምጽአት ድረስ ሁለቱም በእግዚአብሔር ቤት በአንድነት በአንድ የአገልግሎት መድረክ ላይ አንድ ዓይነት አገልግሎት እየፈጸሙ ለመኖራቸውና ለእግዚአብሔር የሚኾነውንና የማይኾነውን የሚለየውም እርሱ ራሱ በረቂቅ ፍርዱ እንደ ኾነ ገልጾልናል፡፡ ስለዚህም በአንዱ የወንጌል እርሻ ላይ እግዚአብሔር የሚወስደውና የሚተወው እንዳለ የሚያውቅ ባለቤቱ ስለ ገለጸልን የተጻፈውን ተረድተን፣ የጌታችንን ቃል ተቀብለን፣ በመኖሩ ከመደነቅ ወጥተን ልናደርገው ስለሚገባን ብቻ ማሰቡ ተገቢ ይኾናል፡፡ ቃሉ ዂላችንንም የሚመለከት የእውነትና የፍርድ ማስጠንቀቂያ ቃል ነውና፡፡

ስለዚህም በመግቢያው አንቀጽ ላይ እንደ ገለጽነው፣ ቅዱስ ጳውሎስን እንደ ገጠመው ዂሉ፣ በአሁኑ ጊዜም ወንጌልን ወይም ነገረ ቤተ ክርስቲያንን ለዓላማና ለጽድቅ የሚላላኩለት አሉ፤ በአንጻሩ ደግሞ እውነተኞቹን አጥፍቶ ፍላጎትን አንግሦ የራስን አጀንዳ ለማራመድ የሚሯሯጡትም አሉ፡፡ እነዚህም ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ገለጸው የንጹሐኑን አግልግሎት ሳይቀር አገልጋዮቹን ለመክሰስና ለመወንጀል በየዘመናቱ ከሚኖሩ የጥፋት አካላት ጋር ወዳጅነትን ለመግዛትና ለመሳሰሉት ይጠቀሙበታል፤ ሕዝብንም ለመቀስቀስና ከራሳቸው ጋር ለማሰለፍ ይሠሩበታል፤ መልካሙን ነገር ለክፉና ለጥፋት እየተረጐሙ ያቀርቡበታል ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስን እንደ ገጠመውም ከቤተ ክርስቲያን ፍላጎት፣ ከሐዋርያት እና ከተላውያነ ሐዋርያት (ከሐዋርያት ተከታዮች) በጎ ምክር ይልቅ የራሳቸውን እና የእኔ የሚሉትን አካል ጥቅም ለማስጠበቅ ብቻ ሊጠቀሙበት ይደክማሉ፡፡ ይህ የየዘመኑ ክሥተት እንደ ኾነው ዂሉ የእኛም ዘመን ትንሽና ደካማ አገልግሎት እንኳን ከዚህ ልታመልጥ አልቻለችም፡፡ ምንም እንኳን ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለፊልጵስዩስ ክርስቲያኖች ‹‹የእነርሱ ጥፋት፥ የእናንተም ሕይወት ይታወቅ ዘንድ የሚቃወሙን ሰዎች በማናቸውም አያስደንግጧችሁ፡፡ ይህንም ጸጋ እግዚአብሔር ሰጥቷችኋል፤ ነገር ግን ስለ እርሱ መከራ ልትቀበሉም ነው እንጂ ልታምኑበት ብቻ አይደለም፤›› (ፊልጵ. ፩፥፳፰-፳፱) ሲል እንደ ገለጸው የማይቀርና ዂሉም ነገር ልንቀበለው የሚገባ ቢኾንም አንዳንድ ጊዜ ግን ነገሩን ከሃይማኖት አንጻር ከማየት ወጥተን እንዳንገኝ ራስን መመርመሩ በእጅጉ የተገባ ነው፡፡

ምንም እንኳን ግብሩና ስሙ ብዙ የተራራቁ እንደ ኾኑ ጥናቶች ቢያመለክቱም የእኛ ዘመን የመረጃ ዘመን ነው ስለሚባል ኢንተርኔትን ተጠቅሞ በዋና መገናኛ ብዙኃንም ኾነ በየማኅበራዊ ሚዲያው የሚሠራጨውን ዂሉ አምኖና ተቀብሎ መሔድ ሳናውቀውም ቢኾን ወሬ ፈጣሪዎቹንና የጥፋት መልእክት አሠራጮችን ከመምሰል የሚያድን አይደለም፡፡ በማኅበራችን በማኅበረ ቅዱሳን ስም የሚሠራጩ አስመስለው ለሚከስሱና ቅዱስ ጳውሎስ እንደ ተናገረው ለተንኮልና መከራ ለመጎተት ኾነ ብለው የሚሠሩትን ከመተባበርም፣ ለይቶ ለማየትም አስቸጋሪ ደረጃ ላይ እንደ ደረሰ ለብዙዎች አያዳግትም፡፡ ማኅበሩ አቋሙን፣ መልእክቶቹንና ለሕዝበ ክርስቲያን ሊደርሱ ይገባቸዋል የሚላቸውን መረጃዎች ዂሉ በራሱ ይፋዊ ሚዲያዎች ወይም ደግሞ ማኅበሩን በሕግ በሚወክሉ አካላት የሚዲያ መግለጫዎች ብቻ የሚገልጽ ቢኾንም አንዳንዶች ግን እነዚህን ዂሉ ሳያጠሩና ሳይመረምሩ በማኅበሩ ስም ለክስ የሚያመቹ አድርገው የሚጽፉ አካላትን መረጃዎች በማኅበራዊ ሚዲያ ሳይቀር እንደሚቀባበሉ፤ የማኅበሩን አገልግሎትና አሠራር ከሚረዱት ምእመናን የሚደርሱት ጥቆማዎች ያመለክታሉ፡፡

ስለዚህም ኾነ ብላችሁና በተንኮልም ባይኾን የማኅበሩ መልእክቶችና አቋሞች መኾናቸውን ከማኅበሩ አካላት ሳትጠይቁና ሳትረዱ፤ ነገሩንም ሳትመረምሩ በችኮላና በስሜት ምን አልባትም ከዚህ በፊት በነበራችሁ የተሳሳተ መረጃና ግምት ምክንያት ለተጻፉና በማኅበራዊ ሚዲያው በሚናፈሱት ዂሉ ማኅበሩን ለምትወቅሱ፣ ለምትተቹና ለምትሰድቡም ዂሉ ወደ ማኅበሩ ቀርባችሁ ኹኔታዎቹን ሳታጣሩና መረጃ ሳትቀበሉ መዘገባችሁን እንድታቆሙ ለማሳሰብ እንወዳለን፡፡ ቢያንስ ቢያንስ የሙያ ሥነ ምግባሩ የሚጠይቀውን ያህል እንኳ ሳትጓዙ ለመፈረጅ መቻኮላችሁ የሚያስገርም ኾኖም አግኝተነዋል፤ በሌላው ላይ የማታደርጉትን ማደረጋችሁን በግልጽ ያመለክታልና፡፡ አውቃችሁና ወዳጅ መስላችሁ ለራሳችሁ የተንኮልና የክስ ዓላማ እንዲጠቅማችሁ በማሰብ ይህን በማኅበሩ፣ በአባላቱና በወዳጆቹ ስም ስማቸው በይፋ በማይታወቁ አካላት ስም ይህን የምታደርጉትንም ቢኾን አይጠቅማችሁምና ከዚህ ድርጊታችሁ እንድትታቀቡ እውነትና ፍቅር በኾነው አምላካችን ስም እናሳስባችኋለን፡፡ ባለማወቅ እና ለማኅበሩ አገልግሎት የሚያግዝ እየመሰላችሁ ይህን የምታደርጉ አባላትም ኾነ ደጋፊዎች ካላችሁም እንደሚባሉት ያሉ የስድብና የጥላቻ መልእክቶች ማኅበሩን ሊጠቅሙ ቀርቶ የአገልግሎቱ አደናቃፊዎችንም ሊጎዱ ስለማይችሉ፤ ሊጎዱ እንኳ ቢችሉ በክርስትናችን የተከለከሉና የተወገዙ ስለ ኾኑ ከማድረግ እንድትቆጠቡ ለማሳሰብ፣ በሐዋርያው ቃልም  ‹‹ወንድሜ ሆይ፥ በጎ አድራጊ እንጂ ክፉ አድራጊ አትኹን፤››  ለማለት እንወዳለን፡፡

የማኅበሩ አባላትና ወዳጆቹ፣ እንዲሁም የአገልግሎት አጋሮቹና ተባባሪዎቹ ዂላችሁ በቅዱሳት መጻሕፍት የተጻፉልንን ምክሮች ከማዘከርና ዂልጊዜም ቢኾን ከክፉው ተጠብቀን መልካም የኾነውን አርአያና አብነት ከማድረግ ልንቆጠብ አይገባንም፡፡ በትንሹ እና ሕይወታችንን በሙሉ ሳይኾን ከትርፋችን የምናገለግላት ቤተ ክርስቲያናችን በምድር ላይ እንዳሉ ሌሎች ተቋማት የዚህ ዓለም አደረጃጀትና አሠራር ብቻ የሚመራት ምድራዊ ተቋም ሳትኾን ረቂቅነትን እና መንፈሳዊነትንም ገንዘብ ያደረገች አካለ ክርስቶስ እንደ መኾኗ መጠን የምንፈጽመው ዂሉ መንፈሳዊነት ከጎደለው፣ ርባና ቢስ መኾኑን ለአፍታም ቢኾን ልንዘነጋው የሚገባ ነገር አይደለም፡፡ ለድርጊቶቻችን አብነት የምናደርገውም ቅዱስ ዮሐንስ እንዳስተማረው ብልሆቹን፣  መልካሞቹንና ደጎቹን እንጂ ሞኞቹን፣ ክፉዎቹንና ተንኮለኞቹን ሊኾን አይችልም፡፡ በዚያውም ላይ ከቅዱሳት መጻሕፍት ምክር ልንወጣ አይፈቀድልንም፡፡ ራሱ ጌታችን ‹‹ብትወዱኝስ ትእዛዜን ጠብቁ›› አለን እንጂ የተቃዋሚዎቻችን ሰይፍና ጎመድ ልንይዝ አልፈቀደልንም፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹ወገኖቻችንም ፍሬ ቢሶች እንዳይኾኑ፥ በሚፈለገውም ሥራ ጸንተው እንዲገኙ በጎ ምግባርን ይማሩ፤›› (ቲቶ. ፫፥፲፬) በማለት እንደ ገለጸው ከቤተ ክርስቲያን ወገን የኾናችሁ ዂሉ፣ በውጭ እንዳሉት ወደ ፍሬ ቢስነት ከሚወስድ ማንኛውም መንገድ ልትቆጠቡ ይገባችኋል፡፡

በእርግጥ ነቢየ እግዚአብሔር ኤርምያስ ‹‹በሕዝቤ መካከል ክፉዎች ሰዎች ተገኝተዋል፤ ሰዎችንም ይዘው ይገድሉ ዘንድ ወጥመድን ይዘረጋሉ፤›› (ኤር. ፭፥፳፮) ሲል እንዳመለከተን፣ በመካከል የተዘሩ አጥማጆችና ባለ ወጥመዶች ሊያሰነካክሉን፣ ስሜታችንን ሊያደፈርሱትና ወደ ወጥመዳቸው ሊያንደርድሩን በተለያየ ዘዴ ይገፉን ይኾናል፡፡ ኾኖም ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ ‹‹ነገር ግን ወንድሞች ሆይ፥ ትበዙና ትጨምሩ ዘንድ እንማልዳችኋለን፡፡  የዋሃንም ትኾኑ ዘንድ፥ ሥራችሁንም ታከናውኑ ዘንድ፥ እንዳዘዝናችሁም በእጃችሁ ትሠሩ ዘንድ፥ በውጭ ባሉት ሰዎችም ዘንድ ከማንም አንዳች ሳትሹ በሚገባ ትመላለሱ ዘንድ እንለምናችኋለን፤›› (፩ኛ ተሰ. ፬፥፲-፲፪) ሲል ያዘዘንን ቃል ማስታወስ አስፈላጊ ነው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም ‹‹ፍጹም ዋጋ እንድታገኙ እንጂ የሠራችሁበትን እንዳታጡ ራሳችሁን ዕወቁ፤›› (፪ኛ ዮሐ. ቍ. ፰) በማለት እንደዚህ ዓይነት ክፉ ተግባር የቀደመ መልካም ተግባራችንን ዋጋ ጨምሮ የሚያጠፋ መኾኑን በማስታወስ ፈጽመን እንዳናደርገው ያስጠነቅቀናል፡፡ ምንም ያህል ፈተና እና መከራ ቢመጣም እኛ ልናደርገው የሚገባን በመልካም ሥራና ልናደርገው የሚገባውን በማደረግ መጽናት ብቻ ይኾናል፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስም ‹‹በእግዚአብሔር የሚያምኑ ሰዎች በመልካም ምግባር ዂሉ መረዳዳትን እንዲያስቡ ታጸናቸው ዘንድ እወዳለሁ፤ ሰውንም የሚጠቅመው በጎ ነገር ይህ ነው፤›› (ቲቶ ፫፥፰) ሲል ለቲቶ ያሳሰበውና ለዂላችንም የደረሰው፣ ጥቅም የሚገኘው በመንፈሳዊነትና በእውነት ኾኖ በመጽናት ብቻ ስለ ኾነ ነው፡፡

አንዳንድ ጊዜ እንዲህ ያለውን ምክር የማይቀበሉና በራሳቸው ዐሳብ ሔደው ለቤተ ክርስቲያን ጥቅምና ረብ ማስገኘት የሚችሉ አስመስለው የሚናገሩ፤ ዐሳባቸውንም በአንዳንድ ጥቅሶች አስደግፈው በተቆርቋሪነት መንፈስ የሚገዳደሩአችሁ እንኳን ቢኖሩ፣ እንዲህ ያለውንም ፈተና በትዕግሥት እንድትወጡትና አሁንም በጎውን እንድትመርጡ እናሳስባችኋለን፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹‹እግዚአብሔር ወገኖቹን ያውቃቸዋል፤ የእግዚአብሔርንም ስም የሚጠራ ዂሉ ከክፉ ነገር ይርቃል› የሚለው ይህም ማኅተም ያለበት የእግዚአብሔር መሠረት ጸንቶ ይቆማል፤›› (፪ኛ ጢሞ. ፪፥፲፱) በማለት ለቅዱስ ጢሞቴዎስ ያሳሰበውም በእግዚአብሔር እና በቤተ ክርስቲያን ስም ሰዎች ያልተገባ ድርጊት ውስጥ እንዳይገቡ ለማስጠንቀቅ ነውና፡፡ ሐዋርያው እንደዚህ ያሉትን ሰዎች ከዚህም አለፍ ብሎ ‹‹እግዚአብሔርን እንደሚያውቁት በግልጥ ይናገራሉ፤ በሥራቸው ግን ይክዱታል፤ እነርሱም ርኩሳንና የማይታዘዙ፥ በበጎ ሥራም ዂሉ የተናቁ ናቸው፤›› (ቲቶ ፩፥፲፮) በማለት ድርጊታቸውን ከክህደት ይደምረዋል እንጂ ተቆርቋሪዎች ብሎ አያመሰግናቸውም፡፡ ይህን እውነት ተረድተናል የምንል ደግሞ ‹‹አሁንም ስለዚህ እናንተ እንደምታደርጉ ወንድሞቻችሁን አጽናኑ፡፡ አንዱም አንዱም ወንድሙን ያንጸው (፩ኛ ተሰ. ፭፥፲፩) በተባለው ቃል ተጠቅመን ልንተራረም እንጂ ልንተቻች አይገባንም፡፡ ቢቻል ቢቻል ‹‹ያን ጊዜም አለቆችና መሳፍንቱ ስለ መንግሥቱ በዳንኤል ላይ ምክንያት ይፈልጉ ነበር፤ ነገር ግን የታመነ ነበርና፥ ምንም በደል አልተገኘበትምና በእርሱ ላይ ሰበብና በደል ያገኙበት ዘንድ አልቻሉም፤››  (ዳን. ፮፥፬-፭) ተብሎ እንደ ተመሰከረለት እንደ ዳንኤል ሰበብ የለሽ እስከ መኾን መድረስ፤ ካልተቻለ ደግሞ ሊያስፈርድብን ከሚገባ ስሕተትና ጥፋት መቆጠብ ለክርስቲያን ዂሉ የሚገባው ተግባር ነው፡፡

ይህ ዂሉ ግን ክሶችንና ውንጀላዎችን ያስቀራል ማለት እንዳልኾነ የተጠቀሱት ጥቅሶች ለመጻፋቸው ምክንያት ከኾኑት ታሪኮች፣ ይልቁንም ከነቢዩ ዳንኤል ታሪክ የምንረዳው ነው፡፡ ኾኖም ክርስቲያኖች ይህን ዂሉ ሊያደርጉት የሚገባቸው በሌላ በምንም ምክንያት ሳይኾን ‹‹ነገር ግን እግዚአብሔር ስለ ፈተነንና ወንጌሉን ለማስተማር የታመን ስላደረገን እንዲህ እናስተምራለን፤ ሰውን ደስ ለማሰኘት እንደሚሠራም አይደለም፤ ልቡናችንን ለመረመረው ለእግዚአብሔር ነው እንጂ፤›› (፩ኛ ተሰ. ፪፥፬) ተብሎ እንደ ተጻፈው አገልግሎታችን እናገለግልሃለን የምንለውን እግዚአብሔርን ደስ ስለማሰኘት ብቻ ነው፡፡ ማኅበሩም ቢኾን ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ ‹‹ልጆቼ በእውነት ሲሔዱ ከመስማት ይልቅ ከዚች የምትበልጥ ደስታ የለችኝም፤›› (፫ኛ ዮሐ. ቍ. ፬) ሲል እንደ ገለጸው አባላቱና ደጋፊዎቹ ብቻ ሳይኾኑ ክርስቲያኖች ዂሉ በእውነት ሲሔዱ ከማየት የተለየ ፍላጎት የለውም፡፡ ስለዚህም ይህ መልእክት የደረሳቸውንም ዂሉ ከታዘዙት በበለጠ እንዲፈጽሙት ይበረቱ ዘንድ ‹‹በመታዘዝህ ታምኜ፥ ካዘዝኹህም ይልቅ እንደምትጨምር ዐውቄ ጻፍኹልህ፤›› (ፊልሞና ፩፥፳፩) የሚለውን ቃለ ሐዋርያ እያስታወስን፤ በቃለ ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ በድጋሜ ‹‹ወንድሜ፣ ወዳጄ (አባል፣ ደጋፊ፣ ተባባሪ፣ ክርስቲያን ዂሉ) ሆይ፥ በጎ አድራጊ እንጂ ክፉ አድራጊ አትኹን›› በማለት ማኅበረ ቅዱሳን መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር!

ማኅበረ ቅዱሳን

በአገልግሎታችን የሚከሰቱ ፈተናዎችን የምናልፋቸው በእግዚአብሔር ኃይል ነው

 ኅዳር 23 ቀን 2007 ዓ.ም.

ማኅበረ ቅዱሳን ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መጠናከር በርካታ ተግባራትን እንደ አንድ የቤተ ክርስቲያን ልጅነቱ ሲፈጽም የቆየ የአገልግሎት ማኅበር መሆኑ ይታወቃል፡፡ ምንም እንኳን ማኅበሩ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ለመንፈሳዊ ዓላማ የተቋቋመ ቢሆንም መልካም ነገርን የማይወደው ጥንተ ጠላት ሰይጣን ዲያብሎስ የተለያዩ ፈተናዎችን ሲጋርጥበት ኖሯል፡፡ ማኅበሩም የሚደርሱበትን ፈተናዎች ከምእመናን፣ ከካህናትና ከብፁዓን አባቶች ጋር በመሆን በትዕግሥትና በጸሎት ሲያልፋቸው ቆይቷል፡፡

 

አንዱን ሲያልፍ ሌላው እየተተካም ከዚህ ደርሷል፡፡ ምንም እንኳን በየጊዜው ፈተናው መልኩን እየቀየረ ቢመጣም ማኅበሩ ከኃይለ እግዚአብሔርና ከአባቶች የኖላዊነት ተግባር ውጭ የሚመካበት ነገር የለውምና ይህንኑ አጋዥ አድርጎ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሚያስፈልጋትን ያህል ባይሆንም “ጋን በጠጠር ይደገፋል” እንዲሉ የተቻለውን አገልግሎት ለመስጠት ጥረት ሲያደርግ ቆይቷል፡፡

በየጊዜው ከተነሡት ፈተናዎች መካከል አንዱ በቅርቡ የተከሰተውና ማኅበሩን ቅድሚያ በማኮላሸትና በመምታት ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ለማጥቃት የሸመቀው የአፅራረ ቤተ ክርስቶያንና የተሐድሷውያኑ ዘመቻ እንዲሁም የቤተ ክርስቲያኒቱን ገንዘብ በመመዝበር የግል ጥቅማቸውን ለማሳካት በሚጥሩ ኃይሎች የተጀመረው የተቀናጀ እንቅሰቃሴ ነው፡፡ እነዚህ አካላት በተደጋጋሚ እያቀዱ የጀመሩት አልሳካ ሲል «እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ባንሔድ፣ ከፈቃዱም ተቃራኒ ብንሆን ነው» ብለው ራሳቸውን ከመመርመር ይልቅ ውስጥ ለውስጥ ሥራቸውን ሲሠሩ ከቆዩ በኋላ በዚህ በያዝነው ዘመን መስከረም ወር መጨረሻ ጀምሮ በስውር ሲያደርጉት የነበረውን ፈተና በስም ማጥፋት መልኩ ወደ ዐደባባይ ማውጣት ጀመሩ፡፡

 

የቤተ ክርስቲያኒቱን አምልኮተ እግዚአብሔር ወደ ተሐድሶ መናፍቅነት ለመቀየርና የግል ጥቅማቸውን ለማካበት የሚፈልጉት እነዚህ አፅራረ ቤተ ክርስቲያን “ለእንቅስቃሴያችን ማኅበሩ እንቅፋት ነው፤ ማኅበሩ ካለ ያሰብነውን ማሳካት አንችልም” የሚል የጥፋት አቅጣጫ ይዘው በመነሣት ከተለያዩ አካላት ጋር ሊያጋጩት ሞከሩ፡፡ የውሸት ክስ ጸንሰውም በዐደባባይ ማኅበሩን ወቀሱት፡፡ አንደበታቸው ባቀበላቸው ልክ የስድብ ናዳ አወረዱበት፡፡ በሠሩት ጎዳና እንደ ልባቸው ለመመላለስ እንዲረዳቸውም ያሸማቀቅንና ያስፈራራን መስሏቸው አገልጋይ ምእመናንንና ለቤተ ክርስቲያን የሚቆረቆሩ ብፁዓን አባቶችን አሻቅበው ተሣደቡ፡፡

በጣም የሚደንቀውና የሚገርመው እነዚህ አፅራረ ቤተ ክርስቲያን ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በዓመት አንድ ጊዜ የምትጠራውን የአጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ፣ ዓለማዊ በሆነ ጥበብ መጠቀሚያ ለማድረግና ውጤቱም በቀጣዩ ቅዱስ ሲኖዶስ ስብሰባ ላይ ተፅፅኖ እንዲፈጥር በማሰብ በስብሰባው ውስጥና በማይጠበቅ ቦታ የማይጠበቅ ተግባር የፈጸሙ መሆኑ ነው፡፡

በዚህ ድርጊት ያዘነው ሕዝበ ክርስቲያን ግን ፈተናዎቹ ዐዲስ ባይሆኑበትም ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያንን ጠብቀው ዐሥራት በኩራታቸውን በሚያዋጡ ምእመናን ገንዘብ የሚኖሩ አገልጋይ ነን ብለው ራሳቸውን በሚያሞካሹ የተወሰኑ ግለሰቦች እንደዚህ ዓይነት አሳፋሪ ተግባር መፈጸሙ እንደ መንፈሳዊነቱ የሚያሳዝን ቢሆንም ለእውነት የቀና ልቡናን ስጣቸው ብሎ ወደ ፈጣሪ ከመጸለይ ውጭ የሚለው የለም፡፡ እግዚአብሔር ዕድሜ ለንስሐ የሚሰጥና ሁሉን የሚፈጽምበት የራሱ ጊዜ አለው፤ እስከዚያው ድረስ ግን ውሸት የሕዝበ ክርስቲያኑን ኃዘን ግምት ውስጥ ሳታስገባና ሕገ ቤተ ክርስቲያን ይገሥጸኛል ሳትል በዐደባባይ ፈረስ መጋለቧን በመቀጠሏ የቤተ ክርስቲያን ልዕልና እየተነካ፣ በቤተ ክርስቲያን የቤተ ክርስቲያን ሰዎች መስለው የሚያደርጓቸው እንቅስቃሴዎች መልካም ስም ላላት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ጥላሸት የሚቀባ እየሆነ መጣ፡፡

 

የራሷን ችግር በራሷ መፍታት የምትችለው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሥርዓት አልባዎች ሥርዓት የሌላት እስከመምሰል ደረሰች፡፡ ማኅበሩ የቤተ ክርስቲያኒቱ የበላይ አካል ቅዱስ ሲኖዶስ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት መስፋፋት ውሳኔ እንደሚሰጥና ችግሮችን ሁሉ እንደሚፈታ ያምናልና በመንፈስ ቅዱስ ለሚመራው ቅዱስ ሲኖዶስ መንፈሳዊ ፍትሕ ያገኝ ዘንድ እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነቱ ጥያቄውን አቀረበ፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱ የበላይ ወሳኝ አካል የሆነው ቅዱስ ሲኖዶስም ሁኔታውን አጥንቶና አጣርቶ በምልዓተ ጉባኤው ውሳኔ ሰጠ፡፡ ይህም በመሆኑ የቤተ ክርስቲያን የሆኑ አካላት ሁሉ እግዚአብሔርን አመሰገኑ፡፡

ማኅበሩም በተፈጸመበት የስም ማጥፋት ድርጊት እጅግ ያዘነ ቢሆንም፣ ከንቱ የሆነውን ውንጀላ እንደ ፈተናነቱ ከመቀበል ውጭ አማራጭ አልነበረውም፡፡ ያላደረገውን አደረገ፤ የሠራውን አልሠራም እየተባለ ፍጹም አሳዛኝ የሆኑ የስም ማጥፋት ጾሮች የተወረወሩበት ማኅበረ ቅዱሳን እግዚአብሔር ሥራውን የሚሠራበት፣ ዕድሜ ለንስሓ ዘመን ለፍስሐ የሚሰጥበት ቀን አለው ብሎ ስለሚያምን እግዚአብሔር እንደፈቀደ አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡ ምእመናን በጸሎትና በዕንባ፣ በየበረሃውና በየገዳማቱ ያሉ መነኮሳት በምኅላ፣ የማኅበሩ አገልጋዮች በትዕግሥት፣ ብፁዓን አበው በውሳኔያቸው የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያልሆነውን መንፈስ ገሠጹት፡፡

ይህንን ከቅዱስ መንፈስ ያልሆነ ትጋት ቅዱስ ሲኖዶስ መርምሮ እንዲቆምና እንዲታረም አቅጣጫ ባይሰጥበት ኖሮ የቤተ ክርስቲያኒቱን ንጹሕ አገልግሎት አዳክሞና ጥላሸት ቀብቶ የሚያልፍ ነበር፡፡ ይህም አፅራረ ቤተ ክርስቲያን መረባቸውን ከላይ እስከ ታች የዘረጉት የተሐድሶ መናፍቃን አቀንቃኞችና በቤተ ክርስቲያኒቱ ሀብትና ንብረት የግል ሀብታቸውን ማካበት የለመዱት አማሳኞች በአጭር ጊዜ ውስጥ የቤተ ክርስቲያኒቱን ልዕልና ተደፋፍረው እንዳልሆነች ለማድረግ በመቀናጀት የተንቀሳቀሱበት ነው፡፡ ነገር ግን በመንፈስ ቅዱስ የሚመራው ቅዱስ ሲኖዶስ የተደበቀውን መርምሮ፣ የራቀውን አቅርቦ ለጥፋት የተነሣሣውን መንፈስ ገሥጾታል፡፡

በዚህ ለቤተ ክርስቲያኒቱ አገልግሎት መጠናከር አኩሪ በሆነው መንፈሳዊ ውሳኔ ምእመናን፣ አገልጋይ ካህናትና የገዳማት አባቶች ከእሱ ፈቃድ ውጭ ምንም ማድረግ የማይቻልበትን እግዚአብሔርን በማመስገን፤ እንደ ቀድሞው ሁሉ ተስፋቸውን በዚሁ የቤተ ክርስቲያኒቱ የበላይ አካል በሆነው በቅዱስ ሲኖዶስ ላይ አድርገዋል፡፡

ከዚህ በኋላም ቢሆን እንኳን ለእኛ ለደካሞቹ፣ ለጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያልተኛው ጠላት ዲያብሎስ የተቃናውን ለማጣመም፣ የቀረበውን ለማራቅና የተሰበሰበውን ለመበተን ጦሩን ወደ ሰገባው አይመልስምና ባንዱ ሲሸነፍ በሌላ አቅጣጫ እየመጣ የቤተ ክርስቲያናችንን አገልግሎት ለማደናቀፍ ጉድጓድ መቆፈሩ ስለማይቀር እንደነዚህና መሰል ችግሮች ከዚህ በኋላም ሊከሰቱ ይችላሉ፡፡ በመሆኑም እንደ ሰሞኑ ሁሉ ወደ ፊት የሚመጣውን የሰይጣን ፈተና ኃይለ እግዚአብሔርን አጋዥ አድርጎ እንዲገሠጽ፤ ከላይ እስከ ታች በየተዋረዱ ያሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ አገልጋዮችና ምእመናን ፈተናውን በክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር ለማለፍ በጸሎትና በአገልግሎት ሊተጉ ይገባል፡፡

ክርስቲያን ኃይሉ እግዚአብሔር ነውና እግዚአብሔርን በጸሎት በመጠየቅ እያንዳንዱ ነገር ሲከሰት ምን ይዞ እንደመጣ፣ የተቀነባበረበትን ዓላማ በመረዳትና በመገንዘብ ለቅድስት ቤተክርስቲያን አገልግሎት «እንደ ርግብ የዋኆች እንደ እባብ ልባሞች ሁኑ» ማቴ. 10÷16 ተብሎ የተጻፈውን አምላካዊ ቃል መፈጸም ይሆናል፡፡ የችግሩን ምንጭ ከሥር መሠረቱ ከተረዱ በኋላም ለቤተ ክርስቲያን በመናገርና ቅዱስ ሲኖዶስ በሚሰጠው ውሳኔና አቅጣጫ መሠረት ሐዋርያዊ ተልዕኮዋ የተጠናከረ ሆና ትቀጥል ዘንድ በአገልግሎትና በጸሎት መትጋት ያስፈልጋል፡፡

ምእምናን፣ በየተዋረዱ ያሉ አገልጋይ ካህናት እንዲሁም ብፁዓን አባቶች ለቤተ ክርስቲያን በሚያደርጉት መንፈሳዊ ጽናትና ትጋት የሰይጣን ቀስት እየወደቀ፣ አቅሙ እየደከመ፣ ተስፋ እየቆረጠ ይሔዳል፡፡ በዚህም የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ከመቼውም በላይ የተፋጠነ ሆኖ፤ ክብሯ ሳይነካ፣ ማንነቷ ሳይበረዝ ሥርዓቷና ትውፊቷ እንደተጠበቀ ከትውልድ ወደ ትውልድ ትቀጥላለች፡፡

ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚቀናው ማኅበረ ቅዱሳን የፈተናዎቹ ጥንስስና ዝግጅት በአፀደ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የማይጠበቅ በመሆኑ ቢያዝንም በአባላቱ ፅናት፣ በምእመናን ድጋፍና በብፁዓን አባቶች ውሳኔ ሥውሩ ደባ ስለተገለጠ፤ በጨለማ ወይም በግንብ ውስጥ ወይም ማንም አላየኝ በሚል በስውር ሆኖ ማንም ቢሠራ ከእሱ ሊሠወር የማይችለው እግዚአብሔር፣ አፅራረ ቤተ ክርስቲያንን ያስታግሥልን፤ አገልግሎታችንን ይባርክልን፤ አባቶቻችንን ይጠብቅልን ከማለት ውጭ የሚለው ነገር የለም፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ፅኑ ዓላማው ኃይለ እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመልካም ጎዳና ላይ እንድትራመድ ሲሆን፤ እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነቱ የሚያዝነው ደግሞ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን መገፋትና የነገረ ሃይማኖት መፋለስ ሲደርስ ነው፡፡

 

በመሆኑም በእውነት በማኅበሩ የተፈጸመው የቤተ ክርስቲያኗ አገልግሎት ከእውነታው ውጭ በሆነ መንገድ በዐደባባይ ሲሰደብና ሲከሰስ እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነቱ አዝኗል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ሲሰጥ ደግሞ ውሳኔው ለቤተ ክርስቲያኒቱ ስለሚበጅ ለእግዚአብሔር ምስጋና ይግባው ብሏል፡፡ ለዚህም የምእመናን ኀዘን፣ በየተዋረዱ ያሉ የአገልጋይ ካህናትና ብፁዓን አባቶች ጥረትና ትጋት እግዚአብሔር ከሰጣቸው ሓላፊነት የሚጠበቅ ቢሆንም፣ ከውንጀላዎቹ በስተጀርባ ከተዘጋጀው ዕቅድ አንፃር የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን አባቶች የኖላዊነት ተግባር ሁላችንም እንድናይ አድርጎናል፡፡

ምንም እንኳን እግዚአብሔር አምላክ ስለ ቤተ ክርስቲያን ለሚገፉና በእውነት ወደ እርሱ ለሚቀርቡ ሰዎች ዋጋ የሚከፍል ቢሆንም፤ በሰው ሰውኛው ደግሞ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚቆጩና የሚያዝኑ ምእመናንንና ደፋ ቀና የሚሉ አባቶችን የአገልግሎት ዘመን ይባርክልን ልንልበት ይገባል፡፡ የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት ምድራዊ ያልሆነ ሰማያዊ ዋጋ ለማግኘት ስለሆነ የሚገፋውና የሚተቸው በዚህ ምክንያት ለቤተ ክርስቲያኒቱ ካለው ቁርጠኛ አቋም የተነሳ ነው፡፡ ዓላማው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትምህርተ ሃይማኖት፣ ሥርዓትና ትውፊት ተጠብቆ ከትውልድ ወደ ትውልድ እንዲተላለፍ ማድረግ ነውና ይህንን ዓላማውን እግዚአብሔርን አጋዥ አድርጎ፣ በብፁዓን አበው ፈቃድ ተመርቶና ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እናት አድርጎ እንደ ባለቤቱ ፈቃድ ይቀጥላል፡፡ ክርስትናና ፈተና እስከመጨረሻው ትግል እየገጠሙ የሚኖሩ እንደ መሆናቸው መጠን የቱንም ያህል ለማገልገል በሚያደርገው ሩጫ ስሕተት ከታየበትም በአባቶች ለመታረምና ለመታዘዝ ዝግጁ ሆኖ አገልግሎቱን ይፈጽማል፡፡ ጠላት ቢነሣበትና ስለ ቤተ ክርስቲያን ግፍ ቢደርስበት እግዚአብሔርን እስከ ያዘ ድረስ ከዓላማው ወደ ኋላ አይልም፡፡

በመሆኑም በየወቅቱ ለሚከሰቱ ፈተናዎች ኃይለ እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ የምድራዊቷን ሳይሆን የሰማያዊቷን ኢየሩሳሌም ወራሽ ለመሆን በጸሎት ከመትጋት ውጭ ክርስቲያን የሆነ ሁሉ ጠላት ዲያብሎስን የሚያሳፍርበት መንገድ የለውምና በቤተ ክርስቲያናችን ላይ በየጊዜው ለሚከሰቱ ችግሮችና በአፅራረ ቤተ ክርስቲያን ለሚነሱ እንዲሁም የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ለሚሸረሽሩ ፀረ ኦርቶዶክሳዊ አቋሞች ሕዝበ ክርስቲያኑ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ውሳኔ መስጠታቸውን በፅናት የተከታተለበት ሁኔታ ምንጊዜም ከአንድ ሕዝበ ክርስቲያን የሚጠበቅ ነው፡፡

ፈተናው በቤተ ክርስቲያን ላይ እንጂ በማኅበሩ ላይ ብቻ የመጣ ስላልሆነ እያንዳንዳችንም ለምድራዊ ሕይወታችን ስንተጋ ቤተ ክርስቲያንን ስለረሳንና እግዚአብሔር ስለሚወደን ፈተናው ለተግሣፅ፣ ለአመክሮና ለተዘክሮ የመጣ ነው ብለን ማመን አለብን፡፡ በመሆኑም ከቤተ ክርስቲያን የራቅን ቀርበን፤ ራሳችንን በቅዱስ ቃሉ በማነፅ፤ በሰበካ መንፈሳዊ አገልግሎት በትጋት በመሳተፍ፤ ዐሥራት በኩራታችንን ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመስጠት፤ ልጆቻችንን ከሕፃንነታቸው ጀምሮ በሰንበት ትምህርት ቤት ተኮትኩተው እንዲያድጉና ተተኪ እንዲሆኑ በማድረግ፤ ሩቅ ሆነን ይህ ጎደለ በሚል ብቻ ጣት ቀሳሪዎች ሳንሆን፤ ባለቤቶችና ችግር ፈቺ እንዲሁም የጎደለ ሞይ፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንና የአባቶች ተላላኪና አጋዥ መሆን እንደሚጠበቅብን ልንገነዘብ ይገባል፡፡

 

ይህ ክስተት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዘመኑን የዋጀች ሆና አገልግሎቷን በሰፊው ለማድረስ ከሚጠበቅባት አንፃር ያለችበትን ሁኔታ እንድናውቅ ያደረገበት አጋጣሚ ስለሆነ፤ ከምንጊዜውም በላይ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ሁላችንም እንደየአቅማችንና ተሰጥዎአችን ድርሻችንን ልንወጣ ያስፈልጋል፡፡ አላወቅንም እንዳንል በምንወደው ድራማ በሚመስል እውነተኛ ታሪክ የተገለጸልን መልእክት ገና ያልበረታን መሆናችንን እግዚአብሔር በማየቱ ለማስተማር ነውና፤ ዋጋ በመስጠት «የሰው ልጅ ሕይወቱንና ዘለዓለማዊ ቤቱን አጥቶ ዓለሙን ቢያተርፍ ምን ይበጀዋል» ተብሎ እንደተጻፈ ማቴ 16÷26 ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከቀድሞው ይልቅ ልንተጋ ይገባል፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ባለማወቅ የእርሱን መለኮታዊ ኃይል በመገዳደር እና በድፍረት ቤተ ክርስቲያኒቱን የሚያሳድዱ አፅራረ ቤተ ክርስቲያንን ልቦናቸውን መልሶ፤ ማስተዋልን ያድልልን፤ ለቤተ ክርስቲያናችን አገልግሎት ደፋ ቀና የሚሉትን ምእመናንን፣ ካህናትንና ብፁዓን አባቶችን ይጠብቅልን፤ ያበርታልን፡፡

በአጠቃላይ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ፈተናዋ ብዙ እየሆነ በመምጣቱ ልጆቼ! በማለት በምትጣራበት በዚህ ዘመን ልትልከውና በትክክለኛ አቅጣጫ ልትመራው የሚቻላትን ልጇን፣ እንደ ባዕድ ሰው ቆጥሮ ይህን ያህል ዘመቻ ለማድረግ የተሄደበት ሁኔታ ላላየው ሰው መታመን የማይችል ቢሆንም በመንፈሳዊ ዐይን ከተመለከትነው፡- ፈተናዎቹ የምንማርባቸውና የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ስም ያስነሱ ከመሆናቸው በቀር በግለሰብ ደረጃ አሸናፊም ሆነ ተሸናፊ የሌለባቸው ናቸው፡፡ በመሆኑም በጉዳዩ ዙሪያ እያንዳንዳችን የቆየንባቸውን መንገዶች አግባብነት በጥበብ ሰማያዊ ደግመን ደጋግመን በመመርመር ለሰማያዊ እንጂ፣ የዚህ ዓለም ለሆነው ከንቱ ነገር እልህ ሳይዘን፣ የቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ አገልግሎት ለማጠናከር የሚያስችሉ ነገሮችን በመተጋገዝና በፍቅር ልንሠራ ይገባል፡፡

 

ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የቆመው ማኅበረ ቅዱሳን ከእግዚአብሔር በቀር ፍጹም የሆነ ማንም እንደሌለ በማመን፣ ካጠፋ ምንጊዜም ለመታረም ዝግጁ፣ በአባቶች ሲታዘዝም የተቻለውን ለመፈጸም የቀና፣ ለሕግና ለሥርዓት ተገዥ ሆኖ የሚሠራ መሆኑን እያረጋገጠ፤ ቀሪ የሆኑት ምድራዊ ሀብቶች እያንዳንዳችንን ጠልፈው ሳይጥሉን፣ የእግዚአብሔርን ኃያልነትና ቻይነት ሳንዘነጋ ራሳችንን እየመረመርን በታሪክ ተወቃሽ፣ በእግዚአብሔርም ተጠያቂ ላለመሆን በሰጠን ጸጋ ለመልካም ነገርና ለተቀደሰው የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ቢያንስ እንቅፋት ላለመሆን ከበረታንም በመክሊታችን አትራፊ በመሆን፣ ምድራዊቷን ሳይሆን ሰማያዊቷን ኢየሩሳሌም ለመውረስና ሌሎችም እንዲወርሱ ምክንያት ለመሆን እንትጋ በማለት ማኅበሩ መልእክቱን ያስተላልፋል፡፡

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን

ምንጭ፡- ሐመር ዘኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ኅዳር 2007 ዓ.ም.

 

 

የማኅበራችን አገልግሎት የክርስቲያናዊ ግዴታችን አካል ነው

 ሚያዚያ 22 ቀን 2006 ዓ.ም.

ክርስቲያኖች የተጠሩት በክርስቶስ እንዲያምኑ በስሙም እንዲጠመቁ ብቻ አይደለም፤ ራሳቸውን ዝቅ አድርገው የፍቅርና የርኅራኄ ሥራ ለሰዎች ሁሉ እንዲሠሩም ነው፡፡ “ስለ እርሱ መከራ ደግሞ ልትቀበሉ እንጂ በእርሱ ልታምኑ ብቻ አይደለም” /ፊል 1÷29/ ያለው የሐዋርያው ቃሉ ይሄንን ያመለክተናል፡፡ ይኸውም የመንፈስ ፍሬዎችን ይዘን እንድንገኝ የታዘዝንበት ነው፡፡ /ገላ 5÷22/

በዚያም ላይ ተመሥርተን ስለ እግዚአብሔር ብለን ስለነፍሳችን ድኅነት መልካሙን ሁሉ እናደርጋለን፡፡ ሰዎች ቢራቡ ማብላት፣ ቢጠሙ ማጠጣት፣ ቢታረዙ ማልበስ፣ ቢታሰሩ መጠየቅ … ወዘተ ሁሉ የመንፈስ ፍሬዎች የሆኑ የፍቅርና የቸርነት ሥራዎች ናቸው፡፡ ይሄንን ለማድረግም በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም አምኖ መጠመቅ ብቻ በቂ ነው፡፡ የተጠመቅነውም ይሄንን የፍቅርና የቸርነት ሥራ ሠርተን በእግዚአብሔር ፊት እንድንከብር ነውና፡፡

በዚህም ምክንያት የማኅበራችን የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ላለፉት ከሃያ ዓመታት በላይ ለሆኑት ጊዜያተ ይሄንን እምነት በመያዝ በየገዳማቱ ላሉ አባቶች፣ በየአብነት ትምህርት ቤቶቹ ላሉ ሊቃውንት በተቸገሩት ነገር ሁሉ በመድረስ ክርስቲያናዊ ምግባረ ሠናይ ተግባራትን ሲፈጽሙ ቆይተዋል፡፡ አባላቱ በሙያቸው፣ በገንዘባቸውና በጉልበታቸው ሁለንተናዊ ተግባራትን ለቤተ ክርስቲያኒቱ አገልግሎት ሲሰጡ ቆይተዋል፡፡ ይሄ ሁሉ የሚፈጸመው ግን የአምልኮ አካል ሆኖ እንጂ በዓለማዊ፣ መሥሪያ ቤቶችና ድርጅቶች እንደሚፈጸም ከምድራዊ ሥልጣንና ከዕለት ጉርስ አንጻር የሚታይ አገልግሎት አይደለም፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ በእንዲህ ዓይነት መንገድ የሚፈጸሙ መንፈሳዊ ተግባራትን ምንነትን ሲያመለክት እንዲህ ማለቱ አይረሳም “ንጹሕ የሆነ፤ ነውርም የሌለበት አምልኮ በእግዚአብሔር አብ ዘንድ ይህ ነው፤ ወላጆች የሌላቸውን ልጆች ባልቴቶችንም በመከራቸው መጠየቅ፥ በዓለምም ከሚገኝ እድፍ ሰውነቱን መጠበቅ ነው።” /ያዕ. 1÷27/

ከልዩ ልዩ ማኀበራዊ አገልግሎቶች በመለስ ስብከተ ወንጌልን በማስፋፋት ለመናፍቃን ጥያቄዎች ሊቃውንቱን ምንጭ አድርጎ መልስ በመስጠት ፍጹም መንፈሳዊ ተግበራትን ሲፈጽምም ቆይቷል፡፡ ማኅበሩ የሚሠራባቸው መንገዶችም ጊዜውን የዋጁ ሆነው በሰፊ መዋቅር ይከናወኑ እንጂ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ ውስጥ በቅዱሳን ስም በተሰባሰቡ የሰንበቴና የጽዋ ማኅበራትም እንደየዘመኑ ሁኔታ ሲፈጸም የቆየ ነው፡፡

በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚገኙ የቤተ ክርስቲያን ልጆች በአቅራቢያቸው ባሉ አጥቢያዎች ተሰባስበው በቃለ እግዚአብሔር በመማር በሰብእናቸውና በመንፈሳዊ ሕይወታቸው አድገው ከሥነ ምግባራዊ ችግሮች ተጠብቀው ለሀገርና ለቤተ ክርስቲያን ተቆርቋሪ እንዲሆኑ ያተጋል፡፡ ከከፍተኛ ትምህርት ተቋማቱም ተመርቀው በሙያቸው በልዩ ልዩ የሥራ ሓላፊነቶች ላይ ሲቀመጡ ቤተክርስቲያንን በሙያቸው በየአጥቢያው እንዲያገለግሉ ያደርጋል፡፡ እነዚህ ሁሉ ሓላፊነቶች ግን ከክርስቲያናዊ ግዴታ የሚመነጩ እንጂ ከተራ ሥጋዊ ምኞትና ዓለማዊ ሐሳብ የመነጩ አይደሉም፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ሁሉም የቤተክርስቲያን አካላትና ምእመናን ቢሆንም እግዚአብሔር በሰጣቸው ጸጋ የፍቅርና የቸርነት ሥራን በመሥራት ሕያዊት የሆነችው ነፍስ የምትድንበትን ሥራ በጋራም በተናጠልም እንዲያከናውኑ የሚሻ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን ጥላ ሥር ያሉ የመንፈሳዊ ማኅበራት ተግባራት ሁሉ ከዚህ አንጻር ሊታይ ይገባል፡፡ እነዚህ ተግባራት በጎ ተግባራት ናቸው፡፡ ለነፍሳችን መዳን ወሳኝ ናቸው፡፡ በጎ መሆናቸውን ካወቅን ደግሞ ሌሎች አካላት ተደሰቱም አልተደሰቱም ሳንፈጽም የምንተወው ነገር አይደለም፡፡ “እንግዲህ በጎ ለማድረግ አውቆ ለማይሠራው ኃጢአት ነውና።” /ያዕ 4÷17/፡፡

ስለዚህ ማንኛውም ወገን እውነታዎችን ፈሪሃ እግዚአብሔር በተሞላበት መነጽር እንዲመለከት እየጠየቅን፤ የማኅበሩ አገልግሎት በመክሊቱ አትርፎ ከመገኘት የመነጨ ዓለማዊ ያልሆነ መንፈሳዊ እንቅስቃሴ መሆኑን በውል ማጤን ይገባዋል፡፡ አገልግሎቱን ቤተ ክርስቲያን ባለችበት በመላው ዓለም እንዲሠራ ፈቃድ የሰጠው ቅዱስ ሲኖዶስና አባቶች በጸሎትና ምክር ማገዛቸው እንዳለ ሆኖ ወደፊትም አገልግሎቱ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ሊያደርጉ የሚችሉ እርምጃዎችን ሊወስዱ ይገባል፡፡

የማኀበሩ አባላትም የምንሠራው በስሙ ተጠምቀን አምነን የተከተልነው የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ትእዛዝ መነሻ አድርገን መሆኑን ሁልጊዜም በማሰብ በሚመጡ ፈታኝ ነገሮች ሁሉ ሳንፈራ ሳንደነግጥ በአገልግሎታችን ልንጸና ይገባል፡፡ “ብረሳሽ ቀኜ ትርሳኝ” ብለን የገባንላትን ቃል ጠብቀን ለእኛና ለመላው ሕዝብ ነፍስ መዳን የምናደርገውን ትጋት እናጠናከር እንላለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

ክርስትና “አክራሪነት”ን የሚያበቅል ነገረ ሃይማኖታዊ መሠረት የለውም

ነሐሴ 21 ቀን 2005 ዓ.ም.
 
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በሀገራችን የሃይማኖት “አክራሪነት” ስጋት እንዳለ በተለያዩ ወገኖች የሚነሣ ሐሳብ አለ፡፡ የ “ሃይማኖት አክራሪነት” በሀገራችን የለም የሚል እምነት አይኖርም፡፡ “አክራሪነት” የሚተረጎመውም የራስን የሃይማኖት የበላይነት ለማስፈን ሲባል ሌላው የሃይማኖት ሐሳቡን እንዳይ ገልጥ፣ ተግባራዊ የአምልኮ ሥርዓቱን እንዳይፈጽም ማድረግ፣ በኃይል ወይም በዐመፅ ቦታ ማሳጣት ተደርጎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ አንድ ቤተ እምነት ራሱ ከሚከተለው እምነት ውጪ ያሉ በቁጥር ትንሽ ወይም ብዙ ተከታይ ያሏቸው እምነቶች በአንድ ሀገር ወይም ቦታ መኖር የለባቸውም ብሎ ማመን ወይም ማድረግ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ይህ ደግሞ የሰዎችን የፈቃድ ነጻነት፣ ምርጫ አለማክበር፤ አለመጠበቅ ነው፡፡

ከላይ የተጠቀሰው አስተሳሰብ ደግሞ በምንም መስፈርት ቢመዘን ክርስትና ሊሸከመው የሚችለው አይደለም፡፡ የሚጋጨውም ከክርስትና መሠረታዊ ባሕርይና አካሔድ ጋር ነው፡፡ ክርስትና ወደ ሰዎች የመጣው በራሱ በሥግው አምላክ ኢየሱስ ክርስቶስ ሥራና ቃል ነው፡፡ ጌታችን ወደ ሰዎች ቀርቦ ወደ እርሱ እንዲመጡ የሳባቸው የፈቃድ ነጻነታቸውን ጠብቆ ነው፡፡ በደዌ ነፍስ የተያዙትን በትምህርቱ፣ በደዌ ሥጋ የተያዙትን በተኣምራቱ ሲፈውስ ሁሉንም “ልትድን ትወዳለህን” እያለ ፈቃዱን ጠይቆ የፈጸመው ነበር፡፡ ልባቸው ወደ እርሱ ያዘነበሉትን “ተከተሉኝ” ብሎ ወደ መንግሥቱ እየጋበዘ ከእርሱ ኅብረት ደምሯቸዋል፡፡ “ሸክማችሁ የከበደ ወደ እኔ ኑ፤ እኔም ዐሳርፋችኋለሁ” ብሏቸዋል፡፡

ጌታችን ያለፈቃዳቸው ከጉባኤው የደመራቸው ወገኖች አልነበሩም፡፡ ተሰብስበውም ከነበሩት የሚያስተምረው ኃይለ ቃል ከምስጢሩ ታላቅነት የተነሣ የጸነናቸው ታዳሚዎች እንኳን ጥለውት በሔዱ ጊዜ አልተቃወመም፡፡ በእግሩ ስር የቀሩ ሐዋርያቱንም “እናንተስ ልትሔዱ ትወዳላችሁን” እያለ ደቀመዛሙርቱን እንኳን ፈቃዳቸውን ያረጋግጥ ነበር እንጂ፤ ከዋልኩበት ውላችሁ፣ ካደርኩበት አድራችሁ፤ አበርክቼ አብልቼ፣ በፍቅሬ ረትቼ፤ በተአምራቴ ፈውሼ፣ ተኣምራት የምትሠሩበትን ኃይል አልብሼ ካቆየኋችሁ በኋላ ስለምን ትተውኛላችሁ ብሎ አምላካዊ ሥልጣኑን ተጠቅሞ ሊጫናቸው አላሰበም፡፡ በመሆኑም ክርስትና “ከአንተ ወደ ማን እንሔዳለን” ያሉ ቅዱሳን ሐዋርያትና በሐዋርያት ትምህርት የጸኑ፣ እስከ ዓለም ፍጻሜ የሚነሡ ምእመናን በፈቃዳቸው የሚኖሩበት ሃይማኖት ነው፡፡   

ጌታችን እንድንቃወም ያስተማረን ሌሎችን በኃይል ወደ እርሱ መሳብን ብቻ ሳይሆን ሊያስገድዱን የሚመጡ፣ መልካሙን እንዳንፈጽም የሚከለክሉንንም ቢሆን በኃይል ለመቋቋም መሞከርንም ነው፡፡ ጌታችን ለጴጥሮስ “ሰይፍን የሚያነሡ በሰይፍ ይጠፋሉ፤ ሰይፍህን ወደ ሰገባው መልስ” ያለው ለዚህ ነበር፡፡ ለዚህም ነው ክርስትና በባሕርዩ “አክራሪነት”ን የሚያስተ ናግድበት መስክ የለውም፤ በጽኑም ይቃወመዋል፡፡

ክርስትና ሰዎች የእምነት ሐሳባቸውን እንዳይገልጹ አይገ ድብም፡፡ ሌሎች በእምነቱ ላይ ያላቸውን ጥያቄ እንዳያቀርቡም አይከለክልም፡፡ ስለያዘው እውነት በራሱ የሚተማመን ሃይማኖት ነው፡፡ ስለሆነም እርሱም ይሔንኑ መብት በጽኑ ይፈልገዋል፡፡ ለሚጠይቁት ሁሉ መልስ ለመስጠት የተዘጋጀ፣ የራሱን የድኅነት መንገድ ለመመስከር የተሰማራ ሃይማኖት ነው፡፡ የክርስቶስን መንግሥቱንና ጽድቁን ለሚሹ ሁሉ “መንግሥተ ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ” እያለ ይጮኻል፡፡ ስለዚህ ክርስትና የ “አክራሪነት” ሐሳብ ከመሠረቱ ሊበቅልበት የማይችል ሃይማኖት ነው፡፡

በተግባርም ቢሆን ከቤተልሔም ዋሻ አንሥቶ እስከ ምድር ጥግ እንዲስፋፋ ያስቻለው በረድኤተ እግዚአብሔር ተደግፎ፣ በፍቅር ስቦ፣ በመግደል ሳይሆን በመሞት የብዙዎችን ነፍስ ለመታደግ የሚኖር ሃይማኖት በመሆኑ ነው፡፡ ስለዚህ የቃለ ሃይማኖቱን ኃይል የተአምራቱን ብዛት የአማኞቹን ጽናት አይተው የራሳቸውን እምነትና ፍልስፍና ለመጫን የሞከሩበትን አምልኮ ባዕዳንን ይከተሉ ከነበሩ ወገኖች ጀምሮ ሃይማኖትን የዕድገት፣ የነጻነት፣ የፍትሕ፣ የእኩልነት ወዘተ ጸር አድርገው እስከሚያስቡ የማርክሲዝም ሌኒንዝም ተከታዮች ድረስ የነበሩ “አክራሪዎች” ክርስትናን ሊያጠፉት ሲሞክሩ ታይቷል፡፡ ነገር ግን ሰይፋቸውን በትዕግስት ተቋቁሞ፣ እነርሱ እያለፉ እርሱ ሳያልፍ ዘላለማዊ ሆኖ እዚህ የደረሰ ሃይማኖት ሆኗል፡፡

ክርስትና በ“አክራሪነት” ሲመላለስ አልኖረም፡፡ በክር ስትና ስም የሚፈጸሙ ወይም በታሪክ ወስጥ የተፈጸሙ አሁን “አክራሪነት” ያልነው ጠባይ የተንጸባረቀባቸው አጋጣሚዎች ቢኖሩ እንኳን በክርስትና ስም ልንቀበለው የምንችለው አይሆንም፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትም “ቢቻላችሁስ ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ” የሚል የፍቅር ቃል ሰጥተውናል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንም ሐዋርያዊ ውርስ ያላት ጥንታዊ ቤተክርስቲያን ስትሆን እነዚህ ከላይ የተሰጡ፣ ጌታችን መድኅኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረውን ትምህርትና ቅዱሳን ሐዋርያት ያስተላለፉትን መልእክት ታከብራለች፤ ትጠብቃለች፤ ነገረ ሃይማኖታዊ መሠረቷም ይኸው ነው፡፡

ስለዚህ ቤተክርስቲያን የእኔ ናቸው በምትላቸው ሕጋዊ መዋቅሮቿ፣ በመዋቅሮቿም ላይ የሚያገለግሉ አገልጋይ ካህናትና ምእመናን ሰንበት ትምሀርት ቤቶችና ማኅበራት ሁሉ ከላይ ከተጠቀሰው ክርስቲያናዊ መንገድ የወጣ በ”አክራሪነት” የሚታሰብባቸውን ተግባራት ሊፈጽሙ አይችሉም፤ ካደረጉም ቤተ ክርስቲያኒቱ ባላት ቀኖናዊ ሕግ መሠረት ይዳኛሉ፡፡ ይታረማሉ፤ ካልሆነም ይለያሉ፡፡

ቤተክርስቲያን ያላት ነገረ ሃይማኖታዊ ሐሳብ ይህ መሆኑን ከተስማማን፣ በዚህ መሠረታዊ አስተምህሮዋ ላይ ቅሬታ የሌለን ከሆነ፣ መልካምነቱን የምንረዳ ከሆነ፣ በዚህ ላይ ያልበቀለ፣ ያላፈራ፣ መልካም ያልሆነ የቤተክርስቲያን እንቅስቃሴ ካለ መመርመር ይገባል፡፡ በዚህ ጊዜ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “መልካም ዛፍ ሁሉ መልካም ፍሬን ያፈራልና፤ ክፉ ዛፍም ክፉ ፍሬን ያፈራል፤ መልካም ዛፍ ክፉ ፍሬን ማፍራት፣ ክፉ ዛፍም መልካም ፍሬን ማፍራት አይችልም፤ መልካም ፍሬን የማያፈራ ዛፍ ሁሉ ይቆረጣል፤ ወደ እሳትም ይጣላል እግዲህ ከፍሬያቸው ታውቋቸዋላችሁ” /ማቴ 7፥17/ ያለው ቃሉን እናስባለን፡፡ 

 
ማኅበረ ቅዱሳንም ከዚህ የወጣ አካሒድ ሊኖረው አይችልም፡፡ በቤተክርስቲያኒቱ መዋቅር ውስጥ ያለ ሓላፊነት የሚሰማው የአገልግሎት ማኅበር ነውና፡፡ “አክራሪነት”ን በመቃወምና የሃይማኖቶችን መከባበር ተገቢነት አስመልክቶ በተደጋጋሚ በገለጻቸው አቋሞቹ አስታውቋል፡፡ ለዚህም በሐመር መጽሔት በግንቦት ወር 2001 ዕትም፣ ስምዐ ጽድቅ በርእሰ አንቀጹ በጥቅ ምትና በኅዳር 1999 ዕትም፣ መጽሔተ ተልእኮ ዘማኅበረ ቅዱሳን በምንለው የማኅበሩ የሕዝብ ግንኙነት መጽሔት በነሐሴ 2004 ዓ.ም ዕትም በዚሁ ጉዳይ ያለውን አቋም ገልጿል፡፡  

ይሁን እንጂ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ “አክራሪነት” እንዳለና አልፎ አልፎም “ማኅበረ ቅዱሳን” ብለው በስም ጠቅሰው ለመፈረጅ የሞከሩ በአንዳንድ አካባቢ ያሉ መንግሥት ያዘጋጀውን የውይይት መድረክ የተጠቀሙ አስፈጻሚዎች ነበሩ፡፡ እነዚህ አልፎ አልፎ መንግሥት “አክራሪነት”ን ለመከላለከል ለሚወስዳቸው እርምጃዎች አጋዥ የሚሆን ውይይት በየደረጃው በሚያደርግበት አጋጣሚ የማኅበረ ቅዱሳንን ስም በኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ ይታያል ላሉት “አክራሪነት” ማሳያ አድርገው ማቅረባቸው ለማኅበሩ አባላት ደስ የሚያሰኝ አልነበረም፡፡

“አክራሪነት” ከላይ በጠቀስነው እሳቤ መሠረት የሚታይ ከሆነ የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ላሳዩት የ‹‹አክራሪነት›› ጠባይ ግልጽና ተጨባጭ ማስረጃ ማቅረብ ያሻል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ከዚህ ቀደምም ከማንም በፊት በሀገራችን የአክራሪነት ዝንባሌዎች እንዳሉ በማመልከት በኩል ግንባር ቀደም ሚና ተጫውቷል፡፡ “አክራሪዎች” በተለያዩ አካባቢዎች አብያተክርስቲያናትን ሲያቃጥሉ ክርስቲያኖችን ሲያርዱ አካሔዱ መልካም አለመሆኑን በመጠቆም እርምጃ መውሰድ እንደሚገባ በማሳሰብ ሀገራዊ ሓላፊነቱን ለመወጣት ሞክሯል፡፡ የሃይማኖቶች መከባበር በመላው ሀገሪቱ እንዲሰፍን ያለውን ቁርጥ አቋምም አንጸባርቋል፡፡

በእርግጥ ማኅበረ ቅዱሳን ቤተክርስቲያናችን ጠንካራ የአስተዳደር፣ የአሠራር፣ የአገልግሎት አካሔድ እንዲኖራት አቋም ይዞ የሚያገለግል ማኅበር ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ካህናትና ምእመናን ሁሉ የጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ቃል አክብረው፤ የሐዋርያትን የሊቃውንት አባቶችን የሃይማኖት ትምህርት፣ ሥርዓት፣ ታሪክና ትውፊት አውቀው እንደ ሃይማኖቱ ሕግና ሥርዓት እንዲመላለሱ ያተጋል፡፡ የተዘጉ አብያተ ክርስቲ ያናት እንዲከፈቱ፣ ሊቃውንቱ በረሃብ በችግር ተፈተው ከአገልግሎት እንዳይቦዝኑ ለማድረግ ይተጋል፡፡ የሌላ ቤተእምነት ተከታዮች በቤተክርስቲያን ትምህርት ላይ ለሚያነሧቸው ጥያቄዎች መልስ በመስጠት የዕቅበተ እምነት ሥራ ይሠራል፡፡

 

በኮሌጅና በዩኒቨርሲቲ ትምህርታቸውን እየተከታተሉ ያሉ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች ካደጉበት መንደር /ቀዬ/ ርቀው ወደ ተለያዩ ትምህርት ተቋማት ሲመጡ በአቅራቢያ በሚገኙ አጥቢያዎች ሰብስቦ በሃይማኖታቸው ተጠብቀው እንዲኖሩ፣ በመልካም ሥነምግባር ታንጸው ሀገራቸውንና ቤተክርስቲ ያናቸውን በታማኝነት እንዲያገለግሉ፣ ከሱስና ከዝሙት ተጠብቀው ከደዌ ሥጋ ደዌ ነፍስ እንዲርቁ ያደርጋል፡፡ በጠረፋማ አካባቢዎች ስብከተ ወንጌልን ያስፋፋል፡፡ በጤናና ትምህርት ጉዳዮችም በማኅበራዊ አገልግሎት ተሳትፎ እንዲኖረው እየጣረ ነው፡፡ እነዚህ ተግባራቱ ሁሉ ከቤተክርስቲያኒቱ የአገልግሎት መንፈስ የተቀዱ ናቸው፡፡ ለየትኛውም ወገን ቢሆን የሚጠቅሙ እንጂ ስጋት የሚሆኑ ተግባራት አይደሉም፡፡ በሃያ ዓመት የአገልግሎት ቆይታውም ያስመዘገባቸው ውጤቶች በስጋት ሳይሆን በአስፈላጊነት ሊያስፈርጀው የሚችል ነው፡፡

ስለዚህ የትኛውም ወገን ቢሆን እውነታውን ለመረዳት ጥረት ማድረግ ይገባዋል፡፡ ቸግሮች አሉ ቢባሉ እንኳን ተገቢነት ከሌላቸው ዘመቻዎች ቆጠብ ብሎ ከቤተክርስቲያኒቷ አባቶችና ጉዳዩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር አግባብነት ያላቸው ውይይ ቶችን ማድረግ በቂ ይሆናል፡፡ ማኅበሩ የቤተክርስቲያኒቱ ሉዓላዊ ሥልጣን ባለቤት የሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ እንዲሠራ ከሰጠው ተግባራት ውስጥ ወደ ‹‹አክራሪነት›› አምባ ያስገባውን ወሰን አለፈ ያስባሉትን ነጥቦች ነቅሶ ማሳየት፣ እንዲህ የሚያስብሉ የተፈጸሙ ተግባራትንና ተግባራቱን ማኅበሩ ሓላፊነት ወስዶ የፈጸመው ተግባር መሆኑን የሚያሳዩ ማስረጃዎችን ማቅረብ አግባብ ይሆናል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ሁልጊዜም ቢሆን የሃይማኖት አባቶች የሚያዙትን እንጂ ከዚያ ተላልፎ በራሱ ፈቃድ የሚፈጽመው አንዳችም ተግባር አለመኖሩን መረዳት ይገባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

  • ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት 21ኛ ዓመት ቁጥር 4 ነሐሴ 2005 ዓ.ም.

 

ብዙ ከተሰጠው ከእርሱ ብዙ ይፈለግበታል

ሐምሌ 4 ቀን 2005 ዓ.ም.

የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ቤተ ክርስቲያናችን ካሏት አህጉረ ስብከት ሁሉ ለየት የሚልበት ባሕርያት አሉት፡፡ ሀገረ ስብከቱ የሀገሪቱ ዋና ከተማ እንደመሆኑ በተለያዩ ምክንያቶች ከሁሉም አህጉረ ስብከት የሚመጡ ክርስቲያኖች አገልግሎት የሚያገኙባቸው ገዳማትና አድባራት ያሉበት ሀገረ ስብከት ነው፡፡ በተለያዩ ቋንቋዎች የሚናገሩ የተለያዩ ባህሎች ያሏቸው የቤተ ክርስቲያን ቤተሰቦች ተገናኝተው በአንድነት መንፈስ አገልግሎት የሚያገኙበትና የሚቀበሉበት ሀገረ ስብከትም ነው፡፡

ሀገረ ስብከቱ በርካታ የቤተ ክርስቲያናችን መምህራን ሊቃውንት የሚገኙበትም ሀገረ ስብከት ነው፡፡ በመንፈሳዊው ትምህርት ብቻ ሳይሆን በዓለሙ የሚሰጠውን ማኅበራዊና የተፈጥሮ ሳይንስ፣ የሙያና የቀለም ትምህርቶች የተማሩ አንቱ የተባሉ የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆችም የሚገኙበት ሀገረ ስብከት ነው፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ ቤተ ክርስቲያንን በታላቅ ፍቅር የሚጠብቃት፣ አገልግሎቷን ዕለት ዕለት የሚሻ ቸርና የዋህ ሕዝበ ክርስቲያን ያለበት ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ቤተ ክርስቲያን የምትተዳደርበትን ብዙ የገንዘብ የቁሳቁስና የሰው ኃይል ሀብት ይዞ የሚገኝ ነው፡፡ ከዚህም የተነሣ አርአያነት ያለው አግልግሎትን ሊሰጥም እንደሚችል የሚታሰብ ነው፡፡

እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት ሀገረ ስብከቱን ልዩ የሚያደርጉ ባሕርያቱ፤ ሀገረ ስብከቱ ያሉትን ብዙ ሀብቶች የሚያሳይ ነው፡፡ ብዙ ካለው ደግሞ ብዙ ይፈለግበታል የሚለው መጽሐፋዊ ቃል ከሀገረ ስብከቱ የምንሻውን ነገር በተሰጠው ልክ እንድንጠብቅ ያስገድዳል፡፡ ከሁሉም በላይ ደግሞ በነገር ሁሉ ለሌሎች አህጉረ ስብከት የሚኖረውን አርአያነት፡፡

ሀገረ ስብከቱ ብዙ ገንዘብ የሚያንቀሳቅስ እንደመሆኑ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ሌሎች አህጉረ ስብከት ምሳሌ የሚሆን የገንዘብ አስተዳደርና አጠቃቀም ሥርዓት ሊኖረው ይገባል፡፡ ብዙ የገንዘብ አስተዳደር ሊቃውንት የሆኑ በርካታ የቤተ ክርስቲያን ልጆች ባለሙያዎች ያሉበት ሀገረ ስብከት በመሆኑ ቀጥሮ በማሠራትም ይሁን የነጻ አገልግሎት ሥርዓት በመዘርጋት አሠራሩን ዘመናዊ፣ ግልጽነት ያለው፣ ተጠያቂነት ያለበት፣ ለሙስና በር የማይከፍት ማድረግ ይቻለዋል፡፡ በአጠቃቀም ረገድም በግልጽነት በተሠራ ዕቅድና የዕቅድ አፈጻጸም ሥርዓት፣ አጠቃላይ አገልግሎቱን ባገናዘበ ሁኔታ፣ አሳማኝ በሆነ መንገድ ሊተገበር ይገባዋል፡፡ የንብረት አስተዳደሩም በተመሳሳይ መቃኘት ይገባዋል፡፡

ሀገረ ስብከቱ ያሉት ቅርሶች አያያዝና ጥበቃ ጉዳይም እንዲሁ መሻሻል ያለበትና በተሻለ አያያዙም ለሌሎች በቅርስ ሀብታቸው ለበለጸጉ አህጉረ ስብከት ምሳሌ ሊሆን ያስፈልጋል፡፡ ያለውን ለአገልግሎት የሚያስፈልግ የሰው ኃይልም ወጥ በሆነ ሥርዓት መምራት አለበት፡፡ አድባራትና ገዳማት ከልክ በታች ወይም ከልክ በላይ መያዝ አለመያዛቸውን፣ ለአገልግሎቱ የሚያስፈልገውን ሙያ ይዘው መገኘት አለመገኘታቸውን፣ ተገቢ እና ወጥነት ባለው የቅጥርና የዝውውር ሥርዓት እየተመራ መሆኑን፣ ከዚያ ጋር ተያይዘው የሚመጡ ሙስናና የአድልዎ አሠራሮች መኖር አለመኖራቸውን መመርመርና ማረጋገጥ ሀገረስብከቱ ወደፊት በአሠራር የለውጥ ሂደቱ ውስጥ ሊመረምራቸው የሚገቡ ነጥቦች ናቸው፡፡ በሀሜት ደረጃ የሚነሡትን የጎጠኝነት፣ የጎሰኝነት እና የቤተሰባዊ አሠራሮች መኖር አለመኖራቸውን መመርመር እንዳይከሠቱም የሚያደርግ ግልጽነት ያለው አሠራር ተግባራዊ ማድረግ ይገባል፡፡

ሀገረ ስብከቱ አርአያ ሊሆን የሚገባው በውስጥ አስተዳደራዊ ሥርዓቱ ብቻ አይደለም በስብከተ ወንጌልና በሌሎችም መንፈሳዊ አገልግሎቶችም ጭምር መሆን አለበት፡፡ በርካታ ሰባክያነ ወንጌልን ማሠልጠን፣ ማፍራት ጊዜው የሚጠይቀውን የትምህርትና ሥልጠና ዘዴዎች ተግባራዊ ለማድረግ መንቀሳቀስ አለበት፡፡ በቂና ብቁ አገልጋይ ካህናትን ማፍራት አለበት፤ ወይም ያሉትን በዚያ ደረጃ ማድረስ ይገባዋል፡፡ በዚህም ላይ ተመሥርቶ ለሃይማኖት ቤተሰቦች ለእንግዶችና መጻተኞች ተፈላጊውን የምስጢራት አገልግሎት ሊሰጥ፣ አርኪ የስብከተ ወንጌል ዐውድማ ሊሆን ይገባል፡፡ ሌሎች አህጉረ ስብከቶችንም ተንቀሳቅሰው የሚያስተምሩ የሚመክሩ ሊቃውንትን ማፍራት አለበት፡፡ ዘመናዊ የሆኑ የመገናኛ ቴክኖሎጂዎችን በመጠቀም ስብከተ ወንጌልን ማስፋፋት ይጠበቅበታል፡፡ በቂ የሚዲያ አውታሮች ያስፈልጉታል፡፡ በርካታ የብቃት ማእከሎችን ሊገነባ ይፈለግበታል፡፡

ከላይ ከተጠቀሱ መንፈሳዊ አገልግሎቶች በተጓዳኝ የልማትና ማኅበራዊ አገልግሎቶችን በማስፋፋት ለሕዝበ ክርስቲያኑም ብቻ ሳይሆን ለሀገሪቱ ዘርፈ ብዙ አስተዋጽኦ ሲያደርግ መታየት አለበት፡፡ ቢያንስ ትምህርት ቤቶችንና የሕክምና ማእከላትን ከዚህ በፊት የነበሩ መልካም ጅምሮችን መነሻ አድርጎ በዓይነት፣ በቁጥርና በጥራት ማሳደግና ማስፋፋት ከዚህ ሀገረ ስብከት በእጅጉ ይጠበቃል፡፡  

ይህ ሁሉ እንዲሆን ግን ሀገረ ስብከቱ የሚሰጣቸውን አገልግሎቶችና የአሠራር ሥርዓቱን በመላና ግምት ሳይሆን በጥናት አስደግፎ በምክክርና አሳማኝ በሆኑ አካሔዶች እንዲመራ ይጠበቅበታል፡፡ ማኅበረ ካህናቱ እርስ በእርስ የሚኖራቸው ግንኙነት ከምእመናን ጋር የሚኖራቸው ትስስር በየጊዜው ሊያድግ ሊሻሻል ይገባል፡፡ ምእመናን በሰበካ ጉባኤያት ያላቸው ተሳትፎ እንዲያድግና ቤተክርስቲያናቸውን በቅርበት የሚያገለግሉበት በቤተክርስቲያናቸው አሠራር ውስጥ አስተያየት እንዲሰጡ እንዲወስኑም ሆነው ሊታቀፉ ይገባል፡፡ በሀገረ ስብከቱ የሚገኙ ገዳማትና አድባራት ከሚታሙበት የሙስናና አድሏዊ አሠራር መጽዳት አለባቸው፡፡ አገልጋይ ካህናቱ በትምህርተ ወንጌልና በተለያዩ ዘርፈ ብዙ ሙያዎች ሊታነጹ ይገባል፡፡ ሕግ የጸናበት ሥርዓት የሚከበርበት ሀገረስብከት መሆን አለበት፡፡

ሀገረ ስብከቱ የማሻሻያ እርምጃ ለመውሰድ አሁን የጀመራቸው ጥረቶች የሚበረታቱ ናቸው፡፡ ከላይ እንደጠቀስነው በጥናትና በጥንቃቄ ለመፈጸም ጥረት የሚደረግ ከሆነ ውጤት እንደሚኖረው ይታመናል፡፡ ለዚህም የሚመለከታቸው ሁሉ ማለትም የሀገረ ስብከቱ ሠራተኞች የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች፣ ማኅበረ ካህናቱ፣ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላትና ምእመናን፤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ቤተሰብ የሆኑ ሁሉ አገልግሎት ማግኛ የሆነው የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በሚፈለገው አርኪ የአገልግሎት ደረጃ ላይ እንዲደርስ የየድርሻቸውን ሊወጡ ይገባል፡፡ የማኅበረ ቅዱሳን አባላትም ሀገረስብከቱ የሚሻውን አስፈላጊ ድጋፍ ሁሉ ለማድረግ ያላቸውን ዝግጁነት ለመግለጽ ይወዳሉ፡፡

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር 

 

  • ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት 21ኛ ዓመት ቁጥር 2 ሰኔ 2005 ዓ.ም.

የቅዱስ ፓትርያርኩ መልእክት ቤተ ክርስቲያኒቱ በአንገብጋቢነት የምትሻውን ወቅታዊ ጥያቄ የሚመልስ አሳብ የያዘ ነው

 በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ

 
ከአራት ዓመት በፊት 2001 ዓ.ም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ቤተ ክርስቲያኒቱን ወደ ተሻለ የአገልግሎት ደረጃ ለማድረስ በመከረበት ጉባኤው ቤተ ክርስቲያኒቱ ያሉባትን ለአገልግሎቱ እንቅፋት የሆኑ ተገቢ ያልሆኑ ድርጊቶችን ለማስወገድ ያሳለፋቸው ውሳኔዎች፣ የተያዙ አቋሞች ነበሩ፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ በጊዜው በቤተ ክርስቲያኒቱ “የአስተዳደር ችግሮች፣ የሙስናና የቤተሰብ አስተዳደር” በቤተ ክርስቲያኒቱ የአገልግሎት መስመሮች ውስጥ ሁሉ መንሰራፋቱን አምኖ ያንን ለማጥራት፣ ዘመኑን የዋጀ በተጠና ዕቅድና አፈጻጸም የሚከናወን፣ ሓላፊነትና ተጠያቂነት የሰፈነበት ዘመናዊ የአስተዳደር ሥርዓት ለመዘርጋት ውሳኔ ማስተላለፉ የሚታወስ ነው፡፡ 

ይሁን እንጂ ወደ ተግባር ለመግባት የተደረገው እንቅስቃሴ ግን ወዲያውኑ ፈተና ገጥሞት ነበር፡፡ ውዥንብር ለመፍጠር፣ አለመግባባትን ለማስፈን የአባቶችን ስም በማጥፋት ለማሸማቀቅ በተለያዩ መንገዶች ጥረት የሚያደርጉ፣ በተናጠልና በቡድን የሚን ቀሳቀሱ የተለያዩ አካላት ስለነበሩ ርምጃው ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ በመሠረተ አሳቡ ግን የቤተ ክርስቲያኒቱን የአገልግሎት አካሄድ የማሳደግና የሚያስወቅሱ ነገሮችን የማስወገድ ብርቱ ፍላጎት እንደነበረው ቅዱስ ሲኖዶስ በአቋሙ አሳይቶ አልፏል፡፡

ይህ የነበረ የቅዱስ ሲኖዶስ ሐሳብ ዛሬ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ በግልጽ የተግባራቸው መጀመሪያ፣ የትኩረት አቅጣጫዎቻቸው ሁሉ ራስ እንደሆነ በቅርቡ ለበዓለ ትንሣኤ ባስተላለፉት ይፋዊ መልእክትና ለእንኳን አደረሰዎ በተዘጋጀው መርሐ ግብር ላይ  ባንጸባረቁት አቋም ከላይ አስቀድመን ያነሣናቸውን የቅዱስ ሲኖዶስ አቋሞች አስተጋብተዋል፡፡ ሃይማኖት በምግባር መገለጽ እንዳለበትና ከሃይማኖቱ አሳብ ጋር ስምሙ የሆነ አካሄድ እንዲኖረን የመከሩት ቅዱስነታቸው “ያረጀው ነገር ሁሉ በክርስቶስ ደም ተቀድሶና ነጽቶ ሐዲስ ሆኗል፡፡ አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሠርቶ የሚያሠራ የመልካም ነገር ሁሉ አርአያ መሪ እንደመሆኑ መጠን አዲሱን መንገድ ከፍቶ እንድንጓዝበት ሲያደርግ እኛም በአዲስ መንፈስ በአዲስ ሕይወት ልንመላለስበት እንጂ እንደገና ወደ አረጀውና ወደ አፈጀው ሕይወት ተመልሰን ልንዘፈቅ አይደለም” ብለዋል፡፡

መልእክታቸው የቤተ ክርስቲያን ልጆችና አገልጋዮች ሁሉ በየደረጃው ያሉ ፍጹም ክርስቲያናዊ ምግባር እንዲላበሱ ያላቸውን አባታዊ ፍላጎት አንጸባርቀዋል፡፡ ይህ የቅዱስነታቸው ምክር በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር አካላትም ዘንድ ሊተኮርበት የሚገባ ነው፡፡ ለመልካም ምግባር እንድንሰለፍ በሥራችንም ሁሉ እንድንበረታ ባስተላለፉት በዚሁ ምክራቸው መሠረት የትኞቹም አገልጋዮች መመላለስ ቢችሉ ቤተ ክርስቲያን አሉባት ከሚባሉ ችግሮች ሁሉ መላቀቅ የሚያስችላት አቅም ይሆናል፡፡

ቅዱስነታቸው በተለይም በዕለተ ማዕዶት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ የቤተ ክህነቱ ከፍተኛ የሥራ ሓላፊዎች፣ የአድባራትና ገዳማት አስተዳዳሪዎች በተገኙበት ባስተላለፉት መልእክት በዓሉ ከዲያብሎስ ቁራኛነት ከሞት አገዛዝ ከአሮጌው እርሾ የተላቀቅንበት መሆኑን ካወሱ በኋላ በዚያው አንጻር የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ከብልሹ አስተሳሰብ፣ ከብልሹ ምግባር ከሙስና፣ ከብልሹ አሠራር መጽዳት እንደሚገባቸው አሳስበዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ያላትን ቅድስና ጠብቃ እንድትኖር ልጆቿ በተለይም አርአያ ሊሆኑ የሚገባቸው ካህናት በጎ ካልሆኑና ቤተ ክርስቲያንን ከሚያስተቹ አስተሳሰብና ተግባር እንዲላቀቁ መክረዋል፡፡ ይህም ቀድሞም የነበረው የቅዱስ ሲኖዶስ ቀርጥ አሳብ ተግባራዊ ምላሽ ሊያገኝ የሚችልበት ዕድል እንዳለ ተስፋ ሰጪ ሆኗል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን የቅዱስነታቸው መልእክት ተገቢና ወቅታዊ መሆኑን የሚያምን ሲሆን ለቤተ ክርስቲያኒቱ አገልግሎት ዕድገት በቀና መንፈስ ለሚያስቡ የቅዱስነታቸው የአገልግሎት ጅማሬ ተስፋ ሰጪ እንደሆነ ያስባል፡፡ ይህ የቅዱስነታቸው አቋም በዚሁ ወቅት በሚካሄደው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ብርቱ ድጋፍ እንደሚያገኝና ጠንከር ያሉ መመሪያዎችን በየደረጃው ላሉ የቤተ ክህነቱ አገልጋዮች ያስተላልፋል ተብሎ ይታመናል፡፡

ከሁሉም በላይ ግን የቅዱስነታቸው መልእክትም ሆነ የቅዱስ ሲኖዶስ አቋም በየደረጃው ባሉ አካላት ተግባራዊ ምላሽ ይፈልጋሉ፡፡ እንደ ከዚህ ቀደሙ ተወስነው የማይተገበሩ ውሳኔዎች፣ ሊራመዱ የማይችሉ አቋሞች ሊሆኑ አይገባም፡፡ ለተግባራዊነቱ ደግሞ ከብፁዓን አባቶች ጀምሮ በርካታ የቤተ ክህነቱ አካላት ድጋፍ እንዳላቸው ቅዱስነታቸው አቋማቸውን በንግግራቸው ባንጸባረቁበት ወቅት በሰጡት ሞቅ ያለ የድጋፍ ምላሽ መረዳት ይቻላል፡፡ ከጥቂት ራስ ወዳዶች በስተቀር የቤተ ክርስቲያኒቱ አገልግሎት ማሻሻያን በብርቱ የማይፈልግ የለም፡፡ በአስቸኳይና በጥብቅ ይፈልገዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱ ገጽታ እንዲጎድፍ የሚሻ የለም፡፡ የጎደፈም ነገር ካለ በፍጥነት ማስተካከያ ለማድረግ መረባረብ ይገባል፡፡ የእርምጃው ቁልፍ ያለው ግን በቅዱስ ሲኖዶስ ጥብቅ አቋም ላይና በቅዱስ ፓትርያርኩ የአስተውሎት ርምጃ ውስጥ ነው፡፡

ለውጥን ምእመናንን በመላው፣ ማኅበረ ካህናቱ በየደረጃው፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶችና ማኅበራት፣ አድባራትና ገዳማቱ፣ ተማሪዎችና መምህራኑ፣ ደቀመዛሙርቱና መዘምራኑ ሁሉ በብርቱ ይፈልጋሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያን የዕረፍት ወደብ መሆን አለባት፡፡ እንደ ቅዱስነታቸው ንግግርም ለቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይሆን ለሀገርም አርአያ መሆን፣ ለዓለሙ ጨው መሆን አለባት፡፡ አሮጌው ነገር ሁሉ ማለፍ አለበት፤ አዲሱ መልካሙ ነገር ሁሉ ሊመጣ ይገባል፡፡ በዚያን ጊዜ ሁሉም አንድ ሆኖ ያስባል፡፡ መንፈሳዊው ሥራ ይሠለጥናል፤ የሥጋው ሥራ ወደ ቤቱ ይመለሳል፡፡

ዛሬ በየአህጉራቱ ያሉ የኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት በብርቱ ተነቃቅተው የዓለምን ብልሹ ነገር ሁሉ እየተዋጉ ነው፡፡ ጠንካራ አደረጃጀትና የአግልግሎት አድማስ ፈጥረው እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ፡፡ የታሪክ፣ የሞራል፣ የዕውቀት፣ የሥነ ምግባርም መሠረት ያላት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ይሔንን አቅም ፈጥሮ ለመንቀሳቀስ የሚያግዳት አንዳችም ነገር የለባትም፡፡ ዋናውና ወሳኙ ነገር የእግዚአብሔርን ቡራኬ ማስገኘት የሚችል በጎ ምግባር፣ ቀና ሐሳብ ቤተ ክህነቱ ይዞ የመገኘቱ ነገር ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ጥቂቱ ብዙ፣ ጥቁሩ ነጭ፣ ክፉው ሁሉ ለመልካም የማይሆንበት ምክንያት እንደማይኖር ማኅበረ ቅዱሳን የጸና አቋም አለው፡፡

በአጠቃላይ ቅዱስነታቸው ያመላከቱንን በጎ መንገድ መከተል ቤተክርስቲያን ያለ አማራጭ ይዛው ልትገኝ የሚገባት አካሄድ ነው፡፡ ለዚህ ጥሪ ምላሽ መስጠት ደግሞ የሁሉም የቤተ ክርስቲያን ቤተሰብ ሓላፊነት ነው፡፡ የማኅበረ ቅዱሳን አባላትም ለዚሁ ጥሪ በጎ ምላሽ ለመስጠት መዘጋጀታቸውን በዚሁ አጋጣሚ ለመግለጽ እንወዳለን፡፡

 

ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት 21ኛ ዓመት ቁጥር 1 ግንቦት 2005 ዓ.ም.

ወስብሐት ለእግዚአብሔር           

ብፁዓን ገባርያነ ሰላም

ጥር 3 ቀን 2005 ዓ.ም.


በፍጡርና በፈጣሪ፤ በፍጡርና በፍጡር መካከል ችግሮችና አለመግባባቶች መፈጠራቸው የዚህ ዓለም ባሕርያዊ ግብር ነው፡፡ በተለይም የሰው ልጅ አለመግባባቶችን ዕለታዊ ባሕርዩ ወደ ማድረግ የደረሰም ይመስላል፡፡ ቅዱሳት መጻሕፍትም የእነዚህን ችግሮች ክሡትነት መጠቆማቸውም የሚሰወር አይደለም፡፡

 

አስቀድመን እንደገለጽነው ሰው በሰብአዊነቱ ከራሱ ጋር፣ ከፈጣሪው ጋርና ከሌሎቹም ሥነ ፍጥረታት ጋር የሚያጋጩት ብዙ ምክንያቶች አሉ፡፡ ከዚህም የተነሣ “ለምን ግጭት ተከሠተ” ብሎ መሞገት ጊዜ መጨረስ ሲሆን “ለምን አልታረቅሁም” ብሎ ራስን መጠየቅ ግን አግባብ ነው፡፡ ምክንያቱም የዕርቀ ሰላም መንገዶች እንደ ግጭቱ መንገድ የተንዛዙ ሳይሆኑ የተቆጠሩና የተሰፈሩ የተለኩ ሃይማኖታዊ እሴቶች ናቸውና፡፡

እነዚህ የተለኩ እሴታዊ የዕርቀ ሰላም መንገዶች ከየትኛውም አቅጣጫ ሊጀምሩ ይችላሉ፡፡ ምንም እንኳን ይቅርታ መጠየቅ ከአዳም ቢጀመርም የዕርቁ ሂደት የተጀመረው ግን ከእግዚአብሔር ነው፡፡ በፈራጅነቱ የሚታወቀው እግዚአብሔር በቸርነቱ፣ በከሃሊነቱና በምሕረቱ ሰውን ሊታረቅ ፈቃዱ ሆኗልና፡፡

 

በዚህ መልኩ የሚመሩ የዕርቀ ሰላም ጉዞዎች ሁለት ነገር ያስፈልጋቸዋል እንላለን፡፡ የመጀመሪያው ሁሉንም ነገር ስለ እግዚአብሔር ብሎ ያለ አንዳች ቅድመ ሁኔታና ስሌት ወይም ድርድር ይቅር ማለት ነው፡፡ “ይቅር ለእግዚአብሔር” የሚለው ኀይለ ቃል ዐረፍተ ነገሩ እንደማጠሩ ሳይሆን ሃይማኖታዊ ውሳኔን የሚጠይቅ የታላላቅ ሰዎች መገለጫም ነው፡፡

 

እንደሰማይ ከዋክብት እንደ ምድር አሸዋዎች የበዙ የግጭት ምክንያቶችን ሁሉ ስለ እግዚአብሔር ወይም ስለ ማምነው ፈጣሪ ስል ትቼዋለሁ ብሎ ወደ ዕርቀ ሰላም ዐደባባይ መዝለቅ የመንፈሳውያን ሰዎች ቁርጠኛ ውሳኔ መሆኑን መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡

 

ሁለተኛው ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አንድነት፣ ለምንኖርባት ምድር በጎነት፣ ለምእመን ፍቅር ስንል “ይቅር ለእግዚአብሔር” ማለት በእጅጉ ይገባናል፡፡ ይህን ማድረግ በራሱ የቸር እረኛነት ማሳያ መነጽር ነው፡፡ ይህን ስንል በግጭትና በጭቅጭቅ ከሚገኝ ትርፍ ይልቅ በይቅርታና በሰላም የሚያጋጥም ኪሣራ/ ካለም/ የበለጠ ትርፋማ መሆኑን ስለምናምን የበለጠም መንፈሳዊ ፍሬ እንደሚገኝ ለሁላችንም ግልጽ ነው፡፡

 

እንደነዚህ ዓይነቶችን የዕርቀ ሰላም ማውረጃ መንፈሳዊ እሴቶች ወደ ጎን በመግፋታችን አንዲቷ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከተፈጥሮአዊ ባሕርይዋ ውጭ ተከፈለች መባሉ በራሱ አንገት አስደፊ መርዶ ነው፡፡

 

ከዚህ አኳያ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በብዙ ምክንያቶች ላለፉት ሁለት ዐሥርት ዓመታት በአንድነቷ፣ በአገልግሎቷ፣ በሥርዐቷና በቀኖናዋ ላይ ጥቂት የማይባሉ ችግሮቹ በዚሁ እንዲቀጥሉ ከፈቀድንላቸው አሁን ከምንገኝበት የበለጠና የከፋ ችግር ተሸክመው ሊመጡ እንደሚችሉ መገመቱን ቀላል ያደርገዋል፡፡

 

በተለይም ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን “ስደተኛ ሲኖዶስ” እና “የአገር ቤቱ ሲኖዶስ” በማለት የነገር ብልት ለሚያወጡ አፅራረ ቤተ ክርስቲያን ጀርባዋን ለግርፋት አመቻችታ እንድትሰጥ ማድረግ ነውና ዕርቀ ሰላሙን ማስቀደም የሁላችንም ተግባር ሊሆን ያስፈልጋል፡፡ እንዲህ መሆኑ ደግሞ በመንፈሳዊነትና በአሳታፊነት እናከናውነዋለን ለምንለው የፓትርያርክ ምርጫውም ሆነ ለተቋማዊ ለውጥ የተመቻቸና የተሻለ መንገድ እንደሚሆን እናምናለን፡፡

 

በይበልጥ ጉዳዩ የሚመለከታቸው ብፁዓን አበው የአንድነቱን ሁለንተናዊ ጥቅም በመመልከትና የዕርቀ ሰላሙ ድርድር ውጤት አልባነት ክትያዎች በምእመኑ መካከል የሚያስከትሉትን ጉዳቶች በማስተዋል ለዕርቀ ሰላሙ ቅድሚያ ሊሰጡ ይገባል፡፡

 

አንድ ቦታ ላይ አቁመን የትናንቱን የውዝግብ አጀንዳ እንዝጋው፡፡ መቃቃርና መገፋፋት በተጠናወተው መንፈስ ስለትናንት ጥፋት ብቻ መነጋገር አቁመን ስለ ነገም የቤተ ክርስቲያን ዕድገት እንምከር፡፡ ትናንት በታሪክ አጋጣሚ ብንቀያየምም ዛሬ ግን በዕርቀ ሰላም በአንድነት መጓዝ እንችላለን፡፡ ይህም ሊሆን የሚችለው ነገ ዛሬ ሳንል በጨዋነትና በግልጽ ተወያይተን፣ ችግሮቻችንን ለይተን ስለ ሰላም ይቅር ስንባባል ብቻ መሆኑን ከአባቶቻችን ይሰወራል ብለን አናምንም፡፡

 

ከይቅርታና ከይቅር ባይነት የበለጠ ነገር በቅዱሳት መጻሕፍትም ሆነ በቤተ ክርስቲያናችን ትውፊት ስለሌሉና ስለማይኖሩ ለዕርቀ ሰላሙ ድርድር ውጤታማነት ትኩረት ሰጥተው ቢሠሩበት እንላለን፡፡

 

ማኅበረ ካህናትና ማኅበረ ምእመናንም እስከአሁን እየተከናወነ ያለውን በጎ ተግባር በመደገፍ ለወደፊቱም ለቤተ ክርስቲያናችንና ለምእመናን አንድነትና ሰላም በጸሎት መበርታት ይገባናል፡፡ የተጀመረው የዕርቀ ሰላም ድርድር ከውጤት እንዲደርስ የድርሻቸውን እያበረከቱ የሚገኙ በሁለቱም በኩል ያሉትን ተደራዳሪ አባቶች፣ አደራዳሪ ሽማግሌዎችና የተለያዩ ግለሰቦችን በምንችለው ሁሉ ልንደግፋቸው ይገባል፡፡

 

በወንጌል እንደተጻፈው ሰላምን የሚያደርጉ ብፁዓን፣ ንዑዳን ናቸው መባሉ ሁላችንንም የሚመለከት የበጎ ተግባር ምስክርነት ስለሆነ ለዕርቀ ሰላሙ ድርድር ውጤታማነት የድርሻችንን ልንወጣ ያስፈልሪጋል እንላለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

  • ምንጭ፡- ጽምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 20ኛ ዓመት ቁ.8 2005 ዓ.ም.

አስቀድመህ ከወንድምህ ጋር ታረቅ /ማቴ. 5፥24/

ታኅሣሥ 10 ቀን 2005 ዓ.ም.

  • ለቤተ ክርስቲያናችን አገልግሎት ስኬት የአባቶቻችን ስምምነት ወሳኝ ነው

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በሥጋ ሕይወት በነበሩበት ባለፉት ዓመታት “ስደተኛ ሲኖዶስ” ተብሎ ከተጠራው በሰሜን አሜሪካ ከሚገኙ አባቶች ጋር ዕርቅ ለመፈጸም ጥረት ይደረግ እንደነበር ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ ተጨባጭ ለውጥ መመዝገብ ሳይችል በእንጥልጥል እንዳለ ቅዱስነታቸው ዐረፉ፡፡

 

የእርሳቸው ዕረፍት ቀጣዩ የቤተ ክርስቲያኒቱ ፓትርያርክ ከመመረጣቸው በፊት በሰሜን አሜሪካ ከሚገኙ ተለይተው ከሚኖሩ አባቶች ጋር ውይይት ለመጀመር አስገዳጅ ሁኔታ አምጥቷል፡፡ ይህ እንዲታሰብ ግድ የሚያደርገውም ቀጣዩ ፓትርያርክ የሚሰየሙበት መንገድ ሁሉን የማያስማማ ከሆነ የነበረውን ልዩነት የሚያሰፋ ውዝግብ በዚህች ታሪካዊ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሊያስከትል እንደሚችል ከወዲሁ መገመት ስለሚቻል ነው፡፡ ይህንን ከግምት አስገብቶ የወቅቱን አንገብጋቢነት ተረድቶ ወደ ዕርቅ የሚያደርስ ውይይት ማድረግ ደግሞ የቤተ ክርስቲያኒቱን ወሳኝ አገልግሎቶች በብቃትና በስፋት ለመስጠት፣ ጠንካራ መሠረትም ለመገንባት ስለሚያስችል ነው፡፡

 

በመሠረቱ ሲኖዶስ ከሐዋርያት ዘመን ጀምሮ በጉልህ የተገለጠ ተግባሩ መለያየቶችን መፍታት ዘመኑን የዋጀ የአገልግሎት አሰጣጥ ሥርዓት መትከል ነው፡፡ ስለዚህ ሲኖዶስ ሲታሰብ ሰላምና አንድነት ይታሰባሉ፡፡ ትሕትናና ፍቅር ይነግሣሉ፡፡ ይህ የሚሆንበት ዋናው ምክንያት ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰጠውን የሐዋርያዊ አገልግሎት አደራ መንጋውን የመጠበቅ ሓላፊነት ከመወጣት ሌላ ለሚሰበሰበው መንጋ አርአያነት ያለው ሕይወት አባቶቻችን እንዲኖራቸው፣ ብርሃናቸውም በዓለም እንዲያበራ ስለታዘዙም ነው፡፡

 

እነዚህ የክርስትና ዐበይት ተግባራት በአባቶቻችን ደግሞ ጎልተው እንዲገለጹ ይፈለጋል፡፡ አባቶች የክርስቶስን መልክ /እርሱን መምሰልን/ እንደያዙ በሚያስበው የእግዚአብሔር መንጋ፣ እንዲሁም የምድር ጨው ሆነን ሕይወታቸውን ለማጣፈጥ እንድንበቃ አደራ በተሰጡን የምድር አሕዛብ ሁሉ ላይ በጎ ተፅዕኖ ለማሳረፍ ብፁዓን አባቶች መልካሙን ጎዳና ሁሉ ሲከተሉ መገኘታቸው ታላቅ ሚና አለው፡፡

 

ከዚህ ጎዳና ወጥተን ፍቅርን በማጣት፣ በጠብ በክርክር ጸንተን ብንገኝ ፍቅር ከሆነ እግዚአብሔር ጋር ለመኖር ባለመፍቀዳችን ብቻ ሳይሆን ሌሎች ከእርሱ ጋር እንዳይኖሩ ማሰናከያ በመሆናችንም ጭምር ያዝናል፤ ይፈርዳል፡፡ ስለዚህ ለብፁዐን አባቶች ብቻ ሳይሆን በክርስቲያኖች ሕይወትም በፍቅር ጸንቶ መኖር፣ ከበደልንም በይቅርታና በዕርቅ ሕይወት ውስጥ ማለፍ ሃይማኖታዊ ግዴታ ነው፡፡ የዚህ ሕይወት መሠረቱ ከሞት ወደ ሕይወት የተሸጋገርንበት እግዚአብሔር ከእኛ ጋር ያደረገው ዕርቅ ነው፡፡ ጠላቶቹ ከሆነው ከእኛ ጋር እግዚአብሔር ታረቀ መባሉ የሕይወታችን መሠረት ፍቅር መሆኑን የሚያመለክት ነው፡፡ ስለ ዕርቅ ሕይወት በብዙ ምሳሌና በብዙ ኃይለ ቃል ራሱ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረንም በመሆኑ በጉልሕ በሕይወታችን መንጸባረቅ የሚገባው የጽድቅ ሥራ ነው፡፡

 

ለእግዚአብሔር ከምናቀርበው ከየትኛውም ዓይነት መባዕ አገልግሎታችን በፊት ከወንድሞቻችን መታረቅ እንደሚገባ ጌታችን አበክሮ ያስተማረው የሕይወት ቃል ነው፡፡ “አስቀድመህም ከወንድምህ ጋር ታረቅ” ያለው የጌታ ቃል ይልቁንም በቤተ መቅደሱ ዕለት ዕለት መሥዋዕት ለሚያቀርቡ፣ ብዙዎችን በጸጋ እግዚአብሔር ባዕለ ጸጋ ለሚያደርጉ፣ ምስጢራትንም ሁሉ ለሚፈጽሙ፣ የሃይማኖትና የሥነ ምግባር ምልክት ለሆኑ ከሁለቱም ወገን ላሉ ብፁዐን አባቶች የሚያስተምሩት ብቻ ሳይሆን ዘወትር እንዲኖሩት የሚጠበቅ ክርስቲያናዊ ሕይወት ነው፡፡

 

ይህ በመሆኑም በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባቶች መካከል “ክርክርና መለያየት አለ” መባሉ ሳይሆን ክርክሩን መፍታት፣ ልዩነትን ወደ አንድነት ስምምነት ማምጣት አለመቻል ከላይ የጠቀስነውን ወሳኝ የሕይወት ቃል የሚፈታተን ይሆናል ማለት ነው፡፡ ከዚያም አልፎ ቤተ ክርስቲያኒቱን ለመምራት ባለን አቅምና በጎ ፈቃድ ላይ ጥያቄ የሚያሥነሣ ይሆናል፡፡ በዚህ የማይደሰተው እግዚአብሔርም ብቻ አይደለም፡፡ ከሕፃን እስከ አዋቂ ያሉ የክርስቶስ ቤተሰቦችም ናቸው፡፡

 

ስለዚህ ቤተ ክርስቲያናችንን ወደ አንድነት የሚያመጣ ዕርቀ ሰላም መፈጸም ከሃይማኖታዊ ሥነ ምግባር አንጻር፣ ለቤተ ክርስቲያን ደኅንነት ከማሰብ አንጻር፣ መንጋውን ከማነጽና ሐዋርያዊ አገልግሎትን ከማቅናት አንጻር ለአባቶቻችን ግዴታ ይሆንባቸዋል፡፡ የሚፈለገው ዕርቀ ሰላም እውን እንዲሆንም ለእግዚአብሔር ፈቃድ፣ ለእውነት፣ ለኅሊና ምስክርነት መገዛት አግባብ ይሆናል፡፡

 

ከዚህ በፊትም ማኅበረ ቅዱሳን እንዳስገነዘበው አባቶች ሰላሙን ለማምጣት የሚያስችሉ ቀኖናዊ ጉዳዮችም ላይ ለመወሰን ለማጽናትም መንፈሳዊ ሥልጣንን የተጎናጸፉ በመሆናቸው ዕንቅፋትን ማራቅ ይችላሉ፡፡ የዕርቅ ሒደቱ ሲፈጸምም ሃይማኖታዊ መልክ ያጡ እና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሊቃውንትና ምእመናንን የማያሳምኑ ቅድመ ሁኔታዎችን ከመደርደር መታቀበ ከተቻለ በተስፋ የተሞላ ሒደት እንደሚሆን ይታመናል፡፡

 

ከማንምና ከምንም በላይ የቤተ ክርስቲያናችንን ቤተሰብ ማሳመን የማያስችሉ እርምጃዎች ውስጥ መግባት ተአማኒነትን ሊያሳጡ ይችላሉ፡፡ ለዓመታት የዘለቀውን መለያየት /ውዝግብ/ ለመፍታት በሚደረገው ጥረት ውስጥም የካህናቱ የሰንበት ትምህርት ቤቶች የአገልግሎት ማኅበራትና በአጠቃላይ የሕዝበ ክርስቲያኑ ሐሳብና አስተያየቶች ከግምት የሚገቡበት አካሔድ ሊኖር ይገባል፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑ ካልተሰማ በቀጣዩ ጊዜ በቤተ ክርስቲያናችን አስተዳደር አካላት ላይ የሚኖረው አመኔታ ይላላል፡፡ በመሆኑም በዚህ በዕርቁ ሒደት ክርስቲያኖች ያላቸው ሐሳብ ሊመረመር ይገባል፡፡ ስለዚህ ሁሉም የሃይማኖት ቤተሰብ ደስ የሚሰኝበት ምዕራፍ ላይ ለመድረስ መትጋት ከአባቶቻችን ይጠበቃል፡፡

 

ስለዚህም ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ለሰላሙ መስፈን አስፈላጊ የሆነ ዋጋ እንዲከፈል ግፊት በማድረግ ሊረባረቡ ይገባል፡፡ ምእመናንም ከካህናት አባቶች ጋር በጸሎት በመትጋት ለዚህ ችግር ዘላቂ መፍትሔ እግዚአብሔር እንዲሰጠን መማጸን ይገባናል፡፡ የተጀመሩትን ሒደቶች ሁሉ በእውነተኛነት በሚዛናዊነት እየተከታተሉ በጎ ተጽዕኖ ማሳደር ይገባናል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ያሳለፈችው ያለፉት ዓመታት ኣሳዘኝ ሁኔታዎች እንዳይቀጥሉ ዛሬ ላይ ማድረግ የሚገባንን ሁሉ ማድረግ እንደሚገባን ማኅበረ ቅዱሳን ያምናል፡፡ ለዚህም ይሠራል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

  • ምንጭ፡- ሐመር መጽሔት 20ኛ ዓመት ቁጥር 8 ታኅሣሥ 2005 ዓ.ም.

ገዳሞቻችንን ለሁሉ ዓቀፍ ልማት አናዘጋጃቸው፡፡

ታኅሣሥ 5 ቀን 2005 ዓ.ም.

 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የበርካታ ገዳማት ባለቤት ነች፡፡ በፈቃደ እግዚአብሔር ከ5ተኛው መቶ ክፍለ ዘመን ጀምሮ በመላው ሀገሪቱ እየተስፋፉና እያደጉ የመጡት እነዚሁ ገዳማት የምናኔና የጸሎት እንዲሁም ድኀነተ ሥጋ ወነፍስ የሚገኝባቸው ቦታዎች ናቸው፡፡ ለቤተ ክርስቲያናችን ዘርፈ ብዙ አገልግሎት ከመስጠት ጎን ለጎን የሊቃውንት መፍለቂያና የበርካታ ቅዱሳን ምንጭ በመሆንም ሲያገለግሉ እንደኖሩ ይታወቃል፡፡ በሀገሪቱ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኀበራዊ እንቅስቃሴዎች ውስጥ አዎንታዊ ተፅዕኖ ከመፍጠራቸውም በላይ የሀገሪቱ የትምህርትና የሥልጣኔ ማእከላት በመሆን አገልግለዋል፡፡

 

የብዝኀ ሕይወት መገኛና መጠበቂያ ማእከላት መሆናቸው በተጨባጭ የሚታይ ሲሆን ለሥጋም ለነፍስም ስንቅ የሆኑ ትምህርቶች መቅሰሚያ ሕያዋን ትምህርት ቤቶች ሆነው ይገኛሉ፡፡ ለኪነ ጥበብና ሥነ ጽሑፍ ዕድገት መሠረት ከመሆናቸውም በተጨማሪ ለኢትዮጵያ ሁለንተናዊ ብልጽግና በቱሪስት መስህብነትና በምጣኔ ሀብት ምንጭነት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያደረጉ እንደሚገኙ መላው ዓለም የሚያውቀው እውነታ ነው፡፡

 

ይህ በዚህ እንዳለ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማት በተለያዩ አዝማናት በሀገሪቱና በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ በደረሱ ውጪያዊና ውስጣዊ የጥፋት ዘመቻዎች ቀጥተኛ ተጠቂዎችም ነበሩ፡፡ ተፈጥሮአዊ በሆኑ ችግሮችም እንደየአካባቢው መልክአ ምድራዊ አቀማመጥ ተጋላጭ ሆነው ኖረዋል፡፡ አጽራረ ቤተ ክርስቲያንም በየጊዜው በተለያየ ስልት የገዳማውያኑን አኗኗር፣ ሥርዓትና ትውፊት ለመበረዝ ሲንቀሳቀሱና ገዳማቱን ሲዋጉ እንደኖሩ ግልጽ ነው፡፡

 

በእኛ ዘመንም ገዳማቱ በሀገሪቱ ሕዝብና መንግሥት የነበራቸውን መልካም ስምና ታሪክ ለማደብዘዝ እያበረከቱት ያለውን መንፈሳዊና ሀገራዊ አስተዋፅኦ ወደጎን በማለት በረቀቀ ስልት በኢትዮጵያ ገዳማት ላይ ዘርፈ ብዙ ዘመቻ እንደተከፈተባቸውም እንገነዘባለን፡፡ ከዘመቻውም በተጻራሪ የዘመኑን ችግር በዘመኑ ጥበብና ዕውቀት እየፈቱ እግዚአብሔር በሰጣቸው ጸጋ ሁሉ አገልግለው በክብር ያረፉ መንፈሳውያን አርበኞች ቁጥር ቀላል አልነበረም፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ከጥንት ጀምሮ ይልቁንም በወሳኝና አስቸጋሪ ወቅቶች እግዚአብሔር እያነሣሣ ሥራ የሠራባቸውንና የሚሠራባቸውን አባቶች፣ እናቶችና ተተኪ ልጆች ያጣችበት ጊዜ እንደሌለም በሚገባ እንረዳለን፡፡

 

በዘመነ ሉላዊነት ዓለማዊነት በገነነበት በዚህ እጅግ አስቸጋሪ ወቅት የገዳሞቻችን ተግዳሮቶችም የዚያኑ ያህል የረቀቁ፣ በቀላሉ ለመለየት የሚያስቸግሩና የተወሳሰቡ እንደሚሆኑ እሙን ነው፡፡ ከዚሁ አንጻር የመንፈሳዊ ሕይወት፣ የመልካም ሥነ ምግባራት፣ የልማት፣ የትምህርትና የዕድገት መሠረትነታቸውንና ማእከልነታቸውን ጠብቆ ለማስቀጠል፣ ብሎም ይህን ገዳማዊ እሴት አጥተው በስም ብቻ የሚጠሩትን ገዳሞቻችንን ስምና ግብራቸው የተጣጣመ እንዲሆን ለማድረግ የዚያኑ ያህል በአግባቡ የታሰበበት፣ የተደራጀ፣ በዕቅድ የሚመራ፣ ሁሉንም ባለድርሻ አካላት ያሳተፈ፣ በየደረጃው ያሉ ወገኖችን ተጠቃሚነት ያረጋገጠና ቀጣይነት ያለው ተግባር ለማከናወን ቆርጦ መነሣት ጊዜው የሚጠይቀው ሰማዕትነት እንደሆነ እናምናለን፡፡

 

ከዚህ አንጻር በገዳማት ዙሪያ ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ በተዋረድ ባሉ የቤተ ክርስቲያናችን መዋቅር ሥር ያሉ የቤተ ክርስቲያን አባቶችና ምእመናን በተደራጀ መንገድም ሆነ በተናጠል ያደረጉት፣ እያደረጉት ያለውና ለማድረግ ያቀዷቸው በርካታ ተግባራት የሚያስመሰግኑ ቢሆኑም ከችግሩ ስፋት፣ ግዝፈትና ጥልቀት አኳያ ሲታይ ደግሞ በቂ ሥራ ሠርተናል የሚያሰኝ አለመሆኑን መረዳት ያስፈልጋል፡፡

 

እናም ዕውቀታችንን፣ ሙያችንን፣ ጉልበታችንንና ገንዘባችንን ከምንም በላይ ደግሞ በጎ ፈቃዳችንንና ጊዜያችንን አቀናጅተን በዘመናት ርዝመት በገዳሞቻችን ላይ የሚታዩትን ተጨባጭ ችግሮች ለመቅረፍ ረጅምና አድካሚውን ጉዞ በጋራ መጀመር ይጠበቅብናል እንላለን፡፡ ይህን ስንል ደግሞ በአንድ ጊዜ የገዳማቱን ችግሮች ሁሉ ማስወገድ ይቻላል በማለት ሳይሆን፤ ቅድሚያ የሚሰጣቸውን እየመረጡ በተለይ ወሳኝ ችግሮች ላይ ስልታዊ በሆነ መንገድ እያነጣጠሩ ተራ በተራ መፍትሔ እንዲያገኙ ማድረግ ያስፈልጋል ማለታችን እንደሆነ መገንዘብ ይገባል፡፡ ገዳማቱም ከጸሎቱ፣ ከውስጥ አገልግሎቱና ከትህርምቱ (ከተጋደሎው) ጎን ለጎን ዘመኑን እየዋጁ ምእመናንን ከኋላቸው አሰልፈው የበረከተ ሥጋ ወነፍስ ተቋዳሽ ለማድረግ የፊት አውራሪነቱን ድርሻ መወጣት ይጠበቅባቸዋል፡፡

 

በዚህ ረገድ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታላላቅ ገዳማት አንዱ የሆነው ታላቁና ታሪካዊው የደብረ ሊባኖስ ገዳም ለቤተ ክርስቲያን፣ ለሀገርና ለወገን ጠቃሚ የሆኑና የገዳሙን መንፈሳዊ እሴት የሚያስጠብቁ ሰፋፊ ፕሮጀክቶችን አስቀርፆ ለተግባራዊነቱ እየተንቀሳቀሰ መሆኑ በእጅጉ የሚያስደስት ጅምር ሥራ ነው፡፡ ይህም ድርጊት ገዳሙን በአርአያነት የሚያስጠቅሰው ከመሆኑም በላይ በአረንጓዴ ልማትና በብዝኃ ሕይወት ጥበቃም (ሀገሪቱ ከምታራምደው ፖሊሲ ጋር የተዛመደ ሆኖ ቦታውን በዚህ ዘርፍ) ከሀገሪቱ ተመራጭ ቦታዎች አንዱ እንደሚያደርገው ጽኑ እምነታችን ነው፡፡

 

ከማኅበረ ቅዱሳን ጋር በመተባበር ኅዳር 9 ቀን 2005 ዓ.ም በተዘጋጀው የምክክር መርሐ ግብር ላይ ገዳሙ ይፋ ያደረጋቸው ሰፋፊ ፕሮጀክቶች የገዳሙን ዘርፈ ብዙ ችግሮች ከመፍታት አንጻር ታላቅ ተስፋ ተጥሎባቸዋል፡፡ በየገዳማቱና በየአብነት ትምህርት ቤቶቹ የተጀመሩ የመታደግና የማልማት ፕሮጀክቶች እየቀጠሉ እንዲህ ያለውን መጠነ ሰፊ ፕሮጀክት ከማስፈጸም አንጻር ከገዳሙ ጋር አብሮ መሰለፍ ጊዜ ሊሰጠው የማይገባ ሥራ ነው እንላለን፡፡ በቀጣይም በየአህጉረ ስብከቱ ለሌሎች ገዳማትና አድባራት ምሳሌ የሚሆኑ ቢያንስ አንዳንድ ገዳማትን በቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓትና ደንብ መሠረት ማደራጀት፣ ማልማትና በሁለንተናዊ ዘርፍ ማብቃት ይዋል ይደር የማይባል ጉዳይ እንደሆነም እናምናለን፡፡

 

በጻድቁ አባታችን አቡነ ተክለሃይማኖት ገዳም የኖሩትንና አሁንም ያሉትን ችግሮች በቅደም ተከተል ለመፍታትና ገዳሙን ለመታደግ በመንፈሳውያን አባቶቻችንና በቤተ ክርስቲያኒቱ ባለሙያ ልጆች «ብዝኃ ሕይወትና ሁሉን ዐቀፍ መሪ ዕቅድ» በሚል ስያሜ መጠነ ሰፊ ፕሮጀክት መዘጋጀቱ ተገቢ ነው፡፡ በዚህ መሪ ዕቅድ የገዳሙን ብዝኃ ሕይወት ባሕላዊ አጠባበቅ ማጥናት፣ መጠበቅና ለቱሪዝም ያለውን ዋጋ ማስተዋወቅ፣ ለገዳሙ ማኅበረሰብ አማራጭ የኀይል አጠቃቀም አሳብ ማቅረብ፣ የተደራጀና የተቀናጀ የገዳም አስተዳደርን ማጠናከር፣ ገዳሙን ለምናኔ ሕይወት አመቺና ተመራጭ የሚያደርጉና የመሳሰሉት ተግባራት ተካተውበት የቀረበ መሆኑ መልካም ነው፡፡ ይህ መሪ ዕቅድ ወደ ተግባር ሲተረጎም የሚያስጠብቀው የገዳሙን ጥቅም ብቻ ሳይሆን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንና የመላው ሀገሪቱን ብሎም የአህጉሪቱንና የዓለምን ጥቅም ጭምር መሆኑን በቅድሚያ መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ መሪ ዕቅዱ በሥራ ተተርጉሞ የታሰበውን ሁሉ ዐቀፍ ጠቀሜታ ያስገኝ ዘንድም የሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያኒቱ፣ የመንግሥትና መንግሥታዊ ያልሆኑ አካላት እንዲሁም መላው የቤተ ክርስቲያን ልጆች ሁሉ ቀርቦ በማየትና በመረዳት የድርሻችንን ለመወጣት በቁርጠኝነት ልንነሣ ያስፈልጋል፡፡

 

ማኅበረ ቅዱሳንም እንደ ቤተ ክርስቲያን አካልነቱ በቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አማካኝነት ባለፉት 10 ዓመታት ባካሄዳቸው ጥናቶች መሠረት የተለያዩ ፕሮጀክቶችን ቀርፆ በ105 ገዳማት እንደየችግሮቻቸው ዓይነትና መጠን እያየ ለአብነት ትምህርት ቤች የመማሪያና የመኖሪያ ግንባታ፣ የንጹሕ መጠጥ ውኃ አቅርቦት፣ የዕደ ጥበብ ማእከላት ግንባታና ሥልጠና እንዲሁም የወፍጮ አገልግሎት እንዲያገኙ አድርጓል፡፡ በእርሻ ፕሮጀክት ዘርፍም የንብ ማነብ፣ የወተት ከብት እርባታ፣ የከብት ማድለብ፣ የዶሮ ዕርባታና የመስኖ አገልግሎትን በሳይንሳዊና ዘመናዊ መንገድ እንዲጠቀሙና ምርታማነትን በማሳደግ ራሳቸውን ችለው ለሌሎችም እንዲተርፉ ለማድረግ የበኩሉን ሲወጣ ቆይቷል፡፡ ለተለያዩ ገዳማትና የአብነት ትምህርት ቤቶች ስምንት ፕሮጀክቶች በአሁኑ ወቅት በመተግበር ላይ ሲሆኑ ጥናታቸው ያለቀላቸው ዘጠኝ ፕሮጀክቶችን ደግሞ የበጎ አድራጊ ማኅበራትንና ምእመናንን ድጋፍ በመጠባበቅ ላይ ይገኛሉ፡፡ ማኅበራችን እየተገበራቸው ያሉትንና የሚተገብራቸውን ቀጣይ ሥራዎች ሳያጓድል በሙያ አገልግሎትና አቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል በኩል ከገዳሙ አስተዳደር ጋር ያጠናውን ይህን ሰፊ ሥራ ለመጀመርና ከዳር ለማድረስ የልጅነቱን ድርሻ የሚወጣ መሆኑን በዚህ አጋጣሚ ይገልጻል፡፡

 

ስለዚህ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ገዳማት ሰው ሠራሽና ተፈጥሮአዊ ችግሮች በሂደት እየተቀረፉ የልማት፣ የትምህርት፣ የመንፈሳዊ ሕይወት፣ የምናኔና የመልካም ሥነ ምግባራት ማእከልነታቸው እንዲጠበቅ ከማድረግ አኳያ ከልሂቅ እስከ ደቂቅ ሁላችንም በመንፈሳዊ ቅንዓት መረባረብ አለብን፡፡ ይህን ማድረግ የምንችል ከሆነ የጸሎት፣ የዕውቀትና የበረከት ምንጭ ከሆኑት ገዳሞቻችን ሀገሪቱም ሆነች ሕዝቦቿ ተጠቃሚዎች እንሆናለን፡፡ የኢትዮጵያን ቀደምት ታሪክ በማስተዋወቅ የጽሑፍና ታሪካዊ፤ የሚዳሰሱና የማይዳሰሱ ቅርሶች ተጠብቀው እንዲቆዩ ከማድረግ አንጻርም የሚያበረክቱትን አስተዋጽኦ ዘላቂና አስተማማኝ ማድረግ እንችላለን፡፡ በቱሪዝም ኢንዱስትሪው ከሚያስገኙት የማይነጥፍ ገቢ ጎን ለጎን በእርሻና በዕደ ጥበብ ምርታቸው የሀገሪቱን አጠቃላይ ዕድገት ደግፈው በምግብ ራስን የመቻል መርሐ ግብር ዕውን ከማድረግ አንጻር የበኩላቸውን ድርሻ እንዲወጡ እናግዛቸዋለን፡፡ ገዳማቱ ጧሪ ቀባሪ ለሌላቸው ወገኖቻችንና ለዕጓለማውታ ሕፃናት የሚሰጡትን አገልግሎት ለማቀላጠፍና ቅዱሳን አባቶቻችን የደነገጉት /የሠሩት/ ሥርዐተ ገዳም በሚመለከታቸው ሁሉ በአግባቡ እንዲፈጸም ለማስቻል ሁለንተናዊ አቅማቸውን በተቀረፁና በሚቀረፁ ፕሮጀክቶች አማካኝነት እንዲያሳድጉ መደገፍ ከሁላችንም የሚጠበቅ መንፈሳዊ ግዴታ ነው እንላለን፡፡

 

  • ምንጭ፡- ጽምዐ ጽድቅ 20ኛ ዓመት ቁጥር 6 ከታኅሣሥ 1-15 ቀን 2005 ዓ.ም.