ጾመ ዮዲት

ዲያቆን ዮሴፍ በቀለ

በናቡከደነጾር ዘመነ መንግሥት ንጉሡ ሥልጣኑን መከታ በማድረግ የእግዚአብሔርን ሕዝብ በግድ እያስገደደ እጅ መንሻ ይቀበል ነበር፡፡ የመንግሥቱን ትእዛዝ ያልተቀበለውንም እየገደለ፣  ጭፍሮቹ ኃያልነቱንና ገናናነቱን በዓዋጅ በጦር አዛዦች ጭምር እያሳወጀ፣ በርካታ የጦር ሠራዊቶችን አሰልፎ ከአይሁድ ከተማ ገባ፡፡ በዚያም ነዋሪዎችን በማስፈራራት የመንግሥቱን ትእዛዝ ያልተቀበሉትን ሁሉ እያሳደደ ስላስጨነቃቸው ማቅ ለብሰው፣ አመድ ነስንሰውና ድንጋይ ተንተርሰው ወደ ፈጣሪያቸው በመጮህ መለመን ጀመሩ። በጭካኔ የተሞላው የጦር አበጋዙ ሆሎፎርኒስም ይበልጥ እጅግ እንዲሰቃዩ ውኃ የሚቀዱበትን ስፍራ ተቆጣጠረው፤ በግዴታ ማርኮም እጅ እንዲሰጡ እንዳደረጋቸው በመጽሐፈ ዮዲት ፪፥፪ ላይ ተጽፏል፡፡ በአካባቢው ይኖር የነበረ ዖዝያን የተባለ አንድ ሰው የአባቶቻቸው አምላክ ጸሎታቸውን እንዲሰማቸው ለአምስት ቀናት በትዕግሥት ይጾሙና ይጸልዩ ዘንድ ሕዝቡን መከራቸው፤ እነርሱም በትዕግሥት ሊጠብቁ ተስማሙ፡፡

የእስራኤል ልጆች የናቡከደነጾርን ጦር ብንችል ተዋግተን እንረታለን፤ ካልሆነም እጅ እንሰጣለን በማለት ይመካከሩ ጀመር። በዚያን ጊዜ ባሏ የሞተባትና በንጽሕና ተጠብቃ፣ በጸሎትና በሕገ እግዚአብሔር የምትኖር ዮዲት የተባለች ሴት ነበረች። (ዮዲት ፯፥፲) እግዚአብሔርን የምትፈራ ብቸኛዋ ሴት እርሷ ነበረችና ምክክራቸውን ስትሰማ ለምን «እግዚአብሔር ያድነናል አትሉም» ብላ ገሠጸቻቸው፡፡ ማቅ በመልበስ፣ አመድ በመነስነስና ድንጋይ በመንተራስም ሱባኤ ገባች። በሦስተኛው ቀንም እግዚአብሔር አምላክ ሕዝቧን የምታድንበትን ጥበብ ገለጸላት፤ ዮዲትም እግዚአብሔር የሰጣትን ውበት ተጠቅማ ሕዝቧን ከጥፋት የምትታደግበትን ጥበብ ተረዳች።

የክት ልብሷን ለብሳ፣ ሽቱ ተቀብታና ተውባ የጠላት ሠራዊት ወዳሉበት የጦር ሰፈር በድፍረት አመራች፡፡ ሠራዊቱም ውበቷን አይተው እጅግ በመደነቅ «ይህችስ ለአለቃችን ትገባለች» ተባብለው ከጦር መሪያቸው ዘንድ ወሰዷት። እርሷም ቀድማ ማምለጫ መንገድ አዘጋጅታ ነበርና ወደ አዛዡ ከገባች በኋላ «ክቡር ጌታዬ ሆይ ርስት ተወስዶብኛል፤ እንድትመልስልኝ አስቀድሜ ደጅ ልጠና መጥቻለውና ርዳኝ፤ ትብብርህ አይለየኝ» አለችው፡፡ በስሜት ፈረስ ታውሮ የነበረው የሠራዊቶቹ አዛዥም የጠየቀችውን እንደሚፈጽምላት ቃል ገባላት። ባማረ ድንካን እንዲያስቀምጧት ሎሌዎቹን አዘዘ። ዮዲትም የተሰጣትን ጥበብ ተጠቅማ፣ መውጣት ስትፈልግ የምትወጣበትን እና የምትገባበትን ዕድል በእግዚአብሔር አጋዥነት ዐወቀች፡፡ ከቀናት በኃላ የጦር አበጋዙ ለሠራዊቱ የምሳ ግብዣ አዘጋጅቶ ዮዲትን ከጎኑ አስቀመጣት፤ ከበሉና ከጠጡ በኋላም ሁሉን ሰው አስወጣ፤ እልፍኙን በመዝጋት ከእርሷ ጋር ብቻውን ሆነ፤ ነገር ግን እንቅልፍ ጣለው፡፡ (ዮዲት ፰፥፪) እርሷም ወደ አምላኳ ጸለየች፤ ፈጣሪዋ እንዲረዳትም አጥብቃ ለመነች። በኋላም ከራስጌው ሰይፍ አንስታ አንገቱን ቀላችው፤ በድኑንም ከመሬት ጣለችው። የሆሎፎርኒስን ሞት ሠራዊቱ ሲሰሙ አውራ እንደሌለው ንብ ተበተኑ፤ ከፊሎቹ ሞቱ። እስራኤላውያንም ከሞት ተርፈው በእግዚአብሔር ኃይል ድል አደረጉ፤ በደስታም ፈጣሪያቸውን አመሰገኑ።

ይህ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ታሪክ የሚያስረዳን ዮዲት ጠላቶቿን ድል ያደረገችው በጾምና በጸሎት እንደሆነ ነው፡፡ ለእኛም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች ምንም እንኳ ወርኃ ጳጉሜን የፈቃድ ጾም ቢሆንም በሀገራችን የተጋረጠውን ችግር እናልፍ ዘንድ በፈቃደኝነት እንጾማለን። እግዚአብሔር አምላካችን ለሁላችንም ጥበብ ሰጥቶናል። ይህም ችግሮችን ሁሉ የምንፈታበት መንገድ ነው። በዚህም የዓመተ መሸጋገሪያና የክረምቱ ወር ማብቂያ በመሆኑ ዕለተ ምጽአት ስለሚታሰብበት በየዓመቱ በጳጉሜ ወር ከሌሊት ጀምሮ በቤተ ክርስቲያን ተገኝተን ጠበል በመጠመቅ፣ በማስቀደስና በመጸለይ እንዲሁም ሥጋ ወደሙን በመቀበል ልናሳልፍ ይገባል። ዕለተ ምጽአትም ከዚህ ዓለም ወደ ወዲያኛው ዓለም መሸጋገሪያችን ነውና በቀኙ እንቆም ዘንድ እንጾማለን፡፡ የሚመጣውን አዲስ ዘመንም በንጽሕና ለመቀበል ስላለፈው ዓመት ኃጢአታችን ንስሓ የምንገባበት ጾምም ነው።   

ከተጋረጠብን ችግር «እግዚአብሔር ያድነናል» በማለት ልክ እንደ ዮዲት ሱባኤ ገብተን፣ ማቅ ለብሰን፣ አመድ ነስንሰንና ድንጋይ ተንተርሰን አብዝተን ልንጾምና ልንጸልይ ይገባል፡፡ ሊለያየን፣ ሊነጣጥለን፣ ሊበታትነን እና ሊገድለን ካሰበው እንዲሁም ፍቅርን፣ መተሳሰብንና አንድነትን ሊነፍገን ከቃጣው ጠላትና ሃይማኖታችንን ሊያስተወን ከሚመጣ ፀረ ሃይማኖት እንድናለን። ስለዚህ ከፊታችን ያለችውን ስድስቱን የጳጉሜን ቀን በፍቅር፣ በአንድነትና በሃይማኖት ጸንተን፣ ጾመን፣ ጸልየን ለዘመነ ዮሐንስ እንድንደርስ እግዚአብሔር አምላካችን ይርዳን፤ አሜን።

ስብሐት ለእግዚአብሔር

በአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን (ጸሎተ ሃይማኖት)

ቤተ ክርስቲያን ሰማያዊት ንጽሕትና ቅድስት የክርስቶስ ማደሪያ ናት፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ «በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቋት ዘንድ እናንተን ጰጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለራሳችሁ እና ለመንጋው ሁሉ ተጠንቀቁ» በማለት ያስጠነቅቃል፡፡ በሰው ልጅ ፈቃድና ሐሳብ ያልተሠራች እግዚአብሔር በደሙ የዋጃት ቅድስት ሥፍራ ናት፡፡ ቤተ ክርስቲያን በሰማይና በምድር ያለች፣ ከሰው ልጅ ዕውቀት ፈቃድና ፍላጎት በላይ የሆነች የእግዚአብሔር ማደሪያ ናት፡፡ እግዚአብሔር የመሠረታት፣ የቀደሳትና የዋጃት፣ ሐዋርያት፣ ነቢያትና ቅዱሳን አበው የሰበኳትና ያጸኗት ቤት ናት፤ ለሰውም በረከተ ሥጋንና በረከተ ነፍስን ታድላለች፡፡

በዘመናችን የቤተክርስቲያን ፈተናዎች

የተከበራችሁ አንባብያን ባለፉት ሠላሳ ዓመታት በቤተክርስቲያንና በክርስቲያኖች ላይ እየደረሰ ያለውን መከራ በተለይም ደግሞ ባለፉት ሁለት ዓመታት የተፈጸመውን ግፍ የሚገልጽ ተከታታይ ጹሑፍ በማቅረብ ላይ መሆናችን ይታወቃል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ይዞታ ነጠቃ፤ የአብያተ ክርስቲያናት ቃጠሎና የምእመናን ግድያ  ዋናዎቹ የግፍ ተግባራት ናቸው፤ ከባለፈው የቀጠለውንና የመጨረሻውን እንደሚከተለው እናቀርባለን፡፡ መልካም ንባብ

በማርክሲዝም ሌሊዝንም አስተምሮ የተበረዘ ሰው ሁል ጊዜ ባላንጣና ጠላት በመፈለግ ጠላቱን ካላጠፋ መኖር እንደማችል ሲሰብክ የሚኖር መሆኑን በሙያው ምርምር ያደረጉ አካላት ይናገራሉ፡፡ ይህ አስተሳሰብ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ወደ ሃይማኖትም እየተጋባ መጥቷል፡፡ ከሃይማኖት ሰዎች የሚጠበቀው እናመልከዋለን የሚሉትን አምላክ በቃልም በምግባርም መግለጥ ነው፡፡ ሌላውን እያጠፉና  አማራጭ እያሳጡ እምነትን ማስፋፋት አይቻልም፡፡ ሌላውን አጥፍተው መኖር የሚፈልጉት የሚያደርጉት ምድራውያን ገዥዎች ናቸው፡፡ ስለሃይማኖት የሚያስተምሩ አካላት ከዚህ ዓለም የተለየ ዘለዓለማዊ ርስት እንዳለ የሚያምኑ በመሆናቸው ዘለዓለማዊ ርስት ማውረስ የሚችለውን አምላክ የሚያስደስቱበትን ተግባር ይፈጽማሉ፡፡ ሰው በመግደልና ተቀናቃኝን በማጥፋት ተደስቶ የሚኖር የሚመሰለው ምድራዊ የሥጋ ፍላጎት ያለው ምድራዊ ገዥ እንጂ ዘለዓለማዊ መንግሥትን የሚሻ መንፈሳዊ ሰው አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ወደ አሕዛብ የምትገባው ወንጌልን ይዛ እንጂ እንደ ቀኝ ገዥዎች በአንድ እጅ ወንጌል በሌላ የጦር መሣሪያ ይዛ አይደለም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ይህን የምታደርገው ባለቤቱ በወንጌል እንዲያምኑ ያደረገው በፍቅር እንጅ በግዳጅ ባለመሆኑ ነው፡፡እንዲህ ያለው እኩይ ተግባር የቤተ ክርስቲያን አለመሆኑን መረዳት የሚገባውም ቤተ ክርስቲያን በሞት እንጂ በመግደል ጸንታ ስለማታውቅ ነው፡፡

ቤተክርስቲያን የገጠማት ፈተና ያላሳሰባቸው አካላት የሰጡት መግለጫ መንግሥትን በሚከተለው መንገድ  አሳስቧል፡፡ ሀገርና ሕዝብን ለመምራት የተቀመጠው መንግሥት  በየአካባቢው  እየደረሰ ባለው  የአብያተ ክርስቲያናት ቃጠሎ፣ የኦርቶዶክሳውያንን መፈናቀል ፣ድብደባ ከዚያም ሲያልፍ አሰቃቂ ግድያ ላይ ያሳየው ቸልተኝነት የበርካታ ሚሊዮን አባሎቻችንን ልብ በእጅጉ የሰበረ ወደፊትም ቢሆን ለደኅንነታችን መጠበቅ ምንም አይነት ዋስትና እንደሌለን እንዲሰማን ያደረገ በመሆኑ የመንግሥትን ለዘብተኝነት በእጅጉ  እንቃወማለን ›› ይላል፡፡ አንድ መንግሥት ለዜጎቹ ዋስትና  ሲሰጥ ዜጎቹን በመንግስት እምነት  ማሳደር ብቻ  ሳይሆን  ለመንግሥትም  ጠበቃ ይሆናሉ፡፡ ምርጫ ቢደረግ ይመርጡታል፤ ቢናገር ይሰሙታል፡፡ ቢያዝዝ ይፈጽሙለታል፤ እንኳንም ተናግሮ ሳይናገርም ማድረግ የሚገባቸውን ይሠራሉ ፡፡ ክርስቲያኖች በዚህ ምድር ላይ ሲኖሩ በጌታ ለገዥዎቻችሁ ታዘዙ ›› የሚለውን  አምላዊ ቃል ሲፈጽሙ ኖረዋል፡፡ ወደ ፊትም ይፈጽሙታል፤ ይህ ማለት ግን በክርስቲያኖች ላይ በደል ሲፈጽም መንግሥትን አያሳስቡም ማለት አይደለም፡፡ ለገዥዎቻችን መታዘዝ እንዳለብን የሐዋርያውን ቃል አምነን እንሠራለን፡፡ አድሎአዊ ተግባር  ሲፈጸም ስናይ ደግሞ እንናገራለን፡፡ ነህምያ የኢየሩሳሌም መፍረስ ሲያሳስበው ስለኖረ ኃዘንና ትከዜው በፊቱ ላይ መነበብ በጀመረ ጊዜ የማረከው ንጉሥ ምን እንዳሳዘነው ጠየቀው ፡፡ ነህምያም ከዚህ በላይ መከራ አለመኖሩን በመረዳት አባቶቼ የሠሯት ኢየሩሳሌም ፈርሳ እንዴት ደስተኛ እሆናለሁ በማለት መለሰለት፡፡ በነህምያ መልስ ቅንነቱን ሲመለከት የኖረው ንጉሥ የሚያመልከው አምላክ የሚመለክበትን ቤተ መቅደስና ሙሉ ከተማዋን እንዲያንዱ ፈቃድ ሰጥቶ ሰደደው፡፡ በእኛ ዘመንም መፈጸም ያለበት እንዲህ ነው፡፡ አንተ ከፈርኦን አታንስ እኛም ከሙሴ አንበልጥ የሚለውን ንግግር ማሰብ ይገባል፡፡

 ሀገራችን ክርስቲያኖችን እያጠፉ የሚደሰቱበት ክርስቲያኖች ደግሞ በኃዘን የሚኖሩባት መሆን የለባትም፡፡ ሁላችንም እኩል ደስታውንም ኃዘኑንም የምንካፍልባት መሆን ይኖርባታል፡፡በሃይማኖት ሰበብ የተቀሰቀሰ ግጭት ቶሎ ስለማይበርድ መፍትሔ መፈለግ ተገቢ ነው እንላለን፡፡

 በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ  ቤተክርስቲያን ሠለስቱ ምእት የመቶ ሃያ ማኅበራት ኅብረት ደግሞ ‹‹ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በጅማ፣ በኢሉባቡር፣በከሚሴ፣በድሬድዋ፣በምሥራቅና በምዕራብ ሐረርጌ፣በፍቼ፣ሶማሌ (ጅጅጋ) ፣በባሌ፣ በአሩሲና በሌሎችም የሀገሪቱ ክፍሎች አብያተ ክርስቲያናት እየተቃጠሉ፤ ክርስቲያኖች እየተገደሉ፤ እየተሰደዱና ተገደው ሃይማኖታቸውን እንዲቀይሩ እየተደረገ፤  ንብረታቸው እየተቀማና እየተቃጠለ የአብያተ ክርስቲያናት ይዞታዎች ጥምቀተ ባሕርን ጨምሮ እየተቀሙ እንደሆነ በተለያዩ ሚድያዎች የሰማነውና በአካልም በቦታው ተገኝተን ያየነው እውነታ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ለሀገር ባለውለታ መሆኗ ተረስቶ ቤተክርስቲያንና አማኞቿን የማይመጥን ስም እየተሰጣት እንዲህ ያሉ ጥቃቶች መንግሥት ባለበት ሀገር እየተፈጸሙ፤ ሰዎች በነፃነት የፈለጉትን የማምለክና በሰላም ወጥቶ የመግባት ሕገ መንግሥታዊ መብታቸውን ተነፍገው በስጋትና በመከራ ውስጥ በመሆናቸው የተሰማንን ጥልቅ ኃዘን እንገልጣለን›› ብለዋል፡፡ ሀገሪቱ የምትታወቅባቸው የመስህብ ቦታዎች የቤተክርስቲያኗ መሆናቸው ይታወቃል፡፡ ቤተክርስቲያንን አጥፍተን ሌላ እንመሥርት ካልተባለ በስተቀር እንዲህ አይነት ተግባር በየትም ተደርጎ አያውቅም፡፡እንዲህ አይነት ዘመኑን የማይመጥን  ጥፋትና አድሎአዊ አሠራር መቆም ይኖርበታል፡፡ሥልጣን ላይ ስንቀመጥ መልካም ብንሠራ እኛ ዘለዓለማዊ አይደለንምና ስንወርድ ደግሞ ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም እንኖራለን፡፡ ሰዎች በመውረዳችን ያዝናሉ መልካም ተግባራችንን ሲዘክሩ ይኖራሉ እንጂ እንኳን ወረዱ አይሉንም፡፡ስለዚህ አጥፊዎች ከእኩይ ድርጊታቸው እንዲታቀቡ ማድረግ አጥፊዎች እንወክለዋለን የሚሉትንም ሆነ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያኖችን፤ አባቶችን አቅርቦ ማወያየትና ችግሩን በመለየት የማያዳግም እርምት መስጠት ይገባል፡፡

      ይቆየን

 ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ፳፮ ዓመት ቁጥር ፲፯

 

በዘመናችን የቤተክርስቲያን ፈተናዎች

የተከበራችሁ አንባብያን ባለፉት ሠላሳ ዓመታት በቤተክርስቲያንና በክርስቲያኖች ላይ እየደረሰ ያለውን መከራ በተለይም ደግሞ ባለፉት ሁለት ዓመታት የተፈጸመውን ግፍ የሚገልጽ ተከታታይ ጹሑፍ በማቅረብ ላይ መሆናችን ይታወቃል፡፡ የቤተክርስቲያን ይዞታ ነጠቃ፤ የአብያተ ክርስቲያናት ቃጠሎና የምእመናን ግድያ ዋናዎቹ የግፍ ተግባራት ናቸው፤ ከባለፈው የቀጠለውን እንደሚከተለው እናቀርባለን፡፡ መልካም ንባብ!

ክርስቲያኖች መከራ ቢገጥማቸውም ፈርተው ከእምነታቸው እንደማያፈገፍጉ፣ ከራሳቸው ሕይወት ይልቅ ለታቦታቱና ለንዋያተ ቅድሳቱ ቅድሚያ እንደሚሰጡ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ያነበብነው፤ በቅርብም ሲፈጸም ያየነው ተግባር ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ከመከራ እንዲሰውራቸው ብቻ ሳይሆን በሰማዕትነት እንዲያበረታቸውም ይለምኑ ነበር፡፡ ቤተክርስቲያን ለሁለት ሺህ ዘመናት ያልተፈተነችበት የመከራ አይነት፣ያልተፈጸመም ተአምር አለመኖሩን ክርስቲያኖች ብቻ ሳይሆን አሕዛብም የሚመሰክሩት እውነታ ነው፡፡ አሕዛብ ቤተክርስቲያንን ለማጥፋት ሲነሡ ክርስቲያኖች ታቦታትና ንዋያተ ቅድሳትን ይዘው እንዲሸሹ ከማድረግ በተጨማሪ  እግዚአብሔር አምላክ በማይታበል ቃሉ ታቦታቱም ሆኑ አብያተ ክርስቲያናቱ እንዲሰወሩ ሲያደርግ ኖሯል፡፡ በግብጽ የነበረ የቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ታቦት በእስላሞች በፈረሰ ጊዜ እግዚአብሔር አምላክ ጽላቱን ሰውሮት ከብዙ ዘመን በኋላ በኢትዮጵያ ውስጥ ከአባ ተክለ ሃይማኖት የትውልድ አካባቢ ጽላልሽ ቤተክርስቲያን ሲተከል  ታቦቱን ሰጥቷቸው አክብረውታል፡፡ እንዲህ አይነት ተአምራት በየዘመናቱ ተፈጽመዋል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን ቤተክርስቲያንን ሊያቃጥሉ፤ ክርስቲያኖችን ሊገድሉ የተሰለፉ ወገኖች ሲጋፉት ለነበሩት ሃይማኖት ጠበቃ እንዲሆኑም አድርጓል፡፡ ከጥፋታቸው አልመለስ ካሉም ተቀስፈው እንዲሞቱ ሲያደርግ ኖሯል፡፡ ይህንን የምንጽፈው በአንድ በኩል በእምነት ያሉትን ለማጽናናት ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ ታሪክን መጥቀስ እንጂ ከታሪክ መማር የማይፈልጉ ወገኖች አንብበው እንዲጠቀሙበት በማሳብ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን እየተሳደደች ትዕግሥቷን አሕዛብ አይተው እንዲማሩ ለማስተማር ጭምር ነው፡፡

የምዕራባውያን ተልእኮ አስፈፃሚ የሆኑ መናፍቃንና ግብረ አበሮቻቸው ኢትዮጵያውያንን የአስተሳሰብ ድሃ ለማድረግና የነጮችን  የበላይነት አምነው እንዳይቀበሉ እንቅፋት የሆነችባቸውንና የሰውን ልጅ  ለሁሉም እኩልነትን የምታስተምረውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን  ለመበቀል የሚችሉትን ሁሉ ያደርጋሉ ዝናራቸውን ቢያራግፉና ቀስታቸውን ቢጨርሱም ለማሸነፍ እንደማይችሉ እያወቁት ራሳቸውን የሚጎዳ ተግባር ይፈጽማሉ፡፡ በዐድዋ በማይጨውና በሌሎች ከውጭ ወራሪዎች ጋር በተደረጉ ጦርነቶች የተሳተፉት ኦርቶዶክሳውያን ብቻ ባይሆኑም ቤተክርስቲያን ለሀገር መሞት ክብር መሆኑን በማወጅ፤ ምሕላ በመያዝ፤ ለዘማቾች የቁም ፍትሐት በማድረግ ያበረከተችውን አስተዋጽኦ በማሰብ መልካቸው እና ቋንቋቸው የሚመስሉንን አሠልጥነው ይልካሉ፡፡ ገንዘብ ማግኝት የሃይማኖተኝነት መስፈርት አስመስለው የዋሃንን ያሳስታሉና በቻሉት ሁሉ የቤተክርስቲያንን አስተዋጽኦ ከትውልድ አእምእሮ አጥበው ለማውጣት ብቻ ሳይሆን የፈጠራ ታሪክ እየፈበረኩ ጥላቻ ሲነዙ ይሰማሉ፡፡የሚያስፈልግውም ይህን የሐሰት ጽሑፍ እውነተኛ መረጃ ይዞ መንግሥት በፍርድ ቤትም መጠየቅ አስፈላጊ ነው፡፡

ኅዳር ፯ እና ፰ በ፲፱፻፺፰ ዓ.ም ኮፈሌ አንሻ በተባለ ቦታ የእስልምና እምነት ተከታዮች ስድስት ክርስቲያኖችን ማረዳቸው እስልምና ባለበት ሀገር ሁሉ ተገዳዳሪያቸውን የማጥፋት ተግባራቸው ማሳያ ነው፡፡በምእመናን ብዛት ከፍተኛውን ቊጥር ያላትን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ማጥቃት፤ ማዳከምና ምእመናንን አስገድዶ ማስለም የሚፈጸሙ ተግባራት ናቸው፡፡ በእምነት ስም የተደራጁ ቡድኖች እና የእምነቱ ተከታዮች ቤተክርስቲያንን ሲያጠቁ እና በተለያዩ ጊዜያት ጥቃቶችን ሲፈጽሙ ይታያሉ፡፡ ክርስቲያኖችን  አስገድዶ በማስለም፤ ፈቃደኛ ካልሆኑ ደግሞ የመግደል ተልኳቸውን ሲፈጽሙ ለደረሰው ጥፋት ክርስቲያኖች ለሚመለከተው አካል  አቤቱታ ሲያቀርቡ ፍትሕ አለመሰጠቱ ወደፊት መስተካከል ይርበታል፡፡ይህ ድርጊት በወቅቱና በጊዜው ካልታረመ መጨረሻ ለሌለው ብጥብጥ እንደሚዳረግ መታወቅ ይኖርበታል፡፡

በቡርቃ ጉዲና እና በአዲስ ልማት ቀበሌዎች ከ፪፻ በላይ ክርስቲያን አባወራዎች ይኖሩ የነበሩ ሲሆን በ፳፻፲፩ ዓ.ም በተደረገው የክርስቲያኖች ቈጠራ ፻፹፭ ሆነዋል፡፡ ይህም የሆነው የክርስቲያኖች ግድያና ስደት ስለተባባሰና ድርጊቱ ሲፈጸም እየታየ ተው ባይ በመጥፋቱ ነው፡፡ ጥፋቱ ተጠናቅሮ በመቀጠሉም ከሚያዚያ ወር  መጀመሪያ እስካሁን ፲፭ አባወራዎች በጋሌ ሰረጡ ቅድስት ኪዳነምሕረት ቤተክርስቲያን ውስጥ ከቤተክርስቲያኑ አስተዳዳሪ ቄስ ጋር በድንኳን ተጠልለው እየኖሩ ነው፡፡ በክርስቲያኖችና በአብያተ ክርስቲያን ላይ እየደረሰ ያለው ጥፋት ይቁም የምንለውም እንዲህ አይነት ኢሰብአዊ ተግባራት ሲፈጸሙ ሰለምንመለከት ነው፡፡ ሀገራችን ለውጥ ላይ መሆኗ ይታወቃል፡፡ ለውጡን ያልፈለጉት ወገኖች ኢትዮጵያውያን ከቀያቸው እንዲፈናቀሉ በማድረግ የሀገራችንን ገጽታ እያበላሹ መሆኑን ባንዘነጋውም በአንዳንድ አካባቢዎች ክርስቲያኖች ላይ ብቻ ያነጣጠረ ጥቃት ሥልጣን ላይ በተቀመጡ አካላት ጭምር ሲፈጸም መታየቱ ለሰላም ሳይሆን ለብጥብጥ  እየተሠራ ያስመስላልና መፍትሔ ሊፈለግለት ይገባል፡፡

የመንግሥት አካላት ሕዝብን ለማገልገል ኃላፊነት እንዳለባቸው ከተረዱ ሁሉንም ኢትዮጵያዊ ዘር፣ቋንቋ፣ቀለም፤ ሃይማኖት፣ሳይለዩ ማገልገል ይኖርባቸዋል፡፡ለሚያልፍ ሥልጣን ታሪክ የማይረሳው ጠባሳ ትቶ ማለፍ ተገቢ አይደለም፡፡ በየቦታው ለሚከሠቱ ግጭቶች መፍትሔ ከመፈለግ ተቆጥበው ተረጋግቶ ለሥራ የተሰማራንና ስለሀገሩ የሚጸልይን ክርስቲያን መነካካት ጥፋት እንጂ ሰላምን አያመጣም፡፡

ሐምሌ ፲፱ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በባሌጎባ በተፈጠረ የሃይማኖት ግጭት ፭ ምእመናን ተገድለዋል፡፡ እንዲህ አይነት ጥፋቶች አሁንም ቀጥለዋል የሃይማኖት ግጭቶች ሲከሠቱ ግጭቶችን ማን እንዳስነሣቸው ማጣራትና ተገቢ የሆነ እርምጃ መስጠት ይገባል፡፡ እየታየ ያለው ግን እየተሰደዱ፣ እየተገደሉ ታቦታችሁን ይዛችሁ ውጡ የሚባሉትን ክርስቲያኖች መብታቸውን ሲጠይቁ ማሰርና ያለፍርድ ማጉላላት ነው፡፡ ይህን ተግባር ለማስታገስ በየአካባቢው የሚገኙ የመንግሥት አካላት ኃላፊነታቸውን በአግባቡ የማይወጡ ከሆነ የክርስቲያኖችን ችግር የፈጠረው ማን እንደሆነ፤ እነ ማን ያላግባብ እንደታሰሩ፤ ማን የሚባል ፖሊስ እንዳሰራቸው፤ ለምን ፍርድ ቤት እንዳላቀረባቸው፤ ፍርድ ቤት ለማቅረብ ጠበቃ የማግኘት መብታቸውን ማን እንዳስከለከለ መረጃውን አደራጅተው ለመንግሥት አካላትም በየደረጃው ለሚገኙ የቤተ ክህነት አገልጋዮችም ማሳወቅ ይኖርባቸዋል፡፡ መንግሥትንም በሕጋዊ መንገድ ለመጠየቅ ያግዛል፡፡ አጥፊዎች እናምንበታለን ከሚሉት  የእምነት ተቋማት ጋር ለመወያየትና አሳማኝ መረጃ ይዞ በፍርድ ቤት ለመጠየቅ ይጠቅማል፡፡ይህ ሁሉ እየተደረገ ጎን ለጎን መረሳት የሌለበት ጉዳይ እግዚአብሔር አምላክ፤ችግሩን እንዲያስወግደው በጾም በጸሎት መጠየቅ ይገባል፡፡ እግዚአብሔርን በንጹሕ ልቡና ሆነን ከጠየቅነው የተፈጠረው ችግር ይርቃል፡፡ በኃጢአታችን ምክንያት ከመጣም ይቅር ይለናል፡፡ ለክብር ከሆነም ያጸናናል፡፡ በእምነት ጸንተን ብንሞት እንኳ ገዳዮቻችንን ማርኮ ያመጣል፡፡ የሰማዕትነት ደም ደርቆ አያውቅም የተባለው ሞታቸው አሕዛብን ማርኮ የሚያመጣ በመሆኑ ነው፡፡

 በክርስቲያኖችና በቤተ ክርስቲያን ላይ እየተፈጸመ ያለው ጥፋት አለመቆሙ ያሳሰበው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የሰ/ት/ቤት ወጣቶች፤ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርትና ምሩቃን እንዲሁም የመንፈሳዊ ማኅበራት ተወካዮች በወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ጉዳዩች ላይ መግለጫ ሰጥቷል፡፡ መግለጫው በአንድ በኩል አጥፊዎች ሕግና ሥርዓት ባለበት ሀገር ከእኩይ ድርጊታቸው እንዲታገሡ ጥፋታቸውን የደረስንበት መሆኑን እንዲረዱ የሚያሳስብ ሲሆን በሌላ በኩል መንግሥትም አጥፊዎችን ለሕግ ማቅረብ  እንዳለበት ለማሳሰብ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ክርስቲያኖች አንድነትና ትብብር የሚያደርጉበትና ከፊት ይልቅ መትጋት የሚገባቸው መሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡ ቤተክርስቲያን ያለችበት ሁኔታ ያሳሰበው የቤተክርስቲያን አካል የቅድስት ቤተክርስቲያናችን ውለታና እያደረገችው ያለው አስተዋጽኦ ተረስቶ ለሀገራዊ ጥፋት  ባለቤት ተደርጋ መኮነኗን በጽኑ እንቃወማለን፤ ቤተክርስቲያን ከትላንት እስከ ዛሬ የሰላም መልእክተኛ እንጂ አጥፊዎች የሐሰት ታሪክ ፈጥረው እንደሚያወሩት ሕዝብን ከሚያስጨፈጭፉ አካላት ጋር ተባብራ ያጠፋች አይደለችም፡፡ በእውነት ለመናገር ካስፈለገ  በደቡብ፤ በምሥራቅ፤ በኦሮምያም ጭምር ክርስትና ያበበው በሀገሩ ባህል ላይ መሆኑን  መረዳት አይሳነውም፡፡ በአንጻሩ ሌሎች እምነቶች በገቡበት ቦታ ግን ነባሩ ባሕል ተደምስሶ ሀገራችን እስከማይመስል ደርሷል፡፡ አስተዋይ አእምሮ ላለው ሰው በታሪክ ተወቃሽ የሚሆነው ነባሩን ባህል አስገድዶ ሃይማኖት ያስለወጠ እንጂ ባህላችሁን ጠብቃችሁ ዘላለማዊ ርስትን የምትወርሱበትን ወንጌልን መቀበል ትችላላችሁ  የምትለው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን መሆን አይደለችም፡፡

ይቆየን

 ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ፳፮ ዓመት ቁጥር ፲፯

 

በዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተና

የተከበራችሁ አንባብያን እንደምን ሰነበታችሁ? ባለፉት ተከታታይ ጽሕፎች ላይ በዘመናችን ቤተ ክርስቲያን የገጠማትን ፈተና በተለይ የቤተ ክርስቲያንን ቃጠሎና የይዞታ መነጠቅን በተመለከተ መጠነኛ መረጃ የሚሰጥ ጽሑፍ ማቅረባችን ይታወቃል፡፡ ቀጣዩን ደግሞ እንደማከተለው አቅርበነዋል፡፡

ሀገራችንን የምንወድና ሰላማውያን ከሆንን ቀርበን መወያየት፣ ጥፋተኞችን መገሠጽ፣ አጥፊዎችን ለሕግ ማቅረብና ለተፈጠረው ጥፋት ይቅርታ ጠይቆ ካሳ ካስፈለገ መክፈል ነው፡፡ በሃያ ሰባት ዓመታት በቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሰውን እንተውና ለውጥ ከመጣ በኋላ የጥፋት ኃይሎች የፈጸሙትን በመጠኑ ለማቅረብ እንሞክር ቢባል እንኳ ተዘርዝሮ አያልቅም፡፡ ‹‹ሚያዝያ ፳፻፲፩ ዓ.ም ሐረር ሳሮሙጢ በሚኖሩ በአራት ካህናትና በምእመናን ላይ የመግደል ሙከራ ተደርጐ ከባድ ድብደባ ቢፈጸምባቸውም በእግዚአብሔር ቸርነት ተርፈው ሆስፒታል ገብተዋል፡፡›› ይህ የሚያሳየው ጥፋቱ ተጠናክሮ መቀጠሉን ነው፡፡ ይህንን ጥፋት እየፈጸሙ ሰላማውያን ነን ቢሉን ማመን አንችልም፡፡ ሰላም የሚመጣው በተግባር እንጂ በቃል አይደለም፡፡ መንግሥት አጥፊዎችን ለሕግ ያቅርብልን፣ ወደ ፊትም ጉዳት እንዳይደርስብን ጥበቃ ያድርግልን የምንለው ለዚህ ነው፡፡ ጥፋቱ አንድ ጊዘ ተፈጽሞ በመቆሙም አይደለም፡፡ በድሬዳዋ፣ በከሚሴ፣ በኤፍራታና ግድም፣ በሰሜን ሸዋ ሰላሌ፣ በምዕራብ ሸዋ፣ ወሊሶ፡ በጅማ ሊሙኮሳ በተከታታይ የተፈጸመውን በማየት እንጂ፡፡

በድሬዳዋ ሀገረ ስብከት የተፈጸመውም ከዚህ ጋር ተቀራራቢ ነው፡፡ በድሬዳዋ ከተማ ዳር የሚገኘውን ‹‹የመካነ ሕይወት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያንን ይዞታ እንወስዳለን በማለት ከመጋቢት ፳፻፲፩ ዓ.ም ጀምሮ ተደጋጋሚ ጥቃቶች በእስላሞች ተፈጽመዋል፡፡ የፖሊስ አባላቱ ችግር በተፈጠረበት ቦታ በሰዓቱ ቢደርሱም ጥቃት ፈጻሚዎቹን በመያዝና ወደ ሕግ በማቅረብ ፈንታ እንዲሸሹ ማድረጋቸውን ለማወቅ ችለናል፡፡ በአንጻሩ ደግሞ የቤተ ክርስቲያንን ይዞታ አናስነካም፣ ቤተ ክርስቲያን ጉዳት ሲደርስባት ቆመን አናይም ያሉ ወጣት ክርስቲያኖችን አስረው በመግረፍ የጥቃቱ ተባባሪ ሆነዋል፡፡››

ማኅበረ ቅዱሳን ወንጀል የሠሩ አካላት አይጠየቁ አላልንም፡፡ ጥፋተኛ ተለቅቆ፣ ተጎጂው የሚታሰርበትና የሚሰቃይበት አሠራር ይስተካከል በማለት ግን እንጠይቃለን፡፡ የፍትሕ አካላትም ከአንድ ወገን የሰሙትን ብቻ ይዘው ወደ ውሳኔ ከመግባት ይልቅ ከሃይማኖት ነፃ በሆነና የተቀመጡበትን ኃላፊነት ባገናዘበ መልኩ ሁለቱንም ወገን ፊት ለፊት አቅርቦ እውነቱን በማውጣት አጥፊዎችን ለሕግ ማቅረብ ይኖርባቸዋል ለማለት ነው፡፡ በወቅቱ የቤተ ክርስቲያኑን ይዞታ ለመቀራመት አሰፍስፈው የነበሩ ወገኖች የምኒሊክ ሃይማኖት ይውጣልን በማለት ይጮኹ እንደነበር የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡ ይህ ድርጊት የሰውን ልጅ የእምነት ነፃነት የሚፃረር ነው፡፡

የቤተ ክርስቲያንን ይዞታ ለመቀራመትና ደኗን ጨፍጭፎ ለማውደም የተሰለፉ ወገኖች ቤተ ክርስቲያኗን ከምኒሊክ ጋር ለማያያዝ ምን ሞራላዊስ ሃይማሃታዊስ ችሎታ ይኖራቸዋል፡፡ ክርስትናም ጌታችን ለሐዋርያት ያስተማረው እንጂ በሰዎች የተፈጠረ ሃይማኖት አይደለም፡፡ ምኒሊክ ከመነሣታቸው ከሁለት ሺህ ዓመታት በፊት ፍጹም አምላክ የሆነው እግዚአብሔር ወልድ ፍጹም ሰው በመሆን የመሠረተው፣ ዓለምን ከጨለማ ወደ ብርሃን ያመጣበት ሃይማኖት ነው፡፡

ቅዱስ ጳውሎስን ሊገድሉ በለስ አልቀናቸው ያሉ አይሁድ የሮማውያን ሕግ የሰጣቸውን መብት በትክክል መጠቀም ሲገባቸው ሕጉን ጠምዝዘው ጳውሎስን ካልገደልን እህል አንበላም፣ ውኃም አነጠጣም ብለዋል፡፡ ታሰሮ የነበረውን ቅዱስ ጳውሎስ ወደ አደባባይ እንዲያወጣላቸው ሀገረ ገዥውን ሕጋውያን መስለው ጠይቀው የግል ጥላቻቸውን በሕግ ሽፋን ለመፈጸም ተማምለው እንደነበር ሁሉ ዛሬም እየተፈጸመ ያለው የጥንቱ ተመሳሳይ ክፍት ነው፡፡ ሕግ የሰጠውን መጠቀም መብት ነው፡፡ ሕግን ጠምዝዞ ግላዊ ፍላጐትን ለማሟላትና ሌላውን ለማጥፋት መሞከር ግን ወንጀል ነው፡፡ የማይገለጥ የተከደነ፣ የማይታወቅ የተሰወረ ጉዳይ ባለመኖሩ ተደብቀን ብናጠፋ ሁለት ቀን ሳናድር እውነቱ ይገለጣል፡፡ የአጥፊዎች አሳብ ታሪክ ምንም ይበል እኛ ብቻ ደኅና ካላሉና ሀገር ብትበተን ምን አገባን ካላሉ በስተቀር ያልተረዱት እውነታ ወደ ሌላው የወረወሩት ቀስት እነሱንም እንደሚወጋቸውና ለሌላው ያነደዱት እሳት ራሳቸውንም እንደሚያቃጥላቸው ነው፡፡

በዚሁ በያዝነው ዓመት ባሳለፍነው የሚያዝያ ወር ሌላም ዘግናኝ ድርጊት በእስልምና እምነት ተከታዮች ጅማ ሀገረ ስብከት ሊሙኮሳ በሚባል ቦታ ተፈጽሟል፡፡ ታሪኩ እንዲህ ነው ‹‹ሚያዝያ አምስት ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ለሚዘክረው አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጽዋ ጉዝጓዝ ቄጠማ ሊያጭድ በሔደበት ሚጡ ወንዝ ዳርቻ አቶ ልየው ጌትነት የተባለን የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ  ቤተ ክርስቲያን የእምነት ተከታይ አንገቱን ቀልተዉ በመጸዳጃ ቤት ጉድጓድ ውስጥ ከጣሉት በኋላ በላዩ የከብት ፍግ ጨምረውበታል፡፡ የመጸዳጃ ጉድጓዱ ባለቤት አቶ መሐመድ ሃምዛ የተባሉ ግለሰብ ነው፡፡ ወዳጅ ዘመዶቻቸው ቄጤማ ሊያጭድ ወጥቶ የቀረውን አቶ ልየው ፍለጋ ቢወጡ የደም ነጠብጣብ በማግኘታቸው ነጠብጣቡን ተከትለው ሲሔዱ ለማመን በሚከብድ ሁኔታ ገድለው ከአጨደው ቄጠማ ጋር መጸዳጃ ቤት ውስጥ ጥለውት ተገኝቷል፡፡›› ይህን ወንጀል የፈጸመው አካል ተጠርቶ ወደ ሕግ አልቀረበም፡፡ ከሁለት ዓመት ላላነሰ ጊዜ በደረሰባቸው ተደጋጋሚ ግፍ በአካባቢው ይኖሩ የነበሩ ክርስቲያኖች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ድንኳን ተክለው መኖር ጀምረዋል፡፡

ቤተ ክርስቲያን ስታስጠልል ዘርና ሃይማኖት እንደማትመርጥ የመካቆሪሾች አባርረዋቸው ለመጡት የመሐመድ ተከታዮች ክርስቲያኑ ንጉሥ አረማህ ተቀብሎ በሰላም እንዲኖሩ የፈቀደላቸው መሆኑን የምንመሰክረው እኛ ብቻ ሳንሆን ምዕራባውያን ጭምር ናቸው፡፡ ይህንንም ጉዳይ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ‹‹የእነሱ መንግሥታት (ምዕራባውያን) በ፳ኛው መቶ ክፍለ ዘመን እኔን የመሰለ ስደተኛ በሀገሩ መቀበሉን እንደ ትልቅ ሰብአዊ ድርጊት ሲቆጥረው፤ የእኔ ሀገር ንጉሦች የጄኔቫ ኮንቬንሽን (ስምምነት)፣ ሰብአዊ መብትና ዲሞክራሲ የሚባል ነገር በሰው ልጅ አእምሮ ባልታሰበበት ከአንድ ሺህ አምስት መቶ ዓመታት በፊት በእምነታቸው ከዘመኑ የሀገራችን ሰዎች እምነት የተለዩ የነቢዩ መሐመድ ተከታዮች ጥገኝነት መስጠታቸውን፣ እነዚህን ስደተኞች መልሱልን በማለት ዓረቦች ለላኩት መልእክተኛ፣ ንጉሣችን በእያንዳንዱ ስደተኛ ክብደት የሚመዝን ወርቅ ብትሰጡኝ እንኳን አሳልፌ አልሰጣችሁም›› (አንዳርጋቸው፣፳፻፲፩፥፲፱) በማለት መመለሳቸውን ጽፈዋል፡፡

ስለዚህ ጉዳይ በጥልቅ ለማወቅ የፈለገ ሰው የእነ ጆን ሰፔንሰር ትሪሚንግሆምን እስላም ኢን ኢትዮጵያን እና የጎበዜ ጣፈጠን እስልምና በአፍሪካ ማንበብ ይጠቅመዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያንን እንግዳ ተቀባይነት በማቃለል ማጣጣል ተገቢ አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ ነገሥታት ጠብቀው ባቆዩዋት ሀገር እየኖሩ ነገሥታትን የሚተቹና ቤተ ክርስቲያንን ከነገሥታት ጋር እየደረቡ ለመምታት የሚፈልጉ ወገኖች እንደሚተርኩት ሳትሆን ትክክለኛ በመሆኗ በቅርቡ በለገጣፎም ሆነ በቡራዩ የተፈናቀሉ የእስልምናም የሌላ እምነት ተከታዮች እንጠጋ ብለው ሲመጡባት አታምኑብኝም የምትል ሳትሆን ልጆቼ ኑ ብላ እጇን ዘርግታ የምትቀበል መሆኗን አሳይታለች፡፡ ቤት ፈርሶባቸው ቤተ ክርስቲያን የተጠለሉ ወገኖች በኢሳት የቴሌቭዥን ጣቢያ ሲናገሩ ሰምተናልና፡፡

የሚጠቅመንም ካለፈው መጥፎ ታሪክ እየተጠነቀቅን መልካም ከሆነው ያለፈ ታሪካችን መማር ነው፡፡ ድሮ ተፈጽሟል እያሉ የሐሰት ታሪክ እየደረቱ የጥፋት ነጋሪት መምታት እልቂት እንጂ ሰላም ስለማያማጣ አጥፊዎች ደግመው ደጋግመው ተረጋግተው እንዲያስቡበት ማሳሰብ እንወዳለን፡፡ መንግሥትም አጥፊዎችን እንዲያስታግሥልን ደግመን እንጠይቃለን፡፡ ይህንን ጽሑፍ የምንዘጋው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች፣ የመንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርትና ምሩቃን እንዲሁም የመንፈሳዊ ማኅበራት ተወካዮች በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ በሰጡት መግለጫ ነው፡፡ እንዲህ ይላል ‹‹እስከ ዛሬ ሲፈጸሙ በኖሩ ጥቃቶች ላይ ከጥንስሱ ጀምሮ እጃቸውን የከተቱ፣ ያለ አንዳች ፍርሃት በአደባባይ ጭምር በክርስቲያኑ ሕዝብ ላይ ሲሳለቁ እና በል ሲላቸውም ዕልቂትን ሲያውጁ በከረሙና እያወጁ ባሉ ከመንግሥት ጭምር የፈረጠምን ነን ባይ ግለሰቦች እና ተቋማት መንግሥት ለፍርድ እንዲያቀርብልን እንጠይቃለን›› ይህ ቃል ሰላም ወዳድ ከሆነ አስተዋይ አካል የሚነገር ነው፡፡ ጥፋትን በጥፋት መመለስ ለሀገር አይጠቅምምና፡፡

 ይቆየን

 ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ፳፮ ዓመት ቁጥር ፲፮

 

በዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተና

የተከበራችሁ አንባብያን እንደምን ሰነበታችሁ? ባለፉት ተከታታይ ዕትሞች ላይ በዘመናችን ቤተ ክርስቲያን የገጠማትን ፈተና በተለይ የቤተ ክርስቲያንን ቃጠሎና የይዞታ መነጠቅን በተመለከተ መጠነኛ መረጃ የሚሰጥ ጽሑፍ ማቅረባችን ይታወቃል፡፡ ቀጣዩን ደግሞ እንደማከተለው አቅርበነዋል፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያለስሟ ስም፣ ያለ ግብሯ ግብር እየተሰጣትና ለማጥፋት ምክንያት እየተፈለገላት መሆኑ እየታየና እየተሰማ ነው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከቅዱስ ሲኖዶስ እስከ አጥቢያ በተዘረጋው መዋቅር መሥራት የሚገባትን፣ ማኅበራት፣ ዘማርያንና ሰባክያን መፈጸም የሚኖርባቸውን፣ ምእመናንና ምሁራን ማከናወን የሚጠበቅባቸውን ማሳወቅ ዘመኑ የማጠይቀው ተግባር ነው፡፡ በአንድ በኩል ከሌሎች የእምነት ተቋማት ጋር መተባበር እና መረጃ በመለዋወጥ መሥራት የሚገባንን፣ በሌላ በኩል እየተፈጸመ ያለውን ጥፋት ለመንግሥት በማሳወቅ በአጥፊዎች ላይ እርምት እንዲወሰድ ማገዝ ይገባል፡፡ የአጥፊዎችን የተሳሳተ ትርክታቸውንና ለቤተ ክርስቲያን ያላቸውን ጥላቻ እንዲያስወገዱ እንዲያደርግ ማሳሰብ ሲገባ በሌላ በኩል ደግሞ ከዛሬ ነገ ይማራሉ፣ በመረጃ የተደገፈ ትንታኔ በማቅረብ አስተማሪ የሆነ ጽሑፍ ያቀርባሉ ብለን ብንጠብቅም ዝም ማለታችንን እንደ ፍርሃት፣ አለመጻፋችንን እንደ አላዋቂነት ለሚቈጥሩ ወገኖች ሚዛኑን የጠበቀና ትክክለኛ መረጃ መስጠት ይገባል፡፡

ከትላንት እስከ ዛሬ የፈጸሙትን ጥፋት በማሳየት ማን ጥፋተኛ እንደሆነ አንባብያን የራሳቸውን ፍርድ እንዲሰጡ ማንቃትና ለተጨማሪ ንባብ መቀስቀስ ያስፈልጋል፡፡ ‹‹ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮኻል›› አካሔዳቸውን መግለጥ ባልቻልን ምንም እውነትን ብንይዝ ካልተገለጠ ጠቀሜታው ይደበዝዛል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ከአንዳንድ ባለሥልጣናት እየተጠጉ የሚፈጽሙትን ጥፋትም ማጋለጥ ያስፈልጋል፡፡ ሥራ አጥ ወጣቶች ሠርተው የሚበሉበት፣ ምሁራን ተመራምረው ሀገር የሚያበለጽጉበት ተግባር ከመፈጸም ይልቅ ሀገሪቱን ሁሉ ቤተ እምነት ካላደረግን፣ የሚያዩትን ባዶ ቦታ ሁሉ ካልሠራንበት የሚለው አካሔድ እንደ ሀገር አስማምቶ ሊያኖረን እንደማይችል ማስገንዘብ ይገባል፡፡ እውነት እንነጋገር ከተባለ ሰማንያ በመቶ የሚሆነው የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታይ ያለው ቤተ እምነትና ፕሮቴስታንትና እስልምና ቢደመር ሃያ በመቶ ባይሆኑም እያንዳንዳቸው ያላቸው ቤተ እምነት ከኦርቶዶክሱ እጥፍ ሊሆን ምንም አይቀረው፡፡ ይህን እያወቅን እንኳ ያልጠየቅነው ከሁሉ በፊት ለሀገር ማሰብና ለሰላም መስፈን መሥራት ይገባል ብለን ስለምናምን ነው፡፡

በቤተ ክርስቲያኗ ላይ እየተፈጸመ ያለው ጥፋት ያሳሰበው ዜና ቤተ ክርስቲያን በጥቅምት ኅዳር ፳፻፲፩ ዓ.ም ዕትሙ ‹‹ለሁሉም በተሰጠው ገደብ የለሽ የእምነት ነፃነት መሠረት፣ ሁሉም የራሱን እምነት በሰላም ማራመድ ሲገባው በተቃራኒው ፀረ ኦርቶዶክስ ዘመቻ በሁለት ግንባር በመካሔድ ላይ ይገኛል፡፡ በአንድ በኩል ቀደም ሲል በዝርዝር እንደተገለጠው ፀረ ክርስትና አቋም ያለው ቡድን በአንዳንድ አካበቢዎች የሚገኙትን የኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያን እያቃጠለ ነው፡፡ ካህናትንና ምእመናንንም እያረደ ነው፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ እነ ፖስተር ኢዩ ጩፋን የመሳሰሉት የእነ ሬንሐርድ ቦነኬ ደቀመዛሙርት በቡድን ተሰማርተው ሕዝቡን በወንጌል ሳይሆን በመናፍስት በማስገደድና በካራቴ በማሳመን የእነርሱ ተከታይ ለማድረግ እየጣሩ ነው›› በማለት በርእሰ አንቀጹ ጽፎ ነበር፡፡

የሚገርመው ይህ ጥፋት በመቀነስ ፈንታ እየጨመረ፣ በመሻሻል ፈንታ እየባሰበት መምጣቱ ነው፡፡ የችግሩ መሞከሪያ፣ የጸጥታው ማስፈጸሚያ ቤተ ክርስቲያንና ክርስቲያኖች እስከሚመስሉ ድረስ በክርስቲያኖች ሞትና መከራ ላይ መከራ እየተደረገ ሀገር ትረጋጋለች ተብሎ ስምምነት ላይ የተደረሰ ያስመስላል፡፡ ይህ ጥፋት ሁል ጊዜ ሰበብ እየተፈለገ እንዲቀጥል አንፈልግም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሲቃጠል በግል የተፈጸመ፣ ክርስቲያኖች ሲገደሉ የግል ጠብ እየመሰለ መነገሩ በጀርባው ሌላ ተንኮል ያለ መሆኑን እየተገለጠልን መምጣቱን መረዳት ይገባል፡፡ ሀገር በጠባጫሪነትና ሁሉ ነገር ለእኔ በሚል መንፈስ መገንባት እንደማትችል የታወቀ ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን መረጃው እያለው እንደ ሌለው፣ ግልጽ አድልዎ እየተፈጸመ መሆኑን እያወቀ ዝም ያለው አጥፊዎችም አደብ ይገዛሉ፣ መንግሥትም እርምት ይወስዳል በማለት ነው፡፡ አሁን ግን የሚፈጸመው ጥፋት እየከፋ መጥቷል፡፡ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስን ማኅበር ለመዘከር የቤት ጉዝጓዝ ሊያጭድ የሔደን ክርስቲያን በገጀራ ከትክቶ ሽንት ቤት መክተት፣ በየቦታው ኦርቶዶክሶች እየተመረጡ አካባቢያቸውን እንዲለቁ መደረጉ የአደባባይ ምሥጢር ነው፡፡ ይህ ሲደረግ መረጃው እንዳይወጣ መደበቁ እንደ ሀገርም እንደ ቤተ ክርስቲያንም መሠራት ያለባቸው ጉዳዮች መኖራቸውን የሚያሳዩ ናቸው፡፡

በቤተ ክርስቲያን እንዳይሠለስ እንዳይቀደስ ከማድረግ በተጨማሪ በደቡብ ክልል ጎፋ ዞን የሚገኘው የመሎላሃ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ጥምቀተ ባሕር ሥልጣን ላይ በተቀመጡ የፕሮቴስታንት ተከታዮች ለአውቶቢስ መናኽሪያ መሰጠቱና ታቦትና ንዋያተ ቅድሳታችሁን ይዛችሁ ውጡ ተብለው በእግራቸው ፻ ኪሎ ሜትር በላይ ታቦትና ንዋያተ ቅድሳት ይዘው መንከራተታቸው በፈጠረው የማኅበራዊ መገናኛ ብዙኃን ጫና የተደናገጡ ባለ ሥልጣናት ታቦቱ ወደ መንበሩ እንዲመለሰ ያደረጉበት ታሪክ የሦስት ወር ትዝታ ነው፡፡ እንዲስተካከል የምንፈልገውም እንዲህ አይነቱ መጥፎ ተግባር ነው፡፡ ሕሊናቸው የመራቸውን፣ መንግሥት የሰጣቸውን ኃላፊነት የሚወጡ የሌላ እምነት ተከታይ ወገኖች እንዳሉ ሁሉ የተሰጣቸውን ኃላፊነት ለጥፋት የሚጠቀሙ መኖራቸው፣ በጥፋት ላይ ጥፋት እያስከተለ በመሆኑ በቶሎ መታረም አለበት፡፡

በሶማሌ ክልል አሥር አብያተ ክርስቲያን እንዲቃጠሉና ከሃያ ሰባት በላይ ምእመናን እንዲገደሉ፣ ብዙዎችም እንዲቈስሉ የተደረገው በመንግሥት መዋቅር ነው፡፡ የዚህን ድርጊት ተገቢ አለመሆን የተረዳው አዲሱ የሶማሌ መንግሥት አመራር ቤተ ክርስቲያኗን ይቅርታ መጠየቁን ጠቅላይ ሚኒሰትሩ የደሴ ከተማ ነዋሪዎችን ባወያዩ ጊዜ ሲናገሩ ሰምተናል፡፡ አጥፊዎች ከስሕተታቸው ቢመለሱና አስቀድመው ጥፋት ከመፈጸማቸው በፊት ደጋግመው ቢያስቡ መልካም ነው፡፡ ይህም ባይሆን ከተፈጸመ በኋላም ይቅርታ መጠየቃቸው የሚያሰመሰግን ነው፡፡ ይቅርታ መጠየቁ ብቻውን በቂ ባለመሆኑም ተጨማሪ ተግባራትን መፈጸም ይገባል፡፡ በያዘው ሥልጣን የቤተ ክርስቲያንን ይዞታ እየነቀለ፣ ክርስቲያኖችን የገደለ በቃሉ ብቻ ይቅርታ በማለት እንዳይቀጥል ደንብና ገደብ ቢኖረው መልካም ነው፡፡ ይቅርታው ከስሕተት መታረሚያ፣ ዳግም ስሕተት ላለመፈጸም ቃል መግቢያ እንዲሆን መሥራት ይገባል፡፡ ይህንን ጉዳይ ወደ ፊት ሰፋ አድርገን ስላምናቀርበው በዚሁ እናቁምና በተለያዩ ቦታቸው የተፈጸሙ በምእመናን ላይ የደረሱትን ግድያዎች እናስከትላለን፡፡

ሐ. በምእመናን ላይ የደረሰ ግድያ፡-

ቤተ ክርስትያን ባለችበት ሁሉ ምእመናን አሉ፡፡ ምእመናን ቤተ ክርስቲያናቸው እየተቃጠለች ቆመው ማየት ስለማይችሉ ወይ አብረው ይቃጠላሉ ካልሆነም በአጥፊዎች ይገደላሉ፡፡ ይህም ፍርሃታቸውን ሳይሆን ጥብዓታቸውን፣ በመግደል ሳይሆን በመሞት አሸናፊዎች መሆናቸውን ማረጋገጣቸውን ያሳያል፡፡ በሊቢያ የሚገኘው አሸባሪው አይኤስአይኤስ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ክርስቲያኖችን ብቻ መርጦ ለመግደል ሲወስዳቸው በሰማዕታቱ ላይ ይነበብ የነበረው በራስ መተማመን ወደ ሞት ሳይሆን ለንግሥና ታጭተው የሚሔዱ ይመስል ነበር፡፡ ብዙዎች የውጭ ሚዲያ ጋዜጠኞችና የማኅበራዊ ብዙኃን መገናኛ ጸሐፊዎች እንዲህ አይነት ምእመናንን በእምነት አንፃ የምታወጣ ቤተ ክርስቲያን አማኝ መሆን የሚያስገኘውን ክብር ሲገልጡ ነበር፡፡ በአንጻሩ በመግደል እናሸንፋለን ብለው ያሰቡ አሸባሪዎች የሚቀናባቸው ሳይሆን የሚጠቋቆምባቸው ቢያተርፉና የሚተቻቸው ቢያገኙ እንጂ የተስተካከለ አእምሮ ካለው ሰው ምስጋና አያገኙም፡፡ አራት ዓመት ቢያልፍም የክርስቲያኖች ጥብዓታቸው፣ ሞትን ለዘለዓለማዊ ሕይወት መውረሻ መሆኑን ስለአወቁ በደስታ መጓዛቸው ዛሬም ድረስ ይተረካል፡፡ ባለፈው ታኅሣሥ የሊቢያ መንግሥት በጅምላ ተገድለው የተቀበሩበትን ቦታ አግኝቶ ለኢትዮጵያ መንግሥት እንደሚመልስ ሲናገር ክብራቸውን በመግለጥ ጭምር ነው፡፡

የክርስቲያኖች መገደል ተገቢ አለመሆኑን የምንገልጠው በዐዋጅ የሚፈጸም ስለሚመስል እንጂ እንደ ዘመነ ሰማዕታት ክርስቲያኖችን የሚፈጅ መንግሥት ቢሆን ለምን ለማለት አይደለም፡፡ መንግሥት በውጭና በሀገር ውስጥ የነበሩትን አባቶች ማስማማቱ፣ የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ሀገር መሆኗን መግለጡ፣ በደርግ ተወስደው የነበሩ ቤቶችን መመለሱ መልካም ነው፡፡ ይህ ብቻ ግን በቂ አይደለም መሬታችን ኦርቶዶክስ ሃይማኖትን እየሰበከ ሕዝቡ የሌላ እምነት ተከታይ እንዲሆን የሚሠሩ ስለአሉ ቆመን ማየት የለብንም፡፡ የአጥፊዎችን ድርጊት ይህንንም በገሀድም ሆነ በስውር የሚደግፉ ስለአሉ መንግሥት መፍትሔ እንዲሰጥ ለማሳሰብ ነው፡፡ መንግሥትን ስናሳስብ የሰማዕትነትን ዋጋ ዘነግተን፣ ሰማዕትነትን ፈርተን ሳይሆን ዕለት ዕለት ሰማዕትነት እንደምንቀበል አምነን ዘመኑ የሚጠይቀውን ለመፈጸም የምንችለውን ሁሉ ለማድረግ ነው፡፡ ይህንንም መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹አይሁድ ስለ ጳውሎስ ከፊት ይልቅ አጥብቀህ እንደምትመረምር መስለህ ነገ ወደ ሸንጎ ታወርደው ዘንድ ሊለምኑህ ተስማምተዋል፡፡ እንግዲህ አንተ በጄ አትበላቸው፤ እስኪገድሉት ድረስ እንዳይበሉና እንዳይጠጡ ተማምለው ከእነሱ ከዐርባ የሚበዙት ሰዎች ያደቡበታልና፤ አሁንም የተዘጋጁ ናቸው፣ የአንተንም ምላሽ ይጠብቃሉ አለው፡፡›› (ሐዋ.ሥ ፳፫፥፳‐፳፪) በማለት የተገለጠውን ማስተዋል ይገባል፡፡ ጥፋትን የሚፈጽሙና የግል ጥቅማቸውን የሚያሳድዱ አካላት ፍትሐዊና ቀና የሆነውን አሠራርና ሕግ ለራሳቸው በሚመች መንገድ የሚጠቀሙበት መሆኑን ይህ ቃል ያስረዳል፡፡ ልንነቃ የሚገባው የአካሔዳቸውን መሠሪነት ነው፡፡ እነሱ ሐሰትን ታሪክ አስመስለው ሲጽፉ ሕሊናቸውን አየቆጠቁጠውም እንዲያውም ለአምላካቸው መብዓ ያቀረቡ የሚመስላቸው አካሔዳቸው ተገቢ አለመሆኑን የሚያስገነዝብ መልስ ሲሰጣቸው ደግሞ መረጃ ይዞ ተከራክሮ እውነቱን ከማውጣት ይልቅ ትክክለኛ ጉዳይ የጻፉትን አካላት ስም በማጥፋትና ጉዳዩን ሌላ መልክ በመስጠተ ሌሎች እንዳይጽፉ ለማድረግ ይሞክራሉ፡፡ የተቀመጡበትን ወንበር መከታ አድርገው ሕዝብን በሕዝብ ላይ እንደማነሣሣት፣ ሃይማኖትን ከሃይማኖት እንደማጋጨት ይቈጥሩታል፡፡ መታወቅ የሚኖርበት ኦርቶዶክሳውያን ሲጽፉ ብቻ ጠብ አጫሪ መባል የማይገባቸው መሆኑን ነው፡፡ የሕዝብ ሰላም የሚያሳጣ፣ ከልማት ጥፋትን የሚያመጣ ተግባር ከፈጸሙ ለዚህ የጥፋት ተልእኮአቸው መልስ መስጠታችን፣ ሕዝበ ክርስቲያኑን ማንቃታችን የማይቀር ነው፡፡ እውነተኞች ከሆኑ የምንለያይበትንና የምንጋጭበትን እየፈለፈሉ በማውጣት ተአማኒነት ያለው ጽሑፍ ማቅረብ ነው፡፡ በዚህ ፈንታ የሚመርጡት በለመዱበት መንገድ መንግሥት በተቀየረ ቊጥር እየተጠጉ ኦርቶዶክሳውያንን ማስጠላት ነው፡፡ ይህን የምንለው እየተፈጸመ ያለው ጉዳይ ለሀገር አንድነት የማይጠቅም በመሆኑ በሌላ በኩል እነሱ በሔዱበት መንገድ መሔድ የሚያደርሰውን ጥፋት በመገንዘብ ነው፡፡

ይቆየን

 ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ፳፮ ዓመት ቁጥር ፲፮

ጾመ ፍልሰታ/ጾመ ማርያም/

መጋቤ ሐዲስ ብርሃን አንለይ

ፍልሰታ ማለት ፈለሰ፤ተሰደደ፤ተጓዘ፤ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ ሄደ ከሚለው የግእዝ ግስ የተገኘ ቃል ሲሆን ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ «ፈለሰት ማርያም እምዘይበሊ ኀበኢይበሊ፤ ድንግል ማርያም ከሚያልፈው ዓለም ወደማያልፈው ዓለም፣ ከምድር ሕይወት ወደ ሰማያዊ ሕይወት፣ ተሻገረች» በማለት ፍልሰታ የሚለውን ቃል ትርጓሜ አመሥጥሮ ገልጾታል፡፡

ጾመ ፍልሰታ ከእመቤታችን ድንግል ማርያም የዕረፍት ታሪክ ጋር የተያያዘ ነው፡፡ እመቤታችን በዚህ ዓለም ፷፬ ዓመታትን በሕይወተ ሥጋ ከቆየች በኋላ ጌታችን የእናቱን ተድላ ነፍሷን እንጂ ተድላ ሥጋዋን አይወድምና ጥር ፳፩ ቀን ፵፱ ዓመተ ምሕርት አረፈች፡፡ ዕረፍቷም እንደሌላው ሰው በሕማምና በድካም አይደለም፡፡ በገነት ዕፀዋት መዓዛ ተመስጣ ቅድስት ነፍሷ ከሥጋዋ ተለይታለች፡፡ ታሪኩ በነገረ ማርያም እንደተጻፈው ሐዋርያት እመቤታችንን በአጎበር አድርገው አክብረው ወደጌቴሴማኒ መካነ መቃብር ይዘዋት ሲሄዱ አይሁድ ለምቀኝነት አያርፉም ነበርና ቀድሞ ልጇን ተነሣ ዐረገ እያሉ ሲያውኩ ኖረዋል፤  እርሷን ደግሞ ተነሣች ዐረገች እያሉ ሊያውኩን ነውና «ኑ የማርያምን ሥጋ በእሳት እናቃጥለው» ብለው በምቀኝነት ተነሱ፡፡ ከመካከላቸው አንድ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊ ከሐዋርያት እጅ ለመንጠቅ ዘሎ ሄዶ የአልጋውን ሸንኮር ሲይዝ የታዘዘ መልአክ በረቂቅ ሰይፉ እጆቹን ቆረጠው፡፡ እጆቹም በአልጋው ሸንኮር ላይ ተንጠልጥለው ቀሩ፡፡ የምሕረት እናት የሆነችው ድንግል ማርያም ቅዱስ ጴጥሮስ ጸልዮ እጆቹን እንዲመልስለት ነግራው እንደነበረ አድርጎለታል፡፡

የእመቤታችን ሥጋዋን መላእክት ከዮሐንስ ወንጌላዊ ጋር በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር ወስደው አስቀምጠውታል፡፡ ሥጋዋ ያለበትን ሐዋርያው ቅዱስ ዮሐንስ አይቶ እነርሱ ባለማየታቸው እመቤታችን ባረፈች በ፮ኛው ወር ከነሐሴ ፩ ቀን እስከ ፲፬ ቀን ድረስ ከጾሙ በኋላ በ፲፬ኛው ቀን ሥጋዋን እንደገና ከጌታ ተቀብለው በጌቴሴማኒ ባለው መቃብር ቀብረውታል፡፡ ከዚህ በኋላ እንደ ልጇ በ፫ኛው ቀን ተነሥታ መላእክት እየዘመሩላት ወደሰማያት ስታርግ፤ ሐዋርያው ቶማስ ከሀገረ ስብከቱ በደመና ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመለሰ ዕርገቷን በማየቱ መላእክት «እመቤትህ እርሷ ናት፤ስገድላት» አሉት፤ እርሱም «ወፈቀደ ይደቅ እምደመናሁ ይላል፤ከደመናው ሊወድቅ ወደደ» ምክንያቱም ቀድሞ የልጇን ትንሣኤ፤ዛሬ ደግሞ የእርሷን ትንሣኤ ለማየት ብሎ ነው፡፡ እመቤታችንም «ትንሣኤየን ያየህ አንተ ነህ ሌሎቹ አላዩም» ብላ ሐዋርያት ገንዘው የቀበሩበትን የሐር ግምጃ ሰጥታ አጽናንታ ሰደደችው፡፡

ቅዱስ ቶማስ ኢየሩሳሌም ሲደርስ የእመቤታችን ነገር እንዴት ሆነ ብሎ ጠየቃቸው፤እነርሱም አግኝተው እንደቀበሯት ነገሩት፤ እርሱም ያየውን ምሥጢር በልቡ ይዞ «ሞት በጥር፤ በነሐሴ መቃብር፤ ለሰሚውም አያምር፤ይህ እንዴት ይሆናል?»፤ ቢላቸው ቅዱስ ጴጥሮስ «ድሮም አንተ ተጠራጣሪ ነህ፤ማን ያርዳ የቀበረ፤ ማን ይናገር የነበረ እንዲሉ፤ ገንዘን የቀበረን እኛ እያለን እንዴት ትጠራጠራለህ» ብለው ወደ መቃብሯ ሄደው መቃብሯን ቢከፍቱት ባዶ ሆኖ አገኙት፡፡ በዚህ ተደናግጠው ተያዩ፤ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ቶማስ «አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችን ተነሣች፤ዐረገች፤ ይኸው ምልክቱ» ብሎ ገንዘው የቀበሩበትን ሰበን አሳያቸው፤እነርሱም አምነው ሰበኗን ለበረከት ተካፈሉት፡፡

በዓመቱ ነሐሴ ፩ ቀን ሐዋርያት በመንፈሰዊ ቅናት ተነሳስተው «ቶማስ ትንሣኤዋን አይቶ እኛ ሳናይ እንዴት ይቀርብናል» በማለት ነሐሴ ፩ ቀን ሱባኤ ጀምረው በ፲፮ኛው ቀን የሐዋርያትን ሱባኤ ተቀብሎ እመቤታችንን መንበር ጴጥሮስን ተራዳኢ፣ ካህን እስጢፋኖስን ሠራዔ ዲያቆን አድርጉ ቀድሶ አቅርቧቸዋል፡፡ ከዚያ ጊዜ በኋላም ከነሐሴ ፩ እስከ ፲፭ ቀን  ጾመ ፍልሰታ ተብሎ ሁሉም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታይ ይጾመዋል፡፡ የጾሙና የትንሣኤዋ በረከት ተካፋይ ያድረገን፤አሜን

«ዕረፍተ ኅሊና»

                                                                                                                             

ዲያቆን ዮሴፍ በቀለ

እውነተኛ ዕረፍት በጎ ኅሊና ነው፤ ይውም ከእግዚአብሔር ጋር የሚያገናኝ ዘላለማዊ ዕረፍት ነው፤ክርስቲያን ዕረፍትን ለመፈለግ ሲል መከራ ሸሽቶ አይሔድም።ይልቁንም ስለ እግዚአብሔር መንግሥት ብሎ በሚደክመው ድካም ውስጥ እጅጉን ይደሰታል።በዚህ ወደ አምላኩ በሚወስደው መንገድ በመጓዝ በሚገጥመው ፈታኝ ጉዞ በሚደርስበት ሥጋዊ ድካም ውስጥ መንፈሳዊ ደስታ ያለበትን ምቾትን ያገኛል። ለዚህ ነው (ሲራክ ፮፥፳፫) ላይ «ልጄ ሆይ ስማኝ፤ በምክሬም ጽና፤ ምክሬን አታቃልል፡፡ እግሮችህን ወደ ቀንበርዋ አግባ፤ ዛንጅርዋንም ባንገትህ እሰር፡፡ጫንቃህን ዝቅ አድርገህ ተሸከማት። በእግር ብረትዋ አትበሳጭ፡፡ በፍጹም ነፍስህም ወደ እርሷ ተሰማራ፤ በፍጹም ኃይልህ መንገዷን ጠብቅ፤ ፍለጋዋንም ተከተል፤ ፈልጋት፤ ታገኛታለህም፤ በፍጻሜህም ዕረፍትን ታገኛለህ፤ደስታም ይሆንሃል»

የዳኞችን ፍርድ በገንዘብ ማስለወጥ ይቻላል፤ ኅሊና ግን ከዚህ ልዩ ነው፡፡ ማንንም የማይገባውን ቅጣት ቀጥቶ አያውቅም፤ አስፈጻሚዎቹ እጅና እግር እና ሌሎች አካሎቻችን ፍርዱን ስለሚያበላሹበት ከኅሊና ፈቃድ ውጪ አይንቀሳቀሱም፡፡ ኅሊናው ሁልጊዜ በሰው ላይ እንጅ በራሱ አልፈርድለት ካለ ይህ ሰው እንስሳ ሆኗል ማለት ነው፤ (መዝ. ፵፰÷፳)፡፡  «ሰው ግን ክቡር ሆኖ ሳለ አላወቅም፤ልብ እንደሌላቸው እንስሳትም ሆነ፤መሰላቸውም» ብሎናል፤ ቅዱስ ዳዊት ዕራቁቱን የሚሄደው ሰው መብዛቱ፤ ቅጥ የሌለው ኑሮ በብዙዎቹ ዘንድ እየተለመደ መምጣቱም የዚህ ምልክት ነው፡፡

የኑሮ ውድነት ዘወትር ሲወራ የኅሊና ዋጋ ክርስትና ከሆነ በብር ለምን ይለካል? የምግብ እጥረት ላጋጠማቸው ምግብ የሚያቀርብ ድርጅት ተመሠረተ፤ የኅሊና ዕረፍት ላጡ እና ሕሊናቸውን ሸጠው ሰውነታቸው መቃብር ለሆነባቸው ሰዎችስ ምን ይደረግ ትላላችሁ? እኔ ግን አንድ ነገር እላችኋለሁ፤ የአምላካችን ቅዱስ ቃል መቃብራትን ይከፍታል፡፡ መቃብር የሆነ ልቡናችሁን ይከፍት ዘንድ ቅረቡ፤ (ማቴ ፳፯፥፶፪)«መቃብሮችም ተከፈቱ፤ ተኝተው ከነበሩ ከቅዱሳን በድኖችም ብዙዎች ተነሡ፤ ይለናል” የሰው ልጅ በዓላማው፣ በአመለካከቱ፣ በመረዳት ችሎታው፣ በአኗኗር ዘይቤው፣ እንደሚለያይ ሁሉ በዓለም ሲኖር የሚገጥሙትን ሥጋዊና መንፈሳዊ ችግሮች የመቋቋምና በትክክለኛ መንገድ የመጓዝ ችሎታውም ይለያያል፡፡ ሰዎች ለነገሮች የሚኖራቸው እይታ የተለያየ ነው፡፡ አንዳንዱ የሚገጥሙትን ተግዳሮቶች ቀለል አድርጎ ሲመለከታቸው ሌላው ደግሞ በጣም አክብዶና አጋኖ ሊመለከታቸው ይችላል፡፡ ሁለት ሰዎች አንድን ተመሳሳይ ክስተት የሚመለከቱበት ወይም የሚረዱበት መንገድ እንደሚለያይ ሁሉ የሚፈቱበት መንገድም ይለያያል፡፡ ለምሳሌ ተመሳሳይ የኢኮኖሚ ደረጃ ያላቸው ሁለት ሰዎች ከሥራ ቢሰናበቱ አንደኛው መታገሥን መርጦ የነገን ሲያልም ሌላኛው ግን ጨለማ ውስጥ እንደገባ መሥሎ ሊታየው ይችላል፡፡የአእምሮ ውጥረትን የመቋቋም ችሎታ በአጭር ጊዜ የሚመጣ ክሂሎት ሳይሆን በረጅም ጊዜ ልምምድ የሚመጣ ክሂሎት ነው፡፡

በኤልያስ ዘመን ፫ ዓመት ከመንፈቅ ሰማይ የነጠፈው ምድርም የተራቆተው (፩ ነገ.፲፯፥፩)፤ በሌላም ጊዜ ውሃን በማዝነም ፈንታ እሳትን እና ዲንን ያዘነመው (ዘፍ.፲፱፥፳፬፣፪፣፳፩፥፲፪)፤ በንጉሥ ሕዝቅያስ ዘመን በለኪሶን ሜዳ በአንድ ሌሊት አንድ መቶ ሰማንያ አምስት ሽህ ሬሳ የተገኘው(ኢሳ.፵፯፥፵፮) በሞዓብ ሜዳ ከነበረው ሕዝብ መካከል ፳፫ ሺህ ሬሳ በአንድ ቀን የተገኘው (፩ ቆሮ.፲፥፰) የሰው ልጅ ድንበር በማፍረሱም አይደል?

ዛሬስ ምድር በሰቆቃ የተሞላች መሆን፤ ለዓለማችን ፈውስ በሌለው ቁስል መመታትና በረከት ማጣት ተጠያቂው ማን ይሆን? ምን አልባት በአእምሮአችን ሌላ መልስ አስቀምጠን ይሆናል እንጅ ክፉውም ሆነ ደጉ ነገር የሥራችን ውጤት ነው፡፡ የፈርኦን ባሪያዎች በግብፅ ለተቃጣው መቅሠፍት ሁልጊዜ ተጠያቂ የሚያደርጉት ሙሴን ነበር እንጅ አንድም ቀን ይህ የኃጢአታችን ደምወዝ ነው ብለው አያውቁም(ዘፀ.፲፥፯)

ዛሬም ያለው ትውልድ ለአየር ንብረት መዛባት በኢንዱስትሪ የበለጸጉ ሀገራትን ለታናናሽ ሀገራት የጦርነት ቀጠና መሆን፤ ኃያላን መንግሥታት ለድኃ ሀገራት አለመበልጸግ ቅኝ ገዥዎችን ምክንያት ማድረግ ልማዱ ነው(የእኛ ለእነርሱ የክፋት ድርጊት ራሳችንን አመቻችተን ማቅረባችንን አናስተውልም)፡፡ የሆነብንን ሁሉ እንደ ነቢይ አምነን ለምንቀበል ሰዎች ስለ ኃጢአታችንና ስለ በደላችን ይህ ሁሉ ሆነ ሳለ ያለ ሕግ የሚበድሉ ሁልጊዜም ያለሕግ ይቀጣሉና(ዳን. ፱፥፲፮-፲፯)፤

ይህን ገጽታውን በግልባጩ የተመለከትነው እንደሆነ ደግሞ ምድረ በዳ የሌለው የአጋንንት ማረፊያ ነው፤ (ማቴ. ፲፪፥፵፫) በጾም እና በጸሎት ከሰው ልጆች እንዲወጡ የተገደዱ አጋንንት ወደ ምድረ በዳው ይሰማራሉ፤ ማረፊያ የሌለው በመሆኑ ግን ተመልሰው ወደ መጡበት ቤት ይገባሉ፡፡ በእርግጥ አሁንም የሚሸጋገሩት ከምድረ በዳ ባዶ ወደሆነ ቤት ነው፡፡ ይህ ለእነርሱ ምቹና ባዶም በመሆኑ አጋንንት ያድሩበታል፡፡ የሥጋ ፍሬን ብቻ ስለሚያፈሩ የመንፈስ ፍሬን ረስተውታልና ስለዚህ ያድሩበታል፡፡ ሰው በገዛ ፈቃዱ ሕይወትን ትቶ የኮበለለ ቢሆንም እግዚአብሔር ግን በሞት ወደ ተቀጣው የሰው ልጅ መጣ፡፡ የደከመውን የሰው ልጆች ባሕርይ ሊያበረታ መንገድ ከመሔድ ደክሞ ሊያርፍ ተቀመጠ ፤ ድካም ሳይኖርበት የሚታየውን እና የማይታየውን ዓለም የፈጠረ አምላክ ዛሬ ግን አዳምን ሊያድነው ወዶ ወደዚህ ዓለም ሲመጣ ለባሕርዩ የማይስማሙ ድካምና ሕማም የቃል ገንዘቦች ሆነው ተነገሩ፡፡«ኢየሱስም መንገድ ከመሄድ ደክሞ በጉድጓድ አጠገብ ተቀመጠ» (ዮሐ.፬፥፮) ተብሎ ለኃያሉ አምላክ ሲነገርለት እንደምን ይገርማል፡፡ መላእክትን ያለ ዕረፍት ሌሊት እና ቀን እንዲያገለግሉ ኃይል የሆናቸው ጌታ እኮ ነው (ራዕ.፬፥፰) ዛሬ ግን ደከመ፤ በእርሱ ድካም ፍጥረት እንዲበረታ ይህ ሁሉ ሆነ፡፡ ያውም ጊዜው ቀትር ነበር፤ የሚያቃጥል ፍጥረት ሁሉ ጥግ ፍለጋ እንዲሸጐጥ የሚያደርግ አስቸጋሪ ሰዓት!ማንም ሰው በኃጢአቱ እንዲሞት የእግዚአብሔር ፈቃድ አይደለም። (ሕዝ. ፲፰፥፴፪)

ክርስቲያን በእምነት ሕይወት ውስጥ ዕረፍትን ያገኛል እንዳለን ነቢዩ ኤርምያስ ፮፥፲፮ ላይ «በመንገድ ላይ ቁሙ፤ ተመልከቱ፤ የቀደመችውንም መንገድ ጠይቁ፤ መልካሚቱ መንገድ ወዴት እንደሆነች ዕወቁ፤በእርሷም ላይ ሒዱ፤ ለነፍሳችሁ ዕረፍትን ታገኛላችሁ»። እንዳለ እውነተኛ ዕረፍት የሚገኘው ከእግዚአብሔር ስለሆነ እኛም ወደ እርሱ በመቅረብ የማያቋርጥ ዕረፍትን እናገኛለን፡፡ እንዲሁም ለምናከናውነው ሥራ ሁሉ ስልቹ አንሆንም፤  ምክንያቱም የምናመልከው አምላክ ዘለዓማዊ ዕረፍትን ስለሚሰጠን ሥራን ሙሉ ለሙሉ በማቆም ማረፍ ሳይሆን መሰላቸትን በማቆም መንፈሳዊ ሥራንና ማኅበራዊ በጎ ሥራ በማከናወን ማረፍ ማለት ነው።

ልዑል እግዚአብሔር ሰውን ከፈጠረበት ጊዜ ጀምሮ በሥርዓትና በሕግ እንዲመራ አድርጎታል። ለአኗኗሩ ሥርዓት አበጅቶለት ፍጥረታትን እንዲገዛ አዞና ሥልጣን ሰጥቶት በገነት እንዳስቀመጠው እውነት ነው። ስለሆነም የእግዚአብሔር ሕግ ስንልም ከእግዚአብሔር ፈቃድ የመነጨ፣ በእግዚአብሔር የተሰጠ፣ አምላካዊ ድንጋጌ ነው። በመጽሐፈ ሔኖክ ፲፱፥፳፪ ላይ የሰው ልጅ እንደ ንጹሐን መላእክት ሃይማኖቱን አውቆና ጠብቆ ፈጣሪውን በመፍራትና በማምለክ እንዲኖር ነው። በመዝሙር ፩፥፪ ላይ፤ «የእግዚአብሔር ሕግ ብቻ ፈቃዱ የሆነ፤ ሕጉንም በቀንና በሌሊት የሚያስብ፤ እርሱም በውኃ ፈሳሾች ዳር እንደተተከለች፤ ፍሬዋን በየጊዜው እንደምትሰጥ፤ ቅጠሏ እንደማይረግፍ ዛፍ ይሆናል፣ የሚሠራውም ሁሉ ይከናወንለታል»

አስተውል! ያንተ ሕይወት ማለት እኮ እስከ ሞት የሚፋለም ባለቤት ያላት የናቡቴ ርስት ናት፡፡ ሕይወትህ በተቃራኒው የቆመች ምድረ በዳ ብትሆንብህም እንኳ አትፍራ፤እግዚአብሔር የምድረ በዳውም ፈጣሪ ነውና ለአርባ ዘመናት የመራውን ሕዝብ የውርጭ መና ከደመና አውርዶ የመገባቸው፤ውኃውንም ከዐለት ላይ አፍልቆ ያጠጣቸው፤ በምድረ በዳ መሆኑን አትርሳ፤ (መዝ ፸፯፥፳-፵) አንተም መናና ውኃ የተባለ የእግዚአብሔር ቃል ተመግበህና ጠጥተህ ምድረ በዳ የሆነ ሕይወትህን ልታለመልምበት ይገባል፡፡ ትናንት ከትምህርት ምድረ በዳ የነበረችውን የእነ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫን ሕይወትና የእነ ቅዱስ ያሬድን ሰውነት በልብህ ተመልከታት፤ትውልድ በልቶ የማይጨርሰው የዘለዓለም ስንቅ ተገኝቶባታልና፡፡

 

ወጣትነትና ፈተናዎቹ

የወጣትነትን የዕድሜ ክልል በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አስተምሮ መሠረት ከሃያ እስከ ዓርባ ዓመት ያለው ዕድሜ ነው፡፡

እንደሚታወቀው የሰው ልጅ ተፈጥሮ ከአራቱ ባሕርያተ ሥጋ ማለትም ከነፋስ፤ ከእሳት፤ ከውሃና፤ ከመሬት ሲሆን አምስተኛ ነፍስን ጨመሮ እነዚህ በአንድ ሰው የሕይወት ዘመን ላይ ሲንጸባረቁ ይኖራሉ፡፡ የሰው ልጅ በሚሞትበት ጊዜ አራቱ ባሕርያት ወደነበሩበት ጥንተ ህላዌ ይመለሳሉ፡፡ በዚህ ጊዜ ሥጋ ይበሰብሳል ይፈርሳል፡፡ በትንሣኤ ዘጉባኤ ደግሞ አራቱም ባሕርያት ከነፍስ ጋር እንደገና  ተዋሕደው ይነሣሉ፡፡ አራቱን ባሕርያተ ሥጋ ረቂቃን ግዙፋን (ክቡዳን ቀሊላን) ብለን እንጠራቸዋለን፡፡ የሚገርመው ክቡዳኑን ከላይ ቀሊላኑን ከታች አድርጎ ነው ያስቀመጣቸው፡፡ እርስ በእርሳቸው ተጠባብቀው እንዲኖሩ አደረጋቸው ምክንያቱም ክቡዳኑ ከላይ ሆነው እንዲጠብቋቸው ነው ቀሊላኑ ግን ከላይ ቢሆኑ ኖሮ ሽቅብ ይሄዱ ነበር ክቡዳኑም ከታች ቢሆኑ ኖሮ ቁልቁል ሲሔዱ በኖሩ ነበር፡፡ ተሸካክመው የሚኖሩት ምሳሌነቱም አራቱ ባሕርያተ ሥጋ ተቻችለው እንደሚኖሩ እኛም ከኛ በላይ ያሉ እንዳሉ በማወቅ ተቻችለን እንድንኖር ነው፡፡ የመሬት መሠረቷ ጽናቷ ነፋስ ነው፡፡ የእኛም ከላይ ሥጋችን መሬት ነው፡፡ መሬትም በውኃ ላይ ናት ይህም ውሃው ደማችን ነው፡፡ የእኛም ሥጋችን በደማችን ነውና የሚጸናው የውሃዎች ሕይወት ነፋስ ነው ውሃው ንጹሕ አየር ከሌለው ይበከላል፡፡ አበው ከአፋፍ ላይ ነፋስ ከአፍ ላይ እስትንፋስ እንዲሉ የሰው ልጅም ሁሉ በዘመኑ ሲተነፍስ ይኖራልና፡፡ የሰው ልጅ የሰውነት ሙቀት ባሕርየ እሳት ለመኖሩም በቂ ማስረጃ ነው፡፡

ከሃያ እስከ አርባ ያለው የዕድሜ ክልል የእሳት ባሕርይ ጎልቶ የሚታይበት ነው፡፡ ይህም ዘመነ እሳት ወይም ምግበ እሳት ይባላል፡፡ ይህም ሰውን ወጣት የሚያሰኘው ዘመን ነው፡፡

በዚህ የወጣትነት ዘመናችን ጥሩና ታላቅ መሆን ካልቻልን የምናጣው ክብርን ብቻ ሳይሆን ማንኛውንም ኃላፊነት ጭምር እናጣለን፡፡ እንደ ኤሳው ስንሆን እንደ ያዕቆብ ያለ ታናሽ ወንድምህ ብኵርናህን ይወስድና አንተ የእሱን እጅ ስታይ ትኖራለህ፡፡ እንዲሁም ታናናሾችህን የመቅጣትና የመገሠጽ መብት አይኖርህም፡፡ አላዋቂ ጎልማሳ ወጣቶችን መገሠጽ እንደማያምርበት ሁሉ አንተ ሕገ ወጥ ወጣት ሆነህ ታናናሾቼን ልቅጣ ልምከር ብትል ማንም አይሰማህም፡፡ ምክንያቱም (ማቴ. ፯፥፭) ላይ አንተ ግብዝ አስቀድመህ ከዓይንህ ምሰሶውን አውጣ፡፡ ከዚያ በኋላ ከወንድምህ ዓይን ጉድፉን ታወጣ ዘንድ አጥርተህ ታያለህ ስለተባልን ይህ በእንዲህ እንዳለ የሰው ልጅ ከልጅነት ወደ ወጣትነት በሚሸጋገርባቸው ወራትና ዓመታት አካላችን እንደሚደራጅና አእምሮአችን እንደሚዳብር ሁሉ ምኞታችንም በዓይነትና በመጠን እየሰፋና እየጨመረ ይሄዳል፡፡ ይህ የወጣቶች ምኞት በአመዛኙ ከመንፈሳዊነት ጋር የሚቃረን ይሆናል፡፡ እንዲሁም በጎልማሶች ላይ የሚከሰተውን ምኞት አስመልክቶ ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ (በ፪ኛ ጢሞ. ፪፥፳፪) ላይ ከክፉ የጎልማሳነት ምኞት ግን ሽሽ ብሎናል፡፡ በእርግጥም በወጣትነት ዘመን የሚገኝ ምኞት እጅግ ክፉ ነው ወጣትነት የሚሠራበት ዘመን እንጂ ክፉ ምኞት የሚመኙበት ዘመን አይደለም፡፡

ወጣቶችና ጾሮቻቸው (ፈተናዎቻቸው)

ሐዋርያው ቅዱስ ያዕቆብ በመልእክቱ ፩፥፲፬ ላይ «ሰው ራሱ በገዛ ምኞቱ ሲሳብና ሲታለል ይፈተናል» በማለት እዳስተማረን፤ በወጣትነት ዘመን የሚገኝ ምኞት ከመጠን በላይ ወደ ጥፋት የሚስብ የሚጎትትና የሚያታልል ነው፡፡ በተለይ ሰው በገዛ ምኞቱ ሲሳብ በወጣትነት ዘመን ምንም አእምሮው የበሰለ ቢሆንም እንኳ ራሱን መግዛት ካልቻለ በብዙ ነገር ይፈተናል በዚህም ወጣቶች ከሚፈተኑባቸው መንገዶች መካከል ዝሙትና ትውዝፍት (የምዝር ጌጥ) መውደድ ነው፡፡ እንዲሁም የወጣቶች ልዩ ልዩ ጾር (ፈተና) ቢኖሩም እነዚህ ዐበይት ጾሮች የኃጢአት መንገድ ጠራጊ ይሆናሉ፡፡

መፍትሔዎች

  • ራስን መግዛት

ይህ ማለት ፍቃደ ሥጋን ለፍቃደ ነፍስ ስናስገዛ፤ በዚህም ሕገ እግዚአብሔርን ስንጠብቅ፤ ራሳችንን ሆነን በተማርነው መኖር ስንጀምር፤ ልማድ የሆነብንን ድርጊት አስወግደን በተቀመጠልን ትእዛዝ ስንኖር እና ሁለንተናችንን ለእግዚአብሔር ስናስገዛ ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት (በመዝ. ፪፥፩) ላይ በፍርሀት በመንቀጥቀጥ ተገዙ ስላለን በመገዛት ውስጥም የማያቋርጥ ዘለዓለማዊ ደስታ እንዳለ አውቀን ራሳችንን መስለን መኖር እንችላለን፡፡ ስለዚህ ነው ቅዱስ ጳውሎስ ለመንፈስ ልጁ ለጢሞቴዎስ (፩ኛ ጢ. ፫፥፭) ላይ ቤቱን ማስተዳደር የማይችል የእግዚአብሔርን ቤት ሊመራ እንደማይችል ሁሉ ሌሎችን ማስተዳደር የምንችለው ራሳችንን ስንገዛ፤ ስንገራና ስንቆጣጠር እንደሆነ ነግሮናል፡፡ እንዲሁም ኖኅን ስንመለከት (ዘፍ. ፮፥፩) ላይ ከነቤተሰቡ ራሱን ገዝቷል፡፡ ሌሎችን ለመናገርና ለመውቀስ መርከቧን በመሥራት፤ አራዊትን፤ እንስሳትንና አዕዋፍን ሁሉ መግዛት ችሏል፡፡ ራስን መግዛት ማለት ቤተ ክርስቲያን ገብተን እስክንወጣ፤ ትዳር እስክናገኝ፤ ሥራ እስክንይዝና እና የፈለግነው ነገር ሁሉ እስኪሳካልን ድረስ አይደለም፡፡ ነገር ግን ራስን መግዛት ማለት መፍረድ ሲቻል አለመፍረድ፤ ማድረግ ሲቻል አለማድረግ ልክ እንደ ዮሴፍ (ዘፍ. ፴፱፥፩) ጀምሮ ሁሉ ሲቻል መተው እንዲሁም ልክ ይሁን አይሁን በነገሮቻችን ሁሉ ራሳችንን ስንገዛ በአጠቃላይ ከአላስፈላጊ የሥጋ ጠባይዓት ሁሉ መራቅ ስንችል ራሳችንን ገዝተናል ማለት እንችላለን፡፡

  • ራስን ማወቅ

ለራሳችን ያለንን አመለካከትና ጠባይ በአጠቃላይ ከሌሎች ሰዎች የሚለየንንና የሚያመሳስለንን ማንነት በመረዳት በዓላማ መኖር ስንችል ራሳችን ማወቅ ቻልን ማለት ነው፡፡ ይህም ሰው ጠንካራና ደካማ ጎኑን ማወቅ ከቻለ በሥጋዊና በመንፈሳዊ ሕይወት አዎንታዊ አስተዋጽዖ ለማበርከትና ዓላማውን ከግቡ ለማድረስ የሚያስችለውን እውቀት ያገኛል፡፡ ሙሴ (በዘፀ. ፬፥፲) ላይ ጌታ ሆይ እኔ አፌ ኮልታፋ ምላሴም ጸያፍ የኮነ ሰው ነኝ ብሎ ነው የተናገረው፡፡ ሆኖም ሙሴ በውስጡ ያለውን ጠንካራ ጎን አልተመለከተም፡፡ ራሱን የሚያውቅ ሰው ለራሱ ሕይወት ኃፊነት ይወስዳል ሌላ ሰው እንዲንከባከበው አይጠይቅም፡፡ በጉብዝናው ወራት ገደል አለ ከተባለ ይሰማል፤ ገደሉ እንደሚጎዳው ስለሚያውቅ፤ ሕይወቱን ለአደጋ አያጋልጥም፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ በመልዕክቱ (፪ኛ ጴጥ. ፩፥፭-፮) ላይ በእምነታችሁ በጎነትን ጨምሩ፤ በበጎነትም እውቀትን፤በእውቀትም ራስን መግዛት፤ ራስን በመግዛትም መጽናትን በመጽናትም እግዚአብሔርን መምሰልን ነግሮናልና፡፡ ስለዚህ ይህን በማድረግ ለሕይወታችን ኃላፊነትን እንወስዳለን፡፡

ራሱን የሚያውቅ ሰው ሰብእናውን ያከብራል፤ ለምን ዓላማ እንደተፈጠረ በመረዳት ሰብእናውን ጠብቆ በደስታ ይኖራል፤ በራሱም ይተማመናል፡፡ የሚያውቀውን በአግባቡ ይናገራል፤የማያውቀውን ይጠይቃል፤ ድክመቱን ሲነግሩት በአዎንታዊ መንገድ ይቀበላል፤ ማንነቱን በቦታና በጊዜ ራሱን አይለዋውጥም የጸና ግንብ ነው፤ በዐለት ላይ ተመሥርቷልና፡፡ ከሐሜት ይርቃል፤ በግልጽ መወያትን ያዘወትራል፤ ለውድቀቱም ራሱን ተጠያቂ ያደርጋል፤ ሌሎቹን ተጠያቂ አያደርግም፤ ለውድቀት በቀላሉ እጁን አይሰጥም የሚጓዝበትን ያውቃልና፡፡ ካለፈው የወጣትነት ሕይወቱ ልምድ በመውሰድ አሁን ያለበትን ሁኔታ በመረዳት ሥጋዊና መንፈሳዊ ሕይወቱ ወዴት ሊያመራ እንደሚችል አስቀድሞ ይዘጋጃል፡፡ ይህም የዛሬ ማንነቱ ለነገ ዘለዓለማዊ ሕይወቱ መሠረት መሆኑን በመረዳት ጠንክሮ በመንፈሳዊ ሕይወቱ ይተጋል፡፡ በመጨረሻም ራሱን የሚያውቅ ወጣት ለመንፈሳዊ ሕይወቱ መሳካት አስፈላጊውን መሥዋዕትነት ይከፍላል፡፡ ራሱን ያላወቀና ያልገዛ ወጣት ዓላማውን ይስታል፤ ለራሱም ለሌሎችም መሆን አይችልም፡፡

ስለዚህ በወጣትነት ዘመናችን ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚያቀርበንን እንጂ የሚያርቀንን ነገር እንድንሠራ አይጠበቅብንም፡፡ እኛ ራሳችንን አድነን ሌሎችን በማዳን ክርስቲያናዊ ግዴታችንን መወጣት ይጠበቅብናል፡፡

ስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ከሰኔ ፩-፲፭ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም

ክርስቲያናዊ ሕይወት

ዲያቆን ዮሴፍ በቀለ

በክርስቲያናዊ ሕይወት ውስጥ መልካም ሥራ ሁልጊዜ ይኖራል፤መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ   በትምህርተ ወንጌል እንዳስተማረን  ድኅነትን የምናገኝው በሕገ እግዚአብሔር ጸንተን ስንኖር እንደሆነ ነግሮናል። የሰው ሕይወቱ የጸጋ ነው፤ በፈቃዱ በሁለት ሞት ነፍሱን/ሕይወቱን/ ይነጠቃል፡፡ የመጀመሪያው ሞት የማይቀር ሲሆን የሁለተኛው ሞት ግን በሕገ እግዚአብሔር ለልደተ ነፍሳት የተሰጠ ነው፤ ራዕ. (፪፥፲፩)፤ ሕያው የሆነ ሰው እንጂ ሕይወት የሆነ ሰው የለምና፡፡

ስለሆነም ለዘለዓለም በሕይወት ለመኖር ይቻለን ዘንድ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ምድር ላይ በቆየበት ጊዜ ያደረገውን ተአምር፤ ያስተማረውን ወንጌልና  ለእኛ የገለጸልንን ፍቅር መሠረት አድርገን መመራት ይጠበቅብናል። ይህንንም በተግባር ለመፈጸም የሚከተሉትን ምግባሮች ማከናወን አለብን፡፡

፩.አገልግሎት

ከሁሉም አስቀድሞ የሰው ልጅ ዕለት ዕለት ፈጣሪውን ሊያመሰግን ይገባል፤ ይህም መጸለይ፤መጾም፤ማስቀደስና መዘመር ይገባዋል፡፡ ከዚህም ባሻገር ነዳያንን ማብላትና ማጠጣት በጉልበትና በሙያ አድባራትን ማሰራት ከአንድ ክርስቲያን የሚጠበቅ ሲሆን አሁን አሁን ግን የምንመለከተው እንደዚህ አይደለም፡፡ የዛሬ ፲ ዓመት ሰንበት ተማሪ የነበረው ልጅ ከዓመት በኋላ የመድረክ ዘፋኝ ይሆናል፤ የዛሬ ፭ ዓመት ሰንበት ትምህርት ቤት ድራማ ይሰራ የነበረው ሰው በኋላ ተለውጦ ሌላ ታሪክ ውስጥ ይገባል፡፡ የሰንበት ትምህርት ቤት ሰብሳቢ፤ ጸሓፊና አባል የነበረው፤ ሚስት ሲያገባ ያንን ሁሉ እርግፍ አድርጎ ይተወዋል፤ ትዳር እኮ የአገልግሎት ጡረታ አይደለም፤ አንዴ ካገቡ አይመለሱም፡፡

ሰንበት ተማሪ ሆኖ ቤተክርስቲያንን እያገለገለ እስከ ሕይወቱ መጨረሻ ዘማሪ፤ ካህን፤ ዲያቆን ወይም ሰባኪ ሆኖ ገዳማትን እያሰራ፤ ነዳያንን እያበላ፤ ጉባኤ እያዘጋጀ፤ ጽዋ ማኅበራትን እየመራና ወዲህ ወዲያ ሳይል፤ ታመምኩ፤ ተቸገርኩ፤ ምስጋና ቢስ ነኝ፤ እጄን በቆረጠው ሳይል የሚኖር ማን ነው? አንዳንዶች ደከምን ብለው አገልግሎትን  የሚተው አሉ፡፡ ታማን ብለን የምንተውም አለን፤ ይህቺን ካልታገስን ታዲያ ስለ ዲዮቅልጥያኖስ ዘመን ለምን እናወራለን? እስከ መጨረሻው የትኛው ሰው ነው የሚጸናው? በክርስቲያናዊ ሕይወት እስከ መጨረሻዋ ዕለት መጽናት ያስፍልጋል፡፡

.ጊዜን ማክበር

ጊዜ ከእግዚአብሔር የተሰጠን ስጦታ ነው፤ እናም በአግባቡ ልንጠቀምበት ያስፈልጋል፡፡ ጉባኤ ላይ በመገኘት፤ ሰንበት ትምህርት ቤት ውስጥ በማገልገል፤ ድሆችን በመጎብኘት፤ ሕመምተኞችን በመጠየቅ፤ ገዳማትንና አድባራትን ለማሰራት በመድከም፤ መምህራኑ ሲያስተምሩና መዘምራኑ ሲዘምሩ በማገልገል ጊዜን ማክበር ያስፈልጋል፡፡ በማቴዎስ ወንጌል  (፳፭፥፴፬-፴፮) ላይ እንደተገለጸው «እናንተ የአባቴ ቡሩካን፤ ዓለም ሳይፈጠር የተዘጋጀላችሁን መንግሥት ትወርሱ ዘንድ ኑ። ተርቤ አብልታችሁኛልና፤ተጠምቼም አጠጥታችሁኛልና፤ እንግዳም ሆኜ ተቀብላችሁኛልና፡፡ ታርዤ አልብሳችሁኛልና፤ ታምሜም ጎብኝታችሁኛልና፤ ታስሬም ወደ እኔ መጥታችሁ  ጠይቃችሁኛልና» ይለናል።

መጠቀም ያለብን ትርፍ ጊዜያችንን አይደለም፤ ያለንን ጊዜ መስጠትና ሙሉ ጊዜን መስጠት ይለያያሉ፤ በወንጌል እንደተጠቀሰው አንድ ሰው ከሞላው ከኪሱ አፈሰና ሰጠ፤ አንዲት  ምስኪን መበለት ደግሞ ሁለት ሳንቲም ነበራትና እሱን ሰጠች፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእነዚህ ሰዎች ሁሉ ይህቺ ጸደቀች አለ፡፡ በሉቃስ ወንጌል (፳፩፥፫-፬) ላይ እንደተናገረው «እውነት እላችኋለሁ፥ይህቺ ደሃ መበለት ከሁሉ ይልቅ አብዝታ ለእግዚአብሔር መባ አገባች፡፡ እነዚህ ሁሉ ከተረፋቸው ለእግዚአብሔር መባ አግብተዋና፤ ይህች ግን ከድህነቷ ያላትን ጥሪቷን ሁሉ አገባች»፡፡ካለን እንድንሰጥ ነው እንጂ ሲተርፈን፤ ሥራ ሠርተን፤ በልተን፤ ጠጥተን፤ተዝናንተን ስንጨርስ መጨረሻ ላይ የት ልሂድ ብለን ቤተክርስቲያን የምንሄድ ከሆነ ይህ ለጊዜ ዋጋ መስጠት አይደለም፡፡ በጊዜያችን ተጨማሪ ልንሰራበት የምንችለውንና ገንዘብ የምናገኝበትን፤ ሰው ቤት ሄደን ጥዑም ምግብ ተመግበን የምንጠጣበትን ጊዜ ሰውተን፤ እንደ አስፈላጊነቱ ስንሰጥ ለጊዜ መሥዋዕት አደረግን ይባላል፤ሲተርፍ መስጠት ዋጋው ትንሽ መሆኑን ወንጌልም ነግሮናልና፡፡

፫. በሃይማኖት መጽናት

በዮሐንስ ራእይ ፲፪፥፲፮-፷ እንደተጠቀሰው ዘንዶው በሴቲቱ ላይ ተቆጥቶ የእግዚአብሔርን ትእዛዛት የሚጠብቁትን የኢየሱስ ምስክር ያላቸውን ከዘሯ የቀሩትን ሊወጋ ሄደ ይላል፡፡ ከዘሯ የቀረነውን የኢየሱስ ክርስቶስ ምስክርነት ያለንን ሊዋጋ ከተነሣው ዘንዶ ጋር ታግሎ ሃይማኖትን መጠበቅ ተገቢ ነው፤ በዚህ ዘመን ሃይማኖት ጸንቶ ሃይማኖትን መጠበቅና ከመናፍቃን ጋር መዋጋት የክርስቲያን ኃላፊነት ነው፤ ይሁዳ (፩፥፫) «ለቅዱሳን የተሰጠችውንም ሃይማኖት ትጋደሉላት ዘንድ አማልዳችኋለሁ» ይላል።

ስለ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መጋደል ክርስቲያናዊ ምግባር ነው፤ ብዙዎቹ ዛሬ በገንዘብና ከንቱ በሆነ ነገር ይታለላሉ፤ ቅዱስ ጳውሎስ እንደተናገረው «ለዚህ ዓለም ስሕተት፥ በክርስቶስ ሕግ ያይደለ፥ በሰው ሠራሽ ሥራዐት ለከንቱ የሚያታልሉ ሰዎች በነገር ማራቀቅ እንዳያታልሉአችሁ፥ተጠንቀቁ» (ቈላ. ፪፥፰)፡፡ በሰይጣን በመታለል ሃይማኖታቸውን የሚለውጡ አሉ፤ ጌታችን በማቴ. (፳፬፥፲፫) ላይ «እስከ መጨረሻው የሚታገሥ ግን እርሱ ይድናል» ብሏል፡፡

፬.እራሳችንን ከፍትወት መጠበቅ

 ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ በዚህ ዘመን ራሳችን ከዚህ ዓለም ፍትወት መጠበቅ  እንዳለብን አሳስበለዋል፡፡ አሁንኮ እስከ ጋብቻ ድረስ በድንግልና መጽናት ከባድ ሆኖብናል፤ የ «መ» ሕጎች እየተባለ በትምህርት ቤቱ ሁሉ መከራ የሚበላው ይህን ሕግ እየረሳን ነው፡፡ ልክ የዚህን ዓለም ፍትወት መቻል በእሳት ውስጥ ማለፍ እንደሆነ፤ ፍትወት ራሱን የቻለ እሳት ነው፤ እሳት እንኳን የቀረበውን የራቀውን ይጠራል፡፡ አባቶቻችን «እሳት ይጠራል»  ይላሉ፤ እኛ የምንኖረው በዓለም ነው፡፡ ስለዚህ ለምን በኅሊናችን የፍትወት ስሜት መጣ? ለምን በዙሪያችን ኃጢአት ኖረ? ማለት አንችልም፤ ግን ወንዙን አቋርጠን ማለፍ እንችላለን፤  ራስን በንጽሕና መጠበቅም አለብን፡፡ ወንድና ሴት ራሳቸውን ከዝሙት ስሜት ጠብቀው ሲኖሩ፤ በቤተክርስቲያን በተክሊል ሲጋቡ አክሊል ይጫንላቸዋል፤ ቤተ ክርስቲያን አክሊል ላደረገችለት ሰው ደግሞ እግዚአብሔር እጥፍ ዋጋን እንደሚከፍል ቅዱሳት መጻሕፍት ላይ ተጽፏል፡፡ እነዚህ ሰዎች እድል ወይም ምድራዊ ጥቅም ሳይኖራቸው ቀርቶ አይደለም፤ ነገር ግን ምድራዊ ፍላጎታቸውን በመግታት ከራሳቸው፤ ከጓደኞቻቸውና ከአካባቢያቸው ጋር በመታገል ለነፍሳቸው መሥዋዕት ለመክፈል ስለሚሹ ነው፡፡

፭. በትዳር መጽናት

 በክርስቲያናዊ ሕይወት ውስጥ አንድ ወንድ በአንዲት ሴት፤ አንዲት ሴት በአንድ ወንድ ጸንተው ይኖራሉ፡፡ ባልና ሚስት በመቻቻል በሰላም መኖር ከቻሉ፤ ሰው የራሱን፤ የአጋሩንና የልጆቹን ጠባይ ችሎ በትዕግሥት ከኖረ፤ ሥጋ ወደሙን ተቀብሎም፤ በሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን  እግዚአብሔርን የሚያገለግል ከሆነ ክርስቲያን ይባላል፡፡ በምንኩስና ሳይወሰኑ ወይም በትዳር አንድ ሳይሆኑ እንዲሁ የሚኖሩ ሰዎች ክርስቲያናዊ ሕይወትን የማይሹ ሰዎች ናቸው፤ ልክ በዘመነ ሰማዕታት ጊዜ እንደነበሩ ለጊዜው ክደናል እንደሚሉት አይነት ናቸው፡፡ ፶ እና ፷ ዓመት በትዳር እየኖሩ የብር፤ የወርቅ፤ የአልማዝና ኢዩቤልዩ የሚያከብሩ ሰዎች ተመችቷቸው እንዳይመስለን፤ ብዙ የችግር ጊዜን አሳልፈው ሊሆን ይችላል፤ እግሬን በሰበረው፤ ምላሴን በቆረጠው፤ አይኔን በሰወረው፤ ብር ብዬ በጠፋው ያሉበት ጊዜም ይኖራል፤ ግን ያን ሁሉ አልፎ መጽናት ያስፈልጋል፡፡

በትዳር ያላችሁ እስከመጨረሻው እንድትጸኑ፤ንጽሕናችሁን ጠብቃችሁ በመዘምርነት የምታገለግሉ፤ በስብከት፤ ለአድባራትና ገዳማት ያላችሁን እየመጸወታችሁ ከቁርሳችሁ ቀንሳችሁ፤ ሁለት ጫማ ካላችሁ አንድ ጫማ፤ ሁለት ልብስ ካላችሁ አንዱን እየለበሳችሁ፤ እኛ ይቅርብን፤ አባቶቻችን ተርበው ከተማ ለከተማ ሲንከራተቱ አንይ ብላችሁ የምታገለግሉ፤ የምታስታርቁ አባቶች፤ የጠፉትን ፈልጋችሁ የምታመጡ፤ መናፍቃንን ተከራክራችሁ የምታሳምኑ፤ አሕዛብን ወደ ጥምቀት የምታመጡ ሰዎች ሁሉ እስከ መጨረሻው ጸንታችሁ፤ ጸንተን፤ ኑ «የአባቴ ብሩካን ዓለም ሳይፈጠር የተዘጋጀላችሁን ርስት ውረሱ» እንድንባል የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን፤አሜን፡፡