‹‹ጥልንም በመስቀሉ ገደለ›› ኤፌ.፪፥፲፮

የዓለም ሰላም የተሰበከውና የተረጋገጠው በመስቀል ላይ በተደረገው የክርስቶስ ቤዛነት ነው፡፡ ለዚህም ነው ሐዋርያው ‹‹ጥልን በመስቀሉ ገድሎ ርቃችሁ ለነበራችሁ ሰላምና የምሥራችን ሰበከ›› ያለው….

መስቀል

መስቀል ነገር በመጀመሪያ የተገለጸው በመላእክት ዓለም ነበር፡፡

መስቀል የሰላም መሠረት ነው

መስቀል  የሰላም መሠረት፤ ሰላምም የመስቀል ፍሬ ነው፡፡ በግእዝ ሰላም የሚለው ቃል ትርጉም ‹‹ፍጹም ጤና፣ ዕረፍት፣ እርቅ፣ ሰላምታ፣ የቡራኬና የምርቃት ቃል፣ ሰው ሲገናኝና ሲለያይ የሚናገረው›› ነው፡፡ መስቀልና ሰላም አንዱ የአንዱ መሠረት አንዱ የአንዱ ፍሬ ሆነው የተሳሰሩትም በዚህ ምክንያት ነው፡፡

ኦርቶዶክሳዊ መንፈሳዊነት

ክርስትና የሕይወት መንገድ ነው፡፡ መንገዱም ደግሞ ወደ ዘላዓለማዊ ክብር የሚያደርስ የሕይወት የድኅነትና የቅድስና መንገድ ነው፡፡ ክርስቲያን ለመሆን በ፵ እና በ፹ ቀን በመጠመቅ የሥላሴ ልጅነትን ማግኘት የቤተ ክርስቲያን አባል መሆን ያስፈልጋል፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ዳግመኛ መወለድ ማለትም ነው፡፡

ጾመ ዮዲት

ዲያቆን ዮሴፍ በቀለ

በናቡከደነጾር ዘመነ መንግሥት ንጉሡ ሥልጣኑን መከታ በማድረግ የእግዚአብሔርን ሕዝብ በግድ እያስገደደ እጅ መንሻ ይቀበል ነበር፡፡ የመንግሥቱን ትእዛዝ ያልተቀበለውንም እየገደለ፣  ጭፍሮቹ ኃያልነቱንና ገናናነቱን በዓዋጅ በጦር አዛዦች ጭምር እያሳወጀ፣ በርካታ የጦር ሠራዊቶችን አሰልፎ ከአይሁድ ከተማ ገባ፡፡ በዚያም ነዋሪዎችን በማስፈራራት የመንግሥቱን ትእዛዝ ያልተቀበሉትን ሁሉ እያሳደደ ስላስጨነቃቸው ማቅ ለብሰው፣ አመድ ነስንሰውና ድንጋይ ተንተርሰው ወደ ፈጣሪያቸው በመጮህ መለመን ጀመሩ። በጭካኔ የተሞላው የጦር አበጋዙ ሆሎፎርኒስም ይበልጥ እጅግ እንዲሰቃዩ ውኃ የሚቀዱበትን ስፍራ ተቆጣጠረው፤ በግዴታ ማርኮም እጅ እንዲሰጡ እንዳደረጋቸው በመጽሐፈ ዮዲት ፪፥፪ ላይ ተጽፏል፡፡ በአካባቢው ይኖር የነበረ ዖዝያን የተባለ አንድ ሰው የአባቶቻቸው አምላክ ጸሎታቸውን እንዲሰማቸው ለአምስት ቀናት በትዕግሥት ይጾሙና ይጸልዩ ዘንድ ሕዝቡን መከራቸው፤ እነርሱም በትዕግሥት ሊጠብቁ ተስማሙ፡፡

የእስራኤል ልጆች የናቡከደነጾርን ጦር ብንችል ተዋግተን እንረታለን፤ ካልሆነም እጅ እንሰጣለን በማለት ይመካከሩ ጀመር። በዚያን ጊዜ ባሏ የሞተባትና በንጽሕና ተጠብቃ፣ በጸሎትና በሕገ እግዚአብሔር የምትኖር ዮዲት የተባለች ሴት ነበረች። (ዮዲት ፯፥፲) እግዚአብሔርን የምትፈራ ብቸኛዋ ሴት እርሷ ነበረችና ምክክራቸውን ስትሰማ ለምን «እግዚአብሔር ያድነናል አትሉም» ብላ ገሠጸቻቸው፡፡ ማቅ በመልበስ፣ አመድ በመነስነስና ድንጋይ በመንተራስም ሱባኤ ገባች። በሦስተኛው ቀንም እግዚአብሔር አምላክ ሕዝቧን የምታድንበትን ጥበብ ገለጸላት፤ ዮዲትም እግዚአብሔር የሰጣትን ውበት ተጠቅማ ሕዝቧን ከጥፋት የምትታደግበትን ጥበብ ተረዳች።

የክት ልብሷን ለብሳ፣ ሽቱ ተቀብታና ተውባ የጠላት ሠራዊት ወዳሉበት የጦር ሰፈር በድፍረት አመራች፡፡ ሠራዊቱም ውበቷን አይተው እጅግ በመደነቅ «ይህችስ ለአለቃችን ትገባለች» ተባብለው ከጦር መሪያቸው ዘንድ ወሰዷት። እርሷም ቀድማ ማምለጫ መንገድ አዘጋጅታ ነበርና ወደ አዛዡ ከገባች በኋላ «ክቡር ጌታዬ ሆይ ርስት ተወስዶብኛል፤ እንድትመልስልኝ አስቀድሜ ደጅ ልጠና መጥቻለውና ርዳኝ፤ ትብብርህ አይለየኝ» አለችው፡፡ በስሜት ፈረስ ታውሮ የነበረው የሠራዊቶቹ አዛዥም የጠየቀችውን እንደሚፈጽምላት ቃል ገባላት። ባማረ ድንካን እንዲያስቀምጧት ሎሌዎቹን አዘዘ። ዮዲትም የተሰጣትን ጥበብ ተጠቅማ፣ መውጣት ስትፈልግ የምትወጣበትን እና የምትገባበትን ዕድል በእግዚአብሔር አጋዥነት ዐወቀች፡፡ ከቀናት በኃላ የጦር አበጋዙ ለሠራዊቱ የምሳ ግብዣ አዘጋጅቶ ዮዲትን ከጎኑ አስቀመጣት፤ ከበሉና ከጠጡ በኋላም ሁሉን ሰው አስወጣ፤ እልፍኙን በመዝጋት ከእርሷ ጋር ብቻውን ሆነ፤ ነገር ግን እንቅልፍ ጣለው፡፡ (ዮዲት ፰፥፪) እርሷም ወደ አምላኳ ጸለየች፤ ፈጣሪዋ እንዲረዳትም አጥብቃ ለመነች። በኋላም ከራስጌው ሰይፍ አንስታ አንገቱን ቀላችው፤ በድኑንም ከመሬት ጣለችው። የሆሎፎርኒስን ሞት ሠራዊቱ ሲሰሙ አውራ እንደሌለው ንብ ተበተኑ፤ ከፊሎቹ ሞቱ። እስራኤላውያንም ከሞት ተርፈው በእግዚአብሔር ኃይል ድል አደረጉ፤ በደስታም ፈጣሪያቸውን አመሰገኑ።

ይህ መጽሐፍ ቅዱሳዊ ታሪክ የሚያስረዳን ዮዲት ጠላቶቿን ድል ያደረገችው በጾምና በጸሎት እንደሆነ ነው፡፡ ለእኛም የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች ምንም እንኳ ወርኃ ጳጉሜን የፈቃድ ጾም ቢሆንም በሀገራችን የተጋረጠውን ችግር እናልፍ ዘንድ በፈቃደኝነት እንጾማለን። እግዚአብሔር አምላካችን ለሁላችንም ጥበብ ሰጥቶናል። ይህም ችግሮችን ሁሉ የምንፈታበት መንገድ ነው። በዚህም የዓመተ መሸጋገሪያና የክረምቱ ወር ማብቂያ በመሆኑ ዕለተ ምጽአት ስለሚታሰብበት በየዓመቱ በጳጉሜ ወር ከሌሊት ጀምሮ በቤተ ክርስቲያን ተገኝተን ጠበል በመጠመቅ፣ በማስቀደስና በመጸለይ እንዲሁም ሥጋ ወደሙን በመቀበል ልናሳልፍ ይገባል። ዕለተ ምጽአትም ከዚህ ዓለም ወደ ወዲያኛው ዓለም መሸጋገሪያችን ነውና በቀኙ እንቆም ዘንድ እንጾማለን፡፡ የሚመጣውን አዲስ ዘመንም በንጽሕና ለመቀበል ስላለፈው ዓመት ኃጢአታችን ንስሓ የምንገባበት ጾምም ነው።   

ከተጋረጠብን ችግር «እግዚአብሔር ያድነናል» በማለት ልክ እንደ ዮዲት ሱባኤ ገብተን፣ ማቅ ለብሰን፣ አመድ ነስንሰንና ድንጋይ ተንተርሰን አብዝተን ልንጾምና ልንጸልይ ይገባል፡፡ ሊለያየን፣ ሊነጣጥለን፣ ሊበታትነን እና ሊገድለን ካሰበው እንዲሁም ፍቅርን፣ መተሳሰብንና አንድነትን ሊነፍገን ከቃጣው ጠላትና ሃይማኖታችንን ሊያስተወን ከሚመጣ ፀረ ሃይማኖት እንድናለን። ስለዚህ ከፊታችን ያለችውን ስድስቱን የጳጉሜን ቀን በፍቅር፣ በአንድነትና በሃይማኖት ጸንተን፣ ጾመን፣ ጸልየን ለዘመነ ዮሐንስ እንድንደርስ እግዚአብሔር አምላካችን ይርዳን፤ አሜን።

ስብሐት ለእግዚአብሔር

በአንዲት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እናምናለን (ጸሎተ ሃይማኖት)

ቤተ ክርስቲያን ሰማያዊት ንጽሕትና ቅድስት የክርስቶስ ማደሪያ ናት፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ «በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቋት ዘንድ እናንተን ጰጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለራሳችሁ እና ለመንጋው ሁሉ ተጠንቀቁ» በማለት ያስጠነቅቃል፡፡ በሰው ልጅ ፈቃድና ሐሳብ ያልተሠራች እግዚአብሔር በደሙ የዋጃት ቅድስት ሥፍራ ናት፡፡ ቤተ ክርስቲያን በሰማይና በምድር ያለች፣ ከሰው ልጅ ዕውቀት ፈቃድና ፍላጎት በላይ የሆነች የእግዚአብሔር ማደሪያ ናት፡፡ እግዚአብሔር የመሠረታት፣ የቀደሳትና የዋጃት፣ ሐዋርያት፣ ነቢያትና ቅዱሳን አበው የሰበኳትና ያጸኗት ቤት ናት፤ ለሰውም በረከተ ሥጋንና በረከተ ነፍስን ታድላለች፡፡

በዘመናችን የቤተክርስቲያን ፈተናዎች

የተከበራችሁ አንባብያን ባለፉት ሠላሳ ዓመታት በቤተክርስቲያንና በክርስቲያኖች ላይ እየደረሰ ያለውን መከራ በተለይም ደግሞ ባለፉት ሁለት ዓመታት የተፈጸመውን ግፍ የሚገልጽ ተከታታይ ጹሑፍ በማቅረብ ላይ መሆናችን ይታወቃል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ይዞታ ነጠቃ፤ የአብያተ ክርስቲያናት ቃጠሎና የምእመናን ግድያ  ዋናዎቹ የግፍ ተግባራት ናቸው፤ ከባለፈው የቀጠለውንና የመጨረሻውን እንደሚከተለው እናቀርባለን፡፡ መልካም ንባብ

በማርክሲዝም ሌሊዝንም አስተምሮ የተበረዘ ሰው ሁል ጊዜ ባላንጣና ጠላት በመፈለግ ጠላቱን ካላጠፋ መኖር እንደማችል ሲሰብክ የሚኖር መሆኑን በሙያው ምርምር ያደረጉ አካላት ይናገራሉ፡፡ ይህ አስተሳሰብ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ወደ ሃይማኖትም እየተጋባ መጥቷል፡፡ ከሃይማኖት ሰዎች የሚጠበቀው እናመልከዋለን የሚሉትን አምላክ በቃልም በምግባርም መግለጥ ነው፡፡ ሌላውን እያጠፉና  አማራጭ እያሳጡ እምነትን ማስፋፋት አይቻልም፡፡ ሌላውን አጥፍተው መኖር የሚፈልጉት የሚያደርጉት ምድራውያን ገዥዎች ናቸው፡፡ ስለሃይማኖት የሚያስተምሩ አካላት ከዚህ ዓለም የተለየ ዘለዓለማዊ ርስት እንዳለ የሚያምኑ በመሆናቸው ዘለዓለማዊ ርስት ማውረስ የሚችለውን አምላክ የሚያስደስቱበትን ተግባር ይፈጽማሉ፡፡ ሰው በመግደልና ተቀናቃኝን በማጥፋት ተደስቶ የሚኖር የሚመሰለው ምድራዊ የሥጋ ፍላጎት ያለው ምድራዊ ገዥ እንጂ ዘለዓለማዊ መንግሥትን የሚሻ መንፈሳዊ ሰው አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ወደ አሕዛብ የምትገባው ወንጌልን ይዛ እንጂ እንደ ቀኝ ገዥዎች በአንድ እጅ ወንጌል በሌላ የጦር መሣሪያ ይዛ አይደለም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ይህን የምታደርገው ባለቤቱ በወንጌል እንዲያምኑ ያደረገው በፍቅር እንጅ በግዳጅ ባለመሆኑ ነው፡፡እንዲህ ያለው እኩይ ተግባር የቤተ ክርስቲያን አለመሆኑን መረዳት የሚገባውም ቤተ ክርስቲያን በሞት እንጂ በመግደል ጸንታ ስለማታውቅ ነው፡፡

ቤተክርስቲያን የገጠማት ፈተና ያላሳሰባቸው አካላት የሰጡት መግለጫ መንግሥትን በሚከተለው መንገድ  አሳስቧል፡፡ ሀገርና ሕዝብን ለመምራት የተቀመጠው መንግሥት  በየአካባቢው  እየደረሰ ባለው  የአብያተ ክርስቲያናት ቃጠሎ፣ የኦርቶዶክሳውያንን መፈናቀል ፣ድብደባ ከዚያም ሲያልፍ አሰቃቂ ግድያ ላይ ያሳየው ቸልተኝነት የበርካታ ሚሊዮን አባሎቻችንን ልብ በእጅጉ የሰበረ ወደፊትም ቢሆን ለደኅንነታችን መጠበቅ ምንም አይነት ዋስትና እንደሌለን እንዲሰማን ያደረገ በመሆኑ የመንግሥትን ለዘብተኝነት በእጅጉ  እንቃወማለን ›› ይላል፡፡ አንድ መንግሥት ለዜጎቹ ዋስትና  ሲሰጥ ዜጎቹን በመንግስት እምነት  ማሳደር ብቻ  ሳይሆን  ለመንግሥትም  ጠበቃ ይሆናሉ፡፡ ምርጫ ቢደረግ ይመርጡታል፤ ቢናገር ይሰሙታል፡፡ ቢያዝዝ ይፈጽሙለታል፤ እንኳንም ተናግሮ ሳይናገርም ማድረግ የሚገባቸውን ይሠራሉ ፡፡ ክርስቲያኖች በዚህ ምድር ላይ ሲኖሩ በጌታ ለገዥዎቻችሁ ታዘዙ ›› የሚለውን  አምላዊ ቃል ሲፈጽሙ ኖረዋል፡፡ ወደ ፊትም ይፈጽሙታል፤ ይህ ማለት ግን በክርስቲያኖች ላይ በደል ሲፈጽም መንግሥትን አያሳስቡም ማለት አይደለም፡፡ ለገዥዎቻችን መታዘዝ እንዳለብን የሐዋርያውን ቃል አምነን እንሠራለን፡፡ አድሎአዊ ተግባር  ሲፈጸም ስናይ ደግሞ እንናገራለን፡፡ ነህምያ የኢየሩሳሌም መፍረስ ሲያሳስበው ስለኖረ ኃዘንና ትከዜው በፊቱ ላይ መነበብ በጀመረ ጊዜ የማረከው ንጉሥ ምን እንዳሳዘነው ጠየቀው ፡፡ ነህምያም ከዚህ በላይ መከራ አለመኖሩን በመረዳት አባቶቼ የሠሯት ኢየሩሳሌም ፈርሳ እንዴት ደስተኛ እሆናለሁ በማለት መለሰለት፡፡ በነህምያ መልስ ቅንነቱን ሲመለከት የኖረው ንጉሥ የሚያመልከው አምላክ የሚመለክበትን ቤተ መቅደስና ሙሉ ከተማዋን እንዲያንዱ ፈቃድ ሰጥቶ ሰደደው፡፡ በእኛ ዘመንም መፈጸም ያለበት እንዲህ ነው፡፡ አንተ ከፈርኦን አታንስ እኛም ከሙሴ አንበልጥ የሚለውን ንግግር ማሰብ ይገባል፡፡

 ሀገራችን ክርስቲያኖችን እያጠፉ የሚደሰቱበት ክርስቲያኖች ደግሞ በኃዘን የሚኖሩባት መሆን የለባትም፡፡ ሁላችንም እኩል ደስታውንም ኃዘኑንም የምንካፍልባት መሆን ይኖርባታል፡፡በሃይማኖት ሰበብ የተቀሰቀሰ ግጭት ቶሎ ስለማይበርድ መፍትሔ መፈለግ ተገቢ ነው እንላለን፡፡

 በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ  ቤተክርስቲያን ሠለስቱ ምእት የመቶ ሃያ ማኅበራት ኅብረት ደግሞ ‹‹ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በጅማ፣ በኢሉባቡር፣በከሚሴ፣በድሬድዋ፣በምሥራቅና በምዕራብ ሐረርጌ፣በፍቼ፣ሶማሌ (ጅጅጋ) ፣በባሌ፣ በአሩሲና በሌሎችም የሀገሪቱ ክፍሎች አብያተ ክርስቲያናት እየተቃጠሉ፤ ክርስቲያኖች እየተገደሉ፤ እየተሰደዱና ተገደው ሃይማኖታቸውን እንዲቀይሩ እየተደረገ፤  ንብረታቸው እየተቀማና እየተቃጠለ የአብያተ ክርስቲያናት ይዞታዎች ጥምቀተ ባሕርን ጨምሮ እየተቀሙ እንደሆነ በተለያዩ ሚድያዎች የሰማነውና በአካልም በቦታው ተገኝተን ያየነው እውነታ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ለሀገር ባለውለታ መሆኗ ተረስቶ ቤተክርስቲያንና አማኞቿን የማይመጥን ስም እየተሰጣት እንዲህ ያሉ ጥቃቶች መንግሥት ባለበት ሀገር እየተፈጸሙ፤ ሰዎች በነፃነት የፈለጉትን የማምለክና በሰላም ወጥቶ የመግባት ሕገ መንግሥታዊ መብታቸውን ተነፍገው በስጋትና በመከራ ውስጥ በመሆናቸው የተሰማንን ጥልቅ ኃዘን እንገልጣለን›› ብለዋል፡፡ ሀገሪቱ የምትታወቅባቸው የመስህብ ቦታዎች የቤተክርስቲያኗ መሆናቸው ይታወቃል፡፡ ቤተክርስቲያንን አጥፍተን ሌላ እንመሥርት ካልተባለ በስተቀር እንዲህ አይነት ተግባር በየትም ተደርጎ አያውቅም፡፡እንዲህ አይነት ዘመኑን የማይመጥን  ጥፋትና አድሎአዊ አሠራር መቆም ይኖርበታል፡፡ሥልጣን ላይ ስንቀመጥ መልካም ብንሠራ እኛ ዘለዓለማዊ አይደለንምና ስንወርድ ደግሞ ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም እንኖራለን፡፡ ሰዎች በመውረዳችን ያዝናሉ መልካም ተግባራችንን ሲዘክሩ ይኖራሉ እንጂ እንኳን ወረዱ አይሉንም፡፡ስለዚህ አጥፊዎች ከእኩይ ድርጊታቸው እንዲታቀቡ ማድረግ አጥፊዎች እንወክለዋለን የሚሉትንም ሆነ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያኖችን፤ አባቶችን አቅርቦ ማወያየትና ችግሩን በመለየት የማያዳግም እርምት መስጠት ይገባል፡፡

      ይቆየን

 ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ፳፮ ዓመት ቁጥር ፲፯

 

በዘመናችን የቤተክርስቲያን ፈተናዎች

የተከበራችሁ አንባብያን ባለፉት ሠላሳ ዓመታት በቤተክርስቲያንና በክርስቲያኖች ላይ እየደረሰ ያለውን መከራ በተለይም ደግሞ ባለፉት ሁለት ዓመታት የተፈጸመውን ግፍ የሚገልጽ ተከታታይ ጹሑፍ በማቅረብ ላይ መሆናችን ይታወቃል፡፡ የቤተክርስቲያን ይዞታ ነጠቃ፤ የአብያተ ክርስቲያናት ቃጠሎና የምእመናን ግድያ ዋናዎቹ የግፍ ተግባራት ናቸው፤ ከባለፈው የቀጠለውን እንደሚከተለው እናቀርባለን፡፡ መልካም ንባብ!

ክርስቲያኖች መከራ ቢገጥማቸውም ፈርተው ከእምነታቸው እንደማያፈገፍጉ፣ ከራሳቸው ሕይወት ይልቅ ለታቦታቱና ለንዋያተ ቅድሳቱ ቅድሚያ እንደሚሰጡ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ያነበብነው፤ በቅርብም ሲፈጸም ያየነው ተግባር ነው፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ከመከራ እንዲሰውራቸው ብቻ ሳይሆን በሰማዕትነት እንዲያበረታቸውም ይለምኑ ነበር፡፡ ቤተክርስቲያን ለሁለት ሺህ ዘመናት ያልተፈተነችበት የመከራ አይነት፣ያልተፈጸመም ተአምር አለመኖሩን ክርስቲያኖች ብቻ ሳይሆን አሕዛብም የሚመሰክሩት እውነታ ነው፡፡ አሕዛብ ቤተክርስቲያንን ለማጥፋት ሲነሡ ክርስቲያኖች ታቦታትና ንዋያተ ቅድሳትን ይዘው እንዲሸሹ ከማድረግ በተጨማሪ  እግዚአብሔር አምላክ በማይታበል ቃሉ ታቦታቱም ሆኑ አብያተ ክርስቲያናቱ እንዲሰወሩ ሲያደርግ ኖሯል፡፡ በግብጽ የነበረ የቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ታቦት በእስላሞች በፈረሰ ጊዜ እግዚአብሔር አምላክ ጽላቱን ሰውሮት ከብዙ ዘመን በኋላ በኢትዮጵያ ውስጥ ከአባ ተክለ ሃይማኖት የትውልድ አካባቢ ጽላልሽ ቤተክርስቲያን ሲተከል  ታቦቱን ሰጥቷቸው አክብረውታል፡፡ እንዲህ አይነት ተአምራት በየዘመናቱ ተፈጽመዋል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን ቤተክርስቲያንን ሊያቃጥሉ፤ ክርስቲያኖችን ሊገድሉ የተሰለፉ ወገኖች ሲጋፉት ለነበሩት ሃይማኖት ጠበቃ እንዲሆኑም አድርጓል፡፡ ከጥፋታቸው አልመለስ ካሉም ተቀስፈው እንዲሞቱ ሲያደርግ ኖሯል፡፡ ይህንን የምንጽፈው በአንድ በኩል በእምነት ያሉትን ለማጽናናት ሲሆን በሌላ በኩል ደግሞ ታሪክን መጥቀስ እንጂ ከታሪክ መማር የማይፈልጉ ወገኖች አንብበው እንዲጠቀሙበት በማሳብ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን እየተሳደደች ትዕግሥቷን አሕዛብ አይተው እንዲማሩ ለማስተማር ጭምር ነው፡፡

የምዕራባውያን ተልእኮ አስፈፃሚ የሆኑ መናፍቃንና ግብረ አበሮቻቸው ኢትዮጵያውያንን የአስተሳሰብ ድሃ ለማድረግና የነጮችን  የበላይነት አምነው እንዳይቀበሉ እንቅፋት የሆነችባቸውንና የሰውን ልጅ  ለሁሉም እኩልነትን የምታስተምረውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን  ለመበቀል የሚችሉትን ሁሉ ያደርጋሉ ዝናራቸውን ቢያራግፉና ቀስታቸውን ቢጨርሱም ለማሸነፍ እንደማይችሉ እያወቁት ራሳቸውን የሚጎዳ ተግባር ይፈጽማሉ፡፡ በዐድዋ በማይጨውና በሌሎች ከውጭ ወራሪዎች ጋር በተደረጉ ጦርነቶች የተሳተፉት ኦርቶዶክሳውያን ብቻ ባይሆኑም ቤተክርስቲያን ለሀገር መሞት ክብር መሆኑን በማወጅ፤ ምሕላ በመያዝ፤ ለዘማቾች የቁም ፍትሐት በማድረግ ያበረከተችውን አስተዋጽኦ በማሰብ መልካቸው እና ቋንቋቸው የሚመስሉንን አሠልጥነው ይልካሉ፡፡ ገንዘብ ማግኝት የሃይማኖተኝነት መስፈርት አስመስለው የዋሃንን ያሳስታሉና በቻሉት ሁሉ የቤተክርስቲያንን አስተዋጽኦ ከትውልድ አእምእሮ አጥበው ለማውጣት ብቻ ሳይሆን የፈጠራ ታሪክ እየፈበረኩ ጥላቻ ሲነዙ ይሰማሉ፡፡የሚያስፈልግውም ይህን የሐሰት ጽሑፍ እውነተኛ መረጃ ይዞ መንግሥት በፍርድ ቤትም መጠየቅ አስፈላጊ ነው፡፡

ኅዳር ፯ እና ፰ በ፲፱፻፺፰ ዓ.ም ኮፈሌ አንሻ በተባለ ቦታ የእስልምና እምነት ተከታዮች ስድስት ክርስቲያኖችን ማረዳቸው እስልምና ባለበት ሀገር ሁሉ ተገዳዳሪያቸውን የማጥፋት ተግባራቸው ማሳያ ነው፡፡በምእመናን ብዛት ከፍተኛውን ቊጥር ያላትን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ማጥቃት፤ ማዳከምና ምእመናንን አስገድዶ ማስለም የሚፈጸሙ ተግባራት ናቸው፡፡ በእምነት ስም የተደራጁ ቡድኖች እና የእምነቱ ተከታዮች ቤተክርስቲያንን ሲያጠቁ እና በተለያዩ ጊዜያት ጥቃቶችን ሲፈጽሙ ይታያሉ፡፡ ክርስቲያኖችን  አስገድዶ በማስለም፤ ፈቃደኛ ካልሆኑ ደግሞ የመግደል ተልኳቸውን ሲፈጽሙ ለደረሰው ጥፋት ክርስቲያኖች ለሚመለከተው አካል  አቤቱታ ሲያቀርቡ ፍትሕ አለመሰጠቱ ወደፊት መስተካከል ይርበታል፡፡ይህ ድርጊት በወቅቱና በጊዜው ካልታረመ መጨረሻ ለሌለው ብጥብጥ እንደሚዳረግ መታወቅ ይኖርበታል፡፡

በቡርቃ ጉዲና እና በአዲስ ልማት ቀበሌዎች ከ፪፻ በላይ ክርስቲያን አባወራዎች ይኖሩ የነበሩ ሲሆን በ፳፻፲፩ ዓ.ም በተደረገው የክርስቲያኖች ቈጠራ ፻፹፭ ሆነዋል፡፡ ይህም የሆነው የክርስቲያኖች ግድያና ስደት ስለተባባሰና ድርጊቱ ሲፈጸም እየታየ ተው ባይ በመጥፋቱ ነው፡፡ ጥፋቱ ተጠናቅሮ በመቀጠሉም ከሚያዚያ ወር  መጀመሪያ እስካሁን ፲፭ አባወራዎች በጋሌ ሰረጡ ቅድስት ኪዳነምሕረት ቤተክርስቲያን ውስጥ ከቤተክርስቲያኑ አስተዳዳሪ ቄስ ጋር በድንኳን ተጠልለው እየኖሩ ነው፡፡ በክርስቲያኖችና በአብያተ ክርስቲያን ላይ እየደረሰ ያለው ጥፋት ይቁም የምንለውም እንዲህ አይነት ኢሰብአዊ ተግባራት ሲፈጸሙ ሰለምንመለከት ነው፡፡ ሀገራችን ለውጥ ላይ መሆኗ ይታወቃል፡፡ ለውጡን ያልፈለጉት ወገኖች ኢትዮጵያውያን ከቀያቸው እንዲፈናቀሉ በማድረግ የሀገራችንን ገጽታ እያበላሹ መሆኑን ባንዘነጋውም በአንዳንድ አካባቢዎች ክርስቲያኖች ላይ ብቻ ያነጣጠረ ጥቃት ሥልጣን ላይ በተቀመጡ አካላት ጭምር ሲፈጸም መታየቱ ለሰላም ሳይሆን ለብጥብጥ  እየተሠራ ያስመስላልና መፍትሔ ሊፈለግለት ይገባል፡፡

የመንግሥት አካላት ሕዝብን ለማገልገል ኃላፊነት እንዳለባቸው ከተረዱ ሁሉንም ኢትዮጵያዊ ዘር፣ቋንቋ፣ቀለም፤ ሃይማኖት፣ሳይለዩ ማገልገል ይኖርባቸዋል፡፡ለሚያልፍ ሥልጣን ታሪክ የማይረሳው ጠባሳ ትቶ ማለፍ ተገቢ አይደለም፡፡ በየቦታው ለሚከሠቱ ግጭቶች መፍትሔ ከመፈለግ ተቆጥበው ተረጋግቶ ለሥራ የተሰማራንና ስለሀገሩ የሚጸልይን ክርስቲያን መነካካት ጥፋት እንጂ ሰላምን አያመጣም፡፡

ሐምሌ ፲፱ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በባሌጎባ በተፈጠረ የሃይማኖት ግጭት ፭ ምእመናን ተገድለዋል፡፡ እንዲህ አይነት ጥፋቶች አሁንም ቀጥለዋል የሃይማኖት ግጭቶች ሲከሠቱ ግጭቶችን ማን እንዳስነሣቸው ማጣራትና ተገቢ የሆነ እርምጃ መስጠት ይገባል፡፡ እየታየ ያለው ግን እየተሰደዱ፣ እየተገደሉ ታቦታችሁን ይዛችሁ ውጡ የሚባሉትን ክርስቲያኖች መብታቸውን ሲጠይቁ ማሰርና ያለፍርድ ማጉላላት ነው፡፡ ይህን ተግባር ለማስታገስ በየአካባቢው የሚገኙ የመንግሥት አካላት ኃላፊነታቸውን በአግባቡ የማይወጡ ከሆነ የክርስቲያኖችን ችግር የፈጠረው ማን እንደሆነ፤ እነ ማን ያላግባብ እንደታሰሩ፤ ማን የሚባል ፖሊስ እንዳሰራቸው፤ ለምን ፍርድ ቤት እንዳላቀረባቸው፤ ፍርድ ቤት ለማቅረብ ጠበቃ የማግኘት መብታቸውን ማን እንዳስከለከለ መረጃውን አደራጅተው ለመንግሥት አካላትም በየደረጃው ለሚገኙ የቤተ ክህነት አገልጋዮችም ማሳወቅ ይኖርባቸዋል፡፡ መንግሥትንም በሕጋዊ መንገድ ለመጠየቅ ያግዛል፡፡ አጥፊዎች እናምንበታለን ከሚሉት  የእምነት ተቋማት ጋር ለመወያየትና አሳማኝ መረጃ ይዞ በፍርድ ቤት ለመጠየቅ ይጠቅማል፡፡ይህ ሁሉ እየተደረገ ጎን ለጎን መረሳት የሌለበት ጉዳይ እግዚአብሔር አምላክ፤ችግሩን እንዲያስወግደው በጾም በጸሎት መጠየቅ ይገባል፡፡ እግዚአብሔርን በንጹሕ ልቡና ሆነን ከጠየቅነው የተፈጠረው ችግር ይርቃል፡፡ በኃጢአታችን ምክንያት ከመጣም ይቅር ይለናል፡፡ ለክብር ከሆነም ያጸናናል፡፡ በእምነት ጸንተን ብንሞት እንኳ ገዳዮቻችንን ማርኮ ያመጣል፡፡ የሰማዕትነት ደም ደርቆ አያውቅም የተባለው ሞታቸው አሕዛብን ማርኮ የሚያመጣ በመሆኑ ነው፡፡

 በክርስቲያኖችና በቤተ ክርስቲያን ላይ እየተፈጸመ ያለው ጥፋት አለመቆሙ ያሳሰበው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የሰ/ት/ቤት ወጣቶች፤ መንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርትና ምሩቃን እንዲሁም የመንፈሳዊ ማኅበራት ተወካዮች በወቅታዊ የቤተ ክርስቲያን ጉዳዩች ላይ መግለጫ ሰጥቷል፡፡ መግለጫው በአንድ በኩል አጥፊዎች ሕግና ሥርዓት ባለበት ሀገር ከእኩይ ድርጊታቸው እንዲታገሡ ጥፋታቸውን የደረስንበት መሆኑን እንዲረዱ የሚያሳስብ ሲሆን በሌላ በኩል መንግሥትም አጥፊዎችን ለሕግ ማቅረብ  እንዳለበት ለማሳሰብ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ክርስቲያኖች አንድነትና ትብብር የሚያደርጉበትና ከፊት ይልቅ መትጋት የሚገባቸው መሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡ ቤተክርስቲያን ያለችበት ሁኔታ ያሳሰበው የቤተክርስቲያን አካል የቅድስት ቤተክርስቲያናችን ውለታና እያደረገችው ያለው አስተዋጽኦ ተረስቶ ለሀገራዊ ጥፋት  ባለቤት ተደርጋ መኮነኗን በጽኑ እንቃወማለን፤ ቤተክርስቲያን ከትላንት እስከ ዛሬ የሰላም መልእክተኛ እንጂ አጥፊዎች የሐሰት ታሪክ ፈጥረው እንደሚያወሩት ሕዝብን ከሚያስጨፈጭፉ አካላት ጋር ተባብራ ያጠፋች አይደለችም፡፡ በእውነት ለመናገር ካስፈለገ  በደቡብ፤ በምሥራቅ፤ በኦሮምያም ጭምር ክርስትና ያበበው በሀገሩ ባህል ላይ መሆኑን  መረዳት አይሳነውም፡፡ በአንጻሩ ሌሎች እምነቶች በገቡበት ቦታ ግን ነባሩ ባሕል ተደምስሶ ሀገራችን እስከማይመስል ደርሷል፡፡ አስተዋይ አእምሮ ላለው ሰው በታሪክ ተወቃሽ የሚሆነው ነባሩን ባህል አስገድዶ ሃይማኖት ያስለወጠ እንጂ ባህላችሁን ጠብቃችሁ ዘላለማዊ ርስትን የምትወርሱበትን ወንጌልን መቀበል ትችላላችሁ  የምትለው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን መሆን አይደለችም፡፡

ይቆየን

 ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ፳፮ ዓመት ቁጥር ፲፯

 

በዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተና

የተከበራችሁ አንባብያን እንደምን ሰነበታችሁ? ባለፉት ተከታታይ ጽሕፎች ላይ በዘመናችን ቤተ ክርስቲያን የገጠማትን ፈተና በተለይ የቤተ ክርስቲያንን ቃጠሎና የይዞታ መነጠቅን በተመለከተ መጠነኛ መረጃ የሚሰጥ ጽሑፍ ማቅረባችን ይታወቃል፡፡ ቀጣዩን ደግሞ እንደማከተለው አቅርበነዋል፡፡

ሀገራችንን የምንወድና ሰላማውያን ከሆንን ቀርበን መወያየት፣ ጥፋተኞችን መገሠጽ፣ አጥፊዎችን ለሕግ ማቅረብና ለተፈጠረው ጥፋት ይቅርታ ጠይቆ ካሳ ካስፈለገ መክፈል ነው፡፡ በሃያ ሰባት ዓመታት በቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሰውን እንተውና ለውጥ ከመጣ በኋላ የጥፋት ኃይሎች የፈጸሙትን በመጠኑ ለማቅረብ እንሞክር ቢባል እንኳ ተዘርዝሮ አያልቅም፡፡ ‹‹ሚያዝያ ፳፻፲፩ ዓ.ም ሐረር ሳሮሙጢ በሚኖሩ በአራት ካህናትና በምእመናን ላይ የመግደል ሙከራ ተደርጐ ከባድ ድብደባ ቢፈጸምባቸውም በእግዚአብሔር ቸርነት ተርፈው ሆስፒታል ገብተዋል፡፡›› ይህ የሚያሳየው ጥፋቱ ተጠናክሮ መቀጠሉን ነው፡፡ ይህንን ጥፋት እየፈጸሙ ሰላማውያን ነን ቢሉን ማመን አንችልም፡፡ ሰላም የሚመጣው በተግባር እንጂ በቃል አይደለም፡፡ መንግሥት አጥፊዎችን ለሕግ ያቅርብልን፣ ወደ ፊትም ጉዳት እንዳይደርስብን ጥበቃ ያድርግልን የምንለው ለዚህ ነው፡፡ ጥፋቱ አንድ ጊዘ ተፈጽሞ በመቆሙም አይደለም፡፡ በድሬዳዋ፣ በከሚሴ፣ በኤፍራታና ግድም፣ በሰሜን ሸዋ ሰላሌ፣ በምዕራብ ሸዋ፣ ወሊሶ፡ በጅማ ሊሙኮሳ በተከታታይ የተፈጸመውን በማየት እንጂ፡፡

በድሬዳዋ ሀገረ ስብከት የተፈጸመውም ከዚህ ጋር ተቀራራቢ ነው፡፡ በድሬዳዋ ከተማ ዳር የሚገኘውን ‹‹የመካነ ሕይወት አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ቤተ ክርስቲያንን ይዞታ እንወስዳለን በማለት ከመጋቢት ፳፻፲፩ ዓ.ም ጀምሮ ተደጋጋሚ ጥቃቶች በእስላሞች ተፈጽመዋል፡፡ የፖሊስ አባላቱ ችግር በተፈጠረበት ቦታ በሰዓቱ ቢደርሱም ጥቃት ፈጻሚዎቹን በመያዝና ወደ ሕግ በማቅረብ ፈንታ እንዲሸሹ ማድረጋቸውን ለማወቅ ችለናል፡፡ በአንጻሩ ደግሞ የቤተ ክርስቲያንን ይዞታ አናስነካም፣ ቤተ ክርስቲያን ጉዳት ሲደርስባት ቆመን አናይም ያሉ ወጣት ክርስቲያኖችን አስረው በመግረፍ የጥቃቱ ተባባሪ ሆነዋል፡፡››

ማኅበረ ቅዱሳን ወንጀል የሠሩ አካላት አይጠየቁ አላልንም፡፡ ጥፋተኛ ተለቅቆ፣ ተጎጂው የሚታሰርበትና የሚሰቃይበት አሠራር ይስተካከል በማለት ግን እንጠይቃለን፡፡ የፍትሕ አካላትም ከአንድ ወገን የሰሙትን ብቻ ይዘው ወደ ውሳኔ ከመግባት ይልቅ ከሃይማኖት ነፃ በሆነና የተቀመጡበትን ኃላፊነት ባገናዘበ መልኩ ሁለቱንም ወገን ፊት ለፊት አቅርቦ እውነቱን በማውጣት አጥፊዎችን ለሕግ ማቅረብ ይኖርባቸዋል ለማለት ነው፡፡ በወቅቱ የቤተ ክርስቲያኑን ይዞታ ለመቀራመት አሰፍስፈው የነበሩ ወገኖች የምኒሊክ ሃይማኖት ይውጣልን በማለት ይጮኹ እንደነበር የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡ ይህ ድርጊት የሰውን ልጅ የእምነት ነፃነት የሚፃረር ነው፡፡

የቤተ ክርስቲያንን ይዞታ ለመቀራመትና ደኗን ጨፍጭፎ ለማውደም የተሰለፉ ወገኖች ቤተ ክርስቲያኗን ከምኒሊክ ጋር ለማያያዝ ምን ሞራላዊስ ሃይማሃታዊስ ችሎታ ይኖራቸዋል፡፡ ክርስትናም ጌታችን ለሐዋርያት ያስተማረው እንጂ በሰዎች የተፈጠረ ሃይማኖት አይደለም፡፡ ምኒሊክ ከመነሣታቸው ከሁለት ሺህ ዓመታት በፊት ፍጹም አምላክ የሆነው እግዚአብሔር ወልድ ፍጹም ሰው በመሆን የመሠረተው፣ ዓለምን ከጨለማ ወደ ብርሃን ያመጣበት ሃይማኖት ነው፡፡

ቅዱስ ጳውሎስን ሊገድሉ በለስ አልቀናቸው ያሉ አይሁድ የሮማውያን ሕግ የሰጣቸውን መብት በትክክል መጠቀም ሲገባቸው ሕጉን ጠምዝዘው ጳውሎስን ካልገደልን እህል አንበላም፣ ውኃም አነጠጣም ብለዋል፡፡ ታሰሮ የነበረውን ቅዱስ ጳውሎስ ወደ አደባባይ እንዲያወጣላቸው ሀገረ ገዥውን ሕጋውያን መስለው ጠይቀው የግል ጥላቻቸውን በሕግ ሽፋን ለመፈጸም ተማምለው እንደነበር ሁሉ ዛሬም እየተፈጸመ ያለው የጥንቱ ተመሳሳይ ክፍት ነው፡፡ ሕግ የሰጠውን መጠቀም መብት ነው፡፡ ሕግን ጠምዝዞ ግላዊ ፍላጐትን ለማሟላትና ሌላውን ለማጥፋት መሞከር ግን ወንጀል ነው፡፡ የማይገለጥ የተከደነ፣ የማይታወቅ የተሰወረ ጉዳይ ባለመኖሩ ተደብቀን ብናጠፋ ሁለት ቀን ሳናድር እውነቱ ይገለጣል፡፡ የአጥፊዎች አሳብ ታሪክ ምንም ይበል እኛ ብቻ ደኅና ካላሉና ሀገር ብትበተን ምን አገባን ካላሉ በስተቀር ያልተረዱት እውነታ ወደ ሌላው የወረወሩት ቀስት እነሱንም እንደሚወጋቸውና ለሌላው ያነደዱት እሳት ራሳቸውንም እንደሚያቃጥላቸው ነው፡፡

በዚሁ በያዝነው ዓመት ባሳለፍነው የሚያዝያ ወር ሌላም ዘግናኝ ድርጊት በእስልምና እምነት ተከታዮች ጅማ ሀገረ ስብከት ሊሙኮሳ በሚባል ቦታ ተፈጽሟል፡፡ ታሪኩ እንዲህ ነው ‹‹ሚያዝያ አምስት ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ለሚዘክረው አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ጽዋ ጉዝጓዝ ቄጠማ ሊያጭድ በሔደበት ሚጡ ወንዝ ዳርቻ አቶ ልየው ጌትነት የተባለን የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ  ቤተ ክርስቲያን የእምነት ተከታይ አንገቱን ቀልተዉ በመጸዳጃ ቤት ጉድጓድ ውስጥ ከጣሉት በኋላ በላዩ የከብት ፍግ ጨምረውበታል፡፡ የመጸዳጃ ጉድጓዱ ባለቤት አቶ መሐመድ ሃምዛ የተባሉ ግለሰብ ነው፡፡ ወዳጅ ዘመዶቻቸው ቄጤማ ሊያጭድ ወጥቶ የቀረውን አቶ ልየው ፍለጋ ቢወጡ የደም ነጠብጣብ በማግኘታቸው ነጠብጣቡን ተከትለው ሲሔዱ ለማመን በሚከብድ ሁኔታ ገድለው ከአጨደው ቄጠማ ጋር መጸዳጃ ቤት ውስጥ ጥለውት ተገኝቷል፡፡›› ይህን ወንጀል የፈጸመው አካል ተጠርቶ ወደ ሕግ አልቀረበም፡፡ ከሁለት ዓመት ላላነሰ ጊዜ በደረሰባቸው ተደጋጋሚ ግፍ በአካባቢው ይኖሩ የነበሩ ክርስቲያኖች ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ድንኳን ተክለው መኖር ጀምረዋል፡፡

ቤተ ክርስቲያን ስታስጠልል ዘርና ሃይማኖት እንደማትመርጥ የመካቆሪሾች አባርረዋቸው ለመጡት የመሐመድ ተከታዮች ክርስቲያኑ ንጉሥ አረማህ ተቀብሎ በሰላም እንዲኖሩ የፈቀደላቸው መሆኑን የምንመሰክረው እኛ ብቻ ሳንሆን ምዕራባውያን ጭምር ናቸው፡፡ ይህንንም ጉዳይ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ ‹‹የእነሱ መንግሥታት (ምዕራባውያን) በ፳ኛው መቶ ክፍለ ዘመን እኔን የመሰለ ስደተኛ በሀገሩ መቀበሉን እንደ ትልቅ ሰብአዊ ድርጊት ሲቆጥረው፤ የእኔ ሀገር ንጉሦች የጄኔቫ ኮንቬንሽን (ስምምነት)፣ ሰብአዊ መብትና ዲሞክራሲ የሚባል ነገር በሰው ልጅ አእምሮ ባልታሰበበት ከአንድ ሺህ አምስት መቶ ዓመታት በፊት በእምነታቸው ከዘመኑ የሀገራችን ሰዎች እምነት የተለዩ የነቢዩ መሐመድ ተከታዮች ጥገኝነት መስጠታቸውን፣ እነዚህን ስደተኞች መልሱልን በማለት ዓረቦች ለላኩት መልእክተኛ፣ ንጉሣችን በእያንዳንዱ ስደተኛ ክብደት የሚመዝን ወርቅ ብትሰጡኝ እንኳን አሳልፌ አልሰጣችሁም›› (አንዳርጋቸው፣፳፻፲፩፥፲፱) በማለት መመለሳቸውን ጽፈዋል፡፡

ስለዚህ ጉዳይ በጥልቅ ለማወቅ የፈለገ ሰው የእነ ጆን ሰፔንሰር ትሪሚንግሆምን እስላም ኢን ኢትዮጵያን እና የጎበዜ ጣፈጠን እስልምና በአፍሪካ ማንበብ ይጠቅመዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያንን እንግዳ ተቀባይነት በማቃለል ማጣጣል ተገቢ አይደለም፡፡ የኢትዮጵያ ነገሥታት ጠብቀው ባቆዩዋት ሀገር እየኖሩ ነገሥታትን የሚተቹና ቤተ ክርስቲያንን ከነገሥታት ጋር እየደረቡ ለመምታት የሚፈልጉ ወገኖች እንደሚተርኩት ሳትሆን ትክክለኛ በመሆኗ በቅርቡ በለገጣፎም ሆነ በቡራዩ የተፈናቀሉ የእስልምናም የሌላ እምነት ተከታዮች እንጠጋ ብለው ሲመጡባት አታምኑብኝም የምትል ሳትሆን ልጆቼ ኑ ብላ እጇን ዘርግታ የምትቀበል መሆኗን አሳይታለች፡፡ ቤት ፈርሶባቸው ቤተ ክርስቲያን የተጠለሉ ወገኖች በኢሳት የቴሌቭዥን ጣቢያ ሲናገሩ ሰምተናልና፡፡

የሚጠቅመንም ካለፈው መጥፎ ታሪክ እየተጠነቀቅን መልካም ከሆነው ያለፈ ታሪካችን መማር ነው፡፡ ድሮ ተፈጽሟል እያሉ የሐሰት ታሪክ እየደረቱ የጥፋት ነጋሪት መምታት እልቂት እንጂ ሰላም ስለማያማጣ አጥፊዎች ደግመው ደጋግመው ተረጋግተው እንዲያስቡበት ማሳሰብ እንወዳለን፡፡ መንግሥትም አጥፊዎችን እንዲያስታግሥልን ደግመን እንጠይቃለን፡፡ ይህንን ጽሑፍ የምንዘጋው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች፣ የመንፈሳዊ ኮሌጅ ደቀ መዛሙርትና ምሩቃን እንዲሁም የመንፈሳዊ ማኅበራት ተወካዮች በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ በሰጡት መግለጫ ነው፡፡ እንዲህ ይላል ‹‹እስከ ዛሬ ሲፈጸሙ በኖሩ ጥቃቶች ላይ ከጥንስሱ ጀምሮ እጃቸውን የከተቱ፣ ያለ አንዳች ፍርሃት በአደባባይ ጭምር በክርስቲያኑ ሕዝብ ላይ ሲሳለቁ እና በል ሲላቸውም ዕልቂትን ሲያውጁ በከረሙና እያወጁ ባሉ ከመንግሥት ጭምር የፈረጠምን ነን ባይ ግለሰቦች እና ተቋማት መንግሥት ለፍርድ እንዲያቀርብልን እንጠይቃለን›› ይህ ቃል ሰላም ወዳድ ከሆነ አስተዋይ አካል የሚነገር ነው፡፡ ጥፋትን በጥፋት መመለስ ለሀገር አይጠቅምምና፡፡

 ይቆየን

 ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ፳፮ ዓመት ቁጥር ፲፮