ለማእከላት ጸሐፊዎችና ለማስተባበሪያ ሓላፊዎች ሥልጠና ተሰጠ

ሰኔ 13 ቀን 2005 ዓ.ም.

ታመነ ተ/ዮሐንስ

ሰኔ 1 እና 2 ቀን 2005 ዓ.ም በማኅበሩ ሥራ አመራርና አስፈጻሚ አካላት አወያይነት የማእከላት መደበኛ ጸሐፊዎች፣ መደበኛ መምህራንና የስድስቱ ማእከላት የማስተባበሪያ ጽ/ቤት ሓላፊዎችን ያሳተፈ ሥልጠናና ውይይት ተካሔደ፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን የሀገር ውስጥ ማእከላትና ግቢ ጉባኤያት ማደራጃና ማስተባበሪያ ዋና ሓላፊ የሆኑት ዲ/ን አንዱአምላክ ይበልጣል በስልጠናው መክፈቻ መርሐ ግብር ላይ በሰጡት ማብራሪያ ተሳታፊዎቹ ለማኅበሩ አገልግሎት ከፍተኛ ድርሻ ያላቸው በመሆናቸው በማኅበሩ የአምስት ዓመት ስትራቴጂክ ፕላን ዙሪያ ማወያየት ለአገልግሎቱ መቃናት አጋዥ የሆነ ሥልጠና መስጠት ተገቢ ሆኖ እንደተገኘ ገልጸዋል፡፡

በዚህም መሠረት በሙያው ልምድ ባላቸውና የማኅበሩ የልማት ተቋማት አስተዳደር ቦርድ አባል በሆኑት በአቶ መንክር ግርማ “Communication & team development” በሚል ርዕስ ሥልጠና የተሰጠ ሲሆን አባላቱ በቀጣይ የአገልግሎት ቆይታቸው ችግሮችን በምን ዓይነት ሁኔታ መፍታት እንዳለባቸው ግንዛቤ እንዲያገኙ ተደርጓል፡፡

በተጨማሪም ማኅበሩ ያለበትን ነባራዊ ሁኔታ ማእከላቱ እንዲረዱ በማድረግ በዋነኝነት ያለባቸው የሥራ ሓላፊነት የስብከተ ወንጌል ማስፋፋትና ማጎልበት ስለሆነ ሰፊውን ጊዜ በስብከተ ወንጌል አገልግሎቱ ላይ ያሉ ችግሮችና መፍትሔዎቻቸው ዙሪያ ውይይትና የልምድ ልውውጥ ተካሒዷል፡፡  

 
በስልጠናው ላይ ከስድስቱ ማስተባበሪያ ማእከላት ሠላሳ አምስት ተሳታፊዎች ተገኝተዋል፡፡

 

በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የሚታየውን የአሠራር ብልሹነት ማሰወገድ እንደሚገባ ተገለጸ

ሰኔ 6 ቀን 2005 ዓ.ም.

በትዕግሥት ታፈረ

በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር ውስጥ የሚታየውን የአሠራር ብልሹነት ማሰወገድ እንደሚገባ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖትና ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ገለጹ፡፡

ቅዱስነታቸው ይህንን የገለጹት በግንቦቱ ርክበ ካህናት የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ባስተላለፈው ውሳኔ መሠረት የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ፤ እንዲሁም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው የተመረጡት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ሓላፊዎችና ሠራተኞች ጋር ሰኔ 4 ቀን 2005 ዓ.ም. የትውውቅ መርሐ ግብር በተካሄደበት ወቅት ነው፡፡

የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ ሆነው የተመረጡት ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ የወላይታና ዳውሮ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በትውውቅ መርሐ ግብሩ ላይ ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል የሁሉም እገዛ እንደሚያስፈልግ የገለጹ ሲሆን “ለቤተ ክርስቲያናችን ተልእኮ ከተመረጥንና እንድናገለግል ከተጠራን አገልግሎታችን የተሻለ መሆን አለበት፡፡ የሚያዘን ሥርዓታችን፤ ፍቅራችንና ሕጋችን እንጂ ሥልጣናችን ሊሆን አይገባም፡፡ ሥልጣናችን የሚያዘን ከሆነ ሥራችን ሙሉ ሊሆን አይችልም፡፡ ትክክለኛ መሪን ማንም አይጠላም፤ መሪዎችን ተመሪዎች የሚጠሏቸው ከቆሙለት ዓላማና ተግባር ውጪ በአምባገነንነት፤ በጉቦኝነት፤ በዘረኝነት፤ በአድሏዊነት ሱስ ሲጠመዱ ተመሪዎች ያኮርፋሉ፤ ይጨነቃሉ፤ ማንንም ስለማያምኑ እንደ ቃየል ጥላቸው ያስደነግጣቸዋል፡፡  ስለዚህ ሀሰትን የምትጠየፉ፤ አሉባልታን የምትንቁ፤ ሥራን የምትወዱ፤ ሰላምን የምትናፍቁ፤ ፍቅር የምትላበሱ መሆን አለባችሁ፡፡ ወደፊት አብረን ስለምንጓዝ  እግዚአብሔር እንዲረዳን ቅድሰት ቤተ ክርስቲያናችንን አሳድገን እኛም ተረድተን ሌሎችን እንድንረዳ ያስፈልጋል” ብለዋል፡፡

በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የቅዱስ ሲኖዶስ ጸሓፊ ሆነው የተመረጡት ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በበኩላቸው ባደረጉት ንግግር “መሰባሰባችን መልካም ነው፡፡ ሁላችንም ግዴታችንን ከተወጣን ያለው ችግር ይወገዳል፡፡ በእውነተኞች ሰዎች ቸርነትና በጎነት አገር ትቀናለች፡፡ አገር ስትቀና ሰው ሁሉ በሰላም ይኖራል፡፡በኅብረት ሆነን ዘመኑን በመዋጀትና በመገምገም በትክክል ሥራችንን ከሠራን ይቃናልናል፡፡” በማለት ተናግረዋል፡፡

የጠቅላይ ቤተ ክህነት አስተዳደርና ሠራተኞች እንዲሁም የተለያዩ የቤተ ክርስቲያኒቱ አካላት ሠራተኞች ችግሮች ናቸው ያሏቸውን አሳቦች ያቀረቡ ሲሆን በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ወጥ የሆነ የአሠራር ዘዴ ያለመኖር፤ አለቆች በተለዋወጡ ቁጥር በሚመጣው ሰው ላይ ሠራተኛው ለመንጠልጠል የራሱን ዘዴ መቀየስ፤ በአሠራር ሥርዓቱ ሁሉም ሠራተኛ እኩል መመራት ያለመቻል፤ ሹማምንትን በመፍራት፤ በመስገድና በመሽቆጥቆጥ አማላጅ በመላክ የተሻለ ሥራ ለማግኘት ጥረት ማድረግ፤ ወዘተ. . . የሚሉት በሠራተኞቹ የተጠቀሱ ሲሆን ይህ አካሄድ በአስተዳደርና በስብከተ ወንጌል ተልእኮ ስኬታማ ጉዞ ላይ አሉታዊ ተጽእኖ እንደሚፈጥር በመግለጽ የአሠራር ዘዴ /System/ መዘርጋት እንዳለበት ጠቁመዋል፡፡

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት በሰጡት ቃለ ምእዳን “ቤተ ክርስቲያናችን ከጥንታዊያንና ከታሪካዊያን የዓለም አብያተ ክርስቲያናት አንዷና አንጋፋዋ መሆኗ የተረጋገጠላት ናት፡፡ ይህ ሊሆን የቻለው አባቶቻችን ከጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ፤ ከሐዋርያትና  ከሊቃውንቱ ተረክበው ሕልውናዋንና ክብሯን ጠብቀው ስላስተላለፉልን ነው፡፡ እኛም ለሚቀጥለው ትውልድ ለማስተላለፍ ትልቅ ሓላፊነት ይጠብቀናል፡፡ ስለዚህ ጥንተ ቅድስናዋን፤ ንጽሕናዋንና ታሪኳን መመለስ አለብን፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን በሃይማኖት እንከን የላትም፡፡ በአሁኑ ወቅት በአስተዳደር ጤነኛ አይደለችም፤ ብዙ ብልሹነት ይታያል፡፡ ለቤተ ክርስቲያናችን የማይስማሙ ነገሮች ወደ ቤተ ክርስቲያናችን ገብተው መንገዳችንን እያበላሹብን ነው፡፡ ሙስና፤ ዘረኝነትና ሌሎችም ክፉ ነገሮች ይታያሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን የመልካም ሥራ መሪ እንድትሆን እንፈልጋለን፡፡ አስተማሪ እንጂ ተማሪ መሆን የለባትም፡፡ ሓላፊነት፤ ተጠያቂነት፤ እውነተኛነት፤ ሃቀኝነትና የሕግ የበላይነት የሰፈነባት መሆን ይገባታል፡፡” ብለዋል፡፡

በባሕረ ጥበባት /Encyclopedia of EOTC/ ዝግጅት ዙሪያ የምክክር ጉባኤ ተካሔደ

ግንቦት 30 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በማኅበረ ቅዱሳን የጥናትና ምርምር ማእከል አስተባባሪነት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የባሕረ ጥበባት /Encyclopedia of EOTC/ ዝግጅት ዙሪያ ከባለ ድርሻ አካላት ጋር የምክክር ጉባኤ ተካሔደ፡፡

ግንቦት 29 ቀን 2005 ዓ.ም. ከቀኑ አስር ሰዓት ጀምሮ በሰሜን ሆቴል በተካሔደው የምክክር ጉባኤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ባሕረ ጥበባት /Encyclopedia of EOTC/ ማዘጋጀትte 30 ያስፈለገበት ዋነኛ ምክንያትን አስመልክቶ በማኅበሩ ሰብሳቢ በቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ ተገልጿል፡፡ በንግግራቸውም በተለያዩ ጊዜያት የቤተ ክርስቲያኒቱን ታሪክና ቅርሶች አጥኚዎች፤ ጎብኚዎችና ምእመናን መረጃዎችን ማእከላዊና ሕጋዊ ከሆነ ቦታ ማግኘት አስቸጋሪ መሆኑን አውስተው አለም አቀፍ ተቀባይነት ያለው፤ ሊቃውንቱ የሚያውቁት የቤተ ክርስቲያንን ማንንት የሚገልጽ መረጃ ማዘጋጀት፤ በተለያዩ ጊዜያት በዘርፉ የተሞከረው እውቀት በአንድ ላይ በማሰባሰብ የታሪክ ቅሰጣ ለማስቀረትና ለመከላከል እንዲቻል ይህንን ባሕረ ጥበባት ማዘጋጀት እንዳስፈለገ አብራርተዋል፡፡  

በተካሔደው ውይይትም የሚዘጋጀው ባሕረ ጥበባት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ትውፊት፤ ታሪክና ሥርዓት እንዲይዝ እንዴት ተደርጎ ይዘጋጃል፤ ማነው የሚያዘጋጀው፤ አቅም / የሰው ሃይል፤ten 30 ገንዘብ . . ./ ፤ ተጀምሮ እንዳይቋረጥ ምን መደረግ አለበት፤ የባለሙያዎች ድጋፍ፤ የባለ ድርሻ አካላት ትብብር፤ የአሰራር ሥልቶች ዝግጅት፤ በስንት ጊዜ ይጠናቀቃል? በሚሉና ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ሰፋ ያለ ውይይት ተካሒዷል፡፡

በመጨረሻም በአማርኛና በእንግሊዝኛ የሚዘጋጀው የዚህ ባሕረ ጥበባት ባለቤት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስትሆን ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ባለድርሻ አካላትን በማስተባበር በገንዘብ በጊዜ በሰው ኃይል የተቀናጀ አደረጃጀት ያለው ሆኖ ሥራውን ግን ማኅበረ ቅዱሳን  በበላይነት ቢመራው የተሻለ እንደሚሆን አስተያየት ቀርቧል፡፡ ለሥራው ግብአት የሚሆኑ አሳቦችንም ለማሰሳሰብ የምክክር ጉባኤው በተደጋጋሚ እንደሚደረግ ተጠቅሷል፡፡

tena
በምክክር ጉባኤው ላይ ከሊቃውንት ጉባኤ፣ ከአዲስ አበባ ዮኒቨርሲቲ፣ ከቤተ ክርስቲያኒቱ መንፈሳዊ ኮሌጆች፤ ከቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለሥልጣን፤ ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ቤተ መዛግብትና መጻሕፍት ኤጀንሲ፣ ከአዲስ አበባ ባሕልና ቱሪዝም ቢሮ፣ እንዲሁም የማኅበረ ቅዱሳን ሥራ አመራርና ሥራ አሰፈጻሚ አባላት ተገኝተዋል፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ተጠናቀቀ

ግንቦት 30 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

senod 2005

ከግንቦት 21 ቀን ጀምሮ እስከ ግንቦት 30 2005 ዓ.ም.  ድረስ ሲካሔድ የሰነበተው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ለቤተ ክርስቲያኗ አስፈላጊ ናቸው ያላቸውን ውሳኔዎች በማሳለፍ ተጠናቀቀ፡፡ በዚህም መሠረት የሚከተሉትን ጠቅለል ያሉ ውሣኔዎች ተላልፈዋል፡፡  በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ የሚታዩ ብልሹ የአስተዳደርና የአሰራር ችግሮችን  ማሻሻል፤ ጥራት የጎደለው የፋይናንስ አያያዝን መዋጋት፤ ሙስናንና ለብክነት የተጋለጡ አሰራሮችን ለመቅረፍ እንዲቻል ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ ምሁራንና ምእመናን የሚገኙበት ዓብይ ኮሚቴ ማዋቀሩን ይፋ ማድረግ፡፡ በተጨማሪም የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት በአንድ ሀገረ ስብከት፤ በአንድ የቅዱስ ፓትርያርክ ረዳት ሊቀ ጳጳስ እንዲመራ የተደረገ ሲሆን ፤ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊ ምርጫም ተከናውኗል፡፡ ከሀገር ውጪ ከሚገኙ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ጋር የተጀመረው የሰላም ውይይት ጥረት እንደሚቀጥልም የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

ዝርዝር መግለጫውን ከዚህ በታች እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡

 

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

    በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቁጥር 164 ላይ ከበዐለ ትንሣኤ በኋላ በሃያ አምስተኛው ቀን  ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ እንዲካሔድ በተደነገገው ቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ከግንቦት 21 – 30 ቀን 2005 ዓ.ም. ተካሒዷል፡፡ ይህ ጉባኤ የርክበ ካህናት ጉባኤ ተብሎ የሚታወቅ ሲሆን ከላ በተጠቀሰው ቀኖና ቤተ ክርስቲያን እንደተገለጸው ብፁዐን ሊቃነ ጳጳሳት በቤተ ክርስቲያን ያለውን አጠቃላይ መንፈሳዊ፤ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ጉዳዮችን በማየት በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ታላላቅ ውሳኔዎችን የሚወሰንበት ዓብይ ጉባኤ ነው፡፡

    ቅዱስ ሲኖዶስ በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ያሉትን ወቅታዊና ነባራዊ ጉዳዮችን ለመመርመርና ለመገምገም ባለው ሐዋርያዊ ኃላፊነት ለቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ ተልእኮ አፈጻጸም እንቅፋት ናቸው ብሎ ያመነባቸውን ጉዳዮች በአጀንዳ ቀርጾ፤ በስፋትና በጥልቀት ተወያይቶ ውሳኔ ሰጥቶባቸዋል፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በምድር ላይ ያለች የእግዚአብሔር መንግስት ማዕከል፤ በባሕርይዋም ንጽሕትና ቅድስት ብትሆንም ኃጢአትና ስሕተት በነገሰበት ዓለም ያለች በመሆንዋ ከእርስዋ መሠረታዊ ባሕርይ ጋር የማይስማሙ ተግባራት እንዳይጋቡባት የመጀመሪያው ጥበቃ በብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ላይ ያረፈ ነው፡፡ በተለይም የአሁኑ ዓላማችን ጥበብ ባፈራው የአሠራር ዕውቀት በየቀኑ በለውጥ ጎዳና በሚራመድበት ጊዜ ቤተ ክርስቲያናችንም ከዓለሙ በተሻለና በበለጠ በመንፈሳዊና በአእምሮአዊ ጥበብ ሕዝበ ክርስቲያኑን መምራት፤ ማስተማርና ማገልገል ይጠበቅባታል፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን እነዚህን የተቀደሱ ተግባራት በሥራ ለመተርጎም ወቅታዊ እንቅፋት ሊሆኑ የሚችሉ ነገሮች ምን ምን ናቸው? በማለት ቅዱስ ሲኖዶስ በጥልቀት ተመልክቶአል፡፡

    በዚህ መሠረት ጉባኤው ብዙ ውይይት ካደረገ በኋላ የሚከተሉትን ዓበይት ውሳኔዎችን አሳልፎአል፡፡

 

  1. በየሥራ ዘርፉ እየተከሠተ ያለው የመልካም አስተዳደርን ችግር በተለይም ብልሹ አስተዳደርና አሠራር፤ ዘመኑን ያልዋጀና ጥራት የጎደለው የፋይናንስ አያያዝ፤ እንደዚሁም ለሙስናና ለብክነት የተጋለጡ አሠራሮች ሁሉ ወሳኝ በሆነ መልኩ ለመቅረፍና ለማድረቅ፣ ከዚህም ጋር ቤተ ክርስቲያናችን በመሪ እቅድ መሥራት የምትችልበትን አሠራር ለመቀየስ፣ ቅዱስ ሲኖዶስ፡- ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ ምሁራን ምእመናን የሚገኙበት ዓቢይ ኮሚቴ ተቋቁሞ ጉዳዮን የማጣራትና የማጥናት ሥራውን እንዲቀጥል ተስማምቶ በአንድ ድምፅ ወሰኖአል፡፡

  2. የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ለሌሎች አህጉረ ስብከት በመልካም አስተዳደርና በፋይናንስ አያያዝ፣ እንደዚሁም በስብከተ ወንጌልና በአገልግሎት አሰጣጥ ለሌሎች እንደዚሁም በመልካም አስተዳደር፣ በፋይናንስ አያያዝና በሰው ኀይል አመዳደብ የሕግ የበላይነትን አክብሮ እንዲሠራ አስፈላጊውን ክትትል ሁሉ በቋሚ ሲኖዶስና በመንበረ ፓትርያርኩ ጥብቅ ክትትል እንዲደረግ፤

  3. የቤተ ክርስቲያናችን የሕይወት ምንጭ የሆነውን የስብከተ ወንግል ትምህርት በሰው ኀይል፣ በሚድያም ጭምር እየታገዘ በመላው ዓለም ላሉ የቤተ ክርስቲያናችን ተከታዮች ትምህርቱን በጥራትና በጥልቀት ይሰጥ ዘንድ አስፈፋሚው አካል ጠንከር ያለ ሥራ እንዲሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ በሙሉ ድምጽ ወስኗል፡፡ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅና የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ ምርጫ በየሦስት ዓመቱ እንዲካሄድ ሕገ ቤተ ክርስቲያን ባስቀመጠው ድንጋጌ መሠረት ብፁዕ አቡነ ማቴዎስ፤ የወላይታ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ፤ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ዋና ሥራ አስኪያጅ፤ ብፁዕ አቡነ ሉቃስ፤ የሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሐፊ አድርጎ ቅዱስ ሲኖዶስ መርጧቸዋል፡፡

  4. ብፁዕ አቡነ እስጢፋኖስ የጅማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ረዳት ሊቀ ጳጳስ ሆነው እንዲሠሩ፤ እንደዚሁም የምራቅና ሰሜን አዲስ አበባ አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዳንኤል በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ዳንኤል በኢየሩሳሌም የኢትዮጵያ ገዳማት ሊቀ ጳጳስ ሆነው እንዲሠሩ ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

  5. በመካከለኛው ምሥራቅና በሌሎች የዓለም ክፍሎች ለሥራ ፍለጋ በሕገ ወጥ መንገድ በሚሄዱ ልጆቻችንና ወገኖቻችን ላይ እየደረሰ ያለውን ዘግናኝ ድርጊት ለማስቆም መንግሥት እያደረገ ያለው ጥረት ቤተ ክርስቲያናችን በሙሉ ልብ እንደምትደግፈውና ለስኬቱም የበኩሏን እንደምትወጣ፣ ለዚህም በየደረጃው ያሉ መምህራን፣ ካህናትና ሰባክያን ሁሉ የዚህን ጎጂነት ደጋግመው በማስረዳትና በማስተማር ሕዝቡ ግንዛቤ እንዲኖረው ጠንክረው እንዲያስተምሩ ቅዱስ ሲኖዶስ መመሪያ ሰጥቷል፡፡

  6. የሀገራችን ሕዝቦች ከድህነትና ከኋላ ቀርነት ተላቀው መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገሮች ጋር እኩል ለማሰለፍ በሚደረገው ሁለንተናዊ የልማት ተግባር ቤተ ክርስቲያናችን ከሕዝቡና ከመንግሥት ጎን በመሆን የሚጠበቅባትን ሁሉ እንደምታደርግ ቅዱስ ሲኖዶስ አረጋግጧል፡፡

  7. ኢትዮጵያ ሀገራችን በሀገር ውስጥ፣ በምሥራቅ አፍሪካ፣ በመላ አፍሪካ ከዚያም በመላው ዓለም ሰላም እንዲሰፍን፣ የሰው ልጅ እኩልነትና መብት እንዲከበር፣ ፍትሐዊ የሆነ የሀብት አጠቃቀም እንዲኖር፣ የአየር መዛባትን ለመቋቋም የአረንጓዴ ልማት ሀብት እንዲስፋፋ የምታደርገውን ያላሰለሰ ጥረት ቅዱስ ሲኖዶስ በእጅጉ እያደነቀ የሀገሪቱን መልካም ዝናና በጎ ገጽታ ለመጠበቅ የበኩሉን ጠንክሮ እንዲሠራ አረጋግጧል፡፡

  8. በሀገራችን የዕድገት ሂደት ከፍተኛ ሚና ይጫወታል ተብሎ በመገንባት የሚገኘው ታላቁ የሕዳሴ ግድብ ሥራው ተጠናቆ ጥቅም ላይ እስኪውል ድረስ ቤተ ክርስቲያናችን አስፈላጊውን ድጋፍ ሁሉ እንደማታቋርጥ ቅዲስ ሲኖዶስ ያረጋግጣል፡፡

  9. ሀገራችን ኢትዮጵያ በጤናው ዘርፍ የኅብረተ ሰቡን ጤንነት ለመጠበቅ በተለይም በሀገር አቀፍ ደረጃ ለእናቶችና ለሕፅናት እየተደረገ ያለው ልዩ የጤና እንክብካቤ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ቤተ ክርስቲያናችን ኅብረተሰቡን ከማስተማርና የጉዳዩን ጠቃሚነት ከማስረዳት ባሻገር ለመርሐ ግብሩ መሳካት አስፈላጊውን ድጋፍ እንደምታደረግ ቅዲስ ሲኖዶስ ይገልፃል፡፡

  10. ከሀገር ውጭ ከሚገኙ የቤተ ክርስቲያን አባቶች ጋር የተጀመረው የላም ውይይት በተለያዩ ምክንያቶች እስካሁን የሚፈለገውን የአንድነት ውጤት ባያስገኝም የቤተ ክርስቲያናችን አንድነትና ሰላም ለቤተ ክርስቲያናችንም ሆነ ለሀገራችን እንዲሁም ለሕዝባችን ያለው ትርጉም የላቀ መሆኑን ቅዲስ ሲኖዶስ ስለሚገነዘብ ሁኔታዎች ተመቻችተው የሰላም ውይይቱ እንዲቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ ወስኗል፡፡

  11. ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቲያኒቱን መንፈሳዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ ተልእኮ ዘመኑ በሚጠይቀው ጥበብና ዕውቀት እየቃኘ ለሃይማኖት፣ ለሀገርና ለሕዝበ ክርስቲያኑ ማበርከት የሚገባውን ሁሉ በብቃት ለመሥራት ከምንም ጊዜ በላይ የተዘጋጀ መሆኑን ሕዝበ ክርስቲያኑቀ ተገንዝቦ እርሱም የበኩሉን ሥራ በቅን መንፈስ እንዲወጣ አበክሮ አሳስቧል፡፡

የቤተ ክርስቲያናችን የመጨረሻ ውሳኔ ሰጭ የሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ በየጊዜው የሚያስተላልፋቸው ውሳኔዎችና መመሪያዎች ሁሉ ተፈጻሚነት ኖሮአቸው ጥሩ ውጤት ሊያስገኙ የሚችሉት በሁሉም ደረጃና አካባቢ የሚገኙ የቤተ ክርስቲያናችን ካህናትና ምእመናን ለቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ ተግባራዊነት በሙሉ ልባዠው ሲሰለፉ እንደሆነ የቅዱስ ሲኖዶስ እምነት ነው፡፡ ስለሆነም ለእናት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ክብርና ሉዓላዊነት መጠበቅ፣ ለሕልውናዋ መቀጠልና ለዕድገትዋ መስፋፋት የሚቆረቆሩ የቤተ ክርስቲያናችን አገልጋዮችና ተከታዮች በሙሉ ቅዱስ ሲኖዶስ የሚያሳልፋቸውን ውሳኔዎችና መመሪያዎች ለመተግበር አስፈላጊውን ትብብር ሁሉ እንዲያደርጉ በአጽንዖት በማሳሰብ ለዐሥር ቀናት ያህል ሲካሄድ የሰነበተውን ጉባኤ ዛሬ ግንቦት 30 ቀን 2005 ዓ.ም. በጸሎት አጠናቅቋል፡፡

እግዚአብሔር ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንንና ሀገራችን ኢትዮጵያን ይባርክ፤ ይቀድስ፤ አሜን!!

 

አባ ማትየስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ
ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት
ግንቦት 30 ቀን 2005 ዓ.ም.

የጀበራ ማርያም ገዳምን እንደገና ለማቋቋም ጥረት በመደረግ ላይ ነው

ግንቦት 3ዐ ቀን 2ዐዐ5 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በበሰሜን ጎንደር ዞን ደንቢያ ወረዳ በጣና ሐይቅ ደሴቶች ውስጥ ከሚገኙት ገዳማት አንዱ የሆነውና ለረጅም ዘመናት ጠፍ ሆኖ፤ ፈርሶ የቆየው የጀበራ ማርያም ገዳምን መልሶ ለማቋቋም ጥረት በመደረግ ላይ ነው፡፡

hamela 5የጀበራ ማርያም ገዳም በአፄ አምደ ጽዮን ዘመነ መንግሥት በ13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተገደመ ሲሆን በደርቡሽ ወረራ ወቅት ከፍተኛ ጉዳት ደርሶበት ሙሉ ለሙሉ ፈርሷል፡፡ ነገር ግን አባቶች መልሰው ገዳሙን በመመሥረት አጽንተውት የነበረ ቢሆንም የኢጣሊያ ጦር ኢትዮጵያን ሲወርር በ1956 ዓ.ም. መምህር ካሳ ፈንታ በሚባሉ አባት ቤተ ክርስቲያኑን በማነጽ፤ ገዳሙን መልሶ በመገደም ጥንት ወደነበረበት ለመመለስ ጥረት አድርገው ነበር፡፡ ነገር ግን እሳቸው ካረፉ በኋላ ከእግራቸው ተተክቶ ገዳሙን አጠናክሮ ለመያዝ የሚችል  አባት በመጥፋቱ ገዳሙ ተፈታ፡፡ የቤተ ክርስቲያኑም እንጨት በምስጥ ተበልቶ በንፋስ ኃይል ስለፈረሰ ታቦቱ ከሐይቁ ማዶ በምትገኘው ቅድስት ሃና ማርያም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ እንዲገባ ተደርጓል፡፡

ገዳሙን መልሶ በማቅናት ላይ የሚገኙት አባ ዘወንጌል በገዳሙ ውስጥ ከዚህ ቀደም ለሦስት ዓመታት ቆይተው፤ በችግር ምክንያት በመውጣት ወደ ዝቋላ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ገዳም ከሔዱ 20 ዓመት ሆኗቸዋል፡፡ “የገዳሙ መፈታት በመስማቴና ህሊናዬ ሊያርፍ ባለመቻሉ አባቶቻችን ያቆዩልንን ገዳም ዳግም ለመመሥረት ወደዚህ መጣሁ፡፡ ከመጣሁም ገና 3 ወራት ብቻ ናቸው የተቆጠሩት” ይላሉ፡፡

በሦስት ወራት ውስጥ ቤተልሔምና ቤተ እግዚአብሔር /ምግብ ማብሰያ/ ተሰርተው ተጠናቀዋል፡፡ በቀጣይነትም ለመናንያን በዓት፤ የእንግዳ ማረፊያ ቤት፤ ከደሴቱ ማዶ በሚገኘውና የገዳሙ ይዞታ በሆነው አንደhamela 4 ሄክታር መሬት ላይ የሞፈር ቤት ለመሥራት በእንቅስቃሴ ላይ ይገኛሉ፡፡ እነዚህ ሥራዎች እንደተጠናቀቁም በጅምር ላይ የሚገኘውን ቤተ ክርስቲያን ለማነጽ ጥረት እንደሚያደርጉ አባ ዘወንጌል ይገልጻሉ፡፡

ጀበራ ማርያም ገዳም ውስጥ በጾም በጸሎት ተወስነው የሚገኙ አባቶች በጸሎታቸው ወቅት  እጆቻቸው እንደ ከዋክብት ያበሩ ስለነበር በአካባቢው የሚገኙ ምእመናን “እጀበራዎች” እያሉ ይጠሯቸው  ስለነበር የገዳሙ ስያሜ ሆኗል፡፡ በአሁኑ ወቅት በገዳሙ ውስጥ ስድስት መናንያን ብቻ ,ይገኛሉ፡፡

የቅዱስ ሚካኤል ታቦት “ካህኑን” አቃጠለ

ግንቦት 30 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ቴዎድሮስ ኃይሉ

 

  • የአብያተ ክርስቲያናት ዝርፊያ ተባብሷል

hamela 3የሐምሌ ቅዱስ ሚካኤል ታቦት ግንቦት 2 ቀን 2005 ዓ.ም. ሌሊት በሌቦች ተዘርፎ ሲወሰድ መንገድ ላይ የዘራፊውን “ካህን” አእምሮውን አስቶ፤ መንገዱን አስትቶ፤ በሰው ማሳ ውስጥ እንዳስገባውና ታቦቱም ወደ ሰማይ እየዘለለ ዘራፊውን እንዳቃጠለ የሀባቦ ጉዱሩ ወረዳ ቤተ ክህነት ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ትጉኀን ብዙዓለም ግንባር ተናገሩ፡፡

“እንዲሁም ተጠርጣሪው ‘ወየው ለእኔ፤ ወየው ለእኔ’ እያለ ሲጮህ በአካባቢው አትክልት ሲጠብቁ ያደሩ ሰዎች እንደሰሙ እና ተጠርጣሪው እስር ቤት ከገባ በኋላም ‘እባቦች እየመጡብኝ ነው’ እያለ ለፖሊስ እንደሚያመለክት፤ ፖሊሶችም ወደ ታሰረበት ክፍል ሲገቡ ምንም እባብ እንዳላገኙ” ሊቀ ትጉኀን ብዙዓለም የቅዱስ ሚካኤልን ድንቅ ተአምር መስክረዋል፡፡

በመጽሐፍ ቅዱስ ታቦት ድንቅ የሆነ ገቢረ ተአምራትን እንደሚያደርግ የተጠቀሰ ነው፤ ያሉት ደግሞ በጉዱሩና በሀባቦ ጉዱሩ ወረዳዎች በሰባኬ ወንጌልነት የሚያገለግሉት ቆሞስ አባ ወልደ ገብርኤል አበበ ሲሆኑ፤ የሐምሌ ቅዱስ ሚካኤል ታቦትም ገቢረ ተአምሩን ሊሰርቅ በሞከረው “ካህን” ላይ አሳይቷል ብለዋል፡፡

የሐምሌ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ቄስ ዋለ ዓለሙ ስለ ሐምሌ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን የዘረፋ ሙከራ እንዳመለከቱት “በዕድሜ ዘመኔ እንዲህ ያለ ነገር ተመልክቼ አላውቅም፡፡ በዚህ ዓመት ብቻ የሐምሌ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ሁለት ጊዜ (ኅዳር 10 እና ግንቦት 2 ቀን 2005 ዓ.ም) ተዘርፏል፡፡ የግንቦት ሁለት ቀን ግን ለየት ያለ ነበር፡፡ በዕለቱ ታቦት፣ ሙዳየ ምጽዋት፣ መስቀልና መጽሐፍ ባልታወቁ “ካህናት” ተዘርፈው ታቦቱ ከአንድ ኪሎ ሜትር ርቀት በላይ ተወሰዶ በአንድ ሕፃን ልጅና በሦስት ሴቶች ተገኝቷል”  በማለት አስረድተዋል፡፡

የተዘረፈውን ታቦት የእርሻ ማሳ ውስጥ ተቀምጦ ከተመለከቱት ልጆች መካከል ብዙነሽ ዓለማየሁ ስለሁኔታው ስትናገር “አራት ሆነን በአህያዎቻችን ዕቃ ጭነን ወደ ገበያ ስንሄድ ከሐምሌ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን አካባቢ ካሉ የእርሻ ማሳ ደረስን፡፡ በዚህን ጊዜ አብሮን የነበረው ሕፃን የቤተ ክርስቲያን መጽሐፍ የሚመስል ነገር አየና ለእኛም አሳየን፡፡ እኛም ወንጌል መስሎን ለመሳለም አንሥተን ለመሳለም ስንሞከር አቃተን፤ አንቀጠቀጠን፡፡ ፈርተን አህዮችን ነድተን ልንሄድ ስንል አህዮች ቀድመው ስለወደቁ መነሣት አልቻሉም፡፡ አህዩችን ለማስነሣት ብንሞክርም አልተቻለም፡፡ በመጨረሻ ነገሩ ተአምር መሆኑን ስለተረዳን ለዲያቆናት ስልክ ደወልን” በማለት ምስክርነቷን ሰጥታለች፡፡

ወንጌል መስሏት ለመሣለም የፈለገችው እንሰኔ ዓለማየሁ ስለተመለከተችው ተአምር ስትገልጽ “ጠጋ ብዬ ላነሣው ስሞክር ቀኝ እጄን አሸማቀቀኝ፣ ለዲያቆን ታደለ ደወልን፤ እርሱ መጥቶ ታቦቱ ላይ ፎጣውን አልብሶ ካህናት ሊጠራ ሔደ፤ ከፎጣው ብርሃን ሲወጣ ስንመለከት፤ ታቦቱ የተቃጠለ መሰሎን አለቀስን፤ ታቦቱ ግን ምንም አልሆነም” ብላለች፡፡ አያይዛም ታቦቱን አስቀድሞ የተመለከተው ሕፃን ሌሊቱን ሙሉ ሲባንን ማደሩን አውስታለች፡፡

የሬፍ ቶኮ ታኔ ቀበሌ ገበሬ ማኅበር ሊቀ መንበር ኮንስታብል ደረጀ ጉቱ ስለሁኔታው  ሲያስረዱ “የቤተ ክርስቲያኑን መሰበር የሰማነው ከጠዋቱ ሁለት ሰዓት ላይ ሲሆን፤ ታቦቱንም ሚግሮ ዳሞት አካባቢ ወድቆ፤ በአካባቢውም መዝሙረ ዳዊትና የተሰበሩ ሦስት ባንኮኒዎችን አገኘን፡፡ በመዝሙረ ዳዊቱ ላይ ባገኘነው ማስታወሻ መሠረት ተጠርጣሪውን ልንይዝ ችለናል” ብለዋል፡፡

“ታቦቱን ካለበት ቦታ ማን ያነሰዋል እያልን ስንመካከር ከመካከላችን የነበረ አንድ የሌላ እምነት ተከታይ ‘እኔ አነሣለሁ’ ብሎ ቀረበ፤ ነገር ግን ታቦቱን ሲቀርብ ፈራ፤ ‘ሰውነቴን አቃጠለኝ ራሴን አቃጠለኝ እንደ አንድ ነገር አደረገኝ’ ብሎ በመደንግጥ ሄደ” በማለት ኮንስታብል ደረጀ ተናግሯል፡፡

hamela 2
ታቦታቱን ለማክበር ከመጡት አባቶች መካከል ቆሞስ አባ ወልደ ገብርኤል ስለሁኔታው ሲናገሩ “ታቦቱን ዘራፊው አስቀምጦት የሄደበት ቦታ ዙሪያ ገባው ጭቃ ነበር፡፡ ይህ ጭቃ ታቦቱን ሳይነካ በታቦቱ ዙሪያ መሆኑ የሚያመለክተው ታቦቱ ሌባውን አስሮት ማቆየቱና ሌባው ታቦቱን በዙሪያው ሲዞር ማደሩን የሚያመለክት ነው” ሲሉ አስገንዝበዋል፡፡

ታቦቱ የተገኘው በእኛ የእርሻ ማሳ ላይ ነው፤ የሚሉት የፕሮቴስታንት እምነት ተከታይ የሆኑት ግለሰቦች በበኩላቸው “ታቦቱ እኛ ማሳ ጋር ሲደርስ አልሄድም ማለቱ እግዚአብሔር ስለወደደን ነው፡፡ ይህ ታቦቱ ያረፈበት መሬት የበረከት መሬት ነው” ሲሉ ታቦቱ የተገኘበትን ቦታ ከልለው ለቤተ ክርስቲያን መስጠታቸውን ተናግረዋል፡፡

ታቦተ ሚካኤል ድንቅ የሆነ ሥራውን በዐደባባይ ሠርቶ በሆታና በዝማሬ ግንቦት 3 ቀን 2005 ዓ.ም ወደ መንበረ ክብሩ መመለሱን ቄስ ጋሸነው እንዳላማው አስታውቀዋል፡፡

በተያያዘም ሊቀ ትጉኀን ቀሲስ ብዙዓለም በወረዳቸው ስለተፈጸሙ የአብያተ ክርስቲያናት ዘረፋ እንዳስታወቁት “ከሰኔ 2004 ዓ.ም እስከ ግንቦት 2005 ዓ.ም በወረዳው ካሉ ዐሥራ አንድ አብያተ ክርስቲያናት ውስጥ በፎቃ መድኀኔዓለም ቤተ ክርስቲያን፣ በእንባቦ ቅዱስ ተክለ ሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን፣ ሎያ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን እና በሐምሌ ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን ላይ ሁለት ጊዜና ከዚያ በላይ ዘረፋና የዘረፋ ሙከራ ተካሂዶባቸዋል፡፡ እንዲሁም ብራና መጽሐፍት፤ መስቀሎች፤ መጋረጃዎችና መጎናጸፍያ እንዲሁም ሙዳየ ምጽዋቶች መወሰዳቸውን ተናግረዋል፡፡

የፎቃ መድኀኔዓለም ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ የሆኑት ቄስ ዘላለም ጌትነት በበኩላቸው በፎቃ መድኀኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ላይ ከፍተኛ የሆነ የዘረፋ ሙከራ እየተደረገ በመሆኑ ለአገልግሎት መቸገራቸውን ተናግረዋል፡፡

የፎቃ መድኀኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ዘበኛ አቶ አሰፋ ትእዛዙ ከዘራፊዎቹ ስለገጠማቸው ጥቃት ሲናገሩ “ዓምና በግንቦት ወር ላይ ከምሽቱ አምስት ሰዓት አካባቢ ሦስት ሌቦች መጥተው የቤተ ክርስቲያኑን በር ነኩ፡፡ በራፉ ላይ ያስቀመጥኩት ቆርቆሮ መሳይ ነገር ወደ መሬት በመውደቅ ድምፅ አሰማኝ፡፡ እኔም በፍጥነት በመነሣት ባትሪ ሳበራ ሌቦቹ ጨለማውን ተገን አድርገው ወደ እኔ መጡ፡፡ በገጀራ ሊመቱኝም ሞከሩ፤ ነገር ግን በእግዚአብሔር ጥበቃ በትራቸውን ዛፉ ከለከለው፡፡ በመጨረሻም እግሬን በአንካሴ ወጉኝ፡፡” ብለው ዘራፊዎቹ የተደራጁ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡

በተመሳሳይም በወረዳው ካሉ አብያተ ክርስቲያናት የዘረፋ ጥቃት ከደረሰባቸው አብያተ ክርስቲያናት መካከል አንዱ የእንባቦ ተክለሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን አንዱ ነው ያሉት ደግሞ አቶ ዘላለም ኩምሳ ናቸው፡፡

አቶ ዘላለም የእንባቦ ተክለሃይማኖት ቤተ ክርስቲያን በንጉሥ ተክለ ሃይማኖት የታነጸና ረዥም ዕድሜ ያለው በመሆኑ ዘራፊዎችም ከፍተኛ ትኩረት ያደርጉበታል፡፡ ለዚህም ለሦስት ጊዜያት ያህል ሌቦች የዘረፋ ሙከራ እንዳካሄዱበትና የቤተ ክርስቲያኑን ቁልፍና ካዝና በመስበር መጋረጃዎች እንደተወሰዱ ተናግረዋል፡፡

በጥርጣሬ የተያዙ አካላትና መዝረፋቸውን ያመኑ ሰዎች አሉ የሚሉት ደግሞ የወረዳው የፖሊስ ናቸው፡፡ ቢሮው ማንኛውንም ችግሮች ለማስወገድ ቀን ከሌሊት እንደሚሠራና በየቀበሌው ፖሊስ በማስቀመጥ፣ ለሕዝቡ ስለ ሌብነት በማስተማር፣ ለጥበቃ አካላት ሥልጠና በመሥጠት እንደ ሀገር ይሠራል፡፡” ብለዋል፡፡

አያይዘውም “በጥርጣሬ የተያዙ ሌቦችንም ማስረጃ አቅርበን ተገቢውን ፍርድ እንደሚያገኙ እናምናለን  ሕዝቡም ሊተባበር ይገባል” ሲሉ አሳስበዋል፡፡

የሀባቦ ጉዱሩ ወረዳ ቤተ ክህነት የሚገኘው ከአዲስ አበባ በስተ ምዕራብ በቀድሞው ወለጋ ሀገረ ስብከት በአሁኑ ደግሞ ሆሮ ጉዱሩ ወለጋ ሀገረ ስብከት ተብሎ በሚጠራው ሥር ሲሆን በወረዳ ቤተ ክህነቱ ሥር አሥራ አንድ አብያተ ክርስቲያናት መኖራቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡ 

የመጻሕፍት ማሰባሰቢያ ሳምንት ተዘጋጀ

ግንቦት 23 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

libraries“አንድ መጽሐፍ ትውልድን ለመቅረጽ” በሚል መሪ ቃል በማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል አስተባባሪነት የማኅበሩን ቤተ መጻሕት በዘመናዊ ሁኔታ ማደራጀትና ክምችቱን ለማሳደግ፤ እንዲሁም ታላቅ የመረጃ ማእከል ለማድረግ ከሰኔ 1 እስከ 22 ቀን 2005 ዓ.ም. የሚቆይ የመጻሕፍት፤ የኮምፒዩተርና የመዛግብት ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር እንደተዘጋጀ የጥናትና ምርምር ማእከሉ ምክትል ዳይሬክተር አቶ ሰይፈ አበበ ገለጹ፡፡

ቤተ መጻሕፍቱ ከማኅበሩ አባላትና ምእመናን በተለገሱ ጥቂት መጻሕፍት በ1998 ዓ.ም. በአነስተኛ መጠለያ /ኮንቴነር/ ውስጥ አገልግሎት መስጠት መጀመሩን፤ በወቅቱም የማኅበሩን አገልግሎትና ጥረት የተረዱት ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ የነበሯቸውን 400 መጻሕፍት በመለገስ እንዲጠናከር የበኩላቸውን ድርሻ መወጣታቸውንና በአሁኑ ወቅት 5000 የሚደርሱ የታተሙ ቅጂ /Hard copy/፤ 1100 ያልታተሙ ቅጂ /Soft copy/ እና 10 የሚደርሱ የተለያዩ የብራና መዛግብት የመረጃ ክምችት ቤተ መጻሕፍቱ እንዳለው አቶ ሰይፈ አበበ ገልጸዋል፡፡

ዓላማውን አሰመልከቶ ሲገልጹም “ማኅበሩ ቤተ መጻሕፍቱን በማጠናከር ዘመናዊ በማድረግ መጻሕፍት፤ ቤተ መዛግብትና ቋሚ ዐውደ ርዕይ /ሙዚየም/ ማቋቋም፤ በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ መልክ የሚገኙ የመረጃ ምንጮችን ማሰባሰብ፤ ማደራጀትና ለምእመናንና ለተመራማሪዎች አገልግሎት መስጠት ነው” ብለዋል፡፡ በተጨማሪም በልዩ በልዩ ቦታዎች /በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ሀገር/ የሚገኙ ከመሰል ቤተ መጻሕፍት ቤተ መዛግብት ጋር ግንኙነት በመፍጠር ጠቋሚ /ዳይሬክቶሪ/ ማዘጋጀት ከዓላማዎቹ መካከል አንዱ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

ቤተ መጻሕፍቱ ወደፊት በዘመናዊ መልኩ በማደራጀት የE- Library አገልግሎት መጀመር፤ የመረጃ ክምችቱን በ40 ሺሕ ማሳደግና በሶፍትዌር ማደራጀት፤ የዲጂታል ቤተ መጻሕፍት ማቋቋምና የዲጂታላይዜሽን ሥራ ለማከናወን ከፍተኛ እንቅስቃሴ እየተደረገ እንደሚገኝ  አክለው ገልጸዋል፡፡

ከአገር ውስጥ ማእከላት 10 ሺሕ፤ ከውጪ ማእከላት 10 ሺሕ፤ ከአባላትና ምእመናን 20 ሺህ የተለያዩ መጻሕፍት የሚጠበቅ ሲሆን መዛግብት በታተመ ቅጂ /Hard copy/፤ ባልታተመ ቅጂ /Soft copy/ በስጦታ መስጠት፤ ኮምፒዩተር፤ ስካነር፤ ፎቶ ኮፒ፤ ወዘተ . . . ቁሳቁሶችንና መጻሕፍትን ለመግዛት የሚያስችል ገንዘብ በመለገስ ተሳትፎ እንዲያደርጉ የጥናትና ምርምር ማእከል ምክትል ዳይሬክተሩ አቶ ሰይፈ አበበ አሳስበዋል፡፡

ሐመር መጽሔት በግንቦት ወር እትሟ….!

ginbot hamer 1

ማኅበረ ቅዱሳን የቴሌቪዥን ሥርጭት አገልግሎቱን በይፋ መጀመሩን አበሰረ

ግንቦት 16 ቀን 2005 ዓ.ም.

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲየን ማኀበረ ቅዱሳን ላለፉት ሃያ ዓመታት በመንፈሳዊ መገናኛ ብዙኃን ሲሰጥ የቆየውን አገልግሎት በማስፋት የቴሌቪዥን ሥርጭት በኦፊሴል መጀመሩን ለምእመናን የሚያበስርበት ጉባኤ ቅዳሜ ግንቦት 17 ቀን 2005 ዓ.ም. በኢትዮጵያ ስብሰባ ማእከል እንደሚያካሂድ ተገለጸ፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች በሚሳተፉበት በዚህ ጉባኤ ማኅበሩ ዐቢይ ተልዕኮ አድርጎ ይዞት የተነሣውን የስብከተ ወንጌል አገልሎት ለማሳካት መንፈሳዊ መገናኛ ብዙኃንን እንዴት ሲጠቀም እንደቆየና በዘርፉ አገልግሎቱን ለማጠናከር ያለው ዕቅድ በብሮድ ካስት መገናኛ ብዙኃን የቴሌቪዥን ሥርጭት አገልግሎትን ለምን እንደጀመረ፣ ወደፊትም አጠናክሮ ለመቀጠል ያለውን ዕቅድና በአገልግሎቱ ምእመናን ሊኖራቸው ስለሚገባው ተሳትፎ መነሻ የሚሆኑ አሳቦች ቀርበው ውይይት እንደሚደረግባቸው ተጠቁሟል፡፡

ማኅበሩ ከየካቲት 16 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ በኢ.ቢ.ኤስ ቴሌቪዥን ሥርጭት ጣቢያ በየሳምንቱ እሑድ ከረፋዱ 5፡30 እስከ 6፡00 እና ሐሙስ ከጠዋቱ 1 ሰዓት እስከ 1፡30 የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ትምህርተ ሃይማኖት፣ ሥርዓተ እምነትና ትውፊት የሚያስተላልፉ ዝግጅቶችን እንደሚያቀርብ ይታወቃል፡፡

የቅዱስ ያሬድ 1500ኛ ዓመት መታሰቢያ በድምቀት ተከበረ

ግንቦት 13 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

img 0442የቅዱስ ያሬድ 1500ኛ ዓመት መታሰቢያ በዓል “ሕያው ዜማከ ወሕያው ድርሳንከ” በሚል መሪ ቃል ስድስት ኪሎ በሚገኘው የኢትዮጵያ ስብሰባ ማእከል አዳራሽ ግንቦት 11 ቀን 2005 ዓ. ም. በድምቀት ተከብሯል፡፡

ከየአድባራቱና ገዳማት የመጡ ታላላቅ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እንዲሁም ምእመናን የተገኙ ሲሆን የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ የእንኳን ደህና መጣችሁ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የታሪክ ትምህርት ክፍል መምህር በሆኑት ዶክተር ውዱ ጣፈጠ በቅዱስ ያሬድ ሕይወት ታሪክና ሥራዎቹ ላይ ያተኮረimg 0335 ጥናት አቅርበዋል፡፡ ከሊቃውንቱ መካከልም በጎንደር መንበረ መንግሥት መድኀኔዓለም የቤተ ክርስቲያኑ አስተዳዳሪና የአራቱ ጉባኤያት የመጻሕፍት መምህር ሊቀ ሊቃውንት ዕዝራ አዲስ የወንጌል ትምህርት ሰጥተዋል፡፡ ከሊቃውንቱ መካከል የቤተልሔም፤ የቆሜና የአጫበር ዜማዎችን በየተራ ያቀረቡ ሲሆን የመርሐ ግብሩ ልዩ ድምቀት ነበር፡፡

በራስ ዳሸን ተራራ ላይ በችግር ውስጥ የሚገኘው የቅዱስ ያሬድ ገዳምን ለመርዳት የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብር የተደረገ ሲሆን የማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል እጅግ አስቸጋሪና የአንድ ቀን ሙሉ የእግር ጉዞ በማድረግ የሚደረስበትን በበረዶ የተከበበው ገዳም ድረስ በመሄድ ገዳሙ ያለበትን ችግር ለማጥናት ጥረት ማደረጉ ተገልጻል፡፡

በገዳሙ ከ70 በላይ መነኮሳትና መናንያን የሚገኙ ሲሆን ከቦታው ተራራማነት የተነሳ ምእመናን የማይደርስበት ቦታ በመሆኑ ገዳማውያኑ የሚረዳቸው በማጣት የአልባሳት፤ የምግብና የመጠለያ ችግር እንዳጋጠማቸው ተጠቅሷል፡፡ በዚህም መሠረት ማኅበረ ቅዱሳን ከገዳሙ አቅራቢያ በ100 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በሚገኘው ደባርቅ ከተማ ላይ ለገዳሙ አገልግሎት የሚውል የአንድ ሺሕ ካሬ ሜትር ቦታ ከከተማው አስተዳደር በመረከብ ሕንፃ ለመገንባት ፕሮጀክት ቀርጾ እየተንቀሳቀሰ ይገኛል፡፡ በመጀመሪያው ዙርም 1.5 ሚሊዮን ብር እንደሚያስፈልግ በመገለጹ የገቢ ማሰባሰቢያ መርሐ ግብሩ ተካሂዷል፡፡

በዕለቱ ከተገኙ ምእመናንም ከግማሽ ሚሊዮን ብር በላይ ቃል የተገባ ሲሆን በማኅበረ ቅዱሳን የአሜሪካ ማእከል ለሕንፃጻው ማሠሪያ የሚውል ገንዘብ ለመላክ ቃል ገብቷል፡፡ማኅበረ ቅዱሳን ለአክሱም ጽዮን ማርያም ገዳም የብር መቋሚያና ጸናጽል በስጦታ ያበረከተ ሲሆን በአዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ የጥቁር አንበሳimg 0363 ስፔሻላይዝድ ሆስፒታል በ2004 ዓ.ም. የተመረቀውና የወርቅ ሜዳልያ ተሸላሚው ዶክተር አምኃ መሸሻ ለቅዱስ ያሬድ ገዳም ሜዳልያውን አበርክቷል፡፡

በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ ዲዮስቆሮስ የደቡባዊ ትግራይ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በሰጡት ቃለምእዳን “ከየገዳማቱና አድባራቱ በዓሉን ለማክበር በመካከላችን የተገኙት ሊቃውንት አባቶቻችን የቅዱስ ያሬድን ፈለግ በመከተል ቤተ ክርስቲያን ያለተተኪ እንዳትቀር አገልጋዮችን በማምረት ላይ ይገኛሉ፡፡ እነዚህ አባቶቻችን የቤተ ክርስቲያናችን የዜማ ፋብሪካዎች ናቸው” ብለዋል፡፡

በመርሐ ግብሩ ላይ የማኅበረ ቅዱሳን መዝሙር ክፍል አባላት የታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም ሰንበት ትምህርት ቤት አባላት እንዲሁም በአዲስ አበባ የሚገኙ ቀዳሚ ዜማ ዘያሬድ የሊቃውንት ማኅበር ያሬዳዊ ዝማሜና ወረብ አቅርበዋል፡፡