በዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተና

የተከበራችሁ አንባብያን በዘመናችን ቤተ ክርስቲያን ያለችበትን ሁኔታና በየአካባቢው እና በየክልሉ በቤተ ክርስቲያንና በክርስቲያኖች ላይ እየተፈጸመ ያለውን ጥቃት አስመልክቶ ክፍል አንድን  ማቅረባችን ይታወቃል ክፍል ሁለትን እነሆ ብለናል፡፡

ምዕራባውያንና የእነሱ ጉዳይ አስፈጻሚዎች ቤተ ክርስቲያንን ለማዳከም ይጠቅመናል ብለው ያሰቡትን ሁሉ ፈጽመዋል፡፡ የአሳባቸው አቀንቃኝ ኢትዮጵያዊ “ፈረንጆችንም” አግኝተዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንንም ሊቃውንቷንም ለመተቸት ያለ ስማቸው ስም ያለ ግብራቸው ግብር በመስጠት ጥላቻውን በመግለጽ አልሜዳ የተባለ ሚሲዮናዊ የፈጠራ ታሪክ ጽፏል፡፡ የእሱን ጥላቻ እየጠቀሱ ቤተ ክርስቲያንን የሚተቹት የግብር ልጆቹ ናቸው፡፡ የእሱን ጥፋት ዳንኤል ክብረት «አልሜዳ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን አምርሮ የሚጠላ ኋላ ቀርና በኑፋቄ የተሞላች አድርጎ የሚፈርጅ ኢየሱሳዊ /ሚስዮናዊ/ ነበር፡፡ በጽሑፎቹ ላይ ይህን ነው ሲያንጸባርቅ የኖረው፡፡ ከዚህ ጠባዩ አንጻርም አቡነ ተክለ ሃይማኖትን ቢተች የሚጠበቅ እንጂ የሚገርም አይደለም» (ዳንኤል፣ ፳፻፲፩፣፫‐፬) በማለት ገልጦታል፡፡ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌም ሆነ ተሐድሶአውያን አቡነ ተክለ ሃይማኖትን የሚተቹት የእሱን አሳብ እየጠቀሱ ነው፡፡ አቡነ ተክለ ሃይማኖትን መንቀፍና ያለ ግብራቸው ግብር መስጠት ቤተ ክርስቲያንን ለማዳከም ይጠቅመናል ብለው ያስባሉ፡፡ ለኋለኞቹ የቤተ ክርስቲያን ተችዎች ጀማሪና ፊታውራሪያቸው አልሜዳ ነው፡፡ የውጭ ጸሐፊዎች የኢትዮጵያውያንን አእምሮ በመበረዝ ቤተ ክርስቲያን ላይ ትችት እንዲያዘንቡ ምክንያት መሆናቸውን ከአልሜዳ ጽሑፍ መረዳት ይቻላል፡፡ ለመነሻ ያህል ይህን ካቀረብን በየዘርፉ የደረሱትን ችግሮች እንደሚከተለው እናቀርባለን፡፡

ሀ. የቤተ ክርስቲያን መቃጠል፡- በየዘመናቱ፣ በየቦታው አብያተ ክርስቲያናት በአክራሪ ሙስሊሞች፣ በግለኝነት በታወሩ የፕሮቴስታንት እምነት ተከታዮችና በአጽራረ ቤተ ክርስቲያን ሲቃጠሉ ቆይተዋል፡፡ ይህን የሚያደርጉት የግል ጥላቻና የተለየ ፍላጎት ያላቸው ግለሰቦች ወይም ቡድኖች እንጂ ሁሉም የሌሎች እምነቶች ተከታዮች እንዳልሆኑ ግልጽ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ስትቃጠል አብረው የሚያዝኑና የሚያለቅሱ፣ ክርስቲያኖች ሲሳደዱና መከራ ሲደርስባቸው በቤታቸው የሚሸሽጉ ብሎም አብረው መከራ የሚቀበሉ፣ ክርስቲያኖች ኃይላቸውን እያሰባሰቡ አቅማቸውን እያጠናከሩ መልሰው ለመገንባት ሲደክሙ ከገንዘብ እስከ አሳብ ድጋፍ የሚያደርጉ የሌላ እምነት ተከታዮች አሁንም በየቦታው መኖራቸው የሚካድ አይደለም፡፡ በዘመናችንም ክርስቲያኖች በጥብዐት መከራውን ተቋቁመው ክርስትና በሞት፣ በስድት፣ በእሳትና በመከራ የማይፈታ መሆኑን አስመስክረዋል፡፡ በዚሁ አንጻር ግን በመገናኛ ብዙኃን በተለያዩ ቦታዎች የሚቃጠሉትን አብያተ ክርስቲያናት ያልታወቁ ግለሰቦች ያቃጠሏቸው እንደሆነ ቢነገርም ታስቦበት፣ ተጠንቶ፣ ምን ለማግኘትና ምን መልስ ለመስጠት አስቀድሞ እየታሰበ ቃጠሎው መፈጸሙን የሚጠቁሙ ማሳያዎች አሉ፡፡ ፲፱፻፺፫ዓ.ም ሚያዝያ ፲፪ ቀን በአርሲ ሀገረ ስብከት ኮፈሌ ወረዳ ጉች ቀበሌ ገበሬ ማኅበር የሚገኘው የመድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን በአክራሪ እስላሞች ለመቃጠል የቻለው ከተማ ላይ ሊያደርሱት የነበረው አደጋ በመከላከያ ሠሪዊትና በፖሊስ ስለተደናቀፈባቸው ነው፡፡ ገጠር በመግባት የክርስቲያኖችን ቤት እየመረጡ ማቃጠላቸው የታቀደና የተደራጀ ጥቃት መሆኑን ለመረዳት ይቻላል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ሃይማኖታዊ ትንኮሳ ከትላንት እስከ ዛሬ መቀጠሉ ታስቦበት እየተሠራ መሆኑን የሚያሳይ ነው፡፡ ይህ ድርጊት በአንድ በኩል አጥፊዎች ልብ እንዲገዙ፣ በሌላ በኩል ደግሞ መንግሥት ከትላንት እስከ ዛሬ እየደረሰ ያለውን ጥፋት በመረዳት ለእምነት ቤቶችና ለክርስቲያኖች ልዩ ጥበቃ እንዲያደርግ ሊያነቁ፣ ምእመናንም ራሳቸውን እንዲጠብቁ፣ እንዲደራጁና አዲስ ነገር ሲገጥማቸው ለፍትሕ አካላት እንዲያቀርቡ ትምህርት ሊሆን ይገባል፡፡ ክርስቲያኖች የሚማሩት ከመከራ፣ ቅድስናቸው የሚገለጠው በፈተና መሆኑ የተጻፈ፣ ክርስቲያኖች በተግባር ፈጽመው ያሳዩት ሕይወት ነው፡፡

በጅማ ሀገረ ስብከት ከመስከረም ፲፮ እስከ ጥቅምት ፬ ቀን ፲፱፻፺፱ ዓ.ም ጨጉ ቅዱስ ገብርኤል፣ ቦሬ ቅዱስ ገብርኤልና በሻሻ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ አብያተ ክርስቲያናት በአክራሪ እስላሞች ተቃጥለዋል፡፡ ንዋያተ ቅድሳት ተዘርፈዋል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም በጅማ፣ በምዕራብ በወለጋና በኢሉባቡር ከ፲፫ በላይ አብያተ ክርስቲያን ንዋያተ ቅድሳት ተዘርፈዋል፡፡ ኅዳር ፮ ቀን ፲፱፻፺፰ዓ.ም በአርሲ ሀገረ ስብከት በኮፈሌ ወረዳ የምትገኘው የአይሻ ቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ፀረ ክርስትና አቋም ባለው ቡድን ተቃጥላለች፡፡ አገልጋይ ካህናት በቤተ መቅደስ ውስጥ ታርደዋል፣ አሥር ክርስቲያኖች በገጀራ ተገድለው፣ አብያተ ክርስቲያናትና የክርስቲያኖች መኖሪያ ቤቶች ተቃጥለዋል፡፡ ብዙ ንብረት ወድሟል፤ ነዋሪዎች ከቀያቸው ተፈናቅለዋል፡፡ ይህ የሚያሳየው በሀገራችን ሰላም እንዳይሰፍን ሆን ብለው ግጭት የሚፈጥሩ አካላት መኖራቸውን ነው፡፡

በወቅቱ አጥፊዎችን ሊያስተምር የሚችል እርምጃ መወሰድ ሲገባ ጉዳዩ ለሕዝብ ይፋ እንዳይሆን ከመንግሥት አካላት ተጽዕኖ ይደረግ ነበር፡፡ አጥፊዎችን ማስታገስ ሲገባ ጉዳት የደረሰባቸው ክርስቲያኖች ጉዳታቸውን እንዳይናገሩ መከልከል ላይ ያተኮረ እንቅስቃሴ ሲፈጸም መፈጸም በሕግም በሞራልም የሚያስወቅስ ነው፡፡ ይህ በምንም ዓይነት መንገድ ፍትሐዊ ሊሆን አይችልም፡፡ ይህ ለአጥፊዎች ከለላ መስጠትን እንጂ ለፍትሕ መቆምን አያሳይም፡፡ አጥፊዎች ሲያጠፋና ክርስቲያኖችና አብያተ ክርስቲያናት ሲቃጠሉ ዝም ብሎ ማየት ትዕግሥትን ሳይሆን የጥፋት ተባባሪ መሆንን የሚያሳይ ነው፡፡

በወቅቱ የመንግሥት አካላትን ያሳስብ የነበረው የገደሉትንና አደጋ ያደረሱትን አካላት ለመያዝ ሳይሆን አደጋው በተፈጸመበት ወቅት ከቦታው ተገኝተው የዘገቡትን አካላት ለመያዝ ነበር፡፡ ይህ ተግባር አሁንም ስለቀጠለ ቤተ ክስስቲያን እየተገፋች ድምፅ የሚያሰማላት አካል እያጣች ነው፡፡ አጥፊዎች ለስንት ሺህ ዘመናት የኖረ የሀገር ሀብት ሲያወድሙ እንደ ቀልድ እየታለፈ መሆኑ ለዚህ ጥሩ ማሳያ ነው፡፡ በየካቲት ወር መጨረሻና በመጋቢት ወር መጀመሪያ በድሬደዋ ከተማ አጠገብ የሚገኘውን ደን በመመንጠር የቤተ ክርስቲያንን መሬት በመከፋፈል ላይ ሳሉ ሕግ አስከባሪ አካላት ቢደርሱም አልታዘዝንም በማለት ቆመው ሲመለከቱ አጥፊዎች ከቦታው እንዲሸሹ ሲያደርጉ እንደነበር የዐይን እማኞች ገልጠዋል፡፡ በሊሙ ኮሳ ወረዳ በያዝነው ዓመት በተፈጸመው ጥፋት ከወረዳ አመራር ጀምሮ ሥልጣን ላይ የሚገኙ ወገኖች ጥፋቱን ያደረሱት አካላት በእምነት ስለሚመስሏቸው ወደ ሕግ ለማቅረብ አለመቻላቸውን ወረዳ ቤተ ክህነቱ ለሀገረ ስብከቱ የጻፈው የድረሱልኝ ደብዳቤ ያስረዳል፡፡ ምክንያት ተፈልጐ የሚያዙትና ካለ ፍርድ እስር ቤት እንዲቆዩ የሚደረጉትም ክርስቲያኖች ናቸው፡፡ ይህም ክርስቲያኖች እንዲሞቱ የተፈረደባቸው፣ ለሚደረስባቸው  አደጋ ሁሉ ከለላ የሌላቸው መሆኑን ሲያመለክት አጥፊዎች ደግሞ ሽፋን የሚሰጣቸው ይመስላል፡፡ ይህንም በሐረር ከተማ ጥር ፲፩ ቀን ፲፱፻፺፫ ዓ.ም ለጥምቀት በዓል በወጡ ምእመናን ላይ ለጁምአ ስግደት በአንድ መስጊድ ተሰብስበው የነበሩ ሙስሊሞች በፈጸሙት ትንኮሳ ግጭት ተፈጥሮ የአራት ሰዎች ሕይወት ሲያልፍ በፖሊስ ቊጥጥር ሥር የዋሉት ፲፮ ምእመናን ያለ ምንም ውሳኔ ከስድስት ወራት በላይ መቆየታቸው ማሳያ ነው፡፡ ግጭቱን ማን እንደጀመረው? ዓላማው ምን እንደነበር? አጣርቶ አስቸኳይ ውሳኔ መስጠት፣ አጥፊም በጥፋቱ እንዳይቀጥል ማስተማር ሲገባ ክርስቲያኖችን መርጦ ማሰር መፍትሔ አይሆንም፡፡ ወንጀል የፈጸመ ሰው አይያዝ ባይባልም ክርስቲያኖች ብቻ ተይዘው የሚታሰሩበት፣ ቢታሰሩም ቶሎ ለፍርድ የማይቀርቡበት ምክንያት ሌላ ዓላማ ያለ ያስመስላል፡፡

በአጥፊዎች ላይ ውሳኔ ቢሰጥበትም ቤተ ክርስቲያንን ላቃጠሉ፣ ንዋያተ ቅድሳትን ለዘረፉ አካላት የሚሰጠው ፍርድ አንድ በግ ከሰረቀ ሌባ ጋር ልዩነት የሌለው በነፃ ከማሰናበት ያልተሻለ መሆኑ ለክርስቲያኖችና ለቤተ ክርስቲያን ትኩረት መነፈጉን የሚያሳይ ነው፡፡ መረዳት የሚገባው ቤተ ክርስቲያንን አቃጥለው፣ ቅርሱን አውድመው እስከሚጨርሱ ዝም ከተባለ “ኢትዮጵያን የጎብኝዎች መዳረሻ እናደርጋለን” የሚለው አሳብ የሕልም እንጀራ መሆኑን ነው፡፡ የሚነገረው ቃልም ተፈጻሚነት ሳይኖረው ክርስቲያኖችን በማይሆን ነገር ለማዘናጋት የሚፈጸም መሆኑን የሚያሰገነዝብ ነው፡፡ ይህም በቤተ ክርስቲያን ላይ የተነሡት አፅራረ ቤተ ክርስቲያን ብቻቸውን ሳይሆኑ በጀርባቸው ሌላ አይዞህ ባይ እንዳላቸው የሚያመለክት ነው፡፡ የክርስቲያኖችና የቤተ ክርስቲያን ጉዳይ ትኩረት እንዳይሰጠው፣ በመገናኛ ብዙኃን ሽፋን እንዳያገኝና ሽፋን የሚያገኘውም ዘግይቶ መሆኑ ሌላ ችግር ይዞ እንዳይመጣ መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ የሚሰጠው አስተያየት እውነት የሚመስለው አጽራረ ቤተ ክርስቲያን የሚፈጽሙት እንዲሸፈን መደረጉ ነው፡፡

 በምዕራብ ሐረርጌ ሀገረ ስብከት ሜኤሶን ወረዳ በሚገኘው የአሰቦት ደብረ ወገግ ቅድስት ሥላሴና አቡነ ሳሙኤል ገዳም የካቲት ፳ ቀን ፳፻፬ ዓ.ም ከረፋዱ አራት ሰዓት አካባቢ ለከብት ዘረፋ ወደ ገዳሙ ክልል የገቡ የኢሳ ጎሳ አባላትን ለመከላከል የተደረገውን የተኩስ ልውውጥ ተከትሎ ሰደድ እሳት ተቀሰቀሰ፡፡ በወቀቱ የተቀሰቀሰው ሰደድ እሳት ከ፳፻፩ ዓ.ም በኋላ ለሁለተኛ ጊዜ ነበር፡፡ ከአሥራ አምስት ዓመት በፊት ተቀስቅሶ ለ፲፭ ቀናት የቆየው ሰደድ እሳት ከ፲፩ ሺህ ሄክታር በላይ ደን አውድሟል፡፡ እሳቱ በቊጥጥር ሥር የዋለው ከዋናው የገዳሙ ግቢ ለመድረስ ፭፻ ሜትር ያህል ሲቀረው ነበር፡፡ በወቅቱ ከ፴፰ ያላነሱ ከሰል አክሳዮች ለሰደድ እሳቱ መነሣት ምክንያት ናቸው በሚል ተጠርጥረው በቊጥጥር ሥር ቢውሉም ወዲያው በዋስ ተለቀዋል፡፡ ክስ ይመሥረትባቸው አይመሥረትባቸውም የታወቀ ነገር የለም፡፡ ይህ ሁሉ የሚያሳየው በቤተ ክርስቲያንና በክርስቲያኖች ላይ ለሚደርሰው ጥፋት ማስተካከያ የሚሰጥ አለመኖሩን ያሳያል፡፡

ይቆየን!

ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ከግንቦት ፲፮-፴ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም

በዘመናችን የቤተ ክርስቲያን ፈተና

በተለያዩ መድረኮች ቤተ ክርስቲያን ከእምነት ውጭ የሆኑትን ለማሰቃየት የክፉ አድራጊዎች ጠበቃ የሆነች የሚያስመስሉ ጽሑፎች ይቀርባሉ፡፡ ድብቅ ዓላማ ያላቸው ወገኖች ቤተ ክርስቲያንንና ክርስቲያኖችን ለማጥፋት ሰበብ በመፈለግ ጥፋተኛ እያስመሰሉ ያቀርባሉ፡፡ በመሠረቱ ይህ አስተሳሰብ ሁለት መሠረታዊ ችግሮች አሉበት፡፡ የመጀመሪያው ታሪክ በመሰነድ፣ ትውልድ በምግባር ኮትኩታ ያቆየች ባለውለታ፣ ቅርሶቿ ለሀገር ልዩ መታወቂያ ጐብኝዎችን ማርኮ የሚያመጣ ሆኖ ሳለ ያለ ስሟ ስም መስጠቱ ነው፡፡ ሁለተኛው ደግሞ ከእውነት የራቀ ሐሳብ ይዘው ጥፋተኛ ሳትሆን፤ ጥፋተኛ ስለሆነችና ከአጥፊዎች ስለተባበረች መጥፋት ይገባታል እንበቀላት የሚለው ነው፡፡ እነዚህ ለማጥፋት ምክንያት ፈላጊ ወገኖች ቤተ ክርስቲያንን እያቃጠሉና ምእመናንን እየገደሉ ለምን ሲባሉ ጥፋተኛ ስለሆነች ይላሉ፡፡ መቼ፣ የት፣ በማን፣ እነማንን ተብለው ሲየጠቁ መልስ የላቸውም፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ማቃጠልና ምእመናንን መግደል የእምነቱ ተከታዮች ራሳቸውን ወደ መከላከል ከዚያም ወደ መጉዳት ሊሸጋገሩ እንደሚችሉ መረዳት ይገባል፡፡ ለተፈጸመው ጥፋት አጸፋውን ቤተ ክርስቲያን ብትመልስ በሀገር ላይ ሊከሠት የሚችለውን ጥፋት አስቀድሞ መረዳትም ይጠቅማል፡፡ ጥናትን ሽፋን አድርጎ ለአጥፊዎች ዱላ የሚያቀብሉ አካላትም ከድርጊታቸው መቆጠብ ይኖርባቸዋል፡፡ መንግሥት አጥፊዎችን ለሕግ ከማቅረብ በተጨማሪ ለክርስቲያኖችና ለቤተ ክርስቲያን ከለላ መስጠት ይኖርበታል፡፡ አጥፊዎችም ክርስቲያኖችን ለማጥፋት የመዘዙት ሰይፍ ወደ ራሳቸው እንዳይዞር እና የእርስ በእርስ መጠፋፋት ሊያስከትል እንደሚችል ደጋግመው ሊያስቡበት ይገባል፡፡ በሃይማኖትና በዘር ምክንያት የተቀሰቀሰ ግጭት መብረጃ እንደሌለው በየሀገራቱ የተፈጸሙትን ጥፋቶች ማየት ይገባል፡፡ ታሪክ መጥቀስ ብቻውን የዕውቀት ባለቤት አያደርግም ከታሪክ መማር እንጂ፡፡

ከ፲፱፻፷፮ ዓ.ም ወዲህ በቤተ ክርስቲያን ላይ የደረሰውንና ከዛሬ ነገ እርምት ይወስድበታል በማለት በትዕግሥት ስትጠብቅ መኖሯን ከመግለጻችን በፊት ቤተ ክርስቲያን ለሀገር ያበረከተችውን አስተዋጽኦ በመጠኑ ለመዳሰስ እንሞክራለን፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሰዎችን ለመንግሥተ ሰማያት ስታዘጋጅ፣ በፍቅር ስባ፣ በትምህርት አለዝባ በእምነትም በምግባርም እንዲስተካከሉ በማድረግ ነው፡፡ ከአፍሪካ ሀገራት መካከል ሀገራችን ብቸኛ የራሷ ፊደል ያላት፣ ዘመን ተሻግሮ ከዘመናችን የደረሰ ቅርስ አበርክታ ሀገራችን በመላው ዓለም እንድትታወቅ ያደረች ባለውለታ ናት፡፡ አፍሪካውያን በቅኝ ግዛት ሲማቅቁ ኢትዮጵያውያን የቅኝ ግዛት ቀንበርን ሰብረው ጥለው፣ የነጭን ትምክተኛነት አስተንፍሰው ልጆቻቸው ቀና ብለን እንድንሔድ የመሪነቱን ሚና የተጫወተች ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ በውጭ ሀገራት በልዩ ልዩ ቋንቋዎች ተጽፈው እምነት፣ ዕውቀት፣ ሥነ ምግባር የሚያስተምሩ መጻሕፍት ኢትዮጵያዊ በሆነ ብሂል ተተርጒመው ትውልድ እንዲማርባቸው፣ ሊቃውንቶቿ በአፍሪካ፣ በመካከለኛው ምሥራቅና በአውሮፓ የኢትዮጵያን ባህል፣ ሃይማኖት፣ ታሪክ በማስተዋወቅ የአምባሳደርነት ሚና እንዲጫወቱ ያደረገችው ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ይህን የቤተ ክርስቲያን አስተዋጽኦ ዶክተር አክሊሉ ሀብቴ ‹‹የኢትዮጵያ ምሁራን መነኮሳት በኢትዮጵያ መልክዓ ምድር ክልል ውስጥ ብቻ ሳይሆን ከዚያም ውጭ በመሔድ በታሪክ ሊታወስና ሊጠና የሚገባ አስተዋጽኦ አበርክተዋል፡፡ በኢትዮጵያ አካባቢ በሱዳንና በግብፅ፣ በየመንና በኢየሩሳሌም፣ በአውሮፓ በመሔድ እነሱም እየተማሩ፣ የውጭውንም ሕዝብ ስለ ኢትዮጵያ ቋንቋና ታሪክ፣ ሃይማኖትና ባህል እንዲያውቅና እንዲፅፍ አድርገዋል›› (አክሊሉ፤፹፩) በማለት ገልጠውታል፡፡

እውነተኞቹ ተመራማሪዎች ያለ ኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ኢትዮጵያን ማሰብ እንደሚከብድ በምርምራቸው አረጋግጠው እውነቱን ከሐሰት፣ ብስሉን ከጥሬ፣ የሚጠቅመውን ከሚጐዳው፣ የተፈጸመውን ካልተፈጸመው ለይተው ከጥንካሬያችን እንድንማር ከስሕተታችን እንድንጠበቅ ያደረጋሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ማዳከም ዓላማችንን ያሳካልናል ብለው የሚያስቡ ወገኖች ደግሞ ኢትዮጵያን ቅኝ ለመግዛት ፈልገው ቅስማቸው ተሰብሮ እንዲመለስ ያደረገችው ቤተ ክርስቲያን መሆኗን ስለተረዱ ስሟን ለማጥፋት፣ ታሪኳን ለመበከል የጻፉትን አሉባልታ እውነት አድርገው በመውሰድ ታሪክ ሲያበላሹ፣ በተቀመጡበት የኃላፊነት ቦታ ጥፋት ሲፈጽሙ ይታያሉ፡፡ ሰውን በሰውነቱ እኩል ማገልገል ሲገባቸው በጎሳ፣ በቋንቋ፣ በጎጥ፣ በቡድንና በባህል በመከፋፈል ሥልጣንን ለክፉ ተግባር ይጠቀማሉ፡፡ ሕዝብን ለማገልገል የተሰጣቸውን ሥልጣን ተጠቅመው ቤተ ክርስቲያንንና ምእመናንን የማሳደድ ተልእኮ ይፈጽማሉ፡፡ ሀገር ሰላም ካልሆነችና ዜጎቿ በሰላም ወጥተው ካለገቡ አጥፊዎችም ችግር እንደሚገጥማቸው አልተረዱትም፡፡

በካናዳ፣ በቫቲካን፣ በጀርመንና በሌሎችም ሀገሮች የኢትዮጵያ ጥናት ተቋማት እንዲከፈቱ፣ ተመርምሮ የማያልቅ ዕውቀት የያዙት የብራና መጻሕፍት ለዓለም እንዲተዋወቁ ያደረጉት ቤተ ክርስቲያናችን አስተምራ «ሑሩ ወመሀሩ» ብላ ያሰማራቻቸው ሊቃውንት ናቸው፡፡ በሌላ በኩልም ሀገራችን እንግዳ ተቀባይ የሆነችውና ዓለም ፊቱን ያዞረባቸውን የመሐመድ ተከታዮች ሳይቀር መጠጊያ እንድትሆን ያደረጋት ቤተ ክርስቲያን በእምነት ኮትኩታ፣ በምግባር አንፃ ያስተማረቻቸው እነ ንጉሥ አርማህ ርኅሩኆች ብቻ ሳይሆኑ አስጠጉኝ ብሎ የመጣባቸውን አሳልፈው ለመስጠት ሰብአዊነት የተለያቸው ስላልነበሩ ጭምር ነው፡፡

ወርቅ ላበደረ ጠጠር፣ እህል ላበደረ አፈር እንዲሉ ይህን ውሉ ውለታ ለዋለች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተሰጠው መልስ ነው፡፡ የደረሱበት መረጃ ካለ ማስረጃን መሠረት አድርጎ እውነት ማሳወቅ አንድ ነገር ነው፣ ሐሰትን እውነት እያስመሰሉ ማቅረብና ሰውን ለብጥብጥ መጋበዝ ግን ጤነኛ አእምሮ ያለው፣ በእግዚአብሔር የሚያምን ሰው የሚፈጽመው አይደለም፡፡ በየጊዜው ቤተ ክርስቲያንን የሚያቃጥሉት፣ ክርስቲያኖችን የሚገድሉት፣ ንብረታቸውን የሚቀሙትና የሚያሳድዱት ከመጥፎ ድርጊታቸው እንዲታቀቡ መንግሥት እርምት ይወስዳል ቢባልም ምንም ነገር እንዳልተፈጸመ እየታለፈ፣ የማዘናጊያና የማረሳሻ ተግባር እየተፈጸመ ነው፡፡

ከምዕራባውያን የተኮረጀው ሥርዐተ ትምህርት ባልነበረበት ዘመን የሀገራቸው አምባሳደር የነበሩ፣ የውጭ ዲፕሎማት ሲመጣ አስተርጓሚ ሆነው ሲያገለግሉ የኖሩ ሊቃውንትን ያፈራችን ቤተ ክርስቲያን ከዋለችበት ላለማሳደር፣ ካደረችበት ላለማዋል እየተፈጸመ ያለው ግፍ መቆም አለበት፡፡ የሊቃውንቱን አስተዋጽኦ አክሊሉ ሀብቴ ‹‹ሆኖም እዚያ (ኢየሩሳሌም) የተደራጀው የመነኮሳት ማኅበር ኢትዮጵያን በመወከል ወደ ኢጣሊያም፣ ወደ አርመንም፣ ወደ ቊስጥንጥንያም፣ በመሔድ ግንኙነት ፈጥሮ እንደነበርና ምን አልባትም ከአርመኖች ጋር በነበረው የቅርብ ግንኙነት አርመኖች ፊደላቸውን ሊቀረፁ የቻሉት ከኢትዮጵያ ፊደል እንደሆነም ይነገራል፡፡ ወደ ኢየሩሳሌም በሚመላለሱበት ዘመን እግረ መንገዳቸውንም ከሱዳንና ከግብፅ ክርስቲያኖች ጋር የቅርብ ግንኙነት መፍጠራቸው ይታመናል፡፡ የቀድሞዎቹ የኢትዮጵያ ምሁራን መነኮሳት ፈር ቀዳጅ አስተዋጽኦ እንዲሁ መጠናት የሚገባው ነው›› (አክሊሉ፣ ፷፪) በማለት ገልጠውታል፡፡

ቤተ ክርስቲያን ልጆቿ ሰው አክባሪ፣ ሀገር ወዳድ፣ የሥራ ፍቅር ያላቸው፣ የራሳቸውን የማያስነኩ፣ የሌላውን የማይፈልጉ አድርጋ ስታሳድጋቸው ጠብ አጫሪነትን፣ በጉልበታቸው የሚመኩ መሆንን እንዲጸየፉ በማድረግ ነው፡፡ ጠላታቸውን በጽናትና በትዕግሥት እንዲቋቋሙ፣ ሀገርና ሃይማኖት ሊያጠፋ የመጣውን የጥፋት ኃይል እንዳያሸንፍ ያደረገች ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ይህ ድርጊቷ ያበሳጫቸው ምዕራባውያን በዘመናዊ ትምህርት ሰበብ በየሴሚናሪዎቻቸውና ኮሌጆቻቸው አስተምረው የላኳቸው ወገኖቻችን ነባሩን የኢትዮጵያ ሃይማኖትና፣ የክርስቲያኖች ተጋድሎ የሚያናንቅ፣ መልኩ የእኛ ቢሆንም የነጭ ጉዳይ አስፈጻሚ ሀገሪቱን ለባዕድ አሳልፎ ለመስጠት የባለቤትነት ስሜት የሚያድርበት እንዳይሆን አእምሮውን ለውጠው ሲልኩት ኖረዋል፡፡ በመመረቂያ ጽሑፍ ሰበብ ቤተ ክርስቲያንን ያለ ስሟ ስም፣ ያለ ግብሯ ግብር እየሰጡ የዘመናችን ተመራማሪ ነን ባዮች የግብር አባት ሆኑ፡፡ በዚህ ተግባራቸውም ትውልዱ በሰላም ውሎ እንዳይገባ እንቅልፍ ላጡ ወገኖች መንገድ መሪ የጥፋት ተባባሪ ሆነው አልፈዋል፡፡ ይህን ለማረጋገጥ ራሳቸውን ተሐድሶ ብለው የሠየሙ አካላት በተለያዩ የኅትመትና የብሮድካስት ሚዲያዎች በቤተ ክርስቲያን ላይ የሚያወርዱትን የስድብ ዶፍ መመልከት ይቻላል፡፡ በአካል መግዛት ያልተቻላቸውን ኢትዮጵያውያንን በአእምሮ ለመግዛት መሰሎቻችንንና በሥጋ የሚዛመዱንን አእምሮ እየለወጡ የሚልኩልንንና እነሱም አልፎ ሒያጅ መንገደኞችና ለቤተ ክርስቲያን ጥላቻ ያደረባቸውን ወገኖች እየጠየቁ የጻፉትን አሉባልታ በትክክለኛ ማስረጃ በመሞገት፣ የዕውቀታቸውን ግልብነት፣ የመረጃቸውን ተራነት፣ የትነታኔያቸውን አመክንዮ አልባነት ማሳየት ይኖርብናል፡፡ አጥፊዎች ታጥቀው ሲዘምቱብን ዝም ብሎ ማየት እሳት መቃጠሉን የሰማ የዋህ እኔስ ሣር ውስጥ ተደብቄያለሁ በማለት የመለሰውን የሚያስታውስ ይሆናል፡፡

ቱሪስቶች ሊጐበኙ የሚመጡት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ገዳማት፣ አድባራት፣ ሥዕላት፣ የብራና መጻሕፍትና ንዋያተ ቅድሳት እንዲሁም ክርስቲያን ነገሥታት የገነቧቸውን አብያተ ክርስቲያናት፣ ሐውልቶችና አብያተ መንግሥታት ለመጎብኘት ነው፡፡ ይህን አስተዋጽኦ ያደረገችልን ቤተ ክርስቲያን መደገፍና መጠበቅ ሲገባ ስትጠቃ ዝም ብሎ ማየት ማሯን እንጂ ንቧን አልፈልግም እንደ ማለት ይቈጠራል፡፡ ለጥፋት የተሰለፉ ወገኖች በቤተ ክርስቲያንና በምእመናን ላይ አደጋ ሲያደርሱ የግለሰቦች ጉዳይ እየመሰለ ይቀርባል፡፡ በመገናኛ ብዙኃን ይነገራል፡፡ በሌሎች እምነቶች ላይ የሚፈጸመው ወይም ራሳቸው ፈጽመው ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮሃል የተባለውን ለሚፈጽሙት ግን ከመገናኛ ብዙኃን ጀምሮ የሚሰጠው ሽፋን የሚገርም ነው፡፡ ይህም ክርስቲያኖች ሲገደሉ፣ አብያተ ክርስቲያናት ሲቃጠሉ መረጃው በቶሎ እንዳይነገር ከተቻለም ተዳፍኖ እንዲቀር ለማድረግ እየተሠራ መሆኑን እንድንጠረጥር የሚያደርግ ነው፡፡ ለምሳሌ በቡኖ በደሌ የተፈጸመውን ሰቆቃ በሥልጣን ላይ የተቀመጡ አካላት ወንጀሉን የፈጸሙት አካላት በእምነት ስለሚመስሏቸው ለማዳፈን ሞክረዋል፡፡ በሰሜን ሸዋና በኬሚሴ በክርስቲያኖችና በአብያተ ክርስቲያን ላይ የደረሰው ጥፋት በመገናኛ ብዙኃን የተነገረው ጥፋቱ ከተፈጸመ ከአራት ቀናት በኋላ መሆኑን ኢትዮጲስ ጋዜጣ በሚያዝያ ፮ ዕትሙ አስነብቧል፡፡ በበሻሻ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ እና አካባቢው አብያተ ክርስቲያን ተቃጥለውና ምእመናን ተገድለው አጥፊዎችን መያዝ ሲገባ መረጃው ያላቸውን ክርስቲያኖች ለመያዝ ይደረግ የነበረው ወከባ የቅርብ ጊዜ ትዝታ ነው፡፡

ይቆየን!

ምንጭ ፤ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ከግንቦት ፲፮-፴ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም

የብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ ህልፈተ ሕይወት

 

ያቆን ዘአማኑዔል አንተነህ

ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ በቀድሞው አጠራር በሰሜንና በጌምድር ጠቅላይ ግዛት በአሁኑ ደቡብ ጎንደር ዞን አስተዳደር በደራ ወረዳ አፈሯ እናት በመካነ ሰማዕት ቅዱስ ገላውዴዎስ ደብር ልዩ ስሙ አባ ጉንቸ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ከአባታቸው ከአቶ ፈንታ ወልድዬ ከእናታቸው ከእሙሐይ ጥዑምነሽ አብተው በ፲፱፻፳፯ ዓ/ም ግንቦት ፳፱ ቀን ተወለዱ፡፡ብፁዕነታቸው በአባታቸውና በእናታቸው በሥርዓትና እንክብካቤ ካደጉ በኋላ ዕድሜያቸው ለትምህርት ሲደርስ በወላጆቻቸው መልካም ፈቃድ በተወለዱበት በመካነ ሰማዕት ቅዱስ ገላውዴዎስ ቤተ ክርስቲያን ከታዋቂው የድጓ መምህር ከየኔታ ኃይሉ ፊደል ቆጥረው ዳዊት ከደገሙ በኋላ ጾመ ድጓ፤ ውዳሴ ማርያም ዜማ እስከ አርያም ክስተት አጠናቀው ተመርዋል፡፡

የቁም ጽሑፍ ከአጎታቸው ከቀኝ ጌታ ዓለሙ ወልድዬ ተምረው ከሕጻንነታቸው ጀምሮ ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ከእግዚአብሔር በተሰጣቸው ፀጋ የዲቁና ማዕረግ ከብጹዕ አቡነ ሚካኤል ደብረ ታቦር ከተማ ተቀብለዋል፡፡ ብፁዕነታቸው ባላቸው የትምህርት ፍላጎት መሠረት ትምህርታቸውን በመቀጠል ቅኔ ጎጃም ሞጣ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተ ክርስቲያን ከመምህር ፀሐይ ተምረዋል፡፡ በተጨማሪም የቅኔ ትምህርታቸውን ለማጠናከር ወደ ሰሜን ሽዋ በመሄድ ምንታምር ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ከየኔታ ኃይለ ጊዮርጊስ በመግባት ቅኔ በመማር ተቀኝተዋል፡፡ ዝማሬ መዋሥዕት ለመማር ወደ ደቡብ ጎንደር ተመልሰው ከየኔታ መርዓዊ ዙርአባ በመግባት የዝማሬ መዋሥዕት ትምህርታቸውን አጠናቀው በመምህርነትም ተመርቀዋል፡፡ ከዛም ወደ ደብረ ፅጌ ተመልሰው በመሄድ ከየኔታ ገብረ እግዚአብሔር ደብረ አባይ ቅዳሴ ተማሩ፡፡ ከመምህር ገብረ ሕይወት ሐዲሳት፤ ፍትሐ ነገስት አንድምታ ትርጓሜ፤ ዳዊት  አንድምታ ትርጓሜ፤ ውዳሴ ማርያም  አንድምታ ትርጓሜ፤ ባሕረ ሐሳብ  የኪዳንና ትምህርተ ኅቡአት አንድምታ ትርጓሜም ተምርዋል፡፡

በደብረ ፅጌ በነበሩበት ወቅት ትንቢተ ኢሳይያስና ትንቢተ ዳንኤል አንድምታ ትርጓሜና የቀሩትን መጻሕፍተ ብሉያት ተምረዋል፡፡ በደብረ ፅጌ ከመምህር ቀለመወርቅ አቋቋምም ለመማር ችለዋል፡፡ በወቅቱ ዘመናዊ ትምህርት ለመማር በነበራቸው ፍላጎት ኃይሌ ደጋጋ ከሚባል ትምህርት ቤት ገብተው ከ፩ኛ እስከ ፰ኛ ክፍል በደብረ ጽጌ ተምረዋል፡፡ ብፁዕነታቸው በመንፈሳዊ ትምህርት ቤት እያሉ ከአጎታቸው በተማሩት ቁም ጽሑፍ ተአምረ ማርያም ፤ ፍትሐ ነገስት፤ ፬ቱ ወንጌላትና መልእክተ ጳውሎስ እስከ ዮሐንስ ራእይ እንዲሁም ዚቅ በእጃቸው ጽፈዋል፡፡  ቤተ ክርስቲያንን በመንፈሳዊ አባትነት ለማገልገል መንፈሳዊ ሕይወታቸውን በማጠናከር ደብረ ሊባኖስ ገዳም ገቡ፡፡ አገልግሎታቸውንም በቅንነት፤ በታማኝነትና በትሕትና እየፈጸሙ ከገዳሙ ከቆዩ በኋላ በዛው ገዳም መንኩሰዋል፡፡ ስማቸውም መምህር አባ ኅሩይ ፈንታ እየተባሉ ይጠሩ ነበር፡፡ ከዚያም በመቀጠል ከብፁዕ አቡነ ሚካኤል ኤርትራዊ የቅስና ማዕርግ ተቀበሉ፡፡ብፁዕነታቸው ቤተ ክርስቲያኗን ለማገልገል ጽኑ ፍላጎት ስለነበራቸው ወደ አርባ ምንጭ በመሄድ የሀገረ ስብከቱ ስብከተ ወንጌል ክፍል ኃላፊ ሆነው በሀገረ ስብከቱ ለመጀመሪያ ጊዜ የካህናት ማሰልጠኛ እንዲከፈት ከፍተኛ ጥረት አድርገዋል፡፡ በወቅቱ ከነበሩት ሊቀ ጳጳስ መመሪያ እየተቀበሉ ማሰልጠኛው እንዲከፈትም ሆኗል፡፡ በዚሁ በአርባ ምንጭ ቆይታቸውም ከብፁዕ አቡነ ሰላማ የቁምስና ማዕርግ ተቀብለዋል፡፡ ብፁዕነታቸው በደብረ ሊባኖስ ገዳም ለመኖር ባላቸው ፍላጎት መሠረት ከአርባ ምንጭ ተመልሰው የደብረ ሊባኖስ ገዳም አንዱ አካል በሆነው በደብረ ጽጌ አገልግሎት እየሰጡ ለሕዝበ ክርስቲያኑ አባት በመሆን ስብከተ ወንጌል እያጠናከሩ ለብዙ ዓመታት ቆይተዋል፡፡

ከዚያም ለከፍተኛ የቤተ ክርስቲያን ማዕርግና አገልግሎት ታጭተው ወደ አዲስ አበባ ሄዱ፡፡ ጥር  ፲፫ ቀን በ፲፱፻፸፩ ዓ.ም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለሃይማኖት ፓትርያርክ ሊቀ ጳጳስ ዘኢትዮጵያ  ከተሸሙት ከ፲፫ቱ ሊቃነ ጳጳሳት መካከል አንዱ በመሆንም ብፁዕ አቡነ ኤልሳዕ ተብለው በአንብሮተ ዕድ ቆጶስነት ማዕርግ ተቀብለዋል፡፡

የብፁዕነታቸው የ፵ ዓመታት የሥራ ዘመን

ከ፲፱፻፸፩ አዲስ ዓ.ም እስከ ፲፱፻፸፮ ዓ.ም ድረስ የጅማ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው ተሾሙ፡፡  ለመጀመሪያ ጊዜ ሥራ የጀመሩበት ሀገረ ስብከትም ነበር፡፡ በዚሁ ሀገረ ስብከት መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት ሰጥተዋል፡፡ በጅማ ሀገረ ስብከት ብፁዕነታቸው ተመድበው ሲሄዱ የካህናት ማሰልጠኛ የሌለ በመሆኑ ዲያቆናት፤ካህናት፤መምህራን ካላቸው እውቀት በተጨማሪ በሥልጠና ከዘመኑ ጋር ተዋሕደው ቤተ ክርስቲያናቸውን እንዲያገለግሉ ለማድረግ የካህናት ማሰልጠኛ ከፍተዋል፡፡ ከነበሩት አብያተ ክርስቲያናት በተጨማሪ ፶ አዳዲስ አብያተ ክርስቲያናት በመትከል ሕዝቡን በማስተማርና በመምከር ቅዳሴ ቤታቸውን አክብረው ቤተ ክርስቲያን እንድትስፋፋ አድርገዋል፡፡

ከ፲፱፻፸፮ ዓ.ም እስከ ፲፱፻፸፰ ዓ.ም ድረስ የከፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው ተመድበው ሲሄዱም ሕዝበ ክርስቲያኑን በማስተባበር ተዋሕዶ ሃይማኖት እንዲስፋፋ ባላቸው ጠንካራ አቋም ፳፮ አብያተ ክርስቲያናትን በመትከል ቅዳሴ ቤታቸውንም አክብረዋል፡፡

ብፁዕነታቸው ከ፲፱፻፸፰ ዓ.ም እስከ ፲፱፻፹፩ ዓ.ም ድረስ ለ፬ ዓመታት የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ፀሐፊና የጠቅላይ ቤተ ክህነት ፍትሕ መንፈሳዊ የበላይ ጠባቂ ሆነው በተመደቡበት ወቅት በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ ሀገራት የቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊና ማህበራዊ አገልግሎት እንዲጠናከርና እንዲስፋፋ በማድረግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክተዋል፡፡ በቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ፀሐፊነት ለ፬ ዓመታት ቤተ ክርስቲያኗን እያገለገሉ በቆዩበት ወቅት የጽሕፈት ቤቱን አደረጃጀት በሚገባ በመምራት የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ በአግባቡ እንዲፈጸም በማድረግ ከብፁዕ ወቅዱስ አባታችን አቡነ ተክለ ሃይማኖት ፓትርያርክ የሚሰጡ መመሪያዎችን በመተግበርና በማስተግበር ለቤተ ክርስቲያናችን ትልቅ ሥራ ሰርተዋል፡፡

 ከ፲፱፻፹፩ ዓ.ም እስከ ፳፻፩ ዓ.ም ድረስ ለ፳ ዓመታት የደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ሆነው ሲመደቡ ሀገረ ስብከቱ አዲስ ከመሆኑ የተነሳ ለሊቀ ጳጳስ ማረፊያ (መንበረ ጵጵስና) የሌለው ከመሆኑም በላይ የሀገረ ስብከቱ አደረጃጀትም ገና ብዙ ሥራ ይጠይቅ ነበረ፡፡ በአዲስ መልክ ለማደራጀት ብዙ ድካም የሚጠይቅም ስለነበረ ብፁዕነታቸው ከእግዚአብሔር በተሰጣቸው ፀጋ ራሳቸው አቅደው ሀገረ ስብከቱ ምንም ገንዘብ ባይኖረውም መጀመሪያ መንበረ ጵጵስና መሠረት እንዳለበት ወሰኑ፡፡ ሕዝበ ክርስቲያኑን በማስተባበር አብያተ ክርስቲያናቱም የተቻላቸውን እንዲያወጡና ሀገረ ስብከቱን እንዲያጠናክሩ በማስተማር ከአዲስ አበባና ከውጪ ሀገራት ገንዘብ በማሰባሰብ ለመጀመሪያ ጊዜ ፲ ክፍል ያለው መንበረ ጵጵስና፤  ፳፩ ክፍል ያለው የሀገረ ስብከት ቢሮ ፤ ፩ ንብረት ክፍል፤ ፩ አዳራሽ እና ፩ መጋዝን በማሠራት ሀገረ ስብከቱ እንዲጠናከር በማድረግ ሠራተኞችን አደራጀተው የተሠራውን መንበረ ጵጵስና ከተለያዩ ቦታ የተጠሩ እንግዶች በተገኙበት መርቀው ሀገረ ስብከቱ በይፋ የመንበረ ጵጵስና ቢሮ አንዲኖረው አድርገዋል፡፡

ብፁዕነታቸው ወደ ደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ተመድበው ሲሄዱ ጥንታዊና ታሪካዊ የሆነው የተክሌ ምስክር አቋቋም ጉባኤ ቤት ተዳክሞ ስለነበረ የምስክር አቋቋም ጉባኤ ቤቱን ከአካባቢው ተወላጆች ጋር በመመካከር በአዲስ መልክ በማቋቋም ጉባኤ ቤቱ እንዲጠናከር በማድርግና ዘመናዊ ጉባኤ ቤት በማሠራት በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ (ዶክተር) አስመርቀው ለጉባኤ ቤቱ አድራሾች በጀት አስበጅተው እንዲጠናከር አድርገዋል፡፡ በ፳ ዓመታት የደቡብ ጎንደር ሊቀ ጵጵስና አገልግሎታቸው ውስጥ ሕዝበ ክርስቲያኑን በማስተባበር ቦታ ከመንግሥት በማስፈቀድ ፮፻፹፭ አዳዲስ አብያተ ክርስቲያናት በሀገረ ስብከቱ እንዲተከሉ በማድረግ የቤተ ክርስቲያን ማስፋፋት ሥራ ሠርተዋል፡፡ በደቡብ ጎንደር ሀገረ ስብከት ተተክለው ከቆዩት አብያተ ክርስቲያናት መካከል በደብርነት ያሳደጓቸው ከ፭፻ በላይ ሲሆኑ ወደ አንድነታቸው እንዲመለሱ ያደረጓቸው ገዳማትም ፲፪ ናቸው፡፡ ከእነዚህም በዋናነት ከሚጠቀሱት መካከል ጣና ቂርቆስ፤ጣራ ገዳም እና ምጽሌ ፋሲለደስ በምሳሌነት ይጠቀሳሉ፡፡

ወደ ሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት በቅዱስ ሲኖዶስ መልካም ፈቃድ ሲመደቡ የመጀመሪያ ሥራቸው የሀገረ ስብከቱን ሰላም ማስጠበቅ ነበር፡፡ ሠራተኛው ተግባብቶ ሥራውን እንዲሠራ የተለያዩ ሥራዎችንም ሠርተዋል፡፡ በዚህም በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ፓትርያርክ «የሰላም አባት» የሚል የክብር ዋንጫ ተሸልመዋል፡፡ ብፁዕነታቸው ሀገረ ስብከቱ በልማት ጠንክሮ አብያተ ክርስቲያናት ተስፋፍተው ማየት የሁልጊዜ ሕልማቸው ነው፡፡ሀገረ ስብከቱ የራሱ የሆነ የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ኖሮት፤ ማኀበረ ካህናትንና ምእመናንን አሰባስቦ፤ ስለስብከተ ወንጌል መስፋፋት፤ ስለ ቤተ ክርስቲያን ልማት፤ ስለመልካም አስተዳደርና ሌሎችንም የቤተ ክርስቲያን ጉዳዮች ተሰባስቦ ለመወያየት የራሱ የሆነ የመሰብሰቢያ አዳራሽ አልነበረውም፡፡ ለዚህም በመንበረ ጵጵስናው ግቢ ከሚገኘው ቦታ በስተደቡብ በኩል ዘመናዊ ቢሮ ያለው ሁለገብ የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ለመሥራት ራሳቸው አቅደው ሥራው እንዲጀመር በማድረግ የሕንፃ ማሰሪያ ገንዘቡን በተለያዩ ወረዳዎች ቆላ ደጋ ሳይሉ፤ አቀበት ቁልቁለት ሳይበግራቸው፤ ሕዝበ ክርስቲያኑን በማስተባበር ገንዘብ በማሰባሰብ በተጨማሪም ከክህነትና ከንዋየ ቅድሳት መባረኪያ የሚገኘውን ገቢ በሙሉ ለሕንፃ ግንባታው ሥራ እንዲውል በመፍቀድ ከስድስት መቶ ሽህ ብር በላይ በብፁዕነታቸው ስም ተበርክቷል፡፡

የሀገረ ስብከቱ ንብረት በሆነው በሐዋርያው ጳውሎስ ግቢ ባለ ፬ ፎቅ የገቢ ማስገኛ ሕንፃ ለመገንባትና ሌሎችንም ሥራዎች በግቢው ለመሥራት ዕቅድ አውጥተው የመሠረት ድንጋይ አስቀምጠዋል፡፡ በድርቡሽ ወቅት ከጠፉት ከ፵፬ቱ አብያተ ክርስቲያናት መካከል ፫ቱ ምዕት ቤተ ክርስቲያን በቦታው ለመመለስ ብፁዕነታቸው ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥተው አዲስ ኮሚቴ በማቋቋም በከፍተኛ ጥረት ቀደም ሲል ከነበረበት ቦታ ላይ የ፫ቱ ምዕት ቤተ ክርስቲያን መቃረቢያ እንዲሠራ በማድረግ ታቦተ ሕጉ እንዲገባና ቀድሰው ቅዳሴ ቤቱን አክብረው ታሪክ እንዲመለስ አድርገዋል፡፡ በሰሜን ጎንደር ሀገረ ስብከት ከ፭፻ በላይ አዳዲስ አብያተ ክርስቲያናት እንዲተክሉ በማድረግ ምእመናን እንዲበዙና ቤተ ክርስቲያን እንድትስፋፋ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርከተዋል፡፡ በላይ አርማጭሆ ወረዳ ትክል ድንጋይ ገዳም በበቅሎ በመሄድም አዲስ ገዳም እንዲመሠረት አድርገዋል፡፡ በተለይ ለሀገረ ስብከቱ ካቀዷቸው እቅዶች መካከል፤ በመንበረ ጵጵስናው ግቢ በስተምስራቅ በኩል የሀገረ ስብከቱ ንብረት የሆነ ፬ ክፍል ቤት ተሠርቶበት ከሚገኘው ቦታ ላይ ባለ ፬ ፎቅ ሕንፃ በመሥራት ለገቢ ማስገኛ አገልግሎት እንዲውል አቅደዋል፡፡ ይህን ሥራና ሌሎችንም ባቀዱት መሠረት ለማስፈጸም ደፋ ቀና ሲሉ ባደረባቸው ሕመም ምክንያት የግልና የጎንደር ሪፈራል ሆስፒታል በሕክምና ሲረዱ ከቆዩ በኋላ ሕመሙ ሊሻላቸው ባለመቻሉ በተወለዱ በ፹፬ ዓመታቸው ግንቦት ፲፯ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም. ዐርፈዋል፡፡ የቀብር ሥነ ሥርዓታቸውም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት የመንግሥት ተወካዮች ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ሕዝበ ክርስቲያኑ በተገኙበት በመካነ ሰማዕት ቅዱስ ገላውዲዎስ ቤተ ክርስቲያን ግንቦት ፳ ይፈጸማል፡፡

የጥቅምት ወር ፳፻፲ ዓ.ም ምልዓተ ጉባኤ መጠናቀቁን ተከትሎ ከቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

ጥቅምት ፳፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ መግለጫ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ስብሰባ በዓመት ሁለት ጊዜያት እንዲሆን በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ንዑስ አንቀጽ 164 በተደነገገው መሠረት ምልዓተ ጉባኤው ከጥቅምት 6 ቀን 2010 ዓ.ም. ጀምሮ የመንበረ ፓትርያርኩን አጠቃላይ ሰበካ መንሳዊ ጉባኤና ዓመታዊውን የቅዱስ ሲኖዶስ መደበኛ ስብሰባ ለ15 ቀናት ሲያካሒድ ሰንብቷል፡፡

በዚሁ መሠረት ቅዱስ ሲኖዶስ የመክፈቻውን ሥርዓተ ጸሎት ካደረሰ በኋላ ወሳኝ በሆኑ የአጀንዳ ነጥቦች ተወያይቶ የሚከተሉትን ውሳኔዎች አሳልፎአል፡፡

  1. ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ በጉባኤው መክፈቻ ያደረጉት ታሪካዊ ንግግር የቤተ ክርስቲያናችንን ሁለንተናዊ ሕይወት የቃኘ፣ ለሀገራችንና ቤተ ክርስቲያናችን ዕድገትንና የሰላም አስፈላጊነትን በስፋት የገለፀ በመሆኑ ጉባኤው በሙሉ ድምፅ ተቀብሎታል፡፡
  2. የሠላሳ ስድስተኛውን የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንሳዊ ጉባኤ የገራ መግለጫ አንዳንድ ማሻሻያ በማድረግ የጋራ መግለጫው የ2010 በጀት ዓመት ተግባር ሆኖ ያገለግል ዘንድ ምልዓተ ጉባኤው ተስማምቷል፡፡
  3. የቤተ ክርስቲያናችን እምነትና ሥርዓተ አምልኮ እስከ አሁን ደረስ ተከብሮና ተጠብቆ እንደኖረ ሁሉ አሁንም ከመንበረ ፓትርያርክ እስከ አህጉረ ስብከት የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ያለው የመንፈሳዊና የማኅበራዊ አገልግሎት መዋቅር በበለጠ ተጠናክሮ ይቀጥል ዘንድ መመሪያ ተሰጥቷል፡፡
  4. በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ሒሳብና በጀት መምሪያ ተዘጋጅቶ የቀረበው የ2010 ዓ.ም. በጀት የክፍያው ጣሪያ ተጠብቆ ሥራ ላይ እንዲውል ምልዓተ ጉባኤው ተስማምቷል፡፡
  5. የአንድ ሀገር ዕድገትና መሠረታዊ ፍላጎት ግቡን ሊመታ የሚችለው የሃይማኖቱና የሞራል ስሜቱ የማይወቅሰውን በሚሠራ፣ በመልካም ስነ ምግባር በታነፀ፣ የሥራን ክቡርነት በተረዳና እግዚአብሔርን መፍራት የጥበብ መጀመሪያ መሆኑን ባስተዋለ ትውልድ ተደግፎ ሲገኝ ስለሆነ፣ ኅብረተሰቡ ይህኑ በመረዳት
  • በትዕግሥትና በመቻቻል፣
  • በመካባበርና በመናበብ፣
  • በመደማመጥና በመግባባት መንፈስ በአንድነት ተባብሮ እንዲሠራ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪውን አስተላፏል፡፡
  1. የነገድ፣ የሃይማኖትና የጾታ ልዩነት ሳይኖር ለጋራ ህልውና ለጋራ ልማትና ለጋራ ብልጽግና ለሀገራችን ኢትዮጵያና ለጎረቤት አህጉር ብሩህ ተስፋ ሰንቆ እንደሚመጣ የተነገረለት የዓባይ ሕዳሴ ግድብ ግንባታ ፕሮጀክት ኢትዮጵያዊነቱን እያስመሰከረ ስለመጣ አሁንም የፕሮጀክቱ ሥራ አሁንም የፕሮጀክቱ ሥራ ተጠናክሮ ለውጤት እስከሚበቃ ድረስ ሁሎችም ኢትዮጵያውያን አስፈላጊውን ድጋፍ በመለገስ እንዲተባበሩ ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳስባል፡፡
  2. ትውልድ ሁሉ የሙያና የስነ አእምሮ ብቃቱን አሳድጎ ሥራ የመፍጠር ክሂሎቱን እንዲያረጋግጥ ቅዱስ ሲኖዶስ ጥሪውን አስተላልፏል፡፡
  3. ዕቅድን በተግባር ለማረጋገጥ
  • ሠርቶ ለማግኘት
  • ውሎ ለመግባት
  • አድሮ ለመነሣት
  • ዘርቶ ለማምረት
  • ነግዶ ለማትረፍና በነፃነት ለመኖር ሰላም ያስልጋል፡፡

ስለዚህ ሀገራችን ኢትዮጵያ ለአፍሪካ አህጉር የነፃነት ምልክት እንደሆነች ሁሉ የሰላምና የጸጥታም ምልክት መሆን አለባት፤ ከዚህ አንፃር ሰሞኑን በተለያየ ምክንያት በወገኖቻችን መካከል የተከሰተው ግጭት ተወግዶ ሙሉ ሰላምን የማስፈኑ ሥርዓት ተፋጥኖ እንዲረጋገጥ፣ ከዚህም ጋር በግጭቱ ምክንያት ለተጎዱ ወገኖቻችን ከመንበረ ፓትርያርክ እስከ አህጉረ ስብከት የአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ድረስ ባለው መዋቅር ብር 6,000,000 (ስድስት ሚሊዮን) የገንዘብ ድጋፍ እንዲደረግ፡፡ እንዲሁም ከጥቅምት 27 ቀን 2010 ዓ.ም. ጀምሮ በመላ አገሪቱ ባሉት ገዳማትና አድባራት ለሁለት ሱባዔ ማለትም ለ14 ቀናት ያህል ጸሎተ ምሕላ እንዲደረግ ተወስኗል፡፡

  1. በውጭ ሀገር ከሚኖሩት አባቶች ጋር ቀደም ሲል ተጀምሮ የነበረው ዕርቀ ሰላም አሁንም ተጠናክሮ እንዲቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ አሳልፎአል፡፡
  2. በቃለ ዓዋዲው የቤተ ክርስቲያናችን መተዳደሪያ ደንብ መሠረት የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታዮች የሆኑት ወጣቶች በየአጥቢያ ቤተ ክርስቲያናቸው በሰንበት ትምህርት ቤት ተደራጅተው በየሰበካ ጉባኤው አመራር ሰጭነት እንዲማሩ ምልዓተ ጉባኤው አመራርን ሰጥቷል፡፡
  3. በምሥራቅ ሸዋ ሀገረ ስብከት የሚገኘው የዝዋይ ሐመረ ብርሃን ቅዱስ ገብርኤል ገዳም የካህናት ማሠልጠኛ ተቋም ወደ ኮሌጅ ደረጃ ማደግ ያስችለው ዘንድ ከክፉሉ ሊቀ ጳጳስ የቀረበውን ፕሮፖዛል ጉባኤው ተቀብሎ አጽድቆታል፡፡
  4. በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስም መንፈሳዊ ማሠልጠኛ አቋቁመው ለሚንቀሳቀሱ የተለያዩ ማኅበራት የሚያገለግል እስካሁን ድረስ የተዘጋጀ የማኅበራት ማደራጃ ደንብ የሌለ በመሆኑ ለወደፊቱ ሕገ ቤተ ክርስቲያኑንና ቃለ ዓዋዲውን መሠረት ያደረገ የማኅበራት ማደራጃ ደንብ በሕግ ባለሙያዎች እንዲዘጋጅ ጉባኤው ተስማምቶ ወስኗል፡፡
  5. በጋሻው ደሳለኝ የተባለ ግለሰብ በቤተ ክርስቲያኒቱ ውስጥ ለበርካታ ዓመታት ለምእመናን ሲያስተላልፍ የነበረው የክህደት ትምህርት በመረጃ ተስብስቦ ችግሩ ለቅዱስ ሲኖዶስ ከቀረበ በኋላ ከ15/02/2010 ዓ.ም. የክህደት ትምህርቱን በማውገዝ ከቤተ ክርስቲያናችን እንዲለይ ተደርጓል፣ በቤተ ክርስቲያናችን ስም እንዳያስተምር ተወግዟል፡፡
  6. በተመሳሳይ መልኩም በአሜሪካን ሀገር በዋሽንግተን ዲ.ሲ. የሚያገለግሉት አባ መዓዛ ክርስቶስ በየነ እያስተማሩ ያለው የክህደት ትምህርት ለቅዱስ ሲኖዶስ በመረጃ ቀርቦ የተረጋገጠባቸው ስለሆነ ሥልጣነ ክህነታቸው ተይዟል፤ ያሉበትን ቤተ ክርስቲያን ጨምሮ በማናቸውም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እንዳይሰጡ ታግደዋል፡፡
  7. ወልደ አብ በሚል ርእስ፤ ገብረ መድኅን በተባለ ግለሰብ የተጻፈው የክህደትና የኑፋቄ ትምህርት የቅብዓትንና የጸጋን የክህደት ትምህርት የሚያስፋፋ በመሆኑ ካህናትን ከካህናት ምእመናንን ከምእመናን የሚያጋጭ ከመሆኑ ጋር፤ ከቤተ ክርስቲያናችንም አልፎ በሀገራችን ሁከት ለማስነሣት ታስቦ የተዘጋጀ ሆኖ ስለተገኘ፣ መጽሐፉ ከማናቸውም አገልግሎት እንዲለይ ተወግዟል፡፡
  8. ለገዳማት መተዳደሪያ እንዲሆን የተዘጋጀው ደንብ ረቂቁ ተስተካክሎ የቀረበ በመሆኑ በሥራ ላይ እንዲውል ጉባኤው ተስማምቷል፡፡
  9. ተሐድሶ እየተባለ የሚጠራው የኑፋቄ እምነት ማኅበር እራሱን ኦርቶዶክሳዊ በማስመሰል የቤተ ክርስቲያኒቱን ህልውና እየተፈታተነ ከማስቸገሩ የተነሣ ቅዱስ ሲኖዶስ ቀደም ሲል ፀረ ተሐድሶ ኮሚቴ በየአህጉረ ስብከቱ ተቋቁሞ የመከላከልና ቤተ ክርስቲያኒቱን የመጠበቅ ሥራ እንዲያከናውን ውሳኔን መስጠቱ የሚታወስ ነው፡፡ አሁንም ከቤተ ክርስቲያኒቱ ማዕከላዊ አስተዳደር እስከ አህጉረ ስብከት ባለው መዋቅር የተቋቋመው ፀረ ተሐድሶ ኮሚቴ ተጠናክሮ የመከላከሉን ሥራ እንዲቀጥል ቅዱስ ሲኖዶስ አመራር ሰጥቷል፡፡

ምልዓተ ጉባኤው ከዚህ በላይ በተገለፁትና በሌሎችም መንፈሳዊና ማኅበራዊ ጉዳዮች ላይ ተወያይቶ አስፈላጊውን መመሪያ ከሰጠ በኋላ ስበስባውን በጸሎት አጠናቆአል፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን ለሀገራችንና ለዓለሙ ሁሉ ሰላሙን፣

ለሕዝባችን ፍቅር አንድነቱን ይስጥልን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር አሜን!

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአኵስም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ጥቅምት 21 ቀን 2010 ዓ.ም.

አዲስ አበባ – ኢትዮጵያ

ከመናፍቃን ስውር ደባ ራሳችንን እንጠብቅ

ጥቅምት ፲፰ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ከዲያብሎስ ጋር ተጋድሎዋን የጀመረችው በዓለመ መላእክት ነው፡፡ ቀስቱን ወርውሮ ዝናሩን አራግፎ ቤተ ክርስቲያንን ማሸነፍ ያልቻለው ዲያብሎስ ዛሬም በብዙ መልኩ እየተዋጋት ይገኛል፡፡ በማዕበል መካከል በምትቀዝፍ መርከብ የምትመሰለው ቤተ ክርስቲያን ሁልጊዜም አሸናፊ መሆኗ የታመነ ነው፡፡ ችግሩ መርከቧ ማዕበሉን ብትሻገርም በማዕበሉ የሚናወፁ መኖራቸው ነው፡፡ ከመርከቧ ተሳፋሪዎች ውስጥ ጥቂቶቹ በዓላማ አንዳንዶቹ ደግሞ በየዋህነት በማዕበሉ ተናውጠው ወድቀዋል፡፡ በዓላማ የሚወጡት ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊ በመልእክቱ “ከእኛ ዘንድ ወጡ፥ ዳሩ ግን ከእኛ ወገን አልነበሩም፤ ከእኛ ወገንስ ቢሆኑ ከእኛ ጋር ጸንተው በኖሩ ነበር፤ ነገር ግን ሁሉ ከእኛ ወገን እንዳልሆኑ ይገለጡ ዘንድ ወጡ” ብሎ የተናገረላቸው ናቸው (፩ኛ ዮሐ. ፪፥፲፱)፡፡

እነዚህ ለጥፋት የቆሙና ለገንዘብ ወይም ለሌላ ስውር ዓላማ ቤተ ክርስቲያንን የተዉ ናቸው፡፡ በየዋህነት የሚወጡት ግን በዕውቀት ማነስ፣ በይሉኝታና በመሳሰሉት ተታለው፣ በጠላት ወጥመድ ተጠልፈው የጠፉ ናቸው፡፡ እነዚህ ቀናውን መንገድ (በጎውን) የሚያሳያቸው ቢያገኙ የሚመለሱ ናቸው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ጠላቶች እነዚህን የዋሃን የሚያጠምዱባቸው ብዙ ዘዴዎች አሏቸው፡፡ ከእነዚህ መካከል የኅትመትና የምስል ወድምፅ ውጤቶችን በቅዱሳት ሥዕላት አስውበው በማውጣት የዋሃንን ማደናገርና ከቻሉ በቅዱሳት ሥዕላቱ ሸፍነው የሚፈልጉትን የኑፋቄ ትምህርት የቤተ ክርስቲያን አስመስሎ ማቅረብ ነው፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱሳት ሥዕላት ትልቅ ቦታ ይሰጣቸዋል፡፡ ቅዱሳት ሥዕላትን በሚገባቸው ቦታዎች ላይ ማስቀመጥና የሚገባቸውን ክብር መስጠት ኦርቶዶክሳዊ ትውፊት ነው፡፡ መንፈሳዊ መጻሕፍት ሲጻፉ በመጻሕፍቱ ውስጥ ታሪካቸው የተጠቀሱትን ቅዱሳን ሥዕል በፊት ገጽ ወይም በውስጥ ገጽ ማስቀመጥም የተለመደ ነው፡፡ ምእመናንም በጸሎት ቤታቸው ቅዱሳት ሥዕላትን በማስቀመጥ ለቅዱሳን የሚገባውን ክብር ይፈጽማሉ፡፡ ቅዱሳት ሥዕላትና ኦርቶዶክሳዊ ትውፊት ትልቅ ትስስር ያላቸው ናቸው፡፡ በዚህ ምክንያት ተሐድሶ መናፍቃን በቅዱሳት ሥዕላት የተሸፈኑ የኑፋቄ መጻሕፍትን ገበያ ላይ እስከሚያወጡ ድረስ የቅዱሳንን ሥዕል የያዘ መጽሐፍ ኦርቶዶክሳዊ መጽሐፍ እንደሆነ “ግምት ይወሰድ” ነበር፡፡ በጎውን ሁሉ የሚጠላና ለማስጠላት የሚሠራ ዲያብሎስ ዛሬ ላይ ቅዱሳንን ለማስጠላት ያነሣሣቸው አንዳንዶች የፊት ገጻቸው የቅዱሳን ሥዕላት ውስጣቸው ደግሞ ቅዱሳንን የሚሳደቡ መጻሕፍትን በማሳተም እያሠራጩ ነው፡፡

ከእነዚህ መጻሕፍት መካከል በ፳፻፬ ዓ.ም የተወገዘው፣ የከሣቴ ብርሃን ድርጅት አባል የሆነው ጌታቸው ምትኩ የጻፈው “ገድል ወይስ ገደል” የሚለው መጽሐፍ አንዱ ነው፡፡ ይህ መጽሐፍ በፊት ለፊት ገጹ የአቡነ አረጋዊን ሥዕል የያዘ ሲሆን ውስጡ ግን ቅዱሳንን የሚሳደብና የሚነቅፍ ነው፡፡ “አቡነ ተክለ ሃይማኖት እግራቸውን ያጡት በጸሎት ሳይሆን በጦርነት ነው” ከሚለው ውሸት ጀምሮ የቅዱሳንን ተጋድሎ በማናናቅ በጸጋው የሚገኘውን ድኅነት በራሳቸው ጥረት የተኩ አድርጎ የሚያቀርብ የኑፋቄ መጽሐፍ ነው፡፡

“መሪጌታ ሠረቀ ብርሃን ዘወንጌል” በሚል ስም የተጻፈው “የዘመናት እንቆቅልሽ ሲፈታ” የሚለው የኑፋቄ መጽሐፍም ሌላኛው ሁነኛ ማስረጃ ነው፡፡ መጽሐፉ የአቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስን ሥዕል የሽፋን ገጹ ላይ በመለጠፍ የዋሃንን የሚያደናግር ነው፡፡ መጽሐፉን ወደ ውስጥ ገጹ ዘልቀን ስናየው ግን ቅዱሳንን አንድ በአንድ እያነሣ የሚሳደብ ነው፡፡ ብዙዎቹ የተሐድሶ መናፍቃን ጽሑፎች ሰይጣን “ጠላቶቼን ስደቡልኝ” ብሎ የቀጠራቸው ጸሓፊዎች የጻፏቸው የሚመስሉና ቅዱሳንን የሚሳደቡ ናቸው፡፡ ይህ መጽሐፍም ከእነዚህ መጻሕፍት አንዱ ነው፡፡

ሌላኛው መጽሐፍ ደግሞ “በውኑ በማርያም ማመን ይገባሃልን?” በሚል ርእስ “መጋቤ ጥበብ ሰሎሞን” በተባለ ሰው የተጻፈው ነው፡፡ ይህ ግለሰብ በ፳፻፬ ዓ.ም ከተወገዙት ፲፮ መናፍቃን መካከል አንዱ ነው፡፡ መጽሐፉ በፊት ገጹ ላይ የእመቤታችንን ምስለ ፍቁር ወልዳ ሥዕል አድርጎ በውስጥ ገጹ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን የሚሳደብ መጽሐፍ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያደገ ሰው ይቅርና ጠላት እንኳን በእመቤታችን ላይ ሊናገረው የማይገባውን ብዙ ጸያፍ ነገር አካቷል፡፡ መጽሐፉ፣ ክብር ይግባትና “ማርያም ወላዲተ አምላክ መባል የለባትም”፤ “ከዮሴፍ ጋር በወንድና በሴት ልማድ ኖራለች”፤ “ከጌታችን ውጪ ሌሎች ልጆች አሏት”፤ “ቤተ ክርስቲያን የምታመልከው እግዚአብሔርን ሳይሆን ማርያምን ነው”፤ ወዘተ. የሚሉ የጽርፈት አሳቦችን የያዘ የኑፋቄና የክህደት መጽሐፍ ነው፡፡

ይህ መጽሐፍ ለሁለተኛ ጊዜ ሲታተም አዲስ መጽሐፍ ለማስመሰልና ርእሱም ገበያ ስለከለከለ የተሻለ እንዲሸጥ በሚል እኩይ አሳብ “በእንተ ማርያም” በሚል ርእስ ወጥቷል፡፡ “በእንተ ማርያም” የሚለው ሐረግ የአብነት ተማሪዎች ቁራሽ ለመለመን በየቤቱ ሲዞሩ የሚጠቀሙበት ቋንቋ ነው፡፡ ማንኛውም ኦርቶዶክሳዊ ይህን ቃል ያውቀዋል፡፡ “በእንተ ማርያም” ተብሎ ተለምኖ ሳይሰጥ ዝም ብሎ የሚያልፍ ኢትዮጵያዊ ምእመን የለም፡፡ ይህን በማሰብ ይመስላል ተሐድሶ መናፍቃኑ የመጽሐፉን ርእስ ከ “በውኑ በማርያም ማመን ይገባሃልን?” ወደ “በእንተ ማርያም” በመቀየር እመቤታችንን የሚሳደብ መልእክት ያስተላለፉት፡፡

ጸሓፊዎቹ ሲጽፉ ራሳቸውን “ዲያቆን”፣ “ቄስ”፣ “መምህር”፣ “መጋቤ ጥበብ”፣ “መጋቤ ሐዲስ”፣ ወዘተ. በሚል መዓርግና ስያሜ ነው፡፡ መጻሕፍትን ብቻ ሳይሆን በዚሁ መልክ ባለቤት አልባ በራሪ ወረቀቶችን፣ ጋዜጦችን፣ መጽሔቶችን፣ የድረ ገጽ ጽሑፎችን፣ ሲዲዎችን፣ ቪሲዲዎችን፣ ወዘተ ያወጣሉ፡፡ ለምሳሌ ይህ በራሪ ወረቀት የእመቤታችንን ሥዕል የያዘ ነገር ግን ኢየሱስ ክርስቶስ (ሎቱ ስብሐት) “አማላጅ እንደሆነ ለማስረዳት” ተብሎ የተሠራጨ የመናፍቃን ትምህርት ነው፡፡

በ፳፻፬ ዓ.ም ከተወገዙት ግለሰቦች መካከል አንዱ የሆነው ጽጌ ስጦታው ከግብረ አበሩ ጋር በመሆን ባወጡት ሲዲም ላይ ግለሰቦቹ በአለባበሳቸው የቤተ ክርስቲያን መምህር መስለው ከመቅረባቸውም በላይ የሲዲው የሽፋን ገጽ የድንግል ማርያምና የአባ ሰላማ ከሣቴ ብርሃን ሥዕላትን ይዟል፡፡ እነዚህ ሁሉ ወጥመዶች የተዘረጉት ኦርቶዶክሳውያንን ከበረታቸው ለማስኮብለል ነው፡፡ እነዚህ መጻሕፍትና የምስል ወድምፅ ውጤቶች የእኛ መስለውን በስሕተት ገዝተናቸው ይሆናል፡፡ መጻሕፍቱን አንብበን፣ ሲዲዎችን ዐይተን የተደናገርንም እንኖር ይሆናል፡፡

ማንኛውንም ጉዳይ በሩቅ ዐይተን ውሳኔ ላይ ሳንደርስ ቀርበን መመርመር፣ ከእኛ በላይ የሆነውን እውነተኞች አባቶችን በመጠየቅ ራሳችንን ከስሕተት መጠበቅ ይገባናል፡፡ “በሩቅ ያዩት አህያ ፈረስ ይመስላል” እንደሚባለው በሽፋናቸው፣ በውጫዊ ይዘታቸው የሚበሉ መስለው ውስጣቸው የመናፍቃንን የክሕደት መርዝ የያዙ መጻሕፍት ይኖራሉ፡፡ መጻሕፍቱ ወይም የምስል ወድምፅ ውጤቶች ቅዱሳት ሥዕላትን ስለያዙ፣ በግእዝ ቋንቋ ስለተጻፉ ብቻ የእኛ ናቸው ማለት አይደለም፡፡

ከመናፍቃን ስውር ደባ ራሳችንን ለመጠበቅ ምን እናድርግ?

ተሐድሶ መናፍቃን በየጊዜው መልካቸውን እየቀያየሩ ከሚያዘጋጁት የጥፋት ወጥመድ ራሳችንን ከመከላከል እና ሌሎችን ከመጠበቅ አኳያ ማድረግ ያለብንን ጥቂት የጥንቃቄ ነጥቦችን እንመልከት፡-

፩ኛ. ቤተ ክርስቲያንን እና የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ማወቅ

ቤተ ክርስቲያን በሰማይ ያሉ የቅዱሳን፣ በምድር ያሉ የክርስቲያኖች አንድነት ናት፡፡ ይህች አንድነት አሐቲ፣ ቅድስት፣ ሐዋርያዊትና ኵላዊት ናት፡፡ ክርስቶስ በደሙ የመሠረታት ስለሆነች የክርስቶስ አካል ናት፡፡ የክርስቶስ አካሉ የሆነች ቤተ ክርስቲያንን ለማረም መነሣት “እግዚአብሔርን ለማረም” እንደ መነሣት ነው፡፡ በአስተምህሮዋም ነቅ የሌለባትና ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የተቀበለችውን ትምህርት ከሐዋርያት ጀምሮ ለዓለም ስትመግብ የኖረችና የምትኖር ናት፡፡ ትምህርቷ እንክርዳድ ያልተቀላቀለበት፣ እንግዳ የሆነ ትምህርት ያልታከለበት ጥንታዊና ቀጥተኛ ነው፡፡ አስተምህሮዋ ከአምላኳ የተቀበለችው ንጹሕ ዘር ነው፡፡ የምታስተምረው እግዚአብሔር ለዓለም የገለጠውን እውነት እንጂ ራሷ የፈጠረችውን ታሪክ አይደለም፡፡ የቤተ ክርስቲያን ድርሻ ከእግዚአብሔር የተቀበለችውን ለዓለም መመስከርና ማስተላለፍ እንጂ የተጣመመ ኖሮ ማቅናት፣ የጎደለ ኖሮ መሙላት፣ ያነሰ ኖሮ መጨመር፣ አላስፈላጊ የሆነ ኖሮ መቀነስ አይደለም፡፡ ሃይማኖት ከእግዚአብሔር ለቅዱሳን አንድ ጊዜ ፈጽሞ የተሰጠች መንገድ ናት፡፡ ይህን ለማስተካከል መሞከር ራስን በእግዚአብሔር ቦታ ማስቀመጥ ነው፡፡

ስለዚህ ሁልጊዜም ቤተ ክርስቲያንን እና አስተምህሮዋን ለማወቅ መትጋት ያስፈልጋል፡፡ ብዙ ማወቅ የሚቻለው በመማር ነው፡፡ ስንማር ቤተ ክርስቲያንን እና የቤተ ክርስቲያን የሆነውን ሁሉ ማወቅ እንችላለን፡፡ የቤተ ክርስቲያንን ሊቃውንትና መጻሕፍት ማወቅ እንግዳ በሆነ አዳዲስ ትምህርት ከመወሰድ ያድናል፡፡ “ሕዝቤ ዕውቀት ከማጣቱ የተነሣ ጠፍቷል” (ሆሴ. ፬፥፮) እንደተባለ ዕውቀት ማጣት ብዙ ችግሮችን ያመጣል፡፡ በሌሎች ካለመወሰድ አልፎ ሌሎችን ማትረፍ የሚቻለው በዕውቀት ላይ የተመሠረተ ክርስትናን ገንዘብ በማድረግ ነው፡፡ ስለዚህ ሁልጊዜ መማር፣ በመንፈሳዊ ዕውቀትና በመንፈሳዊ ሕይወት ማደግ ያስፈልጋል፡፡ ይህን ስናደርግ የቤተ ክርስቲያንን ድምፅ ከሌሎቹ ለይተን ማወቅ እንችላለን፡፡ የራሳችንን ካወቅን ደግሞ የሌሎችን የማደናገሪያ ቃል አንሰማም፡፡

፪ኛ. የቤተ ክርስቲያንን ጉዳይ ያገባኛል ብሎ መቀበል

ቤተ ክርስቲያን ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ባለው መዋቅሯ  ውሳኔዎችንና መመሪያዎችን ታስተላልፋለች፡፡ ውሳኔዎች እንዲፈጸሙ መመሪያዎች እንዲተገበሩ ሁሉም የድርሻውን መወጣት አለበት፡፡ ትግበራውን ለማገዝ መጀመሪያ የቤተ ክርስቲያንን ጉዳይ ጉዳዬ ብሎ መቀበል ያስፈልጋል፡፡ የኑፋቄ ትምህርት የሚያስተምሩ ሰዎች የሚወገዙት በትምህርት ያልበሰልነውን እንዳያታልሉ ነው፡፡ የኑፋቄ መጻሕፍት መልስ የሚሰጥባቸው እኛን ከኑፋቄ ለመጠበቅና በመንፈሳዊ ዕውቀታችን ለማሳደግ ታስቦ ነው፡፡ ትምህርት የሚሰጠው፣ ጉባኤ የሚዘጋጀው፣ የቤተ ክርስቲያን የውስጥ አገልግሎት የሚፈጸመው እንድናውቅ ብቻ ሳይሆን እንድንጸድቅም ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ዓላማ ልጆቿን በትምህርትና በምሥጢራት እግዚአብሔርን ወደ መምሰል ማሳደግ ነውና፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎችን መቀበል፣ ማክበርና መፈጸም፤ ጥያቄዎች ሲኖሩንም ኦርቶዶክሳዊ በሆነ መንገድ ማቅረብ፤ ከዚህም ባሻገር ከግለሰቦች ይልቅ ለቤተ ክርስቲያን መታዘዝ ኦርቶዶክሳዊ ትውፊት መሆኑን መረዳት አለብን፡፡ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ ግን የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎች እንዳይፈጸሙ የሚከለክሉ፣ በቤተ ክርስቲያን ስም ግለሰባዊ ፍላጎታቸውን የሚያራምዱ፣ ቅዱስ ሲኖዶስን የማውገዝ ሥልጣን የሌለው አስመስለው የሚያቀርቡ ተሐድሶ መናፍቃንን ሤራ ባለመረዳት የቤተ ክርስቲያንን መልእክት የማያከብሩ የዋሃን አሉ፡፡ በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዐተ ጉባኤ ከተወገዙ የተሐድሶ መናፍቃን ድርጅቶችና ግለሰቦች ጉባኤ ላይ የሚገኙ፤ የእነርሱን የኅትመትና የምስል ወድምፅ ውጤቶች የሚያከፋፍሉ፣ የሚሸጡ፣ የሚገዙ፣ የሚያነቡና የሚያዳምጡም አሉ፡፡ እነዚህ ሁሉ ክፍተቶች የተፈጠሩት የቤተ ክርስቲያንን መልእክት ጉዳዬ ብሎ ባለመስማትና ባለመቀበል ምክንያት ነው፡፡ ስለዚህ የቤተ ክርስቲያንን መልእክት ሰምቶ በመቀበል እንዲህ ዓይነት የመረጃ ክፍተቶችን መሙላት ከሁላችን ይጠበቃል፡፡

፫ኛ . ስለማናውቀው ነገር መጠየቅ

ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮዋን የምታስፋፋባቸው ብዙ መንገዶች አሏት፡፡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ረድኤተ እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ የጻፏቸው ቅዱሳት መጻሕፍት ተጠቃሽ የአስተምህሮ ማስፋፊያ መንገዶች ናቸው፡፡ የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍት የምንላቸው የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ የሚያስጠብቁ ናቸው፡፡ እነዚህ መጻሕፍት የቤተ ክርስቲያን መሆናቸውን ማወቅ የምንችለው ያለንን ዕውቀትና ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን በመጠቀም ነው፡፡ ስለዚህ የቤተ ክርስቲያን መጻሕፍትን ከሌሎች ለመለየት የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ማወቅ ግድ ይሆናል፡፡ ይህም በአንድ ጀንበር የሚሳካ ቀላል ተግባር ባይሆንም መፍትሔው ግን ከባድ አይደለም፡፡ መጻሕፍትን ለመግዛት፣ የምናነባቸውን ለመምረጥ፣ ስናነብ ያልገባንን ለመረዳት፣ ትክክል መስሎ ያልታየን ወይም ያደናገረን ነገር ሲኖር ለማጥራት የቤተ ክርስቲያንን ሊቃውንት እና ከእኛ የተሻለ መንፈሳዊ ብስለት ያላቸውን መምህራን መጠየቅ መልካም ይሆናል፡፡

“ሊሆን ይችላል” ወይም “ለእኔ ተስማምቶኛል” በሚል ሰበብ ሳይገባንና በግል ፍላጎታችን ላይ ተመሥርተን የምንቀበለው “ትምህርት” ሊኖረን አይገባም፡፡ ሁልጊዜም ቢሆን ጠያቂ መሆንና ለመንፈሳዊ ሕይወታችን ዕድገት ምክር የሚሰጡን መሪዎችን መፈለግና ምክራቸውን መተግበር ተገቢ ነው፡፡ ከዚሁ ሁሉ ጋርም ለትምህርት የምንፈልጋቸውን የኅትመትም ሆነ የምስል ወድምፅ ውጤቶች ስንገዛ ጥንቃቄ ማድረግ አለብን፡፡ በራሳችን ገንዘብ የመናፍቃንን ትምህርት ገዝተን ወደቤታችን ማስገባት የለብንም፡፡ ከመግዛታችን በፊት የጸሓፊውን ማንነት፣ የመጽሐፉን ይዘት ማወቅ፤ ካላወቅነውም መጠየቅ አስፈላጊ ነው፡፡ በስሕተት ገዝተናቸው ያነበብናቸውና ጥያቄ የፈጠሩብንም ካሉ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን በመጠየቅ መልስ ማግኘት አለብን፡፡

፬ኛ. መጻሕፍቱ መልስ እንዲሰጥባቸው ለሚመለከተው አካል ማቅረብ

ተሐድሶ መናፍቃን ባዘጋጁት ወጥመድ እንዳንሰናከል ለራሳችን ጥንቃቄ ከማድረግ ጎን ለጎን ሌሎችን የማዳን ሥራም ከሁላችን ይጠበቃል፡፡ የቤተ ክርስቲያን የሆነውን ካልሆነው መለየት የማንኛውም ክርስቲያን ግዴታ ነው፡፡ ባለማወቅ የሚደናገሩትን ከመጠበቅ አንጻር ግን የኅትመትና የምስል ወድምፅ ውጤቶቹ የእኛ አለመሆናቸውን ማወቅ ብቻ በቂ አይሆንም፡፡ ለሚመለከተው አካል ለማቅረብ የኅትመትና የምስል ወድምፅ ውጤቶቹ በማስረጃነት ያስፈልጋሉ፡፡ የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ የሚንዱ፣ ቤተ ክርስቲያንን የሚሳደቡ፣ ቅዱሳንን የሚያቃልሉ የኅትመትና የምስል ወድምፅ ውጤቶች ስናገኝ ለመንፈሳዊ ሕይወታችን ጥቅም ብለን ባንገዛቸውም የዋሃንን እንዳያደናግሩ መልስ እንዲሰጥባቸው አስበን መግዛት ይኖርብን ይሆናል፡፡ በእኛ ዐቅም መልስ ልንሰጥባቸው የማንችል ከሆነም እንኳን በላዔ መጻሕፍት ሊቃውንት ሞልተውናል፡፡ በስሕተት ገዝተን ያስቀመጥናቸው የተሐድሶ መናፍቃን የኅትመትና የምስል ወድምፅ ውጤቶች ለሊቃውንቱ በማቅረብ መልስ እንዲሰጥባቸው ማድረግ ይገባል፡፡ ይህን ስናደርግ ራሳችንንም ሆነ ሌሎችን ማትርፍ እንችላለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ማስገንዘቢያ

ይህ ጽሑፍ፣ ከመስከረም ፲፮ – ፴ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በወጣው የስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ ዕትም፣ በ “ንቁ” ዓምድ ሥር፣ “የተሐድሶ ስውር ደባ” በሚል ርእስ በገጽ ፮፣ ፯ እና ፲፭ ለንባብ መብቃቱን ለማስገንዘብ እንወዳለን፡፡

የ፳፻፲ ዓ.ም የጥቅምት ወር ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤን መጀመር አስመልክቶ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የሰጡት ሙሉ ቃለ ምዕዳን 

ጥቅምት ፲፫ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ

መልእክተ ቅዱስ ፓትርያርክ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ

አሐዱ አምላክ አሜን

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ወኤጲስ ቆጶሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት

እግዚአብሔር አምላካችን በተለመደው ቸርነቱ ከየመንበረ ጵጵስናችን በሰላም አሰባስቦ በዚህ ዓቢይ ዓመታዊ ስብሰባ ተገኝተን ስለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን አንድነት፣ መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት በስሙ እንድንመካከር ለፈቀደልን ለእርሱ ፍጹም ምስጋና ከአምልኮት ጋር እናቀርባለን፡፡

እናንተም ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትና ኤጲስ ቆጶሳት እንኳን በደኅና መጣችሁ፤ እንኳንም ለዚህ ሐዋርያዊና ቀኖናዊ የቅዱስ ሲኖዶስ ዓመታዊ ጉባኤ በሰላም አደረሰን አደረሳችሁ!!

‹‹ወዘንተ ባህቱ አእምር ከመ በደኃሪ መዋዕል ይመጽኣ ዓመታት እኩያት ወይከውኑ ሰብእ መፍቀርያነ ርእሶሙ፤ ነገር ግን በኋኞቹ ዓመታት ሰዎች ራሳቸውን የሚወዱበት ክፉ ዘመን እንደሚመጣ ዕወቅ›› (፪ ጢሞ ፫፥፩)

ይህ መልእክት ቅዱስ ጳውሎስ ለሚወደው ደቀመዝሙሩ ለጢሞቴዎስ ያስተላለፈው ምክር አዘል መልእክት ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ እንደሚታወቀው ዓይነቱ፣ ስልቱና መጠኑ ይለያይ እንደሆነ ነው እንጂ ከሆነ ጊዜ ጀምሮ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከፈተና ተለይታ አታውቅም፤ ይሁን እንጂ ወደመጨረሻው ዘመን አካባቢ የሚሆነው መከራ ግን ከሁሉ የባሰ እንደሚሆን በቅዱሳት መጻሕፍት በተደጋጋሚ የተገለፀ ነው፡፡

ከዚህ አኳያ ቅዱስ ጳውሎስ ተማሪውን ጢሞቴዎስን ሊያስገነዝበው የፈለገው ነገር በመጨረሻ ዘመን የሚከሠተውን ፈተና ምእመናን አውቀው ጥንቃቄ ያደርጉ ዘንድ እንዲያስተምር ነው፡፡ ለወደፊት የሚሆውን ነገር አስቀድሞ የማሳወቅና ወዳጆቹን የማስጠበቅ ኩነት ከጥንት ጀምሮ የነበረ የእግዚአብሔር አሠራር ነው፡፡ በዚህም ቅዱስ ጳውሎስ ለተከታዩ ትውልድ ስለመጨረሻው ዘመን ሁናቴ የማሳወቅ ሥራን ሲሠራ እናስተውላለን፡፡

በተጠቀሰው ክፍለ ምንባብ ላይ የመጨረሻው ዘመን ገጽታ ምን እንደሚመስል በዝርዝር ተገልጾአል፤ ይዘቱን ጠቅለል አድርገን ስንመለከተው በመጨረሻው ዘመን አካባቢ ነገሩ ሁሉ የተመሰቃቀለ እንጂ አንዳች የሚያስደስት ነገር እንደሌለው ነው፤ በተለይም በጥቅሱ ላይ እንደሚታየው የመጨረሻው ዘመን “ሰዎች ከምንም በላይ ራሳቸውን የሚወዱበት ጊዜ” መሆኑ ተነግሮአል፤ ይህ ዓይነቱ አመለካከት ቃለ ቅዱስ ወንጌልን ሙሉ በሙሉ የሚጻረር ነው፡፡

ጌታችን ለተከታዮቹ ያስተማረው “የኔ ሊሆን የሚወድ ሁሉ ራሱን ይካድ” የሚል ነው፡፡ ይህም ማለት የኋለኛው ትውልድ ራስን የሚወድ ከሆነ፣ ጌታ የሚያዘው ደግሞ ራስን መውደድ ሳይሆን ራስን መካድ ከሆነ ነገሩ “ሆድና ጀርባ” ሆኖአል ማለት ነው፤ ከዚህ አንጻር የዘመናችን ክሥተት በዚህ ፈተና ላይ ያለ እንደሆነ በግልፅ ማየት ይቻላል፡፡

ዛሬ የመንፈስ እናታቸው ብቻ ሳትሆን የማንነታቸውና የታሪካቸው ጭምር ማኅደር ከሆነች እናት ኦርቶዶክሳዊት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እያፈተለኩና እየኮበለሉ የሚገኙት በርካታ ወገኖች ራስን ከመውደድ የተነሣ ካልሆነ በቀር ሌላ ትርጉም ሊሰጠው አይችልም፡፡ ክርስቶስ ሌላ አዲስ ክርስቲያን የፈጠረ ይመስል ክርስቲያን የሆነውን ሰው በተለያየ አባባል ወደሌላ የክርስቲያን ጎራ እንዲኮበልል መጣጣር አስኮብላዩም ኮብላዩም ራስን ከመውደድ የተነሣ የሚያደርጉት ነው እንጂ አንዳች የሚጨበጥ ክርስቲያናዊ ትርጉም የለውም፡፡

ራስን በመውደድ የሚታወቀው የዘመናችን ባህርየ ሰብእ በዚህ ብቻ ሳይወሰን በትምህርትም፣ በሐሳብም፣ በአስተያየትም፣ በሥራም፣ ወዘተ የሚገለጸው ራስን ከፍ ከፍ የማድረግና የኔ ከሁሉ ይበልጣል እያሉ ሌላውን የማንኳሰስ አባዜ የሃይማኖት መዓዛ ምግባርን እየበከለው ይገኛል፡፡ ከዚህም የተነሣ የእኔ አውቅልሃለሁ ባይነት ዝንባሌ ሥር እየሰደደ ትሕትናና ፈሪሀ እግዚአብሔር የራቀው ትውልድ እየተበራከተ ይገኛል፡፡

ዛሬ እንደትናንቱ አበው ባሉት እንመራ፣ እንታዘዝ፣ አበውን እናዳምጥ የሚል ትውልድ ሳይሆን ከእናንተ ይልቅ እኛ እናውቃለንና እኛ የምንላችሁን ተቀበሉ በማለት ወደ ላይ አንጋጦ የሚናገር፣ ራስ ወዳድ የሆነ፣ መታዘዝን የሚጠላ ከሃይማኖታዊነት ይልቅ አመክንዮዋዊነትን የሚያመልክ ትውልድ እየመጣ ነው፡፡ ይህ ራስ ወዳድ አስተሳሰብ የሚመነጨው ዘመኑ ያፈራው የሥነ ልቡና ፍልስፍና እንጂ፣ ራሱን በመንፈስ ደሀ አድርጎና ሌላው ከእሱ እንደሚሻል አድርጎ ከሚያስተምር፣ በመንፈሰ እግዚአብሔር ከተጻፈው ከቅዱስ መጽሐፍ የመነጨ አይደለም፡፡

ቤተ ክርስቲያን ደግሞ መመሪያዋ በመንፈሰ እግዚአብሔር የተጻፈ ቅዱስ መጽሐፍ እንጂ በሰዎች ውሱን ጥበብ የተቀነባበረ ሰው ሠራሽ ፍልስፍናና ዘመን አመጣሽ ስልት አይደለም፡፡ በመሆኑም ቤተ ክርስቲያን ስትጠብቀው የኖረች ለወደፊትም የምትጠብቀው በመንፈሰ እግዚአብሔር በታጀበ ጥበብና ስልት እንጂ ከፍልስፍና ብቻ የተገኘ የተውሶ ዕውቀት ሊሆን አይችልምና ሁሉም ሊያስብበት ይገባል፡፡

ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳትና ኤጲስ ቆጶሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን ለሁለት ሺሕ ዓመታት ያህል በአንድነትና በጥንካሬ ጠብቆ ያቆየ ጥበብ ኦርቶዶክሳዊና ሲኖዶሳዊ የሆነ የውሉደ ክህነት አመራር ጥበብ እንጂ የምዕራባውያንና የሉተራውያን ምክር ቤታዊና ዘመን አመጣሽ ፍልስፍና አይደለም፡፡ የቤተ ክርስቲያናችን መርሕ እንደዚያ ቢሆን ኖሮ ዛሬ የምናያት አንዲት ሐዋርያዊትና ኃያል ቤተ ክርስቲያን ሳትሆን የተበታተነች የደከመችና መዓዛ ሐዋርያት የሌላትና የተለያት ቤተ ክርስቲያን ነበር የምናየው፡፡

ይሁን እንጂ አባቶቻችን ካህናት መሪዎች፣ ሕዝቡ ተመሪ ሆኖ በአንድ የእዝ ሰንሰለት እየተደማመጠ ካህኑ ተናገረ ማለት እግዚአብሔር ተናገረ ማለት ነው በሚል ቅንና ትሕትና የተመላ ታዛዥነት እንደዚሁም በውሉደ ክህነት አመራር ሰጪነት የቤተ ክርስቲያናችን አንድነት እስከዛሬ ድረስ ተጠብቆ ቆይቷል፡፡

አሁን ግን ይህ ቀርቶ በአባቶች ላይ ተደራቢ አመራር ሰጪ፣ በአባቶች ላይ የስድብ ናዳ አውራጅ ትውልድ መበራከቱን ካየንና ከሰማን ውለን አድረናል፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን ከጎናችን ሳይሆኑ ከጎናችሁ አለን የሚሉ ወገኖችም ስለድርጊቱ አፍራሽነት በተመለከተ አንድ ቀንስንኳ የተቃውሞ ሐሳብ አለመሰንዘራቸው በስተጀርባው እነርሱራሳቸው ያሉበት እንደሆነ የሚያመላክት መስሎ አሳይቶባቸዋል፡፡

አሁን ዋናው ጥያቄ፣ ይህ ራስ ወዳድ አመለካከት ተቀብሎ የሚመጣውን ጥፋት ማስተናገድ ይሻላል? ወይስ ራስን መካድ የሚለውን የጌታ ትምህርት አሥርፆ ነገሮች ሁሉ በንሥሐ ወደነበሩበት መመለስ፣ ምርጫውን ለዚህ ዓቢይ ጉባኤ አቅርበነዋል፡፡

በሌላ በኩል ቤተ ክርስቲያናችን ያላትን መንፈሳዊና ማኅበራዊ ተልእኮ በሚገባ ለማከናወን ግልፅነትንና ታማኝነትን በማረጋገጥ መልካም አስተዳደርን ማስፈን ለነገ የማይባል የቤተ ክርስቲያናችን ዓቢይ አጀንዳ ሆኖ ይገኛል፡፡ ከዚህ አኳያ የቤተ ክርስቲያናችንን ዙሪያ መለስ ምጣኔ ሀብት በሚገባ ለመያዝና ለማሳደግ እንዲሁም የሰው ኃይላችንን በአግባቡ ለመጠቀም የዘመኑን አሠራር መከተል የግድ ያስፈልገናል፡፡

ሌላው በሀገራችን እየተመዘገበ ያለውን የልማትና የዕድገት ግንባታ በአስተማማኝ ለማስቀጠል የሕዝቡ አንድነትና ሰላም መረጋገጥ ወሳኝነት አለው፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን ከሆነ ጀምሮ የኢትዮጵያ ሕዝብ የሰላም እናት ሆና ሕዝቡን በማስተማር ያስመዘገበችው ጉልህ ታሪክ ዛሬም ተጠናክሮ ይቀጥል ዘንድ ሁላችንም የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ኃላፊነታችንን እንድንወጣ በዚህ አጋጣሚ ጥሪያችንን እናስተላልፋለን፡፡

በመጨረሻም

ይህ ቅዱስ ጉባኤ የቤተ ክርስቲያኒቱን አንኳርና ዓበይት ጉዳዮችን በጥልቀት በመመርመርና በማጥናት ለቤተ ክርስቲያናችን ሊጠቅሙ የሚችሉ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ጉባኤው እንዲቀጥል እያሳሰብን እነሆ ዓመታዊው የጥቅምቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ መከፈቱን በእግዚአብሔር ስም እናበስራለን፡፡

እግዚአብሔር ጉባኤያችንን ይባርክ፤ ይቀድስ፡፡

ሀገራችንንም ይባርክ፤ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ፣

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ፣

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣

ጥቅምት ፲፪ ቀን ፳፻ወ፲ ዓ.ም፤

አዲስ አበባ ኢትዮጵያ፡፡

ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ከትናንት እስከ ዛሬ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ጥቅምት ፫ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ እና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት

ግብረ ኖሎት

በቅዱስ ዮሐንስ ወንጌል እንደተጻፈው ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ ከቅዱሳን ሐዋርያት ጋር ምሳ ተመግቧል፡፡ የተዘጋጀው የምግብ ማዕድ ካበቃ በኋላም ቅዱስ ጴጥሮስን ሦስት ጊዜ ጠርቶ ‹‹ትወደኛለህን?›› እያለ ጠይቆታል፡፡ እንደሚወደው ምላሽ መስጠቱን ተከትሎም ‹‹በጎቼን ጠብቅ፤ ጠቦቶቼን አሰማራ፤ ግልገሎቼን ጠብቅ፤›› በማለት አዝዞታል (ዮሐ. ፳፩፥፩-፲፯)፡፡

ይህ ምሥጢር ለጊዜው ጌታችን ሐዋርያትን፣ ሰብዐ አርድእትንና ሠላሳ ስድስቱ ቅዱሳት አንስትን በአጠቃላይ መቶ ሃያውን ቤተሰብእ እንዲጠብቅና እንዲከባከብ ለቅዱስ ጴጥሮስ ሓላፊነት መስጠቱን ያመላክታል፡፡ ለፍጻሜው የቤተ ክርስቲያን አባቶች (ጳጳሳት) መምህራንን፣ ካህናትን እና ሕዝበ ክርስቲያንን እንዲጠብቁ፣ እንዲያስተዳድሩ በእግዚአብሔር መሾማቸውን የሚያስረዳ ምሥጢር አለው፡፡ መምህራንና ካህናትም በየመዓርጋቸው ወጣንያን፣ ማእከላውያን እና ፍጹማን ምእመናንን የመጠበቅ፣ የማስተማር፣ የመከታተል ሓላፊነት እንዳለባቸው ከዚህ ትምህርት እንገነዘባለን፡፡ ይኸውም ሐዋርያዊ ግብረ ኖሎት (ሐዋርያዊ የእረኝነት አገልግሎት) ነው፡፡

የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ

ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለቅዱሳን ሐዋርያት የሰጣቸውን አምላካዊ ትእዛዝ እና የኖላዊነት ሥልጣን (ሥልጣነ ክህነት) መሠረት በማድረግ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ የኖላዊነት ተልእኮውን በመወጣት ላይ ይገኛል፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ ሐዋርያዊ ተልእኮዉን ለማከናወን የሚያስችሉ ሕግጋትን ለማውጣት፣ መመሪያዎችንም ለማጽደቅ በዓመት ሁለት ጊዜ መንፈሳዊ ጉባኤ ያደርጋል፡፡ የመጀመሪያው ጉባኤ ጥቅምት ፲፪ ቀን (በቅዱስ ማቴዎስ ክብረ በዓል)፤ ሁለተኛው ደግሞ በዓለ ትንሣኤ በዋለ በሃያ አምስተኛው ቀን (በርክበ ካህናት) ይካሔዳል፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ እና ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት ብቻ በሚሳተፉበት በቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ አባቶቻችን በጋራ በመሰባሰብ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተቀላጠፈ አገልግሎት፣ ለምእመናን በሃይማኖት መጽናትና መንፈሳዊ ዕድገት የሚበጁ መመሪያዎችንና ውሳኔዎችን ያሳልፋሉ፡፡

አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ

ከቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ በተጨማሪ ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ጀምሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ያሉ መንፈሳውያን ሰበካ ጉባኤያትም ቃለ ዓዋዲውንና የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔዎችን መነሻ በማድረግ በየጊዜው ጉባኤ በማድረግ ለሐዋርያዊ ተልእኮው መዳረስ፣ ለቤተ ክርስቲያን ዕድገት የሚበጁ የጋራ አቋም መግለጫዎችንና ደንቦችን ያወጣሉ፡፡ ከእነዚህ ጉባኤያት መካከልም የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አንዱና ዋነኛው ነው፡፡

በየዓመቱ በጥቅምት ወር በሚካሔደው በዚህ ጉባኤ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚጠቅሙ፣ ለመንፈሳዊ አስተዳደሯም የሚበጁ መሠረታዊ ጉዳዮች ይነሣሉ፤ መመሪያዎችና ውሳኔዎች ይወጡና በአባቶች ተመዝነው አስፈላጊነታቸው ከታመነበት ይጸድቃሉ፡፡ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት፣ በመላው ዓለም የሚገኙ አህጉረ ስብከት፣ የድርጅቶችና የመንፈሳዊ ኮሌጆች እንደዚሁም የማኅበረ ቅዱሳን የአገልግሎት ሪፖርቶች በዚህ ጉባኤ ይቀርባሉ፡፡ በሪፖርቶቹ ላይም ውይይትና የልምድ ልውውጥ ይደረግና የላቀ ውጤት ያስመዘገቡት ይሸለማሉ፤ ይበረታታሉ፡፡ ዝቅተኛ የአገልግሎት ፍሬ ይዘው የመጡ ደግሞ ከጉባኤው ልምድ ቀስመው አገልግሎታቸውን እንዲያሻሽሉ ይመከራሉ፡፡

የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ አመሠራረት ታሪክ በአጭሩ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ በእጨጌ ገብረ መንፈስ ቅዱስ ሰብሳቢነት፣ በፀባቴ ጥዑመ ልሳን ጸሐፊነት፣ በሰባ ሁለት የአድባራት አስተዳዳሪዎችና አገልጋይ ካህናት አባልነት የቤተ ክርስቲያንን ጉዳይ የሚወስን መንፈሳዊ ጉባኤ መስከረም ፰ ቀን ፲፱፻፲፰ ዓ.ም ተቋቁሞ እንደነበር፤ ከዚያም በ፲፱፻፶፱ ዓ.ም መንግሥት ያወጣው የመሬት ግብር ዓዋጅ በቤተ ክርስቲያን ላይ ችግር በማምጣቱ ቤተ ክርስቲያን የራሷን ተቋማት ለማዋቀር በዓዋጅ ቍጥር ፵፰/፶፱ እና ፹፫/፷፭ ሕጋዊ ፈቃድ እንደተሰጣት፤ በዚህ ሥልጣን መሠረትም ቤተ ክርስቲያናችን በእግዚአብሔር ቃል ተመርታ፣ በሀብቶቿ በምእመናን ተጠቅማ፣ ከመንግሥት ጥገኝነት ነጻ ኾና፣ ራሷን ችላ መተዳደር እንደጀመረች የታሪክ መዛግብት ያስረዳሉ፡፡

ሰማዕቱ ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሁለተኛው ፓትርያርክ ሰማዕቱ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ ምእመናንን የሚያሳትፍ የቤተ ክርስቲያን መተዳደሪያ ደንብ (ቃለ ዓዋዲ) አዘጋጅተው በ፲፱፻፷፭ ዓ.ም የሰበካ ጉባኤ አስተዳደርን አቋቁመዋል፡፡ ወጣቶችን ጭምር የሚያሳትፈው ይህ ቃለ ዓዋዲም አገልጋይ ካህናት የወር ደመወዝ እንዲያገኙ ከማስቻሉ ባሻገር በካህናትና በምእመናን መካከል ያለው ኅብረት እንዲጠናከርም አድርጓል፡፡ ስለዚህም ስለሰበካ ጉባኤ መቋቋም ሲነገር ወጥነት ያለው መንፈሳዊ የአስተዳደር መዋቅር እንዲዘረጋ ከፍተኛ ጥረት ያደረጉት ሰማዕቱ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ቴዎፍሎስ አብረው ይዘከራሉ፡፡

ቅዱስነታቸው የጀመሩት ይኼው መዋቅራዊ አሠራር እና ያፋጠኑት ሐዋርያዊ አገልግሎትም በሦስተኛው ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ዘመን ይበልጥ ተስፋፍቷል፡፡ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ዘመን የሰበካ ጉባኤ ማደራጃ መምሪያ ሓላፊ ኾነው ለበርካታ ዓመታት ያገለገሉት ሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ የሰበካ ጉባኤን በማጠናከር ረገድ ያደረጉት ብርቱ ጥረትም የሚዘነጋ አይደለም፡፡ በዚህ መልኩ እየተጠናከረ የመጣው የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ፣ የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት በማሳደግ፣ አስተዳደሯንም በማቀላጠፍ ዓመታትን አልፎ አሁን ካለበት ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ በአሁኑ ሰዓትም ቅዱስ ሲኖዶስ ባሳለፈው ውሳኔ መሠረት የወቅቱንና የዘመኑን አካሔድ በሚዋጅ መልኩ ቃለ ዓዋዲው ተሻሽሎ ሊታተም ዝግጅት ላይ ነው፡፡

የታሪኩ ምንጮች፡-

  • የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ፣ ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ ካልዕ፤ አክሱም ማተሚያ ቤት፣ አዲስ አበባ፤ ፳፻፯ ዓ.ም፣ ገጽ 168 – 169፡፡
  • ዝክረ ነገር ዘመልአከ ታቦር ተሾመ ዘሪኹን፣ ማኅበረ ቅዱሳን፤ አዲስ አበባ፣ ፳፻፱ ዓ.ም፤ ገጽ 140 – 141፡፡
  • ዐዋጅ ነጋሪ መጽሔት፣ የመጀመሪያው ልዩ ዕትም፤ አዲስ አበባ፣ የካቲት ወር 2001 ዓ.ም፤ ገጽ 14 – 15፡፡

የአጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ዓላማ እና ተግባር

በ፲፱፻፺፩ ዓ.ም ተሻሽሎ በወጣው ቃለ ዓዋዲ አንቀጽ ፭ ላይ እንደተገለጸው የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ዓላማ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን መጠበቅና አገልግሎቷም የተሟላ እንዲኾን ማድረግ፤ የቤተ ክርስቲያንን አገልጋዮች በሐዋርያዊ ተግባር ማደራጀትና ችሎታቸውንና ኑሯቸውን ማሻሻል፤ ምእመናንን ማብዛትና በመንፈሳዊ ዕውቀት ጐልምሰው፣ በምግባር በሃይማኖት ጸንተው በክርስቲያናዊ ሕይወት እንዲኖሩ ማድረግ፤ የቤተ ክርስቲያንን አስተዳደር ማሻሻልና በማናቸውም ጉዳይ ራሳቸውን ማስቻል ነው፡፡

ይህን መንፈሳዊ ዓላማ ለማስፈጸም የተዋቀረው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ መንፈሳዊ ጉባኤም የእያንዳንዱ ሀገረ ስብከት ሥራ አስኪያጆች፤ ከየመንበረ ጵጵስናው የተወከሉ ካህናት፣ ምእመናንና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ከብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት እና ከጠቅላይ ቤተ ክህነት የየመምሪያ ሓላፊዎች ጋር በአንድነት ተሰባስበው የሚመሠርቱት ጉባኤ ሲኾን፣ በዓመት አንድ ጊዜ የሚሰበሰብ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ እንዳለውና ይህም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አጠቃላይ ስብሰባ እንደኾነ በቃለ ዓዋዲው አንቀጽ ፵፮ ላይ ተደንግጓል፡፡

በቃለ ዓዋዲው አንቀጽ ፵፯ ላይ በተቀመጠው ድንጋጌ መሠረት በአጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ዓመታዊ ጉባኤው ላይ ፓትርያርኩ ርእሰ መንበር፤ ብፁዕ ጠቅላይ ሥራ አስኪያጁ ምክትል ሊቀ መንበር፤ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት አባላት፤ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ምክትል ሥራ አስኪያጅ አባልና ጸሐፊ፤ የአጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤው አስተዳደር ጉባኤ (ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ) አባል፤ የአህጉረ ስብከት ሥራ አስኪያጆች አባላት፤ ከየአህጉረ ስብከት መንፈሳውያን አስተዳደር ጉባኤያት የተወከሉ ካህናት፣ ምእመናን እና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች አባላት፤ በውጭ አገር የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተወካዮች አባላት ኾነው የሚሳተፉበት ታላቅ የቤተ ክርስቲያን ጉባኤ ነው፡፡

የአህጉረ ስብከትን ሪፖርቶችና ዕቅዶች ከሰማ በኋላ በጉዳዩ ላይ ተወያይቶ እና ተመካክሮ ውሳኔ ማሳለፍ፤ የቤተ ክርስቲያንን መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት ለማጠናከር ከፍተኛ መንፈሳዊ ት/ቤቶች፣ የካህናት፣ የሰባክያንና የሰንበት ት/ቤት መምህራን ማሠልጠኛዎች እንደዚሁም የልማትና በጎ አድራጎት ተቋማት በሀገረ ስብከት እና በማእከል ደረጃ እንዲቋቋሙና እንዲደራጁ ማድረግ፤ የአጠቃላዩን አስተዳደር ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ (ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ) መምረጥ በቃለ ዓዋዲው አንቀጽ ፵፰ የተዘረዘሩ የጉባኤው ሥልጣንና ተግባራት ናቸው፡፡ በዚሁ አንቀጽ እንደተጠቀሰው የመንበረ ፓትርያርክ አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ተጠሪነቱ ለቅዱስ ሲኖዶስ ነው፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን ተሳትፎ በጉባኤው

ማኅበረ ቅዱሳን በቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ የተመሠረተ ሕጋዊ ማኅበር እንደመኾኑ ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ ላለፉት ሃያ አምስት ዓመታት አመራርና አስፈጻሚ አባላቱን እየወከለ በአጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤው ሲሳተፍ ቆይቷል፡፡ ማኅበሩ ስብከተ ወንልን በማስፋፋት፣ አዳዲስ ምእመናንን በማስጠመቅ፤ ለገዳማትና አብነት ትቤቶች ልዩ ልዩ ድጋፍ በማድረግ፤ ለአባቶች የስብከተ ወንጌልና ከአስተዳደር ጋር የተያያዙ ሥልጠናዎችን በመስጠት ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መስፋፋት ያከናወናቸው ዐበይት ተግባራቱ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤትና ከአህጉረ ስብከት ሪፖርቶች ጋር ተካተው ሲቀርቡ መቆየታቸውም የሚዘነጋ አይደለም፡፡

ለአብነትም በጠረፋማ አካባቢዎች ስብከተ ወንጌልን በማዳረስ በአምስት ዓመታት ውስጥ ከስድሳ ዘጠኝ ሺሕ ለሚበልጡ አዳዲስ አማንያን የሥላሴ ልጅነትን ማሰጠቱ፤ ለአብነት መምህራን እና ደቀ መዛሙርት ወርኃዊ የገንዘብ እና አስቸኳይ የቀለብ ድጋፍ ማድረጉ፤ የአብነትና ዘመናዊ ት/ቤቶችን፣ የመጠጥ ውኃና ልዩ ልዩ የልማት ፕሮጀክቶችን በልዩ ልዩ አህጉረ ስብከት ማስገንባቱ፤ በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ለሚገኙ ከሁለት መቶ ሺሕ በላይ የሚኾኑ የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎችን ትምህርተ ወንጌል ማስተማሩና ዐርባ አምስት ሺሕ ያኽሉን ማስመረቁ፤ ከዚሁ ዅሉ ጋርም ከሰባት መቶ ዐሥር ሺሕ በላይ ልዩ ልዩ የመዝሙር ቅጂዎችንና የኅትመት ውጤቶችን እንደዚሁም ከአንድ ሚሊዮን በላይ የሐመር መጽሔቶችንና ስምዐ ጽድቅ ጋዜጦችን ማሠራጨቱ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት ሪፖርት ተካቶ በ፴፭ኛው አጠቃላይ መንፈሳዊ የሰበካ ጉባኤ ላይ መቅረቡ የሚታወስ ነው (ዐዋጅ ነጋሪ መጽሔት፣ ጥቅምት ወር ፳፻፱ ዓ.ም፤ ገጽ 75)፡፡

በመንፈሳዊ አገልግሎት ዋጋ የሚከፍል እግዚአብሔር ነውና ‹‹ይኽን ሠርተናል፤ ይኽን ፈጽመናል›› ብሎ ስለሠሩት ተግባር መናገርም ሌላ አካል እንዲናገር መሻትም ተገቢ አይደለም፡፡ ኾኖም ግን ለቍጥጥር፣ ለዕቅድና ለክንውን ያመች ዘንድ የአገልግሎት ሪፖርት ማቅረብ አንዱ የሥራ አፈጻጸም አካል ነው፡፡ በጠቅላይ ቤተ ክህነት ልዩ ልዩ መምሪያዎች፣ ድርጅቶችና መንፈሳዊ ኮሌጆች እንደዚሁም የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት በአጠቃላይ ጉባኤው በሪፖርት መልክ የሚቀርበውም ከዚህ አኳያ ነው፡፡ የማኅበሩ አገልግሎት የየአህጉረ ስብከት ሪፖርት አካል ኾኖ መቅረቡ ማኅበረ ቅዱሳን አባላቱንና በጎ አድራጊ ምእመናንን በማስተባበር በሚቻለው አቅም ዅሉ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ ተልእኮ የመደገፍ ዓላማ እንዳለው ያመላክታል፡፡ ከሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያን ሓላፊዎች ጋር በመመካከር የልጅነት ተግባሩን በመወጣት ላይ እንደሚገኝም ያስረዳል፡፡ ማኅበሩ፣ በ፳፻፱ ዓ.ም የአገልግሎት ዘመንም በተመሳሳይ መልኩ በርካታ መንፈሳውያን ተግባራትን አከናውኗል፡፡ ለወደፊትም እግዚአብሔር እስከፈቀደለት ጊዜ ድረስ አገልግሎቱን አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡

፴፮ኛው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ

ለቤተ ክርስቲያን ዅለንተናዊ አገልግሎት አስፈላጊ የኾነው አጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ካሁን ቀደም ይደረግ እንደነበረው ዂሉ፣ በዘንድሮው ዓመትም ከጥቅምት ፮ – ፲፩ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በአዲስ አበባ ከተማ በመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤት የስብከተ ወንጌል አዳራሽ ለሠላሳ ስድስተኛ ጊዜ ይካሔዳል፡፡ በዚህ ጉባኤ ሪፖርት ከማቅረብና መግለጫዎችን ከማውጣት ባለፈ ለቤተ ከርስቲያን አገልግሎት መፋጠን የሚተጉ አባቶች፣ እናቶችና ወንድሞች ይበረታታሉ፡፡ የመንፈሳዊ አገልግሎት ማኅበራትና የበጎ አድራጎት ተቋማት አገልግሎታቸውን እንዲያሰፉ ድጋፍ ያገኛሉ የሚል እምነት አለን፡፡

በአንጻሩ ደግሞ በኑፋቄ፣ ገንዘብ በመመዝበር፣ ሕገ ወጥ አሠራርን በማስፈንና በሌላም ልዩ ልዩ በደል ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን የሚፈታተኑና መንፈሳውያን አባቶችን የሚያስነቅፉ አንዳንድ ግለሰቦች ተመክረውና ተገሥፀው ከስሕተታቸው እንዲመለሱ ይደረጋሉ፤ እንቢ ካሉ ደግሞ አስፈላጊውን ቅጣት ይቀበላሉ ብለን ተስፋ እናደርጋለን፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን በአንዳንድ አገልጋዮች ዘንድ የሚስተዋለውን ሕገ ወጥ አሠራር እና በፍቅረ ንዋይ መታለልን ተከትሎ የሚመጣውን፣ ለብዙዎች መሰናክል የሚኾነውን አእምሯዊ ጥፋት፣ መንፈሳዊ ዝለትና አስተዳደራዊ ግድፈት ለመግታትም የዘንድሮው አጠቃላይ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ የማያዳግም ውሳኔ እንደሚያሳልፍ፤ ውሳኔውንም በቅዱስ ሲኖዶስ አጸድቆ ተግባራዊ እንደሚያደርግ እንጠብቃለን፡፡

ማጠቃለያ

‹‹ለመንጋው ምሳሌ ኹኑ እንጂ ማኅበሮቻችሁን በኃይል አትግዙ፡፡ የእረኞችም አለቃ በሚገለጥበት ጊዜ የማያልፈውን የክብርን አክሊል ትቀበላላችሁ፤›› (፩ኛ ጴጥ. ፭፥፫-፬) ተብሎ እንደተጻፈው ግብረ ኖሎት (የመንፈሳውያን እረኞች ተግባር) ለምድራዊ ጥቅም እና ዝና በመጨነቅ ሳይኾን ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚያገኙትን ዋጋ በማሰብ በበግ የሚመሰሉ ምእመናን በአጋንንት ተኩላዎች እንዳይነጠቁ፣ በለምለሟ መስክ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን እየተሰባሰቡ ምግበ ሥጋ ምግበ ነፍስ የኾነውን ቃለ እግዚአብሔር እንዲመገቡ፣ ሰማያዊ ሕይወት የሚያስገኘውን ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን እንዲቀበሉ በማድረግ በዐቢይነት ወደ ዘለዓለማዊ ማረፊያቸው ገነት (መንግሥተ ሰማያት) እንዲገቡ የድኅነት መንገዱን ማመቻቸት ነው፡፡

ስለኾነም ቅዱስ ሉቃስ ‹‹በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቋት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ዅሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ፤›› (ሐዋ. ፳፥፳፰) በማለት እንዳስተማረው እረኞቻችን የቤተ ክርስቲያን አባቶች ሳያስጨንቁ በሥርዓትና በጥንቃቄ በጎች ምእመናንን መምራት፤ እኛ ምእመናኑም ከአባቶች ጋር የምንወርሰውን የእግዚአብሔር መንግሥት ተስፋ በማድረግ እረኞቻችንን ማክበር፣ ትእዛዛቸውንም መፈጸም ይጠበቅብናል፡፡ ከዚሁ ዂሉ ጋርም እያንዳንዳችን፣ በቤተ ክርስቲያን አስተዳደር የመጨረሻው ወሳኝ አካል በኾነው ቅዱስ ሲኖዶስ የሚወጡ ውሳኔዎችን እና በአጠቃላይ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤው የሚዘጋጁ ድንጋጌዎችን ተቀብለን የመፈጸምና የማስፈጸም ክርስቲያናዊ ግዴታ እንዳለብን አንርሳ፡፡

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የ፳፻፲ ዓ.ም ዘመን መለወጫን አስመልክቶ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ የሰጡት ቃለ በረከት

የተወደዳችሁ የድረ ገጻችን ተከታታዮች! ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት የ፳፻፲ ዓ.ም ዘመን መለወጫን አስመልክቶ የሰጡትን ሙሉዉን ቃለ በረከት እንደሚከተለው አቅርበነዋል፤

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ

ቃለ በረከት ዘብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት ዘተናገረ በበዓለ ርእሰ ዐውደ ዓመት ዘዕሥራ ምእት ወዐሠርቱ ዓመተ ምሕረት

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

  • በአገራችን በኢትዮጵያ በገጠርና በከተማ የምትኖሩ፤
  • ከአገር ውጭ በተለያዩ አህጉር የምትገኙ
  • የአገራችንን ዳር ድንበር ለመጠበቅና ለማስከበር በየጠረፉ የቆማችሁ፤
  • በሕመም ምክንያት በየጠበሉና በየሆስፒታሉ ያላችሁ፤
  • እንደዚሁም የሕግ ታራሚዎች ኾናችሁ በየማረሚያ ቤተ የምትገኙ ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት፤

የዘመናትና የፍጥረታት ፈጣሪ የኾነው እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ከዘመነ ማቴዎስ ሁለት ሺሕ ዘጠኝ ዓመተ ምሕረት ወደ ዘመነ ማርቆስ ሁለት ሺሕ ዐሥር ዓመተ ምሕረት በሰላም አደረሳችሁ፡፡

“አንሶስዉ እንዘ ብክሙ ብርሃን፤ ብርሃን ሳለላችሁ በብርሃን ተመላለሱ” (ዮሐ. ፲፪፥፴፭)

የብርሃን ጸጋ ለሰው ልጆች ወይም በአጠቃላይ ለፍጥረታት ዅሉ ከተሰጠው የእግዚአብሔር ስጦታዎች ትልቁ ነው፤ ብርሃን የሥራ መሣሪያ ነው፤ ብርሃን የመልካም ነገር ሁሉ ተምሳሌት ነው፡፡ እግዚአብሔር ራሱ በባሕርዩ ብርሃን ከመኾኑም ሌላ በእርሱ ዘንድ የማይጠፋ ብርሃን እንዳለ በቅዱስ መጽሐፍ ተገልጿል፡፡ የሰው ልጅ ከወዲያ ወዲህ፣ ከወዲህ ወዲያ ተንቀሳቅሶ፣ ነግዶ፣ አርሶ፣ ሠርቶ፣ ተምሮና አስተምሮ ለኑሮው የሚያስፈልገውን ዅሉ ለማግኘት ብርሃን የግድ ያስፈልጋል፡፡

ከዚኽም ጋር ሙሉ ጤና፣ ቀና የኾነ አእምሮ፣ ሰላምና ፍቅር ለሰው ልጅ ብልጽግና ወሳኝ ቦታ አላቸው፡፡ እነዚህ በሰው ልጅ መንፈሳዊና ሥጋዊ ሕይወት ላይ ያላቸው ጸጋ እጅግ የላቀ በመኾኑ በቅዱስ መጽሐፍ አገላለጽ ብርሃን እየተባሉ ይጠቀሳሉ፡፡ እንደዚሁም ዕድሜና መልካም ዘመን በተመሳሳይ አገላለጽ ብርሃን ተብሎ ይመሠጠራል፡፡ ምክንያቱም ብርሃን በሌለበት ኹኔታ ምንም ሥራ መሥራት እንደማይቻል ሰላማዊ ዘመን ከሌለም ልማትና ዕድገት ማስመዝገብ አይቻልማና ነው፡፡ በመኾኑም ዕድሜና ዘመንም ሌላው ታላቁ የእግዚአብሔር ብርሃን ነው፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ብርሃን ሳለላችሁ በብርሃን ተመላለሱ” ሲል የዕድሜና የጊዜ ብርሃንነትን ማመልከቱ እንደ ኾነ ዐውደ ምንባቡ በግልጽ ያሳያል፡፡ ምክንያቱም እርሱ በዚኽ ዓለም በመምህርነት የተገለጸበት ዘመን ወደ መጠናቀቁ እየተቃረበ በነበረበት ጊዜ የተናገረው ከመኾኑ ጋር ባለችው አጭር ጊዜ የትምህርት ዕድሜ ወይም ዘመን ሰዎች በእርሱ ብርሃንነት እንዲያም የቀሰቀሰበትና ያስተማረበት ትምህርት ነው፡፡ በእርግጥም ላስተዋለውና በሥራ ለተጠቀመበት ጊዜ ታላቁ ብርሃን ነው፡፡ ጊዜ ሲቀና ነገሩ ዅሉ ብርሃን ይኾናል፡፡ ጊዜው ከጨለመ ደግሞ ዙሪያው ዅሉ ጨለማ ይኾናል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት

ዕድሜያችን ወይም ዘመናችን በሕይወታችን ውስጥ ለልማትም ኾነ ለጥፋት፣ ለጽድቅም ኾነ ለኀጢአት፣ ለትንሣኤም ኾነ ለውድቀት መሣሪያነቱ የታወቀ ነው፡፡ ምክንያቱም ዅሉም የሚሠራውና የሚከናወነው በጊዜው ነውና፡፡ በዘመናት ውስጥ ብርሃናውያን የኾኑ ዓመታት እንደ ነበሩ ዅሉ ጽልመታውያን የኾኑ ዓመታትም በአገራችንም ኾነ በሌላው ዓለም እንደ ነበሩ እናውቃለን፡፡ እነዚኽ ተቃራኒ የኾኑ ነገሮች በየፊናቸው ለሰው ልጆች ያተረፉት ስጦታም በስማቸው ልክ እንደ ኾነ ይታወቃል፡፡ ይኹን እንጂ ዘመናትን ብርሃውያን ወይም ጽልመታውያን እንዲኾኑ በማድረግ ረገድ የሰው ልጅ ሚና ትልቅ እንደኾነ የማይካድ ነው፡፡

የሰው ልጅ የማስተዋልና የመቻቻል፣ የመታገሥና የመወያየት፣ የፍቅርና የስምምነት፣ የሰላምና አንድነት ጠቃሚነትን ዘንግቶ በስሜትና በወቅታዊ ትኩሳት፣ እንደዚሁም እግዚአብሔርን የሰላም ድምፅ አልሰማ ብሎ በራስ ወዳድነትና በስግብግብነት ተሸንፎ ወደ ትርምስ ሲገባ ዘመኑ ጽልመታዊ መኾኑ አይቀሬ ነው፡፡ በሰው ችኩልና ደካማ አስተሳሰብ የተጨናነቀ ጽልመታዊ ዘመን ከውድመትና ከጥፋት በቀር አንዳችም ትርፍ እንደሌለው ከአገራችን ተሞክሮ የበለጠ መምህር አይኖርም፡፡

በሌላ በኩል ሰዎች ከእርስ በርስ ግጭት ተላቀው ሰላምንና ፍቅርን፣ አንድትንና እኩልነትን፣ መቻቻልንና መስማማትን፣ መወያየትንና መቀራረብን፣ ወንድማማችነትንና መከባበርን ያረጋገጠ፣ ትዕግሥትና አስተዋይነት የማይለየው የእግዚአብሔርን ድምፅ በመከተልና አእምሮን በማስፋት መኖር ሲጀምሩ ዘመኑ ብርሃናዊ እንደሚኾን፣ ልማቱና ዕድገቱም እንደሚፈጥንና እንደሚረጋገጥ አሁንም በአገራችን ወቅታዊ ተሞክሮ ተረድተዋል፡፡ ይኽ ዅሉ እውነታ የሚያሳየው የዘመን ብርሃንነትና ጽልመትነት የሚወሰነው እኛ ሰዎች በምናውጠነጥነው አስተሳሰብና በምናደርገው እንቅስቃሴ እንደ ኾነ ማስተዋል ተገቢ ነው፡፡ ለዚኽም ነው ሓላፊነቱም ተመልሶ ወደ እኛ የሚመጣው፡፡

ጌታችንም ምርጫውንና ውሳኔውን ለእኛ ትቶ “ብርሃን ስላላችሁ በብርሃን ተመላለሱ” በማለት ገለጻውንና ትምህርቱን ብቻ መናገሩ ከዚህ የተነሣ እንደ ኾነ ማስተዋል ይገባል፡፡ ከእነዚህ ከሁለቱ የሚሻለንን መምረጥና መከተል የእኛ ፈንታ ነው፡፡ ምርጫችን ሰላምና አንድነት ከኾነ ዘመኑ ብርሃን ነው፤ ተቃራኒው ከኾነ ደግሞ የኋልዮሽ ጉዞ ይኾናል፡፡ ስለ ኾነም ምርጫችን ሰላምና አንድነት እንዲኾን ዅላችንም ተስማምተን መወሰን አለብን፡፡

ማንም ሰው ብርሃንና ጨለማ ጎን ለጎን ቀርበውለት የትኛውን ትመርጣለህ የሚል ጥያቄ ቢቀርብለት ያለማመንታት ብርሃኑን እንደሚመርጥ ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ ችግሩ ሰዎች ይህን ግልጽና ጠቃሚ ምርጫ ተቀብለው ተጠቃሚ እንዳይኾኑ ብዙ የሚያታልሉና በድብብቆሽ የሚመላለሱ አካላት በመካከሉ ይገቡና ጨለማውን ብርሃን፣ ብርሃኑንም ጨለማ አስመስለው ሰውን ወደ ገደል መክተታቸው ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ብርሃናዊና መልካም የኾነ ምርጫችንን ጥያቄ ውስጥ እንዲገባ ያድርጉታል፡፡ እኛ ሰዎች አእምሯችንን በሚገባ መጠቀም ያለብን እዚኽ ላይ ነው፡፡ ማለትም እኛው ራሳችን የሚጠቅመንና የማይጠቅመንን የመለየት ዓቅም ስላለን ዓቅማችንን ተጠቅመን ለዘላቂ ጥቅማችንና ለትክክለኛ ምርጫችን መወገን ይኖርብናል ማለት ነው፡፡

ሰዎች የኾን ዅላችን ባለ አእምሮዎች ኾነን ተፈጥረናል፡፡ አእምሮ ከእግዚአብሔር ጋር የሚያመሳስለን ስለ ኾነ ከሀብት ዅሉ የበለጠ ሀብት ነው፡፡ ይህንን አእምሯችንን ካዳመጥነውና ከተከተልነው ሐቁን አይስትም፡፡ አመዛዝኖ፣ ገምግሞ፣ ለክቶ ጠቃሚውን ነገር ከልባችን ውስጥ ቁጭ ያደርግልናል፡፡ ነገር ግን ትዕግሥትን፣ ማገናዘብን፣ ቆም ብሎ ማሰላለሰልን፣ ምክንያታዊ መኾንን፣ ማመዛዘንን፣ ፈሪሀ እግዚአብሔርን፣ ፈቃደ እግዚአብሔርን መከተልን ይፈልጋልና እነዚኽን እንደ ግብአት አድርገን ልናቀርብለት ይገባል፡፡ ይህንን መጠቀም ስንችል የዘመናችንና የዕሜያችን ብርሃን ዋስትና ይኖረዋል፡፡ ጨለማም አያሸንፈውም፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ኢትዮጵያውያንና ኢትዮጵያውያት

ለዐሥር ዓመታት ያህል የተጓዝንበት የሦስተኛው ሺሕ ወይም ሚሊኒየም ዓቢይ ዘመን ለኢትዮጵያ አገራችን ብርሃናዊ ዘመን የፈነጠቀበት ወቅት ነው፡፡ ምክንያቱም በዚህ ዘመን ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ ያልተነካ ሀብታችን እርሱም የዓባይ ወንዝ ሀብታችንን ለመቋደስ የሚያስችል ግዙፍ የልማት ሥራ ተጀምሮ ወደ መጠናቀቅ እየተቃረበ ያለበት እጅግ ብርሃናዊ ዘመን በመኾኑ ነው፡፡

በሠለጠነው የምዕራቡ ዓለም ካልኾነ በቀር በአፍሪካ ምድር ለዚያውም በድርቅ፣ በረኃብና በጦርነት ትታወቅ በነበረችው ኢትዮጵያ ይኾናሉ ተብለው የማይታሰቡ እጅግ ግዙፍ የኾኑና የሕዝባችንን መሠረታዊ የዕድገት ለውጥ የሚያረጋግጡ የኮንስትራክሽንና የኢንዱስትሪ፣ የትምህርትና የጤና ተቅዋማት በፍጥነት እየገሠገሡ መገኘት በዚህ ብርሃናዊ ዘመን የዕለት ተዕት ትእይንት እንደ ኾኑ በዓይን እየታየ ነው፡፡ ይኽ ጸጋ እንዲሁ ያለ መሥዋዕትነት የተገኘ ሳይኾን እኛ ኢትዮጵያውያን ከዅሉ በላይ ሰላምንና ልማትን መርጠን በአንድነት ወደ ብርሃናዊ አስተሳሰብ ስለ ገባን ነው፡፡ እግዚአብሔርም “በብርሃን ተመላሱ” ያለው ይኽን ለማመልከት ነውና በዚህ ምክንያት ትክክለኛ ምርጫችንን እርሱ ስለባረከልን የልማትና የዕድገት ተምሳሌት መኾን እንደቻልን አንስተውም፡፡

ዛሬም ወደማንወደውና ወደማንመርጠው ጨለማ ሊከቱን የሚሹ እንደ ኤች አይ ቪ ኤድስና ሕገ ወጥ የሰዎች ዝውውር፣ እንደዚሁም በሕዝባችን መካከል መለያየትና መቃቃር ሊያስከትሉ የሚችሉ አፍራሽ ድርጊቶች ብቅ ብቅ በማለት እየተፈታተኑን እንደ ኾኑ መዘንጋት የለበትም፡፡ እነዚኽ ዅሉ በተግባር ያየናቸው የሕዝባችን ቀንደኛ ፀርና የጨለማ አበጋዞች፣ የልማታችንና የሰላማችን ዕንቅፋቶች ናቸውና ሕዝቡ በተለመደው ሃይማኖታዊና አርቆ ማሰብ ኀይሉ እንዲመክታቸው በዚህ አጋጣሚ ጥሪያችንን እናቀርባለን፡፡

በመጨረሻም

የዛሬ ዐሥር ዓመት “ታላቅ ነበርን ታላቅም እንኾናለን” በማለት ለሦስተኛው ሺሕ ወይም ሚሊኒየም ዓቢይ ክፍለ ዘመን የገባነውን ቃል በማደስ በአዲሱ ዓመት ካለፈው ዓመት በበለጠ ጠንክረን በመሥራት፣ ልማታችንንና ዕድገታችንን በፍጥነት በማሳደግ፣ የኤች አይ ቪ ኤድስ በሽታን ባለን የተሞክሮ አሠራር በመመከት፣ እንደዚሁም ሕገ ወጥ ዝውውርን፣ አገርንና ሕዝብን የሚጎዳ ድርጊትን በማክሸፍ፣ በሃይማኖትና በሰላም መርሕ በመመራት አዲሱን ዘመን ብርሃናዊ እንድናደርገው መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

አዲሱን ዘመን የሰላም፣ የፍቅርና የብልጽግና ያድርግልን፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን ኢትዮጵያንና ሕዝባችንን ይባርክ፤ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

መስከረም ፩ ቀን ፳፻ወ፲ ዓ.ም

አዲስ አበባ ኢትዮጵያ

የ፳፻፱ ዓ.ም ጾመ ፍልሰታን አስመልክቶ ቅዱስ ፓትርያርኩ የሰጡት ቃለ በረከት

ሐምሌ ፳፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

በአገር ውስጥና በተለያዩ ክፍለ ዓለማት የምትገኙ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ሕዝበ ክርስቲያን በሙሉ!!

እኛን ለክብርና ለምስጋና የፈጠረ እግዚአብሔር አምላካችን እንኳን ለሁለት ሺሕ ዘጠኝ ዓመተ ምሕረት የጾመ ማርያም ሱባዔ በሰላም አደረሳችሁ!!

‹‹ታዓብዮ ነፍስየ ለእግዚአብሔር፤ ነፍሴ እግዚአብሔርን ከፍ ከፍ ታደርገዋለች፤›› (ሉቃ ፩፥፵፯)፡፡

ይህንን የምስጋና ቃል የተናገረችው ወላዲተ እግዚአብሔር ቃልና ማኅደረ መንፈስ ቅዱስ የኾነችው ቅድስት ድንግል ማርያም ናት፤ እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ይህንን የአምልኮ ምስጋና ለእግዚአብሔር ስታቀርብ እርሱ ያደረገላትን ሦስት ዓበይት ምክንያቶች በመጥቀስ እንደ ኾነ ከቅዱስ መጽሐፍ እናስተውላለን፡፡

እመቤታችን ይህንን ምስጋና ከማቅረቧ በፊት እግዚአብሔር ለታላቅ በረከትና ለፍጹም ደስታ እንደ መረጣት፣ የእርሱ ባለሟልና ምልእተ ጸጋ እንዳደረጋት፣ ቅዱሱን የእግዚአብሔር ልጅ በመንፈስ ቅዱስ ፀንሳ እንደምትወልድና እግዚአብሔር ከእርሷ ጋር እንደ ኾነ በመልእክተኛ በቅዱስ ገብርኤል በኩል ነግሮአታል፡፡ እርሷም በቅዱስ ገብርኤል በኩል የተላከላትን የእግዚአብሔር ቃል ተቀብላ ‹‹እነሆ የእግዚአብሔር ባሪያ ነኝ፤ እንዳልኸኝ ይኹንልኝ›› በማለት በታዛዥነትና በትሕትና ለደረሳት መለኮታዊ ጥሪ ተገቢውን የይኹንታ መልስ ሰጥታለች፡፡ በዚህ ጊዜ ቀዳማዊ ወልደ እግዚአብሔር በግብረ መንፈስ ቅዱስ ከቅድስት ድንግል ማርያም ከሥጋዋ ሥጋ ከነፍስዋ ነፍስ ነሥቶ ራሱን በማዋሐድ የዕለት ፅንስ ኾኖ በማኅፀንዋ አደረ፡፡

ጌታችን አምላካዊ ማንነቱን መግለጽ የጀመረው ከማኅፀን አንሥቶ ነውና እመቤታችን እርሱን ፀንሳ ሳለች ኤልሳቤጥን እንዴት ነሽ ብላ የሰላምታ ድምፅን ስታሰማት በማኅፀነ ኤልሳቤጥ ያለው ፅንስ በማኅፀነ ማርያም ላለው ፅንስ በደስታ ሰግዶአል፡፡ ይህ አምላካዊ ምሥጢር በድንግል ማርያም ማኅፀን ውስጥ ያለው ፅንስ የአምልኮ ስግደት የሚገባውና ዅሉን የፈጠረ፣ ዅሉንም ማድረግ የሚችል የባሕርይ አምላክ መኾኑን አሳይቶአል፡፡ ይህ ብቻም አይደለም፤ የቅድስት ድንግል ማርያም የሰላምታ ድምፅ በኤልሳቤጥ ጆሮ በተሰማ ጊዜ በማኅፀንዋ ያለ ፅንስ በደስታ ሲሰግድ፣ በዚያ ቅፅበት ኤልሳቤጥ በመንፈስ ቅዱስ ተሞልታ እግዚአብሔር በቅዱስ ገብርኤል በኩል የገለጸውን የእመቤታችን ክብርና ጸጋ፣ በረከትና ብፅዕና፣ የጌታ እናትነትና ባለሟልነት፣ የልጇ በረከትና አምላክነት በኤልሳቤጥ አንደበትም በድጋሜ  እንዲነገር ማድረጉ የነገሩ ክብደትና ታላቅነት ምን ያህል እንደ ኾነ እንዲታወቅ አስችሎአል፡፡

እግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ በቅዱስ ገብርኤልና በቅድስት ኤልሳቤጥ በኩል ስለ እርስዋ መናገሩና የእግዚአብሔር ወልድ በማኅፀኗ ማደሩ በዚህ ዅሉ እጅግ በጣም ከኃይል ዅሉ የበለጠ ታላቅ ኃይል በእርስዋ ላይ እንደ ተደረገ እመቤታችን በሚገባ አውቃለች፡፡ ይህ እጅግ በጣም ታላቅ የኾነ ጸጋ ለሰው ልጅ ዅሉ የሚተርፍ ልዩ በረከትና የእግዚአብሔር የማዳን ቍልፍ ተግባር እንደ ኾነ ለማመልከትም ‹‹ካንቺ የሚወለደው ሕዝቡን ከኃጢአታቸው የሚያድናቸው ስለ ኾነ ስሙን ‹ኢየሱስ› ትይዋለሽ›› ተብሎ በመልአኩ ተነግሮአታል፤ እርስዋም አምና ተቀብላለች፡፡ ለዚህ ታላቅ በረከትና መዳን በመሣሪያነት እርሷ መመረጥዋንም ልዩ ዕድል መኾኑን አልዘነጋችም፡፡ እንግዲህ እነዚህ ዓበይት ነገሮች በእመቤታችን አእምሮ ውሰጥ ከፍተኛ ስፍራ ነበራቸውና ያለ ምስጋና ልታልፋቸው አልፈለገችም፡፡ በመኾኑም የኾነው ነገር በሙሉ ለእርስዋና ለሰው ልጆች ዅሉ መኾኑን በሚገልጽ ኃይለ ቃል የአምልኮ ምስጋናዋን ለፈጣሪዋ ለእግዚአብሔር ግሩም በኾነ ኹኔታ አቅርባለች፡፡

በምስጋናዋም ‹‹ነፍሴ እግዚአብሔርን ከፍ ከፍ ታደርገዋለች፤ መንፈሴም በአምላኬና በመድኃኒቴ ደስ ይላታል፡፡ የባርያይቱን ውርደት አይቶአልና፤ እነሆ ከዛሬ ጀምሮ ትውልድ ዅሉ ‹ብፅዕት ነሽ› ይሉኛል፡፡ እርሱ ታላላቅ ሥራዎችን ሠርቶልኛልና፤›› የሚል ጥልቅ ምሥጢር ያለው ኃይለ ቃል ይገኝበታል፡፡ ይኸውም ‹‹ብዙኃ አበዝኆ ለሕማምኪ ወለፃዕርኪ በሕማም ለዲ፤ ምጥሽን ጣርሽን እጅግ አበዛዋለሁ፤ በጭንቅም ትወልጂያለሽ›› የሚል መርገም ተሸክማ በመከራ የኖረችውና ይህንን መከራ ለልጆችዋ ያወረሰችው ሔዋን በእርስዋ ጊዜና መሣርያነት ከመርገም ተላቃ ወደ ገነት የምትመለስበት ጊዜ እየተቃረበ መምጣቱን ስታመለክት ‹‹የባርያይቱን ውርደት ተመልክቶአልና ነፍሴ እግዚአብሔርን ከፍ ከፍ ታደርገዋለች›› በማለት አመሰገነች፡፡

የሰው ልጅን በአጠቃላይ ከገጠመው ውድቀት ለመታደግ እግዚአብሔር በጀመረው ነገረ አድኅኖ ከኃይል ዅሉ የበለጠ ኃይል እግዚአብሔር ወልድ በማኅፀኗ ማደሩ፣ እንደዚሁም እርስዋ ለዚህ የበቃች ቅድስት፣ ንጽሕት፣ ቡርክት፣ ልዕልት፣ ብፅዕትና ከሴቶች ዅሉ የተለየች ምልእተ ጸጋ፣ ሙኃዘ ፍሥሐ፣ የእግዚአብሔር ልዩ ባለሟልና የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያ አድርጎ መምረጡንና ማክበሩን ዅሉ ለእርስዋ የተደረጉ ታላላቅ ነገሮች መኾናቸውን በመገንዘብዋ እመቤታችን ‹‹ታላላቅ ሥራዎችን ሠርቶልኛልና መንፈሴ በአምላኬና በመድኃኒቴ ደስ ይላታል›› በማለት ፈጣሪዋን አመስግናለች፡፡ ከዚህም አይይዛ በእግዚአብሔር መልእክተኛ በቅዱስ ገብርኤልና መንፈስ ቅዱስ በሞላባት በቅድስት ኤልሳቤጥ የተገለጸው ቅድስናዋና ብፅዕናዋ ዘመንና የስሑታን ትምህርት ሳይገቱት ከትውልድ ወደ ትውልድ ሳይቋረጥ እንደ ወራጅ ውኃ እስከ ዕለተ ምጽአት እንደሚነገርና እንደሚተገበር በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝታ ተናግራለች፡፡ ቤተ ክርስቲያናችንም የእመቤታችንን ብፅዕና አክባሪና ከአማላጅነቷ ተጠቀሚ ኾና መገኝቷ የእግዚአብሔርን ፈቃድ በደምብ ያወቀችና ቃሉን በምልአት የተቀበለች መኾኗን ያረጋግጣል፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት

ከቅድስት ድንግል ማርያም የምስጋና ቃል የምንማረው ብዙ ትምህርት እንዳለ ማስተዋልና መገንዘብ ተገቢ ነው፡፡ ከዅሉ በፊት ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም የተነገሩ ነገሮች በሙሉ ከፍጡራን መንጭተው የተነገሩ ሳይኾኑ ከእግዚአብሔር በቀጥታ ከተላከው መልአክ ከቅዱስ ገብርኤል፣ መንፈስ ቅዱስ ከሞላባት ከቅድስት ኤልሳቤጥና እንደዚሁም ‹‹መንፈስ ቅዱስ ባንቺ ላይ ይመጣል›› ከተባለላት ከቅድስት ድንግል ማርያም የተነገሩ በመኾናቸው ምንጫቸውና ተናጋሪያቸው ራሱ እግዚአብሔር እንደ ኾነ መገንዘቡ አያዳግትም፡፡ ምክንያቱም ተላኪ የላኪውን፣ መንፈስ ቅዱስ ያደረበት የመንፈስ ቅዱስን ቃል እንደሚናገር ለዅሉም ግልጽ ነውና፡፡

ቅዱስ መጽሐፍም እነዚህን በጥንቃቄ መዝግቦ መገኘቱ ይህንን እንድንገነዘበው ብሎ እንደ ኾነ ጥርጥር የለውም፡፡ ከዚህ አንጻር እግዚአብሔር ራሱ በፍጹም ክብር ያከበራትንና ትውልድ ዅሉ ‹‹ብፅዕት ነሽ›› እያሉ እንዲያመሰግኗት በቅዱስ መንፈሱ ያናገረላትን ቅድስት ደንግል ማርያምን ማክበርና ማመስገን፣ ብፅዕናዋንና ቅድስናዋን ማመን፣ መስበክና ማስተማር የእግዚአብሔርን ቃል በትክክል ተረድቶ ለቃሉ መታዘዝና ለተግባራዊነቱ መቆም እንደ ኾነ ለሕዝበ ክርስቲያን ዅሉ ግልጽ ሊኾንለት ይገባል፡፡    ቅድስት ድንግል ማርያም እግዚአብሔር ላደረገላት ታላቅ ነገር ዅሉ ምስጋናን፣ አምልኮትንና ምስክርነትን በመስጠት ለእኛ መልካም አስተማሪና አርአያ መኾኗን ማስተዋል ከዅላችንም ይጠበቃል፡፡

ዅላችንም ልብ ብለን ካየነው እግዚአብሔር ለሰው ልጅ በአጠቃላይ ታላላቅ ሥራዎችን ያልሠራበት ቀን አይገኝም፡፡ ነገር ግን በየጊዜው ለሠራልን ሥራዎች ተገቢ ዕውቅና በመስጠትና በመመስከር እንደ ቅድስት ድንግል ማርያም በደስታ የአምልኮ ምስጋናን ለእግዚአብሔር የሚያቀርቡ ስንት ናቸው? የሚለውን ጥያቄ ብናነሣ መልሱ አስቸጋሪ ሳይኾን አይቀርም፡፡ ድሮም የተፈጠርነው ለምስጋና ነውና እግዚአብሔር ያለ ማቋረጥ ዅልጊዜም ታላላቅ ነገሮችን እየሠራልን እንደ ኾነ አውቀንና አምነን ለእርሱ የሚገባ የአምልኮ ምስጋና ልናቀርብ ይገባል፡፡ ከዘመነ ሐዋርያት ጀምሮ በቀኖና ጸድቆ በጥንታውያንና በኦርቶዶክሳውያን አብያተ ክርስቲያናት ዅሉ እየተፈጸመ የሚገኘው የቅድስት ድንግል ማርያም ጾመ ፍልሰታ ዓላማም እግዚአብሔርን በምስጋና፣ በቅዳሴ፣ በውዳሴ ለማምለክ፤ ለቅዱስ ቃሉ ፍጹም ታዛዥ በመኾን ምሥጢረ ቊርባንን ለመቀበልና ከኃጢአት ሸክም ተላቀን ከእግዚብሔር ጋር የጠበቀ ግንኙነት ለመፍጠር ነው፡፡

የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ምእመናንና ምእመናት

በዘመነ ብሉይም ኾነ በዘመነ ሐዲስ የእግዚአብሔር ሞገስና ጸጋ አግኝተው ለቅድስና ደረጃ የበቁ ቅዱሳን ዅሉ ጸሎታቸውና ተማኅጽኖአቸው ለራሳቸው ብቻ ሳይኾን ለዓለሙ ዅሉ እንደሚተርፍ ቅዱስ መጽሐፍ በትምህርትም ኾነ በተግባር ያረጋገጠውና የመዘገበው ነው፡፡ ይልቁንም ‹‹እስመ ረከብኪ ሞገሰ በኀበ እግዚአብሔር፤ ከእግዚአብሔር ዘንድ ባለሟልነትን አግኝተሻልና ‹ምልእተ ጸጋ ነሽ፤ ደስ ይበልሽ››› ብሎ እግዚአብሔር በመልእክተኛው ያረጋገጠላት ቅድስት ድንግል ማርያም ባላት ከፍተኛ የእግዚአብሔር ባለሟልነት በጸሎቷ፣ በአማላጅነቷና ወደ እግዚአብሔር በምታቀርበው ተማኅጽኖ ግዳጃችንን እንደምትፈጽም የቃና ዘገሊላው ምልጃዋና የተገኘው በረከት በቂ ማስረጃችን ነው፡፡

በመኾኑም የጾመ ፍልሰታ ሱባዔ እግዚአብሔርን በአባትነት፣ ቅድስት ድንግል ማርያምን በእናትነት የምናገኝበት ልዩ ወቅት በመኾኑ እግዚአብሔር በቃሉ የተናገረውን በመከተልና እንደ ቃሉ በመመላለስ ጾሙን ልንጾም ይገባል፡፡ ከዅሉ በላይ ደግሞ በፍቅርና በሰላም፣ በመተጋገዝና በመረዳዳት፣ በንስሐና በጸሎት፣ ቅዱስ ቊርባንን በመቀበልና ሰውን ሳይኾን እግዚአብሔርን በማዳመጥና በመከተል መጾም ይኖርብናል፡፡ ይህ ጾም የአገራችንን አንድነትና ነጻነት፣ የሕዝባችንን አብሮነትና የእርስ በርስ መተሳሰብ፣ እግዚአብሔርን የመፍራትና ድንግል ማርያምን የመውደድ፣ ሃይማኖታዊና ኢትዮጵያዊ ዕሴቶችን ዅሉ አዳብሮ ጥሩ ሰብእና ያለው ማኅበረሰብን ያፈራ፤ እንደ አሸንዳ የመሳሰሉ ሃይማኖታዊና ሀገራዊ ባህሎችን የገነባ ጾም ስለሆነ ለሃይማኖታችን መጠበቅ፣ ለአገራችን መልካም ገጽታ ግንባታና ለልማት መፋጠን እንደዚሁም ለቱሪዝም ክፍለ አኮኖሚ መበልጸግ የሚሰጠው ጥቅም ከፍተኛ ስለ ኾነ ሃይማኖታዊ፣ ባህላዊና ሀገራዊ ይዘቱ ተጠብቆ እንዲቀጥል ኢትዮጵያዊ የኾነ ዅሉ የበኩሉን ሊወጣ ይገባል፡፡

በመጨረሻም

የጾም ወቅት ምእመናን ከእግዚአብሔር ጋር የሚገናኙበት፣ ርኅራኄና አዘኔታ ለሰው ልጅ ዅሉ የሚያደርጉበት እንደ መኾኑ መጠን፣ ምእመናን እጆቻቸውን ለተቸገሩ ወገኖች እንዲዘረጉ፣ ስለ አገርና ስለ ዓለም ዅሉ ሰላም መጠበቅ ወደ እግዚአብሔር ጸሎት እንዲያቀርቡ፣ በአገራችን እየተካሔደ ያለው ዙርያ መለስ የልማትና የዕድገት ሽግግር እንዲሠምር በፍቅርና በሰላም ቆመው በአንድነት ጸሎታቸውን ዅሉን ወደሚችል ወደ ኃያሉ እግዚአብሔር ለማቅረብ እንዲተጉ አባታዊ መልእክታችንን በእግዚአብሔር ስም እናስተላልፋለን፡፡

‹‹ወትረ ድንግል ማርያም››

እግዚአብሔር አምላክ ኢትዮጵያንና ሕዝባችንን ይባርክ፤ ይቀድስ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

 ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

 ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት

ነሐሴ ፩ ቀን ፳፻ወ፱ ዓ.ም፡፡

የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት በአፋን ኦሮሞ

ሐምሌ ፯ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ሒዱና አሕዛብን ዅሉ በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው ያዘዝኋችሁንም ዅሉ እንዲጠብቁ እያስተማራችኋቸው ደቀ መዛሙርት አድርጓቸው›› (ማቴ. ፳፰፥፲፱) ሲል በአምላካዊ ቃሉ ያዘዘውን መሠረት በማድረግና የቅዱሳን ሐዋርያትን ፈለግ በመከተል ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በርካታ ሰባክያንን እያስተማረች በየቦታው ስታሰማራ ኖራለች፤ ወደፊትም ይህንን ተልእኮዋን አጠናክራ ትቀጥላለች፡፡ ምክንያቱም ስብከተ ወንጌል ቃለ እግዚአብሔርን ለማስተማር ብቻ ሳይኾን የሰውን አእምሮ ለማልማት (መልካም አስተሳሰብን ለመገንባት) የሚያስችል ዋነኛው የቤተ ክርስቲያን መሣርያ ነውና፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መሥራቿ የዅሉም አምላክ፣ የዅሉም ጌታ፣ የዅሉም መድኀኒት የኾነው ኢየሱስ ክርስቶስ ነውና እንደ ጌታዋ ዘር፣ ጎሣ፣ ቀለም፣ ጾታ ሳትለይ በተዋሕዶ ሃይማኖት ጥላ ሥር የተሰባሰቡ ምእመናንን በአንድነት ተቀብላ ታስተናግዳቸዋለች፡፡ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት መፋጠን በልዩ ልዩ የአገልግሎት ዘርፍ የሚሳተፉ ልጆቿም ይህንኑ ዓላማዋን ለማሳካት የመትጋት መንፈሳዊ ግዴታ አለባቸው፡፡ ‹‹ወንድሞች በኅብረት ቢቀመጡ እነሆ መልካም ነው፤ እነሆም ያማረ ነው፤›› (መዝ. ፻፴፪፥፩) ተብሎ በመጽሐፍ ቅዱስ እንደ ተጻፈው፣ በዓለማዊ ብሂልም ‹‹ከአንድ ብርቱ ሁለት መድኀኒቱ›› እንደሚባለው በኅብረት በመሰባሰብ የሚፈጸም መንፈሳዊ ተግባር ውጤታማነቱ የሠመረ ነው፡፡

በማኅበር ተሰባስበው መንፈሳዊ አገልግሎት ከሚሰጡ ማኅበራት መካከል አንዱ የኾነው፤ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ልዩ ልዩ ክፍተት ለመሸፈን የሚያስችል መንፈሳዊ ዓላማ እና ርእይን ሰንቆ በቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ የተመሠረተው ማኅበረ ቅዱሳንም ለሃያ አምስት ዓመታት ያህል ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በትጋት ሲያገለግል እስከ ዛሬ ድረስ ቆይቷል፡፡ ለወደፊቱም እግዚአብሔር እስከፈቀደለት ጊዜ ድረስ አገልግሎት መስጠቱን ይቀጥላል፡፡ በልዩ ልዩ መገናኛ መንገዶች እንደሚገለጸው ማኅበረ ቅዱሳን ከአመሠራረቱ ጀምሮ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልእኮዋን አስፋፍታ፣ መንፈሳዊ ዓላማዋን ከግብ አድርሳ፣ ከችግሮቿ ወጥታ ለሕዝቦቿ መንፈሳዊና ማኅበራዊ የሕይወት ለውጥ ቀዳሚ ሚናዋን እንድትወጣ ለመደገፍ የሚተጋ መንፈሳዊ ማኅበር ነው፡፡

ማኅበሩ በየግቢ ጉባኤያቱ ትምህርተ ሃይማኖትን ከሚያስተምራቸው ወንድሞችና እኅቶች በተጨማሪ ከአባቶችና ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመመካከር በልዩ ልዩ የአገራችን ክፍሎች የሚገኙ ሰባክያነ ወንጌልን በየቋንቋቸው እያሠለጠነ፣ በአባቶች ቡራኬ እያስመረቀ ለስብከተ ወንጌል አገልግሎት እንዲሠማሩ አድርጓል፡፡ በእነዚህ ሰባክያን አገልግሎትም ከሰማንያ አምስት ሺሕ ሰባት መቶ የሚበልጡ በልዩ ልዩ ጠረፋማ አካባቢዎች የሚኖሩ አዳዲስ አማንያን የሥላሴ ልጅነትን አግኝተዋል፡፡ በዚህ መልኩ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እያገለገለ የሚገኘው ማኅበረ ቅዱሳን በአጠቃላይ በልዩ ልዩ ቋንቋ በርካታ መንፈሳውያን ተግባራትን አከናውኗል፡፡ በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ‹‹ይህን ሠርቻለሁ›› ብሎ መናገር ተገቢ ባይኾንም፣ ለቍጥጥር እና ለግምገማ ያመች ዘንድ ማኅበሩ በየጊዜው የአገልግሎት ሪፖርት ያቀርባል፡፡ በዚህ ጽሑፍም በአፋን ኦሮሞ የሚሰጠውን አገልግሎት በሚመለከት አጠር ያለ ግንዛቤ የሚያስጨብጥ መልእክት ይዘን ቀርበናል፡፡

የተወደዳችሁ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባቶች እና ምእመናን!

ማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎቱን ሲጀምር ከነበረበት የሰው ኃይል እና እጥረት አኳያ በአማርኛ ቋንቋ በመጽሔት፣ በጋዜጣ፣ በበራሪ ወረቀት፣ በመጻሕፍት፣ በካሴት፣ በምስል ወድምፅ የሚቻለውን ዅሉ መንፈሳዊ ተግባር ሲያከናውን ቆይቷል፡፡ አሁን አሁን ደግሞ የምእመናን ፍላጎት እየጨመረ፤ ማኅበሩም በሰው ኃይል እየተጠናከረ በመምጣቱ አገልግሎቱን ይበልጥ አሳድጎ በአፋን ኦሮሞ፣ በትግርኛ፣ በወላይትኛ፣ በእንግሊዝኛ፣ በመሳሰሉት የአገር ውስጥ እና የውጭ አገር ቋንቋዎች ወንጌልን ለማስተማር በመፋጠን ላይ ነው፡፡

ከዚህ ቀደም በአፋን ኦሮሞ ከተሠሩ ሥራዎች መካከል ጥቂቶቹን ለመጥቀስ ያህል፡-

  • በግእዝና አማርኛ ቋንቋዎች የታተሙ የትምህርተ ሃይማኖት እና የጸሎት መጻሕፍትን ወደ አፋን ኦሮሞ አስተርጕሟል፤ ከእነዚህ መካከል የዘወትር ጸሎት፣ ውዳሴ ማርያም፣ ውዳሴ አምላክ እና ሰይፈ ሥላሴ ተጠቃሾች ናቸው፡፡
  • ሌሎች አዳዲስ መጻሕፍትንም በቋንቋው አዘጋጅቶ አሠራጭቷል፡፡
  • በሦስት ወር አንድ ጊዜ ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች የምትዘጋጀው ጉባኤ ቃና መጽሔትን ወደ ቋንቋው አስተርጕሞ በየግቢ ጉባኤያቱ አሠራጭቷል፡፡
  • Dhangaa Lubbuu (ዳንጋ ሉቡ) የተሰኘችውን መጽሔት ለዅሉም ክርስቲያን በሚመጥን ዐምድ በየሦስት ወሩ በማዘጋጀት እያሠራጨ ይገኛል፡፡
  • በአፋን ኦሮሞ አራት የመዝሙር አልበሞችን አሠራጭቷል፤ ኦርቶዶክሳዊ የመዝሙር ጥራዝም አሳትሟል፡፡
  • ልዩ ልዩ የቪሲዲ ስብከቶችንና መዝሙሮችን አዘጋጅቶ ለምእመናን እንዲዳረሱ አድርጓል፡፡
  • በክልሉ የሚገኙ አብያተ ክርስቲያናትን አገልግሎትና ታሪክ የተመለከቱ ልዩ ልዩ ጥናታዊ ጽሑፎችን አዘጋጅቶ አሳትሟል፡፡
  • በአፋን ኦሮሞ ለሚያስተምሩ ሰባክያነ ወንጌል በዐሥራ ሦስት ዙር የክረምት ሥልጠና ሲሰጥ ቆይቷል፤ በዚህ ዓመትም ከዘጠና በላይ አገልጋዮችን ለማሠልጠን ዝግጅቱን አጠናቋል፡፡
  • ከአሁን በፊት በአፋን ኦሮሞ የሚተላለፍ ሳምንታዊ መንፈሳዊ የቴሌቭዥን መርሐ ግብር እያዘጋጀ ሲያቀርብ የቆየ ሲኾን፣ ለወደፊቱም ይህንኑ ሥራውን አጠናክሮ ይቀጥላል፡፡
  • መካነ ድር ከማዘጋጀት ባሻገር ወቅታዊ ትምህርት የሚሰጥበት ወርኃዊ ጉባኤ በማካሔድም ሕዝበ ክርስቲያኑን በአፋን ኦሮሞ ወንጌልን በማስተማር ላይ ይገኛል፡፡
  • በአገራችን ግቢ ጉባኤያት ካሏቸው ዐርባ ሰባት ማእከላት በሠላሳ ስምንቱ የአፋን ኦሮሞ መርሐ ግብር እንዲኖርና ተማሪዎች በቋንቋቸው ኮርስ እንዲማሩ፣ የጽዋ እና ጸሎት መርሐ ግብራት እንዲያካሔዱ፣ መዝሙራትን እንዲያጠኑና እንዲያቀርቡ አድርጓል፤ በማድረግ ላይም ነው፡፡
  • በተጠኑ የክልሉ ቦታዎች አዳሪ የአብነት ትምህርት ቤቶችን በመመሥረት አፋን ኦሮሞ የሚችሉ ዲያቆናትና ካህናትን እንዲሁም ሰባክያነ ወንጌልን አስተምሮ ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በማሠማራት ላይ ሲኾን ለዚሁም በምዕራብ ወለጋ የሚገኘውን የቂልጡ ካራ አቡነ ገብረ መንፈስ ቅዱስ እና በጅማ ሀገረ ስብከት ሥር ያለውን የአበልቲ ኪዳነ ምሕረት ገዳማት የአብነት ትምህርት ቤቶችን እንደ ማስረጃነት መጥቀስ ይቻላል፡፡
  • በግቢ ጉባኤያት የምረቃ መጽሔት ላይ ልዩ ልዩ ትምህርታዊ ጽሑፎችና መልእክቶችን በአፋን ኦሮሞ እያቀረበ ነው፡፡
  • በክልሉ ያሉ ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶች እንዲጠናከሩ ፕሮጀክቶችን ቀርፆ በመተግበር፣ መምህራንና ደቀ መዛሙርትን በመደጎም፣ ቋንቋውን የሚችሉ ዲያቆናትና ካህናት እንዲፈሩ በማደረግ በርካታ የክልሉ ምእመናን በሃይማኖታቸው እንዲጸኑ፣ የተዘጉ አብያተ ክርስቲያናት ተከፍተው አገልግሎት እንዲሰጡ የበኩሉን አስተዋጽዖ አበርክቷል፤ የባሌ፣ የምሥራቅ ሐረርጌና የነገሌ ቦረና አህጉረ ስብከት አብነት ትምህርት ቤቶች ተጠቃሾች ናቸው፡፡
  • ከዚሁ ዅሉ ጋርም የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር ሲያዘጋጅ ለኦሮምያ ክልል ቅድሚያ በመስጠት፣ የጉባኤው ተሳታፊዎችን በማስተባበር የገቢ እጥረት ላለባቸው የክልሉ አብያተ ክርስቲያናት በመቶ ሺሕ የሚቈጠር የገንዘብ ድጋፍ እንዲያገኙ አድርጓል፡፡ በመርሐ ግብሮቹ የሚቀርቡ ትምህርቶችንም በአፋን ኦሮሞ በማስተርጐም ለአካባቢው ሕዝበ ክርስቲያን አቅርቧል፡፡

ማኅበሩ ለወደፊት በአፋን ኦሮሞ ለመሥራት ካቀዳቸው ተግባራት መካከል ከፊሎቹ

  • መንፈሳዊ የቴሌቭዥን እና የሬድዮ መርሐ ግብር ማዘጋጀት፣
  • ወርኃዊ የሬድዮ መጽሔት ማዘጋጀት፣
  • ዕቅበተ እምነት ላይ ትኩረት ያደረጉ ልዩ ልዩ መጻሕፍትን ማሳተም፣
  • ልዩ ልዩ ቅዱሳት መጻፍትን ወደ አፋን ኦሮሞ ማስተርጐም፣
  • የሕፃናት መጻሕፍትንና መንፈሳዊ ፊልሞችን ማዘጋጀት፣
  • ወጣቶች ምእመናን የኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ጠንቅቀው እንዲያውቁ የሚያግዙ ማስተማሪያ አፕሊኬሽኖችን ማዘጋጀት ማኅበሩ በዕቅድ የያዛቸው ተግባራት ናቸው፡፡ በተጨማሪም የሬድዮና ቴሌቭዥን መርሐ ግብሮችን መከታተል ለማይችሉ የገጠር ምእመናን የዘመኑን ቴክኖሎጂ በመጠቀም በሚኖሩበት ቦታ ኾነው ቃለ እግዚአብሔርን እንዲማሩ ለማድረግ የሚያስችል ዕቅድም አለው፡፡

የተወደዳችሁ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባቶች እና ምእመናን!

ቤተ ክርስቲያን የሰጠችውን ሓላፊነትና የአባቶችን አደራ ተቀብሎ ወንጌለ መንግሥትን በመላው ዓለም ለማዳረስ የሚተጋው ማኅበረ ቅዱሳን በቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅር ሥር ያለ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተምህሮና መሠረተ እምነት የሚጠብቅና የሚያስጠብቅ፣ በቅዱስ ሲኖዶስ የጸደቀ ደንብ የተሰጠውና በደንቡ መሠረት ብቻ የሚመራ ማኅበር እንጂ ራሱን የቻለ የእምነት ተቋም አይደለም፡፡ አባላቱም ለአንድ መንፈሳዊ ዓላማ ከመላው ኢትዮጵያ የተሰባሰቡ የተዋሕዶ ልጆች እንጂ የአንድ አካባቢ ተወላጆችና አንድ ብቻ ቋንቋ ተናጋሪዎች አይደሉም፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን ምእመናን በሚሰሙት ቋንቋ ዅሉ ቃለ እግዚአብሔርን ተምረው ለመንግሥተ ሰማይ ይበቁ ዘንድ የሚጠበቅበትን መንፈሳዊና አገራዊ ድርሻ በአግባቡ ለመወጣት የሚሠራ፤ በአጠቃላይ ለመንፈሳዊ ተልእኮ የሚፋጠን ማኅበር ነው፡፡

ማኅበሩ በግልጽና በይፋ ከሚፈጽመው መንፈሳዊ አገልግሎት ውጪ በስውር የሚሠራው አንዳችም የተለየ ተልእኮ የለውም፡፡ ምእመናን በሚሰሙት ቋንቋ ቃለ እግዚአብሔርን እንዳይማሩም እንቅፋት አይፈጥርም፡፡ እንደዚህ ዓይነት አሠራርም በፍጹም የለውም፡፡ ማኅበሩ የዅሉንም ሕዝበ ክርስቲያን ፍላጎት ሙሉ በሙሉ አሟልቻለሁ ባይልም ምእመናን በየቋንቋቸው ወንልን እንዳይማሩ አለማድረጉን፤ ለወደፊትም እንደዚህ ዓይነት ተልእኮ የሚፈጽም ማኅበር አለመኾኑን ቅዱስ ሲኖዶስ እና መላው ሕዝበ ክርስቲያን እንዲገነዘቡለት ያሳስባል፡፡ በመጨረሻም ማኅበረ ቅዱሳን በኦሮምያ ለሚገኙ ምእመናን ሰፊ አገልግሎት ለመስጠት ካለው ቁርጠኝነት የተነሣ የአፋን ኦሮሞ ሚዲያ ፕሮጀክት በሚል ስያሜ መርሐ ግብር አቋቁሞ፣ በጀት መድቦ በተጠናከረ መልኩ አገልግሎቱን በመፈጸም ላይ መኾኑን በዚህ አጋጣሚ እየገለጸ፣ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንን አገልግሎት ከዚህ በበለጠ መልኩ እንዲቀላጠፍ ለማድረግ ይቻል ዘንድም መላው ሕዝበ ክርስቲያን ማኅበሩ የሚሰጠውን አገልግሎት ቀርባችሁ ደግፉ ሲል በእግዚአብሔር ስም መንፈሳዊ ጥሪውን ያቀርባል፡፡

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን!

 ማኅበረ ቅዱሳን