በአንድ እጅ ማጨብጨብ እንዳይሆን

ከመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት እና ከየአህጉረ ስብከቱ ሊቃነ ጳጳሳት የስብከተ ወንጌል ፍቃድ ሳይኖራቸው በየቤተ ክርስቲያኑ ዐውደ ምሕረት በሕዝበ ክርስቲያኑ መካከል እየተገኙ እንሰብካለን እናስተምራለን በማለት የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሥርዓትና መመሪያ በሚጥሱ  ሕገወጥ ሰባክያን፤ ከቤተ ክርስቲያን ዕውቅናና ፈቃድ ውጪ በጉባኤ ሊቃውንት ያልታዩና ያልተመረመሩ የተለያዩ የኅትመት ውጤቶች፤ መጻሕፍት፣ የስብከት የመዝሙር የምስል ወድምፅ /ኦዲዮ ቪዲዮ/ ካሴቶች እየተሠራጩ፤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን መሠረተ እምነት፣ ሥርዓትና ትውፊት የሚጥሱ ተግባራት ሲፈጸሙ ይታያል፡፡

ይህንኑ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ሥርዓትና አሠራር ውጪ የሆነ ሕገወጥ ተግባር የተገነዘበው ቅዱስ ሲኖዶስ፤ የቅድስት ቤተ ክርስቲያን መሠረተ እምነትና ሥርዓት አካሔድ አቅጣጫውን ሳይስት ተጠብቆ እንደቆየ ሁሉ ወደፊትም መቀጠል ስላለበት፤ የካቲት 12 ቀን 2001 ዓ. ም. ባደረገው ስብሰባ ውሳኔ ሰጥቷል፡፡ በቁጥር ል/ጽ/382/2001 የካቲት 16 ቀን 2001 ዓ.ም በተጻፈ ደብዳቤ፤

1ኛ. በዚህ ውሳኔ መሠረት፤ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤትና ከየአህጉረ ስብከቱ ሊቃነ ጳጳሳት የስብከተ ወንጌል ፈቃድ ሳይኖራቸው እንዳይሰብኩ በቅዱስ ሲኖዶስ የተከለከለ ስለሆነ፤ የቅዱስ ሲኖዶስ መመሪያ ከሀገረ ስብከት እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን በየደረጃው ባለው መዋቅር ተግባራዊ እንዲሆን፤

2ኛ. የእያንዳንዱ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ የተጣለበትን ሓላፊነት ተገንዝቦ የመቆጣጠሩን ተግባር በማጠናከር የቤተ ክርስቲያኒቱን ህልውና ከሚፈታተን ተግባር    እንዲጠብቅ፤

3ኛ. በጉባኤ ሊቃውንት ተመርምረው ዕውቅና ሳይሰጣቸው በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰም የሚሠራጩ የኅትመት ውጤቶች፤ መጻሕፍት፣ በምስል ወድምፅ /ኦዲዮ ቪዲዮ/ የተዘጋጁ ስብከቶች መዝሙሮች ጥብቅ ቁጥጥር እንዲደረግባቸው፤

4ኛ. በስብከተ ወንጌል ትምህርት አሰጣጡና በሥርጭቱ ረገድ በቁጥጥሩ የሥራ ሒደት አፈጻጸም ወቅት ከቤተ ክርስቲያኒቱ ዕውቅናና ፈቃድ ውጪ የሆነ ከአቅም በላይ ችግር ሲያጋጥም ለሚመለከታቸው የመንግሥት አካላት ጭምር በመግለጽ ችግሩ ሕጋዊ መፍትሔ እንዲያገኝ፤ በማለት መመሪያ ማስተላለፉ ይታወቃል፡፡

ይህንኑ ተከትሎ በአሁኑ ወቅት ጐልተው የሚታዩትን የስብከተ ወንጌል ችግሮች ለመፍታት የሚያስችል ሴሚናር፤ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ አዘጋጅነት መስከረም 11 እና 12 ቀን 2003 ዓ.ም በጠቅላይ ቤተክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሽ መካሔዱም ይታወሳል፡፡

በዚህ ቅዱስ ፓትርያሪኩ በተገኙበትና መመሪያ ባስተላለፉበት፣ ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት፣ በየአህጉረ ስብከቱ፣ አድባራትና ገዳማቱ ስብከተ ወንጌልን በማሰፋፋት ረገድ ዐቢይ ሚና ያላቸው ሓላፊዎች፣ ሰባክያንና ዘማርያን በተሳተፉበት ውይይት፤ የቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓትና አሠራር ተጠብቆ መንፈሳዊ አገልግሎቷም በአግባቡ እንዲፈጸም የሚረዱ ውሳኔዎችም ተወስነዋል፡፡

የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሥርዓትና አሠራር ለማስጠበቅ የተላለፉትን መመሪያዎች በማስፈጸም ረገድ በጠቅላይ ቤተክህነት የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ በርካታ ሥራዎችን አከናውኗል፡፡

በየአህጉረ ስብከቱ ስምሪት በማድረግ ከሚመለከታቸው ሓላፊዎች፣ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት አስተባባሪዎችና መምህራነ ወንጌል በአጠቃላይ ከደቀ መዛሙርት አገልጋዮች ጋር በተካሔዱ ተከታታይ ውይይቶች የተደረሰበት የጋራ ግንዛቤ ለአፈጻጸሙ አጋዥ ኃይል ሆኗል፡፡ በመምሪያው ሥር በሚያገለግሉ ሊቃነ ካህናት አማካኝነት በየአህጉረ ስብከቱ በርካታ የስብከተ ወንጌል ጉባኤያት ተካሒደዋል፡፡

ማእከላዊነቱን የጠበቀ የቤተ ክርስቲያኒቱ አንድ ድምፅ ወጥ ለሆነው የስብከተ ወንጌል አገልግሎት መስፋፋት መሠረት ነው፡፡ ስለዚህ ከቀደሙት አባቶች የተረከብነው የቤተ ክርስቲያኒቱ መዋቅራዊ ቅብብሎሽ እንደተጠበቀ ዶግማዋ፣ ቀኖናዋና ትውፊቷ ወደፊትም ለትውልድ እንዲተላለፍ የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያው ከፍተኛ እንቅሰቃሴ እያደረገ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያኒቱ መምህራነ ወንጌልም ሥርዓትና መመሪያውን ጠብቀው መንፈሳዊ ተልእኮአቸውን እየፈጸሙ ሲሆን፤ መምሪያው ስብከተ ወንጌልን በማስፋፋት ረገድ ከሚመለከታቸው የቤተ ክርስቲያን አካላት ጋር አብሮ በመሥራት ላይ ይገኛል፡፡

በስብከተ ወንጌሉ አገልግሎት ረገድ አበረታች ጥረት እየተደረገ ቢታይም፤ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት መሠረት፤ የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔና መመሪያ በተሟላ ሁኔታ ተግባራዊ ለማድረግ በአንዳንድ አህጉረ ስብከት ችግሮች እያጋጠሙ ነው፡፡ ለምሳሌ በቅርቡ በሐዋሳ ከተማ ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ከጥር 20-22 ቀን 2003 ዓ.ም እንዲካሔድ ለተዘጋጀ ጉባኤ የሲዳማ ጌዲኦ፣ አማሮና ቡርጂ አህጉረ ስብከት ለጠቅላይ ቤተክህነት ስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ መምህራነ ወንጌል እንዲላኩለት ባቀረበው ጥያቄ መሠረት የተላኩት ሦስት መምህራን በተከሠተው ችግር ምክንያት የተላኩበትን የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ሳይፈጽሙ ለመመለስ ተገደዋል፡፡ ይህ ሁኔታ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተቃና መንፈሳዊ አገልግሎት አካሔድ ላይ እንቅፋት የሚፈጥር አሳዛኝ ድርጊት ነው፡፡

ለችግሩ ምክንያት የሆኑትም የራሳቸውን ዓላማና ፍላጐት ለማስፈጸም የሚያስቡና የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ዓላማ ያልተረዱ የተወሰኑ አካላት እንደሆኑ ከስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያው እና ከሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መግለጫ ለመረዳት ይቻላል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ከቤተ ክርስቲያን ዕውቅናና ፈቃድ ውጪ ስለሚሠራጩ የኅትመት ውጤቶች፤ መጻሕፍት፣ የስብከትና መዝሙር የምስል እና ድምፅ ካሴቶች የተላለፈው መመሪያ በአግባቡ ተፈጻሚ አለመሆኑን ከመምሪያው ሓላፊ ገለጻ እንገነዘባለን፡፡

በእርግጥ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ቅድሚያ ትኩረቷ በማስተማርና በመምከር ወደ መልካም መንገድ መመለስ እንደመሆኑ ይህንኑ ተግባሯን ትፈጽማለች፡፡ ሆኖም የቅድስት ቤተ ክርስቲያን እውነተኛ ልጆች አገልጋዮቿና ምእመናን ሁሉ ትምህርቷን ሰምተው፣ ሥርዓቷን   ጠብቀውና መመሪያዋን አክብረው የሚጠበቅባቸውን ሁሉ በአግባቡ መፈጸም ደግሞ ሃይማኖታዊ ግዴታቸው እንደሆነም የሚታወቅ ጉዳይ ነው፡፡

ከዚህ ቀደም በጠቅላይ ቤተክህነት ደረጃ በመምሪያው የተዘጋጀው ሴሚናርና፤ በየአህጉረ ስብከቱ በተደረገው ስምሪት የተካሔደው ውይይት በየደረጃው በሚገኙ ሓላፊዎች፣ ሊቃውንትና ሰባክያነ ወንጌል ዘንድ የጋራ ግንዛቤ እንዲኖር አስችሏል፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔና መመሪያዎች እንዲሁም የስብከተ ወንጌሉን አሠራርና ሥርዓቱን የጠበቀ አፈጻጸም በማስተዋወቅ ረገድ ጠቀሜታው እጅግ የጐላ ነው፡፡

እንዲህ ዓይነቱ በየደረጃው የሚካሔደው ውይይትና ተከታታይነት ያለው ተግባራዊ እንቅስቃሴ በየአህጉረ ስብከቱ እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን የሚገኙ አባቶች መምህራነ ወንጌልና አገልጋዮች ዘንድ የጋራ ግንዛቤና የተቀናጀ አሠራር ለማምጣት ከፍተኛ ጠቀሜታ ስላለው ወደፊትም ይህ ጥረት ተጠናክሮ መቀጠል ይኖርበታል፡፡

የቤተ ክርስቲያኒቷን ሐዋርያዊ ተልእኮ ለማሳካት ሥርዓቷን፣ መዋቅርና አሠራሯን አክብረውና ጠብቀው በየዘርፉ ለተሰማሩ አገልጋዮቿ ሁሉ ስለአገልግሎታቸው ሪፖርት ማቅረብ፤ ያከናወኑትን ተግባር አፈጻጸማቸውንና የአገልግሎታቸውን ውጤት መገምገም፤ በአጋጠሙ ችግሮች ላይ መወያየትና መፍትሔ መፈለግ፤ የወደፊቱን የአገልግሎት አቅጣጫ መተለም እና ማቀድ አስፈላጊ ነው፡፡ ይህ ሲሆን የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሥርዓትና መዋቅር ማስጠበቅ፣ መመሪያና አሠራሯ የበለጠ ውጤታማ እንዲሆን ለማድረግ ይቻላል፡፡ ከቤተ ክርስቲያኒቷ ሥርዓትና አሠራር ውጪ የሚሆኑትንም በአግባቡ ተከታትሎ በወቅቱ ለማረምና ለማስተካከል አመቺ ይሆናል፡፡

ሁላችንም የምንፈልገው ትክክለኛ አሠራርና መልካም ውጤት እንዲመጣ የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔና መመሪያ እንዲሁም የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያ ጥረት ብቻውን በቂ እንደማይሆን እንገነዘባለን፡፡

ለውሳኔዎቹና ለሚተላለፉት መመሪያዎች ተግባራዊ አፈጻጸም መሟላት የሚገባቸው አስፈላጊ ነገሮች ካልተሟሉ ውሳኔውም ሆነ መመሪያው በወረቀት፤ ዕቅዱም በሐሳብ ብቻ ተወስነው ይቀራሉ፡፡

የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሥርዓትና አሠራር አክብሮና ተከትሎ ስብከተ ወንጌልን ማስፋፋት ሌሎች ዘርፈ ብዙ መንፈሳዊ አገልግሎቷን ማስፈጸምም ሆነ መፈጸም ከጠቅላይ ቤተክህነት ጀምሮ እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን በተለያዩ ደረጃዎች የሚገኙ ሓላፊዎች፣ አባቶችና አገልጋዮች ሁሉ ቀዳሚ የሓላፊነት ግዴታቻው መሆኑ ይታወቃል፡፡ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት አክብረው የሚሠሩ ለሐዋርያዊ ተልእኮዋ መሳካት የበኩላቸውን ድርሻ የሚያበረክቱ፤ የተለያዩ ኅትመት ውጤቶች መጻሕፍት፣ የስብከተ ወንጌልና መዝሙር አዘጋጆች፣ ሰባክያነ፣ ዘማርያን፣ አሳታሚና አከፋፋዮች የአገልግሎቱ አካላት እንደመሆናቸው፤ የስብከተ ወንጌል መምሪያው በቤተ ክርስቲያን አሠሪርና መመሪያዎች ላይ በማወያየት የጋራ ግንዛቤ እንዲኖር መሥራት አለበት፡፡ እነሱም የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት እንዲጠበቅ የበኩላቸውን ክርስቲያናዊ ሓላፊነት ይወጡ ዘንድ ይገባልና፡፡ ምእመናንም እንደ ቤተ ክርስቲያን ልጅነታቸው የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሥርዓትና መመሪያ በሚገባ የመፈጸም የልጅነት ድርሻና ሃይማኖታዊ ግዴታ አለባቸው፡፡

እያንዳንዱ የአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ፤ በአጥቢያው የቤተ ክርስቲያኒቷን ዘርፈ ብዙ መንፈሳዊ አገልግሎት በተሳካ ሁኔታ እንዲፈጸም፣ ምእመናን በቤተ ክርስቲያናቸው ላይ ያላቸው እምነትና ተስፋ እንዲጠነክር፣ በሰላምና በፍቅር በተረጋጋ ሁኔታ የአገልገሎቷ ተጠቃሚዎች እንዲሆኑና ለዘለዓለማዊ ሕይወት እንዲበቁ፣ እንዲሁም የልጅነት ድርሻቸውን እንዲወጡ በማድረግ ረገድ፤ በመምራት፣ በማስተባበር፣ በቅርብ ሆኖ በመከታተል የተቃና እንዲሆን የተጣለበት አባታዊና መንፈሳዊ ሓላፊነት እጅግ ታላቅ ነው፡፡ ይህ ታላቅ መንፈሳዊ ሓላፊነት ከግል አሳብና አመለካከት ይልቅ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ዓላማ ቅድሚያ ሰጥተው እንዲያስፈጽሙ የሚያስገድዳቸው እንደሆነ እንገነዘባለን፡፡

ስለዚህ በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔና መመሪያ ላይ እንደተገለጸው፤ የአጥቢያ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪዎች የተጣለባቸውን ሓላፊነት ተገንዝበው በሚገባ የመምራትና የማስተባበር እንዲሁም የመቆጣጠሩን ተግባር በማጠናከር የቤተ ክርስቲያኒቱን ህልውና ከሚፈታተን ተግባር መጠበቅ አለባቸው፡፡

ምእመናንም ትክክለኛውን የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በመቀበል፣ ሥርዓትና መመሪያዋን በአግባቡ በመፈጸም በሰላምና በፍቅር ሃይማኖታዊ የልጅነት ድርሻቸውን መወጣት ይገባቸዋል፡፡

አሁን ባለንበት ዘመን የቴክኖሎጂው እድገትና ተደራሽነት አመቺ በሆነበት እና የሕዝቡም ፍላጐትና ጥያቄ በዚያው መጠን በጨመረበት ወቅት፤ እጅግ በርካታ የኅትመት ውጤቶች፤ መጻሕፍት፣ የስብከትና የመዝሙር የምስል እና የድምፅ ካሴቶች /ኦዲዮ ቪዲዮ/ እየተዘጋጁ መቅረባቸው አስፈላጊነቱ አያጠያይቅም፡፡

ስለዚህ የቤተ ክርስቲያኒቱን አሠራር ዘመናዊና ቀልጣፋ በማድረግ፤ ሊቃውንቱንና በሙያው የተዘጋጁ ብቁ ባለሙያ የሰው ኃይል ማሠማራት፣ አስፈላጊውን የአገልግሎት መሣሪያ ማሟላትና በቂ በጀት መመደብ ያስፈልጋል፡፡ ይህ ሲሆን የቤተ ክርስቲያኒቱን ሥርዓት ጠብቀው ለተዘጋጁ የኅትመት ውጤቶች መጻሕፍት፣ የስብከትና መዝሙር ካሴቶች የዕውቅናና ፍቃድ ጥያቄ አፋጣኝ ምላሽና የተቀላጠፈ አገልግሎት ለመስጠት ይቻላል፡፡

ይህንን ለማስፈጸም የስብከተ ወንጌልና ሐዋርያዊ ተልእኮ መምሪያው ብቸኛ ጥረት ብቻ በቂ እንደማይሆን ይታመናል፡፡

ስለዚህ ከቅዱስ ሲኖዶስ ጀምሮ የጠቅላይ ቤተክህነት ሓላፊዎችና በየደረጃው ያሉ የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ ትኩረትና ተግባራዊ ተሳትፎ ያስፈልጋል፡፡ መምሪያው    የተሰጠውን ተግባርና ሓላፊነት በብቃት እንዲያከናውን የቅርብ ክትትል ማድረግ፣ አፈጻጸሙን እየተከታተሉ በመገምገም አስፈላጊውን ሁሉ ማሟላት ይገባል፡፡ ምክንያቱም የቅድስት ቤተ ክርስቲያን ዶግማ፣ ሥርዓት እና አስተምህሮ እንዲሁም ወጥ የሆነው መዋቅራዊ አሠራሯ     ባልተከበረና በተጣሰ ቁጥር የቤተ ክርስቲያኗ ህልውና አጠያያቂ ሊሆን ይችላል፡፡ ለመናፍቃን ሥውር ተልእኮ ምእመናንን ሊያጋልጣቸው ይችላል፡፡ የግል ፍላጐትና ጥቅማቸውን ለማስጠበቅ የሚንቀሳቀሱ ጥቂት ግለሰቦችም የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን የምሕረት ዐደባባይ ያለአግባቡ እንዲጠቀሙበት ዕድል ይሰጣል፡፡ ስለዚህ የመምሪያው ጥረት ብቻውን በአንድ እጅ ማጨብጨብ እንዳይሆን  ትኩረት ሊሰጠው ይገባል እንላለን፡፡

ምንጭ፡ስምዐ ጽድቅ ከየካቲት 1-15/2003 ዓ.ም.

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

በደማቸው እንዳንጠየቅ ሥጋት አለን

በስብከተ ወንጌል ሐዋርያዊ ጉዞ ወቅት የምናስተውለው ችግር በሕዝቦች መካከል ያለው የቋንቋ ልዩነትና በነዚህ ቋንቋዎች ሠልጥነው የተዘጋጁ ልኡካን ማነስ ነበር፡፡ ይህ ችግር ብዙ ማኅበረሰቦችን ከስብከተ ወንጌል ተለይተው እንዲኖሩ ምክንያት ሆኗል፡፡ ከዚህም ሌላ ሕዝቡ በተለያዩ የእምነት ድርጅቶች እንዲወሰድና ከበረት እንዲወጣም ሆኗል፡፡

 

አሁን አሁን በመጠኑም ቢሆን የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት፣ ሰባክያን፣ መዘምራን፣ ማኅበራት ወዘተ ምእመናን በሚያውቁትና በሚረዱት ቋንቋቸው የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት እንዲያገኙ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ በማድረግ ላይ ይገኛሉ፡፡

መዝሙሮች፣ የትምህርትና የጸሎት መጻሕፍት ወዘተ ወደ ልዩ ልዩ የሀገራችን ቋንቋዎች በመተርጐም ላይ ናቸው፡፡ ከዚህም አለፍ ብሎ በየቋንቋው ትምህርት የሚሰጡ፣ መዝሙር የሚያዘጋጁ፣ የሚቀድሱና የሚናዝዙ ካህናትም እየተገኙ ነው፡፡

ይህን ችግር ለመቅረፍ በሰንበት ት/ቤቶች፣ በሰባክያን፣ በመዘምራን፣ በማኅበራት፣ በዲያቆናትና በካህናት የሚደረገው ጥረት በየአካባቢው ያለውን ሕዝብ ከመናፍቃን ቅሰጣ ታድጐ ቤተ ክርስቲያኑን እንዲያውቅ እያደረገው መሆኑን በየጊዜው የሚሰሙት ዜናዎች ያስረዳሉ፡፡

በበቂ ሁኔታም ባይሆን ማኅበረ ቅዱሳንም ይህን ችግር ለመቅረፍና አገልግሎቱን ለማስፋፋት መዝሙራቱን፣ የትምህርትና የጸሎት መጻሕፍቱን በየቋንቋው ከመተርጐም እና ከማዘጋጀት ባለፈ በአካባቢያቸው /በአፍ መፍቻ/ ቋንቋቸው ትምህርተ ወንጌልን የሚያስተምሩና በመቅደስ አገልግሎት የሚሳተፉ ወገኖች ከየአህጉረ ስብከቱ በየደረጃው ካሉ የቤተክርስቲያን ሓላፊዎች ጋር በመተባበር በርቀት ከጠረፋማ እና ገጠራማ አካባቢዎች ሠልጣኞችን በማስመጣት እያስተማረ ይገኛል፡፡ ለዚህም በቅርቡ ከየካቲት 1 እስከ የካቲት 15 ቀን 2002 ዓ. ም. ድረስ ከጋምቤላ ሀገረ ስብከት ከሰባት የገጠር ወረዳዎች ለተውጣጡ አሥራ ስድስት ተተኪ ሰባክያን የሰጠውን ሥልጠና መጥቀስ ይቻላል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን ስብከተ ወንጌል ካልተስፋፋባቸው የሀገሪቱ ገጠራማ እና ጠረፋማ የወረዳ ከተሞች የተተኪ ሰባክያን ሥልጠና ሲሰጥ ይሄኛው ለ11ኛ ጊዜ ሲሆን፤ እስከ አሁን ከየሀገረ ስብከቱ ሓላፊዎች ጋር በመነጋገር ከ96 የሀገሪቱ ጠረፋማ ወረዳዎች ለተውጣጡ ከሁለት መቶ በላይ ተተኪ መምህራን መሠረታዊ የቤተ ክርስቲያኒቱን ትምህርት ተምረው በቋንቋቸው ሕዝቡን እንዲያስተምሩ አሠልጥኖ አሰማርቷል፡፡

የሥልጠናውን ውጤት ለመዳሰስ እንደተሞከረው የተተኪ ሰባክያን ሥልጠና የወሰዱት ሰባክያን የአካባቢያቸውን ሕዝብ ከባዕድ አምልኮ በመመለስ፣ አስተምሮ በማስጠመቅ፣ አብያተ ክርስቲያናት በመትከልና የሰንበት ትምህርት ቤቶችን በማደራጀት እና በማቋቅም ስብከተ ወንጌልን በማስፋፋት ዓይነተኛ ሚና እየተጫወቱ ነው፡፡

በመጠኑም ቢሆን ይህ ውጤት የተገኘው ለሥራው የየአህጉረ ስብከቱ ሊቃነ ጳጳሳት ድጋፍ፣ ከአጥቢያ ጀምሮ ሥልጠናውን ለመውሰድ የሚመጡትን ሠልጣኞች ከሚገኙበት ገጠራማና   ጠረፋማ ስብከተ ወንጌል ካልተዳረሰባቸው ወረዳዎች በመመልመል የየወረዳው ቤተ ክህነት ሓላፊዎች ቀናና የጋራ ትብብር ስለታከለበት ነው፡፡ ይህ ታላቅ ሥራ የቤተ ክርስቲያን ዋነኛ ተልእኮ የሆነውን የስብከተ ወንጌልን አገልግሎት የሚያስፋፋ በመሆኑ በየአካባቢው የሚሠሩትን መልካም ሥራዎች ብቻ በየራሳቸው እያዩ ከማመስገን ባሻገር አገልግሎቱ የሚስፋፋበትንና የሚጠነክርበትን ሥራ ማመቻቸት እንደሚያስፈልግ መጠቆም እንወዳለን፡፡

በመላው ሀገሪቱ የሚገኙ የተለያዩ ቋንቋ ተናጋሪ የኅብረተሰብ ክፍሎች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በመናፈቅ እየተጠባበቁ እንደሚገኙ ይታወቃል፡፡ እነዚህ ወገኖች ፈጽሞ በመናፍቃኑ ትምህርት ተጠራርገው ከመወሰዳቸው በፊት በቋንቋቸው በማስተማርም ሆነ በቋንቋቸው የሚያስተምሩ ሰዎችን ከየአካባቢያቸው በማሠልጠን ወንጌልን እንዲያስተምሯቸው ማድረግ ጊዜ የማይሰጠው ተግባር መሆኑንም መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡

እነዚህን ወገኖች ወደተፈለገው የአገልግሎት ደረጃ ለማድረስ በቤተ ክርስቲያን የሚሰጡ ሥልጠናዎች እነሱን መሠረት ያደረጉ እንዲሆኑ ሥርዓት መዘርጋት ያስፈልጋል፡፡ እዚህ ላይ የአመላመል ሒደቱ፣ የትምህርት አሰጣጡ፣ የትምህርት መርጃ መሣሪያ አቅርቦቱ፣ ሥልጠናው የሚሰጥበት ማዕከላዊ ቦታ በዋናነት ሊታሰብበት የሚገባው ቁም ነገር መሆኑን መገንዘብ ያሻል፡፡ ከዚህ በተጨማሪም ወደካህናት ማሠልጠኛዎች፣ የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ፣ የቅዱስ ጳውሎስ መንፈሳዊ ት/ቤት፣ የመቀሌ ከሣቴ ብርሃን መንፈሳዊ ኮሌጅ ከሚገቡት ተማሪዎች መካከል በልዩ ልዩ ቋንቋዎች ሊያስተምሩ ለሚችሉት እና በርቀት ለሚገኙት አካባቢዎች የተለየ ትኩረትና ቦታ መስጠት ያስፈልጋል፡፡ እንዲሁም የሥልጠናና የትምህርት ሒደቱን የሚከታተል የትምህርት ክፍል /ዲ¬ርትመንት/ ማቋቋም ይቻላል፡፡

እነዚህን ደቀ መዛሙርት የቤተ ክርስቲያኒቱን ሐዋርያዊ ሥራ ለመሥራት በሚችሉበት መንገድ አሠልጥኖ ማሠማራቱ በሀገሪቱ የሚገኙትን ልዩ ልዩ ሕዝቦች በቀላሉ ለማስተማርና ከቤተ ክርስቲያኒቱ ጋር ያላቸውን የእናትነትና የልጅነት አንድነት ለማጠናከር ይረዳል፡፡ በየቦታው የሚደረገውን የትርጉምና የድርሰት ሥራ፤ በልዩ ልዩ ቋንቋዎች የሚሰጠውን   ሥልጠናና ትምህርትም ሥርዓት በማስያዝ ረገድ ጉልህ አስተዋጽኦ ያደርጋሉ፡፡ ይህ ከሆነ ዛሬ በደስታና ለቤተ ክርስቲያን በመቅናት የተጀመረው በልዩ ልዩ ቋንቋዎች የማስተማር፣ የመዘመር፣ የማሠልጠን፣ የተለያዩ ጽሑፎችን የመድረስና የመተርጐም ሥራ ሠላሳ፣ ስድሳ፣ መቶ ፍሬ ሊያፈራ በሚችልበት መንገድ ልንጠቀምበት እንችላለን፡፡

ይህ ካልሆነ ግን ዛሬ የቤተ ክርስቲያኒቱን እውነተኛና ቀጥተኛ ትምህርት በመናፈቅ    የሚጠብቁንን ሕዝቦች በኃጢአትና በክህደት ተጠልፈው በዲያብሎስ እጅ ወድቀው በሥጋም በነፍስም በመጐዳታቸው ምክንያት በደማቸው እንዳንጠየቅ እንሠጋለን፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

የመከሩ መሰብሰቢያ ጊዜው አሁን ነው

ለሁሉም ጊዜ አለው እንዳለ ጠቢቡ የሚሠራበትም ሆነ መሥራት የሚቻልበት ጊዜ አለው፡፡ ነገሮች ሁሉ የሚከናወኑበት፣ ቀና የሚሆኑበት፣ የሰው ልቡና ለበጎ ነገር የሚነሣሣበት ያለሙት የሚሠምርበት የዘሩት፣ የተከሉት ሁሉ የሚያፈሩበትና የሚጸድቅበት ጊዜ አለ፡፡
ያለንበትን ዘመን ስንቃኘው የመጨረሻው ዘመን ዋዜማ ምልክቶች የሚታዩበት ፍቅር ከሰዎች መካከል የቀዘቀዘበት አስጨናቂ ዘመን ቢሆንም ሕዝቡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን የሚፈልግበት፣ ስብከተ ወንጌል የተጠማበት፣ ገዳማትን ለመርዳት የተፋጠነበት፣ የፈረሱ አብያተ ክርስቲያናትን የሚጠግንበት፣ የተዘጉት አብያተ ክርስቲያናትን የሚያስከፍትበት እንዲሁም ጉባኤያትን እያዘጋጀ መምህራንን የሚጋብዝበት፣ በኅብረት ቤተክርስቲያንን ለማገልግል የሚዘምትበት፣ ከአካባቢው ሕዝብ ሌላ ዐይቷቸው የማያውቃቸውን ጥንታውያን ገዳማትና አድባራትን ሳይቀር ቆላ ደጋ ወጥቶ ወርዶ የሚሳለምበት፤ ከዘፈን መዝሙርን፣ ከዳንስ ማኅሌትን፣ ከዘልማድ ጋብቻ ተክሊልን፣ የመረጠበት ቅዱሳት መጽሐፍትን ከምግቡ ቆጠቦ የሚገዛበት ጊዜ ነው ማለት ይቻላል፡፡

አሁን ያለንበት ዘመን ምንም እንኳን የኢ-አማንያንና የመናፍቃን ሴራና ዘመቻ ያየለበት ተልእኮአቸውና ተንኮላቸው የረቀቀበትና በቤተክርስቲያን መስለው ገብተው የሚፈነጩበት እንዲሁም ዲያብሎስ የሚውጠውን ፈልጎ አፉን ከፍቶ እንደ ቀትር እባብ የሚራወጥበት ጊዜ ቢሆንም፤ ኃጢአት በበዛበት የእግዚአብሔር ጸጋ ትበዛለች ነውና ሠራተኛው ያለችውን ጥቂት ዕረፍቱን ለጉባኤ፣ የኮሌጅ ተማሪው እንደ ዕንቁ የተወደደች ጊዜውን ለወንጌል፣ ነጋዴውና ባለሥልጣኑ በገንዘብና በብዙ ሥራ የምትተመን ጊዜውን ለቤተክርስቲያን አገልግሎት የሰጠበትና ለቤተ ክርስቲያንም መልካም አጋጣሚ የተፈጠረበት  ነው፡፡

ከሀገር ውጪና በጠረፋማ የሀገሪቱ አካባቢ ኢትዮጵያውያን ባሉበት ሁሉ የቻሉ ቤተክርስቲያን እየተከሉ፣ ያልቻሉ ጉባኤ እየመሠረቱ ይህም ባይሳካ በጽዋ ማኅበር ተሰብስበው በቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ጥላ ሥር ተጠልለው የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ለማበርከትም ደፋ ቀና የሚሉበትም ጊዜ ነው፡፡

አባቶች ከልጆች ጋር ለመሥራት የተነሡበት፣ አህጉረ ስብከት ካህናትን ለማሠልጠንና ሕዝቡን በጉባኤ ለማስተማር የተጉበት፤ በምዕራብ በምሥራቅና በደቡብ የሀገሪቱ ክፍል ከግራኝ ወረራ በኋላ ተረሠቶ የነበረው ሥርዓተ ገዳም በትጉኃን ጳጳሳት ጥረትና በቅዱስ ሲኖዶስ ድጋፍ መስፋፋት የጀመረበት ጊዜም ነው፡፡

የምእመኑ ወደ ቤተክርስቲያን መምጣት መልካም አጋጣሚ ስለፈጠረና ጥቂትም ስለሠራን ነው በርቀት ሆነው ታሪኳንና ቀጥተኝነቷን በዝና ብቻ የሚያውቋትና ወደ እርሷም ለመመለስ ይናፍቋት የነበሩት ወገኖቻችን ወደዚህች ቅድስትና ንጽሕት ወደ ሆነች ቤተክርስቲያን እየተመለሱ በሥርዓቷም ለመገልገልና ለማገልገል እየተፋጠኑ የሚታዩት፡፡

«በአዝመራ ጊዜ ጐበዝ ገበሬ ምርቱን መሰብሰብ ካልቻለ ዝንጀሮ ይጫወትበታል» እንደሚባለው፤ እኛም ቅድስት ቤተክርስቲያንን በመናፈቅና በመፈልግ እየመጡ ያሉትን ወገኖችና ለአገልግሎት የተነሡትን ምእመናን በአግባቡ ካልያዝን የቤተክርስቲያንን ሥርዓትና ሕግን ለማፍለስ የተሰለፉ፤ ገዳማትና አድባራትን ጠፍ ለማድረግ ያሰፈሰፉ፤ የቤተክርስቲያንን ይዞታ ለመንጠቅ የዘመቱ፤ በቤተክርስቲያን ውስጥ ሆነው ቤተክርስቲያናችንን በኑፋቄ መርዝ ለመበከል የታጠቁ፣ ቅርስዋንና ንዋየ ቅድሳቷን በመዝረፍ ለመክበር የቋመጡ የውስጥ አርበኞች ወደ ቤተክርስቲያን እየመጡ ያሉትንና ለአገልግሎት የሚፋጠኑትን ማሰናከላቸው አይቀሬ ነው፡፡

የሕዝቡ ወደ ቤተክርስቲያን መምጣት በራሱ አስደሳችና መልካም አጋጣሚ ቢሆንም ካልሠራንበት፤ አጋጣሚው ብቻውን በጐ ቢሆን ውጤት አያመጣም፡፡ በጐ አጋጣሚዎችን አግኝተው፤  በአጋጣሚዎቹ ተጠቅመው ሳይሠሩ ያለፉ አሉና፡፡ በዘመነ ሐዋርያት ከጌታችን ደቀ መዛሙርት ገጽ በገጽ መማር እየቻሉ  አጋጣሚውን ያልተጠቀሙ ነበሩ፡፡

በዚህ ዘመንም ቅድስት ንጽሕት የሆነችውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ወድደውና ፈቅደው የሚመጡ ወገኖቻችን ተገቢውን የቤተክርስቲያን ትምህርት ተጠንቅቀን ካላስተማርን፣ ገዳማትና አድባራትን ለመርዳት ሲነሡ ተቀናጅተው ውጤት የሚያመጡበትን መንገድ ካልመራናቸው፣ የተዘጉትን በሚያስከፍቱበት ጊዜ በቂ አገልጋይ ካላሠማራንላቸው፤ ጉባኤያትን እያዘጋጁ የመምህራን ያለህ ሲሉ ቦታና ሰው ሳንመርጥ በዕለት ድካምና በሰበብ አስባቡ ሳናመካኝ ካልተገኘንላቸው ተሰባስበው ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ሲነሡ ከመንቀፍ ይልቅ በቤተ ክርስቲያን ደንብና ሥርዓት የሚሠማሩበትን ካልቀየስንላቸው፣ ገዳማትና አድባራትን ለመሳለም በሚዘጋጁበት ጊዜ ተገቢውን አቀባበልና ትምህርት እየሰጠን ከቅዱሱ ቦታ በረከት የሚያገኙበትን ሁኔታ ካላመቻቸንላቸው፣ ከዘፈን መዝሙር መርጠው ሲመጡ ትክክለኛውን ያሬዳዊ መዝሙር ካላቀረብንላቸው፣ ከዘልማድ ጋብቻ ተክሊልን መርጠው ሲመጡ ስለትዳር የሚያስተምሩትንና የሚመክሩትን መምህራን በትክክል ካላገኙ፣ ከዕለት ጉርሱ ከዓመት ልብሱ ቆጥቦ ቅዱሳት መጻሕፍትን ገዝቶ ለማንበብ ሲነሣ፣ መንፈሳዊና ማኅበራዊ ሕይወቱን የሚያንጹለትና የሚገነቡለትን ቅዱሳት መጻሕፍት ካላዘጋጀንለት፣ ጋዜጠኛው አርቲስቱ፣ ነጋዴው ሠራተኛው ተማሪው ወታደሩ፣ ¬ፖለቲከኛው ሹፊሩ ወደ ቤተክርስቲያን ሲመጡ ችግሩን ሊፈቱለት አስቀደመው የተጠሩ ሊቃውንት፣ መምህራን፣ መዘምራን፣ አስተናባሪዎች፣ የሰንበት ትምህርት ቤት አመራሮች፣ ደክመውና ሰልችተው በሥጋዋና ግላዊ ምክንያቶች ተጠላልፈው፤ እርስ በእርሳቸው እየተነቃቀፉ ተቃቅረው እንዳይገኙና ዘመኑን ባርኮና ምቹ አድርጎ የሰጠ እግዚአብሔር እንዳያዝን መንቃት ያስፈልጋል፡፡

ትናንት ሲያስተምሩ፣ ሲዘመሩ፣ ከአጥቢያዎቻቸው ውጪ በየገጠሩ ሰንበት ትምህርት ቤት ሲመሠርቱ፣ በየአጥቢያ ቤተክርስቲያናት ያለ እንቅልፍ ሲያገለግሉ የነበሩ፤ በየገጠሩ ገብተው ሕዝቡን ለቤተክርስቲያን አገልግሎት ሲቀሰቅሱ፣ የነበሩና ያልተጠመቁትን ለማስጠመቅ የተጉት፣ የሚበሉትና የሚለብሱት፣ የሚያርፉበትና የሚተኙበት ጊዜ አጥተው ለቤተክርስቲያን ሐዋርያዊ ተልእኮ ተሰልፈው የነበሩ ሁሉ፤ ሩጫቸውን የፈጸሙ እንዳይመስላቸው ያልተወረሰ ብዙ መሬት ገና መቅረቱን የሚረዱበት ጊዜ አሁን ነው፡፡ ኢያ. 13.1፡፡

ከኋላ የነበሩት ወደፊት ሲመጡ ከፊት የነበሩት ወደ ኋላ እንዳይሄዱ፣ በጨለማ የነበሩት ወደ ብርሃን ሲመጡ፣ በብርሃን የነበሩት ወደ ጨለማ እንዳይመለሱ፣ ጥቂቶች እያሉ ብዙ የሠሩ እግዚአብሔር ሕዝቡን ሲያበዛላቸው እንዳይደክሙና እንዳይዝሉ የማሰቢያና ብዙ የመሥሪያ አጋጣሚው አሁን ነው፡፡

በዚህ የፍጻሜ ዘመን መጨረሻ ወደ ቤተክርስቲያን እየመጣ ያለውን ሕዝብና ለአገልግሎት እየተጋ ያለውን ምእመን እንደ አመጣጡና እንድ እድሜ ገደቡ ትምህርት በመስጠት በእምነት ልናጸናው፣ በአገልግሎት ልናበረታው ያስፈልጋል፡፡ ለዚህም መምህራን፣ ካህናት እና የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች የየራሳችን ድርሻ አለን፡፡

በአጠቃላይ ወደ ቅድስት ቤተክርስቲያን የመጡና እየመጡ ያሉትን ወገኖቻችንን የምንቀበልበት ጊዜ አሁን ነው፡፡ ጀንበር ሳለ ለሚሮጥ፣ የጋለውን ለሚቀጠቅጥ፣ ቀን ሳለ የብርሃን ሥራ ለሚሠራ፣ ሠላሳ፣ ስድሳና መቶ የሚያፈራበት ዘመን ዛሬ ነው፡፡ እናም እግዚአብሔርን የተጠሙ ነፍሳትን የምናድንበትና በቤተክርስቲያን ሥርዓት እንዲኖሩ የምናደርግበት የመከሩ መሰብሰቢያ ጊዜው አሁን ነውና እንጠቀምበት፡፡   

ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 17ኛ ዓመት ቁጥር 4/ቅጽ 17 ቁጥር 189 ከኅዳር 1-15 2002 ዓ.ም

የእመቤታችንን ስደት ስናስብ የተሰደዱትን በማሰብ ይሁን

ለክርስቲያን ዓመታት፣ ወራትና ቀናት በሙሉ የተቀደሱ ናቸው፡፡ እያንዳንዱ ቀን በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በቅዱሳን መልካም ምግባር ተቀድሷል፡፡ ለዚህም ነው ቤተክርስቲያን በአንድ ዓመት ውስጥ የሚገኙ 365 ቀናት በቅዱሳን ስም ተሰይመው የሚዘከሩት፡፡
ምእመናን ቤተክርስቲያናቸው በሠራችላቸው ሥርዓት መሠረት በፍቅር በደስታ ከሚዘከሩት ዕለታት ደግሞ ከመስከረም 26 እስከ ኅዳር 6 ቀን የሚዘከረው የእመቤታትን ቅድስት ድንግል ማርያምና የልጇ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ስደት አንዱ ነው፡፡

የእመቤታችን ስደት የመጀመሪያው የአዲስ ኪዳን ስደት ነው፡፡ ወንጌላዊው ማቴዎስ እንደሚለው፤ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተወለደበት ጊዜ ሰብአ ሰገል የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ ወዴት ነው? እያሉ በመጠየቅ ወደ ኢየሩሳሌም ሔደው ነበር፡፡ በዚያ ዘመን ምድረ እስራኤልን ይገዛ የነበረው ሄሮድስ የአይሁድ ንጉሥ ወዴት አለ የሚለውን ቃል ሰምቶ፤ ከኔ ሌላ ንጉሥ ማን አለ? በማለት በአማካሪዎቹ ግፊት ከአንድ ዓመት ተኩል እስከ ሁለት ዓመት የሚሆን ዕድሜ ያላቸውን ሕፃናት እንዲገደሉ አደረገ፡፡
 
በዚያን ጊዜ «እነሆ የጌታ መልአክ በሕልም ለዮሴፍ ታይቶ ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይፈልገዋልና ተነሣ፤ እናቱንና ሕፃኑን ይዘህ ወደ ግብጽ ሽሽ፤ እስክነግርህም ድረስ በዚያ ተቀመጥ አለው»፤ እርሱም ተነሥቶ ሕፃኑንና እናቱን በሌሊት ያዘና ከጌታ ዘንድ በነቢይ ልጄን ከግብጽ ጠራሁት የተባለው እንዲፈጸም ወደ ግብጽ ሔደ፡፡ ሄሮድስ እስኪሞት ድረስም በዚያ ኖረ፡፡ /ማቴ 2-13-15/ ተብሎ እንደተጻፈ ሁሉ፤ እናታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ይዛ፣ ዮሴፍና ሰሎሜን አስከትላ ሦስት ዓመት ከስድስት ወር በግብጽ አውራጃዎች ስደተኛ በመሆን ኖራለች፡፡

ነቢያት ስለጌታ ትንቢት በመናገራቸው፣ እመቤታችን የጌታ እናት በመሆኗ፣ ሐዋርያት ስለጌታ በማስተማራቸው ተሰደዋል፡፡

የጌታ አገልጋይም እናትም የሆነችው የእመቤታችን ስደት ግን. . . ከሁሉ የሚለይ ነው፡፡ የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስና የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ስደት ልዩ የሚያደርገው: –

1.    ሕግን በመተላፉ ከገነት ተሰዶ የነበረውን አዳምን ለመካስ የተደረገ በመሆኑ
2.    በግብጽ ነግሦ የነበረውን አምልኮት ጣኦት ለማሳደድ የተደረገ ስለሆነ የጌታችንና የእናቱ ስደት ልዩ ነው፡፡

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ከናዝሬት ወደ ግብጽ ስትሰደድ የቀን ሐሩር የሌሊት ቁር አግኝቷታል፡፡ እሾህ እየወጋት እንቀፋት እየመታት ተጉዛለች /ተሰዳለች/፤ በስደቷም ረሃብና ጥም፣ ችግርና መከራ ደርሶባታል፡፡ በበረሃው ወንበዴዎችን ባየች ጊዜም በስደት ከሄሮድስ ጭካኔ ከሀገር ያወጣሁትን ልጄን ይገድልብኛል ብላ መሪር እንባ አልቅሳለች፡፡

በስደቷ ወቅት በደረሰባት ረሐብና ጥም የተነሣ ወደ መንደር ገብታ ብትለምን በችግር ምክንያት የሰው ፊት ማየት ከእሳት የበለጠ ወላፈኑ ስለሚያቃጥል የሰው ፊት ገርፏታል፡፡ የትእማን ቤተሰቦች ዘብተውባታል፡፡

«ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ዓለም የመጣው ሸክማችንን ሊሸከም ነውና ውኃውን ለፍጥረታት የሚሰጥ እርሱ እየጠማው፤ እንስሳትን የሚመግብ እየራበው ምድርን በልምላሜ የሚያለብስ፣ ተራቁቶ የኛን ከገነት መሰደድ የመጣብንን ዕዳ ሊክስልን ከእናቱ ጋር ተሰደደ፤ ድንግል ማርያምም የአምላክ እናት ሆና መከራን ቀመሰች፡፡ ጌታን አዝላ በረሐብ አለንጋ ተገረፈች፡፡

በመጨረሻ ግን ያ ሁሉ የመከራና የስቃይ ስደት ሲያበቃ «አንቺ ሱላማጢስ ሆይ ተመለሽ» ሲል በመኃልየ ማኀልይ ዘሰሎሞን ተነግሮ የነበረው ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ከዚያ ሁሉ መከራና ስደት ልጇን ይዛ ወደ ናዝሬት ተመልሳለች፡፡

የእመቤታችንን ስደት ስናስብ «ሲነቅፏችሁና ሲያሳድዷችሁ በእኔም ምክንያት ክፉውን ሁሉ በውሸት ሲነግሩባችሁ ብፁዓን ናችሁ፡፡ ዋጋችሁ በሰማያት ታላቅ ነውና ደስ ይበላችሁ ሐሴትም አድርጉ፡፡ ከእናንተም በፊት የነበሩትን ነብያት እንዲሁ አሳድደዋቸዋልና» /ማቴ 5-11/ የሚለውን የስደት ዋጋ ጭምር እያሰብን መሆን ይገባል፡፡

ይህንንም የእመቤታችንን ስደት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ከመስከረም 26 እስከ ኅዳር 6 ድረስ በማኅሌትና በመዝሙር ትዘክራለች፡፡ ካህናቱም በዕለተ ሰንበት ከምሽት ጀምረው በማኅሌትና በመዝሙር ምስለ ፍቁር ወልዳን /የልጇ እና የእርሷ/ ሥዕል ይዘው ቤተክርስቲያኑን ይዞራሉ፡፡

ይህም የእመቤታችንን ስደት ለማጠየቅ ነው፡፡ ሌሎችም እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የደረሰባቸውን መከራ ለማስታወስ የፍቃድ ጾም ይጾማሉ፡፡

እኛ ክርስቲያኖች በቅድስት ቤተክርስቲያን ተገኝተን በመንፈስ የሩቁን አቅርበን የእመቤታችንን ስደት በእምነት እያየን በማኅሌተ ጽጌ ድርሰታችን በዜማ «መልካሟ ርግብ ማርያም ሆይ ንጹሕ፣ ፀአዳ ፣ቀይህና ብሩህ የሚሆን ልጅሽን ታቅፈሽ ርኅሩኅ የሆነ ቅዱስ ሚካኤልና ቅዱስ ገብርኤልን አስከትለሽ ከሐዘናችንና ከችግራችን ታረጋጊን ዘንድ ፈጥነሽ ድረሽልን» ልንላት ያስፈልጋል፡፡

በቅዳሴያችንም «ድንግል ሆይ ርጉም በሆነ ሄሮድስ ዘመን ከልጅሽ ጋር ከሀገር ሀገር ስትሸሺ ከአንቺ ጋር መሰደዱን አሳስቢ፤ ድንግል ሆይ ከዓይንሸ የፈሰሰውንና በተወደደ ልጅሽ ፊት የወረደውን መሪር እንባ አሳስቢ፡፡ ድንግል ሆይ ረሐቡንና ጥሙን፣ ችግሩንና ሐዘኑን፣ ከእርሱ ጋር የደረሰብሽንም ጭንቅ ሁሉ አሳስቢ እንላለን፡፡

በዚህ መታሰቢያ ወቅት እመቤታችን ከልጇ ጋር መሰደዷን ማስታወስ ብቻ ሳይሆን እኛም በመንፈስ አብረን ከእመቤታችን ጋር መሰደድ ይገባናል፡፡ የመሰደድ ዋጋው ብፅእና ነውና፡፡ ነገር ግን ወዴት እንደምንሰደድ ማወቅ ያስፈልጋል፡፡ ዛሬ ብዙዎች ከጽድቅ ወደ ኃጢአት፣ ከብርሃን ወደ ጨለማ፣ ከእውነት ወደ ሐሰት፣ ከፍቅር ወደ ጸብ ተሰደዋል፡፡ የኛ ስደት ግን መሆን ያለበት ከኃጢአት ወደ ጽድቅ፣ ከጨለማ ወደ ብርሃን፣ ከሞተ ወደ ሕይወት፣ ከሐሰት ወደ እውነት፣ ከጥላቻና ክስ ወደ ፍቅርና መተሳሰብ፣ ከክህደት ወደ እምነት መሰደድ ያስፈልጋል፡፡ ከማሳደድ ይልቅ መሰደድ ይሻላልና፡፡

ዛሬ ብዙዎች ለሥጋ ተድላ በኃጢአት እየተሰደዱ ነው፡፡ እነዚህን ወገኖቻችን ከኃጢአት ስደት እንዲመለሱ በማስተ ማር፣ በመምከርና በመገሰጽ ጭምር ልንመልሳቸው ያስፈለጋል፡፡ መምህራንም ለኃጢአት የተሰደዱትን ወገኖች የንስሐ ፍሬ እንዲያፈሩ ሕይወት የሆነውን ወንጌል ሊያስተምሯቸው ይገባል፡፡

በተለያዩ የዓለም ክፍላት በችግርና በተለያዩ ምክንያቶች ከሀገር የተሰደዱትን በጸሎት ማሰብ በሚያስፈልጉ ድጋፎች ሁሉ መርዳት የክርስቲያን የዘወትር ምግባሩ ቢሆንም በተለይ በዚህ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ስደት መታሰቢያ ጊዜ በልዩ ሁኔታ በችግር የተሰደዱትን ልናስባቸው ያስፈልጋል፡፡

የእመቤታችንን ስደት ስናስብ በኃጢአትና በመከራ የተሰደዱትን በማሰብ ይሁን፡፡

 
ወስብሐት ለእግዚአብሔ

ማኅበረ ቅዱሳን ማን ነው? ክፍል ሦስት

በልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት

ይህ ዘርፍ ማኅበረ ቅዱሳን ከሚሰጣቸው መንፈሳዊ አገልግሎቶች በተጨማሪ የተለያዩ ማኅበራዊ እና ኢኮኖ ሚያዊ ሥራዎች የሚሠራበት ዘርፍ ነው፡፡ በዚህም ለቅዱሳት መካናት፣ ለአብነት ትምህርት ቤቶች መምህራን እና ተማሪዎች፣ ለምእመናን ብሎም ለጠቅላላው ኅብረተሰብ አቅም በፈቀደ መጠን ዘላቂ የልማት ሥራዎችን በማከናወን ረገድ በገንዘብ፣ በዓይነት፣ በዕውቀት እንዲሁም በጉልበት እገዛ እያደረገ ይገኛል፡፡ ከእነዚህም መካከል ለአብነት ትምህርት ቤቶች መምህራን እና ተማሪዎች ድጎማ፣ ለገዳማት፣ አድባራት እና የገጠር አብያተ ክርስቲያናት ጊዜያዊ ርዳታ፣ የዘላቂ ገቢ ቋሚ የልማት ፕሮጀክት ቀረፃና ትግበራ፣ ጉዳት ለደረሰባቸው አብያተ ክርስቲያናት የአስቸኳይ ጊዜ ድጋፍ የማድረግ፣ ኤች.አይ.ቪ/ ኤድስን የመከላከልና የመቆጣጠር ሥራዎችን ያከናውናል፡፡ በቀጣይም የተለያዩ ማኅበራዊ ችግሮችን በመፍታት ዙርያ ለመሥራት በዝግጅት ላይ ይገኛል፡፡ እንዲሁም በትምህርት መስክ በአዲስ አበባ ሦስት ቦታዎች ላይ፣ በአዋሳ፣ በደብረ ብርሃንና፣ በባሕርዳር፣ ሃገረ ማርያም ወዘተ የራሱን መደበኛ ት/ቤት በመክፈት ሕፃናት በመንፈሳዊና በዘመናዊ ዕውቀታቸው ዳብረው እንዲወጡ እያደረገ ይገኛል፡፡

ሀ. አብነት ት/ቤቶችን ከመደገፍ አንጻር

አብነት ትምህርት ቤት የቤተ ክርስቲያን ትምህርት፣ ሥርዓት፣ ታሪክና ትውፊት ከትውልድ ወደ ትውልድ ማስተላለፍ የሚቻልበት ብቸኛ መድረክ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓቷን፣ ትውፊቷንና ትምህርቷን በየዘመኑ የሚቀበል ትውልድ እንዳታጣ የአብነት ት/ቤቶች ከፍተኛ አስተዋጽኦ አላቸው፡፡ ነገር ግን በአሁኑ ጊዜ የአብነት ት/ቤቶች በተለያየ የተፈጥሮ እና ሰው ሠራሽ ችግር ምክንያት የከፋ አደጋ ላይ ይገኛሉ፡፡ በተለይም ጥንታውያን የሆኑት የአብነት ት/ቤቶች እና ሊቃውንቶቻቸው ቀደም ሲል የነበረው የመሬት ባለቤትነታቸውን በማጣታቸው እና የአካባቢው ምእመንም ቀደም ሲል ያደርግላቸው የነበረውን ድጋፍ በኑሮው ጫና ምክንያት በማቆሙ፣ መምህራኑ ወንበራቸውን አጥፈው ለመሰደድ፤ ተማሪዎቻቸውም ለመበታተን ተዳርገዋል፡፡ የነዚህ ለመላው አብያተ ክርስቲያናት የአገልጋይ ምንጭ የሆኑ የአብነት ትምህርት ቤቶች ችግር ምክንያት፤ በደቡብ በምሥራቅ እና በምዕራቡ ላሉት አብያተ ክርስቲያናት የካህናት እጦት መንስኤ በመሆን አብያተ ክርስቲያናቱ እንዲዘጉ አድርጓል፡፡ ማኅበሩ ይህንን ችግር በመረዳት፤ የአብነት ት/ቤቶች መምህራንን እና ተማሪዎችን በመደጎም፣ ጥንታውያን የሆኑት የቀድሞ ይዞታቸው ተጠብቆ ለትውልድ እንዲተላለፍ ለማድረግ እና በደቡብ፣ በምሥራቅ እና በምዕ ራቡ የሀገሪቱ ክፍል ደግሞ የአካባቢውን ልጆች በማስተማር አገልጋይ ካህናትን በማፍራት የበኩሉን ጥረት እያደረገ ይገኛል፡፡ ድጎማው በሀገር ውስጥ እና በውጭ ሀገር የሚገኙ በጎ አድራጊዎችን በማስተባበር በወር ከአንድ መቶ እስከ ሦስት መቶ ሃምሳ ብር፣ ለስልሳ ሦስት መምህራን ድጎማ እንዲሁም አራት መቶ ሃያ ስምንት ለሚሆኑ ተማሪዎች ደግሞ በወር በሁለት መንገድ የሚፈጸም ነው፡፡ የመጀመሪያው ለመምህራኑና ለተማሪዎቹ የምግብ፣ የአልባሳት፣ የመጻሕፍትና ከሠላሳ እስከ መቶ ሃያ ብር ይደጉማል፡፡ በዚህም ለአብነት ደመወዝ /ለመምህራኑ/ ድጎማ ሲሆን፤ ሁለተኛው የአብነት ት/ቤቶች ራሳቸውን እንዲችሉ ዘላቂ የልማት ፕሮጀክቶችን መቅረፅና ተግባራዊ ማድረግና ለመምህራን እና ተማሪዎች ድጎማ ያደርጋል፡፡ በዓመት እስከ ዘጠኝ መቶ ሺሕ ብር፣ እንዲሁም የገንዘብ ድጎማ ለማይደረግላቸው አንዳንድ የአብነት ት/ቤቶች በጊዜያዊነት ለልብስ፣ ለምግብ፣ ለመጻሕፍት እና ሌሎች ወጪዎች እስከ ስልሳ ሺሕ ብር በዓመት ያወጣል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በተመረጡ የአብ ነት ት/ቤቶች ተማሪዎቹ ከአብነት ትምህርቱ ጎን ለጎን ትምህርተ ሃይማኖት፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናትና የስ ብከት ዘዴ እንዲማሩ በማድረግ ለተሻለ አገልግሎት አቅም እንዲኖራቸው በማድረግ ላይ ይገኛል፡፡

ለ. ገዳማትና አድባራትን ከመደገፍ አንጻር

ማኅበሩ ከአብነት ት/ቤቶች በተጨማሪ ችግር ላለባቸው አድባራትና ገዳማት ጊዜያዊ ርዳታ በማድረግ እና ዘላቂ መፍትሔዎችን በማመቻቸት የገዳማቱንና አድባራቱን ችግር በመጠኑም ቢሆን እየፈታ ይገኛል፡፡ በጊዜያዊ ርዳታ የተለያዩ የመባዕ /ጧፍ፣ ነዕጣን፣ ዘቢብና ሻማ/፣ የተለያዩ ንዋየ ቅድሳት /ልብሰ ተክህኖ፣ መጎናጸፊያ ወዘተ/፣ የዘወትር ልብስ፣ የምግብ እህልና ሌሎችን ርዳታዎችን እያደረገ ይገኛል፡፡ በዓመት በአማካይ ለሠላሳ ቅዱሳት መካናት የልብሰ ተክህኖ ድጋፍ፣ ለሁለት መቶ ቅዱሳት መካናት የመባዕ፣  እንዲሁም የምግብ፣ የአልባሳት እና ለሌሎች ድጋፎች በዓመት እስከ ዘጠና ሺሕ ብር ወጪ ያደርግላቸውል፡፡ በ1995 ዓ.ም በሁለት የአብነት መምህራን የተጀ መረው ድጎማ ዛሬ ቁጥሩን ከፍ በማድረግ ስልሳ ለሚሆኑ ለተመረጡ አብነት ት/ቤቶች ድጎማ ያደርጋል።

በሌላ በኩል ደግሞ ገዳማትና አድባራት ያሉባቸውን ችግሮች በዘላቂነት ለመፍታት ማኅበሩ የተለያዩ የልማትና ማኅበራዊ ፕሮጀክቶችን አጥንቶ በመተግበር ላይ ይገኛል፡፡ ቅዱሳት መካናቱ ያላቸውን ነባራዊ ሁኔታ፣ ያላቸውን የተፈጥሮ ሀብት እና የሰው ኃይል መሠረት በማድረግ የአነስተኛ መስኖና አትክልት ልማት፣ የወተት ላም ርባታ፣ ዘመናዊ ንብ ርባታ፣ የከብት ማድለብ፣ ወፍጮ ቤት፣ ሽመና፣ የጥበበ ዕድ ፕሮጀክቶች የሚከራይ ቤት ግንባታ፣ የአብነት ተማሪዎች መኖሪያ ቤት እና የመሳሰሉትን በመሥራት ላይ ይገኛል፡፡ በዚህም ቅዱሳት መካናቱን ወደ ቀደመው የልማት አውታርነታቸው ለመመለስ፣ የአካባቢውን ኅብረተሰብ የምርቶቻቸው ተጠቃሚ እንዲሆኑ ከማ ድረግ በተጨማሪ ለአካባቢው አርሶ አደሮችም ሠርቶ ማሳያ እንዲሆኑ አስችሏል፡፡

እስከ 2000 ዓ.ም መጨረሻ ድረስ በተለያዩ አህጉረ ስብከቶች ከአንድ መቶ ሃያ በላይ የተጠኑ የልማት ፕሮጀክቶች ያሉ ሲሆን ከእነዚህ ፕሮጀክቶች መካከል እስከ 2000 ዓ.ም መጨረሻ ድረስ በጠቅላላው ከሁለት ሚሊዮን ብር በላይ የፈጁ ሃያ ሦስት የልማት ፕሮጀክቶች ተጠናቀው ገዳማቱ ተረክበዋቸው ሥራ ጀምረዋል፡፡ በ2001 ዓ.ም ከአንድ ሚሊዮን ብር በላይ የሚፈጁ ሃያ ስድስት ከአለፈው የቀጠሉ ፕሮጀክቶች እና ሰባት አዳዲስ ፕሮጀክቶችን ለመተግበር ከተለያዩ የሀገር ውስጥ እና የውጭ ሀገር በጎ አድራጊዎች የገንዘብ እርዳታ ማሰባሰብ ሥራ በመሠራት ላይ ይገኛል፡፡  የእነዚህ ፕሮጀክቶች የእያንዳንዳቸው ጠቅላላ ወጪ ከ35,000 እስከ 350,000 ብር የሚደርስ ሲሆን እንደ ፕሮጀክቱ ዓይነት ሊለያይ ይችላል፡፡ በዚህም የአምስት ዓመት ጉዞ በአብነት ትምህርቱ፣ በገዳማትና አድባ ራት ድጋፍ ከሃያ ሚሊዮን ብር በላይ በዘላቂና ጊዜያዊ ፕሮጀክቶች ላይ ወጪ ተደርጓል፡፡

ሐ. ጉዳት ለደረሰባቸው የኅብረተሰብ ክፍሎች ድጋፍ ማድረግ

ማኅበሩ በተለያዩ ሰው ሠራሽም ሆኑ ተፈጥሮአዊ ምክንያቶች ችግር ከደረሰባቸው ገዳማትና አድባራት ባሻገር በችግር ውስጥ ያሉ ምእመናንንም በመታደግ እንቅስቃሴ ያደርጋል፡፡ በመስከረምና ጥቅምት 1999 ዓ.ም በአክራሪ እስልምና እንቅስቃሴ ጉዳት ለደረሰባቸው የጅማ፣ ኢሉባቦር እና የምዕራብ ወለጋ አህጉረ ስብከት ምእመናንን እና አባላትን በማስተባበር የመልሶ ማቋቋም ሥራ ሠርቷል፡፡ በዚህም ለተፈናቀሉት የኅብረተሰብ ክፍሎች የምግብ ርዳታ ጤፍ፣ በቆሎና ማሽላ በጠቅላላው ለዘጠኝ መቶ ሃያ ስድስት አባወራ አምስት መቶ አሥራ አንድ ኩንታል ገዝቶ አከፋፍሏል፡፡ በኢሊባቦር ለተቃጠሉ ቤቶችም መልሶ ግንባታ ለሃምሳ አንድ አባወራ ለእያንዳንዳቸው አርባ ቆርቆሮና ሚስማር ሰጥቷል፡፡ በኢሊባቡር እና በምዕራብ ወለጋ ለተቃጠሉ ሦስት አብያተ ክርስቲያናት ማሠሪያ ሁለት መቶ ሃምሳ ቆርቆሮ፣ ሦስት መቶ ኩንታል ሲሚንቶ እና አንድ መቶ ሺሕ ብር አስረክቧል፡፡ በአካባቢው ያሉ አብያተ ክርስቲያናትንና ሰንበት ት/ቤቶችን ለማጠናከር ለአሥር አብያተ ክርስቲያናት ሙሉ አልባሳትና አንድ መቶ ዘጠና ሁለት መጽሐፍ ቅዱስ ገዝቶ ያከፋፈለ ሲሆን ለአምስት መምህራንና ለሁለት አብያተ ክርስቲያናት ካህናትና ዲያቆናት የአንድ ዓመት ደመወዝ መድቧል፡፡ የሁለት መምህራንን ቅጥርም አካሒዷል፡፡ በጅማ አካባቢ ያሉትን አብያተ ክርስ ቲያናትና ምእመናን በደረሰው ጉዳት ወላጆቻቸውን ያጡ ልጆችን ለመርዳት ሁለት የኤሌክትሪክ እና ሁለት በናፍጣ የሚሠሩ ወፍጮዎችን ገዝቶ ያስተከለ ሲሆን እንዲሁም ስድስት ክፍል ያለው መጸዳጃ ቤት በማሠራት ለገዳሙ አስረክቧል፡፡ በምዕራብ ወለጋ ሀገረ ስብከት ላሉ ሠላሳ ሁለት ካህናት ሥልጠና ሰጥቷል፡፡

በ2000 ዓ.ም ደብረ ወገግ አሰቦት ገዳም ላይ ለደረሰው የቃጠሎ አደጋ የመልሶ ማቋቋም ሥራ ተሠርቷል፡፡ ለገዳሙ መናንያንም በየወሩ ለቀለብ የሚሆን ስምንት ሺሕ ብር ድጎማ ያደርጋል፡፡ ከዚህ ሌላም በገዳሙ የበቀሉ አላስፈላጊ እፅዋትን ለማስወገጃ ከስልሳ ሺሕ ብር በላይ ወጪ ተደርጓል፡፡ በያዝነው በ2001 ዓ.ም «አንድ መጽሐፍ ይለግሱ» የተሰኘ ፕሮጀክት በመቅረጽ ከአባላትና ከምእመናን ከሶስት ሺሕ አምስት መቶ በላይ መጻሕፍትን በማሰባሰብ ለተለያዩ የአብነት ት/ቤቶችና ሰንበት ት/ቤቶች የማሠራጨት ሥራ ተሠርቷል፡፡

መ. ኤች አይ ቪ/ኤድስን የመከላከልና የመቆጣጠር ሥራ

ማኅበሩ ኤች አይ ቪ/ኤድስን በመከላከልና በመቆጣጠር ረገድም ከተለያዩ አካላት ጋር በመሆን እየሠራ ይገኛል፡፡ የተለያዩ መገናኛ ብዙኃንን በመጠቀም ለማኅበረሰቡ ግንዛቤ እያስጨበጠ ይገኛል፡፡ የቤተ ክርስቲ ያን ትምህርትን መሠረት ያደረጉ የመከላከያ እና የመቆጣጠሪያ ዘዴዎች ላይ ያተኮሩ ፕሮጀክቶችን በመቅረጽ ከስዊድን የሕፃናት አድን ድርጅት፣ ከዓለም ባንክ፣ ከአክሽን ኤይድ እና ቪ.ኤስ.ኦ. ከተባሉ ዓለም አቀፍ ግብረ ሰናይ ድርጅቶች ጋር በመተባበር የተለያዩ ሥራዎችንም ሲሠራ ቆይቷል፡፡ ከተሠሩትም ሥራዎች መካከል ተከታታይ ጽሑፎች በ«ስምዐ ጽድቅ» ጋዜጣ እና «ሐመር» መጽሔት በማውጣት፣ አርባ የሚሆኑ ፀረ ኤች.አይ.ቪ/ ኤድስ ክበባትን ማቋቋም፣ ለዘጠኝ መቶ ዘጠና ሦስት ካህናትና ካውንስለሮች ሥልጠና በመስጠት፣ ለስድስት መቶ አምስት የግቢ ጉባኤ ተማሪዎችና ሰንበት ት/ቤት ተማሪዎች የአቻ ለአቻ የምክር አገልግሎት በመስጠት፣ ውይይቶችና በሃያ አምስት አህጉረ ስብከት ላይ በኤች አይ ቪ/ኤድስ ዙሪያ የዳሰሳ ጥናቶች ማድረግ ተጠቃሾች ናቸው፡፡ በ2001 ዓ.ም ከጥቅምት ወር ጀምሮ ከብሔራዊ የኤች አይ ቪ/ ኤድስ መቆጣጠሪያና መከላከያ ጽ/ቤት በተገኘ ከአምስት መቶ ሺሕ ብር በላይ በሆነ ገንዘብ ጠበልን ከፀረ ኤች አይ ቪ መድኃኒት ጋር አስማምቶ መጠቀም ላይ ግንዛቤ የመፍጠር ሥራ እየተሠራ ይገኛል፡፡

በዚህ ዘርፍ ማኅበሩ ለቤተ ክርስቲያን፣ ለምእመናን ብሎም ለጠቅላላው ኅብረተሰብ አቅም በፈቀደ መጠን በገንዘብ፣ በዓይነት፣ በዕውቀት እንዲሁም በጉልበት እገዛ እያደረገ ይገኛል፡፡

ሠ. የሙያ አገልግሎት

የማኅበሩ አባላት በገቡት ቃል መሠረት የተለያየ ሙያ ያላቸው አባላት ማኅበሩንና ቤተ ክርስቲያንን በሙያቸው፣ በዕውቀታቸው፣ በገንዘቸው፣ በጉልበታቸው እያገለገሉ ይገኛሉ፡፡ በተለይም በምህንድስና እና ጥበበ ዕድ ክፍል ባለሙያዎች ለተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት የዲዛይን፣ የቅየሳ፣ የሱፐርቪዥን ወዘተ ሥራ በመሥራት በሚሊዮን የሚቆጠር ብር ለቤተ ክርስቲያን እያዳኑ እና የቤተ ክርስቲያን ትውፊት እንዲጠበቅ አስተዋጽኦ እያደረጉ ይገኛሉ፡፡ ለአብነት ያህል ከ1995 ዓ.ም ወዲህ ከተሠሩትና በዋነኛነት ከሚጠቀሱት ውስጥ ለስምንት የመኖሪያ ቤት ፕሮጀክቶች ዲዛይንና የዋጋ ዝርዝር፣ ለሰባ አምስት አብያተ ክርስቲያናት ሕንፃ ዲዛይን፣ ከሠላሳ በላይ ለሆኑ አብያተ ክርስቲያናት የጥገና ዲዛይን፤ እንዲሁም ከሠላሳ በላይ ለተለያዩ አዳዲስ ፕሮጀክቶች ዲዛይኖችን ሠርተው አስረክበዋል፡፡ ይህም ቤተ ክርስቲያን ልታወጣ የነበረውን ከሰባት ሚሊዮን ብር በላይ የሚሆን ገንዘብ እንዳታወጣና ወጭ እንድትቆጥብ አድርጓታል፡፡ የሕግ ባለሙያዎቹም የሕግ ምክር አገልግሎት ለሚፈልጉ የቤተ ክርስቲያን አካላት የምክር አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ፡፡ እንዲ ሁም የተለያዩ የሒሳብና የአስተዳደር ማንዋሎች ተሠርተዋል፡፡ ለቱሪዝም ቅርስ ጥበቃና ክብካቤ የሚረዳ ስትራቴጂክ ዕቅድ በማዘጋጀት ለጠቅላይ ቤተ ክህነት አስረክቧል፡፡ «ቅርስና ቱሪዝም በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን» በሚል ርዕስ ከቅርስና ቱሪዝም ጋር ግንኙነት ላላቸው ባለሙያዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና ሰጥቷል፡፡ የተለያዩ ጥናታዊ ጽሑፎች በማዘጋጀት ባለድርሻ አካላት ባሉበት አቅርቦ ውይይቶች እንዲካሔዱ አድርጓል፡፡ በማኅበራዊና ምጣኔ ሀብት ክፍል ለአብነት ትምህርት ተማሪዎችና ገዳማዊያን ያሉባቸውን የጤና ችግሮች ላይ መፍትሔና ቅድመ ትምህርት ተሰጥቷል፡፡ በተጨማሪም ከተለያዩ አብያተ ክርስቲያናት የሚመጡ የተለያዩ ፕሮጀክቶችን የመገምገምና የማበልጸግ ሥራዎች ተሠርተዋል፡፡

ማኅበሩ አገልግሎቱ እየሰፋ በመጣ ቁጥር በየቦታው በተበታተነ ሁኔታ የሚከራያቸው ቤቶች ለቢሮ አገልግ ሎት አስቸጋሪ በመሆናቸው ቀደም ሲል በጽሕፈት ቤትነት ተከራይቶ ይጠቀምበት የነበረውነ ቦታ በአባላት ልዩ መዋጮና በበጎ አድራጊዎች ርዳታ በ1.3 ሚሊዮን ብር በመግዛት የሕንፃ ግንባታው ሥራ ተጀምሯል፡፡ እስከ ሚያዝያ 2001 ዓ.ም መጨረሻም የመሠረቱንና እስከ አራተኛው ፎቅ ወለል ያለውን ሥራ አጠናቆአል፡፡

ረ. አቡነ ጎርጎርዮስ አፀደ ሕፃናትና አንደኛ ደረጃ ት/ቤት

ማኅበሩ በአሁኑ ጊዜ የቤተ ክርስቲያንን ማንነት የሚያውቁና በግብረ ገብ ትምህርት የታነፁ ሕፃናት ቁጥር  ትንሽ መሆኑን በመገንዘብ ትምህርት ቤት ከፍቷል፡፡ ትምህርት ቤቱ ሰባት ቅርንጫፎች ያሉት ሲሆን፤ ሦስቱ በአዲስ አበባ፣ አንድ በአዋሳ፣ አንድ በባሕርዳር፣ አንድ በሀገረ ማርያም እና አንድ በደብረ ብርሃን ይገኛሉ፡፡ ትምህርት ቤቱ በ2001 ዓ.ም የትምህርት ዘመን በሰባቱ ቅርንጫፎች ከአንድ ሺሕ ስድስት መቶ ተማሪዎች በላይ ተቀብሎ ከአፀደ ሕፃናት እስከ አምስተኛ ክፍል እያስተማረ ይገኛል፡፡ ትምህርት ቤቱ ከሃያ ለሚበልጡ ሕፃናትም የነፃ የትምህርት ዕድል ሰጥቷል፡፡

ሰ. የልማት ተቋማት

ማኅበሩ «ሐመር» መጽሔት፤ «ስምዐ ጽድቅ» ጋዜጣ፤ መጻሕፍት እና ሌሎችም የኅትመት ውጤቶቹን አሳትሞ በማሠራጨት እንዲሁም ሌሎች የማኅበሩን አገልግሎት ለመደገፍ የሚያስችሉ የልማት ሥራዎችን የሚያከናውን በልማት ተቋማት አስተዳደር ቦርድ የሚመሩ የራሱ የልማት ተቋማት አሉት፡፡ የልማት ተቋማቱ በ18 ማዕከላት /አዲስ አበባን ጨምሮ/ የሚገኙ የማኅበሩን የኅትመት ውጤቶችና ንዋያተ ቅድሳት ማቅረቢያዎች ሲኖሩት በዓይነታቸውም የሚከተሉትን ያካትታሉ፡፡ የካህናት አልባሳት፣ የሞካሽ ሥራ፣ የቆብ እና ጃንጥላ ሥራ ኢንዱስትሪ፣ ንዋያተ ቅድሳት መሸጫ ሱቆች /በቁጥር ሦስት/፣ ምግብ ቤት /በቁጥር ሁለት/፣ ሐመርና ስምዐ ጽድቅ ማከፋፈያዎች /በቁጥር ዐሥራ ዘጠኝ/፣ የመብዐ /የተቀመመ ዕጣን፣ የተለቀመ ነዕጣን፣ ጧፍ፣ ዘቢብ፣ ሻማ/ ማምረቻ ኢንዱስትሪን እንዲሁም የትምህርት ማዕከል በሥሩ ያቅፋል፡፡ ከእነዚህ ገቢ ማስገኛ ተቋማት የሚገኘው ገንዘብ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ለስብከተ ወንጌል ማጠናከሪያ የአብነት ትምህርት ቤቶችና ገዳማትን ለመደገፍ የሚውል ነው፡፡

 ማኅበረ ቅዱሳን ሥርዐተ ቤተክርስቲያን ከማስጠበቅና ቤተክርስቲያንን ከአሕዛብና ከመናፍቃን ከመከላከል አንጻር ምን ሥራ ሠራ?

ማኅበረ ቅዱሳን እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ በተሰጠው የሥራ መመሪያ መሠረት ካከናወናቸው ሥራዎች በተጨማሪ የቅሰጣ ዓላማቸውን በቤተክርስቲያን ላይ ለመጫን በውስጥም በውጪም ከሚንቀሳቀሱ የመናፍቃንና ቤተክርስቲያንን እናድሳለን ብለው እስከተነሱት እኩዮች ሥራቸውን እየተከታተለ በቅዱስ ሲኖዶስና በምእመናን በመረጃ ላይ የተደገፈ ሪፖርት ሲያቀርብ ቆይቷል፡፡ አሁንም እያቀረበ ነው፡፡ ወደፊትም ያቀርባል፡፡ ከዚህም ሌላ በእስልምና ስም የሚንቀሳቀሱ አንዳንድ አክራሪዎች በቤተክርስቲያን ላይ እያደረሱ ያሉትን የጥፋት ዘመቻ ለማስታገስና ምእመናን እንዲረጋጉ ለማድረግ አክራሪዎቹ በቤተክርስቲያን ላይ ላነሱት ጥያቄ ማብራሪያ ያለው መልስ ሲሰጥ ቆይቷል፡፡

ማኅበረ ቅዱሳን እስልምናን በተመ ለከተ የሠራቸው ሥራዎችን በሚከተ ለው መንገድ ማጠቃለል ይቻላል፡፡

1. ከመጀመሪያው ጀምሮ ምእመናን አክራሪውንና ነባሩን ሰላማዊውን እስልምና ነጥለው እንዲመለከቱ ከፍተኛውን ድርሻ ተወጥቷል፡፡

2.. ለሚያነሷቸው ታሪካዊና ዶግማዊ ጥያቄዎች በተጻፉት ጽሑፎች መጠንና ቁጥር ጋር ሊነጻጸር ቀርቶ እዚህ ግባ   የሚባል ባይሆንም መጠነኛ ምላሾችን ሰጥቷል፡፡

3. ተቻችሎና ተከባብሮ ስለመኖር ከየትኛውም አካል በፊት እና በከፍተኛ ሽፋን ሠርቷል፡፡

4. ስለ አክራሪ እስልምና እና ስለ ትንኮሳው እጅግ አነሥተኛ እና ክስተት ተኰር የሆኑ መረጃዎችን በመስጠት ችግሩ ሲያጋጥም ለመንግሥት ማመልከት እንደሚገባ አቅጣጫ ለማሳየት ሞክሯል፡፡

 የፕሮቴስታንትና የተሐድሶ መናፍቃንን ሴራ በማጋለጥ ረገድ

ከላይ ለመግለጽ እንደሞርነው ማኅበረ ቅዱሳን የፕሮቴስታንትና የተሐድሶ መናፍቃንን ሴራ በማጋለጥ ረገድ ቤተክርስቲያንንና ምእመናን እንዲጠነቀቁ እንዲሁም የመናፍቃኑን ማንነት እንዲያውቁ በማድረጉ ረገድ በጣም ብዙ ሥራዎች ሠርቷል፤ እየሠራም ነው፡፡ ከነዚህም ውስጥ «የዘመቻ ፊሊጶስን» የመናፍቃን ባለብዙ በጀት ሰፊ እንቅስቃሴ ቀድሞ መረጃ ለቤተክርስቲያንና ለምእመናን በመስጠት ሴራው እንዲከሽፍ ምእመናንም እንዲጠበቁ አድርጓል፡፡ በዚህም የመናፍቃኑ ሴራ በታሰበበት ሁኔታ ሳይሔድ ተኮላሽቷል፡፡

ሌላው እግራቸውን በቤተክርስቲያን ታዛ ልባቸውን በመናፍቃኑ አዳራሽ አድርገው በቤተክርስቲያን ውስጥ በመሽሎክሎክ የሚሠሩ ተሐድሶ መናፍቃንን ማንነት መረጃ በማቅረብና በማጋለጥ ከድብቅ ዓላማቸው እንዲገቱና እንዲወገዙ አድርጓል፡፡ በዚህ መረጃም ምእመናን ማንነታቸውን እንዲለዩና እንዲጠነቀቁም ተደርጓል፡፡ /በአሁኑ ጊዜ ደግሞ የነዚህ የተሐድሶ መናፍቃን እንቅስቃሴ በገሃድ በቤተክርስቲያኒቱ ሰርገው በመግባትና ለተልዕኮ ባስቀመጧቸው የውስጥ ሰዎች አማካኝነት ተጠናክረው እየሠሩ ነው፡፡ የነዚህንም ማንነት መረጃዎቻችንን አጠናክረን ስንጨርስ ለቅዱስ ሲኖዶስና ለምእመናን የምናሳውቅ መሆኑን በዚህ አጋጣሚ እንገልጻለን፡፡/

በተጨማሪም ላይችሉት የተቀበሉትን የምንኩስና ሕይወት ትተው በመናፍቃኑ አዳራሽ በድብቅ ጉባኤ ያደረጉትን ግለሰቦች ማንነት በማጋለጥ ለምእመናንና ለቤተክርስቲያን አባቶች ለማቅረብ የተደረገውና መናፍቃኑ የቤተክርስቲያንን የዋሀንን ለማሳሳት አስመስለው ከሚያሳትሟቸው የሕትመት ውጤቶችና የድምፅ መልእክቶች ምንነትና ማንነት በማጋለጥ ማኅበረ ቅዱሳን መረጃ ሲሰጥ ቆይቷል፤ አሁንም ወደፊትም ይሰጣል፡፡ በእግዚአብሔር ፈቃድ በዐለት ላይ የተመሠረተ ማኅበር ነውና ቤተክርስቲያን የሰጠችውን ሓላፊነት በብቃት ይወጣል፡፡

በመሆኑም ቅዱስ ሲኖዶስ አጽድቆ በሰጠው መመሪያና ደንብ መሠረት ማኅበሩ በዓይን የሚታይ፣ በእጅ የሚዳሰስ ለውጥ ያመጣ ሥራ ሠርቶ አሳይቷል፡፡ በማሳየት ላይም ነው፡፡ እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ ወደፊትም ያሳያል፡፡ ነገር ግን በውስጥ ያሉ ሥራቸው ያልታወቀባቸው የመሰላቸው የመናፍቃኑ ዐርበኞች ማኅበሩን ሳያውቁት አልያም ለማወቅ ባለመፈለግ ጥቅመኛ አድረገው የሚያስወሩት አሉባልታ ከእውነት የራቀ መሆኑን ማንም የሚገነዘበው ሐቅ መሆኑን ሊረዱት ያስፈልጋል፡፡

እነዚህ እኩያን የቤተክርስቲያን ጠላቶች ማኅበረ ቅዱሳን ባሉት አባላትና በበጎ አድራጊ ምእመናን ድጋፍ በጉልበት በዕውቀትና በገንዘብ ቤተ ክርስቲያን ያለባትን ክፍተት እያጠና ይሞላል እንጂ ከቤተክርስቲያን ዜሮ አምስት ሣንቲም በጀት እንደ ማይመደብለት እያወቁ አለማወቃቸው ነው፡፡ በጀት ከመምሪያቸው በመመደብ ማኅበሩን ያንቀሳቀሱት ይመስል ቤተክርስቲያን ይሠሩልኛል ብላ ያስቀመጠቻቸው አንዳንድ በሓላፊነት ቦታ ላይ ያሉ የመናፍቃኑ ተላላኪዎች ግን ማኅበሩ ሒሳቡን ኦዲት እንደማያደርግና እንደማያስደርግ ጊዜያዊ ትርፍ የሚያገኙ መስሏቸው አሉባልታ በመንዛት ማኅበሩን ያልሆነ ስም ለማሰጠት ሲጣጣሩ እየተሰማና እየታየን ነው፡፡ እውነቱ ግን ይኼ አይደለም፡፡ ማኅበሩ ሲኖዶሱ ባጸደቀለት ግልጽ መመሪያን መሠረት በሚያገለግሉ ባለሙያ አባላቶቹ በየጊዜው ሒሳቡን እያሰላና እያስመረመረ ነው ሥራውን በጥራት እየሠራ የሚገኘው፡፡ ይኼንን አሠራር ለማወቅ ለሚፈልግ ማንኛውም አካል ሁሉ ማኅበሩን ቀርቦ ማየት፤ በማኅበሩም በተለያዩ አህጉረ ስብከት የተሠሩትን ሥራዎች መመርመር ይችላል፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን አሠራሩ ግልጽ አገልግሎቱም የሚታይ ነው፡፡ እነዚህ የማኅበሩን አገልግሎት ለማሳጣት ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ የሚለፍፉት አንዳንድ የመምሪያ ሓላፊዎች ባልሆነ ነገር ላይ ጊዜያቸውንና ጉልበታቸውን ከሚያባክኑ ይልቅ ቤተክርስቲያኒቱ የመደበችላቸውን በጀት በአግባቡ ባለመጠቀማቸው ምክንያት በየጊዜው በየጠቅላላ መንፈሳዊ ሰበካ ጉባኤ ላይ በሪፖርት ላይ ከመወቀስ ቢድኑ መልካም ይሆን ነበር፡፡

ስለ ማኅበረ ቅዱሳን ለማወቅ ለሚፈልጉ ሁሉ ስለ ማኅበሩ አሠራር ብዙ ማለት ይቻል ነበር፤ ነገር ግን ምእመናን ከአሳሳቾች ትጠበቁ ዘንድ ስለማኅበሩ አገልግሎት ከብዙ በጥቂቱ ይኽን እውነታ እንድታውቁ እንወዳለን፡፡

                                                           ወስብሐት ለእግዚአብሔር

«ማኅበረ ቅዱሳን ለሁሉም ግልጽ አሠራር አለው» ክፍል ሁለት

ስምዐ ጽድቅ፦ አንዳንዶች ማኅበረ ቅዱሳን የተወሰነ ብሔር ስብስብ ነው የሚል አስተያየት አላቸው፤ ማኅበሩ ለዚህ ዓይነት አስተያየት የሚሰጠው መልስ ምንድነው?

ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ፡-  በመሠረቱ ማኅበረ ቅዱሳን የክርስቲያኖች የአገልግሎት ማኅበር ነው፡፡ የክርስቲያኖች አገልግሎት ደግሞ «ሑሩ ወመሐሩ፤ ወደ ዓለም ሁሉ ሒዱና አስተምሩ» ማር.16÷15 በሚለው የክርስቶስ ቃል ላይ የተመሠረተ በመሆኑ አገልግሎቱ ለሀገርም፣ ለአህጉርም ብቻ አይደለም ለዓለም ሁሉ ነው፡፡ ስለዚህ ለማገልገልም ለመገልገልም በቋንቋ ወይም በቀለም ወይም በጾታ… ላይ የተመሠረተ የወገንተኛነት አካሔድ ከሃይማኖታችን መሠረታዊ ሐሳብ ጋር የሚጋጭ ነው፡፡ ስለዚህ ማኅበራችን ማገልገልም መገልገልም የሚፈልጉ የትኞቹንም  ወገኖች ከልብና በእውነት የማገልገል ፍላጎት አለው፡፡ ከአፍሪካ የተለያዩ ሀገሮች የመጡ ወንድሞቻችንን ለጥ ምቀት እንዳበቃን ሁሉ ከአውሮ­ ከአሜሪካ  የመጡና በዚያውም ያሉ በቋንቋና በዜግነት ኢትዮጵያዊ ያልሆኑ ሰዎችን ሁሉ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን አምላክነትና መድኃኒትነት አምነው ለጥምቀት  በቅተዋል፡፡ ስለዚህ ማኅበሩ እጅግ ሊታሰብ በማይችል ጠባብነት ታጥሮ የአንድ የተወሰነ ወገን ስብስብ ሆኖ የሚሠራ ነው የሚለው ሐሜት ካለማወቅ ወይም ደግሞ ሌላ ዓላማ ካለው ወገን የሚመጣ ነው የሚል እምነት አለን፡፡ ማኅበሩ ከተለያዩ ብሔረሰብ ለተውጣጡ ምእመናን ሥልጠና በመስጠት በተለያዩ ቋንቋዎች ወንጌል ለሁሉም እንዲደረስ በትምህርትና ሐዋርያ ዋና ክፍሉ አማካኝነት ከፍተኛ ጥረት እያደረገ ነው፡፡ አባላቱም ዕድሉን አግኝተው ወደ ከፍተኛ ተቋማት በመግባት በማኅበሩ አገልግሎት የታቀፉ ሁሉ ወይም የማኅበሩን አገልግሎት ተረድተው አባል ለመሆን ፈቃደኛ ሆነው የቀረቡ ሁሉ ናቸው፡፡ የአባልነት መመዘኛም የቤተክርስቲያን ልጅ በመሆን የሰበካ ጉባኤ ወይም ሰንበት ት/ቤት አባል መሆን ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- የ­ለቲካ አቋምን በተመለከተስ?

ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ- ከላይ ለመጥቀስ እንደሞከርኩት የእኛ ማኅበር ሃይማኖታዊ አገልግሎት ለመስጠት በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ስር የተቋቋመ የአገልግሎት ማኅበር ነው፡፡ ስለዚህ ማኅበሩ እንደ ተቋም የሚሰጠውም አገልግሎት ሃይማኖታዊ ነው፡፡ ለየትኛውም የፖለቲካ ዓይነትና አደረጃጀት የሚያግዝ /የሚሠራ/ እንዲሆን መቼም ቢሆን ፍላጐቱ የለንም፡፡ በማኅበሩ መተዳደሪያ ደንብ አንቀጽ አምስት እንደተቀመጠው «ማኅበሩ በማንኛውም የፖለቲካ እንቅስቃሴ ውስጥ ምንም ዓይነት ጣልቃ ገብነት አይኖረውም»  ይላል፡፡ የዚህን አንቀጽ ይዘት ተግባራዊ ለማድረግ እንዲቻል በማኅበሩ ያሉ የተወሰኑ አካላት በሓላፊነት ላይ እያሉ የማንኛውም የፖለቲካ አባል እንዳይሆኑ በ1998 ዓ.ም የሥራ አመራር ጉባኤያችን ወስኗል፡፡ በውሳኔውም መሠረት የሥራ አመራር ጉባኤ አባላት፣ የሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ አባላት፣ የማኅበሩ መደበኛ መምህራን፣ የኤዲቶሪያል ቦርድ ጽ/ቤት አባላት፣ የኦዲትና ኤንስፔክሽን አገልግሎት ጽ/ቤት አባላት፣ ጋዜጠኞች፣ የማዕከላት ሰብሳቢዎች በሓላፊነት ላይ ያሉ መደበኛ አገልጋዮች የማንኛውም የፖለቲካ ­ፓርቲ አባል አይሆኑም፡፡

ይህ ማለት ግን ­ለፖለቲከኞች በማኅበሩ የማገልገል ዕድል አይኖራቸውም ማለት አይደለም፡፡ ለፖለቲካ ዓላማቸው ማኅበሩን መጠቀም ግን አይችሉም፡፡ ስለዚህ የትኛውንም የማኅበሩን አባል በግሉ የ«ሀ» ወይም የ«ለ» ­ፓርቲ ደጋፊ፣ አባል ወይም አመራር እንዲሆን ወይም እዳይሆን ምንም ዓይነት ተቋማዊ ተጽዕኖ በማኅበሩ የሚፈጠርበት ዕድል የለም፡፡ ይህ ግን ሀገርን በመገንባት ረገድ ለአጠቃላዩ ማኅበረሰብ ትርጉም ያለው ልማታዊ ተግባራትን የማከናውን ዓላማና እንቅስቃሴ የለውም ማለት አይደለም፡፡ እንደሚታወቀው ቤተ ክርስቲያን በታሪኳ ያላት የሀገራዊ ልማት ተሳትፎ ከፍተኛ ነው፡፡ ይህ ደግሞ ቀጣይነት እንዲኖረው ክርስቲያን ምሁራንና ወጣቶች ባላቸው አቅም ሁሉ ይሳተፋሉ፡፡ የልማት ተሳትፎአቸው ለሀገርና ለትውልድ እንዲጠቅም፣ ቤተክርስቲያንም ያላትን ድርሻ እድትወጣ በማሰብ ነው፡፡ ብዙዎቹ ልማታዊ ተግባሮቻችን ደግሞ በቀጥታ የቤተክርስቲያናችንን ጥቅም የሚያስጠብቁ በመሆናቸው እንቅስቃሴያችን ለሌላ ትርጉም በሚጋለጥ መልኩ የሚደረግ ነው የሚል እምነት የለንም፡፡  

በእርግጥ እንደተባለው በሀገር ውስጥም በውጪም በ­ፖለቲካ ወገንተኝነት ማኅበሩን ለማማት የሚፈለጉ ወገኖች እንዳሉ እናውቃለን፡፡ በጣም የሚገርመው ግን የሚሰጡት አስተያየቶች የተዘበራረቁ መሆናቸው በራሳቸው መሠረት የሌላቸው አስተያየቶች መሆናቸውን ያመለክታሉ፡፡ በሀገር ውስጥ ያለው ማኅበሩ የ«ሀ» ፖርቲ ደጋፊ ነው ሲል በውጪ ሀገር ያሉ አንዳንድ ወገኖች ደግሞ የ«ለ» ፖርቲ ደጋፊ ነው እያሉ ተጨባጭነት የሌለውና ምናልባትም የማኅበራችን አባላት በሆኑ የአንዳንድ ግለሰቦች ተሳትፎን መነሻ አድርጐ የሚሰጥ ሚዛናዊ ያልሆነ ድምዳሜ ነው፡፡ ዞሮ ዞሮ ግን ማኅበራችን ቅዱስ ሲኖዶስ በሰጠው መተዳደሪያ ደንብ ላይ ተመርኩዞ አስፈላጊ በሆነ ጊዜ ሁሉ ባለው የፖለቲካ ሥርዓት ከሚቋቋመው መንግሥት ጋር መሥራት ሃይማኖታዊም ሕገ መንግሥታዊም ግዴታው ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን ማኅበሩ እንደተቋም የትኛውንም የፖለቲካ አስተሳሰብ /Ideology/ በመደገፍ ወይም በመቃውም ከፖርቲዎች ጋር ግንኙነት ስለሌለው /ስለማይኖረው/ ለማንም ስጋት ወይም ዕድል ልንሆን አንችልም፡፡ በዚህ ደረጃ ፈርጆን የሚነሣ አካል ካለ ግን ለመፈረጅ ያበቁትን የመረጃ ምንጮች እንዲመረምር በዚሁ አጋጣሚ ሳልጠቁም አላልፍም፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ማኅበሩ አክራሪ ነው ስለሚባለውስ?

ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ፡- እኛ «አክራሪ» የሚለውን ቃል በጥንቃቄ ነው የምንመረምረው?  አክራሪ ማለት የሃይማኖቱን ሕግ አክብሮ የሚኖር ተግቶ የሚጾም፣ የሚጸልይ በሃይማኖቱ ላይ ለሚነሡ ጥያቄዎች መልስ የሚሰጥ፣ ታሪኩን፣ ቤተክርስቲያኑን የሚወድ፣ ለሃይማኖቱ የሚቀና የማይዋሽ ወይም ወደ ከፍተኛ ሥነ ምግባራዊ ሕይወት ራሱንም የሃይማኖት ወገኑን ሁሉ ለማድረስ የሚተጋ ከሆነ የማኅበራችንን አባላት ሊገልጽ ይችላል፡፡ ሰዎች ምናልባት በልማድ በዚህ ብያኔ ለመጥራት ፈልገው ከሆነ ችግር ላይኖረው ይችላል፡፡ ነገር ግን በዚህ ሁኔታ የሚመላለሱትን ክርስቲያኖች «አክራሪ» ተብ ለው ከሚጠሩ አጥባቂ፣ ዐቃቤ ሃይማኖት ቢባሉ የተሻለ ነው፡፡

በሌላ በኩል ግን «አክራሪ» የሚለው የሚያሰቃይ፣ የሚገድል፣ የሚያስገድድ፣ የሚሳደብ፣ የሌላውን ሳይነኩ የራሳቸውን አምልኮ እየፈጸሙ ያሉትን የሚረብሸ፣.. ወዘተ ለማለት የተቀመጠ ብያኔ ከሆነ በወንጌል የሚያምኑ፤ አምነውም የሚያስተምሩ ክርስቲያኖች ሊያደርጉት አይችሉም፡፡ ምክንያቱም ከላዩ የተጠቀሱት ተግባራት ከክርስትና ሃይማኖት አስተምህሮ ጋር ተጣጥመው አይሔዱም፡፡ ማኅበራችንም ስብከተ ወጌልን በመላው ሀገሪቱ  እና ዓለማት የማስፋፋት ዓላማ ይዞ የሚሠራ በመሆኑ ለፍቅርና ለመከባበር ትልቅ ቦታ አለው፡፡

ምናልባት በማስጨነቅ ወይም በማስገደድ ሃይማኖታችንን ለማስጣል የሚደረጉ እንቅስቃሴዎች ሲኖሩ ቅሬታችንን መግለጻችንና በሃይማኖታችን ላይ በኅትመት ወይም በኤሌክትሮኒክስ ሚዲያ አማካኝነት የሚሰጡ አስተያየትና ጥያቄዎች ሲኖሩ መልስና የአጸፋ አስተያየቶችን መስጠታችን በዚህ ደረጃ አስ ፈርጆን ከሆነ ሚዛናዊ ነው የሚል እምነት የለኝም፡፡ እነዚህን የምናደርገው በሃይማኖታችን ላይ ጥያቄ ያነሣውን ወይም አስተያየት የሰጠውን አካል ለመተቸት ወይም ለመሳደብ ተፈልጐ ሳይሆን እነዚህ አካላት ካሠራጯቸው መልእክቶች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንን ሐሳብ እንዳይበረዝ፣ ሃይማኖታችን መልስና አስተያየት የሌለው መስሎ ለምእመናን እንዳይታሰብ ለመጠበቅ የሚደረጉና ለጠየቁን መልስ እንድንሰጥ በሃይማኖታችንም የታዘዘውን መንፈሳዊ ተግባር ለመፈጸም ነው፡፡

መከራ የደረሰባቸውና የሚደርስባቸው ክርስቲያኖች ሲኖሩ ቅሬታችንን መግለጻችን ተገቢ ይመስ ለኛል፡፡ ምክንያቱም ለሀገር ሰላምም የሚበጀው ችግሮች መኖራቸውን ጠቁሞ ሕዝብም መንግሥትም መፍትሔ እየሰጣቸው ሲሔዱ ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ ግን ስሜታዊ በሆነ መልክና ከጀርባው ሌላ ዓላማ ያለው እንቅስቃሴን በክርስቲያኖች ስም ማካሔድን በጽኑ የምንቃወመው ነው፡፡ በአንጻሩ ደግሞ ማኅበረ ቅዱሳን ለቤተክርስቲያን ያለውን ተቆርቋሪነት ከግምት አስገብቶ የተለያዩ አካላት በስሜት የሚያካሒዷቸው ግልጽና ሥውር እንቅስቃሴዎችን ሁሉ ማኅበረ ቅዱሳን ሳይሆን አይቀርም የሚሉ አካላት እንደሚኖሩ እናምናለን፡፡ ሌላው ቀርቶ በዓውደ ምሕረት ቆሞ ያለ ሕግና ሥርዓት የሚያስተ ምሩ መምህራንን ሁሉ የማኅበረ ቅዱሳን መምህራን ናቸው የሚሉም እንዳሉ እናውቃለን፡፡ ነገር ግን በጭፍን የሚሰጡ እነዚህን የሚመስሉ አስተያየቶች ተገቢ አይደሉም፡፡ ምክንያቱም እነዚህ አካላት ማኅበሩ ያሰማራቸው መሆን አለመሆኑን ማጣራትም ወይም ሆኖም ከተገኘ ማኅበሩ ባለው አሠራር ርምጃ እንዲወስድ ማሳሰብ የተሻለ መንገድ ነው፡፡ ስለዚህ በዚህ ዓይነት አቋም ላይ ያለን ማኅበር አክራሪ የሚሉት አካላት ካሉ ያን ለማለት መነሻ ያደረጓቸውን ጭብጦች ማጤን ይኖርባቸዋል እላለሁ፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- ማኅበረ ቅዱሳን ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሰንበት ት/ቤቶች ማደራጃ መምሪያ ጋር ያለው ግንኙነት የሻከረ ነው፤ ማኅበሩም ለመምሪያው ለመታዘዝ ፈቃደኛ አይደለም የሚሉ አስተያየቶችም አሉ፡፡ እርስዎ እንደ ሰብሳቢ ምን ይላሉ?

ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ፡- ማኅበረ ቅዱሳን ሕገ ቤተክርስቲያን የቤተ ክርስቲያኒቱም ደንብና መመሪያዎች እንዲጠበቁ በጸኑ የሚሠራ ማኅበር ነው፡፡ ይህ ዋነኛ አጀንዳ ያለው አካል የማደራጃ መምሪያውን አሠራር ጠብቆ አይንቀሳቀስም ከተባለ ­ራዶክስ /መጣረስ/ ይፈጥራል፡፡ ማኅበሩ በመምሪያው የአሠራር ሥርዓት ላይ ችግር የመፍጠር ፍላጐትም ሥልጣንም የለውም ነገር ግን መምሪያውን ከሚመሩት ግለሰብ ዓላማና አቅም ላይ ግን ጥያቄ አለው፡፡ መከሩ ብዙ ሠራተኞቹ ግን ጥቂት በሆኑበት ቤተክርስቲያን ውስጥ ለአገልግሎት የተሰማሩ ማኅበራት እና ሰንበት ት/ቤቶችን በመምራት ረገድ የሚከተሉት የራሳቸው ፖሊሲ  እንደተመሪ /ባለድርሻ/ ምቹ አይደለም፡፡ ማኅበሩ ላይ አሉ የሚሏቸውን ችግሮች በውይይትና በክርስቲያናዊ የምክክር ሥርዓት ከመፈጸም ይልቅ በግልጽና በስውር የማኅበሩን ስም ማጥፋትን ሥራዬ ብለው ይዘዋል፡፡ የተለያዩ አካላትም በማኅበሩ ላይ የተዛባ አመለካከት እንዲኖራቸው ያላ ሠለሰ ሚና ተጫውተዋል፡፡ ማኅበሩ ችግር አለበት፤ ለመምሪያውም አይታዘዝም… ወዘተ የሚለውን የራሳቸውን ሓሳብ መነሻ አድርገው የሚጽፏቸውን ደብዳቤዎች ምስክር እያደረጉ መናፍቃን ደግሞ በመጻሕፍት አሳትመው ሲሰድቡን እያየን ነው፡፡ ስለዚህ ይህንን እያየን ማኅበረ ቅዱሳንን ከሚጠሉ መናፍቃን ጋር እርሳቸው ተመጋግበው እየሠሩ ነው ላለማለት ዋስትና አይሰጥም፡፡ የማኅበሩ አሠራር ችግር አለበት ብለው ቢያስቡ እንኳን ከሠሯቸው በጐ ተግባራት፣ የወጣት ምሁራን ክርስቲያኖች እንቅስቃሴን አስፈላጊነትና አሁን ቤተክርስቲያን ከአጽራረ ቤተ ክርስተያን በኩል እየደረሰበት ካለው ፈተና አንጻር በስብከተ ወንጌል ረገድ ያለውን ርምጃ በመመልከት ችግሮቹን ከሚመለከታቸው ከተለያዩ አካላት ጋር ተግባብቶ በመፍታት ግልጽ አሠራር ማስፈን ይገባቸው ነበር፡፡ ያንን አላደረጉም፡፡ ስለዚህ በአንዳንድ ማኅበሩ የአሠራር ችግሮች እንዳሉበት ለመምሪያውም እንደማይታዘዝ አድርጐ በማናፈስ ሺሕዎች የተሰለፉለትን ቤተክርስቲያን የመጠበቅ ተልእኮ ማነቆ እንዲያጋጥመው እያደረጉ ነው፡፡ ይህ ደግሞ በግለሰቡ ተልእኮ ላይ ማኅበሩ ጥርጣሬ እንዲያድርበት ሆኗል፡፡ ማኅበሩ ለ17 ዓመታት ከተለያዩ መምሪያ ሓላፊዎች ጋር በምክክር ሠርቷል፡፡ ውጤትም ማስመዝገብ ችሏል፡፡ እኛ ጥያቄያችን ዛሬ እርሳቸው ያገኙት አዲስ ነገር ምንድነው የሚል ነው፡፡

ስምዐ ጽድቅ፡- የመምሪያው ዋነኛ ጥያቄ የማኅበሩን ገንዘብና ንብረት ኦዲት በመደረጉ ጉዳይ ነው፡፡ ማኅበሩ በዚህ ላይ ያለው አቋም  ምን ስልሆነ ነው ችግሮች የተፈጠሩት?

ቀሲስ ዶ/ር ሙሉጌታ- ማኅበራችን ለአገልግሎት የሚያስፈልገውን ከፍተኛ ገንዘብ በሀገር ውስጥና ከውጪ ሀገር ካሉ ከማኅበሩ አባላት የሚያገኘው በማኅበሩ የውስጥ ኦዲተሮች የሚሠሩት ሪፖርት ተአማኒነት ስላለውና የሚታዩ ውጤታማ ክንውኖችን መሠረት አድርጐ ነው፡፡ የኦዲት ሪፖርቱ የማይታመንና ግልጽነት የጎደለው ከሆነና ሥራችንም በጎና ውጤታማ ባይሆን ለቀጣዩ ተግባሮቻችን የሚሆን የገንዘብ መዋጮን መሰብሰብ ባልቻልን ነበር፡፡ ስለዚህ አባላቱ መዝናናት ሳያምራቸው በመጠን እየኖሩ ለቤተ ክርስቲያን ከሚከፈሉት ዓሥራት በኩራት ተጨማሪ ለማኅበሩ አገልግሎት  የሚሰጡትን ገንዘብ፣ ጊዜና ንብረት በአግባቡ መያዝ የእያንዳንዱ አባል ሓላፊነት ያለባቸው አካላት ሁሉ ግዴታ ነው፡፡ ለዚህ ዋስትና የሚሰጠው ደግሞ የኦዲት ሥራው ነው፡፡ ስለዚህ የኦዲት ሥራን ለማኅበራችን ደኅንነት እንደ አንድ ግብ የምናስብ ነን፡፡ ቅዱስ ጳዉሎስ «ስለዚህ ለጋስ ስጦታ ማንም እንዳይነቅፋችሁ ተጠንቀቁ» ያለውን ቃሉን ሁሌ እናስባለን፡፡ ስለዚህ በየጊዜው የኦዲት ሥራዎች የውስጥ ኦዲተሮቻችን ይደረጋሉ፡፡ ያንን አለማድረጋችን ከማደራጃ መምሪያው ይልቅ የሚጐዳው ማኅበሩን ስለሆነ ስለነገሩን ሳይሆን ስለሚያስፈልገን መቼም ቢሆን እናደርገዋለን፡፡ ማኅበሩ በጠቅላላ ጉባኤው የቤተክርስቲያን መምሪያ ሓላፊዎች ባሉበት የሂሳብ ሪፖርት ያቀርባል፡፡ ጠቅላላ ጉባኤውም ሆነ የሚመለከተው አካል የሂሳብ ሪፖርቱ አላረካኝም በውጪ ኦዲተር ይቀርብ ብሎን አያውቅም፡፡ ጥያቄው ከቀረበ ምንግዜም ማድረግ ይቻላል፡፡

አሁን ግን የተሻለ አደረጃጀትና ሰፊ አገልግሎት በሀገር ውስጥና በውጪም መስጠት ስንጀምር መምሪያው በማኅበሩ አገልግሎት የማይደሰቱ ግለሰቦች እና አካላት ጉዳይ አስፈጻሚ ሆኖ መገኘቱ በእጅጉ ያሳስበናል፡፡ ከምንም በላይ ደግሞ የመመሪያ ሓላፊው የእኛን ስም ለማጥፋት በመ ጠመዳቸውና ጊዜያቸውን ለዚያ እየሠው በመሆኑ በኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ሰ/ት/ቤቶች ከመምሪያው የሚፈልጉትን ያህል ድጋፍ ለማግኘታቸው ከፍተኛ ጥርጣሬ አለን፡፡ ከሁሉ በላይ ሊያሰጨንቀን የሚገባ የቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊ አገልግሎት እንጂ ሌላ አልነበርም በእኛ በኩል ግን የሚጠበቅብንን በማድረግ መልካም ግንኙነት እንዲኖረን ሁሌም እንሻለን፡፡ ችግራችንም ከመዋቅሩ /ከመምሪያው/ ጋር ሳይሆን ከመምሪያው ሓላፊ ጋር መሆኑ ሊታወቅ ይገባል፡፡

ጾመ ፍልሰታ ለቤተ ክርስቲያን ሰላም

ኢትዮጵያ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የአሥራት አገር ናት፡፡ ሊቃውንትም ነቢያት የተነበዩትን ትንቢት የቆጠሩትን ሱባዔ መሠረት በማድረግ ቅድስት ድንግል ማርያም በኪደተ እግሯ ኢትዮጵያን መባረኳን ያስተምራሉ፡፡ «ነቢዩ ዕንባቆም የኢትዮጵያ ድኳኖች ሲጨነቁ ዐየሁ፤» ዕንባ. 3፡7 ብሎ የተናገረው ቃለ ትንቢት እመቤታችን የኢትዮጵያን አውራጃዎች ለመባረኳ ማስረጃ መሆኑን ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይተረጉማሉ፤ ያመሠጥራሉ፡፡

ኢየሱስ ክርስቶስ ኢትዮጵያን ለእናቱ አሥራት አድርጐ በመሥጠቱ በእርሷ በኩል ለሰው ልጆች ሁሉ የሚሆን የነገረ ድኅነት ምሥጢር በመከናወኑ ኢትዮጵያውያን ለእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም የተለየ ፍቅር አለን፡፡ የአብነት /የቆሎ/ ተማሪዎች በትምህርት ዓለም ከአንዱ ወደሌላው እየተዘዋወሩ /የአብነት/ ትምህርት ሲማሩ በእንተ ስማ ለማርያም፤ ስለማርያም እያሉ፡፡ የእመቤታችን ስም ስንቅ ምግብ ሆኗቸው ይጠቀሙበታል፡፡ ግሼን ደብረ ከርቤ የልጇ ግማደ መስቀል ከከተመበት አምባም የሚጓዙ ምእመናን «አንድ እፍኝ ሽምብራ አልያዝኩም ከቤቴ ስሟ ስንቅ ነው የእመቤቴ» እያሉ በፍቅሯ ተማርከው ግብር ሰፍረው ዕጣን ቋጥረው ሱባዔ እየገቡ ይማፀኗታል፡፡ እርሷም ከልጇ ዘንድ ባገኘችው የመወደድ ሞገስ ምልጃቸውን በመቀበል ጸሎታችውን በማሣረግ የእናትነት ሥራ ሥትሠራላቸው ኖራለች፡፡ ዛሬም እየሠራች ነው፡፡ እመቤታችን ከልጇ ያገኘችውን /የተቀበለችውን ቃል ኪዳን መሠረት በማድረግ በዐራቱ ማእዘን «ሰዓሊ ለነ ቅድስት፤ ቅድስት ሆይ ለምኝልን» የማይላት የለም፡፡
በፍቅሯ ተደስተው በአማላጅነቷ ተማምነው «የእመቤቴ ፍቅሯ እንደ ሰማይ ክዋክብት፣ እንደምድር አሸዋ በዝቶልኝ፣ እንደ ልብስ ለብሼው፣ እንደምግብ ተመግቤው» እያሉ ተማጽነው ልመናቸው ሠምሮ ቅዱስ ኤፍሬም ሶርያዊው፣ ቅዱስ ያሬድ ዘኢትዮጵያና አባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ ያዘጋጁላትን፣ አባ ጽጌ ድንግል የደረሱላትን የምስጋና መጻሕፍት በመድገም እመቤታችን ዘወትር መማጸን የቀደምት ኢትዮጵያውያንም የዛሬዎች ገዳማውያንና ምእመናን ዕለታዊ ግብር ነው፡፡
ጌታችን ለቀደሙት ቅዱሳን ሐዋርያት እመቤታችን አማላጅ እና እናት ሆኗ እንድታገለግል በገቢርም በነቢብም ከአደራ ቃል ጋር አስረክቧል፡፡ በገቢር በቃና ዘገሊላ የሰውን ችግር ፈጥና የምትረዳ ርኅርኅሪት እናት አማላጅ መሆኗን አሳይቷል፡፡ «ለዚሁም የወይን ጠጅ አልቆባቸዋል» ብላ ያቀረበችው ቃለ ምልጃ ምስክር ነው፡፡ እናት ሆኗ እንድታጽናናቸው በቅዱስ ዮሐንስ በኩል ከእግረ መስቀሉ ስር ሰባቱን አጽራሐ መስቀል ሲያስተጋባ ቅዱስ ዮሐንስን ጠርቶ «እኖኋት እናትህ፤ ድንግል ማርያምን ጠርቶ እነሆ ልጅሽ» ዮሐ. 19፡26፡፡ በማለት እመቤታችን የእናት ሥራ ለሁሉም ቅዱሳን ሐዋርያት እንድትሠራላቸው ምእመናንም ልጅ እንዲሆኗት በማያሻማ ቃሉ ተናግሯል፡፡
ቅዱሳን ሐዋርያት እመቤታችንን በእናትነት ከተረከቧት ጊዜ ጀምረው ልጇ በዕርገት በአካለ ሥጋ ሲለይ እንደ ልጅ አገልግለዋታል፡፡ በቤታቸው አኑረዋታል፤ ብትሠወርባቸው ፈልገዋታል፡፡ ብትርቃቸው ናፍቀዋታል፡፡ እርሷም ሲጠሯት ታደምጣቸዋለች፣ ሲፈልጓት ትገኝላቸዋለች፡፡ ይኸውም የሆነው ልጇ በአዳምና በልጆቿ ኃጢአት ምክንያት የፈረደውን ለራሱም ያላስቀረውን ሥጋዊ ሞት እናቱ ብትቀምስ በእናትነት የተረከቧት ቅዱሳን ሐዋርያት መካነ ዕረፍት ለይተው በንጹሕ በፍታ ከፍነው በጌቴ ሰማኒ እንደቀበሯት ስለ እመቤታችን የተጻፉ መጻሕፍት በዝርዝር ያስረዳሉ፡፡
የእመቤታችን ሥጋዊ ዕረፍት «ከመ ትንሣኤ ወልዳ» እንደ ልጇ ትንሣኤ ነውና ሙስና መቃብር ሳያገኛት ከሦስት ቀናት ሥጋዊ ዕረፍት በኋላ ከሞት ተነሥታ ወደ ሰማይ ስታርግ በዕለተ ቀብሯ ያልተገኘው ቅዱስ  ቶማስ ደመና ጠቅሶ በደመና ሰረገላ ሲመጣ ዕርገቷን ይረዳል፡፡ እማኝ ደግሞ የተከፈነችበትን በፍታ /ጨርቅ/ ይቀበላታል፡፡ ለቅዱስ ቶማስ የተገለጠው የዕረፍቷ ምሥጢር ሌሎች ቅዱሳን ሐዋርያት እንዲገለጥላቸው ቢማጸኑ እመቤታችን ዳግም ተገልጻላቸው፡፡ ትንሣኤዋን ለማየት በቅተዋል፡፡
እነዚህ በቅድስናቸው የተመሠከረላቸው ቅዱሳን እመቤታችንን በሁለት ሱባዔ ማግኘታቸውን መሠረት በማድረግ በቤተ ክርስቲያናችን ከነሐሴ 1-16 በየዓመቱ አንደሚጾም ይታወቃል፡፡ ይህ እመቤታችንን የምንማጸንበት ጾመ ፍልሰታ ቤተ ክርስቲያናችን መፍትሄ የምትፈልግባቸውን ጉዳዮች ለእመቤታችን የምታቀርብበት ሰዓት ነው ብለን እናምናለን፡፡
ኢትዮጵያ የእመቤታችን አሥራት አገር ስትሆን እመቤታችን ለኢትዮጵያውያን እናት መሆኗ እየተነገረ ለምን በፈተና ውስጥ አለፍን? ልጇ በአሥራት ኢትዮጵያን የሰጠባት ሀገር አባቶች ማስፈራሪያ ሲደርስባቸው መንፈሳዊነት /ኀይለ መንሳዊ/ ተዘንግቶ ሥጋዊ ጥበብ በቤተ ክርስቲያን መድረክ ሲታይ ምን ይባላል? «እንግዲህ በነቢዩ በዳንኤል የተባለውን የጥፋት ርኩሰት በተቀደሰችው ሥፍራ ቆሞ ስታዩ አንባቢው ያስተውል በዚያን ጊዜ በይሁዳ ያሉት ወደ ተራራዎች ይሽሹ» ማቴ. 24፡15፡፡ የተባለው ቀን ደርሶ ይሆንን?
ቤተ ክርስቲያን ለረጅም ዓመታት ለገጠማት ችግር መፍትሔ እመቤታችን እጅ ላይ አለ ብለን እናምናለን፡፡ እመቤታችን ብትሠወርባቸው አባቶች ሱባዔ ገብተው እንዳገኟት የፍቅር እናት ናትና ፍቅር አንድነት እንድትሰጠን እርሷን መማጸን፤ የዶኪማስን ጓዳ እንደሞላች የጐደለውን እንድትሞላ ውዳሴዋን እየደገሙ ድንግልን መማጸን ያስፈልጋል፡፡
በውዳሴ ማርያም፣ በጸሎተ ማርያም የሚመካ በጉልበቱ አይመካም፡፡ ጊዜ ረዳኝ ብሎ በወገኖቹ ላይ ግፍ አይፈጽምም፡፡ ስለዚህ በዚህ በወርኀ ጾም እመቤታችን ምልጃዋ ከአገራችን፣ ከቤተ ክርስቲያናችን ጋር እንዲሆን በሱባዔ እንማጸናት፡፡
በጾመ ፍልሰታ ከሊሂቅ እስከ ደቂቅ በማስቀደስ፣ በጾምና በጸሎት ሁለቱን ሳምንታት እንደሚያሳልፉት ይታወቃል፡፡ በሱባዔው የቤተ ክርስቲያናችን ችግሮች የሚወገድበት ምእመናን በበረከት የሚጐበኙበት ቅድስና የሚሰፍንበት መንፈሳዊነት ትልቅ ከበሬታ የሚገኝበት ጾም እንዲሆን ሁሉም ምእመን መትጋት አለበት፡፡
ሁለቱ ሳምንታት በቅጽረ ቤተ ክርስቲያን ዘወትር እየተገኘን ምሕላ የምናደርስበት፣ የተጣላነውን ይቅር ለእግዚአብሔር፣ የበደልነውን የምንክስበት ጾም መሆን አለበት፡፡
ቀናቱን እየቆጠርን እስከተወሰነው ሰዓት ብቻ መጾም ብቻ በሕይወታችን መሠረታዊ ለውጥ አያመጣም፡፡ እመቤታችን የአገራችን አሥራት የሁላችን እናት በመሆኗ የእናትነት ሥራ እንድትሠራልን በሚገባ ልንማጸናት ይገባል እንጂ በቅጽረ ቤተ ክርስቲያን ሱባዔ ብለን ውዳሴ ማርያም በደገመ አፋችን ሰው የምናማ በሰው ሕይወት ገብተን የምንፈተፍት ከሆነ እመቤታችንን አናውቃትም፡ እመቤታችንም አታውቀንም፡፡ ስለዚህ ጾመ ፍልሰታን እስኪ ሁላችን ኢትዮጵያውያን የተዋሕዶ ልጆች ድንግልን በአንድ ድምፅ እንጥራት፡፡
የእመቤታችንን ጾመ ፍልሰታ፤ እንደ ብርሃን ተስፋ በማድረግ በተለይም ለቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የሚተጉ አባቶች እና ምእመናን ለተሰደዱ፣ ለተራቡ፣ በፈተና ውስጥ ለሚገኙ ይማጸኑ እንላለን፡፡ ውዳሴ ማርያሙ፤ ሰዓታቱ ጨለማን ተገን አድርጐ ከሚቃጣ ማስፈራሪያ እና ዛቻ ድርብ ኀይል አለው፤ እስኪ ለቅድስና፣ ለንጽሕና ለመንፈሳዊነት ቅድሚያ እንስጥና የእግዚአብሔርን ብድራት እንጠብቅ፡፡ ጾመ ፍልሰታ መንፈሳዊነት፣ እውነት፣ ቅድስና የጠራ አሠራር፣ በቤተ ክርስቲያን የሚሰፍንበት እንዲሆን እንመኛለን፡፡
 
                                                             ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ስለወደዱ …/ዮሐ.3-19/

ብርሃን ወደ ዓለም ስለመጣ፣ ሰዎችም ሥራቸው ክፉ ነበርና ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ስለወደዱ ፍርዱ ይህ ነው፡፡ ክፉ የሚያደርግ ሁሉ ብርሃንን ይጠላልና፡፡ ሥራውም እንዳይገለጥ ወደ ብርሃን አይመጣም፤ እውነትን የሚያደርግ ግን ሥራው በእግዚአብሔር ተደርጐ እንደሆነ ይገለጥ ዘንድ ወደ ብርሃን ይመጣል፡፡ /ዮሐ.3-19/

ለዚህ እትም መልእክታችን መግቢያ ጌታችን እና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከብርሃን ይልቅ ጨለማን ከእውነት ይልቅ ሐሰትን የመረጡ ሰዎችን ማንነት ለመግለጥ የተናገረውን አምላካዊ ቃል መርጠናል፡፡ ብርሃን እውነት፤ ብርሃን የጠራ አሠራር፤ ብርሃን የዘመድ አሠራር ባላንጣ፤ ብርሃን የሕገ ሲኖዶስ መከበር፤ ብርሃን የቤተ ክርስቲያን ልዕልና መገለጫ ነው፡፡ ጨለማ ግን የብርሃን ተቃራኒ ነው፡፡

ካሳለፍነው ወርኃ ግንቦት መጋመሻ ጀምሮ በቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያናችን ለዘመናት ሰፍኖ የቆየውን የአስተዳደር ችግር በሠለጠነ መንገድ፣ በመወያየት፣ በመተማመን ለመፍታት ሁሉም የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ከስምምነት ላይ መድረሳቸውን ባለፈው እትም ከመንበረ ፓትርያርክ ጽሕፈት ቤት የወጣውን መረጃ መሠረት በማድረግ አሰንብበናል፡፡

በቤተ ክርስቲያን አባቶች ዘንድ ተፈርቶ ይፋ ሳይወጣ ለዘመናት ሲጉላላ የቆየው የአስተዳደር ችግር፣ የቤተ ዘመድ አሠራር፣ ሙስና፣ ተገቢውን ሰው በተገቢ ቦታ አለመመደብ፣ የተዝረከረከ የሒሳብ አሠራር እና ተገቢ ያልሆነ የሀብት አጠቃቀም ችግር ይፋ ወጥቶ የመወያያ አጀንዳ ሆኖ በቃለ ጉባዔ ሰፍሮ መቀመጡ ለነገዋ ቤተ ክርስቲያን ዕድገት አንድ እርምጃ ነው፡፡

«አትስረቅ፣ መመለጃ አትቀበል፣ እውነቱን እውነት በሉ» የተባሉት አምላካውያት ቃላት መመሪያዋ በሆነ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ከሠናይ ይልቅ እኩይ ሥነ ምግባሮች በቅለው ሐዋርያዊ ጉዞዋን በፍጥነት እንዳይካሔድ የኋሊት ሲጓተት እያዩ «ሆድ ይፍጀው» ብለው ማለፍ ቀርቶ ብፁዓን አባቶች ችግሮችን አፍረጥርጠው መነጋገራቸው ያስደስታል፡፡

በቤተ ክርስቲያን አባቶች መኖራቸው የታመነባቸው ችግሮች እንዲፈቱ በቅዱስ ሲኖዶስ አባላት የሥራ አስፈጻሚ አባላት መመረጣቸውም ይታወሳል፡፡ ለሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላቱ ቅዱስ ሲኖዶስ በሰጣቸው ሓላፊነት መሠረት የቤተ ክርስቲያን ችግር ለመፍታት ሲንቀሳቀሱ በተፈጠረው አለመግባባት ችግሩ ወርኃ ሐምሌ ላይ ደርሷል፡፡ እኛም የተፈጠረው ችግር ከምንም በላይ የቤተ ክርስቲያን ክብር ባስቀደመ መልኩ እንዲፈታ ሐሳባችን ሰንዝረናል፡፡ በመግቢያችን እንደጠቀስነው «ብርሃን ወደ ዓለም ስለመጣ» የቤተ ክርስቲያን የአስተዳደር ችግር ይፈታ ስለተባለ፤ ሥራቸው ክፉ የነበረው «የዘመድና የብልሹ አሠራር ተጠቃሚ የሆኑ ሰዎች ከቤተ ክርስቲያን የአስተዳደር ችግር መፍታት ይልቅ ጨለማን ስለወደዱ ወደ ብርሃን አንመጣም አሉ፡፡ ጨለማን ተገን አድርገው የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ቤት መዝጊያ ሰበሩ፣ ፎከሩ፣ አስፈራሩ፣ ዛቱ፣ ቆይ ትኖራላችሁ አሉ፡፡ ዛቻና የድብደባ ሙከራ የተፈጸመባቸው የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት እንደገለጹት ድርጊቱ የቤተ ክርስቲያንን ክብር ዝቅ ያደረገና አሳፋሪ ተግባር ነው፡፡ ይህ ሁሉ የሆነው «ክፉን የሚያደርግ ብርሃንን ይጠላልና ሥራውም እንዳይገለጥ ወደ ብርሃን አይመጣም» እንደተባለው  ክፉ የሚያደርጉ ቤተ ክርስቲያንን የሚመዘብሩ ሰዎች ብርሃንን ስለሚፈሩ ነው፡፡

ብርሃን እውነትን የሚፈሩ የጨለማው ቡድን አካላት፤ «በሊህ እገሪሆሙ ለኪኢወ ደም፤ ደም ለማፍሰስ እግራቸው ፈጣን ነው» «ሐሳር ወቅጥቃጤ ውስተ ፍኖቶሙ፤ ጥፋት ጉስቁልና በመንገዳቸው አለ፤ የሰላም መንገድ አያውቋትምና እግዚአብሔርን መፍራት በዓይናቸው ፊት የለም» ሲል ነቢዩ ቅዱስ ዳዊት የገለጣቸው ዓይነት ናቸው፡፡ መዝ. 13-6፡፡ በኃይል፣ በዛቻና በማስፈራሪያ የቤተ ክርስቲያን ችግር ስለማይፈታ የእነዚህ ቡድኖች ዓላማ ቤተ ክርስቲያን ወደተሳ ሳተ ጐዳና የሚመራ ነው፡፡ የጨለማ ቡድን ዘመቻ ከቤተ ክርስቲያን ልጆች አልፎ ወደ ብፁዓን አባቶች አምባ መደረሱ እጅግ ያሳዝናል፡፡

ሕገ ሲኖዶስ እንዳይከበር እንቅስቃሴ የሚያደርጉ የጨለማው ቡድን አባላት» እውነት ተድበስብሶ እንዳይወጣ የሚያደርጉት እኩይ ጥረት ከሠመረ ቤተ ክርስቲያን «ቤትየሰ ትሰመይ ቤተ ጸሎት አንትሙሰ ረሰይክምዋ በአተ ፈያት ወሠረቅት፤ ቤቴስ የጸሎት ቤት ትባላላች እናንተ ግን የወንበዴዎች ዋሻ» አደረጋችኋት፡፡ የሚለው ዕጣ ይገጥማታል፡፡

ቤተ ክርስቲያን ከጨለማ አስተዳደር ወደ ብርሃን እንድትወጣ «እውነትን የሚያደርግ ግን ሥራው በእግዚአብሔር ተደርጐ እንደሆነ ይገለጥ ዘንድ ወደ ብርሃን ይመጣል» እንደተባለ የቤተ ክርስቲያን የአስተዳደር ችግር እንዲፈታ ጨለማ የሆኑ ወደ እውነት እና ወደ ብርሃን መምጣት አለባቸው፡፡

በቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ የተመረጠው ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ሥራውን እንዲቀጥል እገዳ እንደተነሳለት ከመንበረ ፓትርያርክ የተሰጠው መግለጫ ያመለክታል፡፡ በመሆኑም ቅዱስ ሲኖዶስ የመረጣቸውና ሓላፊነት የተሰጣቸው የሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባላት በጠቅላይ ቤተ ክህነት አሉ የተባሉ ችግሮች እንዲፈቱ ቤተ ክርስቲያን የጣለችባቸውን ሓላፊነት መወጣት አለባቸው፡፡ በቤተ ክርስቲያን ያለው ብልሹ አሠራር መፈታት ከምእመናን ጀምሮ እስከ መንግሥት አካላት እንደ ሚደግፉት እናምናለን፡፡

ችግሩን ለመፍታት ሐሳብ የሰጡ ብፁዓን አባቶችን የማሸማቀቅ አሳፋሪ ተግባር ማንነታቸው ባልታወቁ ግለሰቦች ስለተፈጸመባቸው መንግሥት አስፈላጊውን ጥበቃ ሊያደርግላቸው ይገባል፡፡ የብፁዓን አባቶች ዓላማ መንፈሳዊ ዓላማ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያንን ችግር ከመፍታት ውጪ የተለየ አንዳች ዓላማ እንደሌላቸው ከሰጡት ሐሳብ መረዳት ይቻላል፡፡

በመሆኑም ምንጊዜም የሕዝብን በሕይወት የመኖር መብት የሚያስከብረው መንግሥት ጨለማን ተገን አድርገው የቤተ ክርስቲያንን ሕልውና ነፃነት ደፍረው በብፁዓን አባቶቻችን ላይ የመዝጊያ ሰበራ፣ የድብደባ ሙከራ የፈጸሙ አካላትን በቁጥጥር ስር አውሎ የእርምት ርምጃ መወሰድ አለበት፡፡

ከሀገር ሀገር ዞረው «በእንተ ስማ ለማርያም» ብለው የተማሩ አባቶች ዕድሜ ዘመናቸውን ሁሉ በእግርና በፈረስ ተዘዋውሮ ቤተ ክርስቲያን ያገለገሉ «ሕገ ቤተ ክርስቲያን ሕገ ሲኖዶስ ይክበር» በማለታቸው ዛቻ፣ ማስፈራሪያ፣ የመዝጊያ ሰበራ ሲፈጸምባቸው መሰማት ቤተ ክርስቲያን ወደየት እየተጓዘች ነው ያሰኛል፡፡

በአጽራረ ቤተ ክርስቲያን በቤተ ክርስቲያን የውስጥ ጠላቶች መከራ መቀበል የአባቶች ሕይወት ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ለማገልገል በቅዱስ መሰዊያው ፊት ቃል ኪዳን የገቡት አባቶቻችን ስለቤተክርስቲያን ክብር ዛቻና እንግልት ቢፈጸምባቸው እንኳ መከራውን በአኮቴት ተቀብለው ሓላፊነታቸውን መወጣት ይኖርባቸዋል፡፡ በሰላማዊ መንገድ በሠለጠነ መንገድ ችግሮች እንዲፈቱ እግዚአብሔርን አጋዥ በማድረግ መወያየት የጀመሩትን ከፍጻሜ ማድረስ አለባቸው፡፡

ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ ካህናት፣ የሰንበት ት/ቤት አባላት፣ የሰበካ ጉባኤ አካላት፣ በአጠቃላይ ምእመናን ምን ጊዜም እውነተኛዋ ቤተ ክርስቲያን በማዕበል የምትገፋ መሆኗን ተረድተው በተፈጠረው ችግር መረበሽ የለባቸውም፡፡ የተፈጠረው የአስተዳደር ችግር በጠራና አስተማማኝ በሆነ መንገድ እስከሚፈታ ድረስ በመረጋጋት፣ በጾም፣ በጸሎት መትጋት ይኖርባቸዋል፡፡

«የገበያ ግርግር ለቀጣፊ ያመቻል» እንዲሉ የተፈጠረውን ችግር መነሻ በማድረግ በቤተ ክርስቲያን አካባቢ ምዝበራ፣ ዘረፋ፣ ሕገ ወጥ ድርጊት እንዳይስፋፋ ምእመናን የቤተ ክርስቲያን ንብረት ንብረታቸው፤ ሕልውናዋ ሕልውናቸው ስለሆነ ቤተ ክርስቲያናቸውን መጠበቅ አለባቸው፡፡

 
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የቅርሶች ዘረፋን ለመከላከል

የኢትየጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን የረጅም ዘመን ታሪክና የበርካታ ውድና ምትክ የሌላቸው እንዲሁም ማንኛውም መጠን ያለው ገንዘብ የማይተካቸው ታሪካዊና ዓለማቀፋዊ እውቅና ያላቸው ቅርሶች ባለቤት ነች፡፡ እነዚህ ሃይማኖታዊ እና ተፈጥሮአዊ ቅርሶቻችን ከቀደምት አባቶቻችንና አያቶቻችን የወረሰናቸው እኛም በተራችን ጠብቀንና ተንከባክበን ለቤተክርስቲያን ዕድገትና ለሀገራዊ ልማት እያዋልን ለመጪው ትውልድ የምናስተላልፋቸው መተኪያ የሌላቸው እሴቶቻችን ናቸው፡፡ ቅርሶች ያለፈውን፣ ነባሩንና ተተኪውን ትውልድ የሚያገናኙ የኅብረ ትውልድ ድልድዮች ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያን የእነዚህ ንዋይ ሊተምነው የማይችል ቅርሶች ግምጃ ቤት መሆኗ እና እኛም ልጆቿ የዚህ ታሪክ ተረካቢዎች በመሆናቸን መንፈሳዊ ፍስሐ ይሰማናል፡፡

ስለ አገራችን ቅርስ ሲነሣ በአብዛኛው በቅርስነት የተመዘገቡትና የሚጎበኙት የቤተክርስቲያናችን ቅርሶች ናቸው፡፡ ይህም ሁኔታ የኢትዮጵያ ታሪክና የቤተክርስቲያን ታሪክ የማይነጣጠሉ የአንድ ሣንቲም ሁለት ገጽታዎች አድርጓቸዋል፡፡ ስለዚህ ሁላችንም የሀገሪቱ ዜጎች ስለ ቅርስ ጥበቃ የሚኖረን ግንዛቤ ለታሪካችን ካለን አመለካከት የሚነሳ ነው፡፡ አንድ ሕዝብ ቅርስ አለው ስንል ታሪክ አለው፣ ክብር አለው፣ ተደማጭነት እንዲያገኝ የሚያደርግ ማሰረጃ አለው ማለት ስለሆነ ለቅርስ የሚደረግ እንክብካቤና ጥበቃ በታሪክ መዘክርነት ለሚቀርብ ማስረጃ የሚደረግ ጥበቃ መሆኑን ተገንዝበን ለቅርስ ጥበቃው ከግል ፍላጎትና እምነት ነፃ ሆነን ሀገራዊና ሕዝባዊ አስተያየትን ማዳበር ያስፈልጋል፡፡
 
ይሁን እንጂ ዛሬ ብዙ ሃይማኖታዊ ተፈጥሯዊና ታሪካዊ የቅርስ ሀብት እንዳለን ስንገልጽ፣ በርካታ ቅርሶቻችንን በተፈጥሮና ሰው ሰራሽ ችግሮች ምክንያት ማጣታችን መዘንጋት የለብንም፡፡ እንዲሁም እያየን ነው፡፡ ይልቁንም አሁን በእጃችን ካለው የቅርስ ሀብታችን አብዛኛዎቹ አንድም ባሳለፍናቸው የእርስ በእርስ ግጭቶችና ያለተቋረጡ የባዕድ ወራሪዎችን ለመከላከል በተደረጉ ጦርነቶች ወድመዋል ተመዝብረዋል፡፡ ከዚያም ያለፈው በራሳችን ሰዎች፣ በወራሪ ኃይሎች፣ በጎብኚዎች፣ በተመራማሪነት ስምና በልዩ ልዩ ዲኘሎማሲያዊ መብቶች ሽፋን በየጊዜው በሚመጡ ግለሰቦች ተዘርፈው ተወስደዋል፡፡
 
በጦርነት የወደመውን የቅርስ ሀብታችንን «የፈሰሰ ውሃ» እንዲሉ አበው መፍትሔ ባናገኝለትም እንኳ እጅግ ድንቅ የሆኑ ታሪካዊና ሃይማኖታዊ እንዲሁም ባሕላዊ ቅርሶቻችን ታሪኩ ታሪካቸው ባሕሉ ባሕላቸው፤ ሆኖ በማይዘክሩለት ባዕዳን ሀገራት እጅ ተከማችተው ይገኛሉ፡፡ ለእነዚህ አካላት የገቢ ምንጭ ሆነዋል እነዚህን ቅርሶች ስለ ሀገሩ ባሕል፣ ታሪክና ሃይማኖት እንዲሁም ወግ ለማጥናት የፈለገ ኢትዮጵያዊ ተመራማሪ ከፍተኛ ገንዘብ  በማውጣት ያባቶቹን ሀብትና የእሱነቱን መገለጫ የታሪክ ቅርስ መረጃዎችን ለማግኘት በባዕዳን ሙዚየሞችና ቤተ መጻሕፍት እየዞረ የመንከራተቱ መራር እውነት በብዙ ወንድሞቻችን አንደበት በየጊዜው የሚነገር ነው፡፡ ይሄን እውነት እነርሱ እንኳን ብንለው ችግሩ ከቶ ሊያስረሳን አይችልም፡፡
 
ለዚህም አብነቶችን ማንሣት ይቻላል፡፡ በእንግሊዝ ሠራዊት የተዘረፈውን አንድን የመጾር መስቀል ፎቶ ግራፍ ለማንሳት ብቻ በመቶ ሺህዎች የሚቆጠር ገንዘብ ቅርሱን በያዘው ክፍል መጠየቁ እንዲሁም የቅዱስ ላሊበላ አፍሮ አይገባ መስቀላችንን ከቤልጅም በከፍተኛ ዋጋ መግዛታችን የቅርብ ጊዜ ትዝታዎቻችን ናቸው፡፡
 
ይህ አልበቃ ብሎ ቅርሶቻችን ያለ አግባብ በሕገ ወጥ መንገድ ከሀገር እየወጡ በአሜሪካና አውሮፖ በመረጃ መረቦች አማካ ኝነት በግልጽ እየተቸበቸቡ ይገኛሉ፡፡ ዛሬም ቅርሶች የሚገኙባቸው አድባራት፣ ገዳማትና አብያት ክርስቲያናት፣ ተቋማት መካነ ቅርሶች መደፈራቸውና በውስጣቸው የሚገኙ ብርቅና ድንቅ ሃይማኖታዊ፣ ታሪካዊና ባሕላዊ ቅርሶች መዘረፋቸው አልተገታም፡፡
 
ቅርሶች ለጊዜያዊ አፍቅሮተ ንዋይ ሲባል ያለ አግባብ የመዘረፋቸው የመበላሽታቸውና የመባከናቸው መርዶ አልቆመም፡፡ ከዚህ አንፃር ይህ ወቅት ለእኛ ለአሁን ትውልድ ወጣቶች፣ ለቤተክርስቲያን አባቶችና ለመንግሥት ሁለት ሊታለፉ የማይችሉ ፈተናዎች ለምርጫ ከፊት ለፊታችን ተደቅነዋል፡፡ እነዚህ ምርጫዎች አንድም ቅርሳችንን ሕገ ወጥ ዝርፊያ ማስቆም፣ ያለ አግባብ የተዘረፉትን ለማስመለስ በተጀመረው ጥረት ሳይታክቱና ሳይሰለቹ መቀጠልና በእጃችን ያሉትን ጠብቆና ተንከባክቦ ለቤተክርስቲያን ዕድገትና ለሀገር ልማት እያመቻቹ ለተተኪው ትውልድ በማስተለለፍ ታሪካዊና ሃይማኖታዊ ግዴታዎችን መውጣት፤ ወይም አሁን በአብዛኞቻችን እየተደረገ እንዳለው ዘረፋና ጥፋቱን በግዴለሽነት በመመልከት ድሀ ደካማና መረጃ አልባ ሀገር እና ቤተክርስቲያን ለትውልድ ጥሎ በማለፍ የታሪክና ትውልድ ተወቃሽ መሆን ናቸው፡፡
 
ያለ ማወላወል ለማንኛውም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ እምነት ተከታይ አገልጋይ ካህናት እንዲሁም ሀገር ወዳድ እና ቅን ዜጋ ምርጫ ሊሆን የሚገባውና የሚሆነው የመጀመሪያው ነው፡፡ በመጀመሪያው ምርጫችን መሠረት ከመንግሥት ለቅርስ እንክብካቤ የሚጠበቀው ሚና ቅርሶችን ለመጠበቅ፣ ለመንከባከብና ለማልማት በርካታ ሕጐችን፣ አዋጆችንና ፖሊሰዎችን ማውጣቱንና ዓለም ዓቀፋዊ እና አህጉራዊ የቅርስ ስምምነቶችን መፈራረሙ ይታወቃል፡፡ ለምሳሌ በሕገ መንግሥቱ አንቀጸ 91 ላይ ስለ ቅርስ መደንገጉ የቅርስ ጥናትና አጠባበቅ አዋጅ መውጣቱ፣ የባሕል ፖሊሲ መቀረጹ እና ሀገሪቱ ቅርሱን አስመልክቶ ዓለም አቀፋዊ ስምምነቶችን መፈራረሟ የሚያሳየው መንግሥት ለጉዳዩ ልዩ ትኩረት መስጠቱን ነው፡፡
 
ይሁን እንጂ ዓለም አቀፍ ስምምነቶች መፈራረምና ሕጎችንና አዋጆችን ቢወጡም አሁን የሚታየውን የቅርስ ዘረፋ ቀጥሏል፡፡ በቅርስ ዘረፋ ተሰማርተው ለተያዙት ሰዎች የሚሰጠውም ቅጣት ለሌሎች አስተማሪ ባለመሆኑም ለዘራፊዎች መበራከት ተጠቃሽ ምክንያት ነው፡፡ የቅርስ ዘረፋን አስመልክቶ ቀድሞም ሆነ አሁን  ተሻሽለው የወጡት ሕጎችና አዋጆች ግን ጉዳዩን አስመልክተው ያወጡት የቅጣት ውሳኔ ከፍተኛ ነበር፡፡ በቅርስ ጉዳይ ላይ በወጡ የተለያዩ ዓለም አቀፍ ስምምነቶች የሚደረጉት ቅርሶች ከአንድ ሀገር ወደ ሌላ ሀገር በሕገ ወጥ መንገድ እንዳይተላለፍ ለመከላከል በማሰብ ነው፡፡ ኢትዮጵያም እነዚህን ዓለም አቀፍ ስምምነቶች በመፈራረሟ በስምምነቱ  ተጠቃሚ ልትሆን ይገባት ነበር፡፡ ሀገራችን ከውጪ ወደ ውስጥ የምታስገባው ቅርስ ባይኖረም፤ ከእርሷ ግን ብዙ ቅርሶች በሕገ ወጥ መንገድ የተዘረፋት ቅርሶች ወደ የሀገራችው እንዳመለሱ ያዛል፡፡ ይሁን እንጂ ይህንን ጉዳይ ተግባራዊ ለማድረግ እና የተዘረፍብን ቅርሶችን ወደ ሀገር ለማስመለስ እየተደረገ ያለው ጥረት ጥሩ ቢሆንም በውጪ ካለን የቅርስ ብዛት አንፃር ሲመዘን ከቁጥር የሚገባ ባለመሆኑ በዚህ ረገድ የሕገ አስፈጻሚ አካላት ብዙ መሥራት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ይህም ብቻ አይደለም፤ ቅርሶችን አስመልክቶ የወጡት ሕጎች በትክክል እንዲፈጸሙ ገቢራዊ ማድረግ ያስፈልጋል፡፡
 
የቅድስት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን አባቶች የእምነቱ ተከታዮች የቅርሰ ዘረፋን ሕገ ወጥ ዝውውርን ይበልጥ የመንከባ ከብና የመጠበቅ ግዴታ እንዳለብን ልናውቅ ይገባል፡፡ አሁን በሥራ ላይ ባለው አዋጅ ቁጥር 2ዐ9/1992 ዓ.ም ላይ የቅርስ ባለቤት የሆነ ሰው በእጅ የሚገኘውን ቅርስ ተገቢውን  ጠበቃና እንክብካቤ ካላደረገ… ለቅርሱ አጠባበቅ የሚወጡ ደንቦችንና መመሪያዎችን ያላከበረ እንደሆነ ወይም በይዞታው እንዲጠቀምበት በተሰጠው መሬት ላይ የሚገኝ ቅርስ በሚገባ የማይጠብቅ ከሆነ ወይም ቅርሱን የሚያሰተላልፍ ሰው የቅርሱን ማስተላለፍ ለባለስልጣኑ /ለመንግሥት/ ያላሳወቀ እንደሆነ… ይህን አስመልክቶ የወጣውን አዋጅ የማያስፈጸም ከሆነ እሰከ ስድስት ወር እስራት እንደሚቀጣና ወይም እስከ 1 ሺሕ አምስት መቶ ብር እንደሚቀጣ ተደንግጓል፡፡
 
በየጊዜው ትኩረት እየተሰጣቸው አዋጆች ገቢራዊ እንዲሆኑ  የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ክትትል ማድረግ አለባቸው፡፡ በቅድሚያ የአገራችን ሕዝብ ሁሉ የኢትዮጵያ መገለጫና የቱሪስት መስህብ የሆኑ ቅርሶች የአገራቸው ሀብት በመሆናቸው በባዕዳን ሲዘረፉ ሲቃጠሉ በቸልታ መመልከት የለባቸውም፡፡ ምእመናንም ቀደምት አበው ቀን በጽሕፈት ሌሊት  በጸሎት ተገተው ያዘጋጇቸው መጻሕፍት የገዳሟቸው ገዳማት ያካበቷቸው ንዋያተ ቅድሳት የእምነታቸው መገለጫ በመሆናቸው በእኔነት ስሜት ሊጠብቋቸው፤ ተዘርፈው ሲሄዱ ጥብቅና ሊቆሙላቸው ይገባል፡፡

የቅርስ ባለቤት የሆነችው ቅድስት ቤተክርስቲያን በየገዳማቱና አድባራቱ የሚገኙ ቅርሶቿን ሥርዐት ባለው መንገድ መመዝገ ብና ስለ ቅርሶቿ ተጨባጭ የሆነ መረጃ መስጠት አለባት፡፡ ከሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት ጋርም በመቀናጀት ቅርሶች ሲዘረፉ፣ ሲቃጠሉ በፍጥነት ለሕግ አስፈጻሚ አካላት ተገቢን እገዛ ማድረግ ይጠበቅባታል፡፡ ይኸውም ባለቤት በማጣት በግለሰቦችና በእግዚቢትነት ተይዞ የሚገኝ ቅርሶቿን ለማስመለሰ ይረዳታል፡፡
 
በአጠቃላይ ቅርሶች የሀገራችን ሀብታት የቀደሙት አበው ሥልጣኔ መገለጫ ዛሬ ላይ ቁጨ ብለን የትላንትን የምናይባቸው የክብራችን ገላጭ የእኛነታችን መለያ አሻራ በመሆናቸው በኅብረት እንክብካቤ ልናደርግላቸውና ጥብቅና ልንቆምላቸው ይገባል፡፡
የሕግ አስፈጻሚ አካላት ቢሆኑም በቅርስ ዙሪያ የወጡ ሕጎችንና አዋጆችን በትክክል መፈጸማቸውን ይከታተል፤ የቅርስ ዘረፋን እና ሕገወጥ ዝውውርን ለመግታት ሕጎች በትክክል ሊፈጸሙ ይገባል፡፡

 

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር