ጥር 9/2006 ዓ.ም.
በእንዳለ ደምስስ
• “የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች ቤተ ክርስቲያኗ የምታምንባችሁ፤ እናንተም የቤተ ክርስቲያኒቱ ታማኝ ልጆች እንደሆናችሁ እናምናለን፡፡” /ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ /
• በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ተንሰራፍቶ ያለውን ሙስና፤ ዘረኝነት፤ ብልሹ አሠራሮች አንገታችንን ደፍተን እንድንሔድ አድርጎን ነበር፡፡/የሰንበት ትምህርት ቤት ወጣቶች/
የአዲስ አባባ ሰንበት ትምህርት ቤቶች አንድነት ሓላፊዎችና አባላት በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የተንሠራፋውን ብልሹ አስተዳደር፤ ሙስናና ዘረኝነትን ያስተካክላል ተብሎ የተዘጋጀውን አዲሱን መዋቅራዊ ለውጥ እንደሚደግፉ ጥር 8 ቀን 2006 ዓ.ም. በጠቅላይ ቤተ ክህነት ስብከተ ወንጌል አዳራሸ ቅዱስ ፓትርያርኩና ብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት በተገኙበት አስታወቁ፡፡
ተወካዮቹ በመግለጫቸው “በርካታ የሰንበት ትምህርት ቤት አባላት እስከ እስር ድረስ በመድረስ ሲታገሉለት የነበረውንና አይነኬ የሚመስለውን በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ የተንሰራፋውን ብልሹ አሠራርን እናወግዛለን፡፡ እነዚህን ዘርፈ ብዙ ችግሮችን ለመቅረፍ በሚደረገው ጥረት ውስጥም በግንባር ቀደምትነት እንሰለፋለን፡፡ እስካሁን በቤተ ክርስቲያናችን ውስጥ ተንሰራፍቶ ያለውን ሙስና፤ ዘረኝነት፤ ብልሹ አሠራሮች አንገታችንን ደፍተን እንድንሔድ አድርጎን ነበር፡፡ ዛሬ የቤተ ክርስቲያናችን ትንሣኤ ደርሷል፡፡ የጥንቷን ቤተ ክርስቲያናችን ክብር እንደሚመለስልን እናምናለን፡፡ እኛም ከቅዱስነትዎና ከቅዱስ ሲኖዶስ ጎን በመሰለፍ የሚጠበቅብንን ለማበርከት ተዘጋጅተናል” ብለዋል፡፡