ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለምን ጾመ?

ዲያቆን ዮሴፍ በቀለ  

በገዳም ቆሮንቶስ ፵ ቀንና ለሊት የጾመው

ሀ/ ሕግን ሊፈጽም

የሕግ ሁሉ ባለቤት የሆነው አምላካችን እግዚአብሔር ጾምን ለአዳም የሰጠው ጥንታዊው ሕግ ከእግዚአብሔር ዘንድ ሰማያዊ ዋጋ የሚያገኝበት ጸንቶ እንዲቆም የሚያስችለውና ከክፉ የሚጠብቀው መንፈሳዊ መከላከያው መድኃኒት ሆኖ የተሰጠው ፤  ኦሪትም የተሰራችው በጾም ነበር፡፡ አባታችን ሙሴ ኦሪት ዘዳግም  ፱፥፱ ላይ “ሁለቱን የድንጋይ ጽላት እግዚአብሔር ከእናንተ ጋር የተማማለባቸውን የቃልኪዳን ጽላት እቀበል ዘንድ ወደ ተራራ በወጣሁ ጊዜ በተራራውም አርባ ቀንና አርባ ለሊት ተቀምጬ ነበር፤ እንጀራ አልበላሁም፤ ውሃም አልጠጣሁም”፤ አለ፡፡ በዚህም ሙሴ የኦሪትን ሕግ ተቀበለ፤ እናም ሕግን ለመቀበል በቅድሚያ መጾም ያስፈልጋል ፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ሕግን ሲፈጽም በቅድሚያ የወንጌል መጀመሪያ ያደረገው ጾምን ነው፤ የማቴዎስ ወንጌል ፬፥፩-፲፩ ላይ “እኔ ሕግ ልሽር ሳይሆን ልፈጽም ወደ ምድር ወርጃለሁ”፤ አለ፡፡

ለ/ዕዳችንን ሊከፍል (ካሳ ሊሆነን)፤

እግዚአብሔር ለአባታችን አዳም “ይህንን ዕፀ በለስ አትብላ፤ የበላህ እንደሆነ ትሞታለህ”፤ ብሎት የነበረውን ትእዛዝ ተላልፎ በራሱ ፍቃዱ ተጠቅሞ የተከለከለችዋን ፍሬ በላ፤ ሕግንም ጣሰ፡፡ ስለዚህ አዳም በመብላት ያመጣውን ሞት ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከተጠመቀ በኋላ  ለ፵ ቀን ለ፵ ለሊት ባለመብላት ባለመጠጣት ዕዳችንን ከፈለ፡፡ ደሙን አፍሶ፤ ሥጋውን ቆርሶ፤ በቀራንዮ አደባባይ ተሰቅሎ አዳምን ከሞት ወደ ሕይወት፤ ከሲኦል ወደ ገነት መለሰው፡፡

ሐ/ለአርያነት፤ የመንፈሳዊና የበጎ ምግባር ሁሉ መነሻው ጾም ነው፡፡  የዕለተ ዐርብ የማዳኑን ሥራ በጾም ጀመረ፤ የወንጌል ሥራ መጀመሪያም አደረጋት፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዚህ ዓለም በዮርዳኖስ ከተጠመቀ በኋላ  ሥራውን በጾም እንደ ጀመረ ሐዋርያትም ስለተረዱ እርሱን በመምሰል ሥራቸውን በጾም ጀመሩት፡፡ አባቶቻችን ጾምን የትምህርት መጀመሪያ አደረጓት፤ በዚህም ለዘለዓለም ከእግዚአብሔር ጋር በመንግሥቱ እንዲኖሩ በር ስለከፈተላቸው ለአርአያነት ነው ብለን ተቀበልነው፡፡ ሆኖም ሳይጾም ጹሙ አላለንም፤ በምድር እስካለንና እርሱ አርአያ እስከሆነን ድረስ  ከመዓትና ከዘላለም እሳት ለመዳን በጾምና ጸሎት ልንኖር ያስፈልጋል፡፡፡

መ/ሊያስተምረን፤ የተፈቀደውን እየፈጸምን፤ የተከለከልነውን በመተው ሕግ እያከበርን በትምህርተ ወንጌል ድኅነትን እንድናገኝና የነፍሳችን ቁስል እንዲፈወስ ለክርስቶስ ሕይወታችንን መስጠት አለብን፡፡ እንዲሁም ለመጾም ድፍረት ያላት ነፍስ ቀጣይነት ባለው መንፈሳዊ ልምምድ ራስን መግዛት ለሥጋ ፈቃድ የሚያስፈልገውን ምግብና መጠጥ በመተው የሥጋ ፈቃድን ድል በመንሣት ለነፍስ ፈቃድ ማስገዛት ይቻላል ፡፡ ይህቺ ነፍስ ክርስቶስ ያስተማራትን ከተገበረች የሚመጣባትን ከባድ ነገር ሁሉ እስራቱንና ግርፋትን መቋቋም ይቻላታል፡፡ ስለዚህ መጾም በኃጢአታችን እንድንጸጸትና ወደ አግዚአብሔር እንድንመለስ (እንድንቀርብ )ብቻ ሳይሆን ለዘለዓለም ከእግዚአብሔር ጋር ለመኖር ያለንን ፍቅር ለመግለጽ እንድንችል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስተምሮናል፡፡

ሠ/ ዲያብሎስን ድል ለመንሣት፤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በማቴዎስ ወንጌል ፬፥፩-፲፩ ላይ መዋዕለ ጾሙ ሲፈጸም ሰይጣን በሦስት ነገር ማለትም በስስት፣ በትዕቢትና በፍቅረ ንዋይ ተፈታተነው፡፡ በስስት ቢፈትነው በትዕግስት፣ በትዕቢት ቢቀርበው በትሕትና፤ በፍቅረ ንዋይ ሊያታልለው ቢሞክር በጸሊአ ንዋይ ድል ነሣው፡፡ ዛሬ እነዚህን ማሳቻ መንገዶች ለይተን ጠላታችንን ድል መንሣት እንችላለን፤ ክርስቶስ ሳጥናኤልን ስለ እኛም ተዋጋው፤ በገሃነም ጣለው፡፡ በዮሐዋንስ ወንጌል ፲፮፥፴፫ ላይ “ስለዚህ እኔ ዓለምን ድል ነስቼዋለኹና ድል ንሱ” ያለበት ምክንያትም ጾም ደዌ ነፍስን ትፈውሳለችና፡፡ የሥጋ ምኞትን አጥፍታ የነፍስን ረኃብ ታስታግሳለችና፤ ከዲያብሎስ ቁራኝነት በማላቀቅ ከክርስቶስ ጋር አንድ ታደርጋለች፡፡

እኛ ለምን እንጾማለን?

ጌታችን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመጾም ለነፍሳችን ካሳ እንደሆነን ሁሉ እየጾምን፤ ጠላታችን ሳጥናኤልን ድል ነሥተን አባቶቻችን የወረሱትን ርስት እንድንወርስ እንጾማለን፡፡ ጾም በመንፈሳዊ ሕይወት የመበልጸጊያና የሰውነት መሻትን ለእግዚአብሔር መሥዋዕት አድርጎ የማቅረቢያ መንገድ ነው፡፡ በዚህም ጾም የወንጌልና የበጎ ሥራ ሁሉ መጀመሪያና የትሩፋት ጌጥ እንደሆነ ሁሉ፤ መጀመሪያና መጨረሻ የሌለው፤ አልፋና ኦሜጋ ልዑል እግዚአብሔር ለአዳም የሰጠው የመጀመሪያ ትእዛዙ ነው፡፡ ዘፍጥረት ፪፡፲፯ ላይ “ነገር ግን መልካሙንና ክፉን ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ፤ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና”፤ ብሎ ያዘዘው ትእዛዝ ይህ ነውና፡፡

ጾም ስንል፤ ፩ኛ እግዚአብሔርን የምንፈራበትና ከእግዚአብሔር ምሕረት የምንለምንበት መንገድ ነው፡፡

ዕዝራ ፰፡፳፫ ላይ “ስለዚህም ነገር ጾምን ወደ እግዚአብሔር ለመንን፤ እርሱም ተለመነን”፤ በማለት ጾም እግዚአብሔርን መለመኛ እና ጸሎታችንን እንዲሰማን የምናደርግበት መሣሪያችን መሆኑን በተግባር እንዳገኙ እንረዳበታለን፡፡

፪ኛ ኀዘናችንን እና ችግራችንን ለእግዚአብሔር የምንነግርበትና  የምናቀርብበት መንገድ ነው፡፡

ነቢዩ ኢዩኤልም ሕዝበ እስራኤልን ሐዘን በገጠማቸው ጊዜ፤ በመከራም ሳሉ ትንቢተ ኢዩኤል ፩፥፲፬ ላይ የነገራቸው ቃል “ጾምን ቀድሱ፤ ጉባኤውንም አውጁ፤ ሽማግሌዎችንና በምድር የሚኖሩትን ሁሉ ወደ አምላካችሁ ወደ እግዚአብሔር ቤት ሰብስቡ፤ ወደ እግዚአብሔር ጩኹ”፤ በማለት ወደ እግዚአብሔር መጸለይ እንደሚገባ ነግሮናል፡፡ ትንቢተ ኢዩኤል ፪፡፲፪ ላይም “እግዚአብሔር በፍጹም ልባችሁ በጾምም፣በለቅሶና በዋይታ ወደ እኔ ተመለሱ፤ በጽዮን መለከትን ንፉ፤ ጾምንም ቀድሱ፤ ጉባኤውንም አውጁ”፤ በማለት ነግሮናል፡፡ ስለዚህ ለእግዚአብሔር በመብላት፣ በመጠጣትና በሥጋ ፍላጎት ሆነን የፍላጎታችን፣ የሰላማችንንና የአንድነታችን መሻት መጠየቅ የለብንም፡፡ መጀመሪያ እራሱ ክርስቶስ ማድረግ ያለብንን የተግባር ሥራ እንድንሰራ የነገረን ከችግራችንና ከሐዘናችን ለመላቀቅ በምድር ለምንኖር ሁሉ መጾም እንዳለብን እራሱ ባለቤቱ እግዚአብሔር በነቢያት አድሮ ነግሮናል፡፡

፫ኛ ስብራታችን የምንጠግንበትንና መልካም የሆነ ትውልድ የሚታነጽበት መሣሪያ ነው፤

ትንቢተ ኢሳያስ ፶፰፡፲፪ ላይ “ከድሮ ዘመን የፈረሱት ስፍራዎችህ ይሠራሉ፤ መሠረትህም ለልጅ ልጅ ዘመን ይሆናል፤ አንተም ሰባራውን ጠጋኝ የመኖሪያ መንገድንም አዳሽ ትባላለህ”፡፡ እንዲሁም በቁጥር ፭ ላይ “እኔ ይህንን ጾም የመረጥሁ አይደለሁም”፤ እንደዚችም ባለች ቀን ሰው ራሱን ማሳዘን እንደሌለበትና በዚህም ጾም ራሱን ቢያስገዛ በዚያን ጊዜ በእግዚአብሔር ይታመናል፤ በምድርም በረከት ላይ ይኖረዋል፤ እግዚአብሔርም በያዕቆብም ርስት ይመግበዋል፤ እርሱ እግዚአብሔር ተናግሯልና”፡፡

፬ኛ የአምልኮ መንገድ ነው፤

የሐዋርያት ሥራ ፲፫፡፩-፪ ላይ እንደተገለጸው መንፈስ ቅዱስ ለሥራ የጠራቸውን በርናባስንና ሳውልን ያሰናበቷቸውም በጾምና በጸሎት ነበር፡፡ በዚያም ጊዜም ከጾሙ፤ ከጸለዩ፤ እጃቸውንም ከጫኑ በኃላ አሰናበቷቸው፡፡ አንድ ሰው የአምልኮ መንገድ ሲጀምር መጾም መጸለይ እንዳለበት እራሱ ኢየሱስ ክርስቶስ እንዳስተማረን፤ ጾም የአምልኮ መንገድ ስለሆነች ነው፡፡ ሐዋርያትንም የጠፋውን ትውልድ ለመፈለግ ሐዋርያዊ ጉዞ ከማድረጋቸው በፊት ጾመዋል፡፡

፭ኛ አጋንትን የምናወጣበት እና ርኩሳን መናፍስትን የምንዋጋበት መሣሪያችን ነው፤ማር ፱፡፳፱  ጌታችን ደቀመዛሙርቱ ማውጣት አቅቷቸው የነበረውን ጋኔን እርሱ ካወጣው በኋላ ወደ እርሱ ቀርበው “እኛ ልናወጣው ያልቻልን ስለምን ነው?” ብለው በጠየቁት ጊዜ ስለ እምነታቸው ማነስ መሆኑን ነገራቸው:: “ይህ ወገን በጸሎትና በጾም ካልሆነ በምንም ሊወጣ አይችልም’ ነው ያላቸው፡፡ ስለሆነም ያለ ጾምና ጸሎት አጋንንት ማውጣት አይቻልም፡፡ ጾምን እየነቀፉና እያጥላሉ እንዲሁም በተግባር ሳይጾሙ አጋንንት እናወጣለን ማለት፤ የአጋንንት መዘባበቻና መጫወቻ እንደሆነ መረዳት ያስፈልጋል፡፡

ቤተ ክርስቲያንን ከጠላት ስውር ደባ ለመጠበቅ ጾምና ጸሎት ያስፈልጋል!

           

በሕይወት ሳልለው

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የመሠረታት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የድህነታችን መገኛና መገለጫ ናት፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “ለእግዚአብሔር የሚገባ ቅንዓት እቀናላችኋለሁና፤ ወደ እርሱ አቀርባችሁ ዘንድ ለአንዱ ንጹሕ ድንግል ሙሽራ ለክርስቶስ አጫቻችኋለሁና” (፪ቆሮ ፲፩፥፪) ሲል በቆሮንቶስ መልእክቱ ገልጿል፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን በጠላት ስትታደን እንደኖረች ታሪክ ያስረዳናል፡፡ ልጆቿም እንደሷ ብዙ መከራን እንዳዩ፤ ያለበደላቸው መከራን እንደታገሱና ለእምነታቸው ብዙ መሥዋዕትነት እንደከፈሉም አንብበን ተረድተናል፡፡ ለምሳሌ “ዘመነ ሰማዕታት ብዙ መከራን ያሳለፈችበት ዘመን ነበር፡፡ ሁልጊዜ ቤተ ክርስቲያንን ስናይ ዕለተ ዐርብን እናስባለን፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደሙ የመሠረታት፤ካህናት፤ ቀሳውስትና አገልጋዮች የሥራ ድርሻቸውን የሚያካሂዱባት የተቀደሰች ስፍራ ቤተ ክርስቲያን ናት” በማለት መጋቤ ሐዲስ ቀሲስ መንግሥቱ ማርያም፤ በአዲስ አበባ ሀገር ስብከት የቦሌ ቡልቡላ መድኃኔዓለም ቤተ ክርቲስያን የስብከተ ወንጌል ሐላፊ አስረድተዋል፡፡

የኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ህልውናዋ ሊጠበቅ ይገባል፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በየክፍለ ሀገራቱ አብያተ ክርስቲያናት እየተቃጠሉ መሆኑ በይፋ እየተነገረ ነው፡፡ ከጅማው ክስተት በኋላ ቤተ ክርስቲያናችን ላይ በተደጋጋሚ ችግር ደርሷል፡፡ ለዚህ የሀገር ጉዳይ መፍትሔ ለማግኘት የሃይማኖት አባቶች፤ አገልጋዮችና የሁላችንም ኃላፊነት ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ያቃጠሉ ሰዎች ሲያልፉ በዘመነ ሰማዕታት ውስጥ ያለፈች ቤተ ክርስቲያን ግን ዛሬም ነገም ምእመኖቿን አስተምራ፤ሥጋ ወደሙን እያቀበለች ትኖራለች፡፡

“የምእመናን ድርሻ ደግሞ ቤተ ክርስቲያንን መጠበቅ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን መከራ እንዲቆም ጾምና ጸሎት ያስፈልጋል፤ያለበለዚያ ግን እሳትን ሰማዕትነት ነው ብለን አናስበውም፤መከራ ነው እንጂ፡፡  ሰማዕታት የሃይማኖት ፍሬ እንዳያመልጣቸውና አክሊልም እንዳያልፈን በማለት ይሯሯጡ ነበር፡፡ በመጀመሪያ፤ እንኳን መንፈሳዊ ሥራ ሥጋዊ  ሥራም ያለ የእግዚአብሔር ፍቃድ አይሳካም” ሲሉም መጋቤ ሐዲስ ቀሲስ መንግሥቱ ማርያም ጨምረው አብራርተዋል፡፡

ይህ የጠላት ሴራና ክፋት በተለያየ መንገድ ምእመናንንና ቤተ ክርስቲያንን ለማጥፋት የሚደረግ በመሆኑ ከሥር መሠረት ልንመረምረው ይገባል፡፡ “የአማኞችን መብት ጠብቀው የአምልኮት ሥርዓታቸውን በሀገራቸው በነፃነት እንዲፈጽሙ የሃይማኖት መሪዎች ጥብቅና ሊቆሙላቸው ይገባል፡፡ ሲሰደዱ፤ ሲገደሉና ለተለያየ ጥቃት ሰለባ ሲሆኑ ዝም ብለን ማየት የለብንም፡፡ ይህ የአገልጋዮች ምግባር እየቀዘቀዘ በመሄዱ፤ ቤተ ክርስቲያን ለዚህ አይነት ተፅዕኖ ተዳርጋለች፡፡ አንዳንድ ሰዎች በኃይል ወይም በነውጥ የሚያደርጉት አግባብ የሌለው ተግባር ሊወገዝ ይገባል” ሲሉ የቅዱስ ጳውሎስ የሐዲስ ኪዳን መምህር መጋቤ ሐዲስ አእምሮ ደምሴ ገልጸዋል፡፡

የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እንድትደክም፤ ምእመናን ላይ ጥርጣሬ እንዲፈጠር እንዲሁም የትክክለኛዋ ሃይማኖት ተከታይና ክርስቲያናዊ ምግባር እንዳይኖር በስውር ተመሳስለውና በስመ ሰባኪ የጠላትን ምኞት ለማሳካት ደፋ ቀና የሚሉ ተኵላዎችም በዝተዋል፡፡ “የበግ ለምድ ለብሰው ወደ እናንተ ከሚመጡ ከሐሰተኞች ነቢያት ተጠንቀቁ፤ በውስጣቸው ግን ነጣቂ ተኩላዎች ናቸው”፤(ማቴ ፯፥፲፭) ሲል ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስቀድሞ ነግሮናል፡፡

ከኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት የራቁ ሰዎች ከቤተ ክርስቲያን ቀኖና፤ ሥርዓትና ትውፊት ውጪ በመሆን ከራሳቸውም አልፎ ሌሎችን ያስታሉ፡፡ ጠላታችን ዲያብሎስ ከጥንት ጀምሮ ምእመናንን ተስፋ ማስቆረጥ፤ ከእምነታቸውና ሃይማኖታቸው ማስወጣት ተግባሩ ነውና  ልንጸና ይገባል፡፡ ይህም የሚሆነው አምነን፤ተጠምቀን በበጎ ምግባር ታንጸን በሕገ እግዚአብሔር መኖር ስንችል ነው፡፡ በመጽሐፍ እንደተጻፋው እነዚህ ጸንተው ይኖራሉ የሚላቸው ሦስት ነገሮች እምነት፤ተስፋና ፍቅር  ናቸው፤ (፩ቆሮ ፲፫፥፲፫)፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ በቆሮንቶስ መልእክቱ እንደገለጸው “ደስ የሚላችሁን እንድታደርጉ እንረዳችኋለን እንጂ እንድታምኑ ግድ የምንላችሁ አይደለም”፤ (፪ቆሮ ፩፥፳፬) ፡፡

እንዲህ እምነት በጠፋበት፤ የመናፍቅ ቅሰጣ በበዛበት፤ ዓለም በኃጢአት ማዕበል በምትናወጥበት ወቅት ከሐሰተኞች ትንቢት መጠንቀቅ ይኖርብናል፡፡ ጌታችንም እንደተናገረው “የሚያስታችሁ እንዳይኖር ተጠንቀቁ፤ ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉና፤ብዙዎችንም ያስታሉ፤ጦርነትን፥ የጦርነትንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ፤ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠንቀቁ፤ አትደንግጡ፤ ነገር ግን ፍጻሜው ገና ነው”፤(ማቴ ፳፬፥፬-፮)፡፡

ከጠላት ስውር ደባ ለማምለጥ የእግዚአብሔር ቸርነት ከእኛ ጋር ሊሆን  ያስፈልጋል፡፡ ከሃይማኖት አባቶች ጋር ያለንን ኅብረት ማጠንክር ስንችልም ፈጣሪያችን ያድነናል፡፡ እያንዳንዳችን ቤተ ክርስቲያን መሔድ፤ ክርስቲያናዊ ምግባርን ማዘውተር፤ ዘወትር መጸለይ፤ ንስሓ መግባትና መጾምም  ይጠበቅብናል፡፡

 

 

 

 

ዘወረደ እምላዕሉ አይሁድ ሰቀሉ፤ ከላይ(ከሰማይ) የወረደውን አይሁድ ሰቀሉት፤(ቅ/ያሬድ)

 

 

ዲያቆን አቢይ ሙሉቀን

በቦታ የማይወሰነው አምላክ ሥጋን በመዋሕዱ ወረደ፤ ተወለደ፤ ተሰደደ፤ ተራበ፤ ተጠማ፣ ተሰቀለ እየተባለ ይነገርለታል፡፡ የእኛን ሥጋ ተዋሕዶ ወደዚህ ዓለም መጥቶ በአጭር ቁመት በጠባብ ደረት በመወሰን ተወለደ፤ ሦስት ዓመት ከሦስት ወር ወንጌልን ዞሮ አስተማረ፤ በመስቀል ላይ መከራን ተቀበለ፤ ሞተ፤ተቀበረ፤ተነሣ፤ ዐረገ፡፡ ዘለዓለማዊ አምላክ በመሆኑም በሁለም ስፍራ ይኖራል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ በዐቢይ ጾም እግዚአብሔር ሊመሰገንበት የሚገባውን ምስጋና በጀመረበት ክፍሉ “ሃሌ ሃሌ ሉያ ዘወረደ እምላዕሉ አይሁድ ሰቀሉ ወሚመ ኢያእመሩ እግዚአ ኵሉ ዘያሐዩ በቃሉ፤ ቅድመ ዓለም የነበረ፣ ዛሬም ያለ፣ ዓለምን አሳልፎ የሚኖር፤ ከላይ (ከሰማይ) የወረደውን አይሁድ ሰቀሉት፤” ብሏል፡፡ ነገር ግን  አላወቁም፤ በቃሉ የሚያድን የሁሉ ጌታ ነውና” በማለት ጾመ ድጓ በሚባለው ድርሰት ይገልጸዋል፡፡

በዚህ ክፍለ ንባብ ሊቁ ቅድመ ዓለም የነበረ፣ ዛሬም ያለ፣ ወደፊትም ዓለምን አሳልፎ የሚኖር እንደ ሆነ፣ እንዲሁ ስለ ልዕልናው በሰማያት የምትኖር ይባላልና ከሰማይ የወረደውን አይሁድ ሰቀሉት አለ፡፡ እርሱ ራሱ ለደቀ መዛሙርቱ የጸሎት ሥርዓት ሲያስተምራቸው “አባታችን ሆይ በሰማያት የምትኖር…” ብላችሁ ጸልዩ ብሎ የእርሱ አባትነት ሰማያዊ እንጂ ምድራዊ እንዳልሆነና ከምድራዊ አባት የተለየ እንደሆነ በማስረዳት “በሰማያት የምትኖር በሉኝ” አለ፡፡ ሊቁም ይህን መሠረት አድርጎ “ከሰማይ የወረደውን አይሁድ ሰቀሉት” አለን፡፡

ከሰማይ የወረደው ቅድመ ዓለም አብ ያለ እናት በማይመረመር ጥበቡ የወለደው ድኅረ ዓለም ድንግል ማርያም ያለ አባት በማይመረመር ጥበብ የወለደችው ኢየሱስ ክርስቶስ ወልደ አብ ወልደ ማርያም ነው፡፡ ሥጋዊ ልደት የሆነ እንደሆነ ከአባት ዘር ከእናት ደም ተከፍሎ ይወለዳል፡፡ የኢየሱስ ክርስቶስ ልደት ግን ከአብ ያለእናት፤ ከእናት ያለአባት ሲሆን  እንዲህ ነው ተብሎ አይመረመርም፡፡ በማይመረመር ልዩ ጥበብ ስለተወለደ ስለልዕልናው በሰማይ የምትኖር ይባላል፡፡ ዘበእንተ ዕበይከ ትትሜሰል በደመናት፤ ስለልዕልናህ በደመናት ትመሰላለህ እንዲል፤ ስለዚህ ከላይ ከሰማይ የወረደውን ማለት በልዕልና ያለውን የሚኖረውን አምላክ አይሁድ ሰቀሉት፡፡

የአይሁድን ግብዝነት የጌታን ሁሉን ቻይነትም ሲያስረዳን፤  “ምንም አላወቁም፤ የሰቀሉት በቃሉ የሚያድነውን የሁሉን ጌታ ነው” ይለናል፡፡ በማቴዎስም ወንጌል ፱፥፲፰ ታሪኩ ተመዝግቦ እንደምናገኘው የመቶ አለቃው ልጁ በታመመበት ጊዜ “እባክህ አድንልኝ” በማለት ተማጸነው፤ “እኔ መጥቼ አድንልኃለሁ” ብሎትም ነበር፡፡ የመቶ አለቃውም በበኩሉ ፍጹም እምነትን የተሞላ ስለነበር “ሁሉ ይቻልሃል፤ በቃልህ ብቻ ተናገር ልጄ ይድናል” ብሎ ስለሁሉን ቻይነቱ  በምሳሌ ተናገረ፡፡ ጌታም የመቶ አለቃውን እምነት አድንቆ እንደወደድክ ይደረግልህ አለው፤ ልጁም ተፈወሰ፡፡ ይህንም የሚያውቀው ሊቁ ቅዱስ ያሬድ “እግዚአ ኵሉ ዘየሐዩ በቃሉ የሚያድን የሁሉ ጌታ” በማለት ገልጾታል፡፡

እንግዲህ ቤተ ክርስቲያን ጌታ ከሰማየ ሰማያት መውረዱን፣ ከድንግል ማርያም መወለዱን፣ መሰደዱን፣ መጠመቁን፣ በገዳመ ቆሮንቶስ መጾሙን በአጠቃላይ የነገረ ድኅነት ጉዞ ብላ ትገልጸዋለች፡፡ ገዳመ ቆሮንቶስ ገብቶ ፵ መዓልት  ፵ ሌሊት ጾመ፡፡ የዐቢይ ጾም ሳምንት መግቢያ የሆነውን የመጀመሪያውን ሳምንት “ዘወረደ፤ ከሰማይ የወረደው አምላክ” በማለት ታስበዋለች፡፡

በዚህም ሳምንት ከሰማየ ሰማያት መውረዱን፣ ከድንግል ማርያም መወለዱን፣ ለዓለም ቤዛ ሲል መከራ መቀበሉን የምናስብበት ሳምንት ነው፡፡ ይህ ሳምንት ጾመ ሕርቃል በመባልም ይታወቃል፡፡ ጾመ ሕርቃል የተባለበትም ምክንያት ጌታችን የጾመው ፵ መዓልት ፵ ሌሊት ሲሆን እኛ ግን ፶፭  ቀናት እንጾማለን ፡፡  ይህም የሆነበት ምክንያት ጌታ ከጾመው ፵ ቀን በተጨማሪ ቅዳሜና እሁድ ለብቻው ተቆጥሮ አንድ ሳምንት፡፡ በመጨረሻ ያለው አንድ ሳምንት ሰሙነ ሕማማት በመሆኑ በመጀመሪያ ያለው አንድ ሳምንት ደግሞ ጾመ ሕርቃል ይባላል፡፡ ሐዋርያት፡- ጌታ ፵  መዓልት ፵  ሌሊት ከዘረጋ ሳያጥፍ ከቆመ ሳይቀመጥ ነው የጾመው፤ እኛ ደግሞ እሑድና ቅዳሜ አንጾምም በማለት በመጀመሪያ ያለውን አንድ ሳምንት ጨምረው ጹመውታል፡፡

ሌላው በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ ፲፭ እንደምናገኘው በ፯ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በኢየሩሳሌም ፎቃ፣ በሮም ደግሞ ሕርቃል የሚባሉ ነገሥታት ነበሩ፡፡ ይህ የኢየሩሳሌሙ ንጉሥ ፎቃ ጨካኝና ለክርስቲያኖች የማይራራ ሆነ፡፡ በዚህ ጊዜ ሕዝቡ፤ ለሮሙ ንጉሥ “እባክህ ከእንዲህ ካለው ጨካኝ ንጉሥ አድነን፤ እኛ ላንተ እንገዛለን” በማለት ይልኩበታል፡፡ እርሱም ለጊዜው ቸል ብሏቸው ቆይቶ ነበር፡፡ከዕለታት አንድ ቀን “ግዙራን ይነሥእዋ ለመንግሥትከ፤ ክርስቲያኖች መንግሥትህን ይወርሷታል” የሚል ራእይ አይቶ፤ ይህ የኢየሩሳሌሙ ንጉሥ ነው በማለት እንደገና የላካችሁብኝን ነገር አልረሳሁትም፡፡ ነገር ግን ሐዋርያት ነፍስ ያጠፋ ዕድሜ ዘመኑን ይጹም ብለዋልና፤ ያን ብፈራ ነው እንጂ አላቸው፡፡ እነሱም የአንድ ሰው ዕድሜ ፸ ፹ ነው፤ እኛ ተከፋፍለን እንጾምልሃለን ብለውት ጠላታቸውን አጥፍቶላቸዋል፡፡ እነሱም ተከፋፍለው አንድ ሳምንት ጹመውታል፡፡

ስለዚህም በንጉሡ በሕርቃል ምክንያት ስለተጾመ ጾመ ሕርቃል ይባላል፡፡ ታሪክ ያላወቁት አንድ ጊዜ ብቻ ጾሙ፡፡ ታሪክ ያወቁት ደግሞ ቀድሞም ሐዋርያት ጹመውታል በማለት መጾም ቀጥለዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ይህን መሠረት አድርጋ ከጌታ ጾም መግቢያ ላይ እንዲጾም ሥርዓት ሠርታለች፤ በመሆኑም ምእመናን ከጾሙ በረከት ያገኙ ዘንድ እንዲጾሙ ታስተምራለች፡፡ በዘመኑ ክርስቲያኖች ከጨካኙ ግዛት የዳኑበት ነው፡፡ ዛሬም ምእመናን ከጨካኙ ዲያብሎስ ፈተና፣ መከራና የጭካኔ አገዛዝ ነጻ የሚወጡበት ነውና ሊጾሙት ይገባል፡፡

በአጠቃላይ ይህ ጾም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ከሰማየ ሰማያት መውረድ፤ ከቅድስት ድንግል ማርያም መወለድና ወደዚህ ዓለም መምጣት የሚታሰብበት ስለሆነ “ዘወረደ” ተብሎ ተሰይሟል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ “እስመ ጾም ትፌውስ ቁስለ ነፍስ ወታጸምም ኵሎ ዘሥጋ ፍትወታተ፤ጾም የነፍስን ቁስል ታድናለች፤ የሥጋን ፍላጎትንም ታስታግሳለች፡፡” ጾመን፤ ጸልየን፤ የሚታገለንን የሥጋ ፍላጎት ለማስታገሥ፣ ነፍሳችንን ለማዳን፣  ከእግዚአብሔር ጋር ለመገናኘት፣ የኃጢአት ስርየት ለማግኘት ይህን ጾም በመጾም በረከተ ሥጋ በረከተ ነፍስን እናገኝ ዘንድ እግዚአብሔር ይፍቀድልን፤ አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

አእመረ አሸብር “የቅዳሴ ሥርዓት” ሲያካሔድ በቁጥጥር ሥር ዋለ

 

“የቅዳሴ ሥርዓት” እየፈጸምን ነው በማለት ሲያጭበረብሩ

                                                                                                                            በእንዳለ ደምስስ

 በጥቅምቱ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በኑፋቄው ምክንያት የተወገዘው አእመረ አሸብር ከግብረ አበሮቹ ጋር በግለሰብ ቤት ውስጥ “የቅዳሴ ሥርዓት” ሲያካሔድ የካቲት ፲ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም በቁጥጥር ሥር ዋለ፡፡

 “መዳን በማንም የለም” በሚል ርእስ በ፳፻፲፩ ዓ.ም ባሳተመው የኑፋቄ መጽሐፉ በቅዱስ ሲኖዶስ ተወግዞ የተለየው አእመረ አሸብር በአርባ ምንጭ ከተማ በጫሞ ቀበሌ በግለሰብ መኖሪያ ቤት ውስጥ ከግብረ አበሮቹ ጋር ቅዳሴ እንቀድሳለን በማለት የቤተ ክርስቲያንን ንዋያተ ቅድሳት በመጠቀም ልብሰ ተክህኖ ለብሰው፣ ክክርስቶስ ሥጋና ደም ጋር የማይገናኝ ተራ ነገር በማቅረብ “ሥጋ ወደሙ” ነው በማለት፣ የመጾር መስቀል በመጠቀም “የቅዳሴ ሥርዓት” ሲያካሄዱ እንደነበር ከሥፍራው የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

     ከዓርብ የካቲት ፰ ቀን ጀምሮ እስከ እሑድ የካቲት ፲ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ጉባኤ ማዘጋጀታቸውንና ዓርብና ቅዳሜ የትምህርትና የምክክር ጉባኤ፣ እሑድ “ቅዳሴ” እናካሒዳለን በማለት ቀደም ብለው በማኅበራዊ ድረ ገጽ ላይ በለቀቁት ማስታወቂያ እንዲሁም ከተማው ላይ ማስታወቂያ በባነር አሠርተው በይፋ መስቀላቸውን የዓይን እማኞች ገልጠዋል፡፡

         የሀገረ ስብከቱ የፀረ ተሐድሶ እንቅስቃሴ ኮሚቴ፣ የአርባ ምንጭ ደ/መ/መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ፣ የስብከተ ወንጌል ኃላፊዎች እንዲሁም ኦርቶዶክሳውያን ምእመናን በመሆን ወደ ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ በመሄድ ጉዳዩን አሳውቀዋል፡፡ ብፁዕነታቸውም ቅዳሜ የካቲት ፱ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም “የቤተ ክርስቲያንን ንዋያተ ቅድሳትን ስለማስከበር” በሚል ለሚመለከታቸው አካላት ጉዳዩን ትኩረት ሰጥተው መፍትሔ እንዲፈልጉ ለአርባ ምንጭ ከተማ ፖሊስ ጽ/ቤት፣ ለአርባ ምንጭ ከተማ ፍትሕና ፀጥታ ጽ/ቤት፣ ለጋሞ ጎፋ ዞን ፍትሕና ፀጥታ ጽ/ቤት፣ ለጋሞ ጎፋ ዞን ፖሊስ መምሪያ ጽ/ቤት በደብዳቤ አሳውቀዋል፡፡

   ብፁዕነታቸው ለሚመለከታቸው አካላት በላኩት ደብዳቤም ከዚህ ቀደም በኑፋቄያቸው በሀገረ ስብከቱ ተወግዘው የተለዩ ግለሰቦች ቅዳሴ እንቀድሳለን በማለት ቤተ ክርስቲያን ላይ በማላገጥና የራሷን የሆኑትን ቅዳሴዋንና ንዋያተ ቅድሳቷንና ከራሷ ያገኙትን መዓርግ በመያዝና በመጠቀም በ፲/፮/፳፻፲፩ ዓ.ም ፕሮግራም ሊያካሔዱ ማሰባቸውን ያስረዳል፡፡ ፕሮግራም እንደሚያካሄዱም በማኅበራዊ ድረ ገጽ ላይ በመልቀቅ ምእመናንና ቤተ ክርስቲያንን ያስቆጣ ድርጊት በአርባ ምንጭ ደ/መ/መድኃኔዓለም ሰበካ ጉባኤ የቀረቡ የሕዝብ አቤቱታዎች እንደደረሳቸው የገለጹት ብፁዕነታቸው የሚመለከተው አካል ለሰላም ሲባል ትልቅ ትኩረት በመስጠት መፍትሔ ሊሰጥ ይገባዋል በማለት አሳውቀዋል፡፡

ብፁዕነታቸው በተጨማሪም በዚሁ አቤቱታቸው “የዚህች ቤተ ክርስቲያንም ሆነ የሀገረ ስብከቱ አቋም ሰላምን መስበክ ነው” ያሉት ብፁዕነታቸው ከዚህች ቤተ ክርስቲያን እስከወጡ ድረስ የቤተ ክርስቲያኒቱን መገልገያ ንብረቶች (ንዋያተ ቅድሳት) ሥርዓቷንም ሆነ ከቤተ ክርስቲያኒቱ ያገኙትን መዓርጋት ሊተዉና የራሳቸውን እምነት ሊያካሔዱ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡ የራሳቸውን ፕሮግራም ማካሔዱን እንደማይቃወሙና የቤተ ክርስቲያን የሆኑትንም ንብረቶች እና ሥርዓቶች ሊመልሱ ይገባል ብለዋል፡፡

እሑድ ጠዋት በቦታው መረጃው የደረሳቸው የሕግ አካላት ባለመገኘታቸው ከፀረ ተሐድሶ እንቅስቃሴ ኮሚቴ፣ ከሰበካ ጉባኤ እንዲሁም ከስብከተ ወንጌል የተውጣጡ አባላትና ወጣቶች እንዲሁም ምእመናን ተሰባስበው ቅዳሴ ወደሚያካሔዱበት ቤት በመሔድ ግለሰቦቹ ሲጠቀሙባቸው የነበሩትን ንዋያተ ቅድሳት እንዲመልሱ ቢጠየቁም ፈቃደኛ ባለመሆናቸው የለበሱትን ልብሰ ተክህኖ በማስወለቅ፣ ከበሮ፣ መስቀል፣ መጻሕፍትና ሌሎች ንዋያተ ቅድሳት ይዘው ወደ አርባ ምንጭ ደ/መ/መድኃኔዓለም ሲመለሱ፣ የሕግ አካላትም በመድረስ ግለሰቦቹን በቁጥጥር ሥር በማዋል ወደ ፖሊስ ጣቢያ ተወስደዋል፡፡

ሰኞ ጠዋት የችግሩን አሳሳቢነት በመግለጽ አስፈላጊና ሕጋዊ መንገድ ተከትሎ የቤተ ክርስቲያኗ ጥያቄ እንዲመለስ በማለት በብፁዕነታቸው የተጻፈው ሁለተኛ ደብዳቤ በመያዝ ለሚመለከተው አካል ቢያመለክቱም የሚመለከተው አካል ደብዳቤውን ተቀብሎ ጉዳዩ ከባድ በመሆኑ ከዞኑና ከከተማው ኃላፊዎች ጋር መመካከር አለብን በማለቱ ክስ እስካሁን አለመመሥረቱ ተገልጿል፡፡

ብፁዕ አቡነ ኤልያስ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ቅዱስ ሲኖዶስ እያከናወነ ስላለው  ጥረት ሲገልጹ “ቅዱስ ሲኖዶስ የቤተ ክርስቲያናችን መገለጫ የሆኑትን ያሬዳዊ ዜማና ንዋያተ ቅድሳት ለማስጠበቅ ውይይቶችን ሲያደርግ እንደቆየና በአሁኑ ወቅትም የአእምሮ ንብረት በሚል ኮሚቴ ተቋቁሞ በጥናት ላይ ይገኛል” ብለዋል፡፡ የጋሞ ጎፋ ሀገረ ስብከትም በቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ አማካይነት የፀረ ተሐድሶ ኮሚቴ አዋቅሮ እስከ አጥቢያ ድረስ ሥራዎችን እየሠራ እንደሚገኝ ለዝግጅት ክፍላችን ገልጠዋል፡፡

     በሕግ አካላት ቁጥጥር ሥር ውለው ከነበሩት ግለሰቦች ውስጥ አንዱ አእመረ አሸብር ሲሆን፣ ከዚህ ቀደም የሊቃውንት ጉባኤ አባል የነበረና በኑፋቄው ምክንያት የተወገዘ ግለሰብ  ነው፡፡ የካቲት ፲፩ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ጠዋት ከፖሊስ ጣቢያ እንደተለቀቁም የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡

የቤተ ክርስቲያን ንዋያተ ቅድሳት እንዲከበሩ ሀገረ ስብከቱ          ለሚመለከታቸው አካላት የጻፈው ደብዳቤ

የነነዌ ሰዎች እምነት ንስሓና የጾም አዋጅ

 

መ/ር ቢትወደድ ወርቁ

ትንቢተ ዮናስ አራት ምዕራፎች ያሉት፤ እስከ ዓለም ፍጻሜ የሚነሣ ትውልድ ሁሉ ሊማርበትና ራሱን ሊያስተካክልበት የተጻፈ ታላቅ የትንቢት መጽሐፍ ነው፡፡ በዚህ የነቢዩ ዮናስ መጽሐፍ የተጠቀሱት ነቢዩ ዮናስን ጨምሮ የነነዌ ሰዎች ፣ንጉሡ ፣ዮናስ በየዋህነት ከእግዚአብሔር ፊት ወደ ተርሴስ ሊኮበልልበት የተሳፈረበት መርከብ ባለቤቶች /መርከበኞች/ እና ሌሎች ፍጥረታት ዓሣ አንበሪው፣የባሕር ማዕበሉ፣እግዚአብሔር ነቢዩ ዮናስን ያስተማረበት ትልና ቅሉ ሁሉ የነነዌ ሰዎች በኃጢአት ምክንያት ከመጣባቸው የጥፋት ዋዜማ አንስቶ ከኃጢአት ተመልሰው መዓቱ በምሕረት ቊጣው በትዕግሥት እሰከ ተለወጠላቸውና ከቅጣቱም እስከዳኑበት ጊዜ ድረስ የነበራቸው ተግባርና እግዚአብሔር የሠራላቸው የቸርነት ሥራዎች የተገለጡበት መጽሐፍ ነው፡፡

  መጽሐፉም እያንዳንዱ ቢዘረዘር ትልቅ መጽሐፍም ሊወጣው የሚችል ከመሆኑ አንጻር ያን ወደ ቤተክርስቲያን መጥተን ሊቃውንቱንና መምህራንን በመጠየቅ እንዲሁም ሌሎች ምሥጢራትን የሚያብራሩ  ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብ መረዳት እንችላለን፡፡ አሁን ግን ባለንበት ወቅት በግላዊ፤ ቤተሰባዊና ሀገራዊ አኗኗራችን ከገባንበትና ሊገጥመን ከሚችሉ ችግሮች አንጻር የነነዌ ሰዎችን ታሪክ መስተዋት አድርገን ራሳችንን እንመለከትበት ዘንድ ታሪካቸውን በአጭሩ መቃኘትና የንስሓ መንገዳቸውን መከተል ተገቢ ይሆናል ፡፡ በመጽሐፍ ያለው ታሪክ በሙሉ የተጻፈልን ለፍጹም ትምህርትና ለበጎ ሥራ ሁሉ የተዘጋጀን እንሆን ዘንድ እንዲሁም ለተግሣጽ ልባችንንም ለማቅናት በጽድቅም ላለው ጥበብ ይጠቅማልና (፪ጢሞ ፫÷፲፮-፲፯)

                የነነዌ ሰዎች የጥፋት ዋዜማ

ለነነዌ ሰዎችና ለከተማይቱ ጥፋት ምክንያት ሊሆን የነበረው  ምን እንደነበር መጽሐፍ ሲነግረን “የእግዚአብሔር ቃል ወደ አማቴ ልጅ ወደ ዮናስ እንዲህ ሲል መጣ፤ ተነሥተህ ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፤ ክፋታቸውም ወደፊቴ ወጥቶአልና፤ በእርሷ ላይ ስበክ”(ዮናስ ፩÷፪ )ይላል፡፡ የነነዌን ከተማ “ታላቂቱ ከተማ” ያሰኛት ብልፅግናዋና እድገቷ ብቻ ሳይሆን በሥሯ የነበሩ ሰዎች ይፈጽሙ የነበረው ታላቅ ክፋት ነበር፡፡ስለዚህም የነዋሪዎቿ ክፋት እግዚአብሔርን አሳዝኖት ከክፋታቸው እንዲመለሱ የክፋት ሥራቸውን እንዲተውና ንስሓ እንዲገቡ ይነግራቸው ዘንድ ነቢዩ ዮናስን ወደ እነርሱ እንዲሄድ ላከው ፡፡ ባዕድ አምልኮትንና ጣዖትን ማስፈን፤ ለጣዖታት መስገድና መሠዋት ፣ ጥንቆላን ማስፋፋት ፣ሥር እየማሱ ቅጠል እየበጠሱ የሰዎችን አኗኗር ማጎሳቆልና ማዘበራረቅ ፣በዘፈንና አስረሽ ምችው ሰክሮ ዝሙትንና ሌሎች የሥጋ ፈቃዳትን በራስና በሌሎች ላይ ማንገሥ ነው፤ (ገላ ፭÷፲፯-፲፱)፡፡  የኃጢአት ሥራ  ከእግዚአብሔር ይልቅ ደስታና ተድላን በመውደድ ለዚያም በሰዎች መካከል ጠብን ከመዝራትና እንዲጋጩ ከማድረግ አንስቶ የራስን ጥቅም ብቻ በመመልከትም ማታለልን ሰዎች የሚጠፉበትንም መንገድ መቀየስና ለዚያም ቀንና ሌሊት በመትጋት ወደ ፍጻሜ ማድረስ ነው፤(ምሳ ፮÷፲፮-፲፱)፡፡ ክፉ ሰዎች የሚጠፉበትንና እግዚአብሔር የሚያሳዝኑበትን ሐሳብ ንግግርና ተግባራትን አጠቃሎ ይይዛል፡፡

   ክፋትንም የሚያደርግ ሁሉ በእግዚአብሔር  ዘንድ የተጠላ ነው፤ ዘዳ ፳፭÷፲፭፡፡  የነነዌ ሰዎችንም ለጥፋት ያቀረባቸውና ከተማይቱንም “በሦስት ቀን ውስጥ ትገለበጣለች” (ዮናስ ፫÷፬) እስከ መባል ያደረሳት ክፋታቸው ነው፡፡ ሰው ልቡናውን ከክፋት ካላራቀ ራሱም ይጠፋል፡፡ ክፋቱም በዙሪያው ላሉት ሁሉ ተርፎ ሌላ ጥፋትን ይወልዳል ፡፡ አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር በቀድሞው ዘመን ለእስራኤል ዘሥጋ ” ኢየሩሳሌም ሆይ ትድኚ ዘንድ ልብሽን ከክፉ ነገር እጠቢ”፤ (ኤር ፬÷፲፬ ) ማለቱም ለዚህ ነው፡፡ ዛሬም ከራሳችን አንስቶ ዙሪያችንን ስንመለከት እግሮቻችን ወደ ክፋት የሚሮጡ፤ እጆቻችንም ደምን ለማፍሰስ የሚፋጠኑና በራሳችንም የክፋት ሐሳብ እየተራቀቅን ጠቢባን ሆነናል የምንል ሰዎች በዝተናል (ምሳ ፩÷፲፮)፡፡ ልበ አምላክ ክቡር ዳዊት እንደተናገረውም “ከኃጢአታችን ተመልሰን ንስሓ ካልገባን ክፋታችን ይገድለናል”፤(መዝ ፴፫÷፳፩)፡፡ የነነዌ ሰዎች ጥፋታቸው እስኪነገራቸው ድረስ በኃጢአት ሥራ ጸንተው ይኖሩ እንደ ነበር፤ ዛሬም በክፉ ሐሳብ ንግግርና ተግባር ላይ ካለን እኛም በጥፋት ዋዜማ ላይ እንደሆን ልንረዳ ይገባናል ፡፡

                  የእግዚአብሔር ቸርነትና የንስሓ ጥሪ

የነነዌ ሰዎች በመጥፎ ምግባራቸውና ኃጢአታቸው ምክንያት ሊጠፉ ሲገባቸው የቸርነት ባለቤት አምላካችን እግዚአብሔር እንዳይጠፉ በነቢዩ ዮናስ አንደበት የቸርነቱን የንስሓ ጥሪ አሰምቷቸዋል፡፡ “ተነሥተህ ወደዚያች ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፤ የምነግርህንም ስብከት ስበክላት”(ዮናስ ፫÷፪) እንዲል፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን እኛ ከኃጢአታችን ከተመለስን ከስሕተታችን ተምረን ለመታረምና ሕይወታችንን ለማስተካከል ከፈቀድን እንደ ወጣችሁ፤ እንደ ጠፋችሁና እንደ ረከሳችሁ ቅሩ አይልም፡፡ በበደላችንና በኃጢአታችን ካሳዘነው ይልቅ በኃዘንና በጸሎት ፍጹም በሆነ ንስሓ ከተመለስን ይደሰታል፡፡ እርሱ ብቻ ሳይሆን ቅዱሳን መላእክቱም በሰማይ ይደሰታሉ፤ “ንስሓ በሚገባ በአንድ ኃጢአተኛ ምክንያት በሰማይ መላእክት ዘንድ ታላቅ ደስታ ይሆናልና”(ሉቃ ፲፭÷፲) እንደተባለ፡፡ ስለሆነም ዛሬም በገባንበት የጥፋት መንገድ ፣ ተመቻችተንና ተደላድለን እየኖርን ካለንበት የኃጢአት መንደር በመውጣት ንስሓ በመግባት ሰላማዊ አኗኗርንና መንግሥተ ሰማያትን ገንዘብ እንድናደርግ ያስተምረናል ፡፡ “ንስሓ ግቡ፤ ኃጢአትም እንቅፋት እንዳይሆንባችሁ ከኃጢአታችሁ ተመለሱ፤ የበደላችሁትን በደል ሁሉ ከእናንተ ጣሉ፤ አዲስ ልብና አዲስ መንፈስም ለእናንተ አድርጉ፤ የእስራኤል ቤት ሆይ ስለምን ትሞታላችሁ ? የሟቹን ሞት አልፈቅድምና ይላል ጌታ እግዚአብሔር፤ ስለዚህ ተመለሱና በሕይወት ኑሩ” (ሕዝ ፲፰÷፴-፴፪ )እንዲል፡፡ዛሬም ቢሆን በኃጢአት እየኖርን የሚታገሠን ንስሓ እንድንገባ ነው፤ (፪ጴጥ ፫÷፱) ንስሓ ካልገባንም ቅጣት መምጣቱ የማይቀር መሆኑን ልብ ማለት ይገባናል፤(ሮሜ ፲፩÷፳፪)፡፡

የነነዌ ሰዎች መመለስ

የነነዌ ሰዎች ንስሓ እንደማይገቡና በልባቸው ትዕቢት ሞልቶ፤ ከጀመረ ይጨርሰኝ ካፈርኩ አይመልሰኝ፤ብለው በበደላቸው ጸንተው እንደሚኖሩ ሰዎች አልሆኑም ፡፡ ኃጢአታቸውና በደላቸው እንዲሁም ንስሓ ካልገቡ ሊመጣ ያለው ጥፋት ሲነገራቸው በዙፋን ካለው ንጉሥ በዐደባባይ እስካለው ችግረኛ ሁሉም በአንድነት ሆነው ነቢዩ ዮናስ የሰበከውን የንስሓ ስብከት በልቡናቸው አምነው ተቀበሉ፡፡ ማመናቸውንም ከንጉሣቸው ጋር በመሆን ለጾም አዋጅ በመንገር ገለጡ፡፡ እምነታቸውንና ጾማቸውንም በንስሓ አጅበው አለቀሱ፡፡በዚህም እግዚአብሔር ቊጣውን በትዕግሥት መዓቱን በምሕረት ለወጠላቸው ፡፡

 “የነነዌ ሰዎችም እግዚአብሔርን አመኑ፤ ለጾም አዋጅ ነገሩ፤ ከታላቁ ጀምሮ እስከ ታናሹ ድረስ ማቅ ለበሱ፤ንጉሡም ከዙፋኑ ተነሥቶ መጎናጸፊያውን አውልቆ ማቅም ለበሰ፤ በአመድም ላይ ተቀመጠ” (ዮናሰ ፫÷፭-፮) ተብሎ እንደ ተነገረ፡፡ ኃጢአታቸውን አምነው ንስሓ በማይገቡ ሰዎች እግዚአብሔር “የወደቁ አይነሡምን ? የሳተስ አይመለስምን ? ምን አድርጌሃለው ብሎ ከኃጢአቱ ንስሓ የገባ የለም …”(ኤር ፰÷፬) በማለት ይገረማል፤ ይደነቃልም፡፡ የነነዌ ሰዎች ግን በእምነታቸው፤በንስሓቸውና በጾማቸው እግዚአብሔርን አስደሰቱት፡፡ በዚህም በሐዲስ ኪዳን አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ንስሓ በማይገቡ ላይ እንደሚፈርዱ ሲመሠክርላቸው “የነነዌ ሰዎች በፍርድ ቀን ከዚህ ትውልድ ጋር ተነሥተው ይፈርዱበታል፤ በዮናስ ስብከት ንስሓ ገብተዋልና ብሏል”፤ (ማቴ ፲፪÷፵፩)፡፡ ስለሆነም ከጥፋት እንድንድን ከክፉ ሐሳባችን፤ ንግግራችንና ተግባራችን ተመልሰን ንስሓ እንግባ ፡፡ “የንስሓ ኃዘን መዳንን፤ የዓለምም ኃዘን ሞትን ያመጣልና”፤(፩ ቆሮ ፯÷፲) እምነትን፤ ንስሓንና እውነተኛ ጾምን ገንዘብ አድርገን ለክብር ለመብቃት እንድንችል እግዚአብሔር በቸርነቱ ይርዳን፤ እመቤታችንም በምልጃዋ፤ ቅዱሳንም ሁሉ በጸሎታቸው አይለዩን አሜን!!

ከኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥርዓት ጋር የሚጻረር የሥልጣኔ ተጽእኖ

በሕይወት ሳልለው

የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሥነ ምግባርን፤ ጥበብን፤ ጽሕፈትን፤ ሥነ ጥበብንና ኪነ ሕንፃን የምታስተምር፤ አንድነትን፤ ፍቅርን እና መተሳሰብን የምትሰብክና ምእመናን ሰብስባ የምትይዝ የክርስቶስ ቤት ናት፡፡

ከጥንት ጀምሮ ቤተ ክርስቲያን የሀገር መሪም ነበረች፡፡ ልጆቿንም በሥርዓት ታሳድግና ታስተምር ነበር፡፡ ነገሥታት በቤተ ክርስቲያን ሕግ በሚመሩበት ወቅት ዜጎቿም በሥነ ምግባር የታነፁ ነበሩ፡፡ የአክሱምና የጎንደር ዘመነ መንግሥትን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ከዚያን ዘመን ጀምሮም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ወደ ውጭ ሀገራትም ተስፋፍታለች፡፡

ከጥቂት ዓመታት በፊት የቤተ ክርስቲያን ቀኖና እና ትውፊት ያልሆኑ ሥርዓቶች  በተለይም የበዓላት አከባበርና የክርስቲያናዊ አለባበስ ላይ ሥልጣኔ ተፅዕኖ አሳድሯል፡፡ ለምሳሌ የልደት በዓል አከባበር መቀየር ከጀመረ ሰነባብቷል፡፡ የምዕራባውያን ተፅእኖ ካሳደረው የአመለካከት ለውጥ የተነሣ ያልተለመዱ ምግባሮችን ከፈረንጆች በመውረስ ከክርስትና ጋር የሚጻረር ሥርዓት መከተል የጀመሩ ብዙዎች ናቸው፡፡ የገና ዛፍ በሚል ስያሜ፤ ፅድ መሰል ሰው ሰራሽ ዛፍ በማስጌጥ አላስፈላጊ ክብር እየሰጡ፤ እንዲሁም ክርስቲያናዊ ምግባሮችን በመዘንጋት አብዛኛውን ጊዜ ትኩረታቸውን የቴክኖሎጂ ምርቶች ላይ በማድረግ ግለኝነትና እራስ ወዳድነትን በመላበስ ከቤተሰብ ፍቅርና ከቀኖናዊ ሕይወት የራቁ በርካቶች አሉ፡፡ ከገና በዓል አከባባር ጋር ተያይዞም ከምዕራባውያን  የወሰዱትን ልምድ ማለትም፤ የገና አባትን በመምሰልና ለሕፃናት ማጫወቻ በአሻንጉሊት መልክ በመሥራት አላስፈላጊ ወጪ ከማውጣታቸው ባሻገር የእኛን ሥርዓት እንደሚበርዝ ባለማስተዋል የተሳሳተ መንገድ ይከተላሉ፡፡

የአለባበስ ሥርዓትን ስንመለከት ሥነምግባርን የሚገልፅ በመሆኑ ከክርስቲያናዊ አለባበስ ውጪ ከሆነ ሰውነትን የሚያዋርድ ይሆናል፡፡ የሰው ልጅ በክብሩ በገነት ሲኖር፤ ልብሰ ብርሃንን /የፀጋ ልብሱን/ ሲገፈፍበትና ራቁቱን መሆኑን ሲያውቅ ሰውነቱን ለመሸፈን ቅጠል ለብሷል፡፡ ሥልጣኔ ራቁት የሚያስኬድ ከሆነ የሰውን ልጅ ክብር ይገፋል፡፡ ክርስቲያናዊ አለባበስን የሚጻረር ልብስ፤ (ሴቶች  እኅቶቻችን የተቦጫጨቀ ሱሪ፤ ከጡታቸው በታች የሆነ ልብስ ሲያደርጉ፤ ወንዶች ደግሞ ሱርያቸውን መቀመጫቸው እስኪታይ ድረስ ወደታች በጣም ዝቅ አድርገው) ይለብሳሉ፡፡ ይህ ቤተ ክርስቲያንንና ትምህርተ ሃይማኖትን አለማወቅም ጭምር ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን ያስተማረችን ሰውነትን የሚሸፍን፤ ረጅም ቀሚስ እና ነጠላ መልበስ ነው፡፡ ሴቶች አንዳንድ ጊዜ በጣም አጭር ነጠላ በመልበስ ቤተ ክርስቲያን ሲደርሱ ከግራና ቀኝ ትከሻቸው ላይ ለመልበስ በሚሞክሩ ጊዜ ስለማይበቃቸው ሲጨናነቁ እናያለን፡፡ ወንድ የሴት፤ ሴት ደግሞ የወንድን ልብስ ማድረግ ሕጉ ይከለክላል፤ (ዘዳ ፳፪-፭)፡፡ ካህናትም ይህንን ተግባር ላይ ለማዋል በቤተ ክርስቲያን ከራሳቸው ጀምሮ የአለባበስ ሥርዓትን መጠበቅ፤ ሌሎችንም ማስተማር፤ማሳወቅና መገሰፅ አለባቸው፡፡ ትውልዱ ከግማሽ ወደሙሉ ራቁትነት ከመሻጋገሩ በፊት ማስተማር ይገባል፡፡

የማስተማር ኃላፊነት የአለባቸው የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት መሪዎች፤ የቤተ ክርስቲያን  አገልጋዮች እንዲሁም ወላጆችና ቤተስቦቻቸው ናቸው፡፡ በልጆችና ወጣቶች ምግባረ ብልሹነት ተጠያቂ በመሆናቸው መገሰፅ፤ ማስተማርና ትክክለኛውን ሕግ ማሳወቅ ያስፈልጋል፡፡

ወደ ቅደስት ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዳሴ ለማስቀደስና ጉባኤ ለመካፈል ሲመጡ ክርስቲያናዊ አለባባስ መልበስ እንዳለባቸው ማስተማር ይጠበቅባቸዋል፡፡ ነገር ግን ካህናቱም ቢሆን ደፍረው አይገስፁም፡፡ በዚህም የተነሣ አንዳንድ የነፍስ ልጆች የሌላቸው ካህናት እንዲሁም የንስሐ አባት የሌላቸው ክርስቲያኖች ኃላፊነታቸውን ለመወጣት አልቻሉም፡፡ እውነቱን መንገር ግን ያስፈልጋል፡፡ መጽሐፉ “ሕዝቤ ዕውቀት በማጣቱ ጠፍቷል” ይላል (ሆሳዕ ፬፥፮)፡፡

የአለባበስ ሥርዓትን ለማስተካካል ኃላፊነት ያለባቸው የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ብቻ ሳይሆኑ ወላጀችም ጭምር በመሆናቸው ሕገ ቤተ ክርስቲያን የሚፈቅደውን የአለባበስ ሥርዓት ለልጆቻቸው ማስተማር ይጠበቅባቸዋል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም የመንፈስ ቅዱስ ልጁን ጢሞቴዎስን አርአያ እንዲሆን መክሮታል፤ (፩ኛጢሞ ፬፥፲፪)፡፡

የሩቅ ምሥራቅ ግንኙነት ጣቢያ በህንድ ሀገር ፭ተኛ ዙር ሐዊረ ሕይወት አደረገ

         ሕይወት ሳልለው

 

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን፣ በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ  የማኅበረ ቅዱሳን የሩቅ ምሥራቅ ግንኙነት ጣብያ በህንድ ሀገር የሚኖሩ አባላቱንና ምእመናንን በማስተባበር ከጥር ፲፭ እስከ ጥር ፳፩ ቀን  ፳፻፲፩ ዓ/ም ወደ ኬሬላ ፭ተኛውን ዙር የሐዊረ ሕይወት ጉዞ አካሄደ፡፡

በአባ ጂኦ ዮሴፍ መሪነት ፺፱ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታዮች መንፈሳዊ ጉዞ አድርገዋል፡፡ በህንድ ኬሬላ ግዛት ኮታይም ከተማ ወስጥ በሚገኙ ቅዱስ ጊዮርጊስና የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን  ማርታ ማርያም ኦርቶዶክስ ሴርያን ቤተ ክርስቲያን፣ የመነኮሳት ገዳም፣ ማር ባስልዮስ ገዳም እንዲሁም የኦርቶዶክስ ቲኦሎጂካል (ነገር መለኮት) ሴሚናሪ እና የማር ባስልዮስ ክርስቲያን የኢንጅነሪንግና ቴክኖሎጅ ኮሌጅንም በዋነኛነት ጎብኝተዋል፡፡

ኮትያም ወደሚገኘው ኦርቶዶክስ መንፈሳዊ ኮሌጅ በተደረገው ጉዞ ላይ ለምእመናኑ፤ “የቤተ ክርስቲያን ምሥጢራት” በሚል ርእስ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ከህንድ ቤተ ክርስቲያን ጋር ያነጻጸረ ትምህርት በዶ/ር ረጂ ማቲው ተሰጥቷል :: በዚሁ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በተማሪዎች የበገና መዝሙርና በህንዳውያን ዘማሪዎች በህንድ ቋንቋ የተዘጋጀ መዝሙር በጋራ ቀርቧል፡፡ በጉዞው ላይ የነበሩት አባ ኦ ቶማስም “የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በባህልና በበርካታ ንዋያተ ቅድሳት የታጀበች ናት” ሲሉ አድነቀዋል፡፡  በሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ የተመሠረተችው ዘቫላካራ ማርታ ማርያም ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በቀድሞው የኢትዮጵያ ፓትርያርክ አቡነ ጳውሎስ እንደተጎበኘ አባ ጂኦ ለምእመናኑ አስታውቀዋል፡፡፡፡

ከማእከሉ በአውቶብስ ሦስት ሰዓት፤ በጀልባ አንድ ሰዓት ተኩል የሚፈጀው እና በደሴት ወደተከበበው የቅዱስ ቶማስ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ጉዞም ያደረጉ ሲሆን ቤተ ክርስቲያኗ በቁጥር ትንሽ አባላት እና ጥቂት አገልጋይ እንዳሏትም አስገንዝቧቸዋል፤ ከዚህ ባሻገር በቅዱስ ቶማስ የተመሠረተችው የቅድስት ማርያም ቤተ ክርስቲያን ውስጥ በወቅቱ ሲጠቀሙበት የነበሩት ባህላዊ ቅርሶችና ንዋየ ቅድሳትን ጎብኝተዋል፡፡ የጉዞው ተሳታፊዎችም “ከቦታው በረከትን አግተኝናል” ሲሉም የምስክርነታቸውን ቀል ሰጥተዋል፡፡

በከበሮ፣ በጸናጽል፣ በመቋሚያና በበገና ህብር የቀረበው ያሬዳዊ ዝማሬ መርሐ ግብር ላይ ሰፊ ማብራሪያ የሰጠው መ/ር ሳምሶን ስለመሳሪያዎቹ ለህንድ አባቶችና ለምእመናን ገለጻ አድርጓል፡፡ ስለአጠቃላይ መርሐግብሩ ከተሳታፊዎች ሐሳብ ተሰብስቦ፣ የአጋጠማቸው ችግሮች ላይ ውይይት በማድርግና የመፍተሔ አቅጣጫ በመስጠት፣ ፭ተኛው ዙር ሐዊረ ሕይወት  በሰላም ተጠናቋል፡፡

 

 

በገጠሪቱ ኢትዮጵያ ለስብከተ ወንጌል የሚሰማሩ ሰባክያነ ወንጌል ተመረቁ

 

                               ተመራቂዎች በከፊል

በእንዳለ ደምስስ

  በማኅበረ ቅዱሳን አዳማ ማእከል ሥር የሚገኘው የደብረ ዘይት ወረዳ ማእከል ከአዳአ ወረዳ ቤተ ክህነት፤ ከበጎ አድራጊ ምእመናንና ማኀበራት ጋር በመተባበር በሁለተኛ ዙር ገጠር ተኮር የስብከተ ወንጌል አገልግሎትን ለማጠናከር በአፋን ኦሮሞ ቋንቋ ለ፰ ወራት በሂዲ ቅዱስ ጊዮርጊስ ወካህን መልከ ጼዲቅ አብያተ ክርስቲያናት ያሰለጠናቸውን ፴፬ ተተኪ ሰባክያነ ወንጌል ጥር ፭ ቀን ፳፻፲ወ፩ ዓ.ም የአድአ ወረዳ ቤተ ክህነት ሊቀ ካህን፤የየአጥቢያዎቹ አስተዳዳሪዎች፣ በጎ አድራጊ ምእመናንና የደብረ ዘይት ወረዳ ማእከል አባላት በተገኙበት አስመረቀ፡፡

ሰልጣኞቹ ከ፲ አጥቢያዎች የተመለመሉ ሲሆን፣፱ የትምህርት አይነቶችን ሲከታተሉ መቆየታቸውን፣አብዛኛዎቹ ሰልጣኞችም ካህናትና ዲያቆናት መሆናቸው አቶ ሀብታሙ ዘውዱ የወረዳ ማእከሉ ሰብሳቢ በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ ባቀረቡት ሪፖርት ገልጸዋል፡፡ካህናቱና ዲያቆናቱ የስብከተ ወንጌል አገልግሎት ስልጠናውን መውሰዳቸውም ለወደፊቱ ከስብከተ ወንጌል አገልግሎት በተጨማሪ የቤተ የመቅደስ አገልግሎትን ለማጠናከር መልካም አጋጣሚ እንደሆነና አብያተ ክርስቲያናቱም ለሥልጠና የሚሆኑ ቦታዎችን በማመቻቸት የነበራቸው ተሳትፎ ታላቅ እንደነበር ጠቅሰዋል፡፡

“የሥልጠናው ዋና ዓላማ ምእመናን በሚያውቁት ቋንቋ በማስተማር ከነጣቂ ተኲላዎች ለመጠበቅ ነው፡፡ የሥልጠናው ሙሉ ወጪም ብር 123,348.90 (አንድ መቶ ሀያ ሦስት ሺህ ሦስት መቶ ዐርባ ስምንትብር ከዘጠና ሳንቲም) በባሕር ዳር ዩኒቨርስቲ የቀድሞ ግቢ ጉባኤ ተመራቂዎች የተሸፈነ ነው” ብለዋል፡፡ የቀድሞ ተመራቂዎቹ ያበረከቱት አስተዋጽኦ በአርአያነት የሚጠቀስ መሆኑን የጠቆሙት ሰብሳቢው ይህንን መልካም ተሞክሮ ሌሎችም ማኀበራት በመውሰድ ሊማሩበት እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡

ለተመራቂዎቹ ባስተላለፉት መልእክትም “ሰልጣኞች ከምረቃ በኋላ ትምህርት በቃን ሳትሉ ከሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን እግር ሥር  ቁጭ ብላችሁ መማር፣ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብ ይገባችኋል፡፡ ዋናው ዓላማችሁንም ባለመዘንጋት ስብከተ ወንጌል ባልተስፋፋባቸው ቦታዎች እየተዘዋወራችሁ ቤተ ክርስቲያን የጣለችባችሁን ኃላፊነት እንድትወጡ ይጠበቅባችኋል” በማለት በሪፖርታቸው አስገንዝበዋል፡፡

የደብረ ዘይት ወረዳ ማእከል አባላት ከግልና ከማኀበራዊ ጉዳያቸው ቅድሚያ ለሥልጠናው ልዩ ትኩረት መስጠታቸው፣ የአዳአ ወረዳ ቤተ ክህነት ለአገልግሎት የሚያስፈልጉ ነገሮችን በማሟላትና ለአጥቢያዎች መመሪያ በመስጠት ስልጠናው የተሳካ እንዲሆን ታላቅ አስተዋጽዖ ማበርከታቸውን በመግለጽ ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

የወረዳ ቤተ ክህነቱ ሊቀ ካህን መልአከ ፀሐይ ቀሲስ እንዳለ ሐረገወይን ባስተላለፉት መልእክትም የወረዳ ማእከሉ ለስበከተ ወንጌል አገልግሎት መስፋፋት የሚሰጠውን አገልግሎት አጠናክሮ መቀጠል እንዳለበት ያሳሰቡ ሲሆን ለተመራቂዎችም “በቋንቋ ምክንያት የሚጠፋውን ትውልድ ከሞት ወደ ሕይወት የመመለስ አደራ አለባችሁ” ብለዋል፡፡

የደብረ ዘይት ወረዳ ማእከል ከአድአ ወረዳ ቤተ ክህነት፣ ከበጎ አድራጊ ምእመናንና ማኅበራት ጋር በመተባበር በአፋን ኦሮሞ ቋንቋ ተተኪ ሰባኪያነ ወንጌል ለማፍራት ፕሮጀክት ቀርጾ በመጀመሪያው ዙር በድሬ መድኃኔዓለም ቤተ ክርስቲያን ከ፰ አጥቢያዎች የተመለመሉትን ፳፫ ሰልጣኞችን ለስምንት ወራት አሰልጥኖ የካቲት ፳፭ ቀን ፳፻፲ ዓ.ም በአባቶች ቡራኬ አስመርቋል፡፡

ምንጭ፤ምዐ ጽድቅ ጋዜጣ 26ኛ ዓመት ቊ8ቅጽ 26ኛ ቊጥር 398 ከጥር 1-15 ቀን2011ዓ.ም

 

 

 

የምእመናን ተሳትፎ የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት የጠበቀ ሊሆን ይገባዋል

                     

በሕይወት ሳልለው

የሰው ልጅ ሕይወት፤ድኀነት፤ሰላም፤ ፍቅርና ደስታ መገኛ እግዚአብሔር፤ ከሕገ ኦሪት ጀምሮ በሰጠን የድኀነት መንገድ፤ በመስቀሉ ላይም በከፈለልን መሥዋዕትነት የተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፤ከጥንት ጀምሮ ምእመናንን በመሰብሰብና በማሰተባበር ሥርዓተ አምልኮን እንዲፈጽሙ ስታስተምር ኖራለች፡፡ በሕገ ወንጌልም አምላካችን በአስተማረን መሠረት የክርስቲያኖች መማፀኛ የሆነችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፤ልጆቿን በፍቅርና በሥርዓት እንድታሳድግ ፈቅዷልና በእምነት፤ እንድናከብራት የእግዚአብሔር  ፈቃድ ነው፡፡

 “በብሉይ ኪዳን ይኖሩ የነበሩ ምእመናን በሕገ ልቦና (ባልተጻፈ ሕግ) ይመሩ የነበሩ አበው እና በሕገ ኦሪት (በተጻፈ ሕግ) የነበሩ ቅዱሳን አባቶች አካሄዳቸውን ከእግዚአብሔር ጋር በማድረጋቸው የእግዚአብሔር ረድኤት ያልተለያቸው ነበሩ፡፡የሐዲስ ኪዳንን ስንመለከት “በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የባሕር አምላክነት አምነው፤ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የተጠመቁ ክርስቲያኖች ናቸው”፤ (የምእመናን ድርሻ በቤተ ክርስቲያን)፡፡

 አንድ አምላክ፤አንዲት ጥምቀት፤ አንዲት ሃይማኖት፤(ኤፌ4፥4) ይህን የክርስትና ሕይወት መርሕ መሠረት አድርገው የሚኖሩ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታዮች፤ ለብዙ ዓመታት  ሥርዓተ አምልኮን በሚፈጽሙባት ቤተ ክርስቲያን፤ ከሃይማኖት አባቶች፤ ከካህናት፤ እንዲሁም ከሌሎች አገልጋዮች ጋር የሚያደርጉት ሱታፌ እምነታችውን፤ሥርዓታቸውንና አምልኮታቸውን ለማጠንከር ይረዳልና፤ በሕገ ቤተ ክርስቲያን መኖር ያስፈልጋል፡፡ አብዛኞቹ  ኦርቶዶክሳውያን  ምእመናን  ዓመታዊ ክብረ በዓላት ላይ ብቻ ነው፡፡

መንክር መኩሪያና ዳዊት ጌታቸው ጥር ፲፩ ቀን ፳፻፲፩ የጥምቀት በዓልን በጃንሜዳ ሲያከብሩ ያገኘናቸው ወጣቶች ናቸው፡፡መንክር ጥምቀትን ከልጅነት ጀምሮ ስለሚያከብር በየዓመቱ ጃንሜዳ ይመጣል፡፡“በዘንድሮ በዓል በበገናውና መሲንቆ፤በመዘምራንንና መዝሙሮች የቀደመውን ሥርዓት የበለጠ ወድጄዋለው፡፡አገልጋዩቹም ባሕልና ትውፊታቸንን ይዘው በመቅረባቸው እናመሰግናቸዋለን”፡፡

 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ትውፊት፤ሥርዓትና፤ቀኖና በዓላትን ከማክበር በተጨማሪ የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት በተገቢው የመፈጸም ኃላፊነት እንዳለብን ያስታውሰናል፡፡ ወጣት  መንክር “አንዳአንድ የአስተዳዳር ችግር በመኖሩ ቅር ብሎኛል፡፡ካህናት እንዲሁም ሌሎች አገልጋዩች እኛን ሰብስበው አልያዙንም ከዘመኑ ጋር የመራመድ መሠረታዊ ችግር አለ፡፡ በዓልን ለማክበር ብቻ መገናኘት በቂ  አይደለም፡፡ የሃይማኖት አባቶች በጎቻቸውን  ተግተው መጠበቅ ይኖርባቸዋል”፤ሲል ቅሬታውን ገልጿል፡፡ዳዊትም ይህንን ሀሳብ በመጋራት “የአከባበር ሥርዓቱ ደስ ቢልም፤ የካህናትና የምእመናንን ኅብር ለበዓል ብቻ መሆን የለበትም፡፡ካህናት የሰንበት ትምህርት ቤቶችን ማበረታታና ድጋፍ መስጠት አለባቸው”፡፡ ብሏል

አስተባባሪዎችና ሌሎች የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች አስፈላጊውን አገልግሎት በበዓላት ቀንና በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በወቀቱ እንደሚሰጡ ቢታመንም፤እነዚህ ችግሮች ሊከሰቱ የቻሉት በአስተዳደር ችግር መሆኑን እንደ መንክር ያሉ ግለሰቦች ይናገራሉ፡፡

 የቅዱስ ጳውሎስ የሐዲስ ኪዳን መምህር መጋቤ ሐዲስ አእምሮ ደምሴ ስለዚህ ጉዳይ አነጋግረናቸው ነበር፡፡ እሳቸውም “ጉድለቶች አይጠፉም፡ የምእመናን ሱታፌ ለመጨመር ሁሉም የየድርሻቸውን መወጣት አለበት፡፡የካህናቱ ድርሻ መቀደስ፤ ማስተማርና  እና መዘመር በመሆኑ ከምእመናኑ ጋር ኅብር ለመፍጠር የሚቻለው ምእመናን የምስጋናንና፤የመዘመርን ሥርዓት ሲያዘወትሩ ነው” ይላሉ፡፡ሆኖም ግን ትምህርተ ሃይማኖትን በበቂ ሁኔታ አለመማርና አለመተግበር በወጣቱ ላይ ያመጣው አሉታዊ ተፅእኖ እንዳለም ጨምረው ገልጸዋል፡፡ በማኀበር የተደራጁ ወጣቶች ስሕተት መሆኑን ባለመረዳት ቅዱሳት ሥዕላትን ባልሆነ ቦታ ላይ የሚለጥፉና ለማስዋቢያ የሚጠቀሙ እንዳሉም ታይቷል፡፡ነገር ግን እነዚያ ቅዱሳት ሥዕላት በክብር ቦታቸው ሆነው የሚጸለይባቸው ስለሆኑ ተገቢ ባልሆነ ስፍራ መታየት እንደሌለባቸው በአጽንዖት አሳስበዋል፡፡

 “በቲሸርትና ሌሎች አልባሳት ላይ ቅዱሳት ሥዕላትን ማሳተም ትክክል አይደለም፡፡ ምክንያቱም ልብሱ ሊቆሽሽ፤ሊቀደድና ሊጣል ይችላል፡፡እነዚያ ሥዕሎች ቅዱስ በመሆናቸው ለበረከት ብለን የምናደርገው ወደ መርገም እንዳይለወጥብን ለቅዱሳት ሥዕላት ጥንቃቄ ማድረግ አለብን፡፡የምናገለግለውንም አገልግሎት ያደበዝዝብናል፡፡ሌሎች ጹሑፎችን መጻፍ ለምሳሌ የእንኳን አደረሳችሁ መልእክትን ማስተላለፍ ይቻላል” ይህ የግንዛቤ እጥረት የፈጠረው ችግር ለምእመናን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት  ሥርዓትና ትውፊት እንዳልሆነ ማስረዳት ይገባል፡፡እነዚህንም ወጣቶች ከስሕተት ለመመለስ የሃይማኖት መሪዎች የማስተማርና የመምከር ከባድ  ኃላፊነት አለባቸው፡፡

በሌላ በኩል ግን መጋቤ ሐዲስ  አእምሮ የበዓል አከባባር ላይ ወጣቶች ቤተ ክርስቲያን የማገልገል ሥራ በራሳቸው ተነሳሽነትና ለበረከትም የሚያደርጉትን ተግባር ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የጠበቀ እንዲሆን በማስገንዘብ፤ በዐበይት በዓላት አከባባር ላይ ከአዲስ አበባ ጅምሮ እስከ ገጠር ቤተ ክርስቲያን ድረስ ወጣቱ የሚሰጠው አገልግሎት በአስተማሪነቱ የሚወሰድ መልካም ተግባር ነው፡፡ታቦታት ወደ ማደሪያቸው ከመድረሳቸው አስቀድመው አካባቢውን በማጽዳት፤ ሕዝቡን በመቀስቀስ፤ታቦታቱ የሚያርፉበትንና የሚጓዙበትን መንገድ በማስዋብ፤ ምንጣፍ በማንጠፍና ቄጤማ በመጎዝጎዝ፤ አቧራንና ድካምን ችለው ሲያገለግሉ ይውላሉ” ሲሉ የወጣቶችን ተሳትፎ በአድናቆት ይገልጹታል፡፡

ከማኅበረ ቅዱሳን የተሰጠ ወቅታዊ መግለጫ፡፡

በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሀዱ አምላክ አሜን፡፡

ጥር  17 ቀን  2011 ዓ.ም

እንግዲህ እንደ ባለ አእምሮ አስቡ፡፡ / 1ኛ ጴጥ 4፤7/

በማንኛውም የሰው ልጅ ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶችንና ግድያዎችን ሁሉ እናወግዛለን፡፡  በየቦታው የተከሰቱ ችግሮች እንዲቆሙም በድርጊቱ የሚሳተፉ አካላትን ሁሉ እንማጸናለን፤  እናሳስባለንም፡፡ ማኅበረ ቅዱሳን

የክርስትና ሃይማኖት ማእከላዊ ጉዳዩ ሰው ነው፡፡ አምላክ ሰው ሆነ፣፤ ሰውም አምላክ ሆነ፣ የሚለው የትምህርቱ አስኳል ዋና ነጥብም የሚያመለክተው የነገራችን ሁሉ ማእከል ሰው መሆኑን ነው፡፡ ይህም ለሰው ሲባል አምላክ እንኳ ራሱን ዝቅ አድርጎ በተዋሕዶ ሰው ሆኖ መገለጡንና በዚሀም ሰውን ከወደቀበት ማንሣቱን፤  ከዚያም በላይ ሰውን በተዋሕዶ ለአምላክነት ክብር ማብቃቱን የሚገልጽ ትምህርት ነው፡፡ ስለዚህ  ሀገራዊ ብቻ ሳይሆን ዐለምአቀፋዊ ሆነው በትልቁ የሚከበሩት የአምላካችን ልደት፣ ጥምቀት፣ ስቅለት፣ ትንሣኤና ዕርገት ሁሉ ማእከላዊ ነጥባቸው ሰው ነው፡፡ ሁሉም ነገሮች አምላክ ለሰው ሲባል ያደረጋቸው ናቸውና፡፡

ሌሎች አስተምህሮዎች ሁሉ አሁንም ሰውን ለማስረዳት ሲባል የተለያዩ አርእስት ይሰጣቸው እንጂ ማእከላዊ ነጥባቸው አንድ ነው፤ የሰው ድኅነትና ደኅንነት፡፡ የአንድ ሰው ጽድቁም ኃጢአቱም የሚለካው ለሰው በሚያደርገው ወይም በሰው ላይ በሚያደርገው ነው ማለት ይቻላል፡፡ ስለዚህም በምድር ላይ ከሰው በላይ የከበረና ጥንቃቄ ሊደረግለት የሚገባው ምንም ፍጥረት የለም፡፡ በምድር ላይ ጥንቃቄና ዕርምት የሚወሰድበት ነገር ሁሉ የመጨረሻ ዓላማው ሰውን ለመጥቀም ነው፡፡ ከዚህም የተነሣ ከሰው የሚጣላ ከአምላኩም ከአጠቃላይ ከፍጡራንም ሁሉ ጋር የሚጣላ ይሆናል፡፡ በሰው ላይ ያልተገባውን ድርጊት የሚፈጽም ሁሉ በፈጣሪው ላይ የሚያደርግ መሆኑን መዘንጋት የለበትም፤ ፈጣሪ ሰው መሆንን በተዋሕዶ ገንዘብ አድርጎ ሰው ሆኖ ተገልጧልና በሰው የሚደረግ ሁሉ በእርሱ ላይ የሚደረግ መሆኑ የታወቀ ነው፡፡

የክርስትና ሃይማኖት መምህራንና ተቋማት ዋና ዐላማና ተልእኮም ሊመነጭ የሚችለው ከዚህ መሠረታዊ የሰው ክብርና ዋጋ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ስለዚህ በየትኛውም የዓለም ክፍል በማንኛውም ሰው ላይ የሚፈጸሙ መጥፎ ተግባራት ይልቁንም ከሕግ ማሕቀፍ የወጡትንና በሴራና በተንኮል የሚፈጸሙትን እንደ ማኅበር አብዝተን እናወግዛቸዋለን፤ እንጸየፋቸዋለንም፡፡ ይልቁንም በሀገራችን በኢትዮጵያ ከዕለት ወደ ዕለት እየጨመረ የመጣው ንጹሐንን ሰለባ እያደረገ ያለው የተቀነባበረና የተነጣጠረ የሚመስለው ጥቃት በእጅጉ የሚያሳስብ መሆኑ ለማንም የተሰወረ አይደለም፡፡

Read more