‹‹ሰላም ለኒቆዲሞስ ለወልደ ማርያም ዘአምኖ››

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዚያ 5/2011 ዓ.ም.
በቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓት፣ ከዐቢይ ጾም ሳምንታት መካከል ሰባተኛው ሳምንት በኒቆዲሞስ ተሰይሟል፡፡ ሳምንቱ በስሙ ከመጠራቱም ባሻገር በቤተ ክርስቲያን የሚቀርበው ትምህርትም ኒቆዲሞስ ከጌታ የተማረዉን ምሥጢረ ጥምቀት መሠረት ያደረገ ነው፡፡ ይኸውም የሰው ልጅ የእግዚአብሔርን መንግሥት ለመውረስ ከውኃ እና ከመንፈስ ቅዱስ መወለድ እንደሚገባው ያትታትል፡፡ ቅዱስ ማርቆስ በወንጌሉ ምዕራፍ ፲፮ ቍጥር ፲፮ ላይ ‹‹ያመነ፣ የተጠመቀ ይድናል፤ ያላመነ፣ ያልተጠመቀ ግን ይፈረድበታል፤›› በማለት ያስተማረው ትምህርትም ከዚህ መልእክት ጋር የሚስማማ ነው፡፡ Read more

ገብር ኄር

መምህር ሶምሶን ወርቁ

የዐቢይ ጾም ስድስተኛ ሳምንት ገብር ኄር የተሰየመው በቅዱስ ያሬድ ነው፡፡ በዚህ ሳምንት ለሰው ሁሉ የማገልገያ ጸጋ መሰጠቱን፣ ሰጪው እግዚአብሔር አምላክ መሆኑን፣ ቅን አገልጋዮች ስለሚቀበሉት ዋጋ ፣ ሰነፍ አገልጋዮች ስለሚጠብቃቸው ፍርድ ይሰበካል፡፡ «ገብር ኄር ወገብር ምእመን ዘአሥመሮ ለእግዚኡ፤ ጌታውን ያስደሰተው አገልጋይ ታማኝና ቸር አገልጋይ ነው፤መኑ ውእቱ ገብር ኄር፤ ቸር አገልጋይ ማን ነው?» እያሉ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ይዘምራሉ፤ በቅዳሴው ደግሞ የማቴዎስ ወንጌል ፳፭፤፲፬-፴ ይነበባል።

. የምሳሌው ትርጉም

የመክሊቱ ባለቤት አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፤ ባለ አምስት፤ ባለ ሁለትና ባለ አንድ መክሊት የተቀበሉት በጥምቀት ጸጋ መንፈስ ቅዱስን የተቀበሉ፤ተምረው የሚያስተምሩ መምህራን ናቸው፡፡ የስጦታው መለያየት መበላለጥን ለማሳየት ሳይሆን የአንዱ ጸጋ ከሌላው እንደሚለይ የሚያጠይቅ ነው፤ «መንፈስ ቅዱስ አንድ ሲሆን ስጦታው ልዩ   ልዩ ነው፡፡ ጌታም አንድ ሲሆን ልዩ ልዩ አገልግሎቶች አሉ» ፩ቆሮ ፲፪፥ ፬፡፡

ባለ አምስትና ባለ ሁለት መክሊት የተባሉት አገልጋዮች ቃለ እግዚአብሔርን ከተማሩ በኋላ መክረው አስተምረውና ራሳቸውን አስመስለው ያወጡ ናቸው፡፡ ባለ አንድ መክሊት የተባለው ዐላውያን ነገሥታት፤ ዐላውያን መኳንንት እሳት ስለት አሳይተው ቢያስክዱኝ፣መናፍቃን ተከራክረው ቢረቱኝ፣ ምላሽ ቢያሳጡኝ፣ ሃይማኖቴን ቢያስቱኝ ብሎ ከማገልገል ይልቅ ሃይማኖቱን የማያስተምርና የማይመሰክር ነው፡፡  «ስለዚህ በሰው ፊት ለሚመሰክርልኝ ሁሉ እኔም በሰማያት በአለው አባቴ ፊት እመሰክርለታለሁ፤ በሰው ፊት የሚክደኝን ግን እኔም በሰማያት በአለው አባቴ ፊት እክደዋለሁ» ብሏል፤ ማቴ ፲፤፴፪ ፡፡ ስለዚህ በተሰጠን መክሊት በተባለ ጸጋ በሰው ሁሉ ፊት በማገልገል ልንመሰክር ይገባል፡፡

አምስትና ሁለት መክሊት የተቀበሉ አገልጋዮች ጠባይ

እነዚህ አገልጋዮች ለጌታቸው ታማኝ የነበሩ፤ በተቀበሉት መክሊት ወጥተው፤ ወርደውና አትርፈው የተገኙ ናቸው፡፡ መክሊታቸውን ከተቀበሉ በኋላ በእምነት ሊሰማሩ ወጡ እንጂ በሥጋት እጅና እግራቸውን አጣጥፈው አልተቀመጡም፡፡ እነርሱም በተሰጣቸው መክሊት መጠን በእምነት በማገልገላቸው ሁለቱም ገብር ኄር (ቸር አገልጋይ) የሚል የክብር ስም ተሰጣቸው፤ «ወደ ጌታህ ደስታ ግባ» የሚለውን የምሥራች ቃል ሰሙ፡፡

. አንድ መክሊት የተቀበለው አገልጋይ ጠባይ

እምነት የጎደለው ተጠራጣሪ ነበረና ማትረፉን ሳይሆን መክሰሩን፣ ማግኘቱን ሳይሆን መድከሙን፣ ብቻ አሰበ፡፡ በተቀበለው መክሊት ባለማትረፉ ራሱን ከመውቀስ ይልቅ ሰጪውን ጌታ አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፤ ካልበተንህበት የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው ብሎ የጽርፈት ንግግርን ተናገረ፡፡ ጌታው አስቀድሞ መክሊቱን ሲሰጠው አልቀበልም ሳይል ምን ሠራህና ምን አተረፍህ ሲባል ጌታውን ከሰሰ፡፡ ልቡ የደነደነ፣ጥፋቱን ለማመን የማይፈቅድ፣ለመመለስ የዘገየ ነበረና ወደ ውጭ ልቅሶ፤ ጥርስ ማፏጨት ወዳለበት አውጡት የሚለውን የፍርድ ቃል ሰማ፡፡ ዛሬ መልካም ሥራ ላለመሥራታቸው ምክንያት የሚያበዙ፣ ሃይማኖታቸውን ለመመስከር የሚያፍሩ፣ የሚፈሩና ኀጢአት ለመሥራት ግን የሚደፍሩ ሰዎች ባለ አንድ መክሊቱን አገልጋይ ይመስላሉ፡፡ እንግዲህ «በጎ ነገር ማድረግን የሚያውቅ፤ የማይሠራትም ኀጢአት ትሆንበታለች» ተብሏልና፤ያዕ ፬፥፲፯፡፡

ለአገልግሎት ተፈጥረናል

እግዚአብሔር ሰውን በአርአያው ፈጥሮ፤ በልጅነት ጸጋ አክብሮ፤ ሁሉን አዘጋጅቶ ለአዳም አንድ ልጁን ለመስቀል ሞት ያዘዘው በዓላማ ነው፡፡ ይኸውም «እንመላለስበት ዘንድ እግዚአብሔር አስቀድሞ ላዘጋጀው በጎ ሥራ በኢየሱስ ክርስቶስ  የፈጠረን ፍጥረቱ ነንና» ኤፌ ፪፥፲፡፡ ለመልካሙ ሥራ ሁሉም ሰው ተጠርቷል፤ በጥምቀት ዳግም የወለደንና በመስቀሉ ያዳነን በመልካም ሥራ እንድናገለግል ነው፡፡

እኛ በመክሊታችን ምን አተረፍን?

ጸጋችንን እናውቃለን? ለማወቅስ እንሻለን? በተሰጠን ጸጋ አትርፈናልን? ካላተረፍን ለምን? በእርግጥ አለማትረፋችን ግድ ይለናል? ከእግዚአብሔር ዘንድ ጸጋ ያልተቀበለ የለም፤ ሰው ጸጋውን አለማወቁ አልተቀበለም፤ ጸጋ የለውም አያሰኝም፡፡ ከሁሉ አስቀድመን ጸጋ እንደ ተሰጠን ማመን ይጠበቅብናል፡፡ የተሰጠንን ጸጋ ለማወቅ ለሕይወታችን በሚጠቅም አገልግሎት  ራሳችንን መፈተን መሞከር ይጠበቅብናል፤ ሳንሰማራና ራሳችንን ሳንፈትን ጸጋችንን ማወቅም ሆነ ማትረፍ አይቻልም፡፡ ጸጋ እንደተሰጠን አምነን ስንረዳና ራሳችንን ለአገልግሎት ስናዘጋጅ ማትረፊያ አገልግሎቱን መመልከት እንችላለን፡፡ በምን ማገልገል እዳለብን አለማወቅ አገልግሎትን ውስን አድርጎ መመልከት፣ለአገልግሎት መዘግየትና እንዴት ማገልገል እንዳለብን አለመረዳት ምክንያቶች ሊሆኑ ይችላሉ። ስለዚህ፡-

ሀ) በምን እናገልግል?

አንዳንዶች ምን ጸጋ ኖሮኝ ነው የማገለግለው? ሲሉ ይሰማሉ፤ ነገር ግን ከጸጋ እግዚአብሔር የጎደለ ሰው የለም፡፡ «መንፈስ ግን አንድ ሲሆን ስጦታው ልዩ ልዩ ነው፤ ጌታም አንድ ሲሆን  ልዩ ልዩ አገልግሎቶች አሉ፡፡ ሁሉን በሁሉ የሚያደርግ እግዚአብሔርም አንድ ሲሆን ልዩ ልዩ አሠራር አለ፡፡ በመንፈስ ቅዱስ የጥበብ ቃል የሚሰጠው አለ፡፡ በመንፈስ ቅዱስም የዕውቀት ቃል የሚሰጠው አለ፡፡ለአንዱም በአንዱ መንፈስ የመፈወስ ስጦታ፤ ለአንዱም ተኣምራትን ማድረግ፤ ለአንዱም ትንቢትን መናገር፤ ለአንዱም መናፍስትን መለየት፤ለአንዱም በልዩ አይነት ልሳን መናገር፤ለአንዱም በልሳኖች የተነገረውን መተርጐም ይሰጠዋል» ይላል፤፩ቆሮ ፲፪፥፬–፲፡፡ ስለዚህ በአለን ጸጋ ማገልገል ይገባናል፡፡

ለ) አገልግሎት ውስን ነውን?

አገልግሎት በቤተ ክርስቲያን፤ በበዓላትና በአጽዋማት ብቻ የሚመስላቸው፣ ካልቀደሱና ካላወደሱ፣ ካልዘመሩና ካላስተማሩ አገልግሎት የሌለ የሚመስላቸው ሰዎች አይጠፉም፡፡ ነገር ግን አገልግሎት በጊዜና በቦታ፤ በሁኔታም ሆነ በዓይነት አይወሰንም፡፡ «ደግሞ በኢየሱስ ክርስቶስ ለእግዚአብሔር ደስ የሚያሰኝ መንፈሳዊ መሥዋዕትን ታቀርቡ ዘንድ፤ ቅዱሳን ካህናት እንድትሆኑ፤ መንፈሳዊ ቤት ለመሆን ተሠሩ» ፩ጴጥ ፪፥፭፡፡ የእግዚአብሔር ቤተመቅደስ ስንሆን ሕዋሳቶቻችን እግዚአብሔርን የምናገለግልባቸው ንዋየ ቅድሳት ናቸው፡፡ በዐይናችን ቅዱሳት መጻሕፍትን ስናነብ፣ በጆሮአችን የተገፉትንና የተቸገሩትን ሰዎች ጩኸት ስንሰማ፣አፋችንን ለጸሎት ለምስጋና ስንክፈት፣ እጆቻችን ለአሥራት በኩራት ለምጽዋት ሲዘረጉ፣እግሮቻችን ማልደው ወደ ቤተክርስትያን ለጸሎት ሲገሰግሱ፣መንፈሳዊ ቤት ለመሆን እየሠራን እያገለገልን ነው፡፡ በጊዜያችን የታመሙትንና የታሰሩትን ብንጠይቅ፣ በጉልበታችን ደካሞችን ብንረዳ፣ በዕውቀታችን ያላወቁትን ብናሳውቅ ፣ በገንዘባችን የተቸገሩትን ብንጎበኝ፤ በጸጋ ላይ ጸጋና በበረከት ላይ በረከት እናተርፋለን፡፡ ወደ ጌታ ደስታ ግቡ የሚለውን የምስራች ቃል እንሰማለን፤ የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ እንሆናለን፡፡

ሐ) ለአገልግሎት ብንዘገይስ?

አንዳንድ ሰዎች ማገልገል እንዳለባቸው ቢያውቁም ለውሳኔ ይዘገያሉ፡፡ «ዛሬ ወይም ነገ ወደዚያች ከተማ እንሄዳለን ፤ በዚያችም ዓመት እንኖራለን፤ እንነግዳለንም፤ እናተርፋለንም፤ የምትሉ እናንተ ተመልከቱ፤ ነገ የሚሆነውን አታውቁምና» ያዕ ፬፥፲፫-፲፬፡፡ ዛሬ እንኑር ነገ ስለማናውቅ የኛ የሆነውን ተረድተን ልናገለግል ይገባል፡፡ «ማንም ሊሠራ የማይችልባት ሌሊት ትመጣለች» ዮሐ፤፱፥፬፡፡ ሌሊት የተባለው ዕለተ ሞትና ዕለተ ምጽአት  ነው፤ በሞት ከተጠራን በኋላ ልማር ላስተምር፣ ልወድስ ልቀድስ፣ ላጉርስ ላልብስ ማለት የለምና ለአገልግሎት ልንፈጥን ይገባል፡፡

መ) እንዴት እናገልግል?

ማገልገል አንድ ነገር ሆኖ ሳለ እንዴት ማገልገል እዳለብን ካልተረዳን አገልግሎታችን ያለእምነት የተሟላ አይሆንም፡፡ «ያለ እምነትም እግዚአብሔርን ደስ ማሠኘት አይቻልም» ዕብ ፲፩፥፮፡፡ ሰማያዊ ዋጋን እያሰብን እናገልግል፤ «ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየኛል? መከራ ነውን? ኀዘን ነውን? ስደት ነውን? ራብ ነውን? ጭንቀት ነውን? ሾተል ነውን?» ሮሜ.፰፥፴፭፡፡ ሰማያዊውን ዋጋ ስናስብ በፈተና በመከራ እንጸናለን፤ በትሕትና  ሆነን እናገልግል «ከእኔ ተማሩ፤ እኔ የዋህ ነኝና፤ ልቤም ትሑት ነውና» ብሏል፤ ማቴ ፲፩፡፳፱፡፡

እንግዲህ መክሊት የተቀበሉትን አገልጋዮች ስናስብ፤ አምስትና ሁለት መክሊት የተቀበሉ፤ ለጌታቸው ታማኝ የነበሩ፤ በተቀበሉት መክሊትም መከራን ታግሰውና በእምነት በማገልገላቸው ሁለቱም ገብር ኄር (ቸር አገልጋይ) ተባሉ፡፡ አንድ መክሊት የተቀበለው አገልጋይ እምነት የጎደለው ተጠራጣሪ ነበረና ማትረፉን ሳይሆን መክሰሩን ብቻ የሚያስብ ደካማ፤ የተፈጠረበትን  ዓላማና የተሰጠውን ተልእኮውን ያልተረዳ ሰው ነበር። እኛም በጥምቀት ዳግም የተወለድነውና በመስቀሉም የዳንነው ተልእ£ችንን ተረድተን በመልካም ሥራና በታማኝነት እንድናገለግል ነው፡፡ ቀደምት ቅዱሳን አባቶቻችንን አርአያ በማድረግ ለምን፤ በምንና እንዴት ማገልገል እዳለብን ልንረዳ ይገባል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ ወወላዲቱ ድንግል፤ ወመስቀሉ ክቡር!

በሰሜን ሸዋ ሰላሌ ሀገረ ስብከት የተሰረቁት የቅዱስ ገብርኤል፤የቅዱስ ዮሐንስና የገብረ ክርስቶስ ጽላቶች መገኘታቸውን ፖሊስ ገለጸ

በሕይወት ሳልለው

ሰኞ መጋቢት ፲፮ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም.፤ የቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ከመቃጠሉ በፊት የቅዱስ ገብርኤልና የበዓለወልድ ጽላቶች በመሰረቃቸው በወቅቱ በአካባቢው ሰዎች መካከል የተፈጠረውን አለመግባባት መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ለወረዳው ፖሊስ አስተዳደር በማመልከታቸውም በተደረገው ከፍተኛ ርብርብ፤ የቅዱስ ገብርኤል ጽላት ከሂደቡ አቦቴ ወረዳ እንድሪስ ወንዝ ውስጥ ሊገኝ እንደቻለ ፖሊስ ይፋ አድርጓል፡፡ ሆኖም ግን የበዓለወልድ ጽላት እስከአሁን እንዳልተገኘ አያይዞ አስታውቋል፡፡

በተመሳሳይ መልኩም መጋቢት ፲፬ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ከቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን የተሰረቁት የቅዱስ ዮሐንስና የገብረ ክርስቶስ ጽላቶች መገኘታቸውንም ፖሊስ ጨምሮ ገልጿል፡፡በዕለቱ የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎችና የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ከሌሊቱ ፲ ሰዓት ኪዳን ለማድረስ ወደ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን በደረሱበት ወቅት የቤተ መቅደሱ በር ተከፍቶ እንዳገኙትና በመደናገጥ ፍለጋ ቢጀምሩም ማግኘት እንዳልቻሉ ተናግረዋል፡፡ የቅዱስ ዮሐንስና የገብረ ክርስቶስ ጽላት፤ እንዲሁም ንዋያተ ቅድሳት በቦታቸው እንዳልነበሩ ሊገነዘቡም ችሏል፡፡ የማኅበሩ አባላትና የሰንበት ተማሪዎቹም በመደናገጥ ሁሉም በየፊናቸው ከሌሊቱ ፲፩ ሰዓት ጀምሮ ለፍለጋ እንደተሰማሩና እስከ ማግሥቱ ቀን ፲ ሰዓት ድረስ ማግኘት እንዳልቻሉ ጠቅሷል፡፡

ነገር ግን የሰንበት ተማሪ በሆነው ወጣት አብርሃም ታደሰ አማካኝነት በተገኘው ፍንጭ ከተጠረጠሩት ግለሰቦች አንደኛውን በመለየት ወንጀሉን ለፖሊስ አሳውቀዋል፡፡ የቀረበውን ሪፖርት በመመርኮዝ ፖሊስም የተጠረጠሩትን ሦስት ግለሰቦች በመከታተል መኖሪያ ቤታቸውን ከማወቁም በላይ ፍተሻ በማድረግ ከተጠርጣሪዎቹ አንደኛው ቤት ውስጥ የቅዱስ ዮሐንስና የገብረ ክርስቶስ ጽላትን ለማግኘት ችሏል፡፡ የጠፉትንም ንዋያተ ቅድሳት ተራራ ላይ ወስደው ማቃጠላቸውን ወንጀለኞቹ ከሰጡት ሪፖርት አረጋግጧል፡፡ ይህንንም ችግር ለመፍታት የሃይማኖት አባቶች በዚህ ወቅት ስብሰባ በማካሄድ አፋጠኝ የመፍትሔ እርምጃ እንደሚወስዱ ለማኅበራችን አሳውቀዋል፡፡

‹‹ወዕለቱሰ ለእግዚአብሔር ግብተ ትመጽእ ከመ ሰራቂ፤ የእግዚአብሔር ቀን እንደሌባ ድንገት ትመጣለች›› (፪ ጴጥ.፫፥፲)

መጋቤ ሐዲስ ምስጢረ ሥላሴ ማናየ

ደብረ ዘይት ጌታችን ለደቀ መዛሙርቱ ምሥጢረ ምጽአቱን ያስተማረበት፤ የገለጠበት፤ ደቀ መዛሙርቱም የመምጣቱን ምሥጢር የተረዱበት፤ ከኢየሩሳሌም በስተምሥራቅ የሚገኝ በወይራ ዛፍ የተሞላ፤የተከበበ ተራራ ነው፡፡ ጌታችን በመዋዕለ ሥጋዌው አዘውትሮ ከተመላለሰባቸው ቦታዎችም አንዱ ነው፡፡ ቀን በምኩራብ ሲያስተምር ውሎ ሌሊት ሌሊት በደብረ ዘይት ያድር እንደነበር ቅዱስ ወንጌል ምስክር ነው፡፡

 ‹‹መዓልተ ይሜህር በምኩራብ ወሌሊተ ይበይት ውስተ ደብረ ዘይት፤ ዕለት ዕለት በመቅደስ ያስተምር ነበር፤ ሌሊት ግን ደብረ ዘይት ወደሚባል ተራራ ወጥቶ ያድር ነበር›› እንዲል ሉቃ፤ ፳፩፥፴፯። ጌታችን ምሥጢረ መለኮቱን በደብረ ታቦር እንደገለጠ ምሥጢረ ምጽአቱን በደብረ ዘይት ገልጧል፡፡ ይህንንም ሲገልጥ ሦስቱ የምሥጢር ደቀ መዛሙርት ተብለው የሚጠሩት ያዕቆብ፣ ዮሐንስ፣ ጴጥሮስ የዚህ ምሥጢር መደበኞች እንደነበሩ መተርጒማን አስተምረዋል፡፡ ከእነዚህ ደቀ መዛሙርት አንዱ የነበረው ቅዱስ ጴጥሮስ ማን ያርዳ የቀበረ፤ ማን ይንገር የነበረ እንዲሉ አበው ያን ጊዜ የተገለጠለትን የጌታችንን የመምጣት ቀን ‹‹የእግዚአብሔር ቀን እንደሌባ ድንገት ትመጣለች›› በማለት በዘመኑ፣ ኅልፍተ ሰማይ ወምድር፣ በዘመኑ ሙታን ትንሣኤ ሙታን የለም የሚል የስንፍና ትምህርት ይዘው ክርስቲያኖችን ያወናብዱ ለነበሩ ቢጽ ሐሳውያን ትንሣኤ ሙታን እንዳለ ገልጾ ጽፏል፡፡

ታዲያ ከእኛ ቀድመው የሞቱት ለምን ቀድመውን ተነሥተው አናይም? መከር አንድ ጊዜ ይካተታልን? ከሰማይስ ከፊሉ ታንጾ፣ ከመሬቱስ እኩሌታው ተጐርዶ ሲወርድ ለምን አናይም? እያሉ ሲያስቸግሩ ትምህርቱን ሲነቅፉ የክርስትናውን ትምህርት ሲያጐድፉ ለነበሩት በክሕደት ለሚመላለሱ ሰዎች ነው ይህን የጻፈው፡፡ የእግዚአብሔር ቀን ማን ናት? የሚለውን ማየት ጥሩ ነው፤ የእግዚአብሔር የተለየች ቀንስ አለችው? ቀናት በሙሉ የማን ሆነው ነው? የሚል ሐሳብ በውስጣችን መመላለሱ አይቀርም፤ እውነት ነው! ቀናቱ ሁሉ የእርሱ ናቸው፡፡ እርሱ ያለ ቀንና ያለ ጊዜ ከዘመን በፊት የነበረ ‹‹ያለና የሚኖር›› አምላክ ሲሆን ቀናትን የሰጠን ዘመናትን በልግስና የቸረን እርሱ ነው፤ ሁሉ ቀናት የእርሱ ገንዘቦች መሆናቸውን መጻሕፍት ያስተምራሉ፤ ‹‹ዚኣከ ውእቱ መዓልት ወዚኣከ ውእቱ ሌሊት – አቤቱ ቀኑ ያንተ፤ ሌሊቱም የአንተ ነው›› መዝ.፸፫፥፲፮። ሁሉም ባሪያዎችህ ናቸው፤ ቀኑ በትእዛዝህ ይኖራል፤ መዝ ፻፲፱፥፲፮፡፡

ዕለተ ምጽአት

የቀናት ሁሉ ማጠቃለያ፤ የሁሉም ፍጻሜ ዕለተ ምጽአት፣ ዳግም ምጽአት፣ የመጨረሻዋ ዕለት ናት፡፡ ቀን የምትባለው ከዕለተ ፍጥረት ጀምሮ ያለው ሥጋዊና ደማዊ ፍጥረት ሁሉ ፍጻሜውን የሚያገኝባት፤ ክፉም ደጉም የሠራው እንደየሥራው መጠን ዋጋውን የሚቀበልባት፤ የጭንቅ፣ የመከራ ቀን፤ ይህ ዓለም የሚያልፍባት፤ የሁሉም ፍጻሜ የሆነች ቀን ናት፡፡ ጌታችን ስለሚመጣባት የጌታ ቀን ተብላም ትጠራለች፡፡ ስለዚህ የመጨረሻዋ ቀን ዕለተ ምጽአት ወይም  በሌላ አነጋገር የፍርድ ቀን ስለተባለችው ነቢያት፣ ራሱ ጌታችንና ቅዱሳን ሐዋርያት አስተምረዋል፡፡ ቀዳማዊ ምጽአቱን እንደ ዘር ደኃራዊ ዳግም ምጽአቱን እንደ መከር አድርጐ ዓለም ይጠብቀዋል፤ በመጀመሪያው ምጽአቱ ትሕትናውን በዳግም ምጽአቱ ግርማውን ዓለም ሁሉ ያያል፤ መጀመሪያ በትሕትና መጣ ዓለምን አስተማረው፤ በኋላ በግርማ መንግሥት በክበበ ትስብእት ይመጣል፤ ይህ የጌታ ቀን ተበሎ ይጠራል፡፡ ‹‹እነሆ እንደ ምድጃ እሳት የሚነድ ቀን ይመጣል፤ ትዕቢተኞችና ኃጢአትን የሚሠሩ ሁሉ ገለባ ይሆናሉ፤ የሚመጣውም ቀን ያቃጥላቸዋል፤ ሚል.፬፥፩፡፡

ታላቁና የሚያስፈራው የእግዚአብሔር ቀን ሳይመጣ ነቢዩ ኤልያስን እልክላችኃለሁ››ሚል.፬፥፭፡፡ ‹‹የጭንቀት ቀን ሳይመጣ በጉብዝናህ ወራት ፈጣሪህን አስብ መክ.፲፪፥፩። ያ ቀን የመዓት፤ የመከራ፤ የጭንቀት፤ የመፍረስ፤ የመጥፋት፤ የጨለማ ፤ የጭጋግ፤ የደመናና፤ የድቅድቅና ጨለማ ቀን ነው›› ሶፎ. ፩፥፲፭።

‹‹እግዚአብሔር በግልጥ ይመጣል፤ መጥቶም ዝም አይልም፤ እሳት በፊቱ ይነድዳል›› መዝ. ፵፱፥፫። በዚያች ቀን ለእያንዳንዱ እንደየሥራው መጠን የሚከፍል መሆኑን አስረድቷል፤ እንደ ቀድሞው በትሕትና ሳይሆን በግርማ መንግሥቱ እንደሚመጣም ያሳያል፡፡ ‹‹ጌታ እግዚአብሔር እንደ ኃይል ይመጣል፤ እነሆ ዋጋው ከእርሱ ጋር ደመወዙም በፊቱ ነው›› ኢሳ. ፵፥፲።

‹‹እነሆ የእግዚአብሔር ቀን ይመጣል፤ በዚያም ቀን እግሮቹ በኢየሩሳሌም ትይዩ በምሥራቅ በኩል ባለው በደብረ ዘይት ተራራ ይቆማሉ›› ዘካ. ፲፬፥፩‐፭።  ክብር ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህችን ዕለት ከእነምልክቶቿ ያስተማረው በደብረ ዘይት ነው፤ ይህች ዕለትና የጌታ ምጽአት ምሥጢር ናቸው፤ ምሥጢረ ምጽአቱን በደቀ መዛሙርቱ አማካኝነት ለዓለም ገልጧል፤ አስረድቷልም፡፡

የምጽአት ምልክቶች

‹‹ብዙዎች እኔ ክርስቶስ ነኝ እያሉ በስሜ ይመጣሉ፤ ብዙዎችን ያስታሉ፡፡ ጦርነትን፤ የጦርነትንም ወሬ ትሰሙ ዘንድ አላችሁ፤ ይህ ሊሆን ግድ ነውና ተጠንቀቁ፤ አትደናገጡ፤ ዳሩ ግን መጨረሻው ገና ነው፡፡ ሕዝብ በሕዝብ ላይ፤መንግሥትም በመንግሥትም ላይ ይነሣሉ፤ በየሀገሩም ረሀብ፣ ቸነፈርም፤ የምድር መናወጥም ይሆናል፡፡ እነዚህም ሁሉ የምጥ ጣር መጀመሪያ ናቸው፡፡ ያንጊዜም ለመከራ አሳልፈው ይሰጡአችኋል፤ ይገድሉአችኋልም፤ ስለ ስሜም በሰዎች ሁሉ ዘንድ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ፡፡ ያንጊዜም ብዙዎች ሃይማኖታቸውን ይለውጣሉ፤ እርስ በእርሳቸውም አሳልፈው ይሰጣጣሉ፤ እርስ በእርሳቸውም ይጣላሉ፡፡ ብዙዎች ሐሰተኞች ነቢያትም ይመጣሉ፤ ብዙዎችንም ያስታሉ፡፡ ከዐመፅም ብዛት የተነሣ ፍቅር ከብዙዎች ዘንድ  ትጠፋለች፡፡ እስከ መጨረሻው የሚታገስ ግን እርሱ ይድናል፡፡ በሕዝብ ሁሉ ምስክር ሊሆን ይህ የመንግሥት ወንጌል በዓለም ይሰበካል፤ ያንጊዜም ፍጻሜ ይደርሳል›› ማቴ. ፳፬፥፭‐፲፬።

በዚያን ጊዜ የሰው ልጅ በክብሩ ከቅዱሳን መላእክት ጋር  በዙፋን ይቀመጣል፤ አሕዛብ ሁሉ በፊቱ ይሰበሰባሉ፤ እረኛም በጐችን ከፍየሎች እንደሚለይ እርስ በእርሳቸው ይለያቸዋል፤ በጐችን /ጻድቃንን/ በቀኝ ፍየሎችን /ኃጥኣንን/ በግራ ያቆማቸዋል፡፡ ‹‹ሙታንን ያስነሣቸዋል፤ ሙታን ይነሣሉ፤ በመቃብር ያሉ ሬሳዎችም ሕያዋን ይሆናሉ፤ ከአንተ የሚገኝ ጠለ ረድኤት ሕይወታቸው ነውና››፤ ኢሳ. ፳፮፥፲፱።

የዘለዓለም ሕይወት ይሰጣል፤ ሕይወት ለማይገባቸውም የዘለዓለም ቅጣት ይፈርድባቸዋል፡፡ በመቃብር ያሉት ድምፁን የሚሰሙበት ሰዓት ይመጣል መልካም ያደርጉ ለሕይወት ትንሣኤ ክፉ ያደርጉ ለፍርድ ትንሣኤ ይመጣሉ፤ ዮሐ.፭፥፳፰-፳፱። ከላይ እንዳየነው ጻድቃን በቀኝ ኃጥአን በግራ ይቆማሉ ማለት ጻድቃን በክብር መንግሥተ ሰማያትን ይወርሳሉ ኃጥኣን በውርደት ወደ ገሃነመ እሳት ይሄዳሉ፤ ‹‹እነዚያም ወደ ዘለዓለም ቅጣት ይሄዳሉ ጻድቃን ግን ወደ ዘለዓለም ሕይወት ይሄዳሉ›› እንዲል፤ ማቴ.፳፭፥፵፮፡፡

የእኛንም እድል ፈንታ ከጻድቃን ጋር ያድርግልን፤አሜን!

በሰሜን ሸዋ ሰላሌ ሀገረስብከት በኤጀሬ ወረዳ የቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ተቃጠለ

 

በሕይወት  ሳልለው

በትናትናው ዕለት በሰሜን ሸዋ በሰላሌ ሀገረስብከት በኤጀሬ ወረዳ የቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን መቃጠሉን የወረዳው ፖሊስ አስታወቀ፡፡ ማንነታቸው ያልታወቁ ግለሰቦች የቤተ ክርስቲያኑን ጣሪያና መጋረጃ በማቃጠል ግድግዳውን ሙሉ ለሙሉ አፍርሰዋል፡፡ቁጥራቸው ባልተረጋገጠ ግለሰቦች ላይ ከባድ ጉዳት ሲያደርሱ የቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያንንም እንደዘረፉ ፖሊስ አያይዞ አስታውቋል፡፡

በተጨማሪም እንደተገለጸው፤ በቃጠሎው ሳቢያ በወቅቱ ረብሻ ተነስቶ ነበር፡፡ ሌሎች ሶስት ቤተ ክርስቲያናት ላይም ተመሳሳይ ጥፋት ሊፈጽሙ የነበሩ ግለሰቦችን የአካባቢው ሰዎች ባደረገለት ትብብር ፖሊስ በቁጥጥር ስር ለማዋል ችሏል፡፡

እኛም በቀጣይ ዝርዝር መረጃ ሲደርሰን እንገልጻለን፡፡

«ጌታችን ኢየሱስ መፃጒዕን ፈወሰው» (ዮሐ.፭፥፮-፱)

በሕይወት  ሳልለው

«መፃጒዕ» ለ፴፰ ዓመት የአልጋ ቁራኛ የነበረና ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዕለተ ሰንበት የፈወሰው ሰው ነው፡፡ ጌታችንም ያን ሰው በአልጋ ተኝቶ ባየው ጊዜ መዳን እንደሚፈልግ አውቆ ጠየቀው፤ «ልትድን ትወዳለህን?»  መፃጒዕም «አዎን ጌታዬ ሆይ፤ነገር ግን ውኃው በተናወጠ ጊዜ ወደ መጠመቂያው የሚያወርደኝ ሰው የለኝም፤እኔ በምመጣበት ጊዜ ሌላው ቀድሞኝ ይወርዳል፤ አለው»፤ ጌታም «ተነሥና አልጋህን ተሸክመህ ሂድ» ባለው ጊዜ፤ ወዲያውኑም ድኖ አልጋውን ተሸክሞ ሄደ፤ያች ቀንም ሰንበት ነበረች፤ዮሐ.፭፥፮-፱

በኢየሩሳሌም የነበሩ አይሁድ ግን ጌታችን ያደረገለትን ተአምር ባለማመን፤ በሰንበት ቀን አልጋ ተሸክሞ መሄድ ዕለቱን ማርከስ እንደሆነ መፃጒዕን ለማሳመን ሞከሩ፤ ዕለተ ሰንበት ከዐሥርቱ ትእዛዛት አራተኛው «የሰንበትን ቀን ቅዱስ አድርገህ መጠበቅ እንዳለብህ አትርሳ፤»ይላልና ዘፀአት ፳፥፰-፲፡፡

እርሱ ግን ለ፴፰ ዓመት ከአልጋ ላይ መነሳት እንኳን ባልቻለበት ሁኔታ ያ ያዳነው ሰው አልጋውን ተሸክሞ እንዲሄድ ባዘዘው ጊዜ ያለ ምንም ጥርጣሬ፤ በእምነት ተፈውሶና ተነሥቶ መሸከም እንደቻለ ነገራቸው፡፡ እነርሱም በመጓጓት ያዳነውን ሰው ማንነት ቢጠይቁትም ሊነግራቸው አልቻለም ፤ጌታችን ከእነርሱ ተሰውሮባቸው ነበርና፡፡

በዚህች የተቀደሰች ሰንበት ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሌሎች ድውያንን እየፈወሰ፤ ጎባጣዎችን እያቀና ፣ ዕውራንን እያበራ፣ አንካሶችን እያዳነ፤ ለምፃሞችንም በመለኮታዊ ኃይሉ እያነጻ፤ልምሾዎችን እያዳነና አጋንንትን እያወጣ የዋለበት ዕለትም ነበር።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን አምስት ገበያ ሕዝብ ይከተለው እንደ ነበር በቅዱሳት መጻሕፍት በስፋት ተገልጾም እናገኛለን፡፡ «አምስት ሺህ ሰዎች ያህሉ ነበርና ለደቀ መዛሙርቱ በየክፍሉ አምሳ አምሳውን አስቀምጡአቸው አላቸው፤» (ሉቃ.፱፤፲፬) እንዲል፡፡ ሕዝቡም ጌታችንን  የተከተሉበት የተለያየ ዓላማና ምክንያት ነበራቸው፡፡ በትምህርቱ ተማርከው፣ ተአምራቱን ሰምተው፣ ከተያዙበት የአጋንንት ቁራኝነት ለመፈወስ፣ ረሀባቸውንና ጥማቸውን ለማስታገስ፣ መልኩን ለማየት፣ ጎዶሏቸውን ይሞላላቸው ዘንድ ይከተሉት ነበር፤እንደ መሻታቸውም ተፈጽሞላቸዋል፡፡

በዕለተ ሰንበትም ቤተ ክርስቲያን መሄድ ተገቢ ስለሆነ መፃጒዕ ከበሽታው በመዳኑና መራመድ በመቻሉ ወደዚያው አቀና፡፡ ጌታችንንም በቤተ መቅደስ ውስጥ ሲያስተምር አገኘው፤ ጌታም እንዲህ አለው «እነሆ ድነሃል፤ግን ከዚህ የባሰ እንዳያገኝህ ተጠንቀቅ»፤ዮሐ.፭፥፲፬፡፡ እርሱም የተባለውን በፀጋ ሰምቶ አይሁድ ካሉበት ስፍራ ሔደ፤ ባገኛቸውም ጊዜ ያዳነው ሰው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መሆኑን ነገራቸው፡፡

አይሁድ ግን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በምቀኝነት ሊገድሉት ይፈልጉ ነበር፡፡ አንዱ ክሳቸው ሰንበትን ይሽራል የሚልም ስለነበር መፃጒዕ “በሰንበት የፈወሰኝ እሱ ነው” በማለት ቢመስክርም ለ፴፰ ዓመት ከተያዘበት ሥቃይ የገላገለውን አምላኩን በመካድ በጥፊ እስከ መምታት ደረሰ፡፡

ጻድቁ ኢዮብ «መንገዴን ፈጽሞ ዐወቀ፣ እንደ ወርቅም ፈተነኝ፣ እንደ ትእዛዙ እወጣለሁ፣ መንገዱንም ጠብቄያለሁ፣ ፈቀቅም አላልሁም» በማለት በመከራው ዘመን ለአምላኩ የነበረውን ፍጹም እምነት መሰክሯል፤ ኢዮ.፳፫፣፲፩፡፡

አምላካችን ያደረገለትን ድኅነትና ተአምር ምስክር መሆኑ ተገቢ ቢሆንም፤መፃጒዕ ግን ምላሹን በክሕደት ገለጸ፡፡ ጌታችን በዮሐንስ ወንጌል ፭፥፴፪ ላይ «ነገር ግን ለእኔ የሚመሰክር ሌላ ነው፤ ስለ እኔ የሚመሰክረው ምስክርነቱ እውነት እንደሆነ አውቃለሁ»፤ብሏል፡፡

ምርጥ ዕቃ የተሰኘው ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስንም ከክሕደት፣ አምላኩንም ከማሳደድ መልሶ የወንጌል ገበሬ ስላደረገው «የጽደቅ አክሊል ተዘጋጅቶልኛል» እንዲል (፪ኛ ጢሞ.፬፤፰)፤ እስከ ሞት ድረስ ታመነ፤ አንገቱንም ለሰይፍ አሳልፎ እስከ መስጠት አደረሰው፡፡ መፃጒዕ ግን ለክሕደት ራሱን አሳልፎ ሰጠ፣ ክሕደቱንም በጥፊ በመማታት ገለጸ፡፡

ቤተ ክርስቲያናችን ሁሉንም በሥርዓት የምታከናውን ስንዱ እመቤት ናትና በዐቢይ ጾም ከሚገኙት ሰንበታት ውስጥ ዐራተኛውን ሳምንት መፃጒዕ ብላ ሰይማዋለች፡፡ አምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብንወድቅ እንደሚያነሣን፣ ብንታመም እንደሚፈውሰን ለማስተማር እንዲሁም ደግሞ ከመፃጒዕ ሕይወት እንማር ዘንድ መታሰቢያውን አደረገች፡፡

«ዳግመኛ እንዳትበድል ተጠንቀቅ» ዮሐ.፭፤፲፬፤ እንዳለ ከኃጢአት ወደ ጽድቅ፣ ከሞት ወደ ሕይወት፣ እንሸጋገር ዘንድ፣ የአምላካችንን ቃል መፈጸም እንደሚገባን፣ እሰከ ሞትም መታመን እንዳለብን ያስተምረናል፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ ቅፍርናሆም በገባ ጊዜ አንድ የመቶ አለቃ ወደ እርሱ መጥቶ «አቤቱ ልጄ ሽባ ሆኖ እጅግ እየተጨነቀ በቤት ተኝቷል፤» ብሎ ለመነው፤ ጌታችንም «እኔ መጥቼ እፈውሰዋለሁ» አለው፡፡ የመቶ አለቃውም «አቤቱ አንተ ከቤቴ ጣራ በታች ልትገባ አይገባኝም፡፡ ነገር ግን በቃልህ እዘዝ ልጄም ይድናል» አለ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም መቶ አለቃውን እጅግ አደነቀ፤ «እውነት እላችኋለሁ፣ በእስራኤል ሁሉ እንዲህ ያለ እምነት አላገኘሁም» ብሎ መሰከረለት፤ በመቶ አለቃውም እምነት ተደነቀ፡፡ «እንደ እምነትህ ይሁን» አለው፤ ከዚያም ሰዓት ጀምሮ ልጁ ዳነ፤ ማቴ.፰፤፭-፲፫፡፡

ይህ በእምነት ጽናት የተገለጸ ሕይወት ነው፡፡ መፃጒዕ ግን ያዳነውን አምላኩን በዓይኑ አይቶ፣ በእጁ ዳስሶ፣ ለ፴፰ ዓመታት የተኛበትንና የተሸከመውን አልጋ እንደገና እሱ ተሸክሞት እንዲሄድ ዕድሉን የሰጠውን አምላኩን ካደ፡፡ በእምነት የጸኑ፣ እንደ ቃሉም የተጓዙ፣ እስከ ሞትም የታመኑት ሲድኑ «ኑ የአባቴ ቡሩካን» ሲባሉ፤ በክህደት ያጠናቀቁትን ደግሞ «አላውቃችሁም» ተብለው ጥርስ ማፋጨት፣ እሳቱ ማያንቀላፋበት ጥልቅ እንዲወረወሩ ሁሉ፤ መፃጒዕ ዕድሉን አበላሸ፡፡ ጽድቅ በፊቱ ቀርቦለት መርገምን መረጠ፣ ከዘለዓለማዊ ሕይወት ይልቅ ዘለዓለማዊ ሞትን ምርጫው አደረገ፡፡

ምርጫችን የቱ ይሆን? በዐቢይ ጾም ወቅት ቤተ ክርስቲያናችን ሰንበታቱን ስያሜ ሰጥታ ስናከብር እንማርባቸው ዘንድ ነው፡፡ ጽድቅን በመሻት ሕይወታችን ከእግዚአብሔር ጋር እንድናደርግ፣ መንገዱንም እንከተል ዘንድ ነው፤ «ሕግህ ለእግሬ መብራት፣ ለመንገዴም ብርሃን ነው»፤ መዝ.፻፲፰፤፻፭ ላይ ተብሎ እንደተጻፈው፡፡

የክርስትና ሕይወት ፈተና የተሞላባት ናትና፤ በኑራችን ውስጥ የሚገጥመንን መሳናክልና ውጣ ውረድ ለመቋቋም ሁሌም በእምነትና በሃይማኖት መኖር ብቸኛ መፈትሔ ነው፡፡ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በዚህ ሳምንት ተአምራትን ከማድረጉ በላይ ለሕይወታችን ስንቅ የሚሆነን የወንጌል ቃል አስተምሮበታል፡፡ «ቃሉም የላችሁም፤በእናንተ ዘንድም አይኖርም፤እርሱ የላከውን አላመናችሁምና፤ መጻሕፍትን መርምሩ፤ በእነርሱም የዘላለም ሕይወትን የምታገኙ ይመስላችኋልና፤እነርሱም የእኔ ምስክር ናቸው»፤ ብሏል፤የሐ.፭፥፴፰፥፴፱፡፡

“እግዚአብሔርን የሚፈልግ ልብ ደስ ይበለው” እንደተባለው አምላካችን የጎደለንን እንዲሞላልን በጾም፣ በጸሎት፣ በፍጹም ትሕትና እና እምነት ልንተጋ ያስፈልጋል፤ መዝ.፻፭፣፫፤ ፩ኛ ዜና.፲፮፤፲፡፡ «ዳግመኛ እንዳትበድል ተጠንቀቅ»፤ እንደተባለውም መፃጒዕ የአምላካችንን ቃል ዘንግተን፣ የተደረገልንን መልካም ነገር ሁሉ በክፉ እንዳንለውጥ መጠንቀቅ ከእኛ ኦርቶዶክሳውያን ይጠበቃል፡፡ የአምላካችንን ቃል በሕይወታችን ዘመን ሁሉ በመፈጸም፣ እስከ መጨረሻው እንድንጸና አምላካችን ይርዳን፤ አሜን!

ምኲራብ

                                                                                                                ገብረእግዚአብሔር ኪደ

ምኲራብ ማለት ቤተ ጸሎት ማለት ሲሆን ናቡከደነፆር ቤተ መቅደስን አፍርሶ አይሁድን ወደ ባቢሎን ማርኮ ከወሰዳቸው በኋላ ሕገ ኦሪትን ለመማርና ለጸሎት በየቦታው የሰሩት ቤት ነው፡፡ በኢየሩሳሌም ብቻ ይገኝ በነበረው ቤተ መቅደስ ማንም እስራኤላዊ በዓመት ሦስት ጊዜ አምልኮውን መፈጸም ግዴታው የነበረ ሲሆን፥ በምኵራብ ግን በየዕለቱ እየተገናኙ ቅዱሳት መጻሕፍትን ያነቡ፤ ይተረጕሙና ይሰሙም ነበር (ሕዝ.፲፩፥፲፮፣ ሐዋ.፲፭፥፳፩)፡፡

ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ፥ በልብ መታሰቡ፣ በቃል መነገሩ፣ በቅዱሳት መጻሕፍትም መዘከሩ ከፍ ከፍ ይበልና፤ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምኵራበ አይሁድ እየተገኘ እንዳስተማረ፣ ድውያንን እንደ ፈወሰ፣ በዚያ ይነግዱ የነበሩትንም ማስወጣቱን አስመልክቶ በዐቢይ ጾም ከሚገኙት ሳምንታት መካከል ሦስተኛውን እሁድ ምኵራብ ብሎታል፡፡ “ኢየሱስ ወደ አይሁድ ምኵራብ ገባ፤ የሃይማኖትም ቃል አስተማረ፡፡ ከመሥዋዕት ይልቅ ምጽዋትን እወዳለሁ፡፡ የሰንበት ጌታዋ የምሕረት አባትዋ እኔ ነኝ አላቸው፡፡ የአባቴን ቤት የሸቀጥ ቦታ አታድርጉት፡፡ ቤቴ የጸሎት ቤት ተብሎ ይጠራል፡፡ ወደ ምኵራብ ገብቶ ተቈጣቸው፡፡ ዝም እንዲሉም ገሠጻቸው፡፡ እነርሱም ትምህርቱን፣ የቃሉን ግርማ፣ የአነጋገሩንም ጣዕም የንግግሩንም ርቱዕነት አደነቁ” በማለትም ይዘምራል – በጾመ ድጓው ! ከዚህም መረዳት እንደምንችለውም፡-

አንደኛ ቅዱስ ያሬድ ምኲራብን “የአይሁድ ምኵራብ” ብሎ እንደ ጠራው እንመለከታለን፡፡ በዕለቱ በሚነበበው ወንጌል ላይም፥ ወንጌላዊ ቅዱስ ዮሐንስ ቀርቦ የነበረውን ፋሲካ “የእግዚአብሔር ፋሲካ” (ዘጸ.፲፪፡፥፲፩) ማለትን ትቶ “የአይሁድ ፋሲካ” ብሎ እንደ ጠራው እናያለን (ዮሐ.፪፥፲፪)፡፡ ሊቁ ራሱ ቀጥሎ እንደ ነገረን፥ አይሁድ ከፈቃደ እግዚአብሔር ፈቀቅ ብለው እንደ ነበረ፥ ጌታችን ግን የሰው ሥርዓትንና ወግን ሳይኾን “የሃይማኖትን ቃል” ወይም ወንጌልን እንዳስተማራቸው እንገነዘባለን፡፡

ምንም እንኳን ከላይ እንደ ተናገርነው አይሁድ በዚያ በምኵራብ በየዕለቱ ቅዱሳት መጻሕፍትን ያነበቡ የነበሩ ቢኾኑም፥ በገጸ ንባባቸው ብቻ ድኅነት የሚገኝ ይመስላቸው ስለ ነበረ ጌታችን “የሃይማኖትን ቃል” አስተማራቸው (ዮሐ.፭፡፥፴፱)፡፡ ዳሩ ግን ምን ያደርጋል፤ አብዛኞቹ ይህን አልተቀበሉትም፡፡ ይህን የተመለከተው አፈ ጳዝዮን ዮሐንስ አፈወርቅ በልደት ድርሳኑ ላይ እንዲህ አለ፡- “በአይሁድ ዘንድ ድንግል እንድትፀንስ ተነገረ፤ በእኛ ዘንድ ግን እውነት ኾነ፡፡ ትንቢት ለምኵራብ ሃይማኖት ለቤተ ክርስቲያን ነውና፡፡ ያቺ ትንቢትን ገንዘብ አደረገች፤ ይህችም ሃይማኖትን ገንዘብ አደረገች፡፡ ምኵራብ ምሳሌን ሰጠች፤ ቤተ ክርስቲያን አመነችበት፡፡ ምኵራብ ትንቢት አስገኘች፤ ቤተ ክርስቲያን ተቀበለችው፡፡ ምኵራብ ትንቢቱን በምሳሌ አስተማረች፤ ቤተ ክርስቲያን በሃይማኖት ጸናችበት፥ ረብሕ ጥቅም አደረገችው፡፡ ከዚያም የወይን ሐረግ (መስቀል) ተተከለ፤ በእኛ ዘንድ ግን የጽድቅ ፍሬ ተገኘ፡፡ ያቺ ወይንን በዐውድማ ረገጠች፤ አሕዛብ የምሥጢሩን ገፈታ ጠጡ፡፡ ያቺ የስንዴ ቅንጣትን ዘራች፤ አሕዛብ በሃይማኖት ሰበሰቡት፡፡ አሕዛብ ጽጌረዳን በቸርነቱ ሰበሰቡ (ሃይማኖትን ገንዘብ አደረጉ)፤ እሾኹ ግን በአይሁድ ዘንድ ቀረ፡፡ ይኸውም ክሕደት ኑፋቄ ነው፡፡ ትንሽ ወፍ ሰነፎች ተቀምጠው  ሳሉ  ጥላውን  ጥሎባቸው  ይኼዳል፡፡  አይሁድም በብራና የተጻፈውን መጽሐፍ ተረጎሙ፤ አሕዛብ ግን ምሥጢሩን ተረዱ” እያለ እንዳመሠጠረው (ሃይማኖተ አበው ዘዮሐ.አፈ.፣ ፷፮፥፳፩-፳፬)፡፡

ሁለተኛ ቅዱስ ያሬድ “እግዚአብሔር ከመሥዋዕት ይልቅ ምጽዋትን” እንደሚወድ ነግሮናል፡፡ ይኸውም አብዛኛው አይሁድ ጌታችን እንደ ተናገረ ከአፍ ብቻ ሃይማኖታውያን የነበሩ በውስጣቸው ግን እንዳልነበሩ የሚያመለክት ነው (ማቴ.፳፫፡፳፯)፡፡ እግዚአብሔር ግን የሚፈልገው የልብ መታደስን፣ የሕይወት መዓዛ መለወጥን፥ በአጭሩ እግዚአብሔር መምሰልን ነው፡፡ ስለዚህ ጌታችን “የምሕረት አባትዋ እኔ ነኝ” እያለ ይህን ያስተምራቸው ዘንድ ወደ “አይሁድ ምኵራብ” እንደ ገባ እንመለከታለን፡፡ ምሕረት በሦስት መልኩ የምትፈጸም ስትሆን እነርሱም ምሕረት ሥጋዊ፣ ምሕረት መንፈሳዊና ምሕረት ነፍሳዊ ይባላሉ፡፡ ምሕረት ሥጋዊ የሚባለው ቀዶ ማልበስ ቈርሶ ማጉረስ ነው፡፡ ምሕረት መንፈሳዊም መክሮ አስተምሮ ክፉን ምግባር አስትቶ በጎ ምግባር ማሠራት ነው፡፡ ምሕረት ነፍሳዊ ደግሞ ክፉን ሃይማኖት አስትቶ በጎ ሃይማኖት ማስያዝ ነው፡፡ ስለዚህ እግዚአብሔር አምላካችን ከየትኛውም ዓይነት መሥዋዕት ይልቅ ደስ ብሎ የሚቀበለው ይህን እንደ ሆነ ከዚህ እንማራለን፡፡

ሦስተኛ፥ ቤተ መቅደሱ ቤተ ምሥያጥ ሆኖ እንደ ነበረ ሊቁ ቅዱስ ያሬድ ነግሮናል፡፡ ቤተ መቅደሱ ከተመሠረተበት ዓላማ ርቆ፣ የገበያና የንግድ ቦታ ሆኖ፣ “ተዉ” ብሎ የሚቈጣ ሰው ጠፍቶ፣ “ርግብ ሻጮች” በዝተው እንደ ነበረ በዕለቱ ከሚነበበው ወንጌልም እንመለከታለን (ዮሐ.፪፥፡፲፬)፡፡ ስለዚህ ጌታችን ይህን ያደርጉ የነበሩትን ሲገለባብጥባቸው፥ አንደኛ- ዓላማቸውን ስለ መሳታቸው ሲነግራቸው፣ ሁለተኛ- መሥዋዕተ ኦሪትን ሲያሳልፍ፣ ሦስተኛ- ዛሬም ጭምር ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ በሚፈተትበት ሥፍራ ይህን የሚያደርጉትን “ከቶ አላውቃችሁም” እንደሚላቸው የሚያስገነዝብ ነው፡፡ ዳግመኛም “ርግብ ሻጮች” የተባሉት በተጠመቁ ጊዜም ሆነ ከዚያ በኋላ የተቀበሉትን መንፈሳዊ ሀብት ለምድራዊ ሥራ ለኃጢአት ንግድ የሚጠቀሙበትን “ከእኔ ወግዱ” እያለ በፍርድ ቃሉ ጅራፍ ወደ ውጭ ጨለማ እንደሚያወጣቸው የሚያስተምር ነው፡፡

ቅዱስ ያሬድ ሌላው የነገረንና በአራተኛ ደረጃ ልናየው የምንችለው፥ ክብር ይግባውና ጌታችን ሲያስተምራቸው ሁሉም እንደ ተደነቁ እንመለከታለን፡፡ ይኸውም እንደ ነቢያት “እግዚአብሔር እንዲህ አለ”፣ “ሙሴ እንዳዘዘ”፣ “ሳሙኤል እንደ ተናገረ” በማለት ሳይሆን እንደ ባለ ሥልጣን እንደ ሠራዔ ሕግ “እኔ ግን እላችኋለሁ” እያለ ያስተምራቸው ስለ ነበረ ነው፡፡ ይህም የባሕርይ አምላክነቱን የሚገልፅ ነው፡፡

እግዚአብሔርን የምትወዱት፥ ይልቁንም እግዚአብሔር አብልጦ የሚወድዳችሁ ሆይ ! እንግዲያውስ እኛም እንፍራ፡፡ ከፈቃደ እግዚአብሔር ፈቀቅ ብለን መቅደስ ሰውነታችን የእግዚአብሔር ሳይሆን “የአይሁድ ምኵራብ” እንዳይባል እንፍራ፡፡ ደገኛ ዘር ይኸውም የወንጌል ዘር ተዘርቶብን ሳለ የክፋት ፍሬ ተገኝቶብን ያን ጊዜ እንዳናፍር አሁን እንፍራ፡፡ ምሕረት ሥጋዊን፣ ምሕረት መንፈሳዊንና ምሕረት ነፍሳዊን በቃል ያይደለ፤ እንደ ዓቅማችን በተግባር እንፈጽም፡፡ በእውነት ያለ ሐሰት ብርሃናችን በሰዎች ሁሉ ፊት በርቶ በእኛ ምክንያት እግዚአብሔር የሚከብረው፥ እግዚአብሔርም እኛን የሚያከብረን ያን ጊዜ ነውና፡፡ ቤተ መቅደሱንና ቤተ መቅደስ ሰውነታችን ቤተ ምሥያጠ ኃጢአት አድርገነው እንደ ኾነ ወይም እንዳልኾነ ቆም ብለን እንይ፡፡ ርግብ ሻጮች ሆነን እንዳንገኝና ሥርየት የሌለው ኃጢአት እንዳያገኘን እንፍራ፡፡ ይህን ያደረግን እንደ ሆነም ጌታችን ዳግም በመጣ ጊዜ “ኑ እናንተ የአባቴ ብሩካን” ከሚላቸው ጋር አንድ እንሆናለን፡፡ዛሬም ዘወትርም እስከ ዘለዓለሙ ድረስ ክብርና ጌትነት የባሕርይ ገንዘቡ የሚሆን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በለጋስነቱና ሰውን በመውደዱ ይህን ለማግኘት የበቃን ያድርገን፥ አሜን !

የኀዘን መግለጫ

“ብንኖረም ብንሞትም ለእግዚአብሔር ነን”፤ሮሜ ፲፬፥፰

እሁድ መጋቢት ፩ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም. ከጠዋቱ ፪፡፵፰ ደቂቃ ከአዲስ አበባ ቦሌ ዓለም አቀፍ አየር ማረፊያ ተነስቶ ወደ ኬንያ ናይሮቢ በመጓዝ ላይ የነበረው ET ፫፻፪ የመንገዶኞች አውሮፕላን ከ፮ ደቂቃ በረራ በኋላ ከአዲስ አበባ በቅርብ ርቀት ከምትገኘው ደብረዘይት ወድቆ መከስከሱ ይታወቃል፡፡በመሆኑም ፻፵፱ መንገደኞች ፰ የበረራ አስተናጋጆችን ጨምሮ በድምሩ ፻፶፯ ሰዎች በሙሉ የአደጋው ሰለባ ሆነዋል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ፲፯ ያህሉ ኢትዮጵያውያን ሲሆኑ ሌሎቹ ደግሞ የ፴፫ ሀገራት ዜጎች መሆናቸው ታውቋል፡፡ በዚህ ድንገተኛ ክስተት ለተጎዱ መላው ወገኖቻችን፤ ኢትዮጵያውያንንና ቤተሰቦቻቸውን ጨምሮ እግዚአብሔር አምላክ ነፍሳቸውን በአጸደ ገነት ዕቅፍ ያሳርፍልን ፤ ለቤተሰቦቻቸውም መጽናናትን ይሰጥልን ዘንድ እንጸልያለን፡፡

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያ  ማኅበረ ቅዱሳን

‹‹እንደሚንሿሿ ጸናጽል ሆኛለሁ›› (፩ኛቆሮ.፲፫፥፩)

                                                                                                 ዲያቆን ዮሴፍ በቀለ 

ጸናጽል ድምፁ መልካም የሆነ የምስጋና መሳርያ በመሆኑ ከቀደሙት ሌዋውያን አሁን እስካሉት የሐዲስ ኪዳን ቤተ መቅደስ መዘምራን ፣ ከቀደመው የሙሴ ድንኳን ዛሬ ቤተ ክርስቲያን ድረስ በእግዚአብሔር ፊት ይዘነው የምንቆመው መሳርያ ነው፡፡ ምስጋናችንም ሆነ መዝሙራችን ያለከበሮና ጸናጽል ምን ውበት ሊኖረው ይችላል ብለን እንጀምራለን? አንጀምረውም፡፡ የሊቃውንቱ መዳፍ ያለ ጸናጽል አይንቀሳቀስም፣ ቅኔ ማኅሌቱም ያለ ከበሮ አይደምቅም ፤ እንደ ጾመ ኢየሱስ ያለ ቀን ካልገጠመው በስተቀር ቅኔ ማኅሌት ከነዚህ  ነገሮች አይለይም፤ ይገርማል! ዳሩ ግን አንድም ቀን ቢሆን በዚህ ሁሉ የአገልግሎት ዘመናቸው ወደ ቤተ መቅደስ ገብተው ለሥጋውና ለደሙ ክብር በሚደረገው አገልግሎት ተሳትፈው አይተናቸው አናውቅም፤ ጥንትም ሆነ ዛሬ አገልግሎታቸው ከውጭ ብቻ ነው፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ የባዶ ሕይወት ተምሳሌት አድርጎ ተጠቅሞበታል፤ “የሰውን ሁሉ ልሳን ባውቅ፣ በመላእክትም ቋንቋ ብናገር ፍቅር ግን ከሌለኝ እንደሚጮኽ ነሐስ፤ እንደሚንሿሿም ጸናጽል ነኝ” (፩ቆሮ ፲፫÷፩) ይላል፡፡ ይህን ስመለከት ከልጅነቴ ጀምሮ በቤተ መቅደሱ ያደገች ነፍሴን አሰብኩና እስራኤል ሲማረኩ “ጽዮንን ባሰብናት ጊዜ አለቀስን” ብለው እንደተናገሩ እኔም ለተማረከችውና ባዶዋን ለቀረችው ጽዮን ሰውነቴ አለቀስኩላት፤ ከኔ በቀር ጽዮን ሰውነቴ ባለተስፋ ምድር መሆኗን ማን ያውቅላታል? የተገባላትንስ ቃል ኪዳን ከኔ በቀር ማን ያውቅላታል?

ስለዚህ ደጋግሜ በባቢሎን ወንዞች አጠገብ ሆኜ ምርር ብየ አለቀስኩላት፤ ደግሜ ደጋግሜም እንዲህ አልኳት፤ እንደሚጮኽ ነሐስ፣ እንደ ሚንሿሿም  ጸናጽል ነሽ አልኳት፡፡ እስኪ አስቡት! ያለኔ ማኅሌቱ አይጀመር፣ ዝማሬው አይደምቅ ፣ የሊቃውንቱ ጉሮሮ አይከፈት፣ ሽብሻቧቸው አያምርበት ፣ እጃቸው ያለኔ አይንቀሳቀስ፣ ቅኔው አይጸፋ፡፡ እስኪ ንገሩኝ! ምኑ ነው ያለኔ የሚያምረው፤ በየትኛው አገልግሎት ነው እኔ የማልገባው፤ የትኛውስ ሊቅ ነው ያለኔ በእግዚአብሔር ምስጋና ላይ የተገኘው ፤ ጥንትም ሆነ ዛሬ እኔ ለዚች ቤተ መቅደስ አገልግሎት አስፈልጋለሁ ፡፡

ያለበለዚያማ ማኅሌቱ ምን ውበት ሊኖረው፤ ማንስ ነው እኔ በሌለሁበት ያለ እንቅልፍ የሚያገለግለው፤ ከከበሮው ተስማምቶ በሚወጣው መልካሙ ድምፄ ብዙዎቹ ይመሰጣሉ፣ የድምፄን ውበት በውስጠኛው ጆሯቸው እየሰሙ እንዲህ አሳምሮ የፈጠረኝን “ድምፁ መልካም በሆነ ጸናጽል አመስግኑ” እያሉ ያመሰግናሉ፡፡ የድምፄን መልካምነት ብቻ እየተመለከቱ ወይ መታደል ብለው ያደንቃሉ፤ እኔ እስከማዜም ድረስ በጉጉት ይጠባባቃሉ ፤ሰው ሲዳር፤  ሲሞትም ሆነ ሲሾም ያለኔ ምኑ ያምራል፤ አምጡት፣ አምጡት ይባላል፡፡

ይህን ሁሉ ክብሬን አየሁና በሰዎች መካከል በኩራት ተቀምጨ ሳለሁ ከዕለታት አንድ ቀን የሥጋየን መጋረጃ ግልጥ አደረግሁና ነፍሴን ተመለከትኋት፤ ትጮኻለች! አዳመጥኳት፤ ላደርገው የሚገባኝን እንኳን ያለደረግሁ፤ የማልጠቅም ባሪያ ነኝ፡፡ እንደሚጮኽ ነሐስ፣ እንደሚንሿሿም ጸናጽል ሆኛለሁ እያለች ታንጎራጉራለች፡፡

የሚጎሰመው ነጋሪት፣ የሚመታው ከበሮ፣ የሚንሿሿው ጸናጽል ለራሳቸው ምን ተጠቅመዋል? ከነሱ በኋላ እየተነሣ ስንት ትውልድ ነው የእግዚአብሔርን መንግሥት የወረሰ፣ ከተስፋው  የደረሰ፤ ሌላው በነሱ ተጠቅሞ አድማሳትን በቅድስናው ሲያካልል፣ መላእክትን ሲያክል፤ እነሱ ግን አሁንም ምድራውያን ናቸው፡፡ በዚህኛው ትውልድም አልተለወጡም፤ ጌታ እስኪመጣ ከዚህ ዓይነት ሕይወት የሚወጡም አይመስሉም፤

እኔም እንደነሱ ነኝ! ቃሉን እሰብካለሁ፣ ዝማሬውን እዘምራለሁ፣መወድሱን እቀኛለሁ፣ሰዓታቱን አቆማለሁ፤ ኪዳኑን አደርሳለሁ፤ መጽሐፍ ቅዱስን ከዳር እስከዳር አንብቤአለሁ፡፡ ዳሩ ግን መች እኖርበታለሁ ፤ ሰዎቹ ከአፌ የሚወጣውን ቃሉን እየሰሙ የሕይወቴ ነጸብራቅ እየመሰላቸው ይገረማሉ፤ እንደኔ ለመሆን ይቀናሉ፤ እኔ ግን ሳላስበው እንደሚጮኽ ነሐስ፣ እንደሚንሿሿም ጸናጽል ሆኛለሁ፡፡  እጮኻለሁ እንጅ  ለምን እንደምጮኽ እንኳን አላውቅም፤ በምጮኸው ጩኸት ከቶ አልለወጥም፤ ከኔ በኋላ እየተነሱ ብዙዎቹ ከምሥራቅና ከምዕራብ እየመጡ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ገብተዋል ፤ ከኔ በኋላ ቃሉን የሰሙት በቃሉ ተለውጠው ንስሓ ገብተዋል፡፡ እኔ ግን ዛሬም ሳያውቅ እንደሚጮሕ ነሐስ፣ ሳይወድ እንደሚንሿሿውም ጸናጽል ሆኛለሁ፡፡

የምጮኸው ገብቶኝ ቢሆንኮ ከኔ የሚቀድም ማንም አልነበረም፡፡ ነገር ግን ይህ እንዳይሆን ሕይወት የሌለኝ ቆርቆሮ ነኝ፤ ድምፄ መልካም ነው፣ ትጋቴ ግሩም ነው፡፡ ከምስጋናው ጋር መስማማቴ፣ በሁሉም እጅ መግባቴ መልካም ነበር፤ ሆኖም ፍቅር የለኝምና ምን ይሆናል፡፡  ሥጋየን ለሰማይ አዕዋፍ ብሰጥ ፣ያለኝንም ለድሆች ባካፍል ፣ የድሆች አባት ብባል ፣አጥንቴም እስኪታይ ብጾም ብጸልይ ፍቅር ግን ከሌለኝ ያው እንደሚጮኸው ነሐስ እንደሚንሿሿውም ጸናጽል መሆኔ አይደለ? ሥጋውን ደሙን ካልተቀበልኩ የኔ መጮኽ ምን ሊጠቅም ! ለካ ለሥጋውና ለደሙ የሚያስፈልገው በበጎ ዝምታ ዝም ያላለው እንደኔ የሚንሿሿው ጸናጽል አይደለም ብላ ነፍሴ ስታለቅስ እኔንም አስለቀሰችኝ ፡፡

ኦ!አምላኬ ጸናጽልነቴን ለውጥልኝ፣ነሐስነቴን አርቅልኝ!

  ‹‹እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁኑ›› (ዘሌ.፲፱፥፪)

 

መምህር ኃይለሚካኤል ብርሀኑ

የዐቢይ ጾም ሁለተኛው ሳምንት (ሰንበት) ቅድስት ይባላል፡፡ ስያሜው የቅዱስ ያሬድ ሲሆን የመዝሙሩ ርዕስ የጾመ ድጓው መክፈያ ሆኖ የሚጠራበት ስም ነው፡፡ ከቅድስት ሰኞ ጀምሮ ጾመ ኢየሱስ ይባላል፡፡ በዚህ ሳምንትም ስለ እግዚአብሔር ቅድስና የሚያነሱ መዝሙራት ይቀርባሉ፤ እኛም እግዚአብሔርን መቀደስ (ማመስገን) እንዳለብን የሚገልጹ ምንባባት ይነበባሉ፣ትምህርት ይሰጣል፡፡

እግዚአብሔር ቅዱስ ነው፤ ቅድስናውም ከማንም ያላገኘው የባሕርይ ገንዘቡ ነው፡፡ ይህም ማለት እግዚአብሔር በባሕርዩ ቅዱስ ነው፡፡ ቅዱሳን መላእክት፣ቅዱሳን ጻድቃን፣ቅዱሳን ሐዋርያት፣ ቅዱሳን ሰማዕታት፣ ቅዱሳን አበው፤ ቅዱሳት አንስት፤ ቅዱሳን ሊቃውንት፣ቅዱሳን ጳጳሳት፣ ቅዱሳን መነኮሳት፣ ቅድስናን ያገኙት በባሕርዩ ቅዱስ ከሆነው ከአምላካችን ከቅዱስ እግዚአብሔር ነው፡፡

ቅዱስ የሚለውን ቃል ስንመለከት ምስጉን፣ክቡር፣ንጹሕ፣ የተለየ የሚል ትርጉም ይሰጣል፡፡ እግዚአብሔር ቅዱስ ነው ስንልም ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ ተብሎ የሚመሰገን፤ የቅድስና ምንጭ በቅድስናው የተቀደሰ፤ ቅዱሳንን የሚቀድስ ቅዱሰ ቅዱሳን ነው፤ኢሳ (፮፥፩)፡፡

ፍጡራንስ ቅዱስ ተብለው መጠራታቸው እንዴት ነው? ብለን ብንጠይቅ  እግዚአብሔር ከፍጥረቱ ሁሉ የተለየ ቅዱስ ስለሆነ ወደ እርሱ የተጠሩና የመጡ ለእርሱ ክብር የተለዩ ቅዱሳን ይባላሉ፡፡ ይህም ማለት  ቅድስናን በጸጋ አግኝተው እንዲያጌጡበት የተጠሩት ሰውና መላእክት ሲሆኑ ለእግዚአብሔር አገልግሎት የዋሉ የመቅደሱ ዕቃዎች አልባሳቶች በአጠቃላይ ንዋያተ ቅዱሳቱ ቅዱስ ተብለው ይጠራሉ፡፡ እኛም እግዚአብሔር በክርስቶስ ኢየሱስ ወደ መንግሥቱ ሲጠራንና ልጅነትን ሲሰጠን ለእግዚአብሔር ተለይተን የመንፈስ ቅዱስ ማደሪያዎች እንሆናለንና፤ቅዱሳን ተብለን እንጠራለን፡፡

 እግዚአብሔር ‹‹እኔ ቅዱስ ነኝና ቅዱሳን ሁኑ›› ብሎ እንደተናገረው ንጽሕናን ቅድስናን በጸጋ እግዚአብሔር ገንዘብ ያደረጉ ሰዎች ቅዱሳን ይባላሉ፡፡ እንዲሁም ሰውና መላእክት የሚገናኙባት፣ድኅነተ ሥጋ ድኅነተ ነፍስን የምታስገኝ ቤተ ክርስቲያን ቅድስት ናት ስንል ለእግዚአብሔር አምልኮ የተለየች ክብርትና ንጽሕት ናት ማለት ነው፡፡ ክርስቶስ ለራሱ ትሆን ዘንድ የለያት ነፍሱን ስለ እርስዋ አሳልፎ እስከ መስጠት የወደዳት ፣ በደሙ የዋጃትና በቃሉ ያነጻት የክርስቶስ አካሉ ቤተ ክርስቲያን ንጽሕት ናትና ክርስቶስ ክቡር እንደሆነ ክብርት፣ ንጹሐ ባሕርይ እንደሆነ ንጽሕት፣ ያለ ነውርና ያለ ነቀፋ የኖረች የክርስቶስ ሙሽራ ናት  ማለታችን ነው፡፡

ፍጡራን የቅድስናቸው ምንጭ ቅዱስ እግዚአብሔር ነው፤ ከላይ እንዳየነው እርሱ የቅዱሳን ቅዱስ ነውና፡፡ በሙሴ መጽሐፍ እንደ ተጠቀሰው እስራኤልን እግዚአብሔር ከግብጻውያን እጅ እንዳዳናቸውና ግብጻውያንም እንደሞቱ በባሕር ዳር አዩ፡፡ ቅዱስ እግዚአብሔር በግብጻውያን ላይ ያደረጋትን  ታላቂቱን እጅ አዩ፡፡ ሕዝቡም እግዚአብሔርን ፈሩ፤ በእግዚአብሔርም አመኑ፤ ባሪያውንም ሙሴን አከበሩ፡፡ በአንድነትም በዝማሬ እግዚአብሔርን አመሰገኑ፤ በዝማሬያቸውም የእግዚአብሔርን ቅድስና እንዲህ ሲሉ ገለጹ ‹‹አቤቱ በአማልክት መካከል አንተን የሚመስል ማን ነው? በቅዱሳንም ዘንድ እንደ አንተ የከበረ ማን ነው? በምስጋና የተደነቅህ ነህ፤ ድንቅንም የምታደርግ ነህ፤ ቀኝህን ዘረጋህ ምድርም ዋጠቻቸው›› (ዘፀ ፲፭፥፲፩) በማለት መስክረዋል፡፡

አምላከ አማልክት፤ እግዚአ አጋዕዝት ጌታ በቅድስና የከበረ ነው፡፡ ምስጋናውም ቅዱስ እንደሆነ ያየውና የሰማው ኢሳይያስ ስሙን ቅዱስ ብሎ ጠርቶታል፡፡ ‹‹እንግዲህ እተካከለው ዘንድ በማን መሰላችሁኝ?›› (ኢሳ ፵፥፳፭) ይላል ቅዱሱ እግዚአብሔር፡፡

  ቅዱስ ዮሐንስም በራእዩ እንደተናገው ‹‹አንተ ብቻ ቅዱስ ነህ›› ብለው መላእክት በሰማይ በባሪያው በሙሴ መዝሙር እንደሚያመሰግኑት ጽፎልናል፡፡ ‹‹ሁሉን የምትገዛ ጌታ አምላክ ሆይ! ሥራህ ታላቅና ድንቅ ነው፤ የአሕዛብ ንጉሥ ሆይ መንገድህ ጻድቅና እውነት ነው፤ ጌታ ሆይ አንተን የማይፈራና ስምህን የማያከብር ማን ነው? አንተ ብቻ ቅዱስ ነህና፡፡  በአሕዛብ ሁሉ ላይ ሥልጣን ያለህ አንተ ነህ፤ አቤቱ ፍጥረትህ ሁሉ በፊትህ ይሰግዳሉ፤ ፍርድህ ተገልጦአልና››፤ (ራእ.፲፭፥፫) ይላል፡፡

በአፈ መላእክት ቅዱስ ተብሎ የሚጠራውና የሚቀደሰው በልሳነ ሰብእም ይትቀደስ ስምከ (ስምህ ይቀደስ) እየተባለ የሚጠራ ስሙ ቅዱስ ነው፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ ቅዱሳን መላእክት ቅዱስ ስሙን እየጠሩ እንደሚያመሰግኑት ሲመሰክር “አንዱም ለአንዱ ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ የሠራዊት ጌታ እግዚአብሔር ምድር ሁሉ ከክብሩ ተሞልታለች እያለ ይጮኽ ነበር” ሲል ገልጾታል(ኢሳ.፮፥፫)፡፡

ቅዱሱን የወለደች እመ አምላክ ድንግል ማርያምም “ወቅዱስ ስሙ፤ስሙ ቅዱስ ነው ብላ መስክራለች” (ሉቃ.፩፥፶)፡፡ ቅዱስ እግዚአብሔር ስለ ራሱ ቅድስና ሲናገርም “እኔ እግዚአብሔር አምላካችሁ ቅዱስ ነኝና እናንተም ቅዱሳን ሁኑ” (ዘሌ.፲፱፥፪) ብሏል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስም በመልእክቱ የእግዚአብሔር ፈቃድ በእርሱ ቅድስና እንድንቀደስ እንደሆነ ሲገልጽ “የጠራችሁ ቅዱስ እንደሆነ እንዲሁ እናንተም በአካሄዳችሁ ሁሉ ቅዱሳን ሁኑ” ይላል (፩፥፲፭)፡፡

የጠራን እግዚአብሔር ቅዱስ እንደሆነ በቅድስና መኖር ያስፈልጋል፡፡ ከእግዚአብሔር የተወለድንበት ምሥጢረ ጥምቀት የቅድስናችን መጀመሪያ ስለ ሆነ የመንፈስ ቅዱስ ቤት ለመሆን ተሠራን፡፡ ነገር ግን ከቅድስና የሚያጎድሉንን ክፉ ተግባራት ስንፈጽም እንበድላለንና በጸጋ ያገኘነውን ሀብተ መንፈስ ቅዱስ እናጣለን፡፡ ስለዚህ እንዳንበድልና ቅድስናን እንዳናጣ ተግተን በእውነት እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ መኖር ያስፈልጋል፡፡