የምእመናን ተሳትፎ የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት የጠበቀ ሊሆን ይገባዋል

                     

በሕይወት ሳልለው

የሰው ልጅ ሕይወት፤ድኀነት፤ሰላም፤ ፍቅርና ደስታ መገኛ እግዚአብሔር፤ ከሕገ ኦሪት ጀምሮ በሰጠን የድኀነት መንገድ፤ በመስቀሉ ላይም በከፈለልን መሥዋዕትነት የተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፤ከጥንት ጀምሮ ምእመናንን በመሰብሰብና በማሰተባበር ሥርዓተ አምልኮን እንዲፈጽሙ ስታስተምር ኖራለች፡፡ በሕገ ወንጌልም አምላካችን በአስተማረን መሠረት የክርስቲያኖች መማፀኛ የሆነችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፤ልጆቿን በፍቅርና በሥርዓት እንድታሳድግ ፈቅዷልና በእምነት፤ እንድናከብራት የእግዚአብሔር  ፈቃድ ነው፡፡

 “በብሉይ ኪዳን ይኖሩ የነበሩ ምእመናን በሕገ ልቦና (ባልተጻፈ ሕግ) ይመሩ የነበሩ አበው እና በሕገ ኦሪት (በተጻፈ ሕግ) የነበሩ ቅዱሳን አባቶች አካሄዳቸውን ከእግዚአብሔር ጋር በማድረጋቸው የእግዚአብሔር ረድኤት ያልተለያቸው ነበሩ፡፡የሐዲስ ኪዳንን ስንመለከት “በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ የባሕር አምላክነት አምነው፤ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የተጠመቁ ክርስቲያኖች ናቸው”፤ (የምእመናን ድርሻ በቤተ ክርስቲያን)፡፡

 አንድ አምላክ፤አንዲት ጥምቀት፤ አንዲት ሃይማኖት፤(ኤፌ4፥4) ይህን የክርስትና ሕይወት መርሕ መሠረት አድርገው የሚኖሩ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ተከታዮች፤ ለብዙ ዓመታት  ሥርዓተ አምልኮን በሚፈጽሙባት ቤተ ክርስቲያን፤ ከሃይማኖት አባቶች፤ ከካህናት፤ እንዲሁም ከሌሎች አገልጋዮች ጋር የሚያደርጉት ሱታፌ እምነታችውን፤ሥርዓታቸውንና አምልኮታቸውን ለማጠንከር ይረዳልና፤ በሕገ ቤተ ክርስቲያን መኖር ያስፈልጋል፡፡ አብዛኞቹ  ኦርቶዶክሳውያን  ምእመናን  ዓመታዊ ክብረ በዓላት ላይ ብቻ ነው፡፡

መንክር መኩሪያና ዳዊት ጌታቸው ጥር ፲፩ ቀን ፳፻፲፩ የጥምቀት በዓልን በጃንሜዳ ሲያከብሩ ያገኘናቸው ወጣቶች ናቸው፡፡መንክር ጥምቀትን ከልጅነት ጀምሮ ስለሚያከብር በየዓመቱ ጃንሜዳ ይመጣል፡፡“በዘንድሮ በዓል በበገናውና መሲንቆ፤በመዘምራንንና መዝሙሮች የቀደመውን ሥርዓት የበለጠ ወድጄዋለው፡፡አገልጋዩቹም ባሕልና ትውፊታቸንን ይዘው በመቅረባቸው እናመሰግናቸዋለን”፡፡

 

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ትውፊት፤ሥርዓትና፤ቀኖና በዓላትን ከማክበር በተጨማሪ የቤተ ክርስቲያንን ሥርዓት በተገቢው የመፈጸም ኃላፊነት እንዳለብን ያስታውሰናል፡፡ ወጣት  መንክር “አንዳአንድ የአስተዳዳር ችግር በመኖሩ ቅር ብሎኛል፡፡ካህናት እንዲሁም ሌሎች አገልጋዩች እኛን ሰብስበው አልያዙንም ከዘመኑ ጋር የመራመድ መሠረታዊ ችግር አለ፡፡ በዓልን ለማክበር ብቻ መገናኘት በቂ  አይደለም፡፡ የሃይማኖት አባቶች በጎቻቸውን  ተግተው መጠበቅ ይኖርባቸዋል”፤ሲል ቅሬታውን ገልጿል፡፡ዳዊትም ይህንን ሀሳብ በመጋራት “የአከባበር ሥርዓቱ ደስ ቢልም፤ የካህናትና የምእመናንን ኅብር ለበዓል ብቻ መሆን የለበትም፡፡ካህናት የሰንበት ትምህርት ቤቶችን ማበረታታና ድጋፍ መስጠት አለባቸው”፡፡ ብሏል

አስተባባሪዎችና ሌሎች የቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች አስፈላጊውን አገልግሎት በበዓላት ቀንና በቤተ ክርስቲያን ሥርዓት በወቀቱ እንደሚሰጡ ቢታመንም፤እነዚህ ችግሮች ሊከሰቱ የቻሉት በአስተዳደር ችግር መሆኑን እንደ መንክር ያሉ ግለሰቦች ይናገራሉ፡፡

 የቅዱስ ጳውሎስ የሐዲስ ኪዳን መምህር መጋቤ ሐዲስ አእምሮ ደምሴ ስለዚህ ጉዳይ አነጋግረናቸው ነበር፡፡ እሳቸውም “ጉድለቶች አይጠፉም፡ የምእመናን ሱታፌ ለመጨመር ሁሉም የየድርሻቸውን መወጣት አለበት፡፡የካህናቱ ድርሻ መቀደስ፤ ማስተማርና  እና መዘመር በመሆኑ ከምእመናኑ ጋር ኅብር ለመፍጠር የሚቻለው ምእመናን የምስጋናንና፤የመዘመርን ሥርዓት ሲያዘወትሩ ነው” ይላሉ፡፡ሆኖም ግን ትምህርተ ሃይማኖትን በበቂ ሁኔታ አለመማርና አለመተግበር በወጣቱ ላይ ያመጣው አሉታዊ ተፅእኖ እንዳለም ጨምረው ገልጸዋል፡፡ በማኀበር የተደራጁ ወጣቶች ስሕተት መሆኑን ባለመረዳት ቅዱሳት ሥዕላትን ባልሆነ ቦታ ላይ የሚለጥፉና ለማስዋቢያ የሚጠቀሙ እንዳሉም ታይቷል፡፡ነገር ግን እነዚያ ቅዱሳት ሥዕላት በክብር ቦታቸው ሆነው የሚጸለይባቸው ስለሆኑ ተገቢ ባልሆነ ስፍራ መታየት እንደሌለባቸው በአጽንዖት አሳስበዋል፡፡

 “በቲሸርትና ሌሎች አልባሳት ላይ ቅዱሳት ሥዕላትን ማሳተም ትክክል አይደለም፡፡ ምክንያቱም ልብሱ ሊቆሽሽ፤ሊቀደድና ሊጣል ይችላል፡፡እነዚያ ሥዕሎች ቅዱስ በመሆናቸው ለበረከት ብለን የምናደርገው ወደ መርገም እንዳይለወጥብን ለቅዱሳት ሥዕላት ጥንቃቄ ማድረግ አለብን፡፡የምናገለግለውንም አገልግሎት ያደበዝዝብናል፡፡ሌሎች ጹሑፎችን መጻፍ ለምሳሌ የእንኳን አደረሳችሁ መልእክትን ማስተላለፍ ይቻላል” ይህ የግንዛቤ እጥረት የፈጠረው ችግር ለምእመናን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት  ሥርዓትና ትውፊት እንዳልሆነ ማስረዳት ይገባል፡፡እነዚህንም ወጣቶች ከስሕተት ለመመለስ የሃይማኖት መሪዎች የማስተማርና የመምከር ከባድ  ኃላፊነት አለባቸው፡፡

በሌላ በኩል ግን መጋቤ ሐዲስ  አእምሮ የበዓል አከባባር ላይ ወጣቶች ቤተ ክርስቲያን የማገልገል ሥራ በራሳቸው ተነሳሽነትና ለበረከትም የሚያደርጉትን ተግባር ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን የጠበቀ እንዲሆን በማስገንዘብ፤ በዐበይት በዓላት አከባባር ላይ ከአዲስ አበባ ጅምሮ እስከ ገጠር ቤተ ክርስቲያን ድረስ ወጣቱ የሚሰጠው አገልግሎት በአስተማሪነቱ የሚወሰድ መልካም ተግባር ነው፡፡ታቦታት ወደ ማደሪያቸው ከመድረሳቸው አስቀድመው አካባቢውን በማጽዳት፤ ሕዝቡን በመቀስቀስ፤ታቦታቱ የሚያርፉበትንና የሚጓዙበትን መንገድ በማስዋብ፤ ምንጣፍ በማንጠፍና ቄጤማ በመጎዝጎዝ፤ አቧራንና ድካምን ችለው ሲያገለግሉ ይውላሉ” ሲሉ የወጣቶችን ተሳትፎ በአድናቆት ይገልጹታል፡፡