በሰሜን ሸዋ ሰላሌ ሀገረ ስብከት የተሰረቁት የቅዱስ ገብርኤል፤የቅዱስ ዮሐንስና የገብረ ክርስቶስ ጽላቶች መገኘታቸውን ፖሊስ ገለጸ

በሕይወት ሳልለው

ሰኞ መጋቢት ፲፮ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም.፤ የቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ከመቃጠሉ በፊት የቅዱስ ገብርኤልና የበዓለወልድ ጽላቶች በመሰረቃቸው በወቅቱ በአካባቢው ሰዎች መካከል የተፈጠረውን አለመግባባት መዘገባችን ይታወሳል፡፡ ለወረዳው ፖሊስ አስተዳደር በማመልከታቸውም በተደረገው ከፍተኛ ርብርብ፤ የቅዱስ ገብርኤል ጽላት ከሂደቡ አቦቴ ወረዳ እንድሪስ ወንዝ ውስጥ ሊገኝ እንደቻለ ፖሊስ ይፋ አድርጓል፡፡ ሆኖም ግን የበዓለወልድ ጽላት እስከአሁን እንዳልተገኘ አያይዞ አስታውቋል፡፡

በተመሳሳይ መልኩም መጋቢት ፲፬ ቀን ፳፻፲፩ ዓ.ም ከቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን የተሰረቁት የቅዱስ ዮሐንስና የገብረ ክርስቶስ ጽላቶች መገኘታቸውንም ፖሊስ ጨምሮ ገልጿል፡፡በዕለቱ የሰንበት ትምህርት ቤት ተማሪዎችና የማኅበረ ቅዱሳን አባላት ከሌሊቱ ፲ ሰዓት ኪዳን ለማድረስ ወደ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተ ክርስቲያን በደረሱበት ወቅት የቤተ መቅደሱ በር ተከፍቶ እንዳገኙትና በመደናገጥ ፍለጋ ቢጀምሩም ማግኘት እንዳልቻሉ ተናግረዋል፡፡ የቅዱስ ዮሐንስና የገብረ ክርስቶስ ጽላት፤ እንዲሁም ንዋያተ ቅድሳት በቦታቸው እንዳልነበሩ ሊገነዘቡም ችሏል፡፡ የማኅበሩ አባላትና የሰንበት ተማሪዎቹም በመደናገጥ ሁሉም በየፊናቸው ከሌሊቱ ፲፩ ሰዓት ጀምሮ ለፍለጋ እንደተሰማሩና እስከ ማግሥቱ ቀን ፲ ሰዓት ድረስ ማግኘት እንዳልቻሉ ጠቅሷል፡፡

ነገር ግን የሰንበት ተማሪ በሆነው ወጣት አብርሃም ታደሰ አማካኝነት በተገኘው ፍንጭ ከተጠረጠሩት ግለሰቦች አንደኛውን በመለየት ወንጀሉን ለፖሊስ አሳውቀዋል፡፡ የቀረበውን ሪፖርት በመመርኮዝ ፖሊስም የተጠረጠሩትን ሦስት ግለሰቦች በመከታተል መኖሪያ ቤታቸውን ከማወቁም በላይ ፍተሻ በማድረግ ከተጠርጣሪዎቹ አንደኛው ቤት ውስጥ የቅዱስ ዮሐንስና የገብረ ክርስቶስ ጽላትን ለማግኘት ችሏል፡፡ የጠፉትንም ንዋያተ ቅድሳት ተራራ ላይ ወስደው ማቃጠላቸውን ወንጀለኞቹ ከሰጡት ሪፖርት አረጋግጧል፡፡ ይህንንም ችግር ለመፍታት የሃይማኖት አባቶች በዚህ ወቅት ስብሰባ በማካሄድ አፋጠኝ የመፍትሔ እርምጃ እንደሚወስዱ ለማኅበራችን አሳውቀዋል፡፡