ፍልሰተ ዐፅሙ ለአቡነ ተክለ ሃይማኖት

በዝግጅት ክፍሉ

ግንቦት ፲፩ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ቅዱሳን ጻድቃን በሕይወተ ሥጋ ሳሉም ኾነ ካረፉ በኋላ (በዐጸደ ሥጋም ኾነ በዐጸደ ነፍስ) በጸሎታቸው ለሚታመኑ፣ በቃል ኪዳናቸው ለሚማጸኑ ምእመናን በመጸለይና ወደ እግዚአብሔር በማማለድ ድኅነተ ሥጋ፣ ድኅነተ ነፍስን የሚያስገኙልን የችግር ጊዜ አማላጆቻችንና አስታራቂዎቻችን ናቸው፡፡ ቅዱሳን በጸሎታቸውና በትምህርታቸው ከከበቡን የነፍስ ጠላቶች፤ ከርኲሳን መናፍስትና ከጨለማው ልጆች፤ ከክፉ ሰዎች ሽንገላና ተንኰል ለመሰወርና ለመጠበቅ ከእግዚአብሔር የተቀበሉት ሥልጣን ምን ጊዜም ሲሠራ ይኖራል፡፡ በጻድቃን መኖር አገር ከጥፋት ትድናለች፡፡

የጻድቃንን ስም ጠርቶ እግዚአብሔርን በመለመን በረከትና ረድኤት ይገኛል፡፡ ስለ ጻድቃን ብሎ እግዚአብሔርም ምሕረቱን ያድላል፡፡ እነርሱን ማሰብና ማክበር፣ ሥራቸውንም መዘከር ክርስቲያናዊ ሕይወታችንን ያጐለምሳል፡፡ ለድኅነተ ሥጋ፣ ለድኅነተ ነፍስ ይረባል፤ ይጠቅማል፡፡ ስለዚህም ነው ቅዱስ ወንጌል ቅዱሳን ጻድቃንን እንድናስባቸው፣ በስማቸውም ለድሆችና ለጦም አዳሮች እንድንመጸውት፣ መታሰቢያቸውን እንድናደርግ የሚመክረን፤ የሚያስተምረን (ማቴ.፲፥፵፩-፵፪)፡፡ ከእነዚህ ቅዱሳን መካከልም ኢትዮጵያዊው ጻድቅ አቡነ ተክለ ሃይማኖት አንደኛው ናቸው፡፡

በየዓመቱ ግንቦት ፲፪ ቀን ቅዱስ ሚካኤል ሊቀ መላእክት፣ ኢትዮጵያዊው ንጉሥ እስክንድር፣ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ፣ ቅዱስ መስቀል፣ ቅዱስ እስጢፋኖስ፣ ቅዱስ ሚናስ፣ የመላልዔል ልጅ ያሬድ እና ጻድቁ አቡነ ተክለ ሃይማኖት በቤተ ክርስቲያናችን ይታሰባሉ፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን የጻድቁ አባታችንን የፍልሰተ ዐፅም ታሪክ የስማቸውን ትርጕም በማስቀደም እንደሚከተለው በአጭሩ አቅርበነዋል፤

‹ተክል› ማለት ፍሬያማ ዕንጨት፣ ዛፍ፣ ቅመም፣ ቅጠላ ቅጠል፣ የሚበላ፣ የሚሸተት፣ ገነታዊ ዕፅ፣ እንዲሁም ሕግ ሥርዓት ማለት ነው (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ፤ ማቴ.፲፭፥፲፫)፡፡ ‹ሃይማኖት› ማለት ደግሞ በሀልዎተ እግዚአብሔር፣ በእግዚአብሔር አምላክነት፣ በሥላሴ አንድነትና ሦስትነት፣ በቅዱሳን ተራዳኢነት ማመን፤ አምኖም መመስከር ማለት ነው፡፡ ‹ተክለ ሃይማኖት› የሚለው ሐረግም የሃይማኖት ተክል፣ ይኸውም የጽድቅ ፍሬን ያፈራና ከኃጢአት ሐሩር ማምለጫ ዛፍ፤ ምእመናንን በቃለ ወንጌል ያጣፈጠ ቅመም፤ መዓዛ ሕይወቱ የሚማርክ፣ ቢመገቡት ረኃበ ነፍስን የሚያስወግድ ቅጠል፤ የጻድቃን መጠለያ ዕፅ የሚል አለው፡፡ መጽሐፈ ገድላቸውም ‹‹ተክለ ሃይማኖት ማለት የአብ፣ የወልድ፣ የመንፈስ ቅዱስ ተክል ማለት ነው›› በማለት የስማቸውን ትርጕም ያትታል፡፡ ጻድቁ አባታችን ተክለ ሃይማኖት በአሚነ ሥላሴ ጸንተው ሌሎችንም እንዲጸኑና እንዲያምኑ አድርገዋልና፡፡

‹‹… ስምዑ ወለብዉ ፍቁራንየ መጽሐፈ ዜናሁ ለክቡር ወቅዱስ ወለብፁዕ ፍቁረ እግዚአብሔር ዘይትነበብ በዕለተ ፍልሰተ ሥጋሁ አመ ፲ወ፪ ለግንቦት ውእቱ ድሙር ምስለ በዓለ ትንሣኤሁ ለእግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ ወበዓለ ሚካኤል ሊቀ መላእክት ፍቁሩ ለተክለ ሃይማኖት፤ ወዳጆቼ ሆይ፣ የከበረ፣ የተቀደሰ፣ የተደነቀ፣ የእግዚአብሔር ወዳጅ የሚኾን የአባታችን የተክለ ሃይማኖትን ክብሩን፣ ገናንቱን የሚናገረውን፤ ዐፅሙ በፈለሰበት ግንቦት ፲፪ ቀን የሚነበበውን መጽሐፍ አስተውላችሁ ስሙ፡፡ ይኸውም ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤ በዓል እና ከተክለ ሃይማኖት ወዳጅ ከሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል በዓል ጋር የተባበረ ነው …፤›› (ገድለ ተክለ ሃይማኖት ምዕ.፷፪፥፭-፰)፡፡

አቡነ ተክለ ሃይማኖት በ፲፫ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጀመሪያ አካባቢ በአገራችን ኢትዮጵያ ምድር በሰሜን ሸዋ ሀገረ ስብከት ኢቲሳ (ደብረ ጽላልሽ) ከአባታቸው ካህኑ ጸጋ ዘአብ እና ከእናታቸው እግዚእ ኀረያ አብራክ የተገኙ ቅዱስ አባት ናቸው፡፡ አባታችን ሕይወታቸዉን ሙሉ ለእግዚአብሔር በመስጠት፣ እንደ በሬ ተጠምደው፣ እንደ ገበሬ ታጥቀው ይህንን ዓለም ንቀው፣ በጾም በጸሎት ተወስነው፣ በብሕትውና ከመኖራቸው ባሻገር እንደ ቅዱሳን ሐዋርያት ወንጌልን በመላው ኢትዮጵያ እየተዘዋወሩ የሰበኩ፣ በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ድውያነ ሥጋን በተአምራት፣ ድውያነ ነፍስን በትምህርት የፈወሱ ሐዋርያ ናቸው፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችንም ይህንን ውለታቸውን በማሰብና ከእግዚአብሔር ዘንድ የተሰጣቸውን ቅድስና መሠረት አድርጋ በስማቸው ጽላት ቀርፃ ስታከብራቸው ትኖራለች፡፡

አቡነ ተክለ ሃይማኖት በዚህ ዓለም የኖሩበት ዕድሜ ዘጠና ዘጠኝ ዓመት ከዐሥር ወር ከዐሥር ቀን ነው፡፡ በእናት አባታቸው ቤት ፳፪ ዓመት፤ በከተታ ፫ ዓመት፤ በዊፋት ፱ ወር፤ በዳሞት ፲፪ ዓመት፤ በአማራ ፲ ዓመት፤ በሐይቅ ፲ ዓመት፤ በደብረ ዳሞ ፲፪ ዓመት፤ በትግራይ ገዳማት በመዘዋወርና ወደ ኢየሩሳሌም በመመላለስ ፩ ዓመት፤ ዳዳ በሚባል አገር ፩ ወር፤ በአሰቦ ገዳም ፳፱ ዓመት ከ፲ ቀን መቆየታቸውን መጽሐፈ ገድላቸው ይናገራል (ገ.ተ.ሃ ፶፱፥፲፬-፲፭)፡፡

ጻድቁ አባታችን ምድራዊ ሕይወታቸውን በተጋድሎና በሐዋርያዊ አገልግሎት ከፈጸሙ በኋላ ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ የሚያልፉበት ቀን በተቃረበ ጊዜ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእናቱ ከቅድስት ድንግል ማርያም፣ ከቅዱሳን መላእክት፣ ከቅዱሳን ነቢያትና ከቅዱሳን ሐዋርያት ጋር ወደ እርሳቸው በመምጣት የሚያርፉበት ዕለት መድረሱን ነግሯቸው፣ የተጋድሏቸውን ጽናት አድንቆላቸው በስማቸው መታሰቢያ ለሚያደርጉ፣ ለነዳያን ለሚመጸዉቱ ቤተ ክርስቲያን ለሚያሠሩ የምሕረት ቃል ኪዳን ሰጥቷቸው በክብር በምስጋና ወደ ሰማይ ዐረገ፡፡

አቡነ ተክለ ሃይማኖትም የዕረፍት ጊዜያቸው መቃረቡን ባወቁ ጊዜም የመንፈስ ልጆቻቸውን ጠርተው ጌታችን የነገራቸውን ዅሉ አስረድተው አባታዊ ምክርና ተግሣፅ ከሰጧቸው በኋላ ነሐሴ ፳፬ ቀን ከዚህ ዓለም ድካም ዐረፉ፡፡ የመንፈስ ልጆቻቸውም ለአንድ ቅዱስ አባትና ካህን በሚገባ ሥርዓት በማኅሌት፣ በዝማሬና በምስጋና ቀበሯቸው፡፡ ጌታችንም ከእመቤታችንና ከቅዱሳን መላእክት ጋር ተገልጾ ታያቸው፤ ነፍሳቸውንም ‹‹የጠራሽ፣ ንጽሕት ነፍስ ሆይ! ወደ እኔ ነዪ›› ብሎ በክብር ተቀበላት፡፡

ወደ ፍልሰተ ዐፅማቸው ታሪክ ስንመለስ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ ከተለዩ በ፶፯ኛው ዓመት የካቲት ፲፱ ቀን ለመንፈስ ልጃቸው ለአባ ሕዝቅያስ ብርሃን ለብሰው በሕልም ተገለጡላቸውና ‹‹ወዳጄ ሕዝቅያስ ሆይሰላም ለአንተ ይኹን! ጌታዬበኋለኛው ዘመን ከዚህ ሥፍራ ልጆችህ ሥጋህን ያፈልሳሉያለኝ ዘመን ደርሷልና ሳትዘገይ ልጆቼን ዅሉ ቅጠራቸውና እስከምፈልስበት ቀን ድረስ ግንቦት ፲፪ ቀን ይሰብሰቡ፡፡ እናንተም በምስጋና በጸሎት መንፈሳዊ በዓልን አድርጉ፡፡አባቴ ተክለ ሃይማኖትየሚለኝ ዅሉ በዚህች በፍልሰተ ዐፅሜ ቀን ይምጣ፤ መንፈሳዊ በዓልንም ያድርግ፡፡ እኔና ቅዱስ ሚካኤል ከወዳጄ አባ ፊልጶስ ጋር ስለ እኔ ፍቅር የተሰበሰበውን ሕዝብ ልንባርክ እንመጣለን፤›› ከአሏቸው በኋላ ተሠወሯቸው፡፡

አባ ሕዝቅያስም እንደ ታዘዙት ‹‹የአባታችሁን ዐፅም ከዋሻው ወደ ታላቁ ቤተ ክርስቲያን ታፈልሱ ዘንድ ኑ፤ ተሰብሰቡ›› ብለው የአባታችን ወዳጆች ባሉባቸው አገሮች ዅሉ መልእክት ላኩ፡፡ ምእመናንም ጥሪውን ተቀብለው በዓሉን ለማክበር ከአራቱም አቅጣጫ ተሰበሰቡ፡፡ ዐሥራ ሁለቱ መምህራንም መጡ፤ እነዚህም፡- የወረብ አገሩ አባ አኖሬዎስ፣ የፈጠጋሩ አባ ማትያስ፣ የእርናቱ አባ ዮሴፍ፣ የሞረቱ አባ አኖሬዎስ፣ የመርሐ ቤቴው አባ መርቆሬዎስ፣ የጽላልሹ አባ ታዴዎስ፣ የወገጉ አባ ሳሙኤል፣ የወንጁ አባ ገብረ ክርስቶስ፣ የድንቢው አባ መድኃኒነ እግዚእ፣ የዳሞቱ አባ አድኃኒ፣ የክልአቱ አባ ኢዮስያስ እና የመሐግሉ አባ ቀውስጦስ ናቸው፡፡

እነዚህ መምህራን ከአባ ሕዝቅያስ ጋር በመኾን የአቡነ ተክለ ሃይማኖትን ዐፅም ከዐረፈበት ዋሻ ባወጡት ጊዜ ዐፅማቸው ዕለት የተገነዘ በድን ይመስል ነበር፤ መዓዛውም ሽቱ፣ ሽቱ ይሸት ነበር፡፡ በአባታችን ዐፅም ቀኝና ግራም መስቀል ተተክሎ ነበር፡፡ በዐፅማቸውም ብዙ ድንቅ ተአምራት ተደርገዋል፡፡ ይህንን የአባታችንን ዐፅም አባ ሕዝቅያስና ዐሥራ ሁለቱ መምህራን በሣጥን አክብረው ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ወስደው በመንበሩ ፊት ሦስት ጊዜ አዞሩት፡፡

በዚህች ዕለት አስቀድመው የካቲት ፲፱ ቀን ለአባ ሕዝቅያስ በሕልም እንደ ነገሯቸው ብፁዕ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ከቅዱስ ሚካኤልና ከአባ ፊልጶስ ጋር ወደ ቤተ ክርስቲያኑ መጥተው ዐፅማቸው እስኪያረፍ ድረስ ከመንበሩ ተቀምጠው ቆይተው ዐፅማቸው ካረፈ በኋላ የተሰበሰበውን ሕዝብ ባርከው በክብር ወደ ሰማይ ዐረጉ፡፡ መምህራኑና ምእመናኑም በዓሉን በታላቅ ደስታ አክብረው በሰላም ወደየቤታቸው ተመለሱ፡፡ በዘመኑ የአቡነ ተክለ ሃይማኖት ፍልሰተ ዐፅም በዋለበት ዕለት ርክበ ካህናትም አብሮ መከበሩ በዓሉን ልዩ ድምቀት ሰጥቶት እንደ ነበር በመጽሐፈ ገድላቸው ተገልጿል፡፡ ከዚያን ዘመን ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ በታላቁ ገዳም በደብረ ሊባኖስ ቅዱሳን ፓትርያሪኮች፣ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳትና በርካታ ምእመናን እየተሰበሰቡ በዓሉን በድምቀት ያከብራሉ (ገ.ተ.ሃ ፷፭፥፩-፳፬)፡፡

የብፁዕ አባታችን ዐፅም በፈለሰበት ዕለት ዐሥራ ሁለቱ መምህራን እና በርካታ ምእመናንን እንደ ተሰበሰቡ ዅሉ እኛንም እግዚአብሔር አምላካችን በኢየሩሳሌም ሰማያዊት ይሰብስበን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ምንጭ፡

  • መጽሐፈ ስንክሳር፣ ግንቦት ፲፪ ቀን፡፡
  • ገድለ ተክለ ሃይማኖት፣ ፲፱፻፹፱ .ም፤ አዲስ አበባ፡፡

ዝክረ ቅዱስ ያሬድ ኢትዮጵያዊ

ቅዱስ ያሬድ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ግንቦት  ቀን ፳፻፱ .

በየዓመቱ ግንቦት ፲፩ ቀን ከሚታወሱ ቅዱሳን መካከል የእመቤታችን እናት ቅድስት ሐና፣ ቅድስት ታውክልያ፣ ቅዱስ በፍኑትዩስ፣ አባ አሴር፣ ቅዱስ ያሬድ፣ ብፅዕት አርሴማ፣ ቅድስት ኤፎምያ፣ ቅድስት አናሲማ፣ ቅድስት ሶፍያ፣ አባ በኪሞስ፣ አባ አብላዲስ፣ አባ ዮልዮስ እና ስማቸውን ያልጠቀስናቸው ሌሎች በርካታ ቅዱሳንም ተጠቃሾች ናቸው፡፡ በዛሬው ዝግጅታችን ‹የቤተ ክርስቲያን እንዚራ›፣ ‹የኢትዮጵያ ብርሃን› እየተባለ የሚጠራውን የቤተ ክርስቲያናችን ድምቀት፣ የአገራችን ኩራት የኾነውን የጥዑመ ልሳኑ ማኅሌታይ ቅዱስ ያሬድን ታሪክ በአጭሩ ልናስታውሳችሁ ወደድን፤

ቅዱስ ያሬድ ሚያዝያ ፭ ቀን በ፭፻፭ ዓ.ም በአገራችን በኢትዮጵያ በአክሱም ከተማ ከአባቱ ከአብዩድ (ይስሐቅ) እና ከእናቱ ታውክልያ (ክርስቲና) ተወለደ፡፡ ዕድሜው ለትምህርት ሲደርስ ከአጎቱ ከአባ ጌዴዎን ዘንድ ትምህርት ሊማር ቢሔድም ለበርካታ ዓመታት ትምህርት ሊገባው አልቻለም ነበር፡፡ በዚህም የተነሣ መምህሩ ይገርፉት፣ ይገሥፁት ነበር፡፡ እርሱም ከትምህርቱ ክብደት ባለፈ የመምህሩ ተግሣፅ ሲበረታበት ጊዜ ከአባ ጌዴዎን ቤት ወጥቶ በመሸሽ ላይ ሳለ ደክሞት ከአንድ ዛፍ ሥር ተቀመጠ፡፡

ከዛፉ ሥር ተጠልሎ ሳለ አንድ ትል ፍሬውን ለመመገብ ወደ ዛፉ ሊወጣ ሲል መውጣት ስለ ተሳነው በተደጋጋሚ ሲወድቅ ቆይቶ ከብዙ ሙከራ በኋላ ከዛፉ ላይ ሲወጣ፤ ፍሬውንም ሲመገብ ይመለከታል፡፡ ቅዱስ ያሬድ የትሉን ትጋት ከአየ በኋላ እርሱም በተደጋጋሚ ሙከራ ቢያደርግ የከበደው ምሥጢር እንደሚገለጽለት በማመን ወደ መምህሩ ተመልሶ ይቅርታ በመጠየቅ ትምህርቱን እንደ ገና መቀጠል ጀመረ፡፡ እግዚአብሔርን በጸሎት እየተማጸነ ትምህርቱን ሲከታተል ከቆየ በኋላ በአጭር ጊዜ ውስጥ ልቡናው ብሩህ ኾኖለት የብሉይና የሐዲስ ኪዳን መጻሕፍት ትርጓሜን አጠናቆ መዓርገ ዲቁና ተቀበለ፡፡

እግዚአብሔርም የክብር መታሰቢያ ሊያቆምለት ወዷልና ከኤዶም ገነት ሦስት አዕዋፍን ልኮ በሰው አንደበት እንዲያናግሩት አደረጋቸው፡፡ እነርሱም ካናገሩት በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም ሰማያዊት አወጡትና በዚያም የሃያ አራቱን ካህናተ ሰማይ (ሱራፌል) ማኅሌት ተማረ፡፡ ወደ ምድርም ተመልሶ በአክሱም ጽዮን በሦስት ሰዓት ገብቶ በታላቅ ቃል፡- ‹‹ሃሌ ሉያ ለአብ ሃሌ ሉያ ለወልድ ሃሌ ሉያ ለመንፈስ ቅዱስ ቀዳሚሃ ለጽዮን ሰማየ ሣረረ ወበዳግም አርአዮ ለሙሴ ዘከመ ይገብር ግብራ ለደብተራ፤ ለአብ ምስጋና ይገባል፤ ለወልድ ምስጋና ይገባል፤ ለመንፈስ ቅዱስ ምስጋና ይገባል፡፡ የጽዮን ደገኛዋ ሰማይን ፈጠረ፡፡ ዳግመኛም እንዴት መሥራት እንዳለበት የድንኳንን አሠራር ለሙሴ አሳየው፤ አስተማረው፤›› እያለ በዜማ እግዚአብሔርን አመሰገነ፡፡ የቅዱስ ያሬድን ድምፅ የሰሙ ዅሉ ጳጳሳቱና ነገሥታቱ ሳይቀሩ ካህናቱም ምእመናኑም ወደ እርሱ ተሰብስበው ሲሰሙት ዋሉ፡፡ ይህንንም ምስጋና ‹አርያም› ብሎ ሰየመው፤ ይኸውም በዜማ ትምህርት ቤት ከቃል ትምህርቶች አንደኛው ኾኖ በቤተ ክርስቲያን በመሰጠት ላይ ይገኛል፡፡

መጽሐፈ ስንክሳር ቅዱስ ያሬድን፡- አምሳሊሆሙ ለሱራፌል፤ የሱራፌል አምሳላቸው› ይለዋል፡፡ ከመላእክት ወገን የኾኑት ሱራፌል እግዚአብሔርን ‹‹ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ›› እያሉ በመንበሩ ፊት ቆመው እንደሚያመሰግኑ ዅሉ ቅዱስ ያሬድም ‹‹ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ›› እያለ በመላእክት ቋንቋ እግዚአብሔርን አመስገኗልና፤ ደግሞም የተማረው ከእነርሱ ነውና የሱራፌል አምሳላቸው› ተባለ፡፡ እርሱም፡- ‹‹ሃሌ ሉያ ዋይ ዜማ ዘሰማዕኩ በሰማይ እመላእክት ግናይ እንዘ ይብሉ ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር መልዐ ሰማያተ ወምድረ ቅድሳተ ስብሓቲከ፤ ምስጋና ለእግዚአብሔር ይኹን! ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ እግዚአብሔር፤ የምስጋናህ ስፋት ሰማይና ምድርን መላ፤›› እያሉ ሲያመሰግኑ ከመላእክት የሰማሁት ምስጋና ምንኛ ድንቅ ነው? በማለት ዜማውን የተማረው ከመላእክት መኾኑን በድርሰቱ መስክሯል (ኢሳ.፮፥፫)፡፡

ከዚያ በኋላ በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝቶ ከዓመት እስከ ዓመት ድረስ በየክፍለ ዘመኑ በክረምትና በበጋ፣ በመጸውና በጸደይ፣ በአጽዋማትና በሰንበታት፣ እንዲሁም በመላእክት፣ በጻድቃን፣ በሰማዕታት፣ በደናግል በዓላት የሚደረስ ቃለ እግዚአብሔር በሦስት ዜማዎች ማለትም በግእዝ፣ በዕዝልና በአራራይ ደረሰ፡፡ የሰው ንግግር፣ የአዕዋፍ፣ የእንስሳትና የአራዊት ጩኸት ዅሉ ከእነዚህ ከሦስቱ ዜማዎች እንደማይወጡ መጽሐፈ ስንክሳር ይናገራል፡፡ በዘመኑ የነበረው ንጉሥ ገብረ መስቀል በሊቁ ዜማ ረቂቅነት እና የድምፅ ማማር ከመመሰጡ የተነሣ የቅዱስ ያሬድን እግር በጦር መውጋቱም በመጽሐፈ ስንክሳር እንዲህ ተመዝግቧል፤

በአንዲት ዕለት ቅዱስ ያሬድ ከብሉይና ከሐዲስ፣ እንደዚሁም ከሊቃውንትና ከመነኮሳት የተውጣጣውን መንፈሳዊ ድርሰቱን ከንጉሡ ፊት ቆሞ ሲዘምር ንጉሡ በድምፁ በመማረኩ የተነሣ ልቡናው በተመስጦ ተሠውሮበት (የሚያደርገዉን ባለማወቁ) የቅዱስ ያሬድን እግር በጦር ወጋው፡፡ ከቅዱስ ያሬድ እግር ደምና ውኃ ቢፈስስም ነገር ግን ማኅሌቱን እስኪፈጽም ድረስ ሕመሙ አልተሰማውም ነበር፡፡ ንጉሡም ያደረገዉን ዅሉ ባወቀ ጊዜ ደነገጠ፤ ጦሩንም ከእግሩ ነቅሎ ‹‹ስለ ፈሰሰው ደምህ ዋጋ የምትፈልገዉን ዅሉ ለምነኝ›› እያለ ተማጸነው፡፡ ቅዱስ ያሬድም ‹‹ላትከለክለኝ ማልልኝ›› ብሎ ቃል ካስገባው በኋላ ወደ ገዳም ሔዶ ይመነኵስ ዘንድ እንዲፈቅድለትና እንዲያሰናብተው ለመነው፡፡ ንጉሡም ከመኳንንቱ ጋር እጅግ አዘነ፤ ተከዘ፡፡ ከእርሱ እንዲለይ ባይፈልግም ነገር ግን መሐላዉን ማፍረስ ስለ ከበደው አሰናበተው፡፡

ከዚያም ቅዱስ ያሬድ በአክሱም ጽዮን ቤተ መቅደስ በታቦተ ጽዮን ፊት ቆሞ፡ ‹‹ቅድስት ወብፅዕት ስብሕት ወቡርክት ክብርት ወልዕልት አንቀጸ ብርሃን መዐርገ ሕይወት …፤ፈጽሞ የከበርሽና የተመሰገንሽ፣ ከፍ ከፍም ያልሽ፣ የብርሃን መውጫ የሕይወት ማዕረግ የኾንሽ …›› እያለ አንቀጸ ብርሃን የተሰኘውን የእመቤታችንን ምስጋና እስከ መጨረሻው ድረስ ደረሰ፡፡ ይህንን ጸሎት ሲያደርስም አንድ ክንድ ያህል ከመሬት ከፍ ብሎ ይታይ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ወደ ሰሜን አገር ሔዶ (ሰሜን ተራሮች አካባቢ) በጾም በጸሎት ተወስኖ ሥጋውን እጅግ እያደከመ ኖሮ ገድሉን በዚያው ፈጸመ፡፡ እግዚአብሔርም ስሙን ለሚጠራ፣ መታሰቢያውን ለሚያደርግ ቃል ኪዳን ሰጠው፤ ከዚያም በሰላም ዐረፈ፡፡

(ምንጭ፡መጽሐፈ ስንክሳር፣ ግንቦት ፲፩ ቀን)፡፡

የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት በገድለ ቅዱስ ያሬድ ላይ እና በመጽሐፈ ስንክሳር እንደ መዘገቡልን ግንቦት ፲፩ ቀን ቅዱስ ያሬድ ከዚህ ዓለም ውጣ ውረድ ያረፈበት ቀን ነው፤ እዚህ ላይ ግን አከራካሪ ጉዳይ አለ፤ ይኸውም አንደኛው ቅዱስ ያሬድ ሞቶ ተቀብሯል የሚል ሲኾን፣ ሌላኛው ደግሞ ቅዱስ ያሬድ እስከነነፍሱ ተሠወረ እንጂ አልሞተም የሚል ነው፡፡ በእርግጥ ቃሉን በትኩረት ለተመለከው ሰው ዐረፈ ማለት ሞትን ብቻ ሳይኾን እንደነሄኖክ ከዚህ ዓለም ጣጣ እና እንግልት ተለይቶ በሕይወት እያሉ (ሳይሞቱ) ተሠውሮ መኖርንም ያመለክታል፡፡ የቤተ ክርስቲያን መምህራን እንደሚያስተምሩን እነእገሌ ቀበሩት የሚል ቃል ስለማይገኝ ቅዱስ ያሬድ ተሠወረ እንጂ ሞተ ተብሎ አይነገርለትም፡፡ ለዚህም ማስረጃ እርሱ በተሠወረበት ተራራ አካባቢ እና በስሙ በተመሠረተው በደብረ ሐዊ ቅዱስ ያሬድ ገዳም እስከ አሁን ድረስ የከበሮ (የማኅሌት) ድምፅ ይሰማል፤ የዕጣን መዓዛም ይሸታል፡፡ ይህም ቅዱሱ ከሰው ዓይን ተሠውሮ እግዚአብሔርን እያመሰገነ እንደሚገኝ አመላካች ነው፡፡

በመጨረሻም የቅዱስ ያሬድ ድርሰቶች ለቤተ ክርስቲያን ብቻ ሳይኾን ለአገርም ድንቅና ወደር የሌላቸው ሀብቶች መኾናውን ዅላችንም ልብ ልንለው ይገባል፡፡ በመኾኑም የዜማ ድርሰቶቹ (ድጓ፣ ጾመ ድጓ፣ ምዕራፍ፣ ዝማሬ፣ መዋሥዕት) እንደ ሌሎቹ ቅርሶች ዅሉ በዩኔስኮ እንዲመዘገቡ የሚመለከታቸው አካላት ከፍተኛ ርብርብ በያደርጉ መልካም ነው፡፡ በቅዱስ ያሬድ ዜማ የሚደምቁት በዓለ ጥምቀት እና በዓለ መስቀል በዩኔስኮ ሲመዘገቡ ዜማውን ከበዓላቱ ለይቶ ማስቀረት አይገባምና፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የ፳፻፱ ዓ.ም ርክበ ካህናትን አስመልክቶ ከቅዱስ ፓትርያርኩ የተበረከተ ቃለ ምዕዳን  

ግንቦት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን

‹‹ወይእዜኒ ዕቀቡ ርእሰክሙ ወኵሎ መራዕየ ዘሀሎ ኀቤክሙ፤ አሁንም ራሳችሁንና በእናንተ ሥር ያለውን መንጋ ዅሉ ጠብቁ፤›› (ሐዋ. ፳፥፳፰)፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት

መዋዕለ ጾሙን በሰላም አስፈጽሞና ከበዓለ ትንሣኤው አድርሶ፣ እንደዚሁም ዅላችንን ከየሀገረ ስብከታችን አሰባስቦ በዚህ ዓመታዊና ቀኖናዊ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ ስብሰባ በአንድነት ስለሰበሰበን እግዚአብሔር አምላካችን ስሙ የተመሰገነ ይኹን፤ እናንተም እንኳን በደኅና መጣችሁ!

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት

ከላይ የተጠቀሰው ኃይለ ቃል የመንጋው እረኞች የኾን ዅሉ በቃለ እግዚአብሔር ጐልብተን፣ በመንፈስ ቅዱስ ኃይል ተቃኝተን ራሳችንንና ምእመናንን እንዴት መጠበቅ እንዳለብን የሚያመለክት የእግዚአብሔር ታላቅ የጥሪ ቃል ነው፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትና ቀደምት ቅዱሳን አበው የሥልጣነ ክህነትና የመንበረ ሐዋርያት ወራሽ የኾነው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ በዓመት ሁለት ጊዜ በቋሚነትና በመደበኛነት እንደዚሁም ለቤተ ክርስቲያን ጉዳይ አስፈላጊ ኾኖ በተገኘ ጊዜ ዅሉ እየተሰበሰበ የቤተ ክርስቲያንን ጉዳይ እንዲገመግም፣ እንዲያጠና እና መፍትሔ እንዲሰጥ መደንጋጋቸው ያለ ምክንያት አልነበረም፡፡

የጉባኤው መሠረታዊ ዓላማ ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አስቀድሞ እንደ ተናገረው ከመጀመርያ አንሥቶ ልዩ ልዩ ፈተና ተለይቶአት የማያውቅ ቤተ ክርስቲያን በመከራው ጽናት ተሰቃ ወይም ተስፋ ቈርጣ ዓላማዋን እንዳትስት እስከ ሕይወት መሥዋዕትነት ሊዘልቅ የሚችል ጥብቅ ክትትልና ጥበቃ ለማድረግ እንዲቻል ነው፡፡

ይህም በመኾኑ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ አማካይነት ነገራተ ቤተ ክርስቲያንን በጥልቀትና በአስተዋይነት እየተረጐመች፣ እንደዚሁም መንፈስ ቅዱስን መሪ በማድረግና አስፈላጊው መሥዋዕትነትን በመክፈል ከውጭና ከውስጥ የሚሰነዘሩባትን ጥቃቶችን እየተቋቋመች እነሆ በአሸናፊነት ከዘመናችን ደርሳለች፡፡ ይህም ሊኾን የቻለው በመንፈስ ቅዱስ ኃይል የተቃኙ ቅዱሳን አበው በፈጸሙት ተጋደሎና ወደር የለሽ መሥዋዕትነት እንደ ኾነ አይዘነጋም፡፡

የመንፈሳዊ ጥበቃና ክትትል ተግባር በቤተ ክርስቲያናችን ሥርዓተ ቀኖና መሠረት በቤተሰብ ደረጃ በነፍስ ወከፍ ጠባቂ ካህን ወይም የነፍስ አባት እንዲኖር የተደረገበት ዐቢይ ምክንያትም የጥበቃውንና የክትትሉን ተግባር አስተማማኝና ዘላቂ ለማድረግ ነው፡፡ የተግባሩ መነሻም የጌታችን ትምህርትና ትእዛዝ ነው፡፡

እኛ የቤተ ክርስቲያን መሪዎችና አገልጋዮች ሕፃኑንም ወጣቱንም፣ ጐልማሳውንና ሽማግሌውንም አንድ አድርገን እንድንጠብቅና እንድናሰማራ ጌታችን በባሕረ ጥብርያዶስ ‹‹ግልገሎቼን ጠብቅ፤ ጠቦቶቼን ጠብቅ፤ በጎቼን ጠብቅ፤›› በማለት ለቅዱስ ጴጥሮስ በሰጠው ትእዛዝ መሠረት አዞናል (ዮሐ. ፳፩፥፲፭-፲፯)፡፡ እኛም ትእዛዙንና ሓላፊነቱንም ወደንና ፈቅደን ተቀብለናል፡፡

ከበዓለ ትንሣኤ በኋላ በሃያ አምስተኛው ቀን የሚካሔደውና ረክበ ካህናት ተብሎ የሚታወቀው፣ በዛሬው ዕለት የምንጀምረው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤም መሠረቱ ይህ የባሕረ ጥብርያዶስ የጥበቃ ትእዛዝና ትምህርት እንደ ኾነ ይታወቃል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ዐቢይ እና ዋና ተልእኮም ዐቂበ ምእመናን እንደ ኾነ በቅዱስ ወንጌል በተደጋጋሚ ተጽፏል፡፡ በመኾኑም ቅዱሳን ሐዋርያትም ኾኑ ቅዱሳን አበው ዋነኛ ተግባራቸው ምእመናንን ማስተማር፣ ማሳመን፣ ማጥመቅ፣ ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያንን ማደል፣ ከዚያም ምእመናንን በዕለተ ተዕለት ኑሮአቸው መጠበቅና ክትትል ማድረግ ነበር፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት

ሐዋርያዊት፣ ህልወተ ኵሉ ወይም በዅሉም ያለች፣ አንዲትና ቅድስት የኾነችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በረጅሙ የሁለት ሺሕ ዘመናት ጉዞዋ አንድነቷ ሳይናጋ፣ ሐዋርያዊ ተልእኮዋ ሳይቋረጥ ለዘመናት የዘለቀችው ካህናት በነፍስ አባትነት እያንዳንዱን ቤተሰብ በመጠበቃቸው፣ በማስተማራቸውና በመከታተላቸው ነው፡፡ ዛሬም ቢኾን እየተስፋፋ ለመጣው የምእመናን ቅሰጣ ዋና መከላከያው የነፍስ አባትን ተልእኮ ማእከል ያደረገ በቤተሰብ ውስጥ የነፍስ ወከፍ ጠበቃ ሲጠናከር ብቻ እንደ ኾነ ግንዛቤ ሊወሰድበት ይገባል፡፡

ይህንን የግብረ ኖሎት ሥራ በተፈለገው መጠን ግቡን እንዲመታ በየሀገረ ስብከቱ የካህናት ማሠልጠኛ በማቋቋም፣ ዘመኑን ያገናዘበና በቀላሉ ወደ ተግባር የሚያሸጋግር የሥልጠና መርሐ ግብር በመንደፍ ካህናቱን ከዳር እስከ ዳር በማነቃነቅ፣ አስተማማኝ ጥበቃ ማረጋገጥ ይኖርብናል፤ ይህንን ተግባር ለማፋጠን የሊቃነ ጳጳሳት ፈቃደኝነትና ተነሳሽነት ከፍተኛውን ድርሻ ይወስዳል፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት በከፊል

እንደ እውነቱ ከኾነ ዛሬም ለሃይማኖቱ ተቆርቋሪ የኾነ፣ ለእምነቱ አድርግ የተባለውን የሚያደርግ ሕዝብ እግዚአብሔር አልነሣንም፤ በእኛ በኩል ግን የሚቀር ብዙ ሥራ እንዳለ አይካድም፡፡ ከዚህ አንጻር እተየፈታተነን ያለውን የቅን አገልግሎትና የመልካም አስተዳደር ክፍተት በፍጥነት አስተካክለን ወደ ሕዝቡ የጥበቃ ተግባር መሠማራት ወቅቱ የሚጠይቀው ተግባር መኾኑን ማስተዋል አለብን፡፡

አሁን ባለው የጥበቃና የክትትል ክፍተት ቍጥር በርከት ያለ ወጣት እየኮበለለ እንደ ኾነ ማወቅ አለብን፤ አለሁ የሚለው ወጣትም ቢኾን ኦርቶዶክሳዊ መርሕና ቀኖናን በቅጡ ባለማወቁ ሲደናገርና የተቃራኒ አካላት ባህልና ሥርዓትን ሲደበላልቅ ይታያል፡፡ ይህ ዅሉ ሊኾን የቻለው ጌታችን እንዳስተማረንና እንዳዘዘን ከግልገልነት ዕድሜ ጀምረን ወጣቱን ባለመጠበቃችንና ባለመከታተላችን እንደ ኾነ ሊሠመርበት ይገባል፡፡

ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት የቅዱስ ስኖዶስ አባላት

በቅዱስ ሲኖዶስ አመራር ሰጪነትና የበላይ ተቆጣጣሪነት የሚመራው የግብረ ኖሎት ጥበቃ የምእመናንን ዅለንተናዊ ሕይወት የሚያካልል ሊኾን ይገባል፡፡ ምእመናን ለሃይማኖታቸው የሚታመኑ፤ ለአገራቸው ዕድገትና ልማት የሚቆረቆሩ፤ በአንድነት፣ በስምምነትና በፍቅር የመኖር ጥቅምን የሚገነዘቡ፤ በማንነታቸውና በባህላቸው፣ በታሪካቸውና በእምነታቸው የሚኮሩ በአጠቃላይ የተስተካከለ መንፈሳዊና ሥነ ልቡናዊ ሰብእናን የተላበሱ እንዲኾኑ በርትተን የማስተማር፣ የመጠበቅና የመከታተል ሃይማኖታዊና ሀገራዊ ሓላፊነት አለብን፤ ይህም በታቀደ፣ በተደራጀ፣ በተጠናከረና ተከታታይነት ባለው የአፈጻጸም ሥልት ሊከናወን ይገባል፡፡

በመጨረሻም

በዚህ ዓመታዊና ቀኖናዊ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ የቀረቡትን አጀንዳዎች ቅዱስ ሲኖዶስ በጥልቀት በማስተዋልና ለቤተ ክርስቲያናችን በሚበጅ መልኩ በማጤን፣ እንደዚሁም ለቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ህልውና መጠበቅ የሚያስችሉ ውሳኔዎችን በማሳለፍ ሐዋርያዊ ግዳጁን እንዲወጣ እያሳሰብን የሁለት ሺህ ዘጠኝ ዓመተ ምሕረት የረክበ ካህናት ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ በዛሬው ዕለት መጀመሩን እናበሥራለን፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን የተባረከና የተቀደሰ ጉባኤ ያድርግልን!

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር፤ አሜን፡፡

አባ ማትያስ ቀዳማዊ

ፓትርያርክ ርእሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ

ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወዕጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፤

ግንቦት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም፤

አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ፡፡

ርክበ ካህናት

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ግንቦት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹ርክብ› ወይም ‹ረክብ› የሚለው ቃል ‹ተራከበ፤ ተገናኘ› ከሚለው የግእዝ ግስ የወጣ ሲኾን፣ ትርጕሙም ማግኛ፣ መገኛ፣ መገናኛ ማለት ነው (ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ገጽ ፰፻፴፩)፡፡ ‹ክህነት› የሚለው ስያሜም ከጵጵስና ጀምሮ እስከ ዲቁና ድረስ ያሉትን የቤተ ክርስቲያን መዓርጋት የሚያጠቃልል ቃል ሲኾን ካህን (ነጠላ ቍጥር)፣ ካህናት (ብዙ ቍጥር) በአንድ በኩል ቀሳውስትን የሚወክል ኾኖ በሌላ በኩል ደግሞ የጳጳሳት፣ የኤጲስ ቆጶሳት፣ የቀሳውስት፣ የዲያቆናት የጋራ መጠሪያ ነው፡፡ ‹ርክበ ካህናት› የሚለው ሐረግም የካህናት መገኛ፣ መገናኛ፣ ጉባኤ (መሰባሰቢያ)፣ መወያያ፣ ወዘተ የሚል ትርጕም አለው፡፡ በአጭሩ ‹ርክበ ካህናት› ማለት – የአባቶች ካህናት ማለትም የብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት (የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት) ጉባኤ ማለት ነው፡፡

በቅዱስ ዮሐንስ ወንጌል እንደ ተገለጸው ጌታችን አምላካችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሞት ከተነሣ በኋላ ለሦስተኛ ጊዜ ተገልጦ ከዐሥራ አንዱ ቅዱሳን ሐዋርያት ጋር ምሳ በልቷል፡፡ ከምሳ በኋላም ጌታችን ቅዱስ ጴጥሮስን ሦስት ጊዜ ጠርቶ ‹‹ትወደኛለህን?›› እያለ ከጠየቀው በኋላ እንደሚወደው ምላሽ መስጠቱን ተከትሎ በቅደም ተከተል ‹‹በጎቼን ጠብቅ፤ ጠቦቶቼን አሰማራ፤ ግልገሎቼን ጠብቅ፤›› በማለት የአለቅነት ሥልጣን ሰጥቶታል፡፡ ይህ ምሥጢር ለጊዜው ጌታችን ሐዋርያትን፣ ሰብዐ አርድእትንና ሠላሳ ስድስቱን ቅዱሳት አንስት በአጠቃላይ መቶ ሃያውን ቤተሰብእ እንዲጠብቅና እንዲከባከብ ቅዱስ ጴጥሮስን ማስጠንቀቁን፤ ለፍጻሜው ግን የቤተ ክርስቲያን አባቶች (ጳጳሳት) መምህራንንና መላው ሕዝበ ክርስቲያንን እንዲጠብቁና እንዲያስተዳድሩ በእግዚአብሔር መሾማቸውን የሚያስረዳ ምሥጢር አለው (ዮሐ.፳፩፥፩-፲፯)፡፡

ይህን የጌታችንን ትእዛዝና የሐዋርያትን ሥልጣነ ክህነት መሠረት በማድረግ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ በዓመት ሁለት ጊዜ ጉባኤ ያደርጋል፤ የመጀመሪያው ጉባኤ ጥቅምት ፲፪ ቀን (የቅዱስ ማቴዎስ በዓል) ሲኾን፣ ሁለተኛው ደግሞ ርክበ ካህናት ነው፡፡ በዓሉ (ርክበ ካህናት) ወሩና የሚውልበት ቀን የበዓላትንና የአጽዋማትን ቀመር ተከትሎ ከፍና ዝቅ ቢልም በየዓመቱ የትንሣኤ በዓል በተከበረ በ፳፭ኛው ቀን በዕለተ ረቡዕ ይውላል፡፡ የአጽዋማትና የበዓላት ቀመር ከመዘጋጀቱ በፊት ማለትም በቅዱስ ድሜጥሮስ አማካኝነት ዐቢይ ጾም ሰኞ፣ ስቅለት ዓርብ፣ ትንሣኤ እሑድ፣ ርክበ ካህናት ረቡዕ፣ ዕርገት ሐሙስ፣ ጰራቅሊጦስ እሑድ እንዲኾን ከመደረጉ በፊት ርክበ ካህናት ግንቦት ፳፩ ቀን ይውል ነበር (መጽሐፈ ግጻዌ፣ ግንቦት ፳፩ ቀን)፡፡

ከዚህ በኋላ በዓለ ትንሣኤ በዋለ በ፳፭ኛው ቀን፣ በበዓለ ኃምሳ እኩሌታ በዕለተ ረቡዕ ርክበ ካህናት እንዲዘከር የቤተ ክርስቲያን አባቶች ወስነዋል፡፡ በያዝነው ዓመት በ፳፻፱ ዓ.ም የትንሣኤ በዓል ከተከበረበት ዕለት (ሚያዝያ ፰ ቀን) ጀምሮ ብንቈጥር ፳፭ኛው ቀን ግንቦት ፪ ቀን ነው፡፡ በመኾኑም የዘንድሮው ርክበ ካህናት ግንቦት ፪ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ይውላል ማለት ነው፡፡ ይህ በዓል (ርክበ ካህናት) ከቅዱሳን ሐዋርያት ጀምሮ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሲመሩ የቆዩ አባቶቻችን በጋራ በመሰባሰብ ለቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተቀላጠፈ አገልግሎት እንደዚሁም ለምእመናን አንድነትና መንፈሳዊ ዕድገት የሚበጁ መንፈሳውያን መመሪያዎችን የሚያስተላልፉበት ዕለት ነው፡፡ በዚህ ዕለት ቅዱስ ሲኖዶስ በሚያደርገው ጉባኤ የሚተላለፉ መመሪያዎችና የሚጸድቁ ውሳኔዎች ለቤተ ክርስቲያን ዕድገት፣ ለምእመናን አንድነት፣ ለአገር ሰላምና ደኅንነት የሚጠቅሙ ይኾኑ ዘንድ ዅላችንም በጾም በጸሎት እግዚአብሔርን መጠየቅ ይኖርብናል፡፡

አምላካችን ቤተ ክርስቲያናችንንና አባቶቻችንን ይጠብቅልን፤ እኛንም ለአባቶች የሚታዘዝ ልቡና፣ ሓላፊነታችንን የምንወጣበትን ጥበብና ማስተዋልን ያድለን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ስዊድናዊው ፕሮፌሰር አምሳ ሁለት መጻሕፍትን አበረከቱ

በዲያቆን ኤፍሬም የኔሰው

ሚያዝያ ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

በስዊድን አገር የሉንድ ዩኒቨርሲቲ መምህርና ተመራማሪ የኾኑት ፕሮፌሰር ሳሙኤል ሮቢንሰን በልዩ ልዩ ባለሙያዎችና በተለያዩ አርእስት በእንግሊዝኛ ቋንቋ የተዘጋጁ አምሳ ሁለት መጻሕፍትን ለማኅበረ ቅዱሳን ጥናትና ምርምር ማእከል በስጦታ መልክ አበረከቱ፡፡

ፕ/ር ሳሙኤል ሮቢንሰን መጻሕፍታቸውን ሲያስረክቡ

‹TAITU Empress of Ethiopia; Lake Tana and The Blue Nile an Abyssinian Quest; Education in Ethiopia Prospect and Retrospect; The Abyssinian Difficulty the Emperor Tewodross and the Magdala Campaign 1867-68; Slavery, Slave Trade and Abolition Attempts in Egypt and Sudan› የሚሉት ከአምሳ ሁለቱ መጻሕፍት መካከል የሚጠቀሱ ናቸው፡፡

ዶ/ር ዮሐንስ አድገህ መጻሕፍቱን ሲረከቡ

ወላጅ አባታቸው ፕሮፌሰር ሮቢንሰን፣ ከሌላ እምነት ወደ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት የተመለሱ የቤተ ክርስቲያን ልጅ እንደ ነበሩና በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ (የአሁኑ አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ) ለበርካታ ዓመታት በመምህርነት አገልግሎት እንደ ሰጡ ያስታወሱት ፕሮፌሰር ሳሙኤል፣ ማኅበሩ የሚያከናውነውን የጥናትና ምርምር ተግባር ለመደገፍና ለማበረታታት በውድ ገንዘብ የገዟቸውን እነዚህን መጻሕፍት በወላጅ አባታቸው ስም ለማእከሉ ማበርከታቸውን ተናግረዋል፡፡

በምጣኔ ሀብት፣ በታሪክ፣ በኅብረተሰብና አካባቢ ሳይንስ፣ በፖለቲካ እና ሌላም የትምህርት መስክ የተዘጋጁት መጻሕፍቱ በተለይ ለከፍተኛ ትምህርት ተቋማት መምህራን፣ ተመራማሪዎችና ተማሪዎች የጎላ ጠቀሜታ እንዳላቸው ፕሮፌሰሩ ገልጸዋል፡፡

ፕሮፌሰሩ መጻሕፍቶቻቸውን ለማኅበሩ ያበረከቱት በስዊድን አገር የፒኤችዲ ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ በሚገኙት የቀድሞው የጥናትና ምርምር ማእከሉ ዳይሬክተር ቀሲስ መንግሥቱ ጎበዜ አስተባባሪነት መኾኑን የጥናትና ምርምር ማእከሉ ምክትል ዳይሬክተር አቶ ጌታቸው ሞላ ለዝግጅት ክፍላችን አስታውቀዋል፡፡

አቶ ጌታቸው እንዳስታወቁት መጻሕፍቱ በተበረከቱበት ሚያዝያ ፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም ከልዩ ልዩ ዓለማቀፍ የትምህርት ተቋማት የመጡ የውጭ አገር ዜጎች ከፕሮፌሰር ሳሙኤል ጋር በማኅበሩ ሕንጻ ተገኝተዋል፡፡

የመርሐ ግብሩ ታዳሚዎች በከፊል

በዕለቱ በነበረው መርሐ ግብር፣ ፕሮፌሰር ሽፈራው በቀለ (ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ) የኢትዮጵያን ታሪክ፤ ዶክተር ዮሐንስ አድገህ (የጥናትና ምርምር ማእከሉ ዋና ዳይሬክተር) የማኅበረ ቅዱሳንን አመሠራረትና የማእከሉን ተግባር በአጭሩ ለእንግዶቹ አቅርበዋል፡፡ ቀሲስ መንግሥቱ ጎበዜም ማኅበሩ በጥናትና ምርምር ማእከሉ አማካይነት ለቤተ ክርስቲያን የሚሰጠውን አገልግሎት አስረድተዋል፡፡

ከግራ ወደ ቀኝ፡- ቀሲስ መንግሥቱ ጎበዜ፣ ፕ/ር ሽፈራው በቀለ እና ፕ/ር ሳሙኤል ሮቢንሰን

መጻሕፍቱ አንባብያን ይጠቀሙባቸው ዘንድ በሕጋዊ ደረሰኝ ወደ ማኅበሩ ቤተ መጻሕፍት ገቢ መደረጋቸውን የጠቆሙት አቶ ጌታቸው ሞላ፣ ማኅበረ ቅዱሳን ምሁራንን በማሳተፍ የሚያከናውነውን የጥናትና ምርምር ሥራ የውጭ አገር ዜጎች ለመደገፍ መነሣሣታቸው ‹‹የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በውጩ ዓለም ዘንድ ያላትን ልዩ ቦታ ያመላክታል፡፡ መጻሕፍት ልገሳውም የጥናትና ምርምር ማእከሉን ወደ ተቋም ለማሳደግ የሚደረገውን ጥረት ከግብ ለማድረስ ያግዛል›› ብለዋል፡፡

አቶ ጌታቸው ሞላ የጥናትና ምርምር ማእከሉ ምክትል ዳይሬክተር

በመጨረሻም ፕሮፌሰር ሳሙኤልንና ሌሎች የትምህርት ባልንጀሮቻቸውን በማስተባበር መጻሕፍቱ ለማኅበሩ ቤተ መጻሕፍት ገቢ እንዲኾኑ ያደረጉትን ቀሲስ መንግሥቱ ጎበዜን የማእከሉ ምክትል ዳይሬክተር በቤተ ክርስቲያን ስም አመስግነው ‹‹ማኅበረ ቅዱሳን የሚሰጠውን መንፈሳዊ አገልግሎት ለመደገፍ ፈቃደኛ የኾናችሁ አጋሮቻችን! እንደ ፕሮፌሰር ሳሙኤል ሮቢንሰን ልዩ ልዩ መጻሕፍትን ለቤተ መጻሕፍታችን በማበርከት መንፈሳዊ ድርሻችሁን እንድትወጡ ይኹን›› ሲሉ መልእክታቸውን አስተላልፈዋል፡፡

በጥናትና ምርምር ማእከሉ ሥር የሚገኘው የማኅበረ ቅዱሳን ቤተ መጻሕፍት ቅዱሳት መጻሕፍትን ብቻ ሳይኾን በልዩ ልዩ የትምህርት መስክና ቋንቋ የተዘጋጁ በርካታ ዓለማቀፍ የጥናትና የምርምር ሥራዎችን ለንባብ እንደሚያቀርብ፤ ዘወትር ከሰኞ እስከ ቅዳሜ ከጠዋቱ 2፡3 – ምሽቱ 1፡00 ሰዓት (የምሳ ሰዓትን ጨምሮ) አገልግሎት እንደሚሰጥ ያስረዱት የማእከሉ ምክትል ዳይሬክተር፣ ‹‹መንፈሳዊም ኾነ ዘመናዊ ዕውቀታችሁን ለማዳበር የምትፈልጉ ዅሉ ከማኅበሩ ሕንጻ ስድስተኛ ፎቅ ድረስ በመምጣት በአገልግሎቱ ተጠቃሚ ኹኑ›› ሲሉ መንፈሳዊ ጥሪአቸውን አቅርበዋል፡፡

ትንሣኤ ክርስቶስ በሊቃውንት – ካለፈው የቀጠለ

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

ሚያዝያ ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

‹‹በእርሱ ሞት ከብረናል፡፡ በመለኮቱ ሞት ሳይኖርበት በሥጋ ሞተ፤ ምንጊዜም ቢኾን እርሱ የሕይወት ልጅ ሕይወት ነው፡፡ ይኸውም ከእግዚአብሔር አብ የተወለደው ልደት ነው፡፡ ወደ ሕይወት ሥጋ ደፍሮ በመጣ ጊዜ ሞት እንዲህ ድል ተነሣ፤ መፍረስ መበስበስም በእርሱ (በክርስቶስ) እንዲህ ጠፋ፤ ሞትም ድል ተነሣ፤›› (ቅዱስ ቄርሎስ፣ ሃይ. አበ. ፸፪፥፲፪)፡፡

‹‹ሕማምን፣ ሞትን ገንዘብ አደረ፡፡ በሥጋው የሞተው የእኛን ባሕርይ በመዋሐዱ ነው፡፡ ከዚህ በኋላ ተዋሕዶውን አስረዳ፡፡ ሞት ሰው የመኾን ሥራ ነውና፡፡ ከሙታን ተለይቶ መነሣትም አምላክ የመኾን ሥራ ነውና፡፡ እነዚህ ሁለት ሥራዎችን (ሞትን እና ትንሣኤን) እናውቃለን፤›› (ዝኒ ከማሁ ፸፪፥፴፭)፡፡

‹‹በሥጋ ሞተ እንዳልን ዳግመኛ በሥጋ ተነሣ እንላለን፤ ስለ ትንሣኤም የእርሱ ገንዘብ እንደ ኾነ፤ ሙስና መቃብርም እንዳላገኘው ይነገራል፡፡ ይህ (መሞት፣ መነሣት) ለመለኮት አይነገርም፡፡ የተነሣው ሥጋው ነው እንጂ፤›› (ዝኒ ከማሁ ፸፱፥፱)፡፡

‹‹የሞትን ሥልጣን አጠፋ፤ ዲያብሎስንና ኃይሉን (ኃጢአትን) ሻረ፡፡ የብረት መዝጊያዎችን ሰበረ (ፍዳ፣ መርገምን አጠፋ)፡፡ ሲኦልን በዘበዘ፤ የጣዖት ቤቶችን አፈረሰ፡፡ የምሕረትን በር ከፈተ፡፡ ይህችውም በደሙ የከበረች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ለዅሉ የዘለዓለም ሕይወት መገኛ የሚኾን ልጅነት የተገኘበት ሥጋውን ደሙን ሰጠን፤›› (ቅዱስ ቴዎዶስዮስ፣ ሃይ. አበ. ፹፫፥፮)፡፡

‹‹ለእኛስ እግዚአብሔር ቃል በባሕርየ መለኮቱ እንደ ታመመ፤ እንደ ሞተ፤ እንደ ተቀበረ ልንናገር አይገባንም፡፡ ከሙታን ተለይቶ በመነሣቱ ሞት የሌለበት እንደ ኾነ፣ መድኃኒታችን በሚኾን በሞቱና በሦስተኛው ቀንም በመነሣቱ ትንሣኤን እንደ ሰጠን እናምናለን፡፡ የሞተ እርሱ ከሙታን ተለይቶ ተነሥቷልና፡፡ ዅሉን የሚችል እርሱ ካልተነሣ፣ የችሎታ ዅሉ ባለቤት እርሱ የሌለ ከኾነ፣ እንኪያስ ትንሣኤም ሐሰት ነዋ! ትንሣኤም ሐሰት ከኾነ ሃይማኖታችን ከንቱ ነው፡፡ እንኪያስ አይሁድንም እንመስላቸዋለን፡፡ ሰው እንደ መኾኑ በሥጋ ባይሞትስ በሞት ላይ ሥልጣን ያለው አምላክ እንደ መኾኑ ሞትን ባላጠፋ ነበር፡፡ የአዳም የዕዳ ደብዳቤም ከእግዚአብሔርና ከሰው መካከል ባልተደመሰሰም ነበር፤›› (ቅዱስ ሳዊሮስ፣ ሃይ. አበ. ፹፬፥፲፰-፳)፡፡

‹‹ፈጣሪያችን ክርስቶስ ለጌትነቱ እንደሚገባ ሥጋ መለወጥ የሌለበት እስኪኾን ድረስ ድንቅ በሚያሰኝ ትንሣኤ ሙስና መቃብርን አጥፍቷልና፤ በሥጋ በተቀበላቸው በሚያድኑ በእነዚህ ሕማማት ከጽኑ ሞት፣ ከዲያብሎስም ሥልጣን ያድነን ዘንድ፤ ወደ ቀደመ ቦታችንም ያገባን ዘንድ፤›› (ቅዱስ ዮሐንስ ዘአንጾኪያ፣ ሃይ. አበ. ፺፥፴፬)፡፡

‹‹ይታመም ዘንድ በተገባው በሥጋው፣ ነውር የሌለበትን ሕማም በፈቃዱ በእውነት ተቀበለ እንጂ በምትሐት እንዳልታመመ እናገራለሁ፡፡ እንደ ሕማሙ ሞትንም በመስቀል ላይ ተቀበለ፡፡ ለአምላክነቱ በሚገባ፣ ድንቅ በሚያሰኝ ትንሣኤውም የጌትነቱን ሥልጣን ገለጠ፡፡ ሥጋውንም የማይሞት አደረገ፡፡ ከኃጢአት በራቀ በንጹሕ ማኅፀን በተዋሐደው ጊዜ ለመለኮት ገንዘብ ስለኾነ በሥራው ዅሉ አይለወጥም፤›› (ቅዱስ ቴዎዶስዮስ፣ ሃይ. አበ. ፺፪፥፲፭)፡፡

‹‹ሕማም የማይስማማው እርሱ በሥጋ ሞትን ታገሠ፤ ብረት ወደ እሳት በገባ ጊዜ ዅለንተናው እሳት እንደኾነ እስኪታሰብ ድረስ በእሳት ዋዕይ እንዲግል፤ በመዶሻ በተመታ ጊዜ በመስፍሕ (መቀጥቀጫ) ላይ እንዲሳብ (እንዲቀጠቀጥ)፤ እሳትም ከብረት ጋር ተዋሕዶ ሳለ ፈጽሞ እርሱ እንዳይመታ፤ ከብረቱም እንዳይለይ፤ ግን የመዶሻ ኃይል ሳያገኘው እንዲመታ፤ ለመዶሻ እንዲሰጥ፤ የሚያድን የጌታ ሕማም እንዲህ እንደ ኾነ ዕወቅ፡፡ በዚህ ትንሽ ምሳሌ፤ በእሳትና በብረት ተዋሕዶ ምልክትነት ፍጹም ተዋሕዶን እንወቅ፤ የእግዚአብሔር ቃል ይህ መከራና ሕማምን የሚቀበል ሥጋን ተዋሕዶ በሞተ ጊዜም ከሦስት ቀን በኋላ አምላክነቱ በተገለጠበት ትንሣኤው ሞትን አጠፋው፡፡ ሥጋው በመቃብር በመቀበሩም በመቃብር ውስጥ የነበረ መፍረስ፣ መበስበስን አጠፋልን፤ ከሥሩም ነቀለው፡፡ ለዚህም ማስረጃ ከቅዱሳን ወገን ብዙ ሰዎች ተነሡ፤›› (ቅዱስ ባስልዮስ፣ ሃይ. አበ. ፺፮፥፶-፶፪)፡፡

‹‹ዳግመኛ እርሱ እንደ ሞተ፤ በሦስተኛውም ቀን እንደ ተነሣ፤ ስለ ተነሣም ሥጋው የማይፈርስ የማይበሰብስ፣ የማይታመም፣ የማይሞት እንደ ኾነ እናምናለን፡፡ ሥጋውም ከእርሱ ጋር አንድ ኾኖ ወደ ሰማይ ዐረገ፤ በአርያም በልዑል ዙፋኑ ተቀመጠ፡፡ ዳግመኛም በሙታንና በሕያዋን ይፈርድ ዘንድ ዅሉ አንድ ኾኖ በሚነሣበት ጊዜ እርሱ በጌትነት ይመጣል፡፡ ለዅሉም እንደ ሥራው ይከፍለዋል፡፡ እኛ በእነዚህ ቃላት ሳናወላውል ጸንተን እንኖራለን፤›› (ቅዱስ ዲዮናስዮስ፣ ሃይ. አበ. ፺፱፥፴፪)፡፡

‹‹በፈቃዱ በሥጋው የእኛን ሕማም ታመመ፤ በእውነት የእኛን ሞት ሞተ፡፡ ይኸውም የነፍስ ከሥጋ መለየት ነው፡፡ በፈቃዱ በተለየ አካሉ ሞትን ገንዘብ አደረገ፡፡ በሦስተኛውም ቀን በሥልጣኑ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፤ በክብር ወደ ሰማይ ዐረገ፤ በአባቱ ዕሪና ተቀመጠ፡፡ በኋለኛይቱ ቀንም በሙታንና በሕያዋን ሊፈርድ ይመጣል፤›› (ቅዱስ ፊላታዎስ፣ ሃይ. አበ. ፻፭፥፲፬)፡፡

‹‹በሞቱ ሞትን ያጠፋው እርሱ ነው፤ በሦስተኛው ቀን በመነሣቱም ሲኦልን በዘበዘ፣ ለዅሉም ትንሣኤን ገለጠ፡፡ ፈጽሞ አልተለወጠም፤ ለዅሉ አምላክነቱን አስረዳ፤ ሙስና መቃብርን ከእኛ አጠፋ፤ በቀደመ ሰው በአባታችን በአዳም ትእዛዝ ማፍረስ ምክንያት ሠልጥኖብን ለነበረ ኃጢአት ከመገዛት አዳነን፤›› (ቅዱስ ዲዮናስዮስ ፻፲፩፥፲፫)፡፡

‹‹እሑድ በመንፈቀ ሌሊት ነፍሱን ከሥጋው አዋሕዶ በመለኮታዊ ኃይል ተነሣ፡፡ እርሱ ራሱ ‹ነፍሴን በፈቃዴ አሳልፌ ልሰጥ፣ ሁለተኛም መልሼ ላዋሕዳት ሥልጣን አለኝ፤ ይህን ትእዛዝ ከአባቴ ተቀበልሁ› እንዳለ፡፡ በነጋም ጊዜ ለማርያም መግደላዊት ታያት፤ እጅ ልትነሣው በወደደች ጊዜም ‹ገና ወደ አባቴ አላረግሁምና አትንኪኝ› አላት፡፡ ስለዚህም ሥጋዊ አካሉ ከዚያን አስቀድሞ በአብ ቀኝ እንዳልተቀመጠ ዐወቅን፤›› (አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ፣ መጽሐፈ ምሥጢር ዘትንሣኤ ፺፭)፡፡

‹‹ዮሴፍ ኒቆዲሞስ ከጲላጦስ ተካሰው፣ ከመስቀል አውርደው፣ በድርብ በፍታ ገንዘው በአዲስ መቃብር ቀበሩት፡፡ በሦስተኛው ቀን መቃብር ክፈቱልኝ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ወዳሉበት በዝግ ቤት ገብቶ በጽርሐ ጽዮን ታያቸው፤›› (ቅዳሴ ዲዮስቆሮስ ፩፥፳፱-፴፩)፡፡

‹‹ሰውን ስለ መውደድህ ይህን ዅሉ አደረግህ፤ ከሙታን ተለይተህ መቃብር ክፈቱልኝ፤ መግነዝ ፍቱልኝ ሳትል ተነሣህ፡፡ ከእግረ መስቀል ሙታንን አስነሣህ፡፡ ነፍሳትን ከሲኦል ማርከህ ለአባትህ አቀረብህ፤›› (ቅዳሴ ያዕቆብ ዘስሩግ፣ ፩፥፳፬)፡፡

‹‹በታወቀች በተረዳች በሦስተኛይቱ ቀን መቃብር ክፈቱልኝ መግነዝ ፍቱልኝ ሳይል ተነሣ፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ወዳሉበት በዝግ ቤት ገባ፡፡ የተወጋውን ጎኑን፣ የተቸነከረውን እጁን፣ እግሩን አሳያቸው፡፡ በዓለመ ነፍስ የኾነውን እያስተማራቸው ዐርባ ቀን ኖረ፤›› (ቅዳሴ ዘሠለስቱ ምዕት ፬፥፳፭-፳፯)፡፡

‹‹ሰማያት (ሰማያውያን መላእክት) የደስታ በዓልን ያደርጋሉ፤ ደመናት (ቅዱሳን) የደስታን በዓል ያደርጋሉ፡፡ ምድር (ምድራውያን ሰዎች) በክርስቶስ ደም ታጥባ (ታጥበው) የፋሲካን በዓል ታደርጋለች (ያደርጋሉ)፤ ያከብራሉ (ታከብራለች)፡፡ ዛሬ በሰማያት (በሰማያውያን መላእክት) ዘንድ ታላቅ ደስታ ኾነ፡፡ ምድርም በክርስቶስ ደም ታጥባ የፋሲካን የነጻነት በዓል ታደርጋለች፡፡ የትንሣኤያችን በኩር ክርስቶስ ከሙታን ሰዎች ዅሉ ተለይቶ ቀድሞ ተነሣ፤›› (ቅዱስ ያሬድ፣ ድጓ ዘፋሲካ)፡፡

‹‹ሞትን በሥጋ በቀመሰ ጊዜ መለኮቱ በመቃብር ውስጥ ያለነፍሱ ከበድኑ ጋር ነበር፡፡ በሲኦልም ውስጥ ያለ ሥጋው ከነፍሱ ጋር ህልው ነበር፡፡ በአባቱም ቀኝ ያለ ነፍስና ያለ ሥጋ ህልው ነበር፡፡ በትንሣኤውም ጊዜ ነፍሱን ከሥጋው ጋር አዋሕዶ አስቀድሞ ለአይሁድ ‹ይህን ቤተ መቅደስ አፍርሱት፤ በሦስተኛው ቀን እሠራዋለሁ› ብሎ እንደ ተናገረ፡፡ አይሁድም ‹ይህ ቤተ መቅደስ ተሠርቶ ያለቀው በዐርባ ሰባት ዓመት ነው፤ አንተ ግን በሦስት ቀን እሠራዋለሁ ትላለህ› አሉት፤ ይህንንም የተናገረው ስለ ራሱ ሰውነት ነው፡፡ በተነሣም ጊዜ ደቀ መዛሙርቱ ስለዚህ ነገር እንደ ተናገረ አሰቡ፡፡ በመጽሐፍና ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስም የተናገራቸውን ቃል አመኑ፤ ሁለተኛም ‹ነፍሴን በፈቃዴ አሳልፌ እሰጣለሁ፤ ልለያት መልሼም አዋሕጄ ላስነሣት ሥልጣን አለኝ፤ ይህንንም ትእዛዝ ከአባቴ ተቀበልሁ› ብሏል፡፡ ዳዊትም ‹አቤቱ የመቅደስህን ታቦት ይዘህ ተነሥ› ይላል፡፡ ነቢዩ ‹አቤቱ አንተ የመቅደስህን ታቦት ይዘህ ተነሥ› ለምን አለ? የመቅደሱ ታቦት ከኾነችው ከዳዊት ዘር ከነሣው ሥጋ ጋር በመለኮታዊ ኃይሉ ከሞት እንቅልፍ ከመንቃት በስተቀር የእግዚአብሔር መነሣት ምንድን ነው?›› (አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ መጽ. ምሥጢር ዘትንሣኤ ፸፯-፸፱)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ትንሣኤ ክርስቶስ በሊቃውንት – የመጀመርያ ክፍል

በመምህር ሳሙኤል ተስፋዬ

ሚያዝያ ፲፱ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

የጌታችን አምላካችንና መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ትንሣኤ የድኅነታችን ብሥራት በመኾኑ ለአምሳ ቀናት ያህል በቤተ ክርስቲያን በቅዳሴው፣ በማኅሌቱ፣ በወንጌሉ ወዘተ. ይዘከራል፡፡ በዚህ ሰሙን ‹‹ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን …›› እየተባለ ሞት መደምሰሱ፣ ነጻነት መመለሱ ያታወጃል፡፡ በየጊዜያቱና በየዘመናቱ የተነሡ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንም ስለ ክርስቶስ ትንሣኤ ከዚህ ቀጥሎ የተገለጠውን ትምህርትና ምስክርነት ሰጥተዋል፤

‹‹ከሙታን ተለይቶ ተነሥቶ ሲኦልን ረግጦ፣ በሞቱ ሞትን አጠፋው፤ በሦስተኛው ቀንም ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ ‹አባት ሆይ፤ አመሰግንሃለሁ› ብሎ ሥግው ቃል አመሰገነ፤›› (እልመስጦአግያ ዘሐዋርያት ፭፥፩)፡፡

‹‹እንደ ሞተ እንዲሁ ተነሣ፤ ሙታንንም አስነሣ፡፡ እንደ ተነሣም እንዲሁ ሕያው ነው፤ አዳኝ ነው፡፡ በዚህ ዓለም እንደ ዘበቱበት፣ እንደ ሰደቡት፣ እንዲሁ በሰማይ ያሉ ዅሉ ያከብሩታል፤ ያመሰግኑታል፡፡ ለሥጋ በሚስማማ ሕማም ተሰቀለ፤ በእግዚአብሔርነቱ ኃይል ተነሣ፤ ይኸውም መለኮቱ ነው፡፡ ወደ ሲኦል ወርዶ ነፍሳትን ማረከ፤›› (ቅዱስ ሄሬኔዎስ፣ ሃይ. አበ. ፯፥፳፰-፴፩)፡፡

‹‹እንዲህ ሰው ኾኖም ሰውን ፈጽሞ ያድን ዘንድ ታመመ፤ ሞተ፤ ተቀበረ፡፡ በሦስተኛውም ቀን ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፤›› (ሠለስቱ ምዕት፣ ሃይ. አበ. ፲፱፥፳፬)፡፡

‹‹ሞትን ያጠፋው፣ ከሙታን ተለይቶ በመነሣቱ የሞት ሥልጣን የነበረው ዲያብሎስን የሻረው እርሱ ነው፡፡ ሰው የኾነ፣ በሰው ባሕርይ የተገለጠ አምላክ ነው፡፡ እግዚአብሔር ያደረበት ዕሩቅ ብእሲ አይደለም፤ ሰው የኾነ አምላክ ነው እንጂ፡፡ ፈጽሞ ለዘለዓለሙ በእውነት ምስጋና ይገባዋል፤›› (ቅዱስ አትናቴዎስ፣ ሃይ. አበ. ፳፭፥፵)፡፡

‹‹ሥጋው በመቃብር ያሉ ሙታንን አስነሣ፤ ነፍሱም በሲኦል ተግዘው የነበሩ ነፍሳትን ፈታች፡፡ በዚያም ሰዓት የጌታችን ሥጋው በመስቀል ላይ ተሰቅሎ ሳለ መቃብራት ተከፈቱ፤ ገሃነምን የሚጠብቁ አጋንንትም ባዩት ጊዜ ሸሹ፡፡ የመዳብ ደጆች ተሰበሩ (ሊቃነ አጋንንት፣ ሠራዊተ አጋንንት ድል ተነሡ)፡፡ የብረት ቁልፎቿም ተቀጠቀጡ (ፍዳ፣ መርገም ጠፋ)፡፡ ቅድስት ነፍሱ በሲኦል ተግዘው የነበሩ የጻድቃን ነፍሳትን ፈታች፤›› (ዝኒ ከማሁ ፳፮፥፳-፳፩)፡፡

‹‹ሥጋ ከመለኮቱ ሳይለይ በመቃብር አደረ፤ ነፍሱም ከመለኮት ሳትለይ በገሃነም ተግዘው ለነበሩ ነፍሳት ደኅነትን ታበስር ዘንድ፣ ነጻም ታደርጋቸው ዘንድ ወደ ሲኦል ወረደች፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ እንደ ተናገረው ቃል ዐፅም፣ ሥጋ ወደ መኾን ፈጽሞ እንደ ተለወጠ የሚናገሩ የመናፍቃንን የአእምሮአቸውን ጉድለት ፈጽመን በዚህ ዐወቅን፡፡ ይህስ እውነት ከኾነ ሥጋ በመቃብር ባልተቀበረም ነበር፡፡ በሲኦል ላሉ ነፍሳት ነጻነትን ያበስር ዘንድ ወደ ሲኦል በወረደ ነበር እንጂ፡፡ ነገር ግን ከነፍስና ከሥጋ ጋር የተዋሐደ ቃል ነው፡፡ እርሱ የሥጋ ሕይወት በምትኾን በአካለ ነፍስ ወደ ሲኦል ወርዶ ለነፍሳት ነጻነትን ሰበከ፡፡ ሥጋ ግን በበፍታ እየገነዙት በጎልጎታ በዮሴፍ በኒቆዲሞስ ዘንድ ነበረ፤ ቅዱስ ወንጌል እንደ ተናገረ፡፡ አባቶቻችን ሥጋ በባሕርዩ ቃል አይደለም፤ ቃል የነሣውሥጋ ነው እንጂ ብለው አስተማሩን፤ ይህንን ሥጋም ከሙታን ተለይቶ ከተነሣ በኋላ ቶማስ ዳሠሠው፤ በሥጋው ሲቸነከር ቃል ታግሦ የተቀበለውን የችንካሩን እትራትም (ምልክት) በእርሱ አየ፤›› (ዝኒ ከማሁ ፴፥፴፩-፴፮)፡፡

‹‹አሁን እግዚአብሔር ሞተ ሲል ብትሰማ አትፍራ፤ ‹የማይሞተውን ሞተ ሊሉ አይገባም› ከሚሉ፤ ዕውቀት ከሌላቸው፤ ሕማሙን፣ ሞቱን ከሚክዱ መናፍቃን የተነሣ አትደንግጥ፡፡ እኛ ግን በመለኮቱ ሞት እንደ ሌለበት፤ በሥጋ ቢሞትም በመለኮቱ ሥልጣን እንደ ተነሣ እናውቃለን፡፡ ሞት የሌለበት ባይኾንስ ኖሮ በሥጋ በሞተ ጊዜ ሥጋውን ባላስነሣም ነበር፤ ሥጋው እስከ ዓለም ፍጻሜ በመቃብር በኖረ ነበር እንጂ፤›› (ቅዱስ ባስልዮስ፣ ሃይ. አበ. ፴፬፥፲፯-፲፰)፡፡

‹‹ከመስቀሉ ወደ ሲኦል በመውረዱ አዳነን፤ በአባታቸው በአዳም በደል በሲኦል ተግዘው የነበሩ ጻድቃንን ፈታ፤ ከሙታን ተለይቶ አስቀድሞ በተነሣ በእውነተኛ ትንሣኤውም አስነሣን፡፡ የንስሐንም በር ከፈተልን፤›› (ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘኑሲስ፣ ሃይ. አበ. ፴፮፥፴)፡፡

‹‹በአባታችን በአዳም በደል የተዘጋ የገነት ደጅን የከፈተልን፤ ዕፀ ሕይወትን የሚጠብቅ ኪሩብንም ያስወገደው፤ የእሳት ጦርን ከእጁ ያራቀ፤ ወደ ዕፀ ሕይወት ያደረሰን እርሱ ነው፡፡ ፍሬውንም (ሥጋውን፣ ደሙን) ተቀበልን፡፡ አባታችን አዳም ሊደርስበት ወዳልተቻለው፤ በራሱ ስሕተት ተከልክሎበት ወደ ነበረው መዓርግ ደረስን፡፡ ክፉውንና በጎውን ከሚያስታውቅ፤ ወደ ጥፋት ከሚወስድ፤ በአዳምና በልጆቹም ላይ ኃጢአት ከመጣበት ከዕፀ በለስ ፊታችንን መለስን፤›› (ዝኒ ከማሁ ፴፮፥፴፰-፴፱)፡፡

‹‹የሕይወታችን መገኛ የሚኾን የክርስቶስ ሞት የእኛን ሞት ወደ ትንሣኤ እንደ ለወጠ እናምናለን፤ ክርስቶስም ሞትን አጥፍቶ የማታልፍ ትንሣኤን ገለጠ፤ እንደ ተጻፈ፡፡ ከሰው ወገን ማንም ማን ሞትን ያጠፋ ዘንድ፣ ትንሣኤንም ይገልጣት ዘንድ አይችልም፤ ዳዊት ‹በሕያውነት የሚኖር፤ ሞትንም የማያያት ሰው ማነው? ነፍሱን ከሲኦል፤ ሥጋውን ከመቃብር የሚያድን ማን ነው?› ብሎ እንደ ተናገረ፤›› (ቅዱስ አቡሊዲስ፣ ሃይ. አበ. ፵፪፥፮-፯)፡፡

‹‹በመለኮትህ ሕማም፣ ሞት የሌለብህ አንተ ነህ፡፡ በሥጋ መከራ የተቀበልህ አንተ ነህ፡፡ ከአብ ጋር አንድ እንደ መኾንህ ሞት የሌለብህ አንተ ነህ፡፡ ከእኛም ጋር አንድ እንደ መኾንህ በፈቃድህ የሞትህ አንተ ነህ፡፡ በመቃብር ያደርህ አንተ ነህ፡፡ በኪሩቤል ላይ ያለህ አንተ ነህ፡፡ ከሙታን ጋር በመቃብር የነበርህ አንተ ነህ፡፡ በአንተ ሕማምና ሞትም ድኅነት ተሰጠ፤ ከሙታን ጋር የተቆጠርህ አንተ ነህ፤ ለሙታንም ትንሣኤን የምትሰጥ አንተ ነህ፡፡ ሦስት መዓልት፤ ሦስት ሌሊት በመቃብር ያደርህ አንተ ነህ፤ በዘመኑ ዅሉ ከአብ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር የምትኖር አንተ ነህ፤ በመለኮት ሕማም ሳይኖርብህ በሥጋ የታመምክ አካላዊ እግዚአብሔር ቃል አንተ ነህ፤›› (ቅዱስ ኤራቅሊስ፣ ሃይ. አበ. ፵፰፥፲፪-፲፫)፡፡

‹‹እኛስ ኃጢአታችንን ለማስተሥረይ በሥጋ እንደ ታመመ፤ እንደ ሞተ፤ ከነፍሱም በተለየ ጊዜ ሥጋውን እንደ ገነዙ፤ ከሙታንም ተለይቶ በእውነት እንደ ተነሣ፤ ከተነሣም በኋላ በእውነት ወደ ሰማይም እንደ ዐረገ እናምናለን፡፡ በኋላም በሚመጣው ዓለም እርሱ በሕያዋንና በሙታን ይፈርድ ዘንድ ይመጣል፡፡ የሰውን ወገኖች ዅሉ በሞቱበት፤ በተቀበሩበት ሥጋ ከሞት ያስነሣቸዋል፡፡ ከትንሣኤውም በኋላ ያለ መለወጥ ዅልጊዜ ይኖራል፡፡ እርሱ በዚህ በሞተበት፤ በተገነዘበት ሥጋ ከሙታን አስቀድሞ እንደ ተነሣ፤›› (ቅዱስ ዮሐንስ ዘኢየሩሳሌም፣ ሃይ. አበ. ፶፪፥፲፩-፲፪)፡፡

‹‹የሥጋን ሕማም ለመለኮት ገንዘብ በአደረገ ጊዜ የእግዚአብሔር አካል በባሕርዩ በግድ ሕማምን አልተቀበለም፤ ሕማም በሚስማማው ባሕርዩ ኃይልን እንጂ፡፡ ሞትም በሥጋ ለእግዚአብሔር ቃል ገንዘብ በኾነ ጊዜ ሞትን አጠፋ፡፡ ከሞትም በኋላ ፈርሶ፣ በስብሶ መቅረትን አጠፋ፤›› (ቅዱስ ቴዎዶጦስ ሃይ. አበ. ፶፫፥፳፯)፡፡

‹‹መለኮት በሥጋ አካል በመቃብር ሳለ የሥጋ ሕይወት በምትኾን በነፍስ አካል ወደ ሲኦል ወረደ፤ እንደዚህ ባለ ተዋሕዶ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ፡፡ ከትንሣኤ በኋላ አይያዝም፤ አይዳሰስም፡፡ በዝግ ቤት ገብቷልና፡፡ ነገር ግን ምትሐት እንዳይሉት ቶማስ ዳሠሠው፡፡ የተባለውን ከፈጸመ በኋላ ቶማስ አመነበት፤›› (ቅዱስ ኤጲፋንዮስ፣ ሃይ. አበ. ፶፮፥፴፯-፴፰)፡፡

‹‹ክርስቶስ የሙታን በኵር እንደምን ተባለ? እነሆ በናይን ያለች የደሀይቱን ልጅ አስቀድሞ አስነሣው፤ ዳግመኛም አልዓዛርን በሞተ በአራተኛው ቀን አስነሣው፡፡ ኤልያስም አንድ ምውት አስነሣ፡፡ ደቀ መዝሙሩ ኤልሣዕም ሁለት ሙታንን አስነሣ፤ አንዱን ሳይቀበር፣ ሁለተኛውን ከተቀበረ በኋላ ሥጋውን አስነሣ፡፡ እነዚያ ሙታን ቢነሡ ኋላ እንደ ሞቱ፤ እነርሱ ኋላ አንድ ኾነው የሚነሡበትን ትንሣኤ ዛሬ ተስፋ ያደርጋሉ፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን የሙታን ትንሣኤያቸው በኵር ነው፡፡ ‹እንግዲህ ወዲህም ሞት የሌለበትን ትንሣኤ አስቀድሞ የተነሣ እርሱ ነው፤ ዳግመኛም ሞት አያገኘውም› ተብሎ እንደ ተጻፈ፤›› (ቅዱስ ኤጲፋንዮስ፣ ሃይ. አበ. ፶፯፥፫-፮)፡፡

‹‹ቃል ሥጋውን በመቃብር አልተወም፤ በሲኦልም ካለች ከነፍሱ አልተለየም፡፡ ከነፍስ ከሥጋ በአንድነት ነበረ እንጂ፡፡ ለዘለዓለም ክብር ምስጋና ይግባው፤›› (ቅዱስ ጎርጎርዮስ ዘእንዚናዙ ሃይ. አበ. ፷፥፳፱)፡፡

‹‹ጌታ ለደቀ መዛሙርቱ ‹በትንሣኤ ከእናንተ ጋር እስከምመጣበት ቀን ድረስ ከዚያ ወይን ጭማቂ አልጠጣም፤ በሐዲስ ግብር በምነሣበት ጊዜ የምታዩኝ እናንት ምስክሮቼ ናችሁ› ያለውን የማቴዎስን ወንጌል በተረጐመበት አንቀጽ እንዲህ አለ፤ ሐዲስ ያለው ይህ ነገር ምንድን ነው? ይህ ነገር ድንቅ ነው! መዋቲ ሥጋ እንዳለኝ ታያላችሁ፤ ነገር ግን ከትንሣኤ በኋላ የማይሞትነው፤ አይለወጥም፤ ሥጋዊ መብልንም መሻት የለበትም፤ ከትንሣኤ በኋላ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር ቢበላም ቢጠጣም መብልን ሽቶ አይደለም፤ እርሱ ከሙታን ተለይቶ እንደ ተነሣ ያምኑ ዘንድ በላ ጠጣ እንጂ፡፡ ይህ ድንቅ ሥራ ነው! ያለ መለወጥ ሰው የኾነ ቃል የተቸነከረበትን ምልክት (እትራት) አላጠፋምና፡፡ በሚሞቱ ሰዎች እጅ እንዲዳሠሥ አድርጎታልና፡፡ አምላክ የኾነ ሥጋ የሚታይበት ጊዜ ነውና አላስፈራም፡፡ እርሱ በዝግ ደጅ ገባ፤ ግዙፉ ረቂቅ እንደ ኾነ ሥራውን አስረዳ፡፡ ነገር ግን በትንሣኤው ያምኑ ዘንድ የተሰቀለው እርሱ እንደሆነ የተነሣውም ሌላ እንዳይደለ ያውቁ ዘንድ ይህን ሠራ፡፡ ስለዚህም ተነሣ፤ በሥጋውም የችንካሩን ምልክት (እትራት) አላጠፋም፤ ዳግመኛም ከትንሣኤው አስቀድሞ ደቀ መዛሙርቱ ጧት ማታ ከእርሱ ጋር ይበሉ እንደ ነበረ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር በላ፤ ስለዚህም በአራቱ መዓዝነ ዓለም ትንሣኤውን አስረዱ፡፡ ከትንሣኤውም በኋላ ‹ያየነው ከእርሱም ጋር የበላን የጠጣንም እርሱ ነው› ብለው አስረዱ፤›› (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ሃይ. አበ. ፷፮፥፯-፲፪)፡፡

ይቆየን

በዓለ ትንሣኤን በትንሣኤ ልቡና እናክብር

በገብረ እግዚአብሔር ኪደ

ሚያዝያ ፲፰ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

 ፋሲካ ማለት መሻገር ማለት ነው፡፡ እግዚአብሔር ወልድ እኛን ከወደቅንበት አንሥቶና ተሸክሞ ከዚኽ ምድር ወደ ሰማያት ተሻግሯልና (ተነሥቶ ዐርጓልና)፡፡ ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ፡- ‹‹እንግዲኽ ከክርስቶስ ጋር ከተነሣችኁ ክርስቶስ በእግዚአብሔር ቀኝ ተቀምጦ ባለበት በላይ ያለውን ሹበላይ ያለውን አስቡ እንጂ በምድር ያለውን አይደለም፡፡ ሞታችኋልና ሕይወታችኁም በእግዚአብሔር ከክርስቶስ ጋር ተሰውሯልና፡፡ ሕይወታችኁ የኾነ ክርስቶስ በሚገለጥበት ጊዜ እናንተ ደግሞ ከእርሱ ጋር በክብር ትገለጣላችኁ፤›› እንዳለን /ቈላ.፫÷፩-፬/፣ በጥምቀት ውኃ ሞቱን በሚመስል ሞት ስንሞት፣ አሮጌው ሰውነታችን እንደ ግብጻውያን ተቀብሮ ቀርቷል፡፡ አዲሱ ሰውነታችን ግን እስራኤላውያን ባሕሩ ተከፍሎላቸው እንደ ተሻገሩ ተሻግሯል (ተነሥቷል)፡፡

ብልየት ያለበት የቀዳማዊ አዳም ሰውነታችን በግብረ መንፈስ ቅዱስ ተቀብሮ አዲሱ ሰውነታችን ሕይወትን አግኝቶ ተነሥቷል፡፡ መሬታዊው ሰውነታችን ሞቶ ሰማያዊው ሰውነታችንን ለብሰን መንፈሳውያን ኾነን ተነሥተናል፡፡ ወደ ጥንተ ተፈጥሯችን ተመልሰናል፡፡ አኹን ከእኛ የሚጠበቀው ይኽ ተፈጥሯችንን ሳናቆሽሽ መጠበቅ ነው፤ እንደ ተነሣን መዝለቅ፡፡ ይኽን ለማድረግም ተራራ መውጣት፣ ምድርን መቆፈር፣ የእሳት ባሕርን መሻገር አይጠበቅብንም፡፡ ይኽን ጠብቀን እንድንቈይ እግዚአብሔር ከእኛ የሚፈልገው አንድ ነገር ብቻ ነው፤ ፈቃዳችንን፡፡ የሚሠራው እርሱ ራሱ ነውና /ዮሐ.፲፭÷፭/፡፡ መጽንዒ (የሚያጸና) መንፈስ ቅዱስን ያደለንም ስለዚኹ ነው፡፡

የምናመልከውን አምላክ መስለን በሕይወት ሳንሻገር የመሻገርን በዓል (ፋሲካን) የምናከብረው ምን ጥቅም እንዲሰጠን ነው? ከጨለማ ሥራ ወደ ብርሃን ሥራ፣ ከፍቅረ ዓለም ወደ ፍቅረ ክርስቶስ ሳንሻገር ፋሲካን የማክበራችን ትርጕሙ ምንድነው? እኛው ሳንነሣ የመነሣት በዓልን ማክበራችን በፍርድ ላይ ፍርድ በበደል ላይ በደል ከመጨመር ውጪ የሚሰጠን ጥቅም ምንድን ነው? የምንነሣውስ መቼ ነው? በዐይናችን ጉድፍ ብትገባ ስንት ደቂቃ እንታገሣታለን? ታድያ በነፍሳችን ላይ የተጫነውን የኃጢአት ግንድ መቼ ነው የምናስወግደው? መቼ ነው ወደ ላይኛው ቤታችን ቀና የምንለው? ብዙዎቻችን በሕይወታችን ሳንሻገር ነው በዓለ ፋሲካን የምናከብረው፡፡ ክርስቲያን ኾኖ በመብልና በመጠጥ ብቻ ፋሲካን ማክበር ኢ ክርስቲያናዊ ተግባር ነው፡፡

አዲሱን ሰውነታችን ለብሰን ከተነሣን በኋላ እንደ ቀድሞ ምልልስ የምንጓዝ ከኾነ ግን ተመልሰን ወድቀናል፤ አዲሱ ሰውነታችንን አውልቀን አሮጌውን ሰውነታችንን በድጋሜ ለብሰነዋል፡፡ በእኛነታችን ውስጥ ፍቅረ ንዋይ፣ ፍቅረ ሲመት፣ ፍትወት፣ ይኽንንም የመሰሉ ዅሉ ካለ አዲሱ ሰውነታችን ከእኛ ጋር የለም፤ ቢኖርም ታሟል፡፡ በኃጢአት የመቃጠል ስሜት፣ ርኵሰትና ክፉ ምኞት ከእኛ ዘንድ ካለ አሮጌ ሰው ኾነናል፤ ትንሣኤ ልቡናን ገንዘብ አላደረግንም፡፡ ስለዚኽ ከልቡና ሞት እንነሣና ፋሲካን እናክብር፡፡ እስከ አኹን በኃጢአት ውስጥ ካለን ወደ ብርሃን ክርስቶስ እንምጣ (እንሻገርና) የመሻገርን በዓል እናክብር፡፡ ከክፉ ሥራ ወደ ጽድቅ ሥራ እንሻገርና የእውነት ፋሲካን እናክብር፡፡ ከኃይል ወደ ኃይል እንሻገርና ፋሲካን እናክብር፡፡ ከሞት ሥራ ወደ ሕይወት ሥራ እንነሣና የመነሣትን በዓል እናክብር፡፡

እግዚአብሔር የሚወዳችሁ አንድም እግዚአብሔርን የምትወዱት ሆይ! እኛን የሚያሰነካክል ደግሞም የሚጥለን ፈርዖን (ዲያብሎስ) ተሰነካክሎ ወድቋልና ከግብጽ ሕይወታችን እንውጣ፡፡ ተነሥተንም እንሻገር፡፡ ተሻግረንም ሰማያዊውን ፋሲካ እናክብር፡፡ በግብጽ የነበሩት እስራኤላውያን የበጉን ደም በጉበኑና በኹለቱም መቃን ሲቀቡት አጥፊው ከቤታቸው እንዳለፈ አንብበናል /ዘፀ.፲፪÷፲፫/፡፡ ይኸውም በጉ በራሱ ያንን የማድረግ ኃይል ስለ ነበረው አይደለም፤ ደሙ የክርስቶስ ደም አምሳል ስለ ነበር ነው እንጂ፡፡ እኛ ግን የአማናዊውን በግ /ዮሐ.፩፡፳፱/ ደም በልቡናችን፣ በአስተሳሰባችንና በሰውነታችን ዅሉ እንቀባና (እንቀበልና) እንሻገር፡፡

ይኽን ስናደረግ በእባቡና በጊንጡ ይኸውም በዲያብሎስና በሠራዊቱ ላይ ሥልጣን ይኖረናል /ሉቃ.፲÷፲፱/፡፡ የምንበላው በግ ራሱ ሕይወት ስለ ኾነ ሞት በእኛ ላይ አይነግሥም /ዮሐ.፲፬÷፮/፡፡ በዚኽ ዓለም ሳለን ከዚኽ ደስታ ተካፋዮች ከኾንን (የመዠመሪያውን ትንሣኤ ልቡና በንስሐ ከተነሣን) በሚመጣው ዓለምም በክብር ላይ ክብር፣ በሹመት ላይ ሹመት እንቀበላለን (ኹለተኛውን ትንሣኤ እንነሣለን) /ሉቃ.፳፪÷፲፭-፲፮/፡፡ ብንወድቅ እንኳን መልሰን በመነሣት ከባሕርይ አባቱ ከአብ፣ ከባሕርይ ሕይወቱ ከመንፈስ ቅዱስ ጋር ክብር፣ የክብር ክብር፣ ጌትነት የባሕርዩ በሚኾን፤ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ሰጭነት በመንግሥተ ሰማያት ጸጋ ክብር እናገኛለንና የጭንቅ ቀን ሳይመጣ በዓለ ትንሣኤን እናክብር፡፡ ለዚህም ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የመከረንን የሚከተለውን ኃይለ ቃል በተግባር ላይ ብናውለው እንጠቀማለን፤

‹‹በምነግራችኁ ነገር እያበሳጨኋችሁና እያሳመምችሁ እንደ ኾነ ይገባኛል? ግን ምን ላድርግ? እኔም እናንተም በምግባር በሃይማኖት የታነጽን እንኾን ዘንድ ብቻ ሳይኾን ከዚያም እናመልጥ ዘንድ ነው፡፡ ነገር ግን በኃጢአት ከመጨማለቃችን የተነሣ እንዴት አድርጌ ላሳምማችኁ እችላለኁ? ብትሰሙኝና ብትለወጡስ እኔም ማረፍ እንኳን በቻልኩ ነበር፡፡ ስለዚኽ እስካልተለወጣችሁ ድረስ እናንተን መገሠንና መምከሬን አላቆምም፡፡ ስለ ገነመ እሳት ተደጋግሞ ሲነገር የሚበሳጭ ሰው ሊኖር ይችላል፡፡ እኔ ግን ከዚኽ የበለጠ ያማረ የተወደደ አስደሳች ትምህርት የለም እለዋለኁ፡፡ እንዴት ይኽ አስደሳች ትምህርት ነው ትለናለህ? ልትሉኝ ትችላላችሁ፡፡ እኔም ወደዚያ መጣል ከደስታ ዅሉ የራቀ ነውናብዬ እመልስላችኋለሁ፡፡ ስለዚኽ ነፍሳችን ከመታሠሯ በፊት የነቃን የተጋን እንኾን ዘንድ ይኽን ደጋግሜ እነግራችኋለሁ፡፡ ስሐ ይግባ እንጂ ማንም እንደ ተወቀሰ አያስብ፤ በንግግሬም የሚቆጣ አይኑር፡፡ ዅላችንም ወደ ጠባቢቱ መንገድ እንግባ፡፡ እስከ መቼስ በስንፍና አልጋ እንተኛለን? ዛሬ ነገ ማለት አይበቃንም ወይ? ሰማያዊ ቪላችንን ቀና ብለን ብንመለከት እኮ በዚኽ ምድር ይኽንን ለመሥራት ባልደከምን ነበር፡፡ እስቲ ንገሩኝ! ሩጫችንን ስንጨርስ ከሬሳ ሳጥንና ከመግነዝ ጨርቅ ውጪ ይዘነው የምንሔድ ነገር ምን አለ? ታድያ ለምን እንከራከራለን?›› (ሰማዕትነት አያምልጣችሁ እና ሌሎች፣ ገጽ ፻፶፮ – ፻፶፯)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

ሰሙነ ፋሲካ (ከዕለተ ትንሣኤ እስከ ዳግም ትንሣኤ)

በሊቀ ትጉሃን ኃይለ ጊዮርጊስ ዳኘ

ሚያዝያ ቀን ፳፻፱ .

ከትንሣኤ እሑድ ቀጥለው ያሉት ዕለታት ‹ሰሙነ ፋሲካ› ወይም ‹ትንሣኤ› እየተባሉ የሚጠሩ ሲኾን፣ የየራሳቸው ምሥጢራዊ ስያሜም አላቸው፡፡ ስያሜአቸውንም በአጭሩ እንደሚከተለው እንመለከታለን፤

ሰኞ

የትንሣኤው ማግሥት ሰኞ ጌታችን በትንሣኤው ነፍሳትን ከሲኦል አውጥቶ ወደ ገነት አሻግሮ ለማስገባቱ መታሰቢያ ሰትኾን፣ ‹ፀአተ ሲኦል› ወይም ‹ማዕዶት› ትባላለች (ዮሐ. ፲፱፥፲፰፤ ሮሜ. ፭፥፲-፲፯)፡፡

በዳግም ትንሣኤው ማግሥት ያለችው ሰኞ ደግሞ ገበሬው፡- ወንዶቹ እርሻ ቁፋሮውን፣ ንግዱን፣ ተግባረ እዱን ዅሉ፤ ሴቶቹ፡- ወፍጮውን፣ ፈትሉን፣ ስፌቱን የሚጀምሩባት ዕለት ስለ ኾነች ‹እጅ ማሟሻ ሰኞ› ትባላለች፡፡

ማክሰኞ 

የትንሣኤው ዕለት እሑድ ማታ ጌታችን በዝግ ቤት ገብቶ ለሐዋርያት ሲገለጽ ሐዋርያው ቶማስ ከእነርሱ ጋር አልነበረም፡፡ በኋላ ከሔደበት ሲመጣ ሌሎቹ ሐዋርያት ትንሣኤውን ቢነግሩት ‹‹እኔ ሳላይ አላምንም›› ብሎ ነበር፡፡ በሳምንቱ ቶማስ በተገኘበት ጌታችን በድጋሜ ለሐዋርያት ተገለጸ፡፡ ስለዚህም ይህቺ ዕለት በሐዋርያው ቶማስ ስም ተሰይማለች (ዮሐ. ፳፥፳፬-፴)፡፡ 

ረቡዕ 

ጌታችን ከሞተና ከተቀበረ ከአራት ቀን በኋላ ከመቃብር ጠርቶ ላስነሣው ለአልዓዛር መታሰቢያ ትኾን ዘንድ፤ በክርስቶስ ሥልጣን የአልዓዛርን ከሞት መነሣት አይተው ብዙ ሕዝብ በጌታችን ስለ አመኑ ዕለቲቱ (ረቡዕ) ‹አልዓዛር› ተብላ ትታሰባለች (ዮሐ. ፲፩፥፴፰-፵፮)፡፡ 

ኀሙስ 

ይህቺ ዕለት ‹‹ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ (አምስት ሺሕ ከአምስት መቶ ዓመት ሲፈጸም) ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ፤›› ተብሎ ቃል የተገባለት የአዳም ተስፋው ተፈጽሞ ከነልጅ ልጆቹ ወደ ቀደመ ክብሩ ለመግባቱ መታሰቢያ ኾና ‹የአዳም ኀሙስ› ወይም ‹አዳም› ተብላ ትከበራለች (ሉቃ. ፳፬፥፳፭-፵፱)፡፡

ዐርብ

ከሆሣዕና ቅዳሜ በፊት ያለችው ዐርብ ደግሞ የጌታችን ዐርባው ጾም የሚፈጸምባት የጾመ ድጓው ቁመትም የሚያበቃባት ዕለት በመኾኗ በቤተ ክርስቲያን ‹ተጽዒኖ› ትባላለች፡፡ የከባድ ሥራ ማቆሚያ (ማብቂያ) ዕለት በመኾኗም በሕዝቡ ዘንድ ‹የወፍጮ መድፊያ፣ የቀንበር መስቀያ› ትባላለች፡፡

ዳግኛም በመጀመርያ የሰው ልጆች አባትና እናት የኾኑት አዳምና ሔዋን ስለተፈጠሩባት፤ በኋላም በሐዲስ ኪዳን ጌታችን ለቤዛ ዓለም ስለ ተሰቀለባትና የማዳን ሥራውን ስለ ፈጸመባት ‹ዕለተ ስቅለት፣ አማናዊቷ ዐርብ› ትባላለች፡፡

የሰሙነ ፋሲካዋ ማለትም የትንሣኤ እሑድ ስድስተኛዋ ዐርብ ደግሞ በክርስቶስ ደም ለተመሠረተችው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን መታሰቢያ ትኾን ዘንድ ‹ቤተ ክርስቲያን› ተብላ ትጠራለች (ማቴ. ፳፮፥፳፮-፳፱፤ ሐዋ. ፳፥፳፰)፡፡

ቀዳሚት ሰንበት

በሰሙነ ፋሲካው ያለችው ቀዳሚት ሕዝቡ ከአንዳንዱ በስተቀር ገበያ እንኳን ስለማይገበያይባት ‹የቁራ ገበያ፣ የገበያ ጥፊያ› ስትባል፣ በቤተ ክርስቲያን ግን በዘመነ ሥጋዌው በገንዘባቸውና ጉልበታቸው ላገለገሉት፤ በስቅለቱ ዋይ ዋይ እያሉ እስከ ቀራንዮ ድረስ ለተከተሉት፤ በትንሣኤው ዕለት በሌሊት ወደ መቃብሩ ሽቱና አበባ ይዘው ለገሰገሱት፤ በትንሣኤውም ጌታችን ከዅሉ ቀድሞ ለተገለጸላቸው ቅዱሳት አንስት መታሰቢያ ኾና ‹ቅዱሳት አንስት› ተብላ ትጠራለች (ማቴ. ፳፭፥፩-፲፩፤ ሉቃ. ፳፫፥፳፯-፴፫፤ ፳፬፥፩-፲)፡፡

የዋናው ትንሣኤ ሳምንት እሑድ

በዚህች ሰንበት ከላይ እንደ ተጠቆመው ጌታችን በትንሣኤው ዕለት ማታ በዝግ በር ገብቶ፣ በቅዱሳን ሐዋርያት መካከል ተገኝቶ «ሰላም ለዅላችሁ ይኹን!» ብሎ ትንሣኤውን ሲገልጽላቸው ሐዋርያው ቶማስ አልተገኘም ነበር፡፡

በኋላ ከሔደበት ሲመጣ ጌታችን እንደ ተነሣ እና እንደ ተገለጸላቸው ሐዋርያት በደስታ ሲነግሩት «በኋላ እናንተ ‹አየን› ብላችሁ ልትመሰክሩ፤ ልታስተምሩ፤ እኔ ግንሰምቼአለሁ› ብዬ ልመሰክር፤ ላስተምር? አይኾንም፡፡ እኔም ካላየሁ አላምንም» በማለቱ የሰውን ዅሉ፤ ይልቁንም የመረጣቸው ወዳጆቹን የልብ ሐሳብ የሚያውቀው፣ ቸርነቱ ወሰን የሌለው የባሕርይ አምላክ መድኃኔ ዓለም ክርስቶስ ልክ እንደ መጀመሪያው ትንሣኤ ዕለት አበው ሐዋርያት በተዘጋ ቤት በአንድነት ተሰባስበው እንዳሉ በሩን ሳይከፍት ገብቶ «ሰላም ለዅላችሁ ይኹን!» በማለት በመካከላቸው ቆመ፡፡

ቶማስንም «ያመንህ እንጂ ተጠራጣሪ አትኹን፤ እነሆ የተቸነከሩ እጆቼንና እግሮቼን፣ የተወጋ ጐኔንም ናና እይ፤» ብሎ አሳየው፡፡ እርሱም ምልክቱን በማየቱ፣ በመዳሰሱ ትንሣኤውንና አምላክነቱን እንደ ፍላጎቱ በመረዳቱ «ጌታዬ፣ አምላኬ ብሎ መስክሮ» አመነ፡፡ ስለዚህም ማለትም የትንሣኤው ምሥጢር ለሁለተኛ ጊዜ ለሐዋርያት የተገለጠበት ዕለት በመኾኑ የትንሣኤው ሳምንት እሑድ ‹ዳግም ትንሣኤ› ተብሎ ይጠራል፤ ይከበራል (ዮሐ. ፳፥፳፬-፴)፡፡

በአጠቃላይ በቅድስት ቤተ ክርስቲያን በሰሙነ ፋሲካ የሚፈጸመው መንፈሳዊና ሐዋርያዊ አገልግሎት ዅሉ ልክ እንደ መጀመሪያው የትንሣኤ ሥርዓት ኾኖ ይከናወናል፡፡ ብርሃነ ትንሣኤውን የገለጸልን አምላካችን ለብርሃነ ዕርገቱም በሰላም ያድርሰን!

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡

የትንሣኤ በዓል ትርጕሙና አከባበሩ

በሊቀ ትጉሃን ኃይለ ጊዮርጊስ ዳኘ

ሚያዝያ ፲ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም

እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሰን!

«ትንሣኤ» የሚለው ቃል የግእዝ ቃል መገኛው ‹ተንሥአ = ተነሣ› የሚለው ግስ ሲኾን፣ ትርጕሙም መነሣት፣ አነሣሥ፣ አዲስ ሕይወትን ማግኘት ማለት ነው፡፡ ‹ትንሣኤ› በየመልኩ፣ በየዓይነቱ ሲተረጐም አምስት ክፍል አለው፤

የመጀመርያው ትንሣኤ ሕሊና ነው፤ ይህም ማለት ተዘክሮተ እግዚአብሔር (እግዚአብሔርን ማሰብ) ነው፡፡

ሁለተኛውም ትንሣኤ ልቡና ነው፤ የዚህም ምሥጢሩ ቃለ እግዘብሔርን መስማትና በንስሐ እየታደሱ በሕይወት መኖር ነው፡፡

ሦስተኛው ትንሣኤ ለጊዜው (በተአምራት) የሙታን በሥጋ መነሣት ነው፡፡ ነገር ግን በድጋሜ ሌላ ሞት ይከተለዋል፡፡

አራተኛው ትንሣኤ ክርስቶስ በሥልጣኑ ሞትን ድል አድርጎ መነሣቱን ያመላክታል፡፡ የርእሰ ትምህርታችን መነሻም ይህ ነው፡፡

አምስተኛውና የመጨረሻው የትንሣኤ ደረጃ የባሕርይ አምላክ የጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ትንሣኤ መሠረት ያደረገ ትንሣኤ ዘጉባኤ ሲኾን፣ ይህም ከዓለም ኅልፈት በኋላ ሰው ዅሉ እንደየሥራው ለክብርና ለውርደት፣ ለጽድቅና ለኵነኔ በአንድነት የሚነሣው የዘለዓለም ትንሣኤ ነው፡፡

ወደ ርእሳችን ስንመለስ የትንሣኤ በዓል በምሥጢሩም፣ በይዘቱም ከኦሪቱ በዓለ ፋሲካ ጋር ስለሚመሳሰል ‹ፋሲካ› ተብሎ ይጠራል፡፡ ‹ፋሲካ› ማለት በዕብራይስጥ ቋንቋ ‹ፌሳሕ›፤ በጽርዕ (በግሪክ) ‹ስኻ› ይባላል፡፡ ይህም ወደ እኛው ግእዝና አማርኛ ቋንቋችን ሲመለስ ፍሥሕ (ደስታ)፣ ዕድወት፣ ማዕዶት (መሻገር፣ መሸጋገር)፣ በዓለ ናእት (የቂጣ በዓል፣ እየተቸኮለ የሚበላ መሥዋዕት) ማለት ነው፡፡ የዚህም ታሪካዊ መነሻው በዘመነ ኦሪት ይከበር የነበረው በዓለ ፋሲካ ሲኾን፣ ይህም እስራኤል ዘሥጋ ከግብጽ የባርነት ቀንበር ወደ ነጻነት የተላለፉበት፤ ከከባድ ኀዘን ወደ ፍጹም ደስታ የተሸጋገሩበት በዓል ነው፡፡ በዚህ ኦሪታዊ (ምሳሌ) በዓል አሁን አማናዊው በዓል በዓለ ትንሣኤ ተተክቶበታል፡፡

ፋሲካ (በዓለ ትንሣኤ) በዘመነ ሐዲስ እስራኤል ዘነፍስ የኾንን ምእመናን የክርስቶስን ትንሣኤ የምናከብርበት ዕለት ነው፡፡ ይህ በዓል ከኃጢአት ወደ ጽድቅ፤ ከውርደት ወደ ክብር፤ ከጠላት ሰይጣን አገዛዝ ወደ ዘለዓለማዊ ነጻነት፤ ከአደፈ፣ ከጐሰቆለ አሮጌ ሕይወት ወደ አዲስ ሕይወት የተሻገርንት ከበዓላት ዅሉ የበለጠ የነጻነት በዓል ነው፡፡ ስለዚህም ክርስቲያኖች በታላቅ ደስታና መንፈሳዊ ስሜት በዓሉን እናከብረዋለን፡፡

መድኃኒታችን ሞትን በሞቱ ድል ነስቶ፣ ሙስና መቃብርን አጥፍቶ፣ በሥልጣኑ የተነሣው መጋቢት ፳፱ ቀን በ፴፬ ዓ.ም እንደ ኾነ ታሪከ ቤተ ከርስቲያን ያስረዳል፡፡ የትንሣኤ በዓል መከበር የጀመረው በቅዱሳን ሐዋርያትና በሰብዐ አርድእት፣ ኋላም በየጊዜው በተነሡ ሊቃውንትና ምእመናን ነው፡፡ ድምቀቱና የአከባበር ሥርዓቱ ይበዛ፣ ይቀነስ እንደ ኾነ እንጂ በዓሉ መከበሩ ተቋርጦ አያውቅም፡፡

በቅብብሎሽ ከዚህ በደረሰው ትውፊት መሠረት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰሙነ ሕማማት ግብረ ሕማማቱን ስታነብ ሰንብታ ለትንሣኤ እሑድ አጥቢያ ማታ በ፪ ሰዓት «ለጸሎት ተሰብሰቡ» ስትል የደወል ድምፅ ታሰማለች፡፡ ካህናቱም በቤተ ክርስቲያን ተሰብስበው ሥርዓቱን በጸሎት ይጀምራሉ፡፡ ሕዝቡም በቤተ ክርስቲያን ይሰባሰባል፡፡ ካህናቱ መዝሙረ ዳዊት፣ ነቢያት፣ ሰሎሞንና ውዳሴ ማርያም ከተደረሰ በኋላ «ተፈሥሒ ማርያም ለአዳም ፋሲካሁ» የሚለውን ግጥማዊ የደስታ መዝሙር ይዘምራሉ፡፡

ምንባቡ፣ ጸሎቱና ሌላውም ሥርዓት ከተፈጸመ በኋላ ጸሎተ አኰቴት ተደርሶ ዲያቆኑ ነጭ ልብሰ ተክህኖ ለብሶ፣ አክሊል ደፍቶ፣ መስቀል ይዞ፣ በጌታችን መቃብር በራስጌና በግርጌ በታዩት መላእክት ምሳሌ እንደ እርሱው ነጭ ልብሰ ተክህኖ በለበሱ፣ ድባብ ጃንጥላ በያዙ፣ መብራት በሚያበሩ ሁለት ዲያቆናት ታጅቦ በቅድስት ቆሞ፡- «ወተንሥአ እግዚአብሔር ከመ ዘንቃህ እምንዋም፣ ወከመ ኀያል ወኅዳገ ወይን፣ ወቀተለ ፀሮ በድኅሬሁ፤ እግዚአብሔር ከእንቅልፍ እንደሚነቃ ተነሣ፤ የወይን ስካር እንደ ተወው ኃያል ሰውም ጠላቱን በኋላው ገደለ፤» የሚለውን የዳዊት መዝሙር በረጅም ያሬዳዊ ዜማ ይሰብካል (መዝ. ፸፯፥፷፭)፡፡

ካህናቱም ከበሮ እየመቱና በእርጋታ እያጨበጨቡ ተቀብለው ይዘምራሉ፡፡ ሕዝቡም በጭብጨባና በዕልልታ የደስታ ዝማሬው ተሳታፊ ይኾናል፡፡ ይህ ምስባክ በዲያቆኑና በመላው ካህናት ሁለት ሁለት ጊዜ፤ በዲያቆኑና በመላው ካህናት አንድ ጊዜ (በጋራ) ይዘመራል፡፡ ይህም በድምሩ አምስት መኾኑ አምስት ሺሕ አምስት መቶ ዘመን ሲፈጸም በጌታችን ሞትና ትንሣኤ ዓለም ለመዳኑ ምሳሌያዊ ማስረጃ ነው፡፡ በመቀጠል ካህኑ ትንሣኤውን የሚያበሥር ትምህርት ከማቴዎስ፣ ከማርቆስና ከሉቃስ ወንጌል አውጥቶ ያነባል፡፡ የዮሐንስ ወንጌል በቅዳሴ ጊዜ ይነበባል (ዮሐ. ፳፥፩-፱)፡፡

በማስከተል ከሊቃውንቱ መካከል ሥራው የሚመለከተው ወይም የተመደበው ባለሙያ (መዘምር) መስቀል ይዞ «ትንሣኤከ ለእለ አመነ» የሚለውን እስመ ለዓለም ከቃኘ በኋላ ለበዓሉ ተስማሚ የኾነው አርያም ተመርቶ በመቋሚያ ይዘመማል፡፡ ከዚያም «ዮም ፍሥሐ ኮነ በሰንበተ ክርስቲያን፣ እስመ ተንሥአ ክርስቶስ እሙታን = ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ተነሥቷልና በሰንበተ ክርስቲያን ዛሬ ደስታ ኾነ …፤» የሚለው አንገርጋሪ በመሪና በተመሪ ይመለጠናል፤ በግራ በቀኝ እየተነሣ ይዘመማል፤ ይጸፋል፡፡

በዚህ ጊዜ «በጨለማ የነበራችሁ ሕዝቦች የትንሣኤውን ብርሃን እዩ፤ ብርሃኑንም ወስዳችሁ የብርሃኑ ተካፋይ ኹኑ፤» እያለች ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ያዘጋጀችውን ጧፍ እያበራች ታድላቸዋለች፡፡ ወዲያውኑም ‹‹ትንሣኤከ ለእለ አመነ ብርሃነከ ፈኑ ዲቤነ = ለአመነው ለእኛ ብርሃንህን ላክልን፤›› የሚለውን እስመ ለዓለም እየዘመሩ፣ መብራት እያበሩ ካህናቱና ሕዝቡ ዑደት ያደርጋሉ (ቤተ ክርስቲያኑን ይዞራሉ)፡፡

መዘምራኑና ካህናቱ ከዑደት ሲመለሱ «ይእቲ ማርያም» የተባለው የኪዳን ሰላም ይጸፋና ኪዳን ተደርሶ ሲያበቃ እንደ ቦታው ደረጃ ፓትርያርክ ወይም ሊቀ ጳጳስ ወይም ቆሞስ ወይም ቄስ ዘለግ ባለ ድምፅ በንባብ «ክርስቶስ ተንሥአ እሙታን = ክርስቶስ ከሙታን ተለይቶ ተነሣ» ሲሉ ካህናቱና መዘምራኑ ‹‹በዐቢይ ኃይል ወሥልጣን = በታላቅ ኃይልና ሥልጣን» ብለው ይቀበላሉ፡፡ አሁንም ካህኑ «አሰሮ ለሰይጣን = ሰይጣንን አሰረው» ባለ ጊዜ መላው ካህናት «አግዐዞ ለአዳም = አዳምን አርነት ነጻ አወጣው» ይላሉ፡፡

በመቀጠል «ሰላም = ሰላም፣ አንድነት፣ ፍቅር» ሲሉ ዅሉም «እምይእዜሰ = ከዛሬ ጀምሮ» ብለው ይቀበላሉ፡፡ ካህኑም «ኮነ ፍሥሐ ወሰላም = ሰላምና ደስታ» ብለው ሦስት ጊዜ አውጀው «ነዋ መስቀለ ሰላም» እያሉ መስቀል ሲያሳልሙ ካህናቱና ሕዝቡም «ዘተሰቅለ ቦቱ መድኃኔ ዓለም» እያሉ ይሳለማሉ፡፡ ካህኑም «እግዚአብሔር ይፍታ» ይላሉ፡፡ ግብረ ሕማማት ሲነበብበት ከሰነበተው ጠበልም ይረጫል፡፡ የተረፈውንም ጠበል ሕዝቡ ለበረከት ወደየቤቱ ይወስደዋል፡፡

ከዚያም ልኡካኑ ለቅዳሴ እየተዘጋጁ መዘምራኑ ምስባክ መወድሱን ካዜሙ በኋላ በመቋሚያ ይዘሙታል፡፡ አያይዞም ይትፌሣሕ› የተባለውን መዝሙር ቃኝተው ከዘመሙ በኋላ «… ወምድርኒ ትገብር ፋሲካ፤ ተኀፂባ በደመ ክርስቶስ = … ምድርም በክርስቶስ ደም ታጥባ ፋሲካውን ታደርጋለች፤» እያሉ ይጸነጽላሉ፡፡ አያይዘውም የመዝሙሩን ሰላም ይጸፋሉ፡፡ መንፈቀ ሌሊት ሲኾንም ቅዳሴ ተቀድሶ ሥርዓተ ቍርባን ይፈጸማል፡፡ ከዚያም ሠርሖተ ሕዝብ = የሕዝብ ስንብት ከኾነ በኋላ ካህናቱም ሕዝቡ ወደየቤታቸው ሔደው እንደየባህላቸው ይፈስካሉ (ይገድፋሉ)፡፡

የመግደፊያ ዝግጅት ለሌላቸው ነዳያንም በየመንደሩ እየተዞረ «እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሳችሁ» እየተባለ ከሥጋውም፣ ከአይቡም፣ ከቅቤውም ከመጣጣሙም፣ ከእርጐውም ይታደላል፡፡ ከትንሣኤ እሑድ ጀምሮ እስከ ዳግም ትንሣኤ ድረስ ሕዝበ ክርስቲያኑ «እንኳን ለብርሃነ ትንሣኤው በሰላም አደረሳችሁ» እየተባባለ በዚህ መልኩ አብሮ እየበላ፣ እየጠጣ፣ እየተደሰተ እግዚአብሔርን ሲያመሰግን ይሰነብታል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር፡፡