ኒቆዲሞስ

ሚያዚያ 12 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

እግዚአብሔር “ጾምን ቀድሱ ጉባኤውንም ዐውጁ ሽማግሌዎችንና በምድር የሚኖሩትን ሁሉ ወደ አምላካችሁ ወደ እግዚአብሔር ሰብስቡ ወደ እግዚአብሔርም ጩኹ በጽዮን መለከት ንፉ ጾምንም ቀድሱ” በማለት ዐውጀን መጾም ያለብንን ጾም እንድንፆም በነብዩ ኢዩኤል ነግሮናል፡፡ ኢዩ.1፥14፣ 2፥15

እግዚአብሔር ሙሴን በእሥራኤል ልጆች ዘንድ ከሰውም ከእንስሳም ማኅፀንን የሚከፍት በኲርን ሁሉ ለእኔ ቀድስልኝ በማለቱ /ዘጸ.13፥12 ከሰው፣ ከዕለታትት ተለይተው የተቀደሱ ነበሩ፡፡ አጽዋማትም በዐዋጅ ተለይተው ይጾማሉ፡፡ ከእነዚህ ውስጥም፡- የዐብይ ጾም ይገኛል፡፡

ዐብይ ጾም ዐብይነቱ ነብያት፣ ሐዋርያት፣ ቅዱሳን የጾሙት ጾም ሳይሆን የጠፋውን የሰውን ልጅ ለመፈለግ፣ የሞተውን አዳምን ለማስነሣት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰው ሆኖ ወደዚህ ዓለም የመጣው ወልደ አብ ወልደ ማርያም በመብል የተጀመረውን የሞት መንገድ ለማጥፋት በጾም ስለጀመረው ነው፡፡

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በመዋዕለ ሥጋዌው ያደረጋቸውን የድኅነት ጉዞና ድንቅ ድንቅ ተአምራት ዋጋ የተከፈለባቸው በመሆናቸው አባቶቻችን በሠሩልን ሥርዓት መሰረት በዐብይ ጾም ወራት ዘወረደ ብለን ጀምረን ትንሣኤ ብለን አስከምናከብርበት ድረስ ያሉትን ሰንበታት ለሰው ልጆች የተከፈለልንን ዋጋ እያሰብን እንማረዋለን፣ አንዘምራለን፣ እንጸልያለን፡፡ ከነዚህ ሰንበታት በ7ኛ ደረጃ ላይ የሚገኘው ደግሞ ኒቆዲሞስ ተብሎ ተሰይሞ ይከበራል፡፡

ከፈሪሳውያን ወገን የአይሁድ አለቃ በነበረው በኒቆዲሞስ የተሰየመ ሰንበት ነው፡፡ የአይሁድ አለቆች አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስን “ምልክት አሳየን” እያሉ ይፈታተኑት ነበር፡፡ ስለሞቱና ትንሣኤው በምሳሌ ቢነግራቸው አልገባቸውም፡፡ ሲያስተምር ብዙዎች ያምኑ ነበር፡፡ ለአይሁድ አለቆች ግን ጭንቅ ነበር፤ የታመሙ ሲፈወሱ ሕጋችን ተሻረ ይሉ ነበር፡፡ በዚህ ሁሉ ተአምራትና ትምህርት የአይሁድ አለቆች ክርስቶስን ለመክሰስ በሚፈልጉበት ወቅት ከአይሁድ አለቆች አንዱ ኒቆዲሞስ በቀን እንዳያደርገው አይሁድን ፈርቶ አንድም ጊዜ አላደርሰው ብሎ እንደ አይሁድ አለቆች ኢየሱስን መቃወሙን ትቶ በሌሊት ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ ሄደ፡፡

አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ በነፍስ የታመሙትን በቃሉ በሥጋ የታመሙትን በተአምራቱ ሲፈውስ፤ ኒቆዲሞስ ሰምቶና ተመልክቶ “መምህር ነኝ” ብሎ በመምህርነቱ ሳይኮራ አለቅነቱን መመኪያ ሳያደርግ፡፡ በልቦናው የተሳለውን እውነትን የመፈለግ ስሜት አንግቦ ጌታው መምህሩ ዘንድ በሌሊት ገሠገሠ ዮሐ.3÷1

ደርሶም ምስክርነቱን እንዲህ ሲል መስጠት ጀመረ “መምህር ልታስተምር ከእግዚአብሔር ዘንድ እንደመጣህ እናውቃለን፡፡ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር ከሆነ በቀር አንተ የምታደርገውን ተአምራት ሊያደርግ የሚችል የለምና” ዮሐ.9÷24፣ የሐዋ.ሥራ 10÷38 በማለት መመስከር ሲጀምር ጎዶሎን የሚሞላ፡፡ አላዋቂነት በአዋቂነት የሚለውጥ፡፡ ከምድራዊ እውቀት ወደ ሰማያዊ ምስጢር የሚያሸጋግር አምላክ፡፡ “ዳግመኛ ያልተወለደ የእግዚአብሔርን መንግሥት ለማየት አይችልም” ዮሐ.3÷6 1ጴጥ.1÷23 በማለት የአይሁድ መምህር ለሆነው ኒቆዲሞስ ቢያስተምረው ስለዳግመኛ መወለድ ከመጽሐፍ ቢያገኘውም ምስጢሩ አልተገለጠለትምና “ሰው ከሸመገለ በኋላ ዳግመኛ መወለድ እንደምን ይቻላል? ዳግመኛ ይወለድ ዘንድ ወደ እናቱ ማኅፀን ተመልሶ መግባት ይችላልን?” በማለት ጥያቄ አቅርቧል፡፡

“እውነት እውነት እልሃለሁ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ያልተወለደ ወደ እግዝአበሔር መንግሥት ሊገባ አይችልም፡፡ ኤፌ.5÷26 ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፡፡ ከመንፈስም የተወለደ መንፈስ ነውና፡፡ በማለት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቢያስረዳው ምስጢሩ ከአቅሙ በላይ የሆነበት ኒቆዲሞስ እንደምን ይቻላል? በማለት ጠይቋል፡፡ አበ ብዙኀን አብርሃም ከአምላኩ ሞገስን አግኝቶ፤  የሰዶምና ገሞራ ጥፋት እንዳይደርስ እያማለደ ከእግዚአብሔር ጋር ሲነጋገር እንደ ነበረ፤ ኒቆዲሞስም አላዋቂነቱን አምኖ ያልገባውን ምስጢር አምላኩን የመጠየቅ ዕድል በማግኘቱ ሲጠይቅ፣ ኢየሱስ ክርስቶስም “አንተ የእስራኤል መምህራቸው ነህ ግን ይህን ነገር አታውቅምን? በምድር ያለውን ስንነግራቸው ካላመናችሁ በሰማይ ያለውን ብንነግራችሁ እንደምን ታምናላችሁ? ከሰማይ ከወረደው ከሰው ልጅ በቀር ወደ ሰማይ የወጣ የለም ….፡፡ሙሴ ምድረ በዳ እባቡን እንደ ሰቀለ የሰው ልጅ እንዲሁ ይሰቀላል፡፡ ያመኑበት ሁሉ ለዘለዓለም ሕያው ሆኖ እንዲኖር እንጂ እንዲጠፉ አይደለም…..” ዮሐ.3÷14፡፡ እያለ ለድኅነተ ዓለም እንደ መጣ ሰው በመብል፣ አምላኩን ከድቶ ልጅነቱን ትቶ ከእግዚአብሔር ቢለይም የሰው ልጅ ያጣውን ልጅነት ለመመለስ ስመ ግብርና ሀብተ ወልድን ለመስጠት መምጣቱን አስረዳው፡፡ “ሐወጽከኒ ሌሊተ ወፈተንኮ ለልብየ፡፡ አመከርከኒ ወኢተረከ በዓመፃ በላዕሌየ፡፡ ከመ ኢይንብብ አፉየ ግብረ እጓለ እመሕያው፡፡ ልቤን ፈተንከው በሌሊትም ጎበኘኸኝ ፈተንከኝም ምንም አላገኘህብኝም፡፡ የሰውን ሥራ አፌ እንዳይናገር ፈቃዴ ነው” መዝ.16÷3 እንዳለ ቅዱስ ዳዊት ምስጢረ ሥጋዌን የድኅነት ምስጢር ገልጾለታል፡፡

በሌሊት ከአምላኩ ተምሮ ምስጢሩ የተገለጸለት ኒቆዲሞስ ፍርሃት ርቆለት ቀድሞ በአደባባይ ሄዶ መማርን የፈራ ምስጢሩ ሲገለጽለት አይሁድ በሰቀሉት ዕለት ሳይፈራ ከአርማትያሱ ዮሴፍ ጋር ቅዱስ ሥጋውን ገንዞ ለመቅበር በቃ “ወአልቦ ፍርሃት ውስተ ተፋቅሮትነ፡፡ ፍጹም ፍቅር ፍርሃትን አውጥቶ ይጥላል ማቴ.27÷58፣ 1ዮሐ.4÷18 እንዲል፡፡

ያመነ የተጠመቀ ይድናል፡፡ ያላመነ ያልተጠመቀ ይፈረድበታል ማር.16÷16፡፡ ባለው አማናዊ ቃል ኪዳን መሠረት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስን እንደ አምላክነቱ አምነን  ለመንግሥቱ ዜጋ እንድንሆን ለኒቆዲሞስ ምስጢሩን ጥበቡን የገለጸ አምላክ ለኛም ይግለጽልን፡፡

gedamat 11

የኔታ ይቆዩን የገዳማት ዐውደ ርእይ በፓሪስ ከተማ

ሚያዚያ 11 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ደረጄ ግርማ

 

gedamat 11የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማእከል የፈረንሳይ ግንኙነት ጣቢያ ገዳማትና አብነት ትምህርት ቤቶችን የሚያስተዋውቅ ዐውደ ርእይ ማዘጋጀቱን ገለጠ።

 

ዐውደ ርእዩም የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንን ታሪክና ለሀገር ያበረከተችውን አስተዋጽኦ፣ በተለይም ጥንታዊ ገዳማት ትናንትና ዛሬ እንዲሁም የአብነት ትምህርት ቤቶችን ነባራዊ ሁኔታ የሚዳስስ፤ እየተደረጉ ያሉ ድጋፎችን የሚጠቁም እንዲሁም ከሕዝበ ክርስቲያኑ የሚጠበቀውን ድርሻ የሚያመላክት ዐውደ ርእይ ይቀርባል።

ከዚህም በተጨማሪ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ስኮላርሸፕ፤ የላይ ቤት ትርጓሜ ፕሮጀክት እንዲሁም የቅዱስ ያሬድ 1500 ዓመት መታሰቢያ የሚያመላክቱ ጹሑፎች ቀርበው ውይይት ይደረግባቸዋል፡፡ ዐውደ ርእዩም ሚያዚያ ፲፰ ቀን ፳፻፭ ዓም ለፓሪስ እና አካባቢ ምእመናን እንደሚቀርብ ተገልጿል። ከፓሪስ ደብረ ም/ቅ/ማርያም ሰበካ ጉባኤ ጋር በመተባበር ሚያዚያ ፲፱ ቀን ፳፻፭ ዓም ልዩ የስብከተ ወንጌል መርሐ ግብር የተዘጋጀ ሲሆን በዕለቱም በገዳማት እና አብነት ትምህርት ቤቶች ወቅታዊ ሁኔታ ላይ ውይይት እንደሚካሄድ ከዝግጅቱ አስተባባሪ ኮሚቴ የደረሰን መረጃ አመልክቷል። ለዚህ ዝግጅት አስፈላጊውን ድጋፍ ለማድረግ የማኅበረ ቅዱሳን ቅዱሳት መካናትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አንድ ልዑክ እንዲሚልክ ለማወቅ ተችሏል።

 
በአውሮፓ የምትገኙ ሁላችሁም በዝግጅቱ እንድትታደሙ የተጋበዛችሁ ሲሆን በርቀት ያላችሁ ለመርሐ ግብሩ ስኬት በጸሎት እንድታግዟቸው አስተባባሪ ኮሚቴው ጥሪውን አስተላልፏል።

ዳግመኛ መወለድ(ለሕፃናት)

ሚያዚያ 10 ቀን 2005 ዓ.ም.

በቤካ ፋንታ

እንደምን ሰነበታችሁ ልጆች፡፡ ዛሬ የምንማረው የእግዚአብሔር ልጆች ሁሉ ለሁለተኛ ጊዜ እንደሚወለዱ ነው፡፡

አንድ መምህር በኢየሩሳሌም ነበረ፣ ስሙም ኒቆዲሞስ ይባላል፡፡ ቀን ቀን ተማሪዎቹን ሲያስተምር ይውልና ማታ ፀሐይዋ ስትጠልቅ በጨለማ ወደ አምላካችን ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ ይመጣል፡፡ ከዚያ እግሩ ሥር ቁጭ ብሎ ይማራል፡፡ ያልገባውን እየጠየቀ በደንብ ስለሚከታተል ጌታችንም እስኪገባው ድረስ ግልጽ አድርጎ ያስረዳውና የጠየቀውን ይመልስለታል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን ኒቆዲሞስ የእግዚአብሔርን ቃል ለመማር ከቤቱ ተነሥቶ በሌሊት ወደ ኢየሱስ ክርስቶስ ዘንድ መጣ፡፡ አምላካችንም በዚያ ሌሊት ለኒቆዲሞስ ያስተማረው ትምህርት እንዲህ የሚል ነበር፡፡ “ኒቆዲሞስ ሆይ፥ እውነት እውነት እልሃለሁ፥ ሰው ዳግመኛ ካልተወለደ በቀር ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ወደ መንግሥተ ሰማያት አይገባም፡፡”

ኒቆዲሞስም በጣም ደንግጦ “ዳግመኛ? መወለድ እንዴት ይቻላል? ሰው ደግሞ የሚወለደው አንዴ አይደለም እንዴ? ደግሞስ አንድ ሰው ካደገ ትልቅ ከሆነ በኋላ እንደገና ወደ እናቱ ማኅፀን ገብቶ ሊወለድ እንዴት ይችላል?” እያለ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ጠየቀው፡፡ ጌታችንም የጠየቀውን ጥያቄ በደንብ አድርጎ መለሰለት፡፡

ልጆች አሁን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወደ መለሰለት መልስ ከመሄዳችን በፊት ኒቆዲሞስ የጠየቀውን ጥያቄ ደግሜ ልጠይቃችሁ፡-

  1. የሰው ልጆች የምንወለደው ስንት ጊዜ ነው?

  2. ሁለተኛ ጊዜ የምንወለደው እንዴት ነው?

  3. ዳግመኛ የምንወለደው የት ነው?   

 

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከእግሩ ሥር ቁጭ ብለው ከሚማሩት ተማሪዎች መካከል ይህንን ጥያቄ ለጠየቀው ለኒቆዲሞስ “ዳግመኛ ልትወለዱ ያስፈልጋችኋል ስላልኩ እታድንቅ፡፡ የእኔ ልጆች እንድትሆኑ ዳግመኛ የምትወለዱት እንዴት፣ መቼ እና የት እንደሆነ አስረዳሃለሁ” ብሎ ድምፁን ከፍ አድርጎ ያስተማራቸው ትምህርት እንዲህ የሚል ነው፡-

ተማሪዎቼ ሆይ የሰው ልጆች በእናታቸው ማኅፀን ዘጠኝ ወር ከ5 ቀን ከቆዩ በኋላ ለመጀመሪያ ጊዜ ይወለዳሉ፡፡ ዳግመኛ የሚወለዱት ደግሞ በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም በመጠመቅ ነው፡፡ ሕፃናት ወንዶች እና ሴቶች ከተወለዱ በኋላ ወንድ ከሆነ በ40 ቀን ሴት ከሆነች 80 ቀን ሲሞላት እናትና አባታቸው አቅፈዋቸው ቅድስትና ንጽሕት ወደ ሆነች ወደ እግዚአብሔር ቤት ወደ ቤተ ክርስቲያን ይሄዳል፡፡ ከዚያ ሲደርሱ የእግዚአብሔር አገልጋዮች ቀሳውስትና ዲያቆናቱ ደስ ብሏቸው ሕፃናቱን ተቀብለው ወደ መጠመቂያው ቤት ይዘዋቸው ይገባሉ፡፡

በመጠመቂያው ቤት ቄሶቹ ልብሰ ተክህኖ ለብሰው፣ ትልቅ መስቀል ይዘው፣ ወንጌሉን ዘርግተው ቅዱሱን ወንጌል ካነበቡ በኋላ ቄሱ በትልቁ መስቀል ሕፃናቱ የሚጠመቁበትን በገንዳ ውስጥ ያለውን ውኃ “በአብ በወልድ በመንፈስ ቅዱስ ስም የተባረከ ይሁን” እያሉ ሲያማትቡበት ውኃው ተለውጦ ጸበል ይሆናል፡፡ ከዚህ በኋላ ሕፃናቱን በገንዳው ጸበል ውስጥ ሦስት ጊዜ ብቅ ጥልቅ፣ ብቅ ጥልቅ፣ ብቅ ጥልቅ እያደረጉ “በአብ ስም በወልድ ስም በመንፈስ ቅዱስ ስም አጠምቅሃለሁ” እያሉ ካህኑ ሲያጠምቋቸው ሕፃናቱ ለሁለተኛ ጊዜ ዳግመኛ ከውኃና ከመንፈስ ቅዱስ ይወለዳሉ፡፡

ከጸበሉ ሲወጡ ዲያቆኑ ሕፃናቱን ከፍ አድርጎ ሲይዝ ቄሱ በነጭ፣ በጥቁርና በቀይ ክሮች የተገመደውን ማኅተብ በመስቀል ከባረኩት በኋላ በሕፃኑ አንገት ላይ ያስሩለታል፡፡ መላ ሰውነቱንም ቅባ ሜሬን በተባለው ቅዱስ ቅባት እየቀቡት የልጁን ሰውነት ይባርኩታል፡፡ በመጨረሻም በእናት እና በአባታቸው እቅፍ ሆነው ወደ ቤተ መቅደስ ገብተው የአምላካችንን የኢየሱስ ክርስቶስን ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ይቀበላሉ፡፡

ይህንንም የተቀደሰ ሥርዓት በመፈጸም ዳግመኛ በመወለድ የእግዚአብሔር ልጅ የሆነ ሰው ወደ መንግሥተ ሰማያት ይገባል፡፡ በማለት አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለሚያስተምራቸውና ጥያቄውን ለጠየቀው ለኒቆዲሞስ አስተማራቸው፡፡

ጌታችን ኢየሱሱ ክርስቶስ እንዳስተማረን ትምህርት ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ሁል ጊዜ ይህን ታላቅና ቅዱስ ሥርዓት ለልጆችዋ እየፈጸመች ዳግመኛ ተወልደን የሥላሴ ልጆች እንድንሆን ታደርገናለች፡፡ ይህም ድንቅ ሥርዓት ለአንድ ሰው አንድ ጊዜ ብቻ የሚፈጸም ነው፡፡ ሥርዓቱም ምሥጢረ ጥምቀት በመባል ይጠራል፡፡

ልጆቹ እንድንሆን ዳግመኛ በጥምቀት የወለደን እግዚአብሔር ስሙ የተመሰገነ ይሁን አሜን፡፡

seletena 2 2

ከየማእከላቱ ለተውጣጡ ተጠሪዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና ተሰጠ

ሚያዚያ 9 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዳዊት ደስታ

seletena 2 2በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ከየማዕከላቱ ለተውጣጡ 38 የክፍል ተጠሪዎች ከሚያዝያ 4 ቀን 2005 ዓ.ም. በዋናው ማእከል የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥልጠና ተካሄደ፡፡

የሥልጠናውን ዓላማ አስመልክቶ የቅዱሳት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ዳይሬክተር ዲ/ን አእምሮ ይሄይስ “የማኅበሩን ስልታዊ ዕቅድ ተጠሪዎቹ ግንዛቤ ኖሮአቸው በቀጣይ በየማእከላቱ የሚሠሩትን ሥራ በተግባር ላይ እንዲያውሉ ለማስቻል  ነው” ብለዋል፡፡

አያይዘውም ሥልጠናው በዚህ ዓመት ለመጀመሪያ ጊዜ የተካሄደ ሲሆን፣ በቀጣይም  በገዳማት ላይ የሚሠራውን የልማት ሥራ በጋለ ሆኖ ከታሰበበት ለማድረስ ያግዛል ሲሉ ሓላፊው ገልጸዋል፡፡

ከሥልጠናው ተሳታፊዎች መካከል የደሴ ማእከል የቅዱስት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ክፍል ተጠሪ ወ/ት ስንታየው እሸቱ በሥልጠናው የተለያዩ ግንዛቤዎችን አግኝቻለሁ፡፡ በተለይ የአብነት ትምህርት ቤት ላይ የምንሠራቸውን ሥራ እንዴት ማጠናከርና ገቢ ማሰባሰብ እንዳለብን፣ ፕሮጀክት እንደምንቀርጽና እንደምንተገብር ተንዝቤያለሁ፡፡

ሌላው ከአሰበ ተፈሪ ማእከል የመጣው አቶ ብርሃኑ እንዳለ በሀገራችን በሚገኙአብያተ ክርስቲያናት የአገልጋይ እጥረት ይስተዋላል፡፡ ከዚህ አንጻር የአብነት ትምህርት ቤቶች ተተኪ አገልጋይ የሚፈራባቸው በመሆኑ ብዙ ሊሠራ እንደሚገባ የሚያመለክትና ችግሮችን ለመቅረፍ የሚያስችል ነው ብለዋል፡፡

ለሦስት ቀን በተካሄደው መርሐ ግብር ሉላዊነት እና የቤተ ክርስቲያን የማእከላት ድርሻ ምን መምሰል አለበት፣ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ስኮላር ሺፕ ፕሮግራም አፈጻጸም ማእከላት ድርሻቸው ምን መሆን አለበት፣ ቤተ ክርስቲያን ለልማት ያላት ምቹነትና ተግዳሮቶች፣ የሀብት ምንነት የፕሮጀክት ሠነድ ዝግጅት፣ የንግድ ዕቅድ ዝግጅት (ለገዳማት፣ አብያተ ክርስቲያናት፣ አብነት ት/ቤት ተማሪዎች) በሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ያተኮረ ሥልጠናና ውይይት ተደርጓል፡፡

በመርሐ ግብሩም ላይ የማኅበሩ ዋና ጸሐፊን ጨምሮ ከሁሉም ማእከላት የተውጣጡ 38 የቅዱሳት መካናት ልማት እና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ተጠሪዎች ተሳትፈዋል፡፡

tsebele tsedeke 3

ጸበል ጸዲቅ /ክፍል ሁለት/

ሚያዚያ 8 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

ደብረ ገነት ሸረት መድኀኔዓለም ገዳም
ሚያዚያ 4 ቀን 2005 ዓ.ም.

tsebele tsedeke 3ከንጋቱ 12፡30 ደምበጫ ከተማ ላይ ካረፍንበት የማኅበረ ቅዱሳን ከራድዮን ምግብ ቤት ተነስተን ከወረዳ ማእከሉ ወንድሞቻችን ጋር ሆነን ወደ ጽርሐ አርያም ቅዱስ ሚካኤል ቤተ ክርስቲያን በማምራት ጸሎት አደረስን፡፡ በያዝነው እቅድ መሠረት ዲያቆን ቴዎድሮስ ኃይሉና ዲያቆን ዮሴፍ ይኩኖ አምላክ የጽርሐ አርያምን ቤተ ክርስቲያን ታሪክ እንዲሰሩ እዚያው ትተናቸው የቴሌቪዥን ፕሮግራም አዘጋጁ ቶማስ በየነ፤ የቪዲዮ ካሜራ ባለሙያው ሙሉጌታ፤ ዲያቆን ታደለ ሲሳይና እኔ ሆነን የደብረ ገነት ሸረት መድኀኔዓለም ገዳምን ለመዘገብ ከጠዋቱ 1፡00 ሰዓት ሲሆን እግዚአብሔርን ተስፋ አድረገን በሾፌራችን ነብያት መንግስቴ እየተመራን የ47 ኪሎ ሜትሩን መንገድ ተያያዝነው፡፡

ዋድ የገጠር ከተማን፤ ዋድ ኢየሱስ፤ ዋድ ሥላሴ ቤተ ክርስቲያናትን አልፈን፤ ደግን ወንዝን ተሻግረን፤ ዘለቃን የገጠር ከተማን አልፈን ወደ ገዳሙ መግቢያ ደረስን፡፡ ከተራራው አናት ላይ ሆነው ወደ ገዳሙ ሲመለከቱ እልም ባለ በረሃ ውስጥ ለብቻው ለምልሞ የተገኘ የምድር ገነት ያስመስለዋል፡፡ በገዳሙ ውስጥ እግዚአብሔርን ደጅ በመጥናት በጸሎትና በልማት አገልግሎት ላይ የተጠመዱት መነኮሳትና መነኮሳይያት ማረፊያ ቤቶች፤ የመድኀኔዓለምንና የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያናትን በመክበብ እጅብ ብለው ደምቀው ይታያሉ፡፡  

አርባ ሰባት ኪሎ ሜትሩን ለማገባደድ 2፡30 ሰዓት ፈጅቶብን የደረስነው ከጠዋቱ 3፡00 ላይ ነው፡፡ ከመኪናችን ወርደን በእድሜ ጠገብ ዛፎች፤ ጥላ ተጋርደን የሙዝ፤ የፓፓያ፤ የብርቱካን፤ የአቦካዶ፤ . . . ዘርዝረን በማንጨርሳቸው የፍራፍሬዎችና የሸንኮራ አገዳ ተክሎችን እያለፍን ጸበል መጠመቂያ ሥፍራ ላይ ደረስን፡፡ ከተለያዩ የገዳሙ አቅራቢያ ከተሞችና የገጠር መንደሮች በመጡ ተጠማቂዎች ሕጻናትን ጨምሮ ተሞልቷል፡፡

ከተራራው ሥር የሚፈልቁ ምንጮች መውረጃ ቦይ ተዘጋጅቶላቸው አትክልቶቹን ያለመሰልቸት ያጠጣሉ፡፡ ጸበሉም ተጠማቂዎች ከተጠመቁ በኋላ ወደ አትክልልቶቹ መፍሰሱን ይቀጥላል፡፡ በግዮን፤ ኤፍራጥስና ጤግሮስ ወንዞች የተከበበ እስኪመስል ድረስ የንጹህ ውኃ ጅረቶች ከተለያዩ አቅጣጫዎች በልምላሜ በተሞላው ገዳም ተውጠው ይቀራሉ፡፡ የሚባክን ውሃ የለም፡፡ ድካማችን ሁሉ ከላያችን ላይ ተገፍፎ በብርታት፤ በእርካታና በተመስጦ ተሞልተናል፡፡ የምናያቸው፤ የምንሰማቸው ድምጾች ሁሉ አዳምና ሔዋን የኖሩባንት ገነትን tsebele tsedeke 5በዓይነ ሕሊናችን እንድናስብ አስገድዶናል፡፡ ደብረ ገነት ሽረት መድኀኔዓለም በምድር ላይ ያለች የገነት ተምሳሌት ሆና ታየችን፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ስንገባ በገዳሙ ውስጥ በምናኔና ገዳሙ በሚያከናውናቸው የልማትና የአስተዳደር ሥራዎች አበምኔቱን በማገዝ ላይ የሚገኙት አባ ዳዊትን ከሌሎች መነኮሳት ጋር በመሆን የእለት ተግባራቸውን በማከናወን ላይ እያሉ አገኘናቸው፡፡ ቡራኬ ተቀብለን በገዳሙ ሥርዓት መሠረት አባቶች አደግድገው እግራችንን አጠቡን፡፡

የገዳሙ መሥራችና አበምኔት አባ ገ/ኢየሱስ አካሉ ወደ ገዳሙ የሚያስገባውን ጥርጊያ መንገድ ለማሰራት ዘለቃ ወደሚባለው ከተማ በመሔዳቸው የምንፈልገውን መረጃ አባ ዳዊት ሊሰጡን እንደሚችሉ ተስማማን፡፡

አጭር መረጃ ስለ ገዳሙ፡- tsebele tsedeke 4
የደብረ ገነት ሸረት መድኀኔዓለም ገዳም በአባ ገ/ኢየሱስ አካሉ በ1969 ዓ.ም. ተመሠረተ፡፡ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን በ1973 ዓ.ም. በሣር ክዳን ተተከለች፡፡ ሥፍራው ጥቅጥቅ ያለ ጫካ የነበረ ሲሆን አንበሳ፤ ነብርና ዘንዶ በብዛት ይገኙ እንደነበር አባ ዳዊት ይገልጻሉ፡፡ ቀስ በቀስ ገዳማውያን እየተበራከቱ የልማት ሥራው እየሰፋ ሲሔድ የገዳሙ ይዞታም ሊሰፋ ችሏል፡፡ የክልሉ መንግስት በገዳሙ ውስጥ ከፍተኛ የልማት እንቅስቃሴ ከግምት ውስጥ በማስገባት ሰፊ የእርሻ መሬት ለገዳሙ ተሰጥቷል፡፡ ዳጉሳና በቆሎ እንዲሁም የሸንኮራ አገዳ በስፋት ይመረትበታል፡፡  

በሁለት ቦታዎች ላይ ሞፈር ቤቶች፤ ተራራው ላይ በስተደቡብ አቅጣጫ የአቡነ አረጋዊ ገዳም ቋርፍ ቤት ይገኛል፡፡ በገዳሙ ውስጥ 600 መናንያን ሲኖሩ 320ዎቹ መነኮሳት፤ 280ዎቹ ደግሞ መነኮሳይያት ናቸው፡፡ መነኮሳቱ በወንድ ሊቀ ረድእ፤ መነኮሳይቱ በሴት ለቀ ረድእ ይመራሉ፡፡ የእለት ተእለት ሥራቸውንም በሊቀ ረድኦቻቸው አማካይነት እየተመደቡ ያከናውናሉ፡፡ አረጋውያኑ ደግሞ በጸሎት፤ ቤተ ክርስቲያኑን በመጠበቅ፤ አትክልቶቹን ከአውሬ በመከላከል ገዳሙን ይረዳሉ፡፡ የገዳማውያኑ የጸሎት፤ የሥራና የምግብ ሰዓታትም የተወሰኑ ናቸው፡፡

የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም፤ የቅዱስ ሚካኤል፤ የአቡነ አረጋዊና የአባ ሳሙኤል ዘዋልድባ ታቦት በዚሁ ገዳም ይገኛሉ፡፡ የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተ ክርስቲያን ጣሪያው በሣር ክዳን የተሸፈነ ሲሆን ሳይፈርስ በቅርስነት እንዲያዝ በመወሰኑ ከመድኀኔዓለም ክርስቲያን በስተምእራብ አቅጣጫ ከተራራው ሥር ከሚገኘው ቋጥኝ ድንጋይ እየተጠረበ ቤተ ክርስቲያኑ በመገንባት ላይ ነው፡፡

የዮርዳኖስ ጸበል፤ የአቡነ አረጋዊ፤ የአቡነ ተክለ ሃይማኖትና የቅዱስ ሚካኤል ጸበል በገዳሙ ውስጥ የሚገኙ ሲሆን ሕሙማን እየተጠመቁ ፈውስ በማግኘት ላይ ናቸው፡፡  የዮርዳኖስ ጸበል አፈሩን ከኢየሩሳሌtsebele tsedeke 6ምና ከዋልድባ ገዳማት እንደመጣም አባ ዳዊት ገዳሙን እያስጎበኙን ነግረውናል፡፡

የአብነት ትምህርት ገዳሙ ከተመሠረተበት ጊዜ አንስቶ እየተሰጠ ይገኛል፡፡ ከ1975 ዓ.ም. እስከ 1977 ዓ.ም. በጉባኤ ቤቱ ቅዳሴን ከአባ ገብረ ማርያም ተምረው በማጠናቀቅ አባ ገብረ ማርያም ሌላ ገዳም ለማቅናት በመሄዳቸው ጉባኤውን የተረከቡት መምህር ገብረ ሥላሴ ፈንታ ለ28 ዓመታት የቅዳሴ ትምህርት በማስተማር ላይ ናቸው፡፡ ከሁለት መቶ በላይ ደቀመዛሙርትም እየተማሩ ይገኛሉ፡፡ ታላላቅ ሊቃውንትንም አፍርተዋል፡፡ በገዳሙ ውስጥ በአባ ገብረ ማርያም ከተማሩት አባቶች መካከልም ብፁዕ አቡነ አብርሐም አንዱ ናቸው፡፡

ይቆየን

ጸበል ጸዲቅ (ክፍል አንድ)

ሚያዚያ 8 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

የማኅበረ ቅዱሳን ጋዜጠኞች ቡድንን የያዘና ሰባት አባላትን ያቀፈው ልዑክ በምዕራብ ጎጃም፤ ደቡብ ጎንደርና ሰሜን ጎንደር የተመረጡ ቅዱሳት መካናትና አድባራትን ለመዘገብ ሃያ ሁለት ቀናት ቆይታ ለማድረግ ከሐሙስ ሚያዚያ 3 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ ወደ ሥፍራው ተንቀሳቅሰናል፡፡ በተጓዝንባቸው ቦታዎች ያጋጠሙንና እያከናወንናቸው ያሉትን ሥራዎች ለአንባቢያኑ እናቀርባለን፡፡ ሂደቱን በተመጠነና በቅምሻ መልክ የምናቀርብ በመሆኑ ከዚህም ከዚያም የምናገኛቸውን መረጃዎች ለአንባቢያን እናደርሳለን፡፡ በዚህም ምክንያት የጉዞ ማስታወሻችንን ጸበል ጸዲቅ በሚል ሰይመነዋል፡፡

መነሻ :-
መንገድህን ለእግዚአብሔር አደራ ስጥ፤ በእርሱም ታመን፤ እርሱም ያደርግልሃል /መዝ.36፥5/ እንዲል ቅዱስ ዳዊት መንገድ ከመጀመራችን በፊት በማኅበሩ ጽ/ቤት አሸኛኘት ተደርጎልናል፡፡ እስካሁን ማኅበሩ ካደረጋቸው የጋዜጠኞች የሕብረት ተልእኮ አንጻር ይህ ልዑክ በብዛት ሆኖ መጓዙና ብዛት ያላቸው ቅዱሳት መካናትን በማካለል ረገድ ለየት እንደሚያደርገው የተገለጸለት ሲሆን በጉዞው የተለያዩ ፈተናዎች ቢገጥሙት እንኳን በትዕግሥትና በጥበብ እግዚአብሔርን ተስፋ በማድረግ ተልእኮውን አሳክተን እንድንመለስ  አደራውን ተቀብለን በአባቶች ምክር፤ ጸሎትና ቡራኬ ተደርጎልን ተንቀሳቅሰናል፡፡

ከረፋዱ 4፤05 ሰዓት መነሻንን ብናደርግም ከመኪና ጥገና ጋር በተያያዘ ለተወሰኑ ሰዓታት በመቆየት ከቀኑ 7፡00 ሰዓት ጥገናውን በማጠናቀቅ ጉዞውን ጀመርን፡፡ ጫንጮ፤ ደብረ ጽጌ፤ ዳግማዊት ኢየሩሳሌም ደብረ ሊባኖስ ገዳም መገንጠያ፤ ፍቼ፤ ገደብ፤ ገብረ ጉራቻ፤ ኩዩን አልፈን  ጎሐ ጽዮን ከቀኑ 10፡00 ሰዓት ላይ ደረስን፡፡ ከጎሐ ጽዮን እስከ ዐባይ ድልድይ ያለውን የ20 ኪሎ ሜትር አስፈሪውን መንገድ የመኪናችን ሾፌር ነብያት መኪናውን እየተቆጣጠረ ጠመዝማዛና ቁልቁለታማውን መንገድ ካለ ስጋት እንድንጓዝ አስችሎናል፡፡ ፍርሃትና ጭንቀት ከእኛ እንዲርቁም የቴሌቪዥን ፕሮግራም አዘጋጁ ቶማስ በየነ ፈገግታ አዘል ጨዋታዎች አግዘውናል፡፡ ቪዲዮ ቀራጩ ሙሉጌታም አልፎ አልፎ ለቴሌቪዥን ፕሮግራም ግብአት የሚሆኑ ምስሎችን ለመውሰድ መኪናውን እያስቆመ ወርዶ ይቀርጻል፡፡ ሌሎቻችን ለራሳችን በሚመቸን መልኩ ውስጣችን የተፈጠረውን ስሜት በራሳችን አገላለጽ በማስታወሻ ደብተራችን እንከትባለን፡፡

ሃያ ኪሎ ሜትሩን አገባደን አባይ ድልድይ ደረስን፡፡ የኦሮሚያንና የአማራን ክልል የሚለየውን የአባይ ድልድይ ላይ ሁላችንም ወርደን ለማስታወሻና ለዘገባችን የሚረዳንን ፎቶ ግራፍ በመነሳትና በማንሳት ተመልሰን የአባይን ድልድይ ተሻግረን ቀሪውን እስከ ደጀን ያለውን 20 ኪሎ ሜትር ተያያዝነው፡፡

የአባይን ድልድይ እንደተሻገርን በሃምሳ ሜትር ርቀት ላይ የተተከለውን የአባይ ቅዱስ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን ተሳልመን አለፍን፡፡ የአባይ ቅዱስ ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ ጳጉሜን ሦስት ቀን በድምቀት እንደሚከበርና በእለቱም የአባይ ውኃ ወደ ጸበልነት እንደሚቀየር የቪዲዮ ባለሙያው ሙሉጌታ የሚያውቀውን ነገረን፡፡ ተራራውን እየወጣንም የኪዳነ ምሕረት፤ የቅዱስ ገብርኤል፤የአቡነ ተክለ ሃይማኖት፤ እንዲሁም የቅዱስ ገብርኤልን ቤተ ክርስቲያናትን እየተሳለምን አጠናቀን ደጀን ደረስን፡፡  

ከደጀን የትመን፤ ሉማሜ፤ አምበር፤ ራባ ጫካዎች፤ ደብረ ማርቆስን አልፈን ከምሽቱ 1፡30 ሰዓት ሲሆን ከአዲስ አበባ ደምበጫ ከተማ 350 ኪሎ ሜትር አጠናቀን የደምበጫ ወረዳ ማእከል አባላት ወንድሞቻችን በአክብሮት ተቀበሉን፡፡ ወዳዘጋጁልን ማረፊያም በማምራት በእንግድነት ተቀብለውናልና እግራችንን አጥበው እረፍት አደረግን፡፡ ከእራት በኋላም ውሏችንን በመገምገም እንዲሁም አርብ ስለምንሰራው ሥራ ውይይት በማድረግና ሌሊት የምንነሳበትን ሰዓት በመወሰን በአንድነት ጸሎት አድርሰን ተኛን፡፡
ሚያዚያ ሦስት ውሏችን ይህንን ይመስል ነበር፡፡ እንዲህም አለፈ፡፡

ይቆየን

ተረፈ አይሁዳዊነት በኤልያሳዊነት ስም ሲበቅል

ዲ/ን ማለደ ዋስይሁን

ሚያዝያ 8 ቀን 2005 ዓ.ም.

ባለፉት ሁለትና ሦስት ዓመታት ውስጥ አንዲት ሴት ”መሲህን ልወልድ ነው” እያለች ሰዎችን ታስከትል ነበር፡፡ ይህቺ ሴት አስገራሚ በሆነ ሁኔታ በየገዳማቱ እየዞረች ካህናቱን ሁሉ ለማንበርከክ ተንቀሳቅሳለች፡፡ ለዚህም ወንጪ ቂርቆስ ላይ ያደረገችውን ማስታወስ በቂ ነው፡፡

የዚህች ሴት አካሔድ አነጋጋሪ የሚሆነው ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ራሱ በደሙ በመሠረታት፣ ሥጋውና ደሙም በሚፈተትበት ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የአይሁድ ወገኖች አስተምህሮ የሚመስል ሰበካ ይዛ መገኘቷ ነው፡፡ የክርስቶስ ዳግም ምጽአት በምትጠባበቅ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ክርስቶስ ገና እንደሚወለድ ያለ አስተምህሮ ሲነገር መስማት ማሳፈሩ ብቻ ሳይሆን በጊዜው ቤተ ክርስቲያን ትንሹም ትልቁም በወደደ ጊዜ የሚሻውን የሚፈጽምባት፣ የሚናገርባት ተቋም ሆና እንደ ነበር የሚያሳይ ነው፡፡ ሴቲቱ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሊታሰብ የማይችል በማሰቧ፣ ሊነገር የማይችል በመናገሯ በአብዛኛው የክርስቲያን ወገን ይታሰብ የነበረው የአንዲት ሴት ከንቱ ቅዠት ተደርጎ ነው፡፡ ከዚህ አልፎ ተመሳሳይ ዝንባሌዎች ያቆጠቁጣሉ ብሎ ያሰበ የለም፡፡

 

እነሆ ዛሬ ደግሞ ሌላ የአይሁዳዊነት ዝንባሌ ያለው አስተምህሮ በኤልያስ ስም በተደራጀ ቡድን አማካኝነት ማብቀል ጀምሮ እስከ አራት መቶ ተከታዮች እንዳሉት እየተነገረ ነው፡፡ አስገራሚው ይኸው አስተምህሮ ተለጥፎ የመጣው በዚህችው በመከራ ውስጥ በምትጓዝ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ መሆኑ ነው፡፡ ስሙንም በተዋሕዶነት ሰይሞ ሲጓዝ አላፈረም፡፡ መከፋፈል፣ ማሰለፍ የሚፈልገውም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንን ነው፡፡ አስተምህሮው የተደበላለቀና ወጥ ያልሆነ ዘርፍ፣ መልክ፣ መነሻም መድረሻም የሌለው ክርስትና ይሁን አይሁዳዊነት ፖለቲካ ይሁን ሃይማኖት ጥንቆላ ይሁን እብደት ያለየለት እንቅስቃሴ ነው፡፡

 

ይህ ቡድን አውቆም ሆነ ሳያውቅ ጥለን ወደመጣነው እርሾ ወደ አይሁዳዊነት ያዘነበለ አስተምህሮ ይዞ መገኘቱ ብቻ ሳይሆን ቤተ ክርስቲያንን ለመከፋፈል አንዱን አንሥቶ ሌላውን ለመጣል የሚሞክር አፍራሽ አካሔድም የያዘ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ላይ ባለፉት ዘመናት ከተወረወሩት ፍላጻዎች ተከትሎ የመጣ በአቅሙ ፍላጻ ሆኖ ለማደግ የሚተጋ ነው፡፡

 

በዚህች ቤተ ክርስቲያን ባለፉት ዘመናት በብሕትውና ስም በአጥማቂነት ስም ብዙዎች የተለያዩ ፍላጎቶቻቸውን ለማስተጋባት ምእመናንን ግራ በማጋባት ተሰልፈው እንደነበር አይዘነጋም፡፡ ሁሉም እየታዩ መጥፋታቸው እንዳለ ሆኖ ያጠፉት፣ ተስፋ ያስቆረጡት ያሰናከሉት መንጋ እንዳለም አይረሳም፡፡ በአብዛኛው ግን አሁን አሁን እንደሚታዩት መሠረት የለሽ ከክርስትና ሃይማኖት እሳቤ ፍጹም የወጣ ጽንፍ ይዘው ግን ታይተዋል ማለት አይቻልም፡፡ አብዛኛውም ምእመናን እርካታ ሊሰጣቸው ያልቻለውን የቤተ ክርስቲያኒቱን አስተዳደር በመንቀፍ ስለሚመሠረቱ ተከታዮችን በቀላሉ ለማግኘት አስችሏቸው ነበር፡፡ በአብዛኛው የባሕታውያኑና የአጥማቂዎቹ ትኩረት አስተዳደሩን፣ አገልጋይ ማኅበራትን፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶችን፣ ግለሰቦችን መንቀፍ ላይ የሚያተኩርና ከዚያ አለፍ ሲል የራሳቸውን ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን ለመደንገግ ሲጥሩ መታየታቸው ነው፡፡

 

እነዚህ የአሁኖቹ የአይሁዳዊነት ዝንባሌ ያላቸው እንቅስቃሴዎች ግን የተናቁ ቢመስሉም የአካሔድ ሚዛኑ ፍጹም ፀረ ክርስትና ነው፡፡ ለኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ  ቤተክርስቲያን የሚሠሩ እንደሆነ ይናገሩ እንጂ የሚያሳስባቸው የስብከተ ወንጌል ሥርጭት አይደለም፡፡ የቤተ ክርስቲያን የአገልግሎት አቅም ስለማደግ አለማደጉ አይደለም፡፡ አስተዳደራዊ መሻሻል ስለማምጣት አይደለም፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ውስጥ ለውስጥ ለማዳከምና ለመከ ፋፈል ስለሚሠራው የተሐድሶ ቡድን አይደለም፡፡ ወይም በሀገሪቱ እየተስፋፋ ስላለው ዓለማዊነት አይደለም፡፡ በሀገሪቱ እየተስፋፋ እንደሆነ ስለሚነገርለት ግብረሰዶምና እጅግ የከፋ የኃጢአት ሥራ አይደለም፡፡ ስለ ሰላም ስለ ዕርቅ አይደለም፡፡ እነዚህ ወገኖች የሚያሳስቧቸው ነገሮች ሲመረመሩ የጸሐፍት ፈሪሳውያን እርሾ ከቤተ ክርስቲያን የመወገዱ ጉዳይ ያንገበገባቸውና የቤተ ክርስቲያን አገልግሎትን ሊያሳድጉ ሊያሰፉ ሊያጠናክሩ የሚችሉ ፍንጮች መታየታቸው ያበሳጫቸው መሆኑን መረዳት እንችላለን፡፡ እነዚህ ወገኖች ነግቶ በመሸ ቁጥር የሚናገሯችው የተደበላለቁ ያልሰከኑ ገና እየተደራጁ ያሉ ዝብርቅርቅ ሐሳቦች ያሏቸው ስለሆኑ በሚያነሡት ነጥብ ላይ መልስ በመስጠት ጊዜን ማጥፋት ለጊዜው አስፈላጊ ሆኖ አልተገኘም፡፡ ነገር ግን ይህን የሚወዛወዝ አስተምህሯቸውን ዝንባሌ መጠቆም አግባብ ይሆናል፡፡

የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ኦርቶዶክስ መባል የለባትም 
እነዚህ ወገኖች ክርስትና ማለት ሀበሾች ብቻ ተጠምቀው ይዘውት የሚገኙ ሃይማኖት አድርገው የማሰብ ያህል አጥብበው ያያሉ፡፡ የአሐቲ ቤተ ክርስቲያን እሳቤ የሌላቸውና ለሁሉም ወገን የተሰጠች መሆኗን በመዘንጋት “ተዋሕዶ ብቻ ነን” ይላሉ፡፡ ኦርቶዶክስ መባልን ሲኮንኑ ከኒቅያ ጉባኤ ጀምሮ ያሉ ሊቃው ንትን ከዚያም ለብዙ ምዕተ ዓመታት የነበሩ ሊቃውንትና ምእመናንን አኀት አብያተ ክርስቲያናትን ወዘተ እየኮነኑ መሆኑን እንኳ አላስተዋሉም፡፡ ሃይማኖታችን አንዲት/one/ ኩላዊት/catholic/ ሐዋርያዊት /apostolic/ ቅድስት /holy/ መሆኗን አያውቁም ወይም ብለን እንደምናስተምር ስናስተምርም እንደኖርን ረስተዋል፡፡

 

የጌታችን የመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን ወንጌል ተቀብ ለው የቅዱሳን ሐዋርያትን ትምህርትና ትውፊት የተቀበሉ፣ ያቆዩ፣ ያጸኑ፣ በኒቅያ፣ በቁስጥንጥንያ፣ በኤፌሶን የተደረጉ መንፈ ሳዊ ጉባኤያትን የተቀበሉ፣ ሐዋርያዊ ውርስ ያላቸው፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የምታስተምረውን ምስጢረ ሥላሴ፣ ምሥጢረ ሥጋዌ፣ ምሥጢረ ጥምቀት፣ ምስጢረ ቁርባንና ምስጢረ ትንሣኤ ሙታን ትምህርትን እነርሱም የሚያስተምሩ አኅት አብያተ ክርስቲያናትን ሁሉ ኦርቶዶክስ እንደሚባሉ ማወቅ መረዳት ያለመቻልና ክርስትናን ከብሔርተኛ ስሜት /nationalism/ አስተሳሰብ ጋር አቆራኝተው ማየታቸው ነው፡፡

 

እነዚህ ሰዎች ይህን ለማለት እንደመነሻ የሚያሳብቡት “የቅባት እምነት ተከታይ የሆኑ ካህናት በጎጃም አሉ፤ ዘጠኝ መለኮት የሚሉ በዋልድባ አሉ የሚልና ተሸፍነው የሚኖሩት በኦርቶዶክስ ስም ነውና ኦርቶዶክስ የሚለውን አንቀበልም” የሚል ነው፡፡ እነዚህን አለመቀበላቸው መልካም ነው፡፡ ሊቃውንተ ቤተክርስቲያን ሲታገሏቸው እንደኖሩ አሁንም ያንንኑ መንገድ ተከትለው ቢታገሉ መልካም ነው፡፡ ነገር ግን ጥያቄው ያ አይደለም፡፡ እነዚህ ሰዎች ቤተ ክርስቲያኒቱ የምትጠራበት ስም በራሱ ከእነዚህ የኑፋቄ ወገኖች የተለየች ሆና “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን” ተብላ እንደሆነ እያወቁ “ተዋሕዶ” መባል አለብን የሚል ጉንጭ አልፋ ክርክር ያነሣሉ፡፡ “ተዋሕዶ” የሆነውን እኛን መልሰው “ተዋሕዶ እንሁን” ሲሉን ነገር እንዳለው ሁሉም ወገን መገንዘብ ይገባዋል፡፡ “ተዋሕዶ ነን” ብለን በይፋ የምንጠራበት ስም ካለን፣ ቅባትና ዘጠኝ መለኮትን የሚያነሣ መጠሪያ ከሌለን፣ በእምነትም ተዋሕዶ እምነትን እንደ ምንከተል ከታወቀ የሚፈለገው ምንድነው፡፡ ከዚህ ከሚያነሡት ክርክር ጋር ኦርቶዶክስ መባልንስ የሚያስጥል ምን መነሻ አለ፡፡

 
ኦርቶዶክሳዊነት እጅግ በስፋት ተተንትኖ መታየት የሚችል ለእውነተኛዋ ቤተ ክርስቲያን የተገባ ስም መሆኑን ማሳየት ቢቻልም በዚህ ጽሑፍ ማሳወቅ የተፈለገው ግን የእነዚህ ወገኖች የአለማወቅ ደረጃ በዚህ ላይ ያለ መሆኑን ነው፡፡ ኦርቶዶክስ መባልን ደባ ነው፣ ሸክም ነው ወዘተ እያሉ መለፈፋቸው ብዙ እርምጃ የማያስኬድ መሆኑን አውቀው ሊታረሙበት የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ “ኦርቶዶክስ” የሚለውን ቃል መለካውያን ተጠቅመውበታል ይላሉ፡፡ እነርሱ በመጠቀማቸውም እኛ እንድንጥለው ይመክሩናል፡፡ እነርሱ ክርስቲያን ተብለው እንደሚጠሩ ቤተክርስቲያን ብለው እንደሚጠሩም መገንዘብ አልቻሉም፡፡ ስለዚህ ቆይተው ደግሞ እነርሱ ክርስቲያን ተብለው ተጠርተዋልና እኛ ክርስቲያን መባልን እንድንተው፣ ቤተ ክርስቲያን መባልን እንድናስቀር ሊመክሩን ይነሣሉ ማለት ነው፡፡ ለዚህ ነው ሐሳባቸው የአይሁዳዊነት እርሾ አለው የምንለው፡፡

 
ስም አጠራራችን “አይሁዳዊ” የሚል ነው
እነዚህ ወገኖች ኦርቶዶክሳዊ መባልን ኮንነው ሲያበቁ ሊያሻግሩን የሚጥሩት አይሁዳዊ ወደሚለው መጠሪያ ነው፡፡ ለማስተማር ብለው በበተኑት ወረቀት ላይ ”አይሁዳዊ የሚለውን የጌታን የእመቤታችንን የንጹሐን ኢትዮጵያውያንን የከበረ ስም አጠራር ለዐመፀኛ አሕዛብ አሳልፎ መስጠት ፈጽሞ አይገባም ነበር” ይላሉ፡፡ ኦርቶዶክሳዊ ከሚለው የክርስቲያኖች ስም ሲነጥሉን ያልራሩ ሰዎች በስያሜ ከአይሁድ ጋር ተቀራረቡ በማለት ጭካኔያቸው ሲያይል ያሳዩናል፡፡ ኦርቶዶክሳዊነት የክርስትና ስም ነው፡፡ አይሁዳዊ፣ ግሪክ፣ ኢትዮጵያዊ ወዘተ የሚለው ግን የወገን፣ የብሔር ስም መሆኑን እንኳን አላስተዋሉም፡፡ ለዚህ ነው ዝንባሌው ወደ ጸሐፍት ፈሪሳውያን እርሾ ነው የምንለው፡፡

ሰንበተ አይሁድ እንጂ ሰንበተ ክርስቲያን እሑድ የሚባል የለም
እነዚህ ወገኖች የተረፈ አይሁዳውያን ትምህርት አላቸው ስንል ለዝንባሌያቸው ሌላው መነሻ ስለ ሰንበተ ክርስቲያን መስማት አለመፈለጋቸውና ሰንበተ አይሁድ እንድትነግሥ ማነሣሣታቸው ነው፡፡ “ብዙዎች በየዋሕነት ጌታ ያዘዘው ሐዋርያት የደነገጉት ነው ብለው ዕለተ እሑድን ሰንበት ነች እያሉ እንደሚያስቡ ይታወቃል፤ ነገር ግን እሑድ መቼ እነማን ለምን ዓላማ ሰንበት ተብላ ልትሰየም ቻለች ብለን ስንመረምር የሰይጣንን ተንኮል እናስተውላለን…” እያሉ እሑድ ሰንበት መባሏን የሰይጣን ሥራ ያደርጉታል፡፡

   

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ሰንበተ አይሁድን ቀዳሚት ሰንበት ብላ እንደ ክርስትናው ሕግና ሥርዓት ተገቢውን ክብር እንደምትሰጥ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ ከቅዱሳን ሐዋርያት ጀምሮ እስከ አሁን የክርስቲያን ወገን ሁሉ ሲቀድሳት የነበረችን ሰንበተ ክርስቲያንን ግን ገናና፣ ክብርት፣ ልዕልት ሆና የጌታችን መድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የማዳን ሥራ ሲዘከርባት የኖረችና የምትኖር ናት፡፡ እነዚህ ወገኖች ግን የተረፈ አይሁድን ሐሳብ ዳግም ለማራገብ በመነሣት መከራከሪያ እንድትሆን ጥረት ማድረጋቸው ወደ ኋላ የሚስባቸውን አሮጌ እርሾ ያሳያል፡፡

የዳዊት ኮከብ መሠረቱ የሆነ ትእምርተ መስቀል መለያችን ይሁን
የዳዊት ኮከብ የአይሁድ ምኩራቦች መለያ ምልክት ነው፡፡ የዳዊት ኮከብ ሰሎሞናዊ እንደሆኑ በሚነገርላቸው በኢትዮጵያ ነገሥታት ዘንድ የቤተ መንግሥቱ ትእምርት ሆኖ እንደኖረ እስከ አሁን ድረስ በቤተ መንግሥትና በዩኒቨርሲቲዎቻችን አጥሮች በሚታዩት ምልክቶች እንረዳለን፡፡ ይሁን እንጂ ክርስትናውን አሽቀንጥሮ ለመጣል መሠረቱን ለመናድ ያዋሉት ሳይሆን የቤተ መንግሥቱ ምልክት ሆኖ የመንግሥቱን የትመጣ ለማጠየቅ የተገለገሉበት ትእምርት ነው፤ ከዚህ ባለፈ ግን እኛ ሁላችን ከዳንበት ከጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የመስቀሉ ትእምርት ጋር ቁርኝት የምንፈጥርበት አይደለም፡፡ ስለዚህ እነዚህ ወገኖች አሁንም ክርስትናችንን ከአይሁዳዊነት ጋር የመቀላቀል አሳብ ወይም ሌላ በሃይማኖት ስም ሊተክሉ የሚፈልጉት የፖለቲካ ርእዮት አለ ማለት ነው፡፡ እኛ ሃይማኖታችን ትእምርት የሚያደርገው የዳዊትን ኮከብ ሳይሆን ዳዊትን ጨምሮ ሰዎች ሁሉ የዳኑበትን የክርስቶስን መስቀል መሆኑን በመረዳት ሊታረሙ ይገባል፡፡

 

በሌላም በኩል “ቶ” እንደ ብቸኛ የመስቀል ምልክት አድርጎ ለመጠቀምና በዳዊት ኮከብ ምልክት ላይ ተቀጽሎ እንዲቀርብ ይሰብካሉ፡፡ በአልባሳቶቻቸው አትመው ወይም ቀርጸው ያሳያሉ፡፡ የ “ቶ” ቅርጽ በተለያዩ ዘመናት በተለያዩ የክርስቲያን ማኅበረሰቦች እንደሚታየው በሆነ ዘመንና ሁኔታ ወስጥ የመስቀል ምልክት ሆኖ አገልግሎ ሊሆን ይችላል፡፡ ከዚያ በመለስ ግን የሆነ የቤተ ክርስቲያናችን መለያ እንዲሆን አድርጎ የመቀሰቀስ ሥልጣን ግን ለዚህ ቡድን የሰጠው የለም፡፡ ካልሆነ ግን የሚኖረው ፋይዳ በእነ ዴርቶጋዳ፣ ራማቶሐራ፣ ዣንቶዣራ ከሚነገረን ልቦለዳዊ የርእዮተ ዓለም መግባቢያነት ያለፈ አይሆንም፡፡ በዚያም ልቦለዳዊ ታሪክ እንኳ ቢሆን ይህን የምስጢር መልእክት መቀባበያ አድርጎ ሲጠቀምበት የነበረው ገጸ ባህርይ በቤተ ክርስቲያን ስም የሚኖር አባ ፊንሐንስ የተባለ የይሁዲ እምነት ተከታይ ነበር፡፡ ታሪኩን ስናነብ የሌላዋን ገጸ ባሕርይ የልጁን የሲጳራን ክርስቲያናዊ ሕይወት ለማስጣል የአንገቷን መስቀል ለመበጠስ ሲታገል የነበረ አስመሳይ መነኩሴ ነው፡፡ በዚህ ታሪክ ወስጥ ታዲያ “ቶ” የዚህ አስመሳይ መጠቀሚያ ነበር፡፡ ታዲያ እነዚህ በእውኑ ዓለም ያሉ ወገኖች “ቶ”ን ካልተጠቀመን ሞተን እንገኛለን ሲሉ በክርስትና ስም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እየኖሩ የራሳቸውን ተልእኮ ለማሳካት የሚሮጡ ተረፈ አይሁዳውያን ናቸው አያስብል ይሆን!  

ዮዲት ጉዲት ስሟ ታሪኳ ተዛብቷል
“ደቂቀ ኤልያስ” ብለው ራሳቸውን የሚጠሩት እነዚህ ወገኖች አይሁዳዊ እንደሆነች ታሪክ የጻፈላትን ዮዲት ወይም ጉዲት ወይም እሳቶ የሠራችውን ሥራ እንደበጎ ተቆጥሮ ታሪክ እንዲገለበጥ ይሠራሉ፡፡ ዮዲት ጉዲት አብያተ ክርስቲያናትን ስታጠፋ ክርስቲያኖችን ስታርድ መኖሯን ታሪክ እየመሰከረ ነቢዩ ኤልያስ ነገረን በሚል ማስረጃ እውነታው ተገልብጦ ጠንቋዮችን ዐመፀኛ ካህናትን ወዘተ እንዳጠፋች እንዲታሰብ ሊያግባቡን ይጥራሉ፡፡ ሰልፋቸው የአይሁድን ገጽታ የመገንባት ከተቻለም ከይሁዲነት የሃይማኖት እሳቤዎች እየሸራረፉ ለማጉረስ በመሆኑ እንቅስቃሴው የተረፈ አይሁድ ነው፡፡
 
 
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን መዋቅር በአውሬው መንፈስ የሚመራ ነው
እነዚህ ወገኖች ያዘሉት ጭፍንነት የተሞላበት አካሔድ በአጠቃላይ ቤተ ክርስቲያኒቱን እንደሚጠሏት ያሳብቃል፡፡ በታሪክ ረገድ ከንግሥተ ሳባ እስከ ደቂቀ እስጢፋ፣ በአስተዳደር ዘማዊና መናፍቅ ከሚሏቸው ጳጳሳት እስከ ሰንበት ትምህርት ቤቶች፣ በሃይማኖት ከኦርቶዶክስ አይደለንም እስከ ሰንበተ ክርስቲያንን መሻር ድረስ የተመሰቃቀለ መሠረት የለሽ ቅዠትን ይዘው ተከታይ ለማፍራት መንቀሳቀሳቸው፣ ሊያውም በቤተ ክርስቲያኒቷ ውስጥ መሆኑ ለሃይማኖት ቤተሰቡ ያላቸውን ንቀትና የድፍረት አሠራራቸውን ያስረዳል፡፡ ስለዚህ ሲቀሰቅሱም ቤተ ክርስቲያኒቱ እንደፈረሰች አደርገው ነው፡፡ ለዚህም “የኢትዮጰያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የተባለው መዋቅር ማንንም ሊደግፍና ሊጠልል ቀርቶ እራሱን እንኳን ማቆም ያልቻለ በገዛ ራሱ የፈረሰ የእንቧይ ካብ መሆኑን እንረዳለን” ይሉናል፡፡ ተስፋ ማስቆረጥ ይፈልጋሉ፤ መንጋውን መበተን ይሻሉ፤ ለማን ሊሰጡት እንደሆነ አይታወቅም፤ ግን ምእመኑ እንዲሸሽ ይመክራሉ፡፡ የሆነውም ያልሆነውም በካህናትና መነኮሳት ተሠሩ የሚሏቸውን የሥነ ምግባር ችግሮች መቀስቀሻ ያደርጉታል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ያሉ አስተዳደራዊ ችግሮችን የሃይማኖታዊ አስተምህሮ ችግር ያህል አድርገው ይሰብካሉ፡፡ በእነርሱ እሳቤ የቤተ ክርስቲያኒቱ ዲያቆናት ቀሳውስት ጳጳሳትም ሁሉ የቅባት፣ የዘጠኝ መለኮት ወልድ ፍጡር የሚሉ አሪዮሳውያን ወዘተ ኑፋቄ ተከታዮች ናቸው፡፡ ስለዚህ ከእነርሱ መስቀል መሳለም፣ በእነርሱ እጅ መቁ ረብ የማይገባ ነው፡፡ ስለዚህ ቤተ ክህነቱ መንጋውን እንዲሰበስብ አይፈልጉም፡፡

 

ቤተ ክህነቱ መንጋውን መሰብሰብ እንዳይችል ሆነ ማለት የክህነትን ሥልጣን እንደሌሎች መናፍቃን ካድን ማለት ነው፡፡ እንደውም በኢትዮጵያዊው መልከጼዴቅ ሥርዓተ ክህነት የሆነ አዲስ ሊቀካህን ይኖርና ክህነት እንደ አዲስ ኤልያስ ለመረጣቸው ይሰጣል፤ ይላሉ፡፡ ልብ በሉ “ሊቀ ካህን” የሚለው እሳቤ ዳግም ወደ አይሁድ ዓለም የሚስብ ነው፡፡ ለአንዳንዶችም መስቀል ከሰማይ እንደተላከ ሆኖ ሲሰጣቸው የታየበት መድረክም አለ፡፡ ስለዚህ በእነሱ እሳቤ ሐዋርያዊ ውርስ የሚባል ነገር በክህነት አይታሰብም፡፡ ስለዚህ ክህነቱ ተክዷል፡፡ ይህንን ካላመንን ደግሞ የሚያጠምቀን የሚያቆርበን የሚናዝዘን የሚያመነኩሰን የሚያጋባን የሚፈውሰን በቅብዐ ሜሮን ለእግዚአብሔር የሚለየን ማን ይሆናል፡፡ እንዳትቆርቡ ብለው ሲቀሰቅሱ ከጌታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ እየለዩን ነው፡፡ ስለዚህ እርሱን እንዳንቀበል የሚሠ ሩትስ ለምንድነው፡፡ ካህን ከግብጽ ይመጣል እንዳይሉን ግብፆችም ለእነዚህ ወገኖች መሰሪና ተንኮለኞች ናቸው፡፡

 

“ካህናቱ የበኣል የጣዖት ካህናት ሆነዋልና አትቀበሏቸው” በሚለው በእነዚህ ሰዎች ልፈፋ የሚከሰሰው ሁሉም ከሆነ ቤተ ክርስቲያኒቱ ያለችው ከእነማን ጋር ነው፡፡ ማኅበራቱ፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶቹ ሁሉ በዚህ ቡድን እሳቤ የአውሬው ወገኖች ናቸውና፡፡ ታዲያ ያለክህነት እና ካህናት ያለ አገልጋይ መምህራን ሰባክያነ ወንጌል የምትኖር የተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እንዴት ያለች ናት፡፡ ስለዚህ ያላችሁት ያለሰብሳቢ ነው እያሉን ነው፡፡ ታዲያ የሚፈልጉት እንድንበተን ብቻ ከሆነ “ደቀ መዛሙርቱ ሰርቀውታል እንጂ አልተነሣም” እያሉ በክርስቶስ አምነው የነበሩትን ክርስቲያኖች ተስፋ አስቆርጠው ሊበትኑ ከተነሡት አይሁድ አሠራር በምን ይለያል፡፡ መንገዳቸው ቅስቀሳቸው ሁሉ የማፍረስና የጭካኔ ነውና፡፡

 

ከመጽሐፍ ቅዱስ ማኅበር ከዓለም አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት እንለይ
ለእነዚህ ወገኖች በክርስትና ስም ካሉ ከሁሉም ወገኖች ጋር መጎራበታችንን አይወዱም፡፡ ስለዚህ ከሃምሳ ዓመታት ያላነሰ የኢትዮጵያ ክርስቲያኖች መጽሐፍ ቅዱስን እንዲያነቡ ለማድረግ አስተርጉሞ አሳትሞ በማከፋፈል አገልግሎት እየሰጠ ያለውንና የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም በዋናነት ተሳትፎ ከምታደርግበት ማኅበር እንድንርቅ ይመክራል፡፡ ሰዎችን ያነሣሣል፡፡ እነርሱን ጨምሮ ብዙዎች በሀገራችን በአማርኛና በሌሎችም ቋንቋዎች ተተርጉመው የቀረቡ መጻሕፍት በቀላሉ ማግኘት እንዲቻል ድጋፍ እየሰጠ ያለውን ማኅበር የጥፋት መልእክተኛ ማድረግ ሚዛናዊነት የጎደለው ብቻ ሳይሆን የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ስልታዊ በሆነ መልኩ የማዳከም ፍላጎት ነው፡፡

በመሠረቱ እነዚህ ወገኖች የመጽሐፍ ቅዱስ ማኅበርን ብቻ ሳይሆን መጽሐፍ ቅዱስን የእምነት መሠረት ማድረግን የሚቀበሉ አይደሉም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ቃሉ በተንኮልና በአውሬው አሠራር ተለውጧል ብለው ያስባሉ፡፡ የዚህ ምክንያት ግን ግልጽ ነው እነርሱ ለሚነዟቸው ልፍለፋዎች ሁሉ ደጋፊ የሚያደርጉት መጽሐፋዊ መነሻ አለመኖሩ ነው፡፡ ስለዚህ ሲመቻቸው “በመጽሐፍ ቅዱስ የተነገረው የዓለም የፍጻሜ ዘመን ተቃርቧል” ይላሉ፤ ሳያስፈልጋቸው ደግሞ “መጽሐፍ ቅዱስና መጽሐፍ ቅዱስ ማኅበርን አትመኑ” እያሉ ይቀሰቅሳሉ፡፡ ለእነርሱ ታማኙ የእምነታቸው መጽሐፍ “የኤልያስ ዐዋጅ ነው” የሚሉት በቤተ ክርስቲያናችን ላይ የሚሠራውን ደባ እያቀነባበረ ያለው የእነርሱ “አባትዬ” ተራ ድርሰት ነው፡፡ እርሱ ለዘመናት ተሻግሮ ከመጣው ቃለ እግዚአብሔር በላይ ታማኝ ነው፡፡ ስለዚህ መጽሐፍ ቅዱስን ያስጥላል፡፡  

 

ከዚህም ተሻግሮ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ኅብረት አባል መሆን ገንዘብ መውደድ እንደሆነ አድርጎ አጥብቦ ለማሳሰብ ይሠራሉ፡፡ ከኅብረቱ ወጥቶ እነርሱን መሳብ እንጂ መተባበር ሃይማኖት ያጠፋል ብለው ያስባሉ፡፡ ሃይማኖትን ማስፋፋት ከማይፈቅዱ ወገኖች ጋር ቤተ ክርስቲያን የተባበረች አድርጎ በማሳሰብ የክርስትና ሽታ ካላቸው ኦርቶዶክስ የሚባሉ አኀት አብያተ ክርስቲያናትን ጨምሮ ቤተ ክርስቲያን አጠገባቸው እንድትደርስ አይሹም፡፡ ክርስትናን መሸሹ እንዳለ ሆኖ እንድንጠነቀቅ ከማሳሰብ የሚነሣ ሳይሆን አጠገባቸው እንዳንደርስ በፍርሃትና በጥርጣሬ ተሞልተን፣ ራሳችንን ብቻ አጽድቀን እንድንነሣ ስለሚገፉ አካሔዱ አይሁዳዊ እርሾ የተቆራኘው ነው፡፡ ሌላውን የኃጢአት ጎተራ አድርጎ ከመፍረድ ያልፍና አይሁድ ጌታን በሚከሱበት “የአብሮ በላ አብሮ ጠጣ” ክስ ቤተ ክርስቲያንንም ሊከሱ ይነሣሉ፡፡

 
ሰንበት ትምህርት ቤቶች አያስፈልጉም
እነዚህ ወገኖች የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት ለማዳከም የሚሠሩ ሤረኞች መሆናቸውን በቀላሉ የምንረዳው በዚህ ዘመን ያሉ የቤተ ክርስቲያንን የአገልግሎት ምሰሶዎች ለመነቅነቅ መቋመጣቸው ነው፡፡ ለዚህ ማሳያው ሰንበት ትምህርት ቤቶችን በማመስገን ፈንታ ሲወቅሷቸው፣ በማበረታታት ፈንታ ሲሰደቧቸው መታየታቸው ነው፡፡ እነዚህ ወገኖች በረጩት ጽሑፍ ላይ ያስነበቡንን ስናይ “ሰንበት ትምህርት ቤት አውሬው የቤተ ክርስቲያን ልጆችን ለማጥመድ የመሠረተው ረቂቅ ስውር ወጥመድ ነው” ይላሉ፡፡ ሴቶችን ከሊቃውንት በላይ አድርጎ ወረብ ያስወርባል፤ የአውሮፓ ባህል ነው፣ አስነዋሪ ሥራዎች ይሠሩበታል…ወዘተ እያሉ ተራና ጽንፈኛ ቅስቀሳ ያደርጋሉ፡፡ ይህ ክርስትናን ሃይማኖቴ ነው ብሎ ከሚከተል ወገን የሚሰነዘር አይደለም፡፡

ሰንበት ትምህርት ቤቶች ምእመናንን ከመናፍቃን ለመጠበቅ የሠሩትን፣ ሕፃናትና ወጣቶች ቤተ ክርስቲያንን እንዲያውቋት፣ የፈጸሙትን አገልግሎትና ቤተ ክርስቲያንም የአገልግሎት ውጤቱን አይታ አንድ መምሪያ ያቋቋመችለት መሆኑን እያወቁ፤ ካላቸው የተረፈ አይሁዳዊነት ስውር ተልእኮ አንጻር ሰንበት ትምህርት ቤቶች በሠሩት አገልግሎት ተቆጥተው የሚያስተጋቡት ስም ማጥፋት ነው፡፡ አካሔዳቸው ፀረ ስብከተ ወንጌል ነው፤ ስለዚህ ፀረ ክርስትና ነው፤ ስለዚህም የአይሁድ ቅናትን ያዘለ ነው፡፡

 
ማኅበረ ቅዱሳን አጥማጅ ስለሆነ ይጥፋ
የእነዚህ ወገኖች ሌላው ዒላማ ደግሞ ማኅበረ ቅዱሳን ነው፡፡ ለብዙ መናፍቃን ራስ ምታት የሚሆንባቸው የማኅበረ ቅዱሳን አገልግሎት ለዚህም ኃይል ራስ ምታት ሆኗል፡፡ በዚህ ቡድን ደግሞ ማኅበረ ቅዱሳን የሚነቀፈው እንዲህ እየተባለ ነው “የኢትዮጵያ ቅዱሳን ያዘኑበት፣ የዐመፀኞች ስብስብ፣ ምን ያህል ያጌጠ ሽፋን እንደተከናነበ በውስጥ ግን ምን እንደሚያካሒድ ግልጽ ነው፡፡ ይህ ካለ እኔ ለቤተ ክርስቲያን ማንም የለም እያለ ከመናፍቃንና ከዘማውያን ጳጳሳት ጋር ሽር ጉድ የሚል የኢትዮጵያ ቅዱሳንን ቃል የሚያስተሐቅር ትእቢተኛ ጎራ ጌታ የተለሰኑ መቃብራት ናቸው ሲል የተናገረበት ነው” ብለዋል፡፡ መናፍቃን የቅዱሳንን ገድል ብቻ የሚሰብክ እያሉ የሚተቹትን ማኅበረ ቅዱሳንን እነዚህ ወገኖች ደግሞ የቅዱሳንን ቃል ያስተሐቅራል በማለት በሌላ ጽንፍ ስም ለማጥፋት ይንቀሳቀሳሉ፡፡ የዚህ ሰልፍ መሠረት የተቃውሞው መነሻ ግን የአይሁድ ቅናት ነው፡፡ ማኅበሩ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ላሉ ክርስቲያን ተማሪዎች የሚሰጠው አገልግሎት፣ በሚዲያዎቹና በመምህራኑ የሚሰጠው አገልግሎት፣ ከቤተ ክርስቲያን አባቶች ጋር ተስማምቶ የመሔዱ ነገር፣ ለቤተ ክርስቲያን አንድነት የሚያደርገው ጥረት፣ መናፍቃንን ለማስታገስ የሚጥረው ጥረት፣ ገዳማትና አድባራት እንዳይዳከሙ የሚተጋው ትጋት ወዘተ ሰይጣንን ማስቀናቱ ያመጣው ስድብ ነው፡፡ ቢያንስ ወጣቶች የክርስትና የሞራል ሰብእና ወይም ሥነ ኅሊና እንዲኖራቸው ያደረገው ጥረት አልታሰባቸውም፡፡ ይህ በመሆኑ እነዚህ ወገኖች የሚደሰቱት በተቃራኒው ሲሆን ነው ማለት ነው፡፡ በዚህ ተቃራኒ ሲቆሙ የሚቆሙት የኢትዮጵያ ክርስትናን በመቃረን ነው፡፡ ሰለዚህ ክርስትናን በማጥላላት ወደ ቀደመ በሰው ወግ ወደ ተፈጠረ አሮጌ እርሾ ሊወስዱን መዳዳታቸውን ብንጠረጥር ያስኬዳል፡፡

 
ኤልያስ መጥቷል
ኤልያስ ከብሔረ ሕያዋን መምጣቱንም ሊያበስሩን ይሞክራሉ፡፡ አስገራሚው ነገር ከላይ የተነሡ ሁሉንም ጉዳዮች የገለጠው ያወጀው የፈረጀው የለወጠው የሻረው ያጸደቀው የኮነነው ነቢዩ ኤልያስ እንደሆነ በየምዕራፉ ይነግሩናል፡፡

 

ነቢዩ ኤልያስና ሄኖክ በመጽሐፍ ቅዱስ ቃል መሠረት በምድር ላይ እንደሰው ተመላልሰው በኋላ ግን ሞትን ሳይቀምሱ በማረግና በመሰወር በብሔረ ሕያዋን እስከ አሁን እንደሚኖሩ ይታመናል፡፡ ሰው ሆኖ ተፈጥሮ በለበሱት ሥጋ መሞት ለማንም አይቀርምና ወደዚህ ዓለም መጥተው በሰማዕትነት እንደሚያርፉ የቤተ ክርስቲያናችን ነገረ ሃይማኖት ያትታል፡፡ ከዚያም በመነሣት ስለኤልያስ መምጣት የተነገሩባቸው ሁለት የትንቢት ቃሎች በመጽሐፍ ቅዱሳችን አሉ፡፡ የመጀመሪያው ከመሲሑ ከክርስቶስ መምጣት አስቀድሞ እንደሚመጣ የተነገረው ምጽአት ነው፡፡ ይህም በነቢዩ ሚልክያስ “እነሆ ታላቁና የሚያስፈራው የእግዚአብሔር ቀን ሳይመጣ ነቢዩን ኤልያስን እልክላችኋለሁ፡፡ መጥቼም ምድርን በእርግማን እንዳልመታ እርሱ የአባቶችን ልብ ወደ ልጆች የልጆችንም ልብ ወደ አባቶች ይመልሳል፡፡” ተብሎ የተነገረው ነው /ሚል. 4፥5/፡፡

ሌላው የትንቢት ቃል ደግሞ በዮሐንስ ራእይ መጽሐፍ ላይ የተነገረው የሚከተለው የትንቢት ቃል የተተረጎመበት ክፍል ነው፡፡ “ለሁለቱም ምስክሮቼ ማቅ ለብሰው ሺሕ ከሁለት መቶ ስድሳ ቀን ትንቢት ሊናገሩ እሰጣለሁ፡፡ እነዚህ በምድር ጌታ ፊት የሚቆሙ ሁለቱ ወይራዎችና ሁለቱ መቅረዞች ናቸው፡፡ ማንምም ሊጎዳቸው ቢወድ እሳት ከአፋቸው ይወጣል፡፡ ጠላቶቻ ቸውንም ይበላል፡፡ ማንም ሊጎዳቸው ቢወድም እንዲሁ ሊገደል ይገባዋል፡፡ እነዚህ ትንቢት በሚናገሩበት ወራት ዝናብ እንዳ ይዘንብ ሰማይን ሊዘጉ ሥልጣን አላቸው፤ ውኃዎችንም ወደደም ሊለውጡ በሚፈልጉበትም ጊዜ ሁሉ በመቅሰፍት ሁሉ ምድርን ሊመቱ ሥልጣን አላቸው፡፡ ምስክራቸውን ከፈጸሙ በኋላ ከጥልቁ የሚወጣው አውሬ ይዋጋቸዋል፤ ያሸንፋቸውማል፡፡ ይገድላቸውማል፡፡ በድናቸውም በታላቂቱ ከተማ አደባባይ ይተኛል፡፡ እርሷም በመንፈሳዊ ምሳሌ ሰዶምና ግብፅ የተባለች ደግሞ ጌታቸው የተሰቀለባት ናት፡፡ ከወገኖችና ከነገዶችም ከቋንቋዎችም ከአሕዛብም የሆኑ ሰዎች ሦስት ቀን ተኩል በድናቸውን ይመለከታሉ፡፡ በድናቸውም ወደ መቃብር ሊገባ አይፈቅዱም እነዚህ ሁለት ነቢያት በምድር የሚኖሩትን ስለ ሣቀዩ በምድር የሚኖሩት በእነርሱ ላይ ደስ ይላቸዋል፡፡ በደስታም ይኖራሉ እርስ በእርሳቸውም ስጦታ ይሰጣጣሉ፤ ከሦስት ቀን ተኩልም በኋላ ከእግዚአብሔር የወጣ የሕይወት መንፈስ ገባባቸው፤ በእግሮቻቸውም ቆሙ፡፡ ታላቅም ፍርሐት በሚመለከቱት ላይ ወደቀባቸው፤ በሰማይም ወደዚህ ውጡ የሚላቸውን ታላቅ ድምፅ ሰሙ፡፡ ጠላቶቻቸውም እየተመለከቷቸው ወደ ሰማይ በደመና ወጡ፡፡…” /ራእ. 11፥3-03/ በዚህ ቃለ እግዚአብሔር ውስጥ “ሁለቱ ምስክሮቼ”፣ “ሁለቱ ወይራዎች”“ሁለቱ መቅረዞች”፣ “ሁለት ነቢያት” እያለ የሚጠራቸው በዚህ ዓለም ሞትን ያልቀመሱ ሁለቱ የእግዚአብሔር ወዳጆች ሄኖክና ኤልያስ እንደሆኑ ሊቃውንቱ በትርጓሜ ያስቀምጣሉ፡፡ እነዚህም ቅዱሳን የሚገለጹት ከጥልቁ የሚወጣውን አውሬ ሊዋጉ ነው እንጂ ቤተ ክርስቲያንን ሊዋጉ አይደለም፡፡

 

እነዚህ ከላይ የተጠቀሱ ትንቢቶች ትንቢት እንደመሆናቸው መጠን የተፈጸሙበትን ጊዜና ሁኔታ ሊረዱ የሚችሉት ቅዱሳን ናቸው፡፡ “በመጽሐፍ ያለውን ትንቢት ማንም ለገዛ ራሱ ሊተረጉም አልተፈቀደም” /2ጴጥ.1፥21/ እንደተባለ በሥጋና ደም ሰዎች የሚረዷቸው አይደሉም፡፡ ይህ አካሔድ አይሁድን ከሃይማኖት መንገድ ያስወጣቸው ነው፡፡

አይሁድ በኤልያስ መምጣት ጉዳይም ስተዋልና፡፡ ደቀ መዛሙርቱ ለጌታችን “እንግዲህ ጻፎች ኤልያስ አስቀድሞ ሊመጣ ይገባዋል ስለምን ይላሉ ብለው ጠየቁት” የነቢያት ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስም እንዲህ ሲል መለሰላቸው “ኤልያስማ አስቀድሞ ይመጣል ሁሉንም ያቀናል፤ ነገር ግን እላችኋለሁ ኤልያስ ከዚህ በፊት መጣ የወደዱትንም ሁሉ አደረጉበት እንጂ አላወቁትም” አላቸው፡፡ ስለ መጥምቁ ዮሐንስ እንደነገራቸው አስተዋሉ፡፡/ማቴ.17፥11/ አይሁድ ግን በሥጋና ደም ለትንቢቱ ትርጓሜ አበጅተው ይጠባበቁ ነበር፡፡ በግብሩ፣ በመንፈሱ፣ በአኗኗሩ ኤልያስን መስሎ ንስሐ ግቡ እያለ በምድረ በዳ የሚጮኸው ድምፅ ኤልያስ የተባለው ዮሐንስ መሆኑን አላስተዋሉምና እርሱንም መሲሁንም ሳይቀበሉ ቀሩ፡፡ ለዚህም ነው እንዲህ ያለው አስተሳሰብ የአይሁድ በመሆኑ የአሁኖቹ “ኤልያሳውያን” አካሔድ ተረፈ አይሁዳዊነት ነው የምንለው፡፡

 

በአንድ በኩል ይህንን የነቢዩ ሚልክያስን ቃል ይዘው እየሞገቱን ከሆነ ዮሐንስ መጥምቅን በኤልያስ መንፈስ መምጣቱን አለመቀበልና ብሎም መሲሁን ኢየሱስ ክርስቶስንም እንዳለመቀበል ነው፡፡ ይህ ከሆነ ደግሞ ነገ ከነገወዲያ ባለፉት ዓመታት በየአደባባዩ ስታውከን እንደነበረችው ሴት መሲሁ ተወልዷል ወይም ሊወለድ ነው ሊሉን ተዘጋጅተዋል ማለት ነው፡፡ ይህ በግልፅ የመጣ የይሁዲ እምነት አራማጅነት ነው፡፡

 

በሌላ በኩል ደግሞ በዮሐንስ ራእይ የተቀመጠውን የትንቢት ቃል መነሻ አድርገው እየሞገቱን ከሆነ ደግሞ አስተሳሰቡ አሁንም ትንቢትን ለገዛ ራስ መተርጎም እንዳይሆን ልንጠነቀቅበት የሚገባ ነው፡፡ ለገዛ ራስ መተርጎም የጸሐፍት ፈሪሳውያን እርሾ ነው፡፡ የእነዚህ ሰዎች አካሔድ ሃይማኖትን ተራ ጨዋታ ወደ ማድረግ የሚወስድ ነው፡፡ ሃይማኖትን በንቀት እንዲታይ የማራከስ አካሔድ ነው፡፡ ኤልያስ መጥቷልና አጅቡት ተቀበሉት እያሉ በየመንደሩ መቀስቀስ እገሌን ይጥላል እገሌን ያፈርሳል እያሉ በማውራት ለምእመናንን ምልክት ፈላጊነትን ማለማመድ ነው፡፡ ሰዎች ሃይማኖት ከምግባር ይዘው እንዲገኙ ከማስተማር ይልቅ ኤልያስን ፈልጉት እያሉ ማባዘን ተገቢ አይሆንም፡፡ ይህ “የአመንዝራ ትውልድ” ጠባይ ነው፡፡ ምልክትን የሚፈልግ ማኅበረሰብ እምነትን ይዞ ለመገኘት አይቻለውም፡፡

 

እነዚህ ወገኖች አሳባቸው ሥጋዊ ስለሆነ የትንቢቱን መፈጸም ሊነግሩን የሚቻላቸው አይደሉም ሊባል የሚችልበት ምክንያት አለ፡፡ ለእነዚህ ሰዎች ኤልያስ የሚመጣው የአትዮጵያን ቤተክህነት አፍርሶ ሊያድስ ነው፡፡ የኢትዮጵያን ቤተ መንግሥት  ሊያስተካክል ነው፡፡ ባንዲራውን ከአረንጓዴ ቢጫ ቀይም አልፎ በሰባቱ የቀስተ ደመና ረቂቅ ቀለማት /spectrum/ አስውቦ ሊተክል ነው፡፡ የኢትዮጵያን ታሪክ እየከለሰ ሊያስጠናን ነው፡፡ ስብከተ ወንጌል የሚያካሒዱ ሰንበት ትምህርት ቤቶችና ማኅበራትን ሊያፈርስ ነው፡፡ ሰንበትን ሊሽር ወይም ሊተካ ነው፡፡ ነግሦ የኢትዮጵያን ሕዳሴ ሊያመጣ ነው፡፡ ይህ ፍጹም ብሔርተኛና ፍጹም ሥጋዊ የሆኑ ሐሳቦች ናቸው፡፡ ካልሆነም የጥንቆላና የመናፍስት ሥራ ነው፡፡ ካልሆነም ለሥጋዊ ጥቅም የሚደረግ ሩጫ ነው፡፡ ካልሆነም ብዙዎች እንደሞከሩት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንን ለመፈታተን የመጣ ሌላ አዲስ የዘመቻ ጽንፍ ነው፡፡ በስሕተትም ቢሆን ግን ስሕተቱ ትንቢትን ለገዛ ራስ የመተርጎም ዝንባሌ ነውና ተረፈ አይሁዳዊነት ነው፡፡   

       
 
ማጠቃለያ
እነዚህ ወገኖች ያነሧቸው የማሳሰቻ ቅስቀሳዎች በራሳቸው የትም የማያደርሱ የተሰነካከሉ ሐሳቦች ቢሆኑም ፀጉሩን የገመደ፣ ቆዳ የለበሰ፣ ባዶ እግሩን የሚታይ “ባሕታዊ” አንድ መዓዝን ላይ ሲጮኽ አይተው ቆመው ለሚሰሙ የዋሐን ግን ጥርጥርና ማደናገሪያ ማሳቻ መሆኑ አይቀርም፡፡ ቡድኑ ከዚህ አልፎ በሕዝብ ዘንድ ይታወቃሉ የሚላቸውን አንዳንድ የዋሕ አርቲስቶች ቀስቃሽ ለማድረግ እንደ ስልት መያዙ ደግሞ የምር ታስቦበት ለመዝመት እየተሠራ መሆኑን ያሳያል፡፡

 

እነዚህ ወገኖች በየዓለሙ መዓዝን ዓለም ሊጠፋ ነው ብለው እንደሚቀሰቅሱት ምጽአት ናፋቂዎች ናቸው ብሎ ደፍሮ ለማውራትም የማይመች ነው፡፡ የሚያወሩልን ስለፍፃሜ ዓለምም አይደለም፤ ኢትዮጵያ በኤልያስ ገና ወደ ልዕልና እንደ ምትመጣ፣ በረከት መልካም ዘመን እንደሚቀርብ ሊነግሩን ነው፡፡ ስለዚህ ስለነገረ ምጽአት የሚነግሩን ከሆነ ምጽአት ናፋቂዎች ብለን ልንፈርጃቸው በቻልን፤ ነገር ግን ኤልያስን የሚፈልጉት አይሁድ የክርስቶስን መወለድ ለሚፈልጉበት ለሥጋቸው፣ በዓለሙ ላለ ልዕልናቸው ነው፡፡ የሀገርን ክብርና ልዕልና መመኘት መልካም ነው፤ ነገር ግን በሃይማኖት ስም ሰዎችን እያስጎመጁ እያማለሉ ከመንገዳቸው ማሳት ግን ነውር ነው፡፡

 

የቅዱሳንን ስም የሚያከብረው የኢትዮጵያ ክርስቲያን ወገን በቅዱስ ኤልያስ ስም የመጡ እነዚህን ስዱዳን ማንነት እንዲረዳ ያስፈልጋል፡፡ “ደቂቀ የሎስ” ሆነው የደካሞችን ነፍስ ሊነጥቁ መምጣታቸውን ማስገንዘብ አለብን፡፡ ከተቻለ ሁሉንም ማረምና ማስተካከል የቤተ ክርስቲያን ወገኖች ድርሻ ሊሆን ይገባል፡፡ ካልሆነ በዓላማ ለጥፋት እየሠሩ ካሉት ደበኞች የዋሐኑን መለየት ተገቢ ይሆናል፡፡ አስቀድመን በጽሑፉ መግቢያ ያነሣናት አሳች ሴት እንኳ ለረጅም ጊዜ በማሳቷ ጸንታ ምእመናንን ግራ ስታጋባ መቆየቷ ይታወቃል፡፡ ይህም እንቅስቃሴ ይህቺ ሴት ባደረገችው መንገድ የመናፍስትና የጥንቆላ አሠራር አብሮ እየታከለበት ከሔደ ደግሞ ነገሩ ውስብስብ ስለሚሆን ካሁኑ ሁሉም ወገን የድርሻውን ተወጥቶ በእንጭጩ መቅጨት ይገባል፡፡

 

ሐመር መጽሔት 20ኛ ዓመት ቁጥር 12 ሚያዚያ 2005 ዓ.ም.

“መኑ ውእቱ ገብር ኄር” “ታማኝ አገልጋይ ማነው”? ማቴ.24፥45

ሚያዚያ 4 ቀን 2005 ዓ.ም.

በመ/ር ምስጢረ ሥላሴ ማናየ

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ስያሜ የዐቢይ ጾም ስድስተኛው እሑድ ወይም ሳምንት ገብር ኄር ይባላል፡፡ ሰያሜውን የሰጠውም ኢትዮጵያዊ ሊቅ ቅዱስ ያሬድ ነው፡፡ ጾመ ድጓ በተባለው ከአምስቱ መጻሕፍቶቹ አንዱ በሆነው ጾመ ድጓ መጽሐፍ ሳምንቱን የዐቢይ ጾም ሳምንታት ስያሜዎች ከነሥርዓተ ማኅሌቱ አዘጋጅቷል፡፡ ስለዚህ በስድስተኛው የዐቢይ ጾም ሳምንት ከዋዜማው ቅዳሜ ጀምሮ በቤተ ክርስቲያን፡- የሚዘመረው ዝማሬ፣ የሚሰበከው ስብከት፣ የሚሰጠው ትምህርት ገብርኄርን የሚያወሳ ነው ማለት ስለ ታማኝ አገልጋይ ነው፡፡ በማቴ.25፥14-25 የተገለጸውና በዕለቱ የሚነበበው ወንጌልም የሚነግረን ይህን ነው፡፡

“አንድ ባዕለ ጸጋ ሰው ባሪያዎችን ጠርቶ ለአንዱ አምስት መክሊት ሰጠው፣ ሁለት መክሊት የሰጠውም አለ፣ አንድ መክሊትም የሰጠው አለ፡፡ ከዚህ በኋላ ወደሩቅ አገር ሄደ፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለውም ወጥቶ ወርዶ ሌላ አምስት አትርፎ አስር አደረገ፡፡ ሁለት የተቀበለውም አትርፎ አራት አደረገ፡፡ አንድ የተቀበለው ግን ሄዶ መሬቱን ቆፍሮ በሻሽ ጠቅልሎ የጌታውን መክሊት ቀበራት፡፡

ከብዙ ጊዜ በኋላ ጌታቸው መጥቶ ተቆጣጠራቸው፡፡ አምስት መክሊት የተቀበለው ቀርቦ ጌታዬ አምስት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር እነሆ አምስት አተረፍኩ አለው፡፡ “ገብርኄር ወምዕመን ዘበሁድ ምዕምነ ኮንከ ዲበ ብዙህ እሰይመከ ባዕ ውስተ ፍስሐሁ ለእግዚእከ” “አንተ ታማኝ ባሪያ በጥቂቱ ታምነሃል በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ” አለው፡፡ ሁለት የተቀበለውም ቀርቦ ጌታዬ ሁለት መክሊት ሰጥተኸኝ ነበር እነሆ ወጥቼ ወርጄ ሌላ ሁለት አትርፌ አራት አድርጌአለሁ፡፡ “አንተ ታማኝ በጎ አገልጋይ በጥቂቱ ታምነሃል በብዙ እሾምሃለሁ ወደ ጌታህ ደስታ ግባ” አለው፡፡

አንድ መክሊት የተቀበለው ግን ቀርቦ “ጌታዬ አንተ ክፉና ጨካኝ ካልዘራህበት የምታጭድ ካልበተንህበት የምትሰበስብ እንደሆንክ ስለአወቅሁ መሬቱን ቆፍሬ ቀበርኋት እነኋት መክሊትህ” አለው፡፡ “አንተ ሰነፍ ባሪያ መክሊቴን በጊዜ ልትሰጠኝ በተገባህ ነበር እኔም ወጥቶ ወርዶ ለሚያተርፍ በሰጠሁት ነበር”፡፡

ንዑ የዚህን ሀኬተኛ መክሊት ውሰዱና አስር መክሊት ላለው ስጡት፡፡ ላለው ይሰጡታል ይጨመርለታል ለሌለው ግን ያለውን ይቀሙታል፡፡ ንዑ ይህን ሰነፍና ሃኬተኛ ባሪያ እጅ እግሩን አሥራችሁ ጽኑዕ ጨለማ ወደአለበት ውሰዱት ጩኸትና ጥርስ ማፋጨት ወዳለበት ጨምሩት” አለ ማቴ.25፥14-25፡፡

ባዕለ ጸጋ የተባለው ጌታ ነው፡፡ መክሊት የተባለው ልዩ ልዩ የአገልግሎት ጸጋ ነው፡፡ ያተረፉት በሚገባ በታማኝነት ያገለገሉ ቅዱሳን ሰዎች ናቸው መክሊቱን የቀበረው ደግሞ በታማኝነት በተሰጠው ጸጋ ማገልገል ሲገባው ያላገለገለ ነው፡፡ ጌታቸው ሊቆጣጠራቸው መጣ ማለት በዕለተ ምጽአት ለሁሉም በአገለገለው አገልግሎት ዋጋ ለመስጠት እንደሚመጣ ያሳየናል፡፡

ያገለገሉትን ወደ ጌታህ ደስታ ግባ አላቸው ማለት ታማኝ አገልጋዮች መንግሥተ ሰማያትን ይወርሳሉና፡፡ ሰነፎች ደግሞ ጥርስ ማፋጨት ስቃይ ጽኑዕ ጨለማ ባለበት ሲዖል መግባታቸውን የሚያሳይ ነው፡፡

ከላይ ያነሳነው የቅዱስ ወንጌል ቃል፡- “ታማኝ አገልጋይ ማነው”? ይህ እያንዳንዱ በአርዓያ እግዚአብሔር የተፈጠረ የሰው ልጅ ጥያቄ ነው የዚህን አምላካዊ ጥያቄ መልስ መስጠት ከሰው ልጆች ይጠበቃል፡፡

1.    ታማኝ አገልጋይ ማነው? ሙሴ ነው፡፡
ሙሴ ታማኝ አገልጋይ ነበር ታማኝ አገልጋይ መሆኑን ቅዱሳት መጻሕፍት ይመሠክራሉ፡፡ “በመካከላችሁ ነቢይ ቢኖር እኔ እግዚአብሔር በራእይ እገለጥለታለሁ ወይም በህልም አናግረዋለሁ ባሪያዬ ሙሴ ግን እንዲህ አይደለም እርሱ በቤቴ ሁሉ የታመነ ነው” ዘኁ.12፥6፡፡ ይህ የፍጡር ምስክርነት ሳይሆን በፈጣሪው የተሰጠ ምስክርነት ነው፡፡ በዕውኑ በዘመናችን እንኳን ፈጣሪ ፍጡራን ታማኝነቱን የሚመሰክሩለት አጋልጋይ ይኖር ይሆን? እንጃ የሙሴን ታማኝ አገልጋይነት በረሃ፣ ስደት፣ መከራ፣ የፈርዖን ግርማ እና ቁጣ ያልበገረው አርባ ዓመት ስለ ወንድሞቹ በመሰደድ አርባ ዓመት ደግሞ የተሰደደላቸው ወንድሞቹን በመምራት ባሕር በመክፈል፣ ጠላት በመግደል፣ መና በማውረድ ደመና በመጋረድ ውኃ ከዓለት አፍልቆ በማጠጣት መከራውን ከወገኖቹ ጋር በመቀበል የቀኑ ሀሩር የሌሊቱን ቁር/ ብርድ/ ታግሶ በታማኝነት አገልግሏል፡፡ ታማኝነቱ እስከሞት ነበር፡፡

“ሙሴም ወደ እግዚብሔር ተመልሶ ወዮ እኒህ ሕዝብ ታላቅ ኀጢአት ሠርተዋል፡፡ ለራሳቸውም የወርቅ አማልክት አድርገዋል፡፡ አሁን ይህን ኀጢአታቸውን ይቅር በላቸው ያለዚያ ግን ከጻፍከው መጽሐፍ እባክህ ደምስሰኝ ከባለሟልነትህ አውጣኝ /ዘጸ.32፥31፡፡ አያችሁ ታማኝ አገልጋይ እኔ ልሙት ሌሎች ይዳኑ የሚል ነው አሁን የምናየው ግን ፈጽሞ ከዚህ የተለየ ነው፡፡ ሰዎች ይሙቱ እኔ ልኑር ሰዎች ጦም ይደሩ እኔ ልብላ ሰዎች ይራቆቱ እኔ ልልበስ ሰዎች ይዘኑ እኔ ልደሰት ነው፡፡ ይህ ታማኝ አገልጋይ ያለመሆን መገለጫ ነው፡፡ ታማኝ አገልጋይ ለሚያገለግላቸው ሰዎች ጥቅም ቅድሚያ የሚሰጥ እንጂ የራሱን ጥቅም የሚያስቀድም አይደለም፡፡ ዛሬ በዓለማችን የምንመለከተው ግን “ጩኸት ለአሞራ መብል ለጅግራ” የሚባለውን መሰል ነው፡፡ በታማኝ አገልጋዮች ድካም የሚሸለሙ ታማኝ አገልጋዮች በሠሩት ሪፖርት የሚያቀርቡ፣ የሚወደሱ ከጥቅሙ እንጂ ከድካሙ መክፈል የማይሹ እንቅፋት የሚመታው እግርን ነው፡፡ አክሊል የሚቀዳጀው ግን ራስ ነው፡፡ ታማኝ አገልጋይ ማለት እንደራስ አክሊል ዘውድ የሚጸፋ ብቻ ሳይሆን እንደ እግር እንቅፋቱን፣ እሾሁን፣ መከራውን ውጣ ውረዱን ድካሙን የሚቀበል ነው፡፡ በጥቅም ጊዜ ለራሱ በአካፋ የሚዝቅ ሌሎች በጭልፋ የሚቆነጥር አይደለም፡፡ ሙሴ ባሕር የከፈለው መና ያወረደው ደመና የጋረደው ውኃ ያፈለቀው ለራሱ አልነበረም ለሚመራቸው ሕዝብ ነበር እንጂ፡፡ ታማኝ አገልጋይ ያሰኘውም ይኸው ነው፡፡ በዚህ ከብሮበታል ተመስግኖበታልም፡፡

2.    ታማኝ አገልጋይ ማነው? ዳዊት ነው፡፡
ዳዊት ዘመነ መሳፍንት አልፎ ዘመነ ነገሥት ሲተካ እስራኤልን በንጉሥነት እንዲያገለግል እግዚአብሔር ከበግ ጥበቃ መርጦ በተሰጠው ሥልጣን ያልተመነ የሳዖልን በትረ መንግሥት በሳሙኤል እጅ ተቀብቶ ተቀብሏል፡፡

በተሰጠው ሥልጣን በታማኝነት ሕዝበ እስራኤልን መርቷል፡፡ ታማኝነቱንም እግዚአብሔር ለሙሴ እንደ መሰከረለት ለእርሱም መስክሮለታል፡፡
“እግዚአብሔር እንደልቡ የሆነ ሰው መርጧልና” የዘይቱን ቀንድ ሞልተህ በልጆቹ መካከል ለእኔ ንጉሥ አዘጋጅቻለሁና ወደ እሴይ ወደ ቤተልሔም እልክሃለሁ” 1ሳሙ.13፥13፣ 16፥2፡፡

“ወረከብክዎ ለዳዊት ገብርየ ወቀባዕክዎ ቅብዐ ቅዱስ” እንዲል መዝ.88፥20፡፡ “ባሪያዬ ዳዊትን አገኘሁት የተቀደሰ ዘይትንም ቀባሁት” ይህን አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ሰዓታት በተባለው ድርሰቱ፡- “ረከብክዎ ለዳዊት ገብርየ ብዕሴ ምዕመነ ዘከመልብየ” አገልጋዬ ዳዊትን እንደ ልቤ የታመነ ሰውን ሆኖ አገኘሁት ሲል ተርጉሞታል፡፡ የተገኘው በታማኝነት ነበር ከነገሠ በኋላም ታማኝ ነበር አሁን በዚህ ዓለም የምንኖር እኛ ግን በድኅነት ታማኝ እንሆንና ሀብት ሹመት ሥልጣን ሲመጣ ታማኝነትን እናጣለን፤ እንዲያውም ታማኝነትን እንንቀዋለን፡፡ መስረቅ ጀግንነት ይመስለናል፡፡ መዋሸት ሥልጣኔ ይሆንልናል፡፡ ዳዊት ሳይሾም በጎቹን በመጠበቅ ታማኝ ነበር፡፡ በጎቹን የሚነጥቅ ተኩላ አንበሳ ቢመጣ በኋላው ተከትሎ ነብሩን በጡጫ አንበሳውን በእርግጫ ብሎ በጎቹን ያስጥለው ነበር፡፡

“እኔ ባሪያህ የአባቴን በጎች ስጠብቅ አንበሳ ወይም ድብ ይመጣ ነበር ከመንጋውም ጠቦት ይወሰድ ነበር በኋላውም እከተለውና እመታው ነበር ከአፉም አስጥለው ነበር በተነሳብኝም ጊዜ ጉረሮውን አንቄ እመታውና እገድለው ነበር፡፡ ይህም ፍልስጥኤማዊ ከነዚያ እንደ አንዱ ይሆናል እንግዲህ እገድለው ዘንድ ከእስራኤል ተግዳሮትን አስወግድ ዘንድ ዛሬ አልሄድምን? የሕያው አምላክ ጭፍሮችን ይገዳደር ዘንድ ይህ ቆላፍ ምንድን ነው? ከአንበሳና ከድብ ያስጣለኝ እግዚአብሔር ከዚህ ያልተገረዘ ፍልስጥኤማዊ እጅ ያስጥለኛል” አለ 1ሳሙ.17፥34፡፡

ዛሬስ ቢሆን በእስራኤል ዘነፍስ በምዕመናን ላይ የሚገዳደሩ ብዙ ፍልስኤማውያን ተሰልፈዋል እነዚህን ድል የሚነሣ በጎቹን ምዕመናን ከተኩላ ከአንበሳና፣ ከድብ አፍ የሚታደግ ታማኝ አገልጋይ ማነው ከምእመናን ተግዳሮት የሚያርቅ ፈጣሪዬ ከመከራ ያድነኛል ብሎ የሚታመን የኢአማንያን ብዛት የማያስፈራው ማን ነው? ከትንሽነቱ እስከ ታላቅነቱ የታመነ አገልጋይ ማነው? ለተሾመበት ሓላፊነት ታማኝ ማነው? አሁንም ዓለማችን ከሥጋውያን ባለ ሥልጣናትም ሆነ ከመንፈሳዊያን መሪዎች የምትሻው ታማኝ ሰው ነው በሙስና ያልተዘፈቀ ጉቦ አይኑን ያላጨለመበት ለመንጋው አርአያና ምሳሌ የሚሆን ሰው ታማኝ አገልጋይ ማለት ያ ነው፡፡ በመኀላ የተቀበለውን የአገልግሎት ሓላፊነት የማይዘነጋ ጳጳስ፣ ቄስ፣ ዲያቆን፣ ሰባኪ፣ መምህር፣ ሐኪም፣ ዳኛ፣ ነጋዴ፣ ተማሪ፣ ወታደር፣ የቤት ሠራተኛ፣ የቢሮ ሠራተኛ ታማኝ መሆን አለበት፡፡

መንጋው በክህደት ሲጠፋ ዝም ብሎ የሚያይ ጳጳስ፣ ቄስ፣ ዲያቆን፣ መምህር፣ ሰባኪ፣ ታማኝ አይደለም ታማሚው እየተሰቃየ የሚዝናና ቆይ ሻይ ልጠጣና የሚል ሐኪም ታማኝ አይደለም፡፡ ፍርድ የሚያጎድል ድሆችን የሚበድል ለደሃ አደጎች የማይፈርድ ዳኛ ታማኝ አገልጋይ አይደለም፡፡

ቅቤ በሙዝ እና በድንች ቀላቅሎ በርበሬ በገል ጨምሮ ሌሎችን አጭበርብሮ የሚሸጥ ነጋዴ ታማኝ አገልጋይ አይደለም፡፡ እየነገደ ያለው በሰው ሕይወት መሆኑን መዘንጋት የለበትም፡፡ እንደእየ አቅሙ በተሰጠው የአገልግሎት ዘርፍ ታማኝ መሆን አለበት፡፡

3.    ታማኝ አገልጋይ ማን ነው? ዮሴፍ ነው፡፡
ዮሴፍ ለወንድሞቹ ምግባቸውን ተሸክሞ የእርሱ ስንቅ ቢያልቅ የወንድሞቹን ስንቅ ያልበላ በትንሽ የታመነ ሰው ነበር፡፡ ወንድሞቹ ሸጠውት በቤተ ጴጥፋራ በሚያገለግልበት ጊዜም ታማኝ ነበር፡፡ ታማኝነቱ በጲጥፋራ ቤት ጌታ አድርጎታል፡፡

“ዮሴፍ ተሸጠ አገልጋይም ሆነ እግሮቹ በእግር ብረት ስለሰሉ ሰውነቱም ከብረት አመለጠች ቃሉ ሳይደርስ የእግዚአብሔር ቃል ፈተነው ንጉሥ ላከ ፈታውም የሕዝብ አለቃ አድርጎ ሾመው የቤቱም ጌታ አደረገው በገንዘቡ ሁሉ ላይ ገዢ አደረገው፡፡ አለቆቹን እንደ እርሱ ይገስጽ ዘንድ ሽማግሌዎችን እንደ እርሱ ጥበበኞች ያደርጋቸው ዘንድ” መዝ.104፥17፡ በዚህ ሁኔታ የነበረው ዮሴፍ የጌታው ሚስት ሲወጣ ባቱን ሲገባ ደረቱን እያየች ዐይኗን ጣለችበት በዝሙት አይን ተመለከተችው፡፡

“የጌታውም ሚስት በዮሴፍ ላይ ዐይኗን ጣለችበት ከእኔም ጋር ተኛ አለችው እርሱም እምቢ አለ፡፡ ለጌታው ሚስቱ እንዲህ አላት እነሆ ጌታዬ በቤቱ ያለውን ሁሉ ለእኔ በእጄ አስረክቦኛል፡፡ በቤቱ ያለውን ምንም የሚያውቀው የለም በዚህ ቤት ከአኔ የሚበልጥ ሰው የለም፡፡ ሚስት ስለሆንሽ ከአንቺ በቀር ያልሰጠኝ ነገር የለም እንዴት ይህን ትልቅ ክፉ ነገር አደርጋለሁ? እንዴትስ በእግዚአብሔር ፊት ኀጢአትን እሠራለሁ ይህን ነገር በየዕለቱ ለዮሴፍ ትነግረው ነበር” ዘፍ.39፥7፡፡

በዮሴፍ ታማኝነት የጌታው ቤት ተባርኳል፡፡ ሀብቱ በዝቷል፡፡ በታማኝነቱ በቤቱ ያለውን ሁሉ ተረክቦ ነበር የቀረበለት ፈተና ግን ከባድ ነበር፤ ይህን በታማኝነቱ ማለፍ ችሏል፡፡ ዛሬ በእየአንዳንዱ ጓዳ እንደ እሳት የሚያቃጥሉ አገልጋዮች ናቸው ያሉት ልጅ በፈላ ውኃ የሚቀቅሉ ናቸው የሚበዙት እንኳን በሁሉ ገንዘብ ለመሾም አይደለም፡፡ በጥቃቅን ዕቃዎች እንኳን የሚታመን ጠፍቷል፡፡ ዮሴፍ ግን በታማኝ አገልጋይነቱ በመጣበት መከራ ቢታሰር እንኳ ያለ ሹመት አላደረም የእስረኞች አለቃ ነበር፡፡ ከእስር ቤት ሲወጣም ግብፅን በሙሉ መርቷታል፡፡ በግብፃውያን በሙሉ ተሾሟል በጥቂቱ ታምኗልና፡፡ “በጥቂቱ የታመነ በብዙ ይሾማል” እንዲል ማቴ.25፥24፡፡

ጌታውም መልካም አንተ የታመንህ በጎ አገልጋይ በጥቂት የታመንህ ስለሆንህ በብዙ እሾምሀለሁ” ከነዚህ ሦስት ታማኝ አገልጋዮች ሕይወት ሁሉም የሰው ልጅ ታማኝ አገልጋይነት የሚያሰጠውን ክብርና ጸጋ ተመልክቶ በታማኝነት ማገልገል ይገባዋል፡፡ ታማኝ መሆን መጀመሪያ የሚጠቅመው ለራስ ነው ከዚያ በኋላ ለሀገር ለወገን ለቤተ ክርስቲያን ላመኑት ላላመኑት ሁሉ ይጠቅማል፡፡ በመጨረሻም የጽድቅ አክሊልን ያቀዳጃል መንግሥተ ሰማያትን ያወርሳል፡፡ በሰውም በእግዚአብሔርም ፊት ያስከብራል፡፡

ጻድቃን ሠማዕታት ቅዱሳን በታማኝ አገልግሎታቸው ፈጣሪያቸውን ደስ አሰኝተው ከብረዋል፡፡ በሓላፊው ገንዘብ ያልታመኑት ይሁዳ፣ ሐናንያ፣ ሰጲራ፣ የደረሰባቸውን ጉዳት አይተናል፡፡ በአካን ወልደ ከርሚንም ተመሳሳይ ቅጣት ደርሶበታል ሐዋ.5፥1፣ 1፥25፡፡

ለዚህ ነበር ቅዱስ ዳዊት “አቤቱ አድነኝ ደግ ሰው አልቋልና ከሰው ልጆችም መተማመን ጎድሏልና” መዝ.11፥1፡፡ ስለዚህ ሁሉም በአለበት ያአገልግሎት መስክ ታማኝ አገልጋይ ሆኖ “አንተ በጎ ታማኝ አገልጋይ በጥቂቱ ታምነሃል በብዙ እሾምሀለሁ” የሚለውን የጌታውን የምስጋና ቃል መስማት ይገባዋል፡፡ መልካም አገልግሎት አገልግለን መንግሥቱን እንድንወርስ “ገብርኄር” እንድንባል አምላካችን ይርዳን፡፡

ሐዊረ ሕይወት በሆለታ ደብረ ኤዶም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን

ሚያዚያ 1 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

ሪፖርታዥ

መጋቢት 22 ቀን 2005 ዓ.ም. ሌሊት

ማኅበረ ቅዱሳን ወደ ሆለታ ደብረ ኤዶም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የተዘጋጀው የሐዊረ ሕይወት /የሕይወት ጉዞ/ መርሐ ግብር ላይ ለመሳተፍ ምእመናን ከሌሊቱ 12፤00 ጀምሮ አምስት ኪሎ በሚገኘው በመንበረ ፓትርያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም እና በማኅበረ ቅዱሳን ጽሕፈት ቤት ዙሪያ በመሰባሰብ ወደ ተዘጋጁት መኪናዎች ለመግባት ይጠባበቃሉ፡፡ እያንዳንዳቸው 61 ሰው የመጫን አቅም ያላቸው 85 አንደኛ ደረጃ አውቶቡሶች ከናዝሬት የልጃገረዶች ትምህርት ቤት እስከ ማኅበረ ቅዱሳን ጽሕፈት ቤት ፤ እንዲሁም ከትንሳኤ ዘጉባኤ ማተሚያ ቤት እሰከ መንበረ ፓትረያርክ ቅድስተ ቅዱሳን ማርያም ገዳም ሰልፋቸውን ይዘው፤ በሮቻቸውን ከፍተው ምእመናንን በመጫን ላይ ተጠምደዋል፡፡ ትራፊክ ፖሊሶች አካባቢው በመኪናና ሰው እንዳይጨናነቅ ያስተባብራሉ፡፡

ምእመናን በሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር አስተባባሪዎች አማካይነት የጉዞ ቲኬታቸውን እያሳዩ ለጉዞው የተዘጋጀውን ባጅ እየተቀበሉ ወደ ተዘጋጀላቸው አውቶቡሶች ይገባሉ፡፡ ለምእመናን የተዘጋጀው ባጅ ሁለት መልእክቶችን ያዘለ ሲሆን በጽህፈት ቤት ግንባታ አብይ ኮሚቴ የተዘጋጀው ሰረገላ አስክንድር /በማኅበሩ ሕንፃ ላይ አሳንሰር ለመግጠም እንዲቻል  ምእመናን ድጋፍ እንዲያደርጉ ባለ 15፤ 150 እና ባለ 600 ብር ቲኬት በሽያጭ ላይ ስለመሆኑ የሚልገጽ ባጅ/ ፤ እንዲሁም በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አስተባባሪነት የተዘጋጀ ከመጋቢት 25 እስከ ሚያዚያ 11 ቀን 2005 ዓ.ም. የሚቆይ ለአብነት ትምህርት ቤቶች የጽዳት እቃዎች ማሰባሰቢ ሳምንት በሚል ለኣብነት ትምህርት ተማሪዎች የሚሆኑ የተለያዩ ለጽዳትና ለምግብ ማብሰያና መጠጫ፤ ለአካባቢና ለግል ንጽህና መጠበቂያ የሚሆኑ ቁሳቁስ ምእመናን እንዲለግሱ የሚያሳስብ ባጅ ነው፡፡

ከለሊቱ 12፡30 ሰዓት ጀምሮ መኪናዎቹ ጉዟቸውን ጀምረዋል፡፡ ከአዲስ አበባ ውጪ የሚገኙ ማእከላት ተጓዦቻቸውን ይዘው ወደ ሆለታ በመሔድ ላይ ናቸው፡፡
መርሐ ግብሩን በኢንተርኔት በቀጥታ ሥርጭት ለማስተላለፍ በዝግጅት ላይ የሚገኙት የIT ባለሙያዎችና ጋዜጠኞች የተዘጋጀላቸው መኪና በምእመናን በመያዙ ምክንያት ለስርጭቱ የሚያገለግሉትን የኤሌክትሮኒክስ መሳሪያዎችን ሌሎች መገልገያ እቃዎች በፒክ አፕ መኪና ላይ ጭነው እነሱም ከእቃዎቹ ጋር /ፍጹም፤ ቴዲ፤ ኤይተነው፤ ብዙአየሁ፤ ሄኖክ/ ተጭነዋል፡፡ እኔና በሥርጭቱ ወቅት ጽሁፎችን በመጻፍ እገዛ የምታደርግልን ጸሐፊያችን የምስራች ገቢና ቦታ ተይዞልናል፡፡ የ30 ኪሎ ሜትሩን መንገድ የመኪናውን ፍጥነትና የንፈሱን ግርፋት ተቋቁመው ወደ ሆለታ በሰልፍ የሚተሙት አውቶቡሶችን በማለፍ፤ አልፎ አልፎም ወርደን በካሜራችን የአውቶቡሶቹን በረድፍ መትመም እየቀረጽን ሆለታ ደብረ ኤዶም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲቲያን ደረስን፡፡

በሰፊ ይዞታ ላይ ያረፈው የሆለታ ደብረ ኤዶም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን በማኅበረ ቅዱሳን የሙያ አገልግሎት ክፍል ባለሙያዎች ዲዛይኑ ተዘጋጅቶ በነፃ የተሰጠ ሲሆን ግንባታው በመፋጠን ላይ ነው፡፡ ከአዲሱ ሕንፃ በስተ ምስራቅ አቅጣጫ በ1968 ዓ.ም. የተተከለው አነስተኛ ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በመስጠት ላይ ይገኛል፡፡ የደብሩ አስተዳደር ጽ/ቤት፤ የሰበካ ጉባኤ ጽ/ቤት፤ የሰንበት ትምህርት ቤት አነስተኛ አዳራሽ፤ ለአጸደ ሕጻናት መማሪያነት የተሰሩ አራት ክፍሎች . . . በቤተ ክርሰቲያኑ ዙሪያ ይገኛሉ፡፡  
ቀድመውን የደረሱት አውቶቡሶች ምእመናንን አውርደው በተዘጋጀላቸው ስፍራ ላይ ተደርድረዋል፡፡ ምእመናን ከአውቶቡሶቹ እየወረዱ ቤተ ክርስቲያን እየተሳለሙ በአስተናጋጆች አማካይነት ወደ ተዘጋጀው የዳቦ መክፈልት እየተቀበሉ ወደ ተዘጋጀው ደንኳን በማምራት ቦታቸውን ይይዛሉ፡፡

ጠዋት
ከጠዋቱ 3፡00 ሰዓት ብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ለመርሐ ግብሩ ልዩ ትኩረት በመስጠት ቡራኬያቸውን ለመስጠት በሆለታ በደብረ ኤዶም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን ተገኝተዋል፡፡ የደብሩ የአቋቋም የአብነት መምህራንና ተማሪዎች የአቋቋም ትምህርት ሂደት ለማሳየት መምህራቸውን ከብበው፤ በዝማሬ ትምህርታቸውን ይወጣሉ፡፡ መምህሩ ቀለምና ዜማ እንዳይሰበር ይቆጣጠራሉ፡፡ ቀለም የሚስተውን ወይም ዜማ የሚሰብር ካጋጠማቸው አስተካክል በሚል በዓይናቸው ገረፍ ያደርጉታል፡፡

ከጠዋቱ 3፡30 ሰዓት ሲሆን በብፁዕ አቡነ ሉቃስ የሰቲት ዑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ መሪነትና ቡራኬ መርሐ ግብሩ በጸሎተ ወንጌል ተከፈተ፡፡

የጸሎት መርሐ ግብሩ እንደተጠናቀቀ ከቀደምት ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ከተመሠረቱት ማኅበራት መካከል የማኅበረ ሰላም የመዝሙር ክፍል አባላት ያሬዳዊ ዝማሬ አቅርበዋል፡፡ 

በሰዋሰው ብርሃን መንፈሳዊ ኮሌጅ የቅኔ መምህር የነበሩና በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት በተለያዩ ሓላፊነቶች በመመደብ እያገለገሉ የሚገኙ በመንፈሳዊ ትምህርት የበለጸጉና በዘመናችን ከሚገኙ ሊቃውንት መካከል አንዱ የሆኑት ንቡረ ዕድ ከፍለ ዮሐንስ በተጋባዥ እንግድነት የተገኙ ሲሆን “መንግስተ ሰማያት ሰው ወስዶ በእርሻው የዘራትን የሰናፍጭ ቅንጣት ትመስላለች” /ማቴ.13፡31/ በሚል ርዕስ ሰፋ ያለ የወንጌል ትምህርት ሰጥተዋል፡፡

 
“የእግዚአብሔር መንግሥት የተባለች ቃለ ወንጌል ምሥጢረ ሥጋዌን ሲያመለክት ነው፡፡ሰናፍጭ በመዘራቷ ነው የበቀለችው ትለመልማለችም፤ ብዙም ፍሬ ታፈራለች፡፡ ለእናትነት ከዚህ ዓለም በመረጣት በድንግል ማርያም ትመሰላች፡፡ ከሥጋዋ ሥጋ፣ ከነፍሷ ነፍስ ነስቶ በየጥቂት አድጎና ምስጢረ ጥምቀትን ፈጽሞ እኛን የጠበቀን ያሳደገን መድኀኒታችን ኢየሱሰ ክርስቶስን አስገኝታለችና፡፡ የተበተነውን ሕይወታችንን ሊሰበሰበው ስለፈቀደ ነው፤ ወደ እኛ የቀረበው፡፡ ይህንን ማኅበር የመሠረቱት ጥቂቶች ናቸው፡፡ በሰናፍጭ ቅንጣቱ እንደ ተማርነው በማኅበሩ ጥላ ሥር ብዙዎች በእግዚአብሔር መግቦት ተሰባስበዋል፡፡ እግዚአብሔር እያሠራው ነው፡፡ ይህ ማኅበር ቤተ ክስቲያናችንን፣ አባቶቻችንን እንዲሁም ምእመናንን እንዲያገለግል የእግዚአብሔር ፈቃድ እያሰራው ነው፡፡ ምእመናንም መጠቀም የኛ ፋንታ ነው፡፡ ማኅበሩን ብንጠቀምበት፣ ብንተባበረው መልካም ነው፡፡ ከልጆቻችን ፍቅርን፣ ትሕትናን፣ ራስን ዝቅ ማድረግን፣ በጥሻው ውስጥ የወደቁት አባቶችን መጠየቅ ፤ ማጽናናትን እንማራለን፡፡ በጥምቀት ያገኘነውን ልጅነት አክብረን መኖር አለብን፡፡ ክርስቲያናዊ ሥነ ምግባር የሁል ጊዜ ሥራችንን ሊሆን ይገባል፡፡ በጾም፣ በጸሎት የአጋንንት ክንድ መቁረጥ አለብን ቅዱስ ጳውሎስ ሰይፍን እንድናነሳ የሚነገረን ወንጌልን እንድንጫማ፣ ሥነ ምግባርን ታጥቀን መኖር እንዳለብን ሲያስተምረን ነው፡፡ ዛሬ አስለቃሾች ብንሆን ነገ አልቃሾች እንዳንሆን ልንጠነቀቅ ይገናል፡፡ ወዮባዮች እንዳንሆን በክርስቲየናዊ ሥነ ምግባር ሌሎችን መርዳት ይገባናል፡፡ መዳን ዝም ብሎ ፈረስ ጭኖ፣ መኪና ነድቶ የሚመጣ አይደለም በጎ ሥራ በመሥራት ግን ይገኛል፡፡ ያሰባሰበን እምነታችን ነው፡፡ ለነገ ቀጠሮ መያዝ አያስፈልግም፡፡ ለመዳን የሚፈልግ ሁሉ ይድናል፡፡ እኛም ድነናል፡፡ ልትድን ትወዳለህን የሚለውን አምላካዊ ቃል ሁል ጊዜ የምንጠየቀው ጥያቄ ነው፡፡ አዎ መዳን እንፈልጋለን ብለን የመጣን ነን፤ መዳን ስለምትፈልጉ ትጾማላችሁ፣ ንስሐ ትገባላችሁ፤ ሥጋወ ደሙ ወደሚሰጥበት ቤተክርስቲያን ትገሰግሳላችሁ፡፡ ይህ ሁሉ የሚሆነው መዳን ስለምትፈልጉ ነው፡፡” በማለት ሰፊ ትምህርት ሰጥተዋል፡፡

 

በመቀጠልም በዲ/ን ዘማሪ ቴዎድሮስ ዮሴፍ ዝማሬ የቀረበ ሲሆን በመልአከ ገነት አባ ወ/ጊዮርጊስ አበጀ የደብረ ኤዶም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ የደብሩን ታሪክ በአጭሩ አቅርበዋል፡፡

 

በሆለታ ደብረ ኤዶም ቅዱስ ገብርኤል ቤተ ክርስቲያን የተደረገው የሐዊረ ሕይወት መርሐ ግብር እስከ ምሳ ሰዓት የተካሔደውን ከላይ ያስቃኘናችሁ ሲመስል በመርሐ ግብሩ ላይ በአጠቃላይ 5700 ምዕመናን የአጥቢያው ምእመናንን ሳይጨምር መሳተፋቸውን ከአስተባባሪ ኮሚቴው የደረሰን መረጃ ያመለክታል፡፡ የምሳ መርሐ ግብሩም
በተሳካ ሁኔታ ተካሒዷል፡፡

ከሰዓት በኋላ
ከሰዓት በኋላ በተያዘው መርሐ ግብር መሠረት የማኅበረ ቅዱሳን የመዝሙር ክፍል አባላት ያሬዳዊ ዝማሬ በማቅረብ የተጀመረ ሲሆን ከጠዋት ጀምሮ በመርሐ ግብሩ ላይ በመገኘት ምእመናንን በመባረክ የቆዩት ብፁዕ አባታችን አቡነ ሉቃስ የሰቲት ሑመራ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ከስዓት በኋላ ለሌላ አገልግሎት ወደ አዲስ አበባ ስለሚመለሱ ቃለ ምእዳንና ቡራኬ ሰጥተዋል፡፡   

 
ብፅዕነታቸው በሰጡት ቃለ ምዕዳን “የእግዚአብሔር ልጆች  የእግዚአብሔር ሥራ ይሠራሉ፡፡ መመሰባሰባችን ከሁሉም በላይ ፈቃዱ የእግዚአብሔር ነው፡፡ የክርስትና ጉዞ ተምሮ መቅረት ተገንብቶ መፍረስ አይደለም፡፡ የክርስቶስ ልጆች የምንሆነው የክርስቶስን ሥራ ስንሠራ ነው፡፡ መሠረቱ ደግሞ ፍቅር ነው፡፡ የክርስትና ሃይማኖት እውነት እንጂ  ሐቁን አለባብሶ አቆንጅቶ ማስቀመጥ አይደለም፡፡ የክርስቶስ ሥራዎች በእኛ ሕይወት ውስጥ ሊታይ ይገባል፡፡ ይህ የእግዚአብሔር ጉባኤ ነው፡፡ እግዚአብሔር ባይመራው በፀሐይ እየተመቱ አፈር ላይ ተቀምጦ መማር አይቻልም” ብለዋል፡፡ ብፁዕነታቸውም ቡራኬ ሰጥተው ወደ አዲስ አበባ የተመለሱ ሲሆን ጉባኤው ግን ቀጥሏል፡፡
ከስዓት በኋላ ከተያዙት መርሐ ግብራት መካከል ዲ/ን ብርሃኑ አድማስ “በኢየሩሳሌም የሚኖሩ” መ.ኢያሱ.15፥63  በሚል ርዕስ የዕለቱን የወንጌል ትምህርት ሰፋ አድርገው ሰጥተዋል፡፡  

ዲያቆን ብርሃኑ አድማስ በሰጡት የወንጌል ትምህርት “የከነዓንን ምድር የወረሱት የኤፍሬም ልጆች ናቸው፡፡ በጌዝርም የተቀመጡትን ከነዓናዊያንንም አላሳደዷቸውም እሰከ ዛሬም ድረስ ከነዓናዊያን በኤፍሬም ልጆች መካከል ተቀምጠዋል፡፡ ከነዓን ርጉም ፍሬ ቢስ ማለት ነው የተቀደሰውን የሚረግጥ፣ በጎውን እያየ የማይጠቀም፤ እንቁውን የሚረግጥ…. ኤፍሬም ማለት ደግሞ ፍሬያማ ማለት ነው፡፡ ኢያቡሳውያንም ከአፍሬማውያን ጋር አብረው ኖረዋል፡፡  ዛሬም ኢያቡሳውያን  በቤተ ክርስቲያን ውስጥ በተለያዩ ምክንያቶች አብረውን ይኖራሉ፤ ማጥፋት ባንችልም በግብራቸው ግን ልንተባበር አይገባም፡፡ ኑፋቄውን ማሳደድ መናፍቁን ማዳን፤ የዝሙትን መንፈስ መገሰጽ ዘማዊውን ማንጻት፤ የንፍገት መንፈስን ማሳደድ ንፉጉን ቸር፤ ለጋስ ማድረግ ይገባል፡፡ ይህ ነው መልካም ጦርነት የምንለው፡፡ አንዳንድ ጊዜ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ መልካም ያልሆኑ ነገሮችን ስንመለከት፤ አንዳንድ መናፍቃንን ስንመለከት፤ በቤተክርስቲያን ውስጥ በምግባር እጅግ የራቁና ባልተገባ ሕይወት ውስጥ ቤተ ክርስቲያንን ለማሽከርከር የሚጥሩ ሰዎችን ስናይ እግዚአብሔር ለምን ዝም ይላል እንላለን፡፡

“በየቤቱ እንደ ጸሎት መጽሐፍ የራሱን ኑፋቄ ይዞ የሚዞር አለ፡፡ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ ሆኖ መጥፎ ሥራ የሚሰራውን ተመልክቶ ቤተ ክርስቲያን ትክክል አደለችም ማለት፣ በጎውን ደግሞ አይቶ ቤተ ክርስቲያን መጥፎ የለባትም ማለት አይቻልም፡፡ በኢየሩሳሌም ሁለቱም አይነት ሰዎች አሉና፡፡ ዛሬ በገዳማት ውስጥ ሆነው የሚያጭበረብሩ ሰውን  እንዲህ ታገኛላህ እያሉ የሚያታልሉእንዳሉ ሁሉ ሲያዩአቸው ምናምንቴ መስለው ስለ ሕዝብና ስለ ሀገር የሚጸልዩም አሉ” ብለዋል፡፡  

ከዲያቆን ብርሃኑ አድማስ የወንጌል ትምህርት በኋላ ዘማሪ ዲ/ን ዳዊት ፋንታዬ ያሬዳዊ ዝማሬ በመቅረብ የእለቱ መርሐ ግብር ቀጥሏል፡፡

ምእናን እንዲመለሱላቸው የሚፈልጓቸውን ጥያቄዎች በስልክ፤ በኢሜይል፤ እንዲሁም በአካል በመገኘት ለሐዊረ ሕይወት አስተባባሪ ኮሚቴው ያደረሱትን ምላሽ እንዲሰጥባቸው ማድረግ የመርሐ ግብሩ አንዱ አካል ስለነበር ዲያቆን ያረጋል አበጋዝ በእያንዳንዱ ጥያቄ  ላይ ሰፋ ያለ ትንታኔ በማቅረብ ምላሽ ተሰጥቶባቸዋል፡፡ ከተነሱት ጥያቄዎች መካከልም “በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አርአያ የማደርገው ሰው አጣሁ፡፡ ተስፋ በመቁረጥ ላይ ነኝ፡፡ ምን ትመክሩኛላችሁ?” ለሚለው ዲያቆን ያረጋል ሲመልሱም “ሃይማኖት ከእግዚአብሔር ጋር የሚኖረን ግንኙነት ነው፡፡ ከሰዎች ጋር በተለያየ ምክንያቶች ልንገናኝ እንችላለን፡፡ ከእግዚአብሔር ፍቅር ተነሳ ነው ሰውን የምንወደው እንጂ ስለ ሰዎች ፍቅር ብለን አይደለም እግዚአብሔርን የምንወደው፡፡ መነሻው እግዚአብሔር ነው፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያን ስንመጣ ፤  ክርስትናን ስናውቅ መጀመሪያ ሰዎችን አይደለም ማወቅ ያለብን፡፡ ሰዎች ወደ እግዚአብሔር ሊመሩን ይችላሉ፡፡ እነዚህ መንገዶች ናቸው፡፡ መድረሻው ግን አሁንም እግዚአብሔር ነው፡፡ ስለዚህ መጀመሪያ መተዋወቅ ያለብን ከእግዚአብሔር ጋር ነው፡፡ እኛ ግን ወደ ቤተ ክርስቲያን እንመጣና ከእግዚአብሔር ጋር ሳይሆን ከሰዎች ጋር እንተዋወቃለን፡፡ እግዚአብሔርን ትተን ከሰዎች ጋር እንጣበቃለን፡፡ እነዚያ ሰዎች ሲጠፉ እኛም አብረን እንጠፋለን፡፡ ቤተ ክርስቲያንን በአንዳንድ ወዲህ ወዲያ በሚሉ ሰዎች መለካት የለብንም፡፡ ማሰብ ያለብን የጸኑትን ነው፡፡ ስለዚህ አርአያ የምናደርጋቸው ሰዎች ከእግዚአብሔር እንደማይበልጡ መረዳት አለብን፡፡ ከሰዎች ይልቅ እግዚአብሔርን ማየት ስንጀምር ተስፋ መቁረጥ ከኛ ይርቃል፡፡ አርአያ የምናደርጋቸው ሰዎች ከቤተ ክርስቲያን ቢወጡ እንኳን እኛ ተስፋ ያደረግነው እግዚአብሔር እንዳለን ስለምንረዳ እንጸናለን፡፡” በማለት ምላሻቸውን ሰጥተዋል፡፡

ነብዩ ኤልያስ ከብሔረ ሕያዋን ወደ ምድር ወርዷል፡፡ እኛንም ልኮናል የሚሉ ወገኖች ተነሥተዋልና አስተምህሯቸው ምንድነው? ብታብራሩልን በማለት ለተጠየቀው ጥያቄም ዲያቆን ያረጋል በሰጡት ምላሽ “ሰንበት ቀዳሚት ናት፤ እሁድን ማክበር ስህተት ነው፡፡ ኤልያስ ሰንበትን ወደ ቅዳሜ ይመልሳል፤ እስካሁን እውነተኛው የመልከ ጼዲቅ መሥዋእት ስላልተሰዋ አሁን ኤልያስ እውነተኛውን የመልከ ጼዲቅ መስዋእት ይዞ መጥቷል፤ የጌታችን የመድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በዓለ ልደት ታህሣሥ 29 ሳይሆን መስከረም 1 ቀን ነው መከበር ያለበት፤ የዳዊት ኮከብ ተብሎ የሚጠራው ባለ ስድስት ጫፉ ኮከብን ይዛችሁ ጸንታችሁ ቁሙ፤ በቅርቡ በባሕር ዳር ውስጥ ሰውር ጉባኤ ተካሒዷል፡፡ ከኒቂያ፤ ከኤፌሶንና ከቁስትንትኒያ ጉባኤያት በላይ ተካሒዷል፡፡ በዚህ ጉባኤም ከገነትና ከብሔረ ሕያዋን ቅዱሳን መጥተው ተገኝተዋል፤ ካህናትን የገሰጸችና ከነመጻሕፍቶቻቸው ቤተ መቅደሳቸውን ያጠፋች ዮዲት ቅድስት ናት ይላሉ” በማለት ስለ ኤልያስ ወረዷል እያሉ በማስተማር ላይ ስለሚገኙት ሰዎች አስተምህሯቸውን ገልጸዋል፡፡

በመጨረሻም ቀሲስ ዶክተር ሰሙ ምትኩ የማኅበረ ቅዱሳን ሰብሳቢ የማኅበረ ቅዱሳን አመሠራረት፤ እያከናወናቸው ስለሚገኙ የአገልግሎት ዘርፎች በአጭሩ በመዳሰስ ለምእመናን ግንዛቤ ያስጨበጡ ሲሆን መርሐ ግብሩንም በማጠናቀቅ በጸሎት ተዘግቶ ምእመናን ወደ መኪናዎቻቸው አምርተው በሰላም ጉዞው እንደተጀመረ በሰላም ተጠናቋል፡፡ 

ለአብነት ትምህርት ቤቶች የጽዳት እቃዎች ድጋፍ ማሰባሰቢያ ሳምንት በመካሄድ ላይ ነው

መጋቢት 26 ቀን 2005 ዓ.ም.

በእንዳለ ደምስስ

በማኅበረ ቅዱሳን የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል አስተባበሪነት ለአብነት ትምህርት ቤቶች የጽዳት እቃዎች ድጋፍ ማሰባሰቢያ ሳምንት ከመጋቢት 21 እስከ ሚያዚያ 11 ቀን 2005 ዓ.ም. በማኅበሩ ሕንፃ ላይ በመካሔድ ላይ ይገኛል፡፡

ተማሪው ምንም ዓይነት የምግብ፤ የመጠለያና የአልባሳት ድጋፍ ሳያገኝ ጥሬ ቆርጥሞ ፤ በሳር ጎጆ ተጠግቶ፤ በእራፊ ጨርቅ ተጠቅልሎ ትምህርቱን ይከታተላል፡፡ በቂ ምግብ ፤ ንፁህ የመጠጥ ውኃ ፤ መጸዳጃ ቤት ባለማግኘቱ ለተለያዩ ተላላፊ በሽታዎችም ይጋለጣል፡፡  በአብነት ትምህርት ቤቶች ውስጥ ጎልቶ የሚታየውን ችግር በተለይም ሰማንያ በመቶ የሚሆነው የበሽታ ዓይነት ከግልና ከአካባቢ ንጽሕና ጉድለት የሚመጣ በመሆኑ ማኅበረ ቅዱሳን ይህንን የጤና ችግር ለመቅረፍ 12000 /አሥራ ሁለት ሺህ/ ተማሪዎችን ተጠቃሚ የሚያደርግ መርሐ ግብር ነድፏል፡፡     

በተነደፈው ፕሮጀክት መሠረት ለ10 የአብነት ትምህርት ቤቶች የጋራ መጸዳጃ ቤት ግንባታ ፤ ባለ 200 ግራም 12000 የልብስ ሳሙና፤ 10 ባለ 3000 ሊትር የውኃ ማጠራቀሚያ ታንከር፤ የውኃ ማከሚያ ኬሚካሎች፤ ለውኃ መጠጫ፤ ለማብሰያ ፤ ለመመገቢያ ፤ ለገላና ለልብስ ማጠቢያ የሚያገለግሉ የተለያዩ መጠን ያላቸው ቁሳቁስ፤ መርፌና ምላጭ፤ . . . እንደሚያስፈልግ ከማኅበሩ የቅዱሳት መካናት ልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት ዋና ክፍል ያገኘነው መረጃ ያመለክታል፡፡  

የተማሪዎቹን ሕይወት ለማትረፍና ትምህርታቸውን በሚገባ ተምረው ቤተ ክርስቲያንን የሚያገለግሉበት ሁኔታ ለመፍጠር በጎ አድራጊ ምእመናን በማኅበሩ ሕንፃ ላይ እሰከ ሚያዚያ 11 ቀን 2005 ዓ.ም. በሚደረገው የቁሳቁስ ድጋፍ የበኩላቸውን ልገሳ እንዲያደርጉ ተጋብዘዋል፡፡