aa 001

ሊቀ ጉባኤ ኀይለ ማርያም ዐረፉ

ጥቅምት 20 ቀን 2005 ዓ.ም.

በቀሲስ ለማ በሱፍቃድ


aa 001ሊቀ ጉባዔ ኀይለ ማርያም ንጋቱ ከአባታቸው ከአቶ ንጋቱ ወልደ ሐዋርያትና ከእናታቸው ከወ/ሮ ደመዎዝ ወንድም አየሁ ጥር 12 ቀን 1969 ዓ.ም በሰሜን ሸዋ በሞረትና ጅሩ ወረዳ ልዩ ስሟ ሽነት ቁስቋም በምትባል መንደር ተወለዱ፡፡ ገና በሕፃን ዕድሜያቸው ወደ ታላቁ ገዳም ወደ ደብረ ጽጌ ማርያም በመሄድ ለአጎታቸው ለአባ ፀጋ ወልደ ሐዋርያ በአደራነት ተስጥተው የቅድስት ቤተ ክርስቲያናቸውን ትምህርት ሀ ብለው ንባብ ከአባ ሀብተ ማርያም በሚገባ ካጠናቀቁ በኋላ እዛው ገዳሙ ውስጥ ከሚገኙት ከመምህር አፈወርቅ የቃል ትምህርትና ጾም ምዕራፍ በሚገባ ተማሩ እንዲሁም ከታላቁ ሊቅ ከየኔታ ጽጌ ጾመ ድጓና ድጓ ተምርው በመምህርነት ተመርቀዋል፡፡ ቀጥሎም አቋቋምና ዝማሬ መዋሲእት ከየኔታ መስፍን አበበ በሚገባ ተምርው ተመርቀዋል፡፡ ይህን ሁሉ ትምህርት ተምሬያለሁ በቃኝ ሳይሉ ተጨማሪ ቃለ እግዚአብሔር ፍለጋ በ1984 ዓ.ም ወደ አዲስ አበባ በመምጣት በታዕካ ነገሥት በዓታ ለማርያም ገዳም የካህናት ማሠልጠኛ በመግባት የእውቀት አድማሳቸውን በማስፋት የተክሌ አቋቋምን በመማር በመምህርነት ተመርቀዋል፡፡

 

ሊቀ ጉባዔ ኀይለ ማርይም ንጋቱ በ1986ዓ.ም በገዳሙ ውስጥ በዲቁና እንዲያገለግሉ ተቀጥረዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ በነበራቸው መንፈሳዊ ትጋት የተነሣ በመሪ ጌትነት፣ በሊቀ አርድእትነት፣ በሊቀ ጉባኤነት፣ የትምህርት ቤቱ ተቆጣጣሪና ዋና ጸሐፊ በመሆን ከሃያ ዓመታት ላላነሱ ጊዜያት በልዩ ልዩ የሓላፊነት ቦታዎች በቅንንትና በታማኝነት አገልግለዋል፡፡ ሊቀ ጉባኤ ኀይለ ማርያም  በአስኳላው ትምህርታቸው እስከ አሥራ ሁለተኛ ክፍል ድረስ ተከታትለዋል፡፡

 

ሊቀ ጉባኤ ኀይለ ማርያም ባደረባቸው ሕመም ምክንያት በሕክምናና በጠበል ሲረዱ ቆይተው በተወለዱ በ36 ዓመታቸው ጥቅምት 6 ቀን 2005 ዓ.ም ከዚህች ዓለም በሞተ ሥጋ ተለይተዋል፡፡ ሥርዓተ ቀብራቸውም ጥቅምት 7 ቀን 2005 ዓ.ም በደብረ ሊባኖስ ገዳም ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንና ወዳጅ ዘመዶቻቸው በተገኙበት ተፈጽሟል፡፡ ሊቀ ጉባኤ ኀይለ ማርያም ባለ ትዳርና የአንድ ወንድ ልጅ አባት ነበሩ፡፡