የጥቅምቱ ቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ ተጠናቀቀ

ጥቅምት 21 ቀን 2005 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

 

በፍትሕ መንፈሳዊ አንቀጽ 5 ቁጥር 164 በተደነገገው መሠረት ጥቅምት 11 ቀን 2005 ዓ.ም. ጀምሮ ለአሥር ቀናት ያህል በ17 አጀንዳዎች ላይ ሲነጋገር የሰነበተው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ አስፈላጊ ናቸው ያላቸውን ውሳኔዎችን በማስተላለፍ ዛሬ ከቀትር በፊት ተጠናቀቀ፡፡

 

ባለፈው ዓመት የተከናወነውን ሥራ ለመገምገምና የወደፊቱንም እቅድ ለመንደፍ እንዲችል ከየአህጉረ ስብከቱ ጽ/ቤቶች የቀረቡለትን ሪፓርቶች አዳምጦ አስፈላጊውን መመሪያ የሰጠው ቅዱስ ሲኖዶስ በሰሜን አሜሪካ ከሚገኙት አባቶች ጋር የተጀመረው የእርቀ ሰላም ድርድር ተጠናክሮ ይቀጥል ዘንድ ውሳኔ አሳልፏል፡፡

 

ስድስተኛውን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ምርጫ አስመልክቶ እስከ ኅዳር 30 ቀን 2005 ዓ.ም. ድረስ የፓትርያርክ ምርጫ ሕግ እንዲዘጋጅ ኮሚቴ የተቋቋመ ሲሆን፤ ኅዳር 30 ቀን 2005 ዓ.ም በሚደረገው የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ስብሰባ ሕጉ ተመርምሮ እንዲጸድቅና የምርጫ ሂደቱ እንዲቀጥል ከስምምነት ተደርሷል፡፡

 

የአዲስ አበባን ሀገረ ስብከትን አስመልክቶ ለመንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት አፈጻጸም ያመች ዘንድ በምሥራቅ፣ በምዕራብ፣ በሰሜንና በደቡብ በአራት አህጉረ ስብከት እንዲዋቀር፤ ለእያንዳንዱ ሀገረ ስብከት ከብፁዓን ሊቃነ ጳጳሳት ጀምሮ ሥራ አስኪያጆችና ሠራተኞች እንዲመደቡ ተወስኗል፡፡

 

በብፁዕ አቡነ ናትናኤል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ዐቃቤ መንበረ ፓትርያርክ የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አማካኝነት የተነበበው የቅዱስ ሲኖዶስ መግለጫ፤ የውጭ ግንኙነትን በተመለከተ በአፍሪካ፣ በአውሮፓ፣ በአሜሪካና በሌሎችም አህጉር አገናኝ ዴስክ እንዲቋቋም የቤተ ክርስቲያኒቱ እንቅስቃሴ የሚዳስስ በእንግዚዝኛና በአማርኛ ቋንቋ የሚዘጋጅ ወርኅዊ መጽሔት እንዲኖር፤ መምሪያውንም የበለጠ ለማጠናከር ይቻል ዘንድ በሰው ኀይልና በበጀት እንዲደገፍ ውሳኔ ተላልፏል፤ በሌላ በኩል የአብነት ትምህርት ቤቶችን ገዳማትንና የካህናት ማሠልጠኛዎችን በበጀት አጠናክሮ በበለጠ እንዲሠሩ ለማድረግ የ10 ሚሊየን ብር በጀት እንዳጸደቀ አመልክቷል፡፡

 

ከዚህ በተጨማሪ አንዳንድ “የስም መነኮሳት ነን” ባዮች የቤተ ክርስቲያኒቱን የምንኩስና ልብስ እየለበሱ ሕዝቡን በማትለልና ሃይማኖታችንን በማስነቀፍ ተግባር ተሰማርተው እንደሚገኙ ይታወቃል፤ ስለሆነም ሕዝበ ክርስቲያኑ ከእነዚህ ምግባረ ብልሹ ወገኖች ራሱን ነቅቶ እንዲከላከልና መንግሥትም የሕግ ከለላ እንዲሰጥ ቅዱስ ሲኖዶስ በአጽንኦተ ይጠይቃል፡፡” ብሏል፡፡

 

ከመግለጫው በኋላ ከጋዜጠኞች ለተነሡ ጥያቄዎች ምላሽ የሰጡት የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ጸሓፊና የከፋ ሸካ ቤንች ማጂ ዞን አህጉረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ አቡነ ሕዝቅኤል የጳጳሳትን ንብረት አስመልክቶ፡- “በመሠረቱ ጳጳስ የእኔ፣ የግሌ የሚለው ሀብት ንብረት የለውም፡፡ ሊኖረውም አይገባም፡፡ ንብረቶቹ ሁሉ ምእመናን ናቸው፡፡ ምእመናን ሲባል ቤተ ክርስቲያኒቱን ማለት ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ጎመን የሚዘራበት፣ ሽንኩርት የሚተክልበት የእርሻ ቦታ እንኳ የለውም” በማለት ተናግረዋል፡፡

 

የቅዱስ ሲኖዶስን መግለጫ ዝርዝር ዘገባ በቅርቡ እናቀርባለን፡፡