ክፉ ለሚያደርጉባችሁ ሰዎች መልካምን አድርጉ::

በአዜብ ገብሩ

በአንድ ወቅት ሳኦል የሚባል የእስራኤላውያን ንጉሥ ነበር፡፡ ይህ ንጉስ በዳዊት ላይ እጅግ ይቀናበት ነበር፡፡ ምክንያቱም ዳዊት ፍልስጤማዊው ጎልያድን ስላሸነፈ እስራኤላውያን በጣም ወደውት ነበር፡፡ ታዋቂም ሆኖ ነበር፡፡ ሳኦልም እግዚአብሔር እርሱን ትቶ ከዳዊት ጋር እንደሆነ ማሰብ ጀመረ፡፡ ስለዚህ በተለያየ ጊዜ ዳዊትን ለመግደል ሙከራ ያደርግ ነበር፡፡

 

አንድ ጊዜ ሳኦል የጦር ሰራዊቱን አስከትሎ ዳዊትን ለመግደል ፍለጋ ጀመረ ሳኦል ሳያውቅ ዳዊት ከሰራዊቶቹ ጋር የሚተኛበትና የሚሸሸግበት ዋሻ ስር ተኛ፡፡ ዳዊት ግን በዋሻው ውስጥ ተደብቆ ነበር፡፡ ሳኦልንም አየው፤ ልጆች እናንተ ዳዊትን ብትሆኑ ምን ታደርጉ ነበር? ዳዊት ግን ሳኦልን ሳይገድለው በተኛበት የልብሱን ጫፍ ቆርጦ ወሰደ፡፡ ሳኦልም ከእንቅልፉ ሲነቃ በተኛበት ጊዜ የተፈጠረውን ነገር ምንም አላወቀም፡፡ ዳዊትም ከኋላው ልብሱን እንደቆረጠበት ነገረው፡፡ ሳኦልም አለቀሰ፤ እጅግም አዘነ፡፡ ምክንያቱም ዳዊት እርሱን መግደል ሲችል ስላልገደለው ነው፡፡ ለዳዊትም እንዲህ አለው ‹‹ከእኔ ይልቅ አንተ ፃድቅ ነህ፤ እኔ ክፉ ሳደርግብህ አንተ ግን ክፉ አላደረግህብኝም፤ ስለዚህ ለእኔ ስላደረግኸው ቸርነት እግዚአብሔር መልካሙን ይመልስልህ’’ አለው:: ከዚህም በኋላ ሳኦልና ዳዊት ይቅር ተባባሉ፡፡

አያችሁ ልጆች እኛም ልክ እንደ ዳዊት የእግዚአብሔር ልጆች ስለሆንን ሁሉንም ሰው መውደድ አለብን፡፡ ክፉ ያደረጉብንን፣ የማይወዱንንና ሊጎዱን ያሰቡ ሰዎች ይቅር ማለት አለብን አንድ ሰው ክፉ ሲያደርግብንም እኛ ግን ያንን ሰው ይቅር ልንለውና ልንወደው ይገባል፡፡ የእግዚአብሔር ልጆች ከሆንን ሰዎችን የምንወድና ለሰዎች የምንራራ መሆን አለብን፡፡

lendon.jpg

በለንደን ያሉ ምእመናን ለቅዱሳት መካናት እርዳታ ሰጡ፡፡

በዩናይትድ ኪንግደም ቀጠና ማዕከል

ለገዳማትና የአብነት ት/ቤቶች መርጃ የሚውል የገቢ ማሰባሰቢያና የምሳ መርሐ ግብር ኅዳር 12 ቀን 2003 ዓ.ም በለንደን ከተማ ተካሂዷል። ይህ ሪፖርት እስከ ተጠናቀረበት ኅዳር 27 /2003 ዓ.ም በጥሬ ገንዘብ £5,000.00 ፣በዓይነት አንድ የአንገት የወርቅ ሐብል እና አንድ የወርቅ የእጅ አምባር ሊገኝ ተችሏል።

lendon.jpg
ፎቶ፦ ብፁዕ አቡነ እንጦንስ፣ መልአከ ገነት ቀሲስ ከፍያለው አስቻለውና ተሳታፊ ምዕመናን

በማኅበረ ቅዱሳን አውሮፓ ማዕከል የዩናይትድ ኪንግደም ቀጠና ማዕከል እና ለንደን ከተማ በሚገኘው የስንቄ ሬስቶራንት ትብብር በተዘጋጀው መርሐ ግብር የሰሜን ምዕራብ አውሮፓ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ እንጦንስ የተገኙ ሲሆን “ከሚቀበል ይልቅ የሚሰጥ ብፁዕ ነው’’ የሐዋ ሥራ ምዕ 20፥35 በሚል የመጽሐፍ ቅዱስ ቃል በመነሳት ሰፊ ትምህርት ሰጥተዋል፡፡ ብፁዕነታቸው አያይዘው የገዳማትን ችግር መጠነ ሰፊነት በማውሳት በቤተክርስቲያናችን አስተዳደር ከ44ቱም አህጉረ ስብከት ከሚገባው ገቢ 5% ለተቸገሩ አብያተ ክርስቲያናት እርዳታ እየተደረገ መሆኑ ፤ በሌላም መልኩ በተለይም በአዲስ አበባ ባሉ አብያተ ክርስቲያናት ላለፉት አስር ዓመታት በዓመት አንድ ጊዜ የወር በዓል ገቢያቸውን ለተቸገሩ አብያተ ክርስቲያናት መርጃ መዋሉ፤ የአብያተ ክርስቲያናቱ አገልጋዮች 15% በቋሚነት እንዲያዋጡ መደረጉ እና ሌሎችም ዘዴዎች ለዚህ ተጠቃሽ ይሆናሉ። ይሁን እንጂ ከእርዳታው ስፋት እና ከአብያተ ክርስቲያናቱ ብዛት አንጻር ችግሩን እስከ መጨረሻው መፍታት እንዳልተቻለ አስረድተዋል።

ማኅበረ ቅዱሳን ረዳት ድርጅት ነው፤ ወጣት ስለሆነ ይሮጣል፤ዘርፈ ብዙ ሥራ አለው። ያስተምራል ፤ ይሰብካል ያሳምናል ፤ ቤተ ክርስቲያንን ከመናፍቃን ይጠብቃል። በተለይም የተቸገሩ ገዳማትና አብያተ ክርስቲያናት ከመርዳት አኳያ በተለያዩ ምክንያቶች ሀገረ ስብከቶቹ ሊረዷቸው ያልቻሏቸውን ቦታዎች ፈጥኖ በመድረስና ቦታው ድረስ በመገኘት ይረዳል። በመሆኑም በሀገር ውስጥ በእያንዳንዱ ሀገረ ስብከት ማኅበሩ የሚሰራው ሥራ በሊቃነ ጳጳሳቱ ይታወቃል። ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳን እየሠራ ያለው ሥራ እጅግ ደስ የሚል፤ የሚያስመሰግንና የሞራል ድጋፍ ሊሰጠው የሚገባ እና ቅዱስ ሲኖዶስም በእጅጉ እንደሚደሰትበት ገልጸዋል። ስለሆነም ይህ ዕለት የተቀደሰ ነው፤ እኛ በዚህ ላለነው ጥሩ አጋጣሚ ነው፤ ጥሩ ዕድል ነው፤ ገዳማቱ እና የአብነት ት/ቤቶቹ መረዳት አለባቸው። ስለዚህ ይህን ችግር ከምንጩ ለመቅረፍ ሁላችሁም በጥልቀት በማሰብ የእርዳታ እጃችሁን እንድትዘረጉ አሳስባለሁ ብለዋል።

ለዚህ ዝግጅት ከአሜሪካን ሀገር ተጋብዘው የመጡት መልአከ ሰላም ቀሲስ ያሬድ ገብረ መድኅን “ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች” መዝ 67፥21 በሚል ርዕስ ሰፋ ያለ ትምህርት ሰጥተዋል።

(ፎቶ፦ቀሲስ ያሬድ ገ/መድኅን)

kesisyared.jpgበዚህ ትምህርታቸው ኢትዮጵያ የእግዚአብሔር ሀገር ፤ ሕዝቦቿም ሕዝበ እግዚአብሔር ለመሆናቸው መጽሐፍ ቅዱሳዊና ለብዙ ሺህ ዓመታት በኢትዮጵያውያን ዘንድ ፀንቶ የኖረው ሃይማኖታዊ ባህል ምስክር መሆኑን አብራርተዋል። ኢትዮጵያ  ብሉይና ሐዲስን አስተባብራ ይዛ መገኘቷ ከሌላው ዓለም ተለይታ እግዚአብሔርን ስታመልክ የኖረች ሀገር መሆኗን የሚያረጋግጥ መሆኑን ገልፀዋል። ከዚህም በላይ ታቦተ ጽዮን ፣ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ መስቀል፣ ገዳማቱ ፣ አድባራቱና የአብነት ት/ቤቶቹ ምን ያህል የሃይማኖት፣የታሪክ እና የባህል ሀገር እንደሆነች እንደሚያስረግጡ በሰፊው አስረድተዋል። በመጨረሻም እነዚህን ሃይማኖታዊ ታሪክ የያዙ መካናት እና ቅርሶች መጠበቅ የሁላችንም ድርሻ መሆኑን በማስገንዘብ ወቅታዊና አሳሳቢ ችግር ላይ ላሉት ገዳማት እና የአብነት ትምህርት ቤቶቻችን አፋጣኝ ምላሽ መስጠት እንደሚገባን አሳስባዋል።

ከትምህርቱም ቀጥሎ አጠቃላይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርሰቲያን ገዳማት እና የአብነት ት/ቤቶች አሁን የሚገኙበት ሁኔታ በሚል በመልአከ ሰላም ቀሲስ ያሬድ ገብረ መድኅን ሰፋ ያለ ገለጻ ቀርቧል። ገለጻው ገዳማትና የአብነት ት/ቤቶች በሀገሪቱ ውስጥ በተለያዩ  መስኮች የነበራቸውን ሃይማኖታዊና ማኅበራዊ አስተዋጽኦ እንዲሁም በአሁኑ ወቅት ደግሞ ገዳማትና የአብነት ት/ቤቶች ያሉባቸውን ልዩ ልዩ ችግሮች የዳሰሰና በመረጃ በመደገፍ የተቀነባበረ ነበር። በዚህ ገለጻቸው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ትተዳደርበት የነበረው የእርሻ መሬት “በመሬት ላራሹ” መቀማቷ፣ የምእመናን ኢኮኖሚያዊ አቅም እየተዳከመ መምጣት እና ኅብረተሰቡ ለአብነት ተማሪዎች ያለው አመለካከት እየተለወጠ መምጣት ገዳማት እና የአብነት ት/ቤቶች ላሉባቸው ችግሮች ተጠቃሽ ምክንያቶች መሆናቸው ተገልጿል። ይህ ዝግጅት ታዳሚውን ስለ ገዳማትና አብነት ት/ቤቶች ያለውን ግንዛቤ ከፍ እንዲል ከማድረጉም በላይ በችግሮቹ ዙሪያ ምን እናድርግ የሚል አስተሳሰብን የጫረ ነበር።

በማስከተልም ዲ/ን ሚሊዮን አጀበ በማኅበረ ቅዱሳን የዩናየትድ ኪንግደም ቀጠና ማዕከል ሰብሳቢ በዚህ ዝግጅት በሚገኝ ገቢ ሊረዱ የተመረጡ የሁለት ፕሮጀክቶች ዝርዝር አቅርበው ለተሰብሳቢዎቹ ገላጻ አድርገዋል። በገለጻቸው ማኅበረ ቅዱሳን ከዓላማ እና ተግባሩ ጀምሮ እስከ አወቃቀሩ እና የአባላቱ ስብጥር እንዴት በመላው ሀገሪቱ የሚገኙ ቅዱሳት መካናትን እና የአብነት ት/ቤቶችን ለማዳረስ እንደሚችል፣ እነርሱንም ለመደገፍ ያከናወናቸውንና እያከናወነ ያለውን አገልግሎት አጭር ዳሰሳ እና በዚህ ዝግጅት በሚገኝ ገቢ ሊረዱ የተመረጡት ሁለት ፕሮጀክቶች ዝርዝር ለመርሐ ግብሩ ታዳሚዎች ቀርበዋል። ፕሮጀክቶቹም   በደቡብ ወሎ ሀገረ ስብከት ከላላ ወረዳ ለሚገኘው አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ ገዳም የሕንጻ ግንባታ ፕሮጀክት እና በከፋ ሀገረ ስብከት ቦንጋ ከተማ ለሚገኘው ኪያኬላ አቡነ ተክለ ሃይማኖት ገዳም የአብነት ት/ቤት የዘመናዊ የከብት ርባታ ፕሮጀክት ናቸው።

የገቢ ማሰባሰቡ ሥራ የተከናወነው በተለያየ መልክ ነበር። የመግቢያ ትኬት ሽያጭ፣ የገዳማት ፎቶዎች ጨረታ፣ የቶምቦላ ዕጣ እና የበጎ ፈቃደኞች የገንዘብ ስጦታዎች ነበሩ።

በመርሐ ግብሩ ብፁዕነታቸውን ጨምሮ፣ በለንደን የደብረ ገነት ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን አስተዳዳሪ መልአከ ገነት ቀሲስ ከፍያለው አስቻለው፣ ለዚህ ዝግጅት ከአሜሪካን ሀገር ተጋብዘው የመጡት መልአከ ሰላም ቀሲስ ያሬድ ገብረ መድኅን እና ከተለያዩ አድባራት የመጡ ምዕመናን እና የሰንበት ት/ቤት ወጣቶች ተገኝተዋል።

በመጨረሻም ብፁዕ አቡነ እንጦንስ ዝግጅቱን በማስተባበር የሠሩትን የማኅበሩን አባላት፤ የስንቄ ሬስቶራንት ባለቤትን እና የዝግጅቱን ታዳሚዎች በማመስገን መርሐ ግብሩን በጸሎት ዘግተዋል።

 

ለቅዱስ ቁርባን ስለ መዘጋጀት

                                                                                   በአዜብ ገብሩ
ልጆች ዛሬ ቅዳሴ ስናስቀድስ ወደ ቤተክርስቲያን ስንመጣ ምን ማድረግ እንዳለብን እነግራችኋለሁ፡፡
በቤተክርስቲያን ጸሎት እናደርጋለን፣ እንቆርባለን፣ ትምህርት እንማራለን፡ስናስቀድስ ከእግዚአብሔር፣ከመላእክት እና ከቅዱሳን ጋር ሰለምንገናኝ ማስቀደስ በጣም ደስ ይላል፡፡

ልጆች ልንቆርብ ስንል ምን ማድረግ እንዳለብን ታውቃላችሁ? የሠራነው ኃጢአት ካለ ለእግዚአብሔር እና ለንስሐ አባታችን መናገር አለብን፡፡ የተጣላነው ሰው ካለ ይቅርታ መጠየቅ፣ ውሸት አለመዋሸት አለብን፡፡ ሌላው ልጆች ገላችንን መታጠብና ንጹሕ የሆነ ልብስ መልበስ አለብን፡፡

ምክንያቱም ከሁሉም በላይ የሆነውን የአምላክ ቅዱስ ሥጋና ክቡር ደም ልንቀበል ስለሆነ ነው፡፡ ንጹሕ የሆነውን ልብሳችሁን ከለበሳችሁ በኋላ ቅዳሴ ከመጀመሩ በፊት በቤተክርስቲያን መገኘት አለባችሁ፡፡ ይህንንም ለወላጆቻችሁ ነግራችሁ በጊዜ ይዘዋችሁ እንዲመጡ አድርጉ፡፡ በቅዳሴ ጊዜም እግዚአብሔር የማይወደውን ወሬ ማውራት ስለማይፈቀድ ይህን ማድረግ የለባችሁም ዝም ብላችሁ ቅዳሴውን መከታተል አለባችሁ፡፡ ከጎናችሁ የቆሙ ሕፃናትም ሲያወሩ ካያችሁ ክቡር በሆነው በእግዚአብሔር ቤት እንዳሉ ልትነግሯቸው ይገባል፡፡

የቅዳሴ ሥርዓት እና ምንባብ ያለበት መጽሐፍ ይዛችሁ ጸሎቱን በደንብ መከታተል አለባችሁ፡፡ልትቆርቡም ስትሉ ከጎናችሁ ካለው ልጅ ጋር መጋፋት መሰዳደብና መጣላት አይገባም፤ ተራችሁን በትህትና ቆማችሁ መጠበቅ አለባችሁ፡፡ ከቆረባችሁ በኋላ የቅዳሴ ጸበል ጠጡ፡፡ ቆሻሻ የሆነ ነገር ወደ አፋችሁ እንዳይገባ፣ከአፋችሁ እና ከአፍንጫችሁም ምንም ዓይነት ነገር እንዳይወጣ አፋችሁን በነጠላችሁ ሸፍኑ፡፡ ቅዳሴው አልቆ ዲያቆኑ በሰላም ወደየቤታችሁ ግቡ ብሎ እስኪያሰናብት ድረስ በቤተክርስቲያን ቆዩ፤ቅዳሴው ሲጠናቀቅም እግዚአብሔርን አመስግናችሁ በመንገድ እንቅፋት እንዳይመታችሁ እየተጠነቀቃችሁ ከወላጆቻችሁ ጋር ወደየቤታችሁ ሂዱ፡፡

እኛ ቤተ ክርስቲያን ሄደን ስንቆርብ ጌታችንም ከእኛ ጋር ወደ ቤታችን ይመጣል፤በዚህም ምክንያት ቤታችን ይገባል፤ቤታችንንም ይባርክልናል፡፡

በተሰደብክ ጊዜ

ዲ/ን ሄኖክ ኃይሌ

ቅዱስ ዳዊት በወታደሮቹ ተከብቦ ብራቂም ወደ ተባለ ስፍራ በመጣ ጊዜ፤ ከእርሱ አስቀድሞ ንጉሥ የነበረው የሳኦል ቤተ ዘመድ የሆነ አንድ ሰው በታላቅ ቁጣ ወደ እርሱ መጣ፡፡ በንጉሡ ሠራዊትና በዚህ እንግዳ ሰው መካከል ታላቅ ወንዝ ነበረ፡፡

ይህ ሳሚ የተባለ ሰው ወደ ንጉሡ ወደ ዳዊት ድንጋይ ይወረውርና ትቢያ ይበትን ነበር፡፡ ይህንን ተቃውሞ በሚያሰማበት ወቅት አንደበቱ አላረፈም ነበር፡፡ ይህ ሳሚ በቤተ ክርስቲያናችን የጸሎት መጻሕፍት ላይ በበርካታ ስፍራዎች በተራጋሚነቱ የሚወሳ ሲሆን በቅኔም ተሳዳቢ ሰውን ወክሎ የሚጠቀስ ነው፡፡ በሠራዊት ተከብቦ ያለውን ንጉሥ ዳዊትን ከፍ ዝቅ አድርጎ እየተሳደበና እየተራገመ ነበር፡፡ ‹‹ውጣ! አንተ የደም ሰው ምናምንቴ ሂድ! በፋንታው ነግሠሃልና እግዚአብሔር የሳኦልን ቤት ደም ሁሉ መለሰብህ፤ እግዚአብሔርም መንግሥትህን ለልጅህ ለአቤሴሎም እጅ አሳልፎ ሰጥቶታል፤ እነሆም አንተ የደም ሰው ነህና በመከራ ተይዘሃል!›› እያለ የስድብ ናዳ አወረደበት፡፡

እርግጥ ነው ዳዊት በሳኦል ፈንታ ነግሧል፤ ይሁንና የነገሠው ተራጋሚው ሰው እንደሚለው በጉልበቱና በራሱ ፈቃድ ሳይሆን በእግዚአብሔር ተመርጦ ነው፡፡ በዚያም ላይ ሳኦልን ሊገድል የሚችልበትን አጋጣሚ ‹እግዚአብሔር በቀባው ላይ እጄን አላነሣም› ብሎ አሳለፈው እንጂ በሳኦል ቤት ላይ ደመኛ የሚያሰኝ በደልን አልፈጸመም ነበር፡፡ ከብዙ የሕይወት ውጣ ውረዱ ላይ የገዛ ልጁ አቤሴሎም ባመፀበትና ቀን ጎድሎበት በተከፋበት ጊዜ እንዲህ ዓይነቱን ስድብና ንቀት ከአንድ ተራ ሰው መቀበል ለንጉሡ ለዳዊት በእርግጥ መራራ ነበር፡፡ ይሁንና ንጉሥ ዳዊት በመዝሙሩ ‹‹አንተ ስድቤን እፍረቴንም ነውሬንም ታውቃለህ፤ የሚያስጨንቁኝ ሁሉ በፊትህ ናቸው፡፡ ነፍሴ ስድብንና ኃሣርን ታገሠች›› ብሎ እንደዘመረው ታግሦ ዝም አለ፡፡ (መዝ.88÷22) ስለተሰደበው ስድብም ክፉም በጎም መልስ አልመለሰም፡፡

 

የንጉሣቸው በአንድ ተራ ሰው መሰደብና መንቋሸሽ ያንገበገባቸው ወታደሮቹ ግን ዝም ሊሉ አልቻሉም፡፡ ከወታደሮቹ መካከል የጺሩያ ልጅ አቢሳ በቁጣ ‹‹ይህ የሞተ ውሻ ጌታዬን ንጉሡን ስለምን ይረግማል? ልሻገርና ራሱን ልቊረጠው›› ብሎ በቁጭት ጠየቀ፡፡ ይህን የሎሌውን ለጌታው መቅናት ያየው ንጉሥ ዳዊት ይህንን ወታደር እሺ ብሎ አላሰናበተውም ወይም ስለ ተቆርቋሪነቱ አላመሰገነውም፤ ተቆጣው እንጂ፡፡ ‹‹እናንተ የጺሩያ ልጆች፤ ከእናንተ ጋር ምን (ጠብ) አለኝ? እግዚአብሔር “ዳዊትን ስደበው!” ብሎ አዝዞታልና ይርገመኝ፤ ለምንስ እንዲህ ታደርጋለህ የሚለው ማን ነው?›› አለ፡፡

 

በቅዱስ መጽሐፍ ስድብ ፈጽሞ የተከለከለ የአንደበት ኃጢአት ነው፡፡ የሚሳደብም ሰው ንስሓ እስካልገባ ድረስ ጽኑዕ ፍርድ እንደሚጠብቀው በግልጥ ተነግሯል፡፡ ታዲያ ቅዱስ ዳዊት ‹‹እግዚአብሔር “ዳዊትን ስደበው!” ብሎ አዝዞታልና ይርገመኝ›› ሲል ምን ማለቱ ነው? ተሳዳቢ ይልካልን? የሚል ጥያቄ መነሣቱ የግድ ነው፡፡ ስድብን የሚቃወምና በተሳዳቢዎች ላይ የሚፈርድ እግዚአብሔር አንድ ሰው ሌላውን እንዲሳደብ ፈልጎ ‹እገሌን ስደበው› ብሎ አይልክም፡፡ በእርግጥም እንዲህ ከሆነ ይህ ሰው ምንም አላጠፋም፤ እንዲያውም የእግዚአብሔር መልእክተኛ ነው ማለት ነው፡፡ ታዲያ ቅዱስ ዳዊት ‹ዳዊትን ስደበው ብሎ እግዚአብሔር አዝዞታል› ሲል ምን ማለቱ ነው?

 

እግዚአብሔር የሰው ልጆችን ለማስተማር፣ ለመገሠጽ፣ እምነታቸውንም ለመፈተን ሲል በርካታ መንገዶችን ይጠቀማል፡፡ የተናጋሪዎቹን ነጻ ፈቃድ ሳይነካ እንደገዛ ፈቃዳቸው የሚናገሩትን ኃይለ ቃል በመጠቀም በመልካም ሰዎች ብቻ ሳይሆን፤ በክፉ ሰዎችም ንግግር ያስተምራል፡፡ ለምሳሌ ንጉሥ ሄሮድስ ሰብአ ሰገልን አታለልሁ ብሎ ‹‹ስለ ሕፃኑ በጥንቃቄ መርምሩ ባገኛችሁትም ጊዜ መጥቼ እንድሰግድለት መጥታችሁ ንገሩኝ›› ብሎ ነበር፡፡ ይሁንና እግዚአብሔር ይህንን የሄሮድስ የሸፍጥ ንግግር የሰብአ ሰገልን እምነት ለማጽናት ተጠቅሞበታል፡፡ ምክንያቱም ሰብአ ሰገል ‹ልስገድለት› ማለቱን ሲሰሙ ለካ የሀገሩም ንጉሥ ያምንበታል ብለው እምነታቸው ጸንቶአልና ነው፡፡ የጌራ ልጅ ሳሚንም እግዚአብሔር ሒድ ተሳደብ ብሎ ባይልከውም እንደ ዳዊት ላለ መንፈሳዊ ሰው ግን ራሱን እንዲመረምር የተላከለት  ስጦታ ነበር፡፡ እግዚአብሔር የሳሚን የግልፍተኛነት ደካማ ጎን ተጠቅሞ ባሪያው ዳዊትን ገስጾታል፡፡

 

ንጉሥ ዳዊት በወታደሮች እና በሕዝብ ተከብቦ ያለ ኃያል ንጉሥ ሆኖ ሳለ የዚህን ተራ ሰው ስድብ ታግሦ ከመቀበልም ባሻገር ለሌላ ዓላማ ተጠቀመበት፡፡ ስድቦቹና እርግማኖቹንም እንደፍቱን መድኃኒት የኃጢአት ቍስሉን የሚሽሩ እንዲሆኑለትና ከእግዚአብሔር ምሕረት መቀበያ እንዲሆኑለት ተመኘ፡፡ ‹‹ምናልባት በዚህ ቀን መከራዬን አይቶ ስለ እርግማኑ መልካም ይመልስልኛል›› ብሎ በተስፋ ተናገረ፡፡

ይህን ደገኛ ንጉሥ ስድብን እንዲታገስ ምክንያት የሆኑት ነገሮችም አሉ፡፡ እርግጥ በሳኦል ቤት ላይ ተሳዳቢው ሳሚ እንዳለው ያለ ግፍ አልፈጸመም ይሁንና ሚስቱን ቀምቶ በግፍ ያስገደለው የኦርዮ ደም በእጁ አለ፡፡ ስለዚህ የሳሚን እርግማን ምክንያታዊ ባይሆንም ‹የደም ሰው› አስብሎ የሚያስጠራ በደል ሠርቶ ያውቃልና ለዚያ በደሉ ሥርየት እንዲሆነው እግዚአብሔር ይህንን ቅጣት እንዲያደርግለት በአኮቴት ተቀበለ፡፡

 

የተራገመውን ሰው ለመግደል ወታደሮቹ በተነሡ ጊዜ ቅዱስ ዳዊት ማስተዋልና ብስለት በተሞላበት ንግግር ነበር የከለከላቸው፡፡ በሳሚ ስድብና እርግማን ሳይበሳጭ ልጁ አቤሴሎም አሳድዶት እንደወጣ አስቦ፡- ከወገቤ የወጣው ልጄ ነፍሴን ይሻል፤ ይልቁንስ ይህ የብንያም ልጅ እንዴት ነዋ?›› በማለት የአብራኩ ክፋይ ልጁ ሊገድለው ተነሥቶ እያለ የሌላ ሰው ልጅ ሰደበኝ ብሎ ሊቆጣ እንደማይገባው ተናገረ፡፡ ‹‹ተነሣሒት በመሆኗ የምትታወቅ ነፍስ ወዳለችው ወደ ዳዊት ተመልከቱ! እነዚያን ሁሉ መልካም ነገሮች ካደረገ በኋላ ከሀገሩ ከቤቱ ሌላው ቀርቶ ከሕይወቱ እንኳን ስደተኛ ሆኖ እያለ በመከራው ጊዜ የአንድን ተራ ሰው ስድብ ታገሠ፤ መልሶ አለመሳደብ ብቻ ሳይሆን ከወታደሮቹ አንዱ ሊበቀልለት ሲነሣ ከልክሎ “እግዚአብሔር አዝዞታልና ይርገመኝ” አለ፡፡›› በማለት ቅዱስ ዮሐንስ አፈ ወርቅ ይህን የዳዊት ትዕግሥት ያደንቃል፡፡

 

ሰላም በሰፈነበት ወቅት በሚመስልህ በሚያክልህ አቻህ መነቀፍና መሰደብ ያን ያህል አይከብድህ ይሆናል፤ የሀገር መሪ ሆነህ በተራ ሰው በአደባባይ መሰደብ ግን ለመታገስ የሚከብድህ ነው፡፡ በተለይም በዙፋን ላይ ላለ ንጉሥ ከእርሱ ቀድሞ በነገሠው ንጉሥ ዘመዶች በአደባባይ መተቸት እጅግ የሚፈታተን ጉዳይ ነው፡፡ ንጉሥ ዳዊት ክፉ ቀን በገጠመው፣ የገዛ ልጁ ዐምፆበት በሚንከራተትበትና ሆድ በባሰው ሰዓት እንዲህ ዓይነቱን እርግማን መስማት የሚቋቋመው ጉዳይ አልነበረም፡፡

 

በዚህ ሁኔታ ላይ እያለ ንጉሥ ዳዊት ተሳዳቢውን ሳሚን ቢገድለው ኖሮ ለተሳዳቢው የሚያዝንለትም ሆነ በንጉሡ ላይ የሚፈርድበት ሰው አይኖርም ነበር፡፡ ‹እንደተራ ሰው ከፍ ዝቅ ሲያደርገው አቧራ ሲበትንበት ምን ያድርግ፤ ቀድሞ ነገር ንጉሥን በሠራዊቱ ፊት እንዲህ መዳፈር ይገባ ነበር?› እያለ የየራሱን ማስተባበያ ይሰጣል እንጂ ማንም ንጉሡን አይኮንነውም ነበር፡፡ በዚያ ላይ እግዚአብሔር የቀባውን ንጉሥ ተሳደበ የተባለ ሰው ደግሞ ሞት ቢፈረድበት ሁሉም የሚስማማበት ዘመን ነበር፡፡ (1ነገ. 20÷13፤ 2ሳሙ 19÷21)፡፡

 

ንጉሥ ዳዊት ግን ይህንን ሁሉ ትቶ ስድቡን በደስታ ተቀበለ፤ የቀረበበትን ትችት ተገቢ አለመሆኑን ለሌሎች   ለማስረዳት አልሞከረም፡፡ እኔ ሳኦልን ማጥፋት ስችል ዝም አልኩ እንጂ መች አጠቃሁት?፤ የሳኦልን የልጅ ልጅ ሜምፊቦስቴን እንኳን በገበታዬ አቅርቤው አልነበረም? ብሎ ለመናገር አልፈለገም ‹‹እግዚአብሔር አዝዞታልና ይርገመኝ››አለ እንጂ፡፡

ቅዱሳን ስድብን ታግሠዋል

ቅዱስ ጳውሎስ ‹‹ሲሰድቡን እንመርቃለን ሲያሳድዱን እንታገሣለን ክፉ ሲናገሩን እንማልዳለን፤ እስከ አሁን ድረስ የዓለም ጥራጊ የሁሉም ጕድፍ ሆነናል›› ብሎ እንደተናገረ ስድብን በጸጋ መቀበል የክርስቲያኖች መታወቂያ ነው፡፡ (1ቆሮ. 4÷12) በብዙ ቅዱሳን ሕይወት ውስጥ ያለአግባብ መሰደብ የተለመደና በደስታ የሚቀበሉት ተግሣጽ ነበር፡፡ ቅዱሳኑ ስድብን በደስታ ይቀበሉ የነበረው ለስድብ የሚያበቃ ጥፋት ስለ ሠሩ አልነበረም፡፡ ያለ ስሙ ስም፣ ያለ ግብሩ ግብር ተሰጥቶት በዕለተ ዓርብ በአደባባይ የተሰደበውና የተተፋበትን አምላካቸውን መድኃኔዓለምን በእምነት እያዩ ‹ከእኔ ትለፍ› ያላትን የመከራ ጽዋዕ በመቅመሳቸው ደስ እየተሰኙ ነበር፡፡ ከሸንጎ ፊት ሲወጡም ጮማ እንደቆረጡ፤ ጠጅ እንደጠጡ ሁሉ ፊታቸው በደስታ በርቶ የወጡት ‹‹ስለ ስሙ ይናቁ ዘንድ የተገባቸው ሆነው ስለተቆጠሩ›› ነበር፡፡ (ሐዋ 6÷41)

 

በአበው መነኮሳት ታሪክ ስድብና እርግማንን ሳያስተባብሉ በአኮቴት መቀበልን የመረጡ ብዙ ቅዱሳንን እናገኛለን፡፡ በንጽሕናቸው መላእክትን መስለው ይኖሩ የነበሩት ቅዱሳን ከዝሙት ርቀው ሳለ ዘማውያን ሲሏቸው ታግሠዋል፡፡ አባ መቃርዮስ የተባለ አባት ከአንድ ጎልማሳ የጸነሰች ወጣት ከእርሱ ነው የጸነስኩት ብላ በከሰሰችው ጊዜ እኔ አይደለሁም ሳይል ‹‹እየሠራሁ ልርዳ›› ብሎ ተቀብሏል፡፡ እስክትወልድ ድረስ ሰሌን እየሸጠ ሲረዳት ከቆየ በኋላ በምጥዋ ጊዜ ጭንቋ ሲበዛ እውነቱን ተናግራለች፡፡ ቤተሰቦቿ ይቅር በለን ሊሉት በሔዱ ጊዜ በአቱን ለቅቆ ሔዷል፡፡ (ስንክሳር ዘወርኀ መጋቢት 27)

 

እንደ አባ መቃርዮስ ያለ ስድብን የታገሠው አባ በጥል እና በጾታ ሴት ሆና ሳለ ሴት መሆኗን ሳያውቁ በሐሰት ድንግል ሴትን አስረግዘሻል ብለው ዕድሜዋን ሙሉ የነቀፏት ቅድስት ዕንባ መሪናም ባልሠሩት መነቀፍን መታገሥ እንደሚገባን የሚያስረዱ እንደ ደመና የከበቡን ምስክሮቻችን ናቸው፡፡ እውነተኛ ትሑትም ሲሰድቡት የሚታገስ ነው እንጂ ስድብን የሚያስተባብል አይደለም (ማር ይስሐቅ 6)፡፡

ስድብን በስድብ ፈንታ አትመልሱ !

ቅዱስ ጴጥሮስ ‹‹ክፉን በክፉ ፈንታ ወይም ስድብን በስድብ ፈንታ አትመልሱ በዚህ ፈንታ ባርኩ እንጂ፥ በረከትን ልትወርሱ ለዚህ ተጠርታችኋልና።›› በማለት እንደተናገረ ሲሰድቡት መልሶ መሳደብ የክርስቲያን ተግባር አይደለም፡፡ ምክንያቱም ክርስቲያን ያሰኘን አምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ‹‹ሲሰድቡት መልሶ    አልተሳደበም መከራንም ሲቀበል አልዛተም፥ ነገር ግን በጽድቅ ለሚፈርደው ራሱን አሳልፎ ሰጠ፤›› እንጂ (1ጴጥ.2÷23 ፣3÷9)፡፡

 

በእውነቱ ክርስቲያኖች እንሰኝ እንጂ ተሰድቦ መታገስ ግን ለብዙዎቻችን የሚዋጥ አይደለም፡፡ ተሰድቦ ዝም ማለት በብዙዎቻችን ትርጓሜ ራስን ማስናቅ፣ ፊት መስጠት፣ ፈሪነት እንጂ ትዕግሥት ተብሎ አይጠራም፡፡ አንዳንድ ዝም ያልንባቸው አጋጣሚዎች ቢኖሩም እንኳን በትሕትና ታግሠን አለመሆኑና የዝምታችን ምክንያት ሌላ መሆኑ የመታገሣችንን ደረጃ ዝቅ ያደርገዋል፡፡ ተሰድበን ዝም የምንልባቸው ብዙ ምክንያቶችም አሉ፡-

•    ለተሳዳቢው ቦታ ካለመስጠት ንግግሩን ‹‹እንደ ዘፈን ቆጥሮ›› ‹ያሻውን ይለፍልፍ፣ ምን ያመጣል?› ከሚል ንቀት፤

•    ተሳዳቢው አካል በቀላሉ ልንጋፋው የማንችለው የበላያችን ሆኖ መልስ ብንሰጥ የሚመጣብንን በመፍራት፣

•    በአንደበት መልስ ከመስጠት ይልቅ ሌላ መበቀያ ምቹ መንገድ ለመፈለግ፣

•    በቃል በሚደረግ እሰጥ አገባ የተነሣ በሌሎች ሰዎች ዐይን ትዝብት ውስጥ ላለመውደቅ

በመሳሰሉ ተርታ ምክንያቶች ተሰድበን ልንታገስ እንችላለን፡፡ ይህ ግን ትዕግሥት ሆኖ ዋጋን የሚያሰጥ አይደለም፡፡

አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ብዙ ጊዜ ታግሠን ከቆየን በኋላ በአንድ አጋጣሚ ስንጋጭ ታግሠን ያሳለፍናቸውን ስድቦች ሁሉ ካጠራቀምንበት ልባችን አውጥተን ‹‹ታግሼ ነው እንጂ፤ ለእግዚአብሔር ሰጥቼ ነው እንጂ እንዲህ እንዲህ ብለኸኝ/ ብለሽኝ ነበር›› ብለን እናስታውሳቸዋለን፡፡ ቅዱስ ዳዊት ግን በተግባር ያስተማረን ስድብን መታገስ ብቻ ሳይሆን ይገባኛል ብሎ ማመንንና ከእግዚአብሔር እንደተላከ ተግሣጽ መቀበልን ነው፡፡

 

ውድ ክርስቲያኖች! የጌራ ልጅ ሳሚ ቅዱስ ዳዊትን የሰደበው ስድብ ተገቢ አልነበረም፡፡ እኛን ግን ብዙ ጊዜ ሰዎች የሚሰድቡንና የማንታገሠው ስድብ አንዳች እውነታንም ያዘለ ነው፡፡ ያለ አንዳች ምክንያትም የሚሰድበን የለም፡፡ ይሁንና ሌላው ቀርቶ ስማችንን የመጥራት ያህል ለእኛ በሚመጥን (በሚገባን) ክፉ ስም ሰዎች ሲጠሩን እንኳን ይበሉኝ ብለን ከመታገስ ይልቅ ለጠብ እንቸኩላለን፡፡ ልሳነ ወርቅ ቅዱስ ዮሐንስ እንዲህ ብሏል፡- ‹‹አንድ ሰው “አንተ አመንዝራ” ብሎ ሲሰድብህ ለምን ትቆጣለህ? በሐሳብህም እንኳን ቢሆን አመንዝረህ አታውቅም? ወይም ደግሞ በክፉ የጎልማስነት ምኞት ዝለህ አታውቅም? ስለዚህ ይህንንም ስድብ ለክፉ ሐሳቦችህ እንደ ቅጣት አድርገህ ልትቆጥረው ይገባሃል፡፡››

 

‹ብልህ ሰው ከስድብ ይማራል› የሚሉት ብሂልም በእርግጥ እዚህ ላይ ሊነገር ይችላል፡፡ ‹ወንበዴ ቀማኛ› ከሚለው ስድብ ጀርባ ‹አትስረቅ› የሚል ምክር አለ፣ ‹ዘማዊ አመንዝራ› ከሚለው ነቀፋ ጀርባ ‹አታመንዝር› የሚለው ተግሣጽ አለና በምን ነቀፈው ነቀፋ መነፅርነት ራሳችንን መመልከት ይገባናል፡፡ ከስድብ ጀርባ ምክርና ተግሣጽ አለ ሲባል ግን ስድቡን ከሚሰማው ሰው አንጻር ነው እንጂ ምክርን ያዘለ ነው እያሉ ሰውን መሳደብ ይገባል ማለት እንዳልሆነ ግልጥ ነው፡፡ ላሳዝነው ብሎ ሥር ገብቶ ቤት መርምሮ ዘር ቆጥሮ መሳደብ በእግዚአብሔር ዘንድ   የሚያስፈርድ ነው፡፡ ‹‹ወዘይፀርፍሂ ላዕለ እኁሁ ፀረፈኬ ላዕለ እግዚአብሔር ልዑል፤ ወንድሙን የሚሰድብ ልዑል እግዚአብሔርን ተሳደበ›› ተብሎ እንደተነገረ ሕንፃን መንቀፍ ሐናፂውን መንቀፍ፣ ሥዕልን መንቀፍ ሠዓሊውን መንቀፍ እንደሆነ ሁሉ፤ ፍጡርን መንቀፍም ፈጣሪን መንቀፍ ነው፡፡ ፈጣሪን መንቀፍ ነው የተባለውም ሰውን የሠራ እግዚአብሔር ስለሆነ አንድም ደግሞ ሰው በእግዚአብሔር አርአያና አምሳል ስለተፈጠረ ነው (ተግሣጽ ቀዳማዊ ዘቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)፡፡

 

ቅዱስ ዳዊት ‹እግዚአብሔር አዝዞታልና ይርገመኝ!› እንዳለ ሰዎች በክፉ ቃል በተናገሩን ጊዜ ቀንቶብኝ ነው፣ ተመቅኝቶኝ ነው እያሉ ራስን ከመካብ ይልቅ ‹አምላክ በዚህ ሰው አንደበት አድሮ ኃጢአቴን ሊያመለክተኝ ነው› ብሎ በትሕትና ማሰብ ይገባል፡፡ ትሕትና ማለትም ‹‹ራስን መሳደብ ሳይሆን ሌሎች ሲሰድቡን መታገሥ ነው›› ብሏል ቅዱስ ዮሐንስ በተግሣጹ፡፡

 

ተሳዳቢው ሰው የቱንም ያህል ክፉ ቢሆን፣ የምንሰደበው እኛም የቱንም ያህል ንጹሐን ብንሆን መልሶ መሳደብ አይገባም፡፡ ንጉሥ ዳዊት ስለ በደለው በደል ንስሓ የገባ ጻድቅ ቢሆንም፤ የጌራ ልጅ ሳሚም መናገር የማይገባውን የተናገረው ቢሆንም ታግሦታል፡፡ እኛም የሚሰድቡን ሰዎች ምንም ቢከፉ እኛም የቱን ያህል ብንቀደስ ለስድብ አጸፋ መመለስ አይገባንም፡፡ ከላይ ከተነሣንበት ታሪክ አንጻር ሙሉ በሙሉ ሊተረጎም አይገባም እንጂ አሁን ላነሣነው ሐሳብ የመልአኩን የቅዱስ ሚካኤልን ታሪክ ምሳሌ ልናደርገው እንችላለን፡፡ ይህ ታላቅ መልአክ ከአንዴም ሁለት ጊዜ ዲያቢሎስ የድፍረት ቃልን በተናገረው ጊዜ ‹‹እግዚአብሔር ይጣልህ!›› አለው እንጂ የስድብን ቃል ሊናገረው አልደፈረም፡፡ (ዘካ 3÷2፤ ይሁ 1÷9) ከመላእክት ወገን ከቅዱስ ሚካኤል በላይ የከበረ ከዲያብሎስም በላይ የተዋረደ የለም፤ ከነሠራዊቱ ተዋግቶ የጣለውን ውዱቅ መልአክ እንደ ሰው ቢሆን የጥንቱን አንሥቶ ሊያዋርደው ይቻለው ነበር፤ ይሁንና የከበረው ሚካኤል ለተዋረደው ዲያብሎስ እንኳን ክፉ ሊመልስለት አልወደደም፡፡

 

እኛም ምንም ብንከብር የቅዱስ ሚካኤልን ያህል አንከብርም፤ የሚሰድቡን ሰዎችም ምንም ቢከፉ የዲያብሎስን ያህል አይከፉምና ለመሳደብ በመቸኮል ለአንደበታችን አርነት አንስጥ! የሚገባንን ስድብ ስንሰደብ ራሳችንን በስድቡ ውስጥ እንገሥጽ፣ ያለ ጥፋታችን ስንሰደብ ደግሞ ያለ ጥፋቱ የተሰደበ አምላክ ባሪያዎች መሆናችንን እያሰብን ከቅዱስ ዳዊት ጋር ‹‹ትዕይርቶሙ ለእለ ይትዔየሩከ ወድቀ ላዕሌየ›› ‹‹የሚሰድቡህ ስድብ በላዬ ወደቀ›› ብለን እናመስግን! (መዝ 88÷9)፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ምንጭ፡ሐመር ኅዳር 2003 ዓ.ም

ሐዘን ሲገጥመን ምን እናድርግ? / 2ቆሮ 5÷1-5 /

ዲ/ን ብርሃኑ አድማስ
 
የምንወደው ሰው በሞት ከእኛ ሲለይ በእጅጉ እናዝናለን፤ እናለቅሳለንም፡፡ በርግጥም ማልቀስ በአግባቡ ከሆነ ጠቃሚና አስፈላጊ ነገር ነው፡፡ በመሪር ሐዘን የተቆጣውን ሰውነታችንን የሚያስተነፍስ መፍትሔ፤ዕንባ፡፡ የውስጥ ሰውነቱ ፈሳሽ ነገር ቋጥሮበት ወይም በእግርና በእጁ ላይ መግል የቋጠረ የቁስል ጥዝጣዜ ዕረፍት የነሣው ሰው የቋጠረውን ፈሳሽ ወይም የሚጠዘጥዘውን መግል ሲያፈሱለት ደስ እንደሚለውና ዕረፍት እንደሚሰማው በሐዘን ውስጡ የተጎዳ ሰውነትም ዕንባ ሲያፈስ ዕረፍት ማግኘቱ አይቀሬ ነው፡፡

እግዚአብሔር ሰውን ሲፈጥር ዕንባ እንዲኖረው አድርጎ የፈጠረውም ዕንባ ጠቃሚና አስፈላጊ በመሆኑ ነው፡፡ እስከ አሁን በምናውቀው እንኳ ሦስት ከፍተኛ ጠቀሜታዎች አሉት፡፡

የመጀመሪያው ጠቀሜታው ዕንባ በሰው ልጅ ታሪክ ከተጀመረበት ጊዜ አንሥቶ ያለው ነው፡፡ ዕንባ የተጀመረው በአዳምና በሔዋን ነው፡፡ ያለቀሱትም አትብሉ የተባሉትን ዕፀ በለስ በልተው እግዚአብሔርን በመበደላቸው   ምክንያት ነው፡፡ ስለዚህ ዕንባ የተጀመረው በንስሐ ነው፡፡ ይህ ማለት ግን ከዚያ በፊት በሰውነታቸው ያልነበረ ነገር ተፈጠረ ማለት አይደለም፡፡ በሩካቤ መተዋወቃቸውን /የተዋወቁበትን ጊዜ/ ይዘን በዚያ ጊዜ የመራቢያ ብልታቸው ተገኘ እንደማንለው ዕንባውም እንዲሁ ነው፡፡ በቀሌምንጦስ «አልቦቱ ካልዕ ሕሊና ለአዳም ዘእንበለ ብካይ ላዕለ ኃጢአቱ፤ ለአዳም ስለ ኃጢአቱ ከማልቀስ /ኃጢአቱን እያሰበ ከማልቀስ/ በቀር ሌላ አሳብ /ግዳጅ/ አልነበረውም» ተብሎ እንደተጻፈ ዕንባ የተጀመረው በዚህ ነው፡፡ ስለዚህ የዕንባ ቀዳሚ ጠቀሜታ ሰውን በንስሐ ከእግዚአብሔር ጋር ማስታረቅ ነው ማለት ነው፡፡ ይህም በመጽሐፍ ቅዱስ ተደጋግሞ ተመዝግቧል፡፡ «ወበአንብዕየ አርሐስኩ ምስካብዬ፤ በዕንባዬም መኝታዬን አርሳለሁ» የሚለው ቅዱስ ዳዊት የንስሐ ዕንባውን፣ የጸሎት ዕንባውን ነው፡፡ /መዝ 6÷6/ ጌታችንም በወንጌል «ብፁዓን እለ ይላህው ይእዜ እስመ እሙንቱ ይትፌስሑ፤ ዛሬ የሚያዝኑና የሚያለቅሱ የተመሰገኑ ናቸው፣ መጽናናትን ያገኛሉና» /ማቴ 5÷4/ ሲል ያስተማረው የሚገባው ለቅሶ ወይም ዕንባና ሐዘን የንስሐ መሆኑን ያስረዳናል፡፡ በሌላም ቦታ «እናንተ አሁን የምትስቁ ወዮላችሁ፣ ታዘናላችሁና፣ ታለቅሱማላችሁ» /ሉቃ 6÷25/ ሲል ያስጠነቀቀን ጠቃሚውን ዕንባና ሐዘን ለማስተማር ነው፡፡ መፍቀሬ ጥበብ ሰሎሞንም «ከሳቅ ሐዘን ይሻላል፣ ከፊት ኀዘን የተነሣ ደስ ይሰኛልና፤ የጠቢባን ልብ በልቅሶ ቤት [በንስሐ] ነው፤ የሰነፎች ልብ ግን በደስታ ቤት [ኃጢአት በሚፈጸምበት ቦታ] ነው» በማለት የንስሐ ዕንባን መፈለግ ጠቢብነት እንደሆነ ይነግረናል፡፡ከዚህም በላይ በቅድስና ሕይወት የሚኖሩ ቅዱሳን በዐሥሩ መዓርጋት ሲሸጋገሩ አራተኛው መዓርግ አንብዕ ይባላል፡፡ ይህም ፊታቸው ሳይከፋውና ሰውነታቸው ሳይሰቀቅ ዕንባን ከዓይናቸው ማፍሰስ ነው፡፡ ስለዚህ ዕንባ ይህን የመሰለ ጠቀሜታ ያለው በመንፈሳዊነትም የብቃት ደረጃ ሆኖ እናገኘዋለን ማለት ነው፡፡

ሁለተኛው ጠቀሜታው ደግሞ ተፈጥሮአዊ ነው፡፡ ማንኛውም ሰው በዓይኑ ላይ ሁልጊዜም ስስ የሆነች የዕንባ ሽፋን አለችው፡፡ ሳይንስም ጭምር እንደ ተረጋገጠው ዓይንን በከፍተኛ ደረጃ ከሚጠብቁት ነገሮች አንዷና ዋናዋ ይህች ዕንባ ናት፡፡ ስለዚህ በነፋስ፣ በፀሐይ፣ ጨረርና በመሳሰለው ከፍተኛ ጉዳት እንዳይደርስበት ይህች ዕንባ ትከላከልለታለች፡፡ በነፋስና በሙቀት ደርቃ እንዳታልቅም እግዚአብሔር በጥበብ እንድንጠቀምባት አድርጓል፡፡ ማንኛውም ሰው ዓይኑን ጭፍን አድርጎ ሲከፍተው በዓይኑ ላይ የነበረችውን ስስ የዕንባ ሽፋን ገፍቶ ወደ አፍንጫ በሚያወርደው ቀዳዳ ያስወግድና አዲስ ዕንባ ይተካል፡፡ በዚህ መንገድ በየደቂቃው ወይም ዓይናችንን ጭፍን ግልጥ ባደረግን ቁጥር ይህችን የዕንባ ሽፋን በአዲስ መልክ     ስለምንቀይር ዓይናችንን በረቂቅ መንገድ እንጠብቃለን፡፡ የሀገራችን ሰው «የዓይን አምላክ» የሚለው ለዓይን ይህን የመሰለ ሰፊ የጥበቃ መንገዶችን እግዚአብሔር ስለፈጠረልን ነው፡፡ በመጽሐፍም «ዕቀበኒ እግዚኦ   ከመ ብንተ ዓይን፤ አቤቱ እንደ ዓይን ብሌን ጠብቀኝ» የሚል ቃል ተጽፏል፡፡ ስለዚህ ዕንባ ዓይንን እንዲህ አድርጎ ለመጠበቅ ጠቃሚ ነው ማለት ነው፡፡

ሦስተኛው ጠቀሜታው ደግሞ ሐዘንን ማስወገጃ ማስተንፈሻ የሐዘን ማቅለያ መሆኑ ነው፡፡ ከዛሬው የጽሑፋችን ዓላማ ጋር የሚገናኘውም ይኽኛው ነው፡፡ የመጀመሪያው  አባታችን አዳም የመጀመሪያ ልጁ አቤል በሞተ ጊዜ እጅግ ተጨንቆ ሰውነቱ ሁሉ አባብጦ ተነፋፍቶም እንደነበር ትውፊቱን የመዘገቡ መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡ በመጀመሪያ ሞት ከዚያ በፊት አይታወቅምና ምን ማድረግ እንደነበረባቸው እንኳን አዳምና ሔዋን አያውቁም ነበር፡፡ ዳግመኛም በዚያ ጊዜ     የመጀመሪያዎቹ ሰዎች በምድር ላይ እነርሱ ብቻ ናቸውና የሚያጽናናቸውም ሆነ የሚመክራቸው ሰው ማንም አልነበረም፡፡ በዚህ ምክንያት አዳም ሰውነቱ በሐዘን ተዋጠ፤ ተጨነቀ፤ ሰውነቱም ተቆጣ፤ ታመመም፡፡ በዚህ ጊዜ መላእክት ወደ አዳም መጥተው እንዲያለቅስ አሳዩት፤ አስተማሩት፡፡ እርሱም ሲያለቅስ ውጥረቱ በረደ፤ የተቆጣ አካሉ ተመለሰ፤ ሰውነቱም ዕረፍት አገኘ፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ በሐዘን የሚገጥመንን የሰውነት መታመምና ከባድ ጭንቀት በዕንባ መገላገሉን ይዘን ይኸው እስከ አሁን ዘልቀናል፤ ወደፊትም እንቀጥላለን፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም አልዓዛርን ከተቀበረ ከአራት ቀናት በኋላ ከሞት ሊያስነሣው ሲሔድ በእኅቶቹ ቤት እንደደረሰ መጀመሪያ አልቅሶለታል፡፡ /ዮሐ 11/፡፡ ይህም በሞት ለተለየን ሰው በሐዘን ጊዜ ማልቀስ ተገቢ መሆኑን ይህንም በማድረጋችን ኃጢአት እንደማንሠራ ያስረዳናል፡፡ ጌታ ቸር አምላክ፣ ሰውንም ወዳጅ ነውና ከጥቂት ደቂቃዎች በኋላ ከሞት እንደሚያስነሣው እያወቀ እኅቶቹን ሲያገኛቸው መጀመሪያ ሐዘናቸውን በልቅሶ ተካፈለ፡፡ ከዚያም እነርሱን አጽናንቶ ሞቶ የተቀበረውን ከሞት አሥነሥቶ ከመቃብር አውጥቶታል፡፡ በዚህም እጅግ ብዙና ሰፊ ትምህርቶችን አስተምሮናል፡፡

ለክርስቲያኖች በሐዘን ጊዜ ማድረግ ስለሚገባቸውና ስለማይገባቸው ነገሮች መሠረታዊ የሆኑት የትምህርት መነሻዎች ከላይ የጠቀስናቸው እነዚህን የመሰሉት በቅዱሳት መጻሕፍት የተገለጡት ታሪኮች ናቸው፡፡ ምንም እንኳን በሞት ለተለየን ቤተሰባችን የተሰማንን ሐዘን በለቅሶና በዕንባ መገላገል ተገቢ ቢሆንም ለእነዚህም ጊዜና መጠን አላቸው፡፡

በጊዜ ያልተወሰነ በመጠን ያልተገደበ ከሆነ እንኳን ሐዘን፣ ለቅሶና ዕንባ ቀርቶ ደስታና ጨዋታም በእጅጉ ጎጂ ነው፡፡ ቀደም ብለን እንደገለጽነው ሐዘንን በዕንባ መገላገል ጠቃሚና እግዚአብሔር የፈቀደው ቢሆንም   ከመጠኑ ሲያልፍ ደግሞ ከጥቅሙ በተቃራኒ በእጅጉ ይጎዳል፡፡ በበጋ የደረቀች መሬትን ለማርጠብ፣ ለማለስለስና እህሉንና ሣሩን ለማብቀል የክረምት ዝናም አስፈላጊና ጠቃሚ መሆኑ ይታወቃል፡፡ ከመጠን በላይ ከወረደ ግን እርሻውን አጣጥቦ በመውሰድ፣ የበቀለውን አዝመራ በማጥፋት ከፍተኛ ጉዳት ያደርሳል፡፡ ለቅሶና ዕንባም እንዲሁ ነው፡፡ ዓይንን ለመጠበቅና ሰውነታችን በሐዘን እንዳይጎዳ ለመከለካል የተፈጠረውን ዕንባ ስናበዛው ዓይናችንን ለማጥፋት፣ ሰውነታችንም ጎርፍ እንደበላው መሬት ሸርሸሮ ለማይድን በሽታ    ያበቃዋል፡፡ ስለዚህ ልክና መጠኑን ጠብቆ በጊዜ ተወስኖ የሚፈጸም ብቻ ነው ማለት ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም «እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ የሆነ ኀዘን ጸጸት የሌለበትን፣ ወደ መዳንም የሚያደርሰውን ንስሐ ያደርጋልና፡፡ የዓለም ሐዘን ግን ሞትን ያመጣል፡፡» /2ቆሮ 7÷10/ የሚለን ለዚህ ነው፡፡

አንድ ሰው ከቤተሰብ አንዱ በተለየው ጊዜ የሚያደርገው ነገር በመጠንና በሥርዓት ካልሆነ እንኳን ሥጋውን ነፍሱንም ጨምሮ ይጎዳዋል፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ በሐዘናቸው ምክንያት እግዚአብሔርን ያሳዘኑ እርሱም   ያዘነባቸው ሰዎች አሉ፤ እንዲሁም ደግሞ በሐዘናቸው እግዚአብሔርን ደስ ያሰኙ ሰዎች አሉ፡፡ በወንጌል እንደተጻፈው የሰማዩን ቤት የማያስቡ፤ በጎ የሠሩ ሰዎች በሰማይ ከእግዚአብሔር የሚቀበሉትን በጎ ዋጋ ረስተው የሰውን ሞት ተስፋ እንደሌለው እንደ እንስሳ እና እንደ አራዊት ሞት ወይም ተቆርጦ እሳት በልቶት አመድ እንደሚሆን ካለበለዚያም ወድቆ በስብሶ አፈር ሆኖ እንደሚቀር እንደ ዛፍ እንደ ቅጠል ቆጥረው መሪር ሐዘን የሚያዝኑ ሰዎች ሰነፎች ናቸው፤ እግዚአብሔርን ያሳዝናሉ፤ እግዚአብሔርም ያዝንባቸዋል፡፡ «ሙታናቸውን ይቀብሩ ዘንድ ሙታንን ተዋቸው» ብሎ ጌታ በወንጌል የተናገረላቸው ሰዎች የሰውን ክብር እና የእግዚአብሔርን ኃይል ለማያውቁ ሰዎች ነው፡፡ እንደዚህ ያሉት ሰዎች «ሙታን» የተባሉት በምድር ላይ በሕይወት እየኖሩ ነው፡፡ ሙታን የተባሉት የሞተ ሰው ሥጋው ምንም ሊያውቅ እንደማይችል እነዚህም እየኖሩ የማያውቁና የማያስታውሱ ስለሆኑ ነው፡፡ ስለዚህ አንድ ክርስቲያን ትንሣኤ  እንደሌለን በሰማይ በአባታችን ቤትም ክብርና ጸጋ እንደማይጠብቀን አድርጎ የሚያዝንና የሚያለቅስ ከሆነ እግዚአብሔርን የሚያሳዝን እንደተጻፈውም ቆሞ የሚሔድ ነገር ግን የሞተ ይሆናል፡፡

በተጠቀሰው መንገድ እግዚአብሔርን ያሣዘኑ ሰዎች እንዳሉ ሁሉ እግዚአብሔርን ያስደሰቱትም ደግሞ አሉ፡፡ ከእነዚህ አንዱና ዋናው ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ነው፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ እንደተገለጸው ዳዊት ልጁ በታመመ ጊዜ በእጅጉ አዝኖ ነበር፡፡ ከሞተ በኋላ ግን ያደረገው ብዙዎችን አስገርሟል፤ አርአያነቱም ታላቅ ነው፡፡ ታሪኩን የሚነግረን መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡፡ «እግዚአብሔርም የኦርዮ ሚስት ለዳዊት የወለደችውን ሕፃን ቀሰፈ፣ እጅግም ታምሞ ነበር፡፡ ዳዊትም ስለ ሕፃኑ እግዚአብሔርን ለመነ፤ ዳዊትም ጾመ፣ ገብቶም በመሬት ላይ ተኛ፡፡ የቤቱም ሸማግሌዎች ተነሥተው ከምድር ያነሡት ዘንድ በአጠገቡ ቆሙ፤ እርሱ ግን እንቢ አለ፣ ከእነርሱም ጋር እንጀራ አልበላም፡፡ በሰባተኛውም ቀን ሕፃኑ ሞተ፡፡ የዳዊትም ባሪያዎች ሕፃኑ በሕይወት ሳለ ብንነግረው አልሰማንም፤ ይልቁንስ ሕፃኑ እንደሞተ ብንነግረው እንዴት ይሆን ?» በነፍሱ ክፉ ያደርጋል ብለው ሕፃኑ እንደሞተ ይነግሩት ዘንድ ፈሩ፡፡ ዳዊትም ባሪያዎቹ በሹክሹክታ ሲነጋገሩ ባየ ጊዜ ዳዊት ሕፃኑ እንደሞተ አወቀ፤ ዳዊትም ባሪያዎቹን ሕፃኑ ሞቶአልን? አላቸው፡፡ እነርሱም፡- ሞቶአል አሉት፡፡ ዳዊትም ከምድር ተነሥቶ ታጠበ፣ ተቀባም፣ ልብሱንም ለወጠ፤ ወደ እግዚአብሔርም ቤት ገብቶ ሰገደ፡፡ ወደ ቤቱም መጣ፣ እንጀራ አምጡልኝ አለ፤ በፊቱም አቀረቡለት፣ በላም፡፡ ባሪያዎቹም፡- ይኽ ያደረግኸው ነገር ምንድር ነው? በሕይወት ሳለ ስለ ሕፃኑ ጾምህና አለቀስህ፤ ከሞተ በኋላ ግን ተነሥተህ እንጀራ በላህ አሉት፡፡ እርሱም፡- ሕፃኑ ሕያው ሳለ እግዚአብሔርም ይምረኝ፣ ሕፃኑም በሕይወት ይኖር እንደሆነ ማን ያውቃል? ብዬ ጾምሁ፤ አለቀስሁም፡፡ አሁን ግን ሞቶአል፤ የምጾመው ስለምንድር ነው? በውኑ  እንግዲህ እመልሰው ዘንድ ይቻለኛልን?  እኔ ወደ እርሱ እሔዳለሁ እንጂ  እርሱ ወደ እኔ አይመለስም አለ፡፡» /2ሳሙ 12÷15-23/፡፡ በዚህ ታሪክ ውስጥ ንጉሡ ዳዊት ልጁን ምን ያህል ይወደው እንደነበር፤ ከዙፋኑ ወርዶ ልብሰ መንግሥቱን አውልቆ፤ ማቅ ለብሶ አመድ ነስነሶ በጾምና በጸሎት እንደ ተጋደለ እንመለከታለን፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ከሞተ በኋላ በሰማይ የሚደረገውን ስለሚያውቅ «እኔ ወደ እርሱ እሔዳለሁ እንጂ እርሱ ወደ እኔ አይመጣም» በማለት በሰማይ ቤት ያለውን ጽኑ እምነት፤ ሞተ ማለትም ወደ እግዚአብሔር ሔደ ማለት እንጂ ሌላ ማለት ስላልሆነ ወደ ቤተ እግዚአብሔር ሔዶ ሰግዶ፤ እግዚአብሔርንም አመስግኖ እንደተመለሰ ይነግረናል፡፡

በመጽሐፈ ኢዮብ የተጻፈውን ስንመለከት ደግሞ በሐዘን ጊዜ እግዚአብሔርን እንዴት ማስደሰት እንደሚቻል እንረዳለን፡፡ ኢዮብ በአንድ ቀን ዐሥር ልጆቹ ሞተውበታል፤ በዚያው ቀንም ሊቆጠር የማይችል ሀብትና ንብረቱን አጥቷል፤ እርሱ ግን «እግዚአብሔር ሰጠ እግዚአብሔር ነሣ» አለ እንጂ አላማረረም፤ ሐዘኑንም በቅጡና በሥርዓቱ ተወጥቶታል፡፡ በዚህ ምድር ያለን ሰዎች ለሰው የማይቀረው ሞት አንዱ ቤተሰባችን ሲጠራው ከእኛ መካከልም በሞት ሲወሰድ ተመልክተን ይሆናል፡፡ እንደ ኢዮብ ግን ዐሥር ልጆቹ በአንድ ቅጽበት ያጣ ሰው የለም፡፡ በዚህም ከእግዚአብሔር እጥፍ ድርብ ዋጋ አገኘበት እንጂ አልተጎዳበትም፡፡ እንዲያውም ከቀደሙት የበለጡ ልጆች፣ ከቀድሞው ዕጥፍ ድርብ የሆነ ሀብት ተሰጥቶት፤ እንደተረገመ የቆጠሩት ሰዎች ሁሉ አፈሩ፤ እርሱ ግን በማጣቱም በማግኘቱም ጊዜ፤ በሐዘኑም በደስታውም ጊዜ እግዚአብሔርን ደስ አሰኘው፤ ተባረከበትም፡፡ ታዲያ የሕይወታችን እውነታ እንዲህ ሆኖ ሳለ አንዳንዶቻችን ያለ መጠን የምናዝነው፣ የምንፈተነው እና የምንጨነቀው ለምንድን ነው ? እንደ ኢዮብ እንደ ዳዊት ለመሆንስ ለምን ተሳነን ? ብለን ልንጠይቅ እንችላለን፤ ተገቢም ነው፡፡

የዚህን መልስ በአግባቡ ከተረዳን እኛም እንደ ሌሎቹ ብርቱዎች የማንሆንበት ምክንያት አይኖረንም፡፡ ለጥያቄያችን መልስ የሚሆነውንም ቅዱስ መጽሐፍ ስለመዘገበልን ከዚህ እንደሚከተለው እንመለከታለን፡፡

«ድንኳን የሚሆነው ምድራዊ መኖሪያችን ቢፈረስ፣ በሰማይ ያለ በእጅ ያልተሠራ የዘለዓለም ቤት የሚሆን ከእግዚአብሔር የተሠራ ሕንፃ እንዳለን እናውቃለንና፡፡ በዚህ ውስጥ በእውነት እንቃትታለንና፣ ከሰማይም የሚሆነውን መኖሪያችንን እንድንለብስ እንናፍቃለንና ለብሰን ራቁታችንን አንገኝም፡፡ በእውነትም የሚሞተው በሕይወት ይዋጥ ዘንድ ልንለብስ እንጂ ልንገፈፍ የማንወድ ስለሆነ፣ በድንኳኑ ያለን እኛ ከብዶን እንቃትታለን፡፡ ነገር ግን ለዚሁ የሠራን እግዚአብሔር ነው፣ እርሱም የመንፈሱን መያዣ ሰጠን፡፡» /2ቆሮ 5÷1-5/ በዚህ ጥቅስ ውስጥ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እጅግ እምቅ የሆኑ መሠረታዊ ነገሮችን አስቀምጦልናል፡፡እነዚህን በአግባቡ ከተረዳን ብዙ ጥያቄዎቻችን በአግባቡ ይመለሳሉ፡፡ ስለዚህ ፍሬ አሳቦችን በቅደም ተከተል እንመለከታቸዋለን፡፡ ለዚህ ጽሑፍ በሦስት ብቻ ከፍለን እንመለከታቸዋለን፡፡

ይቆየን
ምንጭ፡ሐመር ኅዳር 2003 ዓ.ም

አይቴ ብሔሩ ለግእዝ?

 

ግእዝ የማን ቋንቋ ነው? የካም ወይስ የሴም ቋንቋ የሚለው የብዙዎች ምሁራን ጥናት እና ጥያቄ እየሆነ መጥቷል፡፡ ግእዝን የሴም የሚያደርጉት የሶቢየት ምሁራን ኤቢ ዶጎልስኪ /A.B. Dogopolsky/ እና ኢጎር ዲያኮኖፍት /Igor Diaknoft/ ግእዝ የደቡብ ሴማዊ ልሳን ሳይሆን በዐረብ ምድር የመጀመሪያዎቹ የአፍሪካውያን ወይም የኩሻውያን ቋንቋ ነው ይላሉ፡፡

 

የዚህን ወገን ሐሳብ የሚጋሩት ደግሞ ቸክ አንተ ዲዮፕ /Cheik Anta Diop1919/ «ተርሰሃሌ» ጥበቡ፣ «አቤንጃ»፣ ኃይሉ ሀብቱ /1987/፣ አስረስ የኔሰው፣ ሺናይደር /1976/ እና አየለ በክሪ/1997/ ወዘተ ናቸው፡፡ ለዚህ ከሚጠቀሱት ምክንያቶች ዋና ዋናዎቹ ከአፍሮ እስያ ቋንቋዎች ብዙዎቹ የሚገኙት በኢትዮጵያ ነው የሚል ሲሆን በተጨማሪም በጣም ብዙ ቋንቋዎች በተለያዩ ቡድኖች በተቀራረበ እና በተወሰነ መልከዓ ምድር ስለሚነገሩ ነው፡፡

 

መርቶኔን /A.Murtonen/ ግእዝን ሴማዊ /ከኢትዮጵያ የወጣ/ ቋንቋ ነው የሚል አቋም አላቸው፡፡ ሊኦኔል ቤኤንደርም በተመሳሳይ ሁኔታ፡፡ ከዚህም አልፈው ግእዝን የአዳም ቋንቋ፤ የመላዕክት ቋንቋ የሚሉት አልጠፋም፡፡ ምንም እንኳን የካም ወይም የሴም ብለው ቢከፍሉትም፡፡ ተጠቃሾቹም ሲዲ ጳውሎስና አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ናቸው፡፡

 

«ሴማዊ ነው»፡፡ የሚለውን ሐሳብ ቢቀበሉትም የግእዝ ተናጋሪዎቹ እነማን እንደነበሩ አላውቅም የሚሉት ጌታቸው ኃይሌ ናቸው፡፡

 

በአንጻሩ ካም ወይም ሴም የሚለውን ቃል ከቋንቋ ጋር በማገናኘት የተጠቀመበት የጀርመን መልእክተኛ ጆህን ሊዊድግከፈ /Johunn Luowigkapf1810-1881/ ነው፡፡ ከርል ፍሬድሪክ ሌፐሲየስ /Karl Freidrich Lepsius/ ካምን ሴማዊ አይደለም ይላል፡፡ ከቋንቋ ጥናት በመነሳት ነው ይህን ሊል የቻለው፡፡ ይሁን እንጂ በአሁኑ ሰዓት ያለው የሥነ ልሳን ጥናት ከሐረገ ዘር ይልቅ መልክዐ ምድራዊ በመሆኑ የካምጠሴም ቋንቋ መባሉ ቀርቶ በአፍሮ እስያነት ውስጥ በአጠቃላይ የሚታይ ነው ይላል ዮሴፍ ግሪን በርገ /Joseph Green berg/፡፡ የዮሴፍ ግሪን በርገ /Joseph Green berg/ ሐሳብ የዚህን ጽሑፍ አቅራቢ ሐሳብ የተስማማ ነው፡፡

 

የዚህ ጽሑፍ አዘጋጅ ካለው ግንዛቤ የተነሣ የኢትዮጵያን ቋንቋ ግእዝን አፍሪካዊ የኢትዮጵያ ልሳን ውልደቱን እና እድገቱን ኢትዮጵያ አድርጎ በዘመነ ባቢሎን ሊነገር የሚችል ዓለም ዓቀፋዊና ጥንታዊ ልሳን ነው ብሎ ያምናል፡፡ የግእዝ የመጀመሪያ ጽሑፍ በ500 ቅ.ል.ክ የተጻፈ ሲሆን በአናባቢ መጻፍ የተጀመረው ግን በ4ኛው መቶ ዓ.ም ነው፡፡ ይህንንም በተከታይዮች አርእስተ ነገር ላይ ለማሳየት እንሞክራለን፡፡

የግእዝ ቋንቋ ፡ –

ሀ. የጽሕፈት ዘዴ አቡጊዳ
ለ. የጽሕፈት አቅጣጫ ከግራ ወደ ቀኝ አግድም /ከሳባ የሚለይበት ነው/
ሐ. እያንዳንዱ ፊደል በአናባቢ የተገለጸ እና አናባቢ የሌለው ሆኖ ሊጻፍ የሚችል ዓለማቀፋዊና ጥንታዊ ልሳን ነው ብሎ ያምናል፡፡
   

3 የግእዝ ቋንቋ ፊደላትና ትርጉም፡-
    

የግእዝ ቋንቋ ፊደላት የራሳቸው መለያ ትርጉም ሥዕላዊ መገለጫ ያላቸውና ከጥንት ጀምሮ ከጥቅም ላይ የዋሉ መሆናቸውን ያስረዳሉ፡፡ የግእዝ ቋንቋ መሠረታዊ ድምጾችን ሳይለቅ ከዘመን ዘመን በሚደረገው የሥነ ጽሕፈት ልውጠትም አዳዲስ ፊደላትን ለመፍጠር ያስቻሉ ፊደላትን ይዟል፡፡ እነዚህ ፊደላትም ለአፍሪካ እንደመሠረትነት ያገለገሉ ከመሆናቸውም በላይ ለአሁኑ የሥነ ጽሑፍ ሀብታችን መሠረቶች ናቸው፡፡ ፊደላቱ በአናባቢ ተዋሕደው ቃላትን ሊወልዱ ቋንቋን ሊያበለጽጉ ችለዋል፡፡ የራሳቸው የሆነ ቅርጽ እና ፍቺም ያልተለያቸው ናቸው፡፡

ነዛሪ የጉሮሮ እግድ – አ – አሌፍ አልፍ አብ
ነዛሪ የከናፍር ፈንጂ – በ – ቤት ባዕል
ነዛሪ የትናጋ ፈንጂ – ገ – ጋሜል ገምል
ነዛሪ የጥርስ ፈንጂ – ደ – ዳሌጥ ዳ/ን/ልት
ነዛሪ የጉሮሮ ፍትግ – ሀ – ሆይ ሆይ ሀወይ
 
የከናፍር ትናጋ ደኃራይ – ወ – ዋው ዋዌ ዋሕድ
ነዛሪ የጥርስ ፍትግ – ዘ – ዘይ ዛይ
ኢነዛሪ የማንቁርት ፍትግ – ሐ – ሔት ሐወት ሕያው ሕይወት
ነዛሪ የትናጋ ፍትግ – ኀ – ኀርም ኄር
ኅዩል ኢነዛሪ የጥርስ ፈንጂ – ጠ – ጤት ጠይት ጠቢብ
ቅሩብ የከናፍር ትናጋ ደኃራይ – የ – ዮድ የማን
ኢነዛሪ የትናጋ ፈንጂ – ከ – ከፍ ከሃሊ
ጎናዊ – ለ – ላሜድ ለዊ ልዑል
ከናፍራዊ ወአንፋዊ – መ – ሜም ማይ ምዑዝ
የጥርስ ወአንፋዊ – ነ – ኖን ነሐስ ንጉሥ
ኢነዛሪ የጥርስ ፍትግ – ሠ – ሣምኬት ሣውት
ነዛሪ የማንቁርት ፍትግ – ዐ – ዐይን ዐቢይ
ኢነዛሪ የከንፈር ፈንጂ – ፈ – ፈፍ ፈቁር
ኀዩል ኢነዛሪ የጥርስ ፍትግ  – ጸ – ጻዴ ጸደቅ ጻድቅ
ፀ – ፀጰ

ኀዩል ኢነዛሪ የትናጋ ፈንጂ – ቀ – ቆፍ ቅዱስ
የድድ ተርገብጋቢ – ረ – ሬስ ራእስ
ኀዩል ኢነዛሪ የጥርስ ፈንጂ – ሰ – ሳን ስቡሕ
ኢነዛሪ የጥርስ ፈንጂ – ተ – ታው ተዊ ትጉህ
ነዛሪ የከንፈር ፈንጂ – ጰ – ጰይት ጴት
ኢነዛሪ የከንፈር ፈንጂ – ፐ – ፐ ፌ
    

ከላይ እንዳየነው የግእዝ ፊደላት ቢሆኑም ቋንቋ ምንጊዜም በለውጥ ስለሚሄድ ስለሚወልድ እና ስለሚረባ ሌሎች ልዩ ልዩ ድምጾችን እንደፈጠረ እንረዳለን፡፡ ለዚህም የ «ሰ»ን ድምጽ የመሰለ «ሠ» የ«በ»ን ድምጽ የመሰለ ፐ እና ጰ ሌሎችም በየዘመናቱ ሲፈጠሩ ከመግባቢያነት አልፈው በሥነ ጽሑፍ ደረጃ ታሪክን አስቀምጠዋል፡፡ በተለይም ዛሬ የማይነገሩ «ደ»ን የመሰለ ደ፣ ዘ የጠበቁ.. ወዘተ በየዘመናቱ እንደነበሩ የሥነ ልሳን ጥናቶች ያስረዳሉ፡፡ የግእዝ ፊደላት ትርጉም እና ሃይማኖታዊ ምስጢ ብቻ ሳይሆን ሥዕላዊ መገለጫዎች እንደነበሩት መዛግብት ያስረዳሉ፡፡ ፊደላቱም በሥዕልነት ብቻ ሳይሆን መሠረተ አኀዝ መሆናቸውንም እንመለከታለን፡፡ ምሳሌ አ አልፋ ሲባል የበሬ ቀንድ እንደሚመስል አልፋም በላሕም ተተክቶ በመ.ቅ ይገኛል፡፡ ምሳሌ፡- አባግዐኒ ወኩሎ አልሕምተ ሲል መዝ. 8.7 በዕብራይስጥ ጾጊ ወአላፊም ይላል /ኪ.ክ/፡፡ ጥናት እንደሚያመለክተውም ላሕም ልሔም /እንጀራ/ ከእብራይስጥ ቃል የተወሰደ እና ከአላፊም ቦታ የገባ መሆኑን የሚጠቁም የሥነ ጹሑፍ መረጃ ይገኛል፡፡ ጋሜል ገመል /አባ ገሪማ የሚገኝ ወንጌል እንደ ሚያስረዳው/፡፡ ከፍ የሚለው ቃልም በትንቢተ ሕዝቅኤል ምዕራፍ 1.7 እግሮቻቸው ከፍ ያሉ እግሮች ነበሩ የእግራቸውም ኮቴ እንደ ጥጃ ኮቴ ነበር ሲል ጥጃ ከፍ መሆኑን ያመለክታል፡፡ በተጨማሪም ዮድ በቀኝ እጅ፣ ነ በእባብ፣ መ በውኀ ሞገድ፣ ዐ በዐይን፣ ፈ በአፍ፣ ረ በራስ፣ ተ በመስቀል፣ በ በቤት… መመሰላቸው ፈጣሪ ለሰው ልጅ ራሱን በሚታይ ነገር ከመግለጽም በላይ የፊደላትን ትርጉም ብቻ ሳይሆን ነገረ ድኅነትንም በመስቀል ምልክት በታው/ተ መደምደሙን ያሳየናል፡፡ በግእዝ ፊደላት የድምጽ ለውጥን በማድረጋቸዉ ከጊዜ ብዛት ትርጉማቸዉ ሲዛባ እና ሥዕላዊ መገለጫቸው በተወሰነ ደረጃ ጎድሎ የዘፈቀደ ትርጉም ሊሰጣቸዉ ይችላል፡፡ ምሳሌ «ጥ»ሽ «ት» ወይም «ት»ሽ «ጥ» በመለወጥ ትርጉም ሊሰጥ ይችላል፡፡ በአንጻሩም በቋንቋው የድምጽ ትርጉም ሊሠራላቸው እና ከአንድ በላይ የተለያዩ ትርጉም ሊኖራቸዉ መቻሉ የማይቀር ነው፡፡ የፊደላቱ መለዋወጥ ግን ትርጉም የሚያበላሽ ምስጢር የሚያፋልስ መሆኑ የተረዳ ነው፡፡ ይኽንኑ ለመግለጽ ሊቁ አለቃ ኪዳነ ወልድ «መዝገብ ፊደል» በተባለው መጽሐፋቸው እንዲህ ብለዋል፡፡

እንዳገኙ መጣፍ በድፍረት በመላ
የቋንቋ ደረመን የመጽሐፍ ቢስ ገላ
ንባብ የሚያሳክክ ምስጢር የሚቆምጥ
መልክአ ትርጓሜ የሚለዋውጥ፡፡
   

ይህን ማለታቸውም የፊደል ቁጥር ማጉደሉ፣ ምስጢር ማበላሸቱ ሥርዓተ ልሳን ማፋለሱ አንድና ብዙ ሩቅና ቅርብ ሴትና ወንድ አለመጠንቀቁ ጸያፍነቱና ግዴለሽነትን በማምጣቱ ነው፡፡ ለዚህም መፍትሔ ይሆን ዘንድ ታላቁ ሊቅ መልአከ ብርሃን አድማስ ጀምበሬ በመልእክታቸው ሊቃውንቱ ተስማምተው ጉባኤ ሠርተው ሊወያዩበት ይገባል ብለዋል፡፡ የፊደላቱ ምንነትና ምስጢር ሊጠፋ የቻለው እንደነ መልአከ ብርሃን አባባል የጽሕፈት ትምህርት ቤት ባህልና ትውፊት መረሳቱና ጸሓፍያን ለፊደላት ትርጉም ሳይጨነቁ ለቅርጽ ማማር ብቻ ትኩረት መስጠታቸው ነውና ይኽንኑ ሥርዓት ባለቅኔዎችም ባለማስተዋል ለቤት መምቻ ውበት መጠቀማቸው ነው፡፡

 

የግእዝ ፊደላት ለአኀዝ መሠረት ናቸው ስንል የምናነሳው ዝምድናቸውን ሲሆን ለምሳሌ የግእዝ 6 7 ቁጥሮች «-» ምልክት ሳይኖራቸዉ ይገኛሉ፡፡

የግእዝ ቁጥሮች መሠረታቸው ፊደል ነው፡፡ ስንል እንደ ፊደሎችም ቁጥሮች ከዘመን ዘመን ቅርጻቸዉን መልካቸውን ሲለዋውጡ እና የአሁኑን መልክ ሲይዙ ይታያሉ፡፡ በአጠቃላይም ቋንቋው የራሱ የሆነ ሥርዓተ ነጥብ የሥነ ጸሑፍ አካሄድ የምንባብ አጀማመር እንዳለው ይታወቃል፡፡

ሁሉን መርምሩ መልካሙን ያዙ

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በአምልኮተ እግዚአብሔር ከሦስት ሺሕ ዘመን ላላነሰ የቆየውን የኢትዮጵያውያንን የሃይማኖት ሕይወት ስትመራና አሁንም በመምራት ላይ ያለች ከመሆኑ አንጻር ዘርፈ ብዙ የጥናትና ምርምር ሥራ እንዲደረግባት የምትጋብዝ ናት፡፡
ቤተክርስቲያናችን በታሪኳ ከፍተኛ የሥነ-ሕንፃና ሥነ-ጽሑፍ፣ የፍልስፍና፣ የሕግና የአስተዳደር፣ የዘመን አቆጣጠር፣ ከፍተኛ የማኅበራዊ ግንኙነትና የባህል መሠረት ናት፡፡

ቤተክርስቲያናችን በቅዱሳት መጻሕፍት ትምህርትና ቀኖና፣ በትምህርተ ሃይማኖት፣ በሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን፣ በትውፊትና ታሪክ በኩልም ለጥናትና ምርምር የሚጋብዝ ከፍተኛ ክምችት አላት፡፡ የዚህ ክምችት ኃይልም ቤተክርስቲያኒቱን የሀገሪቱ የጥናትና ምርምር ዒላማ አድርጓታል፡፡ በሀገራችን ያሉ የኢትዮጵያ ጥናት ላይ የሚያተኩሩ ተቋማት የምርምር ትኩረት በአብዛኛው በቤተ ክርስቲያናችንና ባሏት ዘርፈ ብዙ ቅርሶች ላይ እንዲሆንም አስገድዷል፡፡

በተለይም ሀገራችንና ቤተክርስቲያናችን በታሪክ ዘመን ውስጥ ብዙ ወርቃማ ዘመናትን ቢያሳልፉም፤ በዮዲት፣ በግራኝ፣ በዘመነ መሳፍንት፣ በጣሊያንና በእርስ በእርስ ጦርነቶች የተፈጠረው ምስቅልቅል በቤተ ክርስቲያናችን መንፈሳዊና ቁሳዊ ሀብት ቅብብሎሽ ላይ የፈጠረው ክፍተት ለበርካታ ሊቃውንት የጥናት ጉዳዮች ምንጭ ነው፡፡ በሃይማኖት ትምህርት በኩልም የአይሁድ፣ የካቶሊካውያን፣ የቅባትና የጸጋ ሌሎች የሥጋ ፍልስፍናዎችና የሟርትና ጥንቆላ ሥራዎች በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ዙሪያና ውስጥ ሆነው እውነተኛውን አስተምህሮ ሲፈታተኑት በመኖራቸው እነርሱን በመከላከል በኩል የተደረጉ ተጋድሎዎችና ያረፉ ተጽዕኖዎች ለጥናት የሚጋብዙ አንኳር ጉዳዮች ናቸው፡፡

ይሁን እንጂ የጥናትና ምርምር ሥራን ዘመናዊ ከማድረግና የራሳችንን ታሪክ ባህልና አጠቃላይ ገጽታ ከማጥናት አንጻር ሚና የነበራቸው ኢትዮጵያውያን ያልሆኑ፣ በሃይማኖትም ኦርቶዶክሳውያን ያልሆኑ ወገኖች ነበሩ፡፡ አንዳንዶቹ ተመራማሪዎች በጥናቶቻቸው በሚሰጧቸው ድምዳሜዎች ኢትዮጵያውያን ጥያቄ እንዲያነሡባቸው፤ በጥርጣሬም እንዲታዩ አድርጓል፡፡ ከኢትዮጵያውያን ውጪ የሚደረጉ ጥናቶች ላይ ሁሉ ጥርጣሬ ማሳረፍ አግባብ ባይሆንም የኢትዮጵያውያን የጥናት ተሳትፎ በሚፈለገው ልክ ባለመሆኑ የጥናትና ምርምር ሥራዎች በኢትዮጵያ ሊቃውንት ትኩረት ማግኘት እንዳለባቸው ግን ሁሉንም ያግባባል፡፡
 
መጽሐፍ ሁሉን መርምሩ መልካሙን ያዙ እንዳለ በሊቃውንቱ መካከል በአንዳንድ ጉዳዮች ላይ የገለጻ ወይም የሐሳብ ልዩነት ሲፈጠር ያለ ግጭት ለመፍታት አንድነትንም ለማጽናት በጥናትና ምርምር ሥነ-ምግ ባር ላይ ተመሥርተው የሚዘጋጁ ጥናትና ምርምሮች ፍቱን መድኃኒቶች ናቸው፡፡ በተለይ በዚህ ዘመን በራሳቸው ፈቃድና በቅጥረኝነት ተነሣሥተው የቤተክርስቲያናችንን አዋልድ መጻሕፍት፣ ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን፣ ታሪክና ትውፊት ለሚያብጠለጥሉ ከዚያም በግርግር ቤተክርስቲያንን አንድነቷን ለማናጋት ለሚጥሩ የተሐድሶ መናፍቃን ልጓም ያበጃል፡፡ ጠንካራ የጥናትና ምርምር ተቋማት ለቤተ ክርስቲያናችን የሊቃውንት ጉባኤም ለቅዱስ ሲኖዶስ አገልግሎት ግብዓት ከማቅረብ አንጻርም ትልቅ ሚና ይኖራቸዋል፡፡ በመሆኑም ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን፣ ዘመናዊ ትምህርትንም የተከታተሉ ክርስቲያን ምሁራን ላይ የተመሠረቱ የምርምር ተቋማት መመሥረት እንዳለባቸው ማኅበራችን የጸና እምነት አለው፡፡ ለዚህም የሚመለከታቸው አካላት ጥናትና ምርምር ጊዜው የሚጠይቀውና የቤተ ክርስቲ ያናችንን አንድነት በሀገራችንም ውስጥ ያላትን ግንባር ቀደም ሚና መጫወት እንድትችል አዎንታዊ ሚና እንዳለው ተገንዝበው አስፈላጊውን ሁሉ ሊፈጽሙ ይገባል እንላለን፡፡

የቤተክርስቲያን አስተዳደርም የጥናትና ምርምር ተቋማትን መሥርተው ለመንቀሳቀስ ለሚፈልጉ የክር ስቲያን ወገኖች ምቹ ሁኔታ መፍጠርና እነርሱን የሚያስተናግድ አሠራርና መዋቅራዊ ሁኔታ ማመቻቸት ይገባዋል፡፡ ጠቅላይ ቤተ ክህነትና አህጉረ ስብከቶች ጥናቶች እየተዘጋጁ የሚቀርቡባቸው ጉባኤዎችን በተወሰኑ ጊዜዎች ሊያዘጋጁ ይገባል፡፡ ጥናትና ምርምር የራሱን የአስተዳደሩን የመፈጸም አቅም የበለጠ የሚያጠናክር በመሆኑ ተግባሩን መደግፍ ብልህነት ነው፡፡ በጥንቃቄና በብዙ ሊቃውንት የተዘጋጁ የጥናት ውጤቶችም ጥቅም ላይ እንዲውሉ መጣር አለበት፡፡ ጥናትና ምርምር ተቋምን መመሥረት ከፍተኛ ጥረት የሚጠይቅ መሆኑ የሚታወቅ ሲሆን ቢያንስ ለጥናትና ምርምር ተግባር የሚያግዙ ቤተ መጻሕፍት፣ ቤተ መዛግብትና ሙዚየሞችን በየደረጃው ማደራጀትና ማስፋፋት ለነገ የሚባል ተግባር አይደለም፡፡

ሊቃውንተ ቤተክርስቲያንና ሌሎች ክርስቲያን ምሁራን ይህንን ተግባር ለመደገፍ ያሉበት የዕውቀት ደረጃና ሙያ ግድ ይላቸዋል፡፡ ሊቃውንት ያለጥናትና ምርምር ተቋም ዕውቀታቸውን ማዳበር፣ ዕውቀታቸውን ማካፈል አዳዲስ መረጃዎችንም መስጠት አይችሉም፡፡ በመሆኑም ጥናትና ምርምር ተቋማት እንዲስፋፉ ግፊት ከማድረግ ጀምሮ የሚመሠረቱበትን ብልሀት፣ ከተመሠረቱም በኋላ የሚጠናከሩበትን በዘላቂነት የሚሠሩበትን መላ በመዘየድ፣ በጥናትና ምርምር ሥራዎች በመሳተፍ የጥናትና ምርምር ሥራዎችንም በማስተዋወቅ ሰፊ አስተዋጽኦ ሊያደርጉ ይገባል እንላለን፡፡

በአጠቃላይ ሕዝበ ክርስቲያኑ የጥናትና ምርምር ተቋማትን ከመመሥረት ጀምሮ እስከ ማጠናከር ድረስ በሚደረገው ርብርብ በገንዘባቸው፣ በጉልበታቸው፣ በዕውቀታቸውና አስፈላጊውን አስተዋጽኦ ማድረግ ይገ ባቸዋል፡፡ ቤተክርስቲያናችን ካላት ክብር፣ ታሪክና ቅርስ አንጻር አንድ እንኳን ጠንካራ የምርምር ተቋም ማጣቷ ቆጭቶን አስፈላጊውን ሁሉ ልንፈጽም ይገባል፡፡ ቤተክርስቲያናችን አሉባት የምንላቸውን ችግሮች ሁሉ ለመፍታት ጥናትና ምርምር ያለውን ወሳኝ ሚና በመረዳት የክርስቲያን ወገን ሁሉ ሊረባረብ ይገባዋል፡፡ ቅርሶቻችን እየጠፉ፣ መጻሕፍቱ እየተበረዙ፣ እየተመዘበሩ፣ በአስተዳደራዊ ችግሮች እየታመስን ባለንበት ወቅት፤ የኢኮኖሚ፣ የማኅበራዊ የአካባቢ ጥበቃ ጉዳዮች የቤተ ክርስቲያን አስትዋጽኦ ተፈላጊ በሆነበት በዚህ ጊዜ የጠራና የነጠረ ሐሳብ ይዘን መራመድ ካልቻልን የሚያ ጋጥመን ፈተና ቀላል አይሆንም፡፡ ሰንበት ትምህርት ቤቶችና ማኅበራትም ባሉበት ደረጃ ከቤተ መጻሕፍት ጀምሮ እስከ ከፍተኛ የምርምር ተቋም ድረስ በቤተ ክርስቲያናችን የማስፋፋት ርእይ ሊኖራቸው ይገባል፡፡

ማኅበራችን ማኅበረ ቅዱሳንም ይህንን ወሳኝ ተግባር ከመፈጸም አንጻር አርአያ ለመሆን ጥረት እያ ደረገ ይገኛል፡፡ ለሚያደርገው ጥረትም ማሳያ የሚሆን የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ጥናት መጽሔት /Journal/ በቅርቡ ማውጣቱ የዚህን ተግባር ወሳኝነት ለማጉላት ነው፡፡ በመሆኑም ሁሉም የሚመለከታቸው ወገኖች በየደረጃው የጥናትና ምርምር ተቋማትን ለጥናትና ምርምር መመሥረት አስተዋጸኦ የሚያደርጉ ሌሎች የመረጃ ማእከላትን ማቋቋም ይገባቸዋል እንላለን፡፡

Muyakard.jpg

የምህንድስና አገልግሎት ለቤተክርስቲያን ዕድገት

  ”የምህንድስና አገልግሎት ለቤተክርስቲያን ዕድገት”
 
በሚል መሪ ቃል መርሐ ግብር ተዘጋጅቷል፡፡ ታኅሳስ 17 ቀን 2003 ዓ.ም ከቀኑ 7፡30—11፡30 በማኅበረ ቅዱሳን ሕንጻ ላይ አባ ጊዮርጊስ ዘጋስጫ አዳራሽ፡፡

 

Muyakard.jpg
አዘጋጅ፡- በኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ/በሰንበት ት/ቤቶች ማ/መምሪያ ማኅበረ ቅዱሳን በሙያ አገልግሎትና አቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍል::

ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬም

ዲ/ን ቀለመወርቅ ሚደቅሳ

በኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን የረጅም ዘመን ሐዋርያዊ ጉዞ ላይ በጎ ተፅዕኖ ካላቸው የአራተኛው መ/ክ/ዘመን አባቶች መካከል አንዱ ሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬም ነው፡፡ይህ አባት ምንም እንኳን በቋንቋ ውሱንነትና በቦታ ርቀት በርካቶች ሥራዎቹና ጽሑፎቹ የታወቁለት ባይሆንም ሕይወቱን በብሕትውና የመራ የትርጓሜ መጻሕፍትን ፣የቅኔ፣ የግጥምና የወግ ጽሑፍ በማዘጋጀት የኖረ ባለ በጎ ገድል አባት ነው፡፡

የቅዱስ ኤፍሬምን ሥራዎች በማሰባሰብ በመጽሐፍ መልክ ካወጡ ሰዎች አንዱ የሆነው (ዶ/ር ሰባስትያን ብሮክ) ’the Luminous Eye’’ በሚል ርዕስ ካዘጋጀው መጻሕፍ  ውስጥ ጎላ ጎላ ያሉትን ትምህርቶች እየተረጎምን ልናቀርብ ወደድን፡፡ ይህም ክፍል አንድ መግቢያ ሆኖ የቅዱስ ኤፍሬምን ሕይወትና ሥራዎች በአጭሩ የሚቀርብበት ነው፡፡

የቅዱስ ኤፍሬም ሕይወቱ

የቅዱስ ኤፍሬም ሀገረ ውላዱ ከዋክብትን ከሚያመልኩ ሰዎች መካከል ነው፡፡ አባቱም ክርስትናን የሚጠላ ካህነ ጣዖት ነበር፡፡ አንዳንድ ምንጮች ከቅዱስ ኤፍሬም ሕይወት በመነሳት ወላጆቹ ክርስቲያኖች እንደነበሩ ዘግበዋል፡፡ የሐምሌ አስራ አምስት ስንክሳር ግን የአባቱን ካህነ ጣዖትነት ያረጋግጣል፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም የተወለደው  በ306 ዓ.ም ገደማ “በሜሶፖታሚያ” ውስጥ በምትገኝ “ንጽቢን” እንደሆነ ይታመናል።(ንጽቢን   በደቡባዊ ቱርክ እና በምዕራባዊ ሶርያ መካከል የምትገኝ ቦታ ናት፡፡) ይህቺም ቦታ ከ318ቱ ሊቃውንት አንዱ የነበረው የቅዱስ ያዕቆብ ሀገረ ሰብከቱ የነበረች ናት፡፡

ይህንን ታላቅ አባታችንን የእግዚአብሔር መንፈስ አመላክቶት ወደ ቅዱስ ያዕቆብ ሄዶ ትምህርተ ክርስትናን ተምሮ የተጠመቀ ሲሆን ከወላጆቹ ጋር የኖረው እስከ አሥር ዓመቱ ብቻ ነው፡፡ በትምህርተ ክርስትና አምኖ ከተጠመቀ በኋላ ግን በቅዱስ ያዕቆብ ዘንድ በብሕትውና ተወስኖ በመማርና በማስተማር በንጽቢን ለሚገኘው መንፈሳዊ ትምህርት ቤት ሓላፊ እስክመሆን ደርሶ ነበር፡፡

በ393 ዓ.ም የንጽቢን ከተማ  በወራሪዎች እጅ ስትወድቅ ቅዱስ ኤፍሬም ከሌሎች ክርስቲያኖች ጋር በመሆን የሮም ግዛት ወደነበረችው ኤዴሳ (ታናሽ እስያ፣ዑር) ተሰደደ፡፡ ይህቸ ቦታ ቅዱስ ኤፍሬም ከመናፍቃን ጋር የተጋደለባት፣ በቤተክርስቲያን ትምህርት ላይ ያላቸውን አብዛኞቹን የክህደት ትምህርቶች የሞገተባትና  መጻሕፍቱን ያዘጋጀባት ናት፡፡አብዛኛዎቹን ትምህርቶቹንና መጻሕፍቱን ያዘጋጀው በዚች በኤዴሳ በሚገኘው ትምህርት ቤት ነው፡፡

ቅዱስ ኤፍሬም ከመምህሩ ከቅዱስ ያዕቆብ ጋር በመሆን በአርዮስ ምክንያት በተካሄደው  የኒቅያው ጉባኤ    ( 325 ዓ.ም ) ላይ ተገኝቷል፡፡ በዚህም የአርዮስን ክህደትና ምክንያተ ውግዘት ተገንዝቧል፡፡

ከኒቅያ ጉባኤ መልስ መንፈሰ እግዚአብሔር በራዕይ በገለፀለት መሠረት ቅዱስ ኤፍሬም ከቅዱስ ባስልዮስ (ቁጥሩ ከ318ቱ ሊቃውንት ወገን ነው) ዘንድ ለመገናኘት ወደ ቂሣርያ ሄዷል፡፡ ቅዱስ ባስልዮስም የዲቁና ክህነት ሠጥቶ ከሀገረ ስብከቱ ከፍሎ እንዲያስተምር ወስኖ በእርሱ ዘንድ አኑሮታል፡፤ በዚያም ቦታ ብዙ ተአምራትን አድርጓል( መጻሕፍትንም ጽፏል፡፡

ቅዱስ ኤፍሬም በትውፊት እንደሚታወቀው ምንኩስናን በገቢር ገለጣት እንጂ ሥርዓተ ምንኩስናን መፈጸሙን በግልጽ የሚመለክት ማስረጃ አልተገኘም፡፡ እንዲያውም በሶርያውያን ክርስቲያኖች የሚዘወተረውን ራስን በአንድ ስፍራ ወስኖ በብሕትውናና በመምህርነት ቤተክርስቲያንን የማገልገል (Proto-monasticism) ሕይወት ይኖር እንደነበር ይታመናል፡፡ በትውፊት ቅዱስ ኤፍሬም ቅዱስ ባስልዮስን ለመጎብኘት ወደ ቀጰዶቅያ እንዲሁም አባ ቢሾይን ለመጎብኘት ወደ ግብጽ እንደተጓዘ የሚነገረውም ከዚህ ጋር በተያያዘ ነው፡፡

ፍጹም በሆነ ኦርቶዶክሳዊ ትምህርቱ ምሳሌ በሚሆነው ትምህርቱና የምናንኔ ሕይወቱ የሚታወቀው ቅዱስ ኤፍሬም ሐምሌ አስራ አምስት ቀን በ 370 ዓ.ም አርፏል፡፡በዚህ ሁሉ ትጋቱም ሶርያውያን ክርስቲያኖች ‹ጥዑመ ልሳን›፣ ‹መምህረ ዓለም›፣ ‹ዓምደ ቤተ ክርስቲያን› በማለት ይጠሩታል፣ያወድሱታል፣ያመሰግኑታል፡፡የቅዱስ አባታችን ረድኤትና በረከት ከሁላችን ጋር ይሁን፡፡ አሜን!

የቅዱስ ኤፍሬም ሥራዎች

ቅዱስ ኤፍሬም እንደሌሎች የ4ኛው  መ/ክ/ዘ አበው በርካታ ትምህርቶችንና መጻሕፍትን የጻፈና ያዘጋጃ አባት ነው፡፡ ይህንንም ስንክሳር እንዲህ ይገጸዋል፡፡

እጅግም ብዙ የሆኑ 14 ሺህ ድርሳናትንና ተግሳጻትን ደረሰ፤ ከእርሳቸውም ውስጥ አምላክን የወለደች የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም ውዳሴዋን ነው፡፡ ‹አቤቱ የጸጋህን ማዕበል ግታልኝ ‘ እስከሚል ድረስ ድርሳናትን ደርሶአል፡፡ (ስንክሳር ዘሐምሌ 15 ተመልከት)

በአሁኑ ዘመን የቅዱስ ኤፍሬም መጻሕፍትና ትምህርቶች እንደሌሎቹ የ4ኛው  መ/ክ/ዘ አበው ሥራዎች ጎልተው የታወቁ አይደሉም፡፡ ለዚህም ምክንያቶቹ ሁለት ናቸው፡፡

1. ቅዱስ ኤፍሬም አብዛኛዎቹን ትምህርቶችና መጻሕፍትን ያዘጋጀው በዘመኑ ብዙ ተጽእኖ በነበራቸው በግሪክ ወይም በላቲን ቋንቋዎች ሳይሆን በሱርስት በመሆኑ ነው፡፡ አንዳንድ ሊቃውንት ይህን እውነት እንደ መልካም ነገር ይጠቅሱታል፡፡ ወንጌል በግሪክ ከመጻፏ በፊት የተሰበከችው በሱርስት ነው( ጌታም ያስተማረው በዚሁ ቋንቋ ነው በማለት ይህም የሶርያ ክርስትና በግሪካዊው ፍልስፍና ያልተጠቃ (Little Hellenized) እንዲሆን ያደረገ ነው በማለት እንደመልካም ነገር ይጠቅሱታል። 

2. ቅዱስ ኤፍሬም ትምህርተ ክርስትናን ከሌሎች አበው ለየት ባለ መልኩ በጥበባዊ ስልት (በግጥም፣በቅኔ፣በደብዳቤ፣በጥያቄና መልስ) በማዘጋጀቱና አብዛኞቻችን በዚህ ስልት ጠንከር ያለ ትምህርተ ክርስትና ይገኛል ብለን ስላላመንን ወይም ዝንባሌው ስለሌለን ነው፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ በዚህ ዘመን በርካታ መጻሕፍት የቅዱስ ኤፍሬም ናቸው እየተባሉ ሲሰራጩ እናስተውላለን። አብዛኛዎች ግን የእርሱ አይደሉም ፤በተለይ የመጀመሪያ ጽሕፈተ ቋንቋቸው ግሪክ የሆኑት።ስለዚህ መጻሕፍቱን ከመጠቀማችን በፊት የቅዱስ ኤፍሬም ድርሰቶች መሆናቸውን ማወቅ ይገባል፡፡

የቅዱስ ኤፍሬም የጽሑፍ ሥራዎች

እነዚህን ጽሑፎች ጠቅለል አድርጎ በአራት መክፈል ይቻላል፦
1. ቀጥተኛ ትርጓሜያት፡- ይህ ክፍል ከመጽሐፍ ቅዱስ አንዱን መጽሐፍ በመውሰድ የተጻፉ ትርጓሜያትን የሚያጠቃልል ነው፡፡ ምሳሌ – የኦሪት ዘፍጥረት፣ የኦሪት ዘፀአትና የግብረ ሐዋርያት ትርጓሜያትን መጥቀስ ይቻላል፡፡
2. ጥበበባዊ (Artistic) ትምህርቶች (ትርጓሜያት)፦ በግጥም ወይም በሌላ ጥበባዊ መልክ የተጻፉ ትርጓሜያትን የሚያካትት ነው፡፡ ‹በእንተ ክርስቶስ› (በጥያቄና መልስ የቀረበው) ትምህርት ተጠቃሽ ነው፡፡ እንዲሁም ‹በነገረ ምጽአት ላይ ለፑከሊየስ የተጻፈው ደብዳቤም፡፡›
3. በቁጥር የተደረጉ ስብከቶች (Verse homilies)፦ አንድን ርዕስ በማንሳት የተሰጡ ስብከቶችን የምናገኝበት ክፍል ነው፡፡ ‹በእንተ እምነት› የተሰኘው ስብከቱ ተጠቃሽ ነው፡፡
4. የዜማ ወይም የቅዳሴ ድርሰቶች፡፡

ቅዱስ ኤፍሬምና የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን

የኢትዮጵያ ቤተክርስቲያን ያዘጋጀቻቸውን አብዛኛዎችን የትርጓሜ መጻሕፍት ያጠኑ ሊቃውንት መጻሕፍቱ የኤዴሳ መንፈሳዊ ትምህርት ቤት የትርጓሜ ስልትና የምስጢር ፤ የዘይቤ አንድነት እንደሚስተዋልባቸው ያስረዳሉ፡፡ ከዚያ ውጪ በውዳሴ ማርያምና በአንቀፀ ብርሃን መካከል ያለው የአንድነት ጉዳይ ከትርጓሜ መጻሕፍት ወደ ጸሎት መጻሕፍትም ሊራመድ እንደሚችል ያስገነዝባል፡፡ ለዚህ ሃሣብ መቋጫ የስርግው ሐብለ ሥላሴን ንግግር እናቅርብ፡-

‹ኤፍሬም (ሶርያዊ)› የሶርያ ተወላጅ እርሱ የደረሳቸው መጻሕፍት ወደ ግእዝ ብዙዎቹ ተመልሰዋል፡፡ በተለይ ውዳሴ ማርያም በየዕለቱ በሕዝበ ክርስቲያን የሚጸለይ ጸሎት ነው፡፡

በመጽሐፈ አክሱም እርሱና አባ ሕርያቆስ የተባለው ቅዳሴ ማርያም የደረሰው ወደ አክሱም መጥተው ማይ ከርዋህ በሚባል ስፍራ ተገናኝተው ኤፍሬም ያሬድን ውዳሴ ማርያምን ሕርያቆስን ደግሞ ቅዳሴዋን እንዳስተማረው በሰያፍ መንገድ ይገለጻል፡፡ እዚህ ላይ ዋናው ቁም ነገር ቅዱስ ያሬድ በስድ ንባብም ሆነ በግጥም መልክ የደረሳቸው ድርሰቶች የሶሪያ ቤተክርስቲያን ባህል የተከተሉ መሆናቸውና የሶርያ ቤተክርስቲያን ለኢትዮጵያ መንፈሳዊ እድገት ከፍ ያለ አስተዋጽዖ እንዳደረገች የሚያሳይ ነው፡፡ (አማርኛና የቤተ ክርስቲያን መዝገበ ቃላት ረቂቅ ኤፍሬም የሚለውን ተመልከት)፡፡

ይቆየን !

 

የማይቀበሩ መክሊቶች

   በዲ/ን ምትኩ አበራ

 

«ወደ ሌላ አገር የሚሔድ ሰው ባሮቹን ጠርቶ ያለውን ገንዘብ እንዲሰጣቸው እንዲሁ ይሆናልና፣ ለእያንዳንዱ እንደአቅሙ ለአንዱ አምስት መክሊት ለአንዱ ሁለት ለአንዱም አንድ ሰጠና ወዲያው ሔደ…» ማቴ 25÷14  ይህንን ታሪክ ማንሣታችን በወርኃ ዐቢይ ጾም በዕለተ ገብርሔር አንድም እየተባለ የሚተነተነውን ቃለ እግዚአብሔር ለማውረድ ተፈልጎ አይደለም፡፡

ጌታችን የተናገራቸው ሁለቱ ኃይለ ቃላት የሚያስደምሙ ስለሆኑ ነው «… እንዲሁ ይሆናልና” የሚለውና «ለእያንዳንዱ እንደአቅሙ» የሚሉት፡፡ ጌታችን እንዳለው እንዲሁ እንዳይሆንብን ዳሩ ግን እንዲሁ እንዲሆንልን ቅዱስ ፈቃዱን እየተማፀን ለእያንዳንዳችን እንደአቅማችን የተሰጡንን የማይቀበሩ መክሊቶች በአጭሩ እንመልከት፡፡

እንደ ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ሥርዓትና እምነታችን እኛ በአርባና በሰማንያ ቀናችን በጥምቀት ከቅድስት ቤተክርስቲያናችን የተወለድን ሁላችን፤ ባለጸጎች/የጸጋ ባለቤቶች፣ ነን « እንደተሰጠን ጸጋ ልዩ ልዩ ሥጦታ አለን» ሮሜ 12÷6 ነገር ግን አንዳንዶች የተሰጠንን ጸጋ ባለማወቅ፣ ሌሎቻችንም የያዝነው ጸጋ ስጦታ ሳይሆን በእኛ ጥበብ ያገኘነው እየመሰለን ወዘተ… እንኳንስ ልናተርፍባቸው ቀርቶ ቀብረናቸው፤ የጸጋውን ባለቤት «አንተ ካልዘራህበት የምታጭድ፡፡ ካልበተንህበትም የምትሰበስብ ጨካኝ ሰው መሆንህን አውቃለሁና ፈራሁህ፣ ሔጄም መክሊትህን በምድር ቀበርኩት እነሆ መክሊትህ» ለማለት የተዘጋጀን ይመስላል ማቴ 25÷24፡፡

እንድናተርፍባቸው ከተሰጡንና የማይቀበሩ ከሚባሉት መክሊቶቻችን መካከል ጥቂቶቹ የሚከተሉት ናቸው፡፡

ዕውቀት

ዕውቀት ለፍጡራን ሁሉ የባሕርይ ሳይሆን ተከፍሎ የሚሰጥና የሚነሳ /የሚወሰድ/ ነው፡፡ ይህ ዕውቀት መክሊት/ስጦታ/ ነው፤ 1ቆሮ21÷7 የተሰጠበት ምክንያት ደግሞ እንድንታበይበት ሳይሆን ለሌላው እንድንጠቅምበት ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ «ዕውቀት ያስታብያል»  ስለሚል አበው ሲመርቁ ዕውቀት ያለትዕቢት ይስጥህ፤ ይላሉ 1ቆሮ1-3፡፡ ዲያብሎስ አዋቂ ተደርጐ ተፈጥሯልና አዋቂ ነው፡፡ በዚህ ዕውቀቱ ግን እሱ ጠፍቶበት ሌላውን ለማጥፋት ይተጋበታል እንጅ ለሌላው ለመጥቀም አንዳች አይሠራም፡፡ ሰው በተሰጠው ዕውቀቱ በጎ ሥራን እንዲሠራበትና ለሌላው እንዲተርፍበት እግዚአብሔር ይሻል፡፡ እግዚአብሔር የሚጠይቀን በተሰጠን የዕውቀት መክሊት ክፉ ሥራ ስለሠራንበት ብቻ አይደለም በዕውቀታችን መጠን ያላወቀውን ከማሳወቅ ጀምሮ ምን ያህል እንደሠራንበት ይመረምረናል፡፡ ስለዚህ ብዙ ባወቅን ቁጥር ብዙ ማትረፍ እንዳለብን መረዳት ያሻል፡፡ «ብዙ ከተሰጠው ሰው ሁሉ ከእርሱ ብዙ ይፈለግበታል» ተብሏልና፡፡

 ሀብት

በመጀመሪያ ደረጃ ሀብታም/ባለሀብት/ መሆን በክርስትና ሕይወት አይነቀፍም፡፡ ለእግዚአብሔር ፍርድ ምድራዊ ሀብት መመዘኛ አይሆንም፡፡ እሱ ሀብታሙን ፈርቶ ድሃውን ንቆ ሳይሆን ለሁሉም እንደየሥራቸው ነው የሚፈርድባቸው፤ ራዕ 22÷12 ሀብት በምንለው በዚህ ዓለም በንብረትና ገንዘብ በከበርን ጊዜ ሁላችን ልናስታውሰው የሚገባ ቁምነገር አለ፡፡

•  አንደኛ የሰጠን እግዚአብሔር መሆኑን መዘንጋት የለብንም፡፡ እርግጥ ነው ወጥተን ወርደን ጥረን ግረን ሥራ ሳንመርጥ በላባችን ወዝ ያፈራነው የድካማችን ውጤት ነው፡፡ ግን ይህን ሁሉ ብቻችንን ልናደርገው አንችልም፡፡ በመግባት በመውጣታችን ጊዜ የረዳን፣ ጉልበታችንን ያጠነከረ፣ እጃችንን ያበረታ፣ ጤናውን የሰጠን እግዚአብሔር ነው፡፡ ለዚህ ነው ቅዱስ መጽሐፍ «ጉልበቴ የእጄም ብርታት ይህን ሀብት አመጣልኝ እንዳትል» የሚለን /ዘዳ 8÷17/፡፡

• ሁለተኛው ደግሞ ታማኝ መጋቢ እንድንሆንለት ማለትም ቀን ከፍቶበት ሆድ ብሶት ሲቸገር ያየነውን ወንድማችንን ችግሩን እንድናስወግድለት ላጣውና ለነጣው ድሃ እንድንደርስለት ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ለመንፈስ ቅዱስ ልጁ ለጢሞቴዎስ «ባለጠጎች ሊረዱና ሊያካፍሉ የተዘጋጁ እንዲሆኑ ምከራቸው» ያለው፤ ይህንኑ ለማስታወስ ነው 1ኛ ጢሞ 6÷19 ጠቢቡ ሰሎሞንም ሀብት የማትረፊያ መክሊት መሆኑን ሲያስረዳ «ያለውን የሚበትን ሰው አለ፤ ይጨመርለታልም፤ ያለቅጥ የሚነፍግ ሰውም አለ ይደኸያልም»  ነው ያለው ምሳ 11÷24 ይህ ሰው ለሰዎች ሲሰጥ በምድር ይከፍሉኛል ብሎ አስቦ ባለመሆኑ የሚበትን በማለት በዚህ በሚያልፈው ምድራዊ ሀብት የማያልፈውን ሰማያዊ ሀብት ማትረፍ እንዲቻል የነገረንን ልብ እንበል፡፡ ቀላል ምሳሌ እናስቀምጥ፤ በሰፈራችን አንድ ትልቅ ድግስ ላይ የድግሱ ባለቤት ጐረቤቶቹንና ወዳጆቹን ጠርቶ፤ የድግሱ እድምተኞች ከመምጣታቸው አስቀድሞ፤ አንዱን ወጥቤት፣ ሌላውን ሥጋ ቤት፣ ሌላዋን እንጀራ ቤት ወዘተ እያለ ይመድባል፡፡ እነዚህ ሰዎች የድግስ ቤቱ ሹማምንት ቢሆኑም ድግሱ የእነሱ አይደለም ስለዚህ በሰው ድግስ ለመጠቃቀም አንዱ ባዶ ሳህን ይዞ እያዩ ለሌላው ሁለተኛ እንጀራ ቢደርቡለት፣ አንዱ ደረቅ እንጀራ እየበላ ለሚያውቁት የሰፈራቸው ሰው የወጥ ሳህኑን አቅርበው ወጡን ቢገለብጡለት፣ የሰው ድግስ በማበላሸታቸው ይጠየቁበታል እንጂ አይመሰገኑበትም የዚህ ዓለም ባለጸጐችም እንዲሁ ናቸው የተሰጣቸው ሀብት ሊያጋፍሩበት፣ ሊያስተናብሩበት፣ መክሊት ሊያተርፉበት እንጂ በዚህ ዓለም ሊመራረጡበት በልጠው ሊታዩበት ወዘተ… አይደለም፡፡ « የአመጻ ገንዘብ ሲያልቅ በዘላለም ቤቶች እንዲቀበሏችሁ በእርሱ ወዳጆችን ለራሳችሁ አድርጉ” የተባለውን፤ ባለጸጎች ሁሉ ልብ ሊሉት ይገባል፡፡/ሉቃ 16÷9/

ሥልጣን

ሌላኛው መክሊት ሥልጣን ነው፡፡ ሥልጣን ሲባል ሁሌም ትዝ የሚለን ያየነውም እሱኑ ብቻ ስለሆነ ይመስላል፤ መፍለጥ መቁረጥ፣ ማራድና ማንቀጥቀጥ ነው፡፡ ተረታችንም «ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል» የሚል ነው፡፡ በዚህ መንፈስ ብዙዎች «እኔ እግዚአብሔርን ብሆን ኖሮ…» ብለው የሚፎክሩት አይሆኑም እንጂ ቢሆኑ ኖሮ፤ ከቤተ ክርስቲያን የሚያባርሩት፣ ከሥልጣን የሚሽሩት ወደሞት የሚያወርዱት ባጠቃላይ የሚፈልጡትና የሚቆርጡት ብዙ ነው፡፡ አላወቁትም እንጂ እግዚአብሔርን መሆን እነሱ እንዳሰቡት መቅሰፍ መግደል ብቻ ሳይሆን፤ እግር ማጠብ በጥፊ መመታት፣ በምራቅ መታጠብ፣ የእሾህ አክሊል መድፋት፣ በጦር መወጋት፣ ለሰው ልጆች ድኀነት መሰቀልና መሞትም ነው፡፡  በአንጻሩ በተሰጠው መክሊት ያላተረፈው፤ ሲሾም ያልበላ ሲሻር ይቆጨዋል በሚል አሳብ ተተብትቦ፤ ሥልጣን መፍለጥ መቁረጥ የመሠለው ምስኪን የሚያገኘውን ዕድል በምሳሌ ሲያስረዳ እንዲህ ብሏል፡፡ «ያባሪያ ግን ጌታዬ እስኪመጣ ይዘገያል ብሎ በልቡ ቢያስብ ሎሌዎችንና ገረዶችንም ይመታ፣ ይበላም ይጠጣም ይሰክርም ዘንድ ቢጀምር የዚያ ባሪያ ጌታ ባልጠበቃት ሰዓት ይመጣል ከሁለትም ይሰነጥቀዋል ዕድሉንም ከማይታመኑ ጋር ያደርጋል፡፡» /ሉቃ 12÷42-46/፡፡ ጥሩ ክርስቲያን ባለሥልጣን ሲሆን አይኮፈስም፤ «ጌታው በቤተሰቦቹ ላይ የሾመው፡፡» ተብሎ እንደተጠቀሰው፤ በእግዚአብሔር ፍጥረት ላይ በመሾሙ እንደጠቢቡ ሰሎሞን ይህንን ሕዝብ የማስተዳድርበት ጥበብ ስጠኝ እያለ ወደ ፊጣሪው በመጸለይ መክሊቱን ለማትረፍ ይተጋል፡፡

አንድ ታሪክ እናስታውሳችሁ፤ የሊቀ ጳጳሱ የዲሜጥሮስን ወደ ጵጵስና መዓርግ መምጣት እናቱ ሰምታ «ሹመት ያዳብር» ትለው ዘንድ አስቦ መልእክተኛ ይልክባታል እሷ ግን አንዳች አለመናገሯን ከመልእክተኛው የተረዳው ሊቀጳጳሱ ዲሜጥሮስ «ይህን የሚያህል መዓርግ አግኝቶ እንዴት በመልእክተኛ ይልክብኛል» ብላ ይሆናል ይልና ራሱ ለመሔድ ይወስናል፡፡ የጵጵስና መዓርግ ልብሱን ለብሶ በአጀብ ወደ እናቱ የደረሰው ሊቀጳጳሱ ዲሜጥሮስ የጠበቀው ግን ሌላ ነው፡፡ እናቱ ደስታዋን አልገለጠችለትም፡፡ ይልቁንም «እንዲህ ሆነህ /በመዓርግ ልብሱ/ ከማይህ ሞተህና ተገንዘህ አስከሬንህ በሳጥን ሆኖ ወደመቃብር ስትወርድ ባይህ ደስ ይለኛል፡፡ ምክንያቱም በፊት በራስህ ኃጢአት ብቻ ነበር የምትጠየቀው፡፡ አሁን ግን በተሾምክላቸው ምእመናን ኃጢአትም ትጠየቃለህ» አለችው፡፡ አባታችን ዲሜጥሮስ ይህ የእናቱ ንግግር ተግሣጽ ሆኖት ዕድሜውን ሙሉ የምእመናንን ነፍሳት ለመታደግ ሲወጣ ሲወርድ ኖሯል፡፡ስለሆነም ሥልጣነ ሥጋም ሆነ ሥልጣነ መንፈስ የተሰጠን ለማትረፊያነት ነው፡፡

 ትዳር

ክብር ምሥጋና ይግባውና ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የእውነተኛ ትዳርን አንድነት የባልና የሚስትን ኑሮ ባስተማረበት አንቀጽ ሲናገር እንዲህ ብሎ ነበር «… ፈጣሪ በመጀመሪያ ወንድና ሴት አደረጋቸው…. ስለዚህ ሰው አባቱንና እናቱን ይተዋል ከሚስቱም ጋር ይተባበራል፤ ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ. ….ስለዚህ አንድ ሥጋ ናቸው አንጂ ወደፊት ሁለት አይደሉም እግዚአብሔር ያጣመረውን እንግዲህ ሰው አይለየው … ያለዝሙት ምክንያት ሚስቱን ፈትቶ ሌላይቱን የሚያገባ ሁሉ ያመነዝራል የተፈታችውንም የሚያገባ ያመነዝራል አላቸው … » ማቴ 19÷4-9

ይህንን ትምህርት አጠገቡ ሆነው በቀጥታ ሲሰሙ የነበሩት ደቀመዛሙርቱ የባልና የሚስትን ሥርዓት ጥሩ ነው ብለው አላሳለፉትም፡፡ ይልቁንም « የባልና የሚስት ሥርዓት እንዲህ ከሆነ መጋባት አይጠቅምም» አሉት፡፡ ከዚህ በኋላ ነበር ጌታ «ይህ ነገር ለተሰጣቸው ነው እንጂ ለሁሉ አይደለም…» ብሎ ሐዋርያትን በትዳር ላይ ያላቸውን አቋም እንዲያስተካክሉ ያደረጋቸው፡፡ ይህም ብቻ አይደለም፤ ጌታችን ይህ ነገር ለተሰጣቸው ነው ሲል ትዳር ከእግዚአብሐር ተፈቅዶ የተሰጠና የሚሰጥ መሆኑንም ጭምር ነግሮናል፡፡ ብዙዎች ወዳጅ የሚሏቸውን ጠጋ ብለው «እባክህን ጥሩ ሚስት ፈልግልኝ እባክሽን ጥሩ ባል ፈልጊልኝ» ይሏቸዋል፡፡ ትዳር « ለምኑ ይሰጣችኋል ፈልጉ ታገኙማላችሁ፤ መዝጊያ አንኳኩ ይከፈትላችኋል…» ማቴ 7÷7 ከተባልናቸው ጉዳዮች ውስጥ በመሆኑ፤ ስንፈልግ የምንለምነው እግዚአብሔርን የሚሰጠንም ከእግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ ሰዎች ምክንያቶች ናቸው፡፡ ለዛውም እንደአብርሃም ሎሌ ታማኝና ቅን ከሆኑ ብቻ /ዘፍ 24÷1-97/፡፡እንግዲህ ልብ እንበል፤ ትዳር የዚህን ዓለም ኃላፊና ጠፊ ተድላ፤ ደስታ ብቻ ፈጽመን የምናልፍበት ሳይሆን፤ በሚታየው የማይታየውን፣ በሚጠፋው የማይጠፋውን ገንዘብ እንድናደርግበት ማለትም እንድናተርፍበት የተሰጠን መገበያያ መክሊት ነው፡፡ በጥሩ ክርስቲያናዊ ሥርዓት የመሠረትነው ትዳራችን መክሊት መሆኑን ከተረዳን ትዳርን እንደጦር በመፍራት ከጋብቻ ለሸሹ ሰዎች አርአያ እንሆንበታለን፡፡ ከሁሉ የበለጠው ደግሞ ለቤተ ክህነቱም ሆነ ለቤተመንግሥቱ የሚሆን ምርጥ ዘር አገርንና ወገንን የሚጠቅም ዜጋ /ልጆች/ እናስገኝበታለን፡፡ በዚህ ትርፋችን ይበዛል መክሊት መባሉም ለዚህ ነው፡፡ ከላይ እንዳየናቸው ሁሉ ሙሉ አካላችን፣  ጤናችን፣ ውበታችን፣ ልጆቻችን ወዘተ…እነዚህ ሁሉ   የእግዚአብሔር ስጦታዎች ናቸው፡፡ ስጦታዎቹ ማትረፊያ መክሊቶች በመሆናቸው «ከብዙ ዘመንም በኋላ የነዚያ ባሮች ጌታ መጣና ተቆጣጠራቸው፡፡» ተብሎ እንደተጻፈ ቁጥጥር አለብንና ልናስብበት ይገባል ማቴ 25÷19/፡፡

ዕድሜ

ዕድሜ መስታወት ብቻ ሳይሆን መክሊትም ነው፡፡ ግን ስንቶቻችን በብድር ዕድሜ ላይ እንዳለን እናውቅ ይሆን? እግዚአብሔር አምላክ የሰው ልጅ ዘመንን በዓመት፣ በወር፣ በሳምንት፣ በቀን፣ በሰዓት፣ በደቂቃ፣ በሰኮንድ… ወዘተ እየለካና እየገደበ አመላልሶ በመቁጠር ይጠቀምበት ዘንድ ዘመንን በቁጥር ሰጥቷል፡፡ «… ዘመንን ቀንን በቁጥር ሰጣቸው…» እንዲል /ሲራ17÷1/ በዚህ በሚለካውና በሚሰፈረው የቁጥር ዘመን ውስጥ የእያንዳንዳችን ዕድሜ ይገኝበታል፡፡ ያም በእግዚአብሔር ዘንድ የተወሰነ ነው፡፡ « የሰው ዕድሜ የተወሰነ ነው የወሩም ቁጥር በአንተ ዘንድ ነው፤ እርሱም ሊተላለፈው የማይችለውን ዳርቻ አደረግህለት…» ኢዮ 14÷5 ይለናል፡፡

«ሺሕ ዓመት አይኖር» እያልን የምንገልጸውም ይህንኑ ነው፡፡ ዕድሜ ገደብ አለው ለማለት ነው፡፡ በዚህ ንግግር ዘለዓለም አለመኖርን ለመግለጽ እንደታሰበ ልብ ይሏል፡፡ ቅዱስ ዳዊትም ይህንኑ ሺህ ዓመት አይኖር የሚለውን አባባል ሲያጐላው « የሰው ዕድሜ ሰባ ዓመት ቢበረታም ሰማንያ ዓመት ቢበዛ ግን ድካምና መከራ ነው፡፡» ይላል፡፡/መዝ 89÷10/ይህንን ውሱን የሆነውን ዕድሜያችንን የሚሰጠን እግዚአብሔር ሲሆን፤ ጊዜውም ከየዕለት ደቂቃዎች ጀምሮ ዘመን አልፎ ዘመን ሲተካ ነው፡፡ ይህንንም የሚያደርገው ሥራችን ለዚህ አብቅቶን ሳይሆን በቸርነቱ ነው «በቸርነትህ ዓመታትን ታቀናጃለህ፡፡» ተብሏልና /መዝ 65÷11/

እግንዲህ ጊዜ የተሰጠን፣ ዘመን የተሻገርነው፣ ዕድሜም የተጨመረልን፤ እንደትጉህ ነጋዴ በቅንነት ወጥቶና ወርዶ ነግዶና አትርፎ የጽድቅ ሥራ ሠርቶ ለመገኘት እንጂ፤ እንደዛ ክፉና ሃኬተኛ ባሪያ ልንቀብረው አይደለም አበው ሲመርቁ ዕድሜ ለንስሐ ዘመን ለፍስሐ ይስጥህ የሚሉት፤ በዕድሜያችን ንስሐ እንድንገባበት በዘመኑም እንድንደሰትበት ለእኛ መሰጠቱን ተረድተውት ነው፡፡ የሚያጠግብ እንጀራ እምጣዱ ላይ ያስታውቃል እንዲሉ፤ ከዘመን ዘመን በመሸጋገሪያው ዋዜማ ምሽት ጀምረን በዘፈንና በጭፈራ በማንጋት የተቀበልነው ዕድሜና ዘመን፤ ዘመኑም የፍስሐ ዕድሜውም የንስሐ አይሆንም፡፡ ያውም እኮ የእግዚአብሔር ቃል «የአሕዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት በመዳራትና በሥጋ ምኞችም በስካርም በዘፈንም ያለልክም በመጠጣት ነውርም ባለበት በጣኦት ማምለክ የተመላለሳችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃልና፡፡…» እያለን     1 ጴጥ 4÷3፤ ውሻ እንኳን ወደበላበት ሲጮህ እንዴት የሰው ልጅ የሚያኖረውን፣ ከዘመን ወደ ዘመን የሚያሸጋግረውን ያጣዋል፡፡ «በሬ  የገዢውን አህያም የጌታውን ጋጣ አወቀ ፤ እስራኤል ግን አላወቀም ሕዝቤም አላስተዋለም…» ያለው ቃል ትዝ ሊለን ይገባል በእውነት ጋጣችንን እንወቅ፡፡ /ኢሳ 1÷3/ የተሰጠንን የዕድሜ መክሊት አንቅበረው፡፡

ባለፈው ዓመት ያልታረቅን ዘንድሮ እንታረቅ፤ ባለፈው ዓመት ስንሰክር የነበርን ዘንድሮ ልብ እንግዛ፤ ባለፈው ዓመት ንስሐ ያልገባን ዘንድሮ ንስሐ እንግባ እንቁረብ፤ ባለፈው ስናስጨንቅ የነበርን ዘንድሮ እናጽናና፤ ይኼኔ ነው በዕድሜ መክሊታችን በእጥፍ የምናተርፈውና «አንተ በጎ ታማኝም ባሪያ ወደ ጌታህ ተድላ ደስታ ግባ» የምንባለው፡፡ ዕድሜያችን ልናተርፍበት የተሰጠን መክሊት ያውም በብድር መሆኑን መቼውንም ቢሆን አንዘንጋው፤ ሉቃ 13÷6-9 ዘመኑ ዘመናችን ከሸማኔ መወርወሪያ ይልቅ ይፈጥናል፡፡ «… የማይጠቅመውንም ባሪያ በውጭ ወዳለው ጨለማ አውጡት በዚያ ልቅሶና ጥርስ ማፋጨት ይሆናል፡፡» እንዳንባል ይልቁንም በዚህ አጭርና ፈጣን ዘመናችን ራሳችንንና ሌላውን የእግዚአብሔርን ፍጡር ሁሉ እንጠቀምበት፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ እራሳችንን ብንመረምር ግን ባልተፈረደብንም ነበር፤ እንዳለው፤ እንዳይፈ ረድብን ራሳችንን እንመርምር፡፡ አንድም በስንሐ አንድም የተሰጡንን የምናተርፍባቸው እንጂ የማንቀብራቸውን መክሊቶቻችንን ቀብረናቸው እንዳገŸ ለሁሉም ነገር የእግዚአብሔር ቸርነት የድንግል ማርያም ምልጃ ይርዳን፡፡ 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር