የልደትን ብርሃን መናፈቅ ስብከት፣ ብርሃን ኖላዊ

            በዲ/ን ዘላለም ቻላቸው
መግቢያ

ቅዱስ ጳውሎስ በሮሜ መልእክቱ «በሞቱ እንመስለው ዘንድ ከእርሱ ጋር በጥምቀት ተቀበርን እርሱ ክርስቶስ በአባቱ ጌትነት ከሙታን እንደተነሳ እየተወ እንደ እርሱ አዲስ ሕይወት እንኖራለን» /ሮሜ. 6.4/፤ እንዳለው ክርስትና በጥምቀታችን ከክርስቶስ ጋር ሞተን ከእርሱም ጋር ተነስተን በትንሳኤው ብርሃን በአዲስ ሕይወት የምንመላለስበት የእግዚአብሔርን ፍቅር እየቀመስን ያደረገልንን እያደነቅን ፀጋውን እለት እለት እየተቀበልን፣ እኛ ሞተን ክርስቶስ በእኛ ውስጥ ህያው ሁኖ የምንኖረው ኑሮ ነው፡፡

ይህንንም ዓይነት ኑሮ ለመኖር አምላካችን ያደረገልንን የማዳን ሥራ፣ ስለ ሰው ልጆች ብሎ ያደረጋቸውን ነገሮች ሁሉ /ልደቱን፣ ጥምቀቱን ፣ጾሙን ፣ መከራውን ፣ ስቅለቱን / በተለይም ደግሞ ለትንሳኤያችን በኩር የሆነበትን ትንሳኤውን እና እርገቱን እንዲሁም ዳግም ምጽአቱን ዘወትር ማሰብ ያስፈልጋል፡፡

እነዚህን ድርጊቶች /ነገሮች/ እንደ ትዝታ ማሰብ ብቻ ሳይሆን ልክ በተደረጉበት ወቅት እንደተገኙ ሁኖ መካፈልና መቅመስም የግድ ያስፈልጋል፡፡ ለዚህም ቅዳሴ ዋነኛው መንገድ ነው፡፡ ቅዳሴ ለማስቀደስ በመሰዊያውና በመስዋእቱ ዙሪያ ስንሰበሰብ ልክ ጌታ በተሰቀለበት በዕለት አርብ በቀራንዮ አደባባይ እንደተገኘን ሆነን እንቆማለን፡፡

በአጠቃላይ ሕይወታችን እነዚህን ነገሮች በማስታወስ፣ በማሰብ እና በመካፈል ላይ የተመሠረተ መሆን አለበት፡፡

ዳሩ ግን በኃጢአታችን ምክንያት በጥምቀት የተቀበልነውን አዲስ ሰውነት በማቆሸሻችን እና ራሳችንን ከፀጋ በማራቃችን፣ እንዲሁም በተለያዩ አስፈላጊ እና አላስፈላጊ ጉዳዮች ተጠምደን በወከባ በመኖራችን ይህንን ማድረግ ከባድ ይሆን ብናል፡፡

ስለዚህም ቤተ ክርስቲያን እነዚህን በነገረ ድኅነት ውስጥ ትልቅ ቦታ ያላቸውን ታላላቅ ድርጊቶች ቢያነስ በዓመት አንድ ጊዜ እንድናስባቸው አድርጋለች፡፡ የልደትን፣ የጥምቀትን፣ የስቅለትን፣ የትንሳኤን፣ የዕርገትን … በዓላት የማክበራችን ዋናው ምክንያትም ይኸው ነው፡፡

ነገር ግን አሁንም ቢሆን እነዚህን በዓላት ስናከብር ከሚያስጨንቁንና ህሊናችንን ከሞሉት ነገሮች መልሰን በአንድ ጊዜ ወደ መንፈሳዊ ሃሳብና ተመስጦ መምጣት ስለምንቸገር ቤተ ክርስቲያን ከበዓላቱ በፊት የዝግጅትና የማንቂያ ጊዜያት እና አጽዋማት እንዲኖሩም አድርጋለች፡፡

በእነዚህ ወቅቶች ህሊናችንን ቀስ በቀስ ወደ መንፈሳዊው ሃሳብ እና ወደ በዓሉ ጉዳይ ተመልሶና በዓሉን በናፍቆት ጠብቀን በተገቢው ሁኔታ እንድናከብረው ታደርጋለች፡፡

በዚህም ምክንያት አብዛኞቹ በዓላት ከመከበራቸው በፊት አጽዋማት ይኖራሉ ሥጋ ወደሙን ከመቀበላችንም በፊት እንጾማለን፡፡ ሌሎቹም ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን ከመፈፀማቸው በፊት የጾምና የዝግጅት ወቅቶችን ማሳለፍ ጥንታዊ የቤተ ክርስቲያን ትውፊት ነው፡፡

በዚህ ጽሑፍ ርእስ አድርገን የምንነጋገርበት ጾመ ነቢያት ዋነኛ ዓላማም ምእመናንን የጌታችንን የልደት በዓል እንዲያከብሩ ማዘጋጀት ነው፡፡ በተለይም ከልደት በፊት ያሉት ሦስት ሳምንታት ይህ ጎልቶ እንደሚነገርባቸው ቀጥለን እንመለከታለን፡፡

ብሉይ ኪዳን እና ጾመ ነቢያት

የአዳምን በደል ካሳ ከፍሎ ከራሱ ጋር ሊያስታርቀው ወደዚህ ምድር የመጣውና በተዋህዶ ሰው የሆነው እግዚአብሔር ወልድ በዚህ ምድር ላይ በሥጋ የተገለጠው አዳም የድኅነት ቃልኪዳንን ከእግዚአብሔር ከተቀበለ ከብዙ ሺህ ዓመታት በኋላ ነው፡፡

እነዚህ ዓመታት ለሰው ልጆች በኋላ የሚደረገውን የድኅነት ሥራ /ሥጋዌ፣ ሞት፣ ትንሳኤ/ እንዲረዱ ለማስቻል ዝግጅት የተደረገባቸው ዘመናት ናቸው፡፡ በእነዚህ ዘመናት እግዚአብሔር የራሱ የሆኑ ሕዝቦችን እና ሰዎችን በመምረጥና ከእነዚህ ጋር ቃል ኪዳን በመግባት፣ ለእነዚህ ሕዝቦች ተአምራትን በማድረግና ከጠላቶቻቸው በማዳን፣ ከእነዚህም በላይ ደግሞ ነቢያትን በመላክና በእነርሱ አማካኝነት ሕዝቡን በማስተማር፣ ትንቢት በማስነገርና ተስፋ በመስጠት /በማጽናናት/፣ ሱባኤም በማስቆጠር ማንነቱን እና የሰው ልጆችን ለማዳን ያቀደውን ዕቅድ ቀስ በቀስ፣ በጥቂት በጥቂቱ ገልጧል፡፡

በየዘመኑ የተነሱ ነቢያትም ምንም እንኳን አምላክ ይህን ዓለም እንዴት እንደሚያድነው ሙሉ በሙሉ ግልጥልጥ ብሎ ባይረዱትም እግዚአብሔር ዓለሙን የሚያድንበትን ቀን እንዲያቀርበው እንዲህ እያሉ ይማፀኑ ነበር፡፡

– «አቤቱ እጅህን ከሰማያት ልከህ አድነን» /መዝ. 143.17/
– «ሰማያትን ቀደህ ብትወርድ ምነው)» /ኢሳ.64.1/
ቅዱስ ጴጥሮስ በሁለተኛው መልእክቱ እንደሚነግረንም በመንፈስ እየተነዱ ስለሚመጣው ነገር ሁሉ ትንቢት ተናግረዋል፤ ሱባዔ ቀጥረዋል፤ ህዝቡም የጌታን ማዳን በተስፋ እንዲጠብቅ አስተምረዋል፡፡ ጌታ ሰው ሁኖ የተወለደው ከዚህ ሁሉ ዝግጅት በኋላ ነው፡፡ የአዳኙ መሲህ መወለድ በተለይ ከእስራኤል ዘንድ በጉጉት ይጠበቅ ነበር፡፡

በዚህም ምክንያት ከእስራኤል መካከል ቅን የነበሩትና በእግዚአብሔር መንገድ የተጓዙት፤ «መሲሁን አገኘነው»፤ «ሙሴ በህግ መጻሕፍት፣ ነቢያትም ስለ እርሱ የጻፉለትን የናዝሬቱን ኢየሱስን አገኘነው» /ዮሐ. 1.41፣ ዮሐ. 1.45/ እያሉ ተከትለውታል፡፡

እንግዲህ ይህ ታሪክ ከተፈፀመ ጌታችንም ከተወለደ እነሆ ከ2000 ዓመታት በላይ አልፎታል፡፡ እኛም የተደረገውን ሁሉ በትውፊት ተቀብለን በምስጢራተ ቤተ ክርስቲያን አማካኝነት በዚህ በድኅነት ጉዞ የተሰጡትን ፀጋዎች ተካፍለን ክርስቲያኖች ሆነናል፡፡ በመግቢያችን እንዳየነው ክርስትና እነዚህን ነገሮች ሁሉ ዘወትር እያሰብንና፣ በተመስጦ እንደ አዲስ እየተካፈልን ልንኖረው የሚገባ ኑሮ ነው፡፡

ቤተ ክርስቲያን የጌታችንና የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ የልደት በዓል እንዲከበር ያደረገችው ከእነዚህ ዘወትር ልናስባቸው ከሚገቡ ነገሮች አንዱ የሆነውን ብርሃኑንና ዘወትር ልናየው የሚገባውን የጌታችንን ልደትን ቢያንስ በዓመት አንድ ጊዜ በተመስጦ እንድናስበውና ብርሃኑን እንድናየው ነው፡፡

ይህችን በዓመት አንድ ጊዜ የምትመጣዋን በዓልም ቢሆን ከማክበራችን በፊት አርባ ሦስት ቀናትን በመጾም እንዘጋጃለን፡፡ በመጾም ብቻ ሳይሆን እነዚህ አርባ ሦስት ቀናት ተከፋፍለው የልደት በዓልን በተገቢው መንገድ እንድናከብር የሚያዘጋጁ ትምህርቶችን እንማርባቸዋለን፡፡ በተለይም ከልደት በዓል በፊት ያሉት ሦስት ሳምንታት ይህ ዓላማ አላቸው፡፡

ቤተ ክርስቲያን የጌታችንን የልደቱን ብርሃን ለማየት እንዘጋጅ ዘንድ እነዚህን ሦስት ሳምንታት የጌታችንን ልደት በናፍቆት መበጠበቅ እንደ ብሉይ ኪዳን ሰዎች ሆነን እንድናሳልፍ ታደርጋለች፡፡

በእነዚህ ሳምንታት /በተለይም በእሑዶቹ/ የብሉይ ኪዳን ነቢያት የአዳኙን መምጣትና የጌታን ቀን መገለጥ በመናፈቅ ስላሳለፏቸው ጊዜያት ደጋግመን በመማር እነዚያን የጨለማ ዘመናት እንድናስታውስና እኛም በእነርሱ መንፈስ ተቃኝተን ያለንበትን ሁኔታ በመመርመርና ዘወትር ልንመላለስበት ያጣነውን ነገር ግን በሃጢአታችን ያጣነውን የልደቱን ብርሃን ለማየት እንድንናፍቅ እንደረጋለን፡፡

ሦስቱን ሳምንታት በዚህ ሁኔታ ካሳለፍንና የልደቱን ብርሃን የማየት ፍላጎታችን ከተነሳሳ በኋላ የልደትን በዓል እናከብራለን፡፡ ደጋግመን እንዳልነውም የልደትን በዓል የምናከብረው እንዳለፈ ታሪክ መታሰቢያ አይደለም፡፡ ልክ በዚያች በልደቱ ቀን ከሰብአ ሰገልና ከእረኞች ጋር እንደተገኘን ሆነን እናከብራለን የልደቱን ብርሃን እናያለን እንጂ፡፡

ለዚህም ነው የልደትን በዓል ስናከብር
«ዮም ፍስሐ ኮነ በእንተ ልደቱ ለክርስቶስ»
«ዛሬ በክርስቶስ ልደት ደስታ ሃሴት ሆነ፡፡» የምንለው፡፡
«ዮም፣ ዛሬ» ማለታችን በዓሉ የልደት መታሰቢያ /ትዝታ/ ብቻ ሳይሆን በዚያ በልደት ቀን እንደነበርን የምንሆንበት መሆኑን የሚያመለክት ነው፡፡

ስብከት፣ ብርሃን፣ ኖላዊ

እነዚህ ከልደተ በዓል በፊት ያሉት ሦስቱ የጾመ ነቢያት ሳምንታት ስብከት፣ ብርሃን እና ኖላዊ ተብለው ይጠራሉ፡፡

እነዚህ ሳምንታት ነቢያት አምላክ ይህንን ዓለም እንዲያድን ያላቸውን ናፍቆት የገለጡባቸው እና ይህንን አስመልክተው ያስተማሩባቸው ሦስት የተለያዩ መንገዶች እና ጌታችንም ለእነዚህ መልስ የሰጠባቸው ሁኔታዎች ይታሰቡባቸዋል፡፡

1. ስብከት

ስብከት ማለት ማስተማር ማለት ነው፡፡ ይህ ሳምንት ከሙሴ ጀምሮ የነበሩ ነቢያት በሙሉ አዳኝ /መሲህ/ እንደሚመጣ ማስተማራቸው ጌታችንም እነርሱ ይመጣል ብለው ያስተማሩለት እኔ ነኝ ብሎ ራሱን መግለጡ የሚታሰብበት ነው፡፡
ሙሴ ለጊዜው የጌታችን ምሳሌ ለሆነው ለኢያሱ ፍጻሜው ግን ለጌታችን በሆነው ትንቢቱ «አምላክህ እግዚአብሔር ከወንድሞችህ እንደ እኔ ያለ ነቢይ ያስነሳልሃል፤ እርሱንም ስሙት፡፡» ብሎ ለሕዝበ እስራኤል ነግሯቸው ነበር፡፡ /ዘዳ. 18.15/

እግዚአብሔር ወልድም በሥጋ ማርያም በተገለጠ ጊዜ ራሱን ያስተዋወቀው ያ ነቢያት የተናገሩለት አዳኝ /መሲህ/ እንደሆነ ነው፡፡ «ሙሴ እና ነቢያት ሁሉ ስለ እኔ ይናገራሉ፡፡» ይላቸው ነበር፡፡

ትንቢቱን ያውቁ የነበሩ በእግዚአብሔር መንገድ የሚሄዱ እስራኤላውያንም «መሲሁን አገኘነው»፣ «ሙሴ በህግ መጻሕፍት፣ ነበያትም ስለ እርሱ የጻፈለትን የናዝሬቱን ኢየሱስን አገኘነው» እያሉ ተከትለውታል፡፡ /ዮሐ. 1.41፣ ዮሐ. 1.45/

ሐዋርያትና ሌሎቹ ደቀመዛሙርቱም ከጌታችን ሞትና ትንሳኤ በተለይ የተነገሩትን ትንቢቶች ሁሉ ያውቁ ለነበሩት እስራኤላውያን ያስተማሩት እነዚህን የነቢያት ትምህርቶች እና ትንቢቶች እየጠቀሱ ነበር፤

ቅዱስ ጴጥሮስን በቤተ መቅደስ እንዲህ ብሎ አስተምሯል፤ «አሁንም ወንድሞቼ ሆይ አለቆቻችሁ እንዳደረጉ ይህን ባለማወቅ እንዳደረጋችሁት አውቃለሁ፡፡ እግዚአብሔር ግን ክርስቶስ መከራን እንዲቀበል በነቢያት ሁሉ አፍ እንደተናገረ እንዲሁ ፈፀመ» /ሐዋ. 3.17-18/፡፡

በሁለተኛው መልእክቱ ደግሞ እንዲህ ሲል ጽፏል፡- «ወንድሞች ሆይ የቀደሙ ቅዱሳን ነቢያት የተናገሩትን ቃልና ለእኛ ለሐዋርያትም ያዘዘውን የመድኃኒታችንና የጌታችን የኢየሱስ ክርስቶስን ትእዛዝ ታስቡ ዘንድ… ዕወቁ» /2ኛ ጴጥ. 3.1-3/

ቅዱስ ጳውሎስም በዕብራውያን መልእክቱ መግቢያ ላይ እንዲህ ብሏል፤ «ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዐይነትና በብዙ ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናገረ፤ በኋላ ዘመን ግን ሁሉን ወራሽ ባደረገው፣ ሁሉን በፈጠረበት በልጁ ነገረን፡፡» /ዕብ. 1.1-2/

2. ብርሃን

ነቢያት የአምላክን ማዳን ከጠበቁባቸው እና ከገለጡባቸው መንገዶች አንዱ ብርሃን ነው፡፡ ዘመነ ብሉይ መከራ ሥጋ፣ መከራ ነፍስ የፀናበት፣ ሁሉ ነገር አስጨናቂ የሆነበት፣ ሰው ብርሃን ከሆነው አምላክ ጋር የተራራቀበት ስለነበር ያሉበትን ዘመን «ጨለማ» ብለው በመግለጥ ይህንን ጨለማ የሚያስወግድና ወደ ትክክለኛው መንገድ የሚመራ ብርሃን እንዲመጣ እንዲህ እያሉ ይፀልዩ ነበር፡፡

«ብርሃንህንና ጽድቅህን ላክ፣ እነርሱም ይምሩኝ፣
አቤቱ ወደ መቅደስህ ተራራና ወደ ማደራያህ ይውሰዱኝ» /መዝ. 42.3/
ጌታችንም ወደዚህ ዓለም በመጣ ጊዜ ለዚህ መልስ ሰጥቷል፤
«እኔ የዓለም ብርሃን ነኝ» /ዮሐ. 8.12/
ደቀመዛሙርቱም ስለ ብርሃንነቱ በመመስከር ተባብረዋል፤

– ቅዱስ ዮሐንስ ስለጌታችን ሰው መሆን /ሥጋዌ/ በተናገረበት በወንጌሉ የመጀመሪያ ክፍል ጌታችንን ብርሃን ብሎታል፤ «ሕይወት በእርሱ ነበረ፣ ሕይወትም የሰው ብርሃን ነበረ፤ ብርሃንም በጨለማ ያበራል፤ ጨለማም አላሰነፈውም» /ዮሐ. 1.4-5/

ቅዱስ ጳውሎስም ጌታችን በሚያንፀባርቅ ብርሃን አምሳል እንደተገለጠበት ተናግሯል፡፡ «እኩል ቀን በሆነ ጊዜ በመንገድ በሄደ ከፀሐይ ይልቅ የሚበራ መብረቅ በእኔና ከእኔ ጋር ይሄዱ በነበሩት ላይ ከሰማይ ሲያንፀባርቅ አየሁ፤ … አንተ የምታሳድደኝ የናዝሬቱ ኢየሱስ ነኝ አለኝ፡፡» /ሐዋ. 26.13/

3. ኖላዊ

ኖላዊ ማለት እረኛ ማለት ነው፡፡ ነቢያቱ ራሳቸውን እና ሕዝበ እስራኤልን ብሎም ዓለምን እረኛቸው እንደተዋቸው እና እንደተቅበዘበዙ በጎች በመቁጠር እንዲሰበስባቸውና እንዲያሰማራቸው እንዲህ እያሉ እራሳቸውን ይማፀኑ ነበር»

«ዮሴፍን እንደ መንጋ የምትመራ የእስራኤል ጠባቂ /እረኛ/ ሆይ፣ አድምጥ በኪሩቤል ላይ የምትቀመጥ ተገለጥ፡፡» /መዝ. 79.1/

ጌታችንም ለዚህ ጥያቄ እንዲህ ሲል መልስ ሰጥቷል፤ «ቸር ጠባቂ /እረኛ/ እኔ ነኝ፡፡ ቸር ጠባቂ ስለ በጎቹ ነፍሱን ይሰጣል፡፡»  /ዮሐ10.11/

ምን እናድርግ ?

ዛሬም እኛ በኃጢአታችንና በምታዋክበን ዓለም ምክንያት ዘወትር ልናየውና ልንመላለስበት የሚገባን ብርሃነ ልደቱ ተሰውሮብናል፣ ከቸር እረኛችን የራቅን የተቅበዘበዝን በጎች ሁነናል፡፡ በምናስበው ሃሳብ፣ በምንሰራው ሥራ ውስጥም የአምላክ ሰው መሆን ቦታ የለውም፡፡ የምንኖረው ልክ ክርስቶስ እንዳልተወለደ /as if Christ was not born/ ነው፡፡ ስለዚህ እኛም እንደ ብሉይ ኪዳን ሰዎች ያጣነውን ይህንን ፀጋ ለማግኘት፣ ብርሃነ ልደቱን ለማየት፣ በዚያ ውስጥም ለመመላለስ የክርስትናችንን እና የመንፈሳዊነታችንን ጥልቀት ለመጨመር መሻት አለብን፡፡

ስለዚህ እስኪ እኛም በእነዚህ ሳምንታት የብሉይ ኪዳን ሰዎች የነበሩበትን ሁኔታ እየተዘከርን፣ እኛም ያለንበትን ሁኔታ እየመረመርን፣ ስላጣነው ብርሃን ለማሰብ፣ ያጣነውን መልሰን ማየትንና ማግኘትን ለመናፈቅ እንሞክር፡፡ መጻሕፍትን ለማንበብ፣ በጉዳዩ ላይ በተመስጦ ለማሰብ እና ለመወያየት ጊዜ እንውሰድ፡፡ ብርሃነ ልደቱን ለማየት እንዲያበቃን «አቤቱ ብርሃንህንና ጽድቅህን ላክ፤ ቸሩ እረኛችን ሆይ፣ ተቅበዝብዘናልና እባክህ ሰብስበን» እያልን እንፀልይ፡፡ ሰው ከነኃጢአቱ ወደ እግዚአብሔር ብርሃን ሊቀርብ /ሊያየው/ አይችልምና ራሳችንን በንስሃ እናድን፡፡ እነዚህን ቤተ ክርስቲያን ያስቀመጠችልንን የዝግጅት ጊዜያት በሚገባ ከተጠቀምን ትርጉም ያለው፣ በሕይወታችንና በመንገዳችን ላይ ለውጥ የሚያመጣ ልዩ የልደት በዓል እናከብራለን፡፡

አምላካችን ብርሃነ ልደቱን እንድንመለከት ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ስለ እመቤታችን ቤተመቅደስ መግባት

እህተ ፍሬስብሃት

 

ኢያቄምና ሐና የሚባሉ በተቀደሰ ትዳር የሚኖሩ የእግዚአብሔር ሰዎች ነበሩ፡፡ ሁለቱም እግዚአብሔርን የሚወዱ ደግ ሰዎች ነበሩ፡፡ ነገር ግን ሐና ልጅ መውለድ አትችልም ነበር፡፡ ልጅም ስለሌላቸው በጣም አዝነው ይኖሩ ነበር፡፡ ሁልጊዜ ወደ ቤተ እግዚአብሔር እየሄዱ ልጅ እንዲሰጣቸው ልመና ያቀርቡ ነበር፡፡ ለእግዚአብሔርም ልጅ ከሰጠኸን ለአንተ ብጽአት (ስጦታ) አድርገን እንሰጣለን ብለው ተሳሉ፡፡

 

እግዚአብሔርም ልጅ ሰጣቸው፡፡ ሐናም በግንቦት አንድ ቀን ከፀሐይ የምታበራ ሴት ልጅ ወለደች፡፡ ሕፃኗንም ማርያም ብለው ስም አወጡላት፡፡ ልጃቸው እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን በንጽህና ሲያሳድጉ 3 ዓመት ከሆናት በኋላ በተሳሉት ስእለት መሠረት ወደ ቤተ እግዚአብሔር መውሰድ እንዳለባቸው ተነጋገሩ፡፡ ለመንገድ የሚሆን ስንቅና ለቤተ እግዚአብሔር የሚሆን ስጦታ ሁሉ አዘጋጁ፡፡ 
 

ከዚያም ልጃቸውን ድንግል ማርያምን ይዘው ወደ ቤተመቅደስ ሄዱ፡፡በቤተ መቅደስ የካህናት አለቃ የነበረው ካህኑ ዘካርያስ ተቀበላቸው፡፡ሐና እና ኢያቄም ለእግዚአብሔር የገቡትን ቃል የተደረገላቸውንም ድንቅ ተአምር ነገሩት፡፡
 
ካህኑ ዘካርያስም ለእግዚአብሔር የገቡትን ቃል ባለመርሳታቸው እጅግ ተደሰተ፡፡ ነገር ግን ወዲያው አንድ ነገር አሳሰበው፡፡ምን መሰላችሁ ልጆች እመቤታችንን በዚያ በቤተመቅደስ ስትኖር ማን ይመግባታል ብሎ ነበር የተጨነቀው፡፡ 
 
ወዲያው ከሰማይ ቅዱስ ፋኑኤለ የተባለው መልአክ መጣ መልአኩ እመቤታችን አቅፎ በአንድ ክንፉ ከልሎአት ከሰማይ ያመጣውን ኅብስት እና መጠጥ መግቦአት እንደመጣው ሁሉ ወደ ሰማይ አረገ፡፡ካህኑ ዘካርያስና ህዝቡም እግዚአብሔር ምግቧን እና መጠጧን እንዳዘጋጀላት ተመለከቱ፡፡ካህኑ ዘካርያስ በፍፁም ደስታ እመቤታችንን ተቀብሎ ወደ ቤተ መቅደስ አሥገባት ይህ ዕለት ታኅሳስ 3 ቀን ሲሆን በዓታ ለማርያም ተብሎ በታላቅ ድምቀት ይከበራል፡፡

 

ልጆች እኛም በዓሉን በማክበር ከእመቤታችን በረከትን ማግኘት አለብን፡፡

ይህን ያውቁ ኖሯል?

የመነኮሳት ሕይወት

ምንም እንኳን የድንግልናና የምናኔ ኑሮ ቀደም ብሎ የተጀመረ ቢሆንም የምንኩስና መሥራችና አባት ቅዱስ እንጦንስ ነው፡፡ አባ እንጦንስ ግብፅ ውስጥ በምትገኝ ቆማ በምትባል ቦታ በ251 ዓ.ም ተወለደ፡፡ ወላጆቹ ሀብታሞችና ደጋግ ሰዎች ነበሩ፡፡ ከወላጆቹ ዕረፍት በኋላ የነበረውን ሀብት ለድሆች መጽውቶ መንኩሶ ብዙ ዓመት በብሕትውና ኖረ፡፡

በዚያን ጊዜ ብዙ ታምራትን ስለሠራ ሕዝቡ ግማሹ እሱን አይቶ ለማድነቅ የቀረው ደግሞ በእርሱ ጸሎት ለመፈወስ ወደነበረበት ቦታ ይጐርፍ ነበር፡፡ እርሱም በ356 ዓ.ም ዐረፈ፡፡

አባ ጳኩሚስ የተባለ ሌላው አባት በላይኛው ግብፅ ውስጥ ብዙ ገዳማትን በመሥራት የምንኩስናን ሕግና ሥርዓት በመወሰን ስለምንኩስና መስፋፋት ብዙ ደክሟል /290-347 ዓ.ም/፡፡ አንድ ቀን ወደ ዱር እንጨት ፍለጋ ሔዶ ሳለ የእግዚአብሔር መልአክ ተገለጸለትና እንደ አባቶቻችን ሐዋርያት የአንድነትን ማኅበር ለመሥራት መነኮሳትን እንዲሰበስብ አዘዘው፡፡ ብዙ አማኞች እየናፈቁት ማግኘት ያልቻሉትን ገዳማዊ ሕይወት ያገኙ ዘንድ ገዳም ለመመሥረት የሚስችለውንና የሚያስተዳድርበትን በነሐስ ላይ የተቀረጸ ሕግ ሰጠው፡፡ አባ ጳኩሚስም ከመልአኩ በተሰጠው ሕግ መሠረት የሚተዳደር ገዳም አቋቋመ፡፡ ይኸውም መነኮሳቱ ጠዋትና ማታ አብረው እንዲፀልዩ በአንድነት እንዲሠሩ ገቢና ወጪያቸው አንድ ላይ እንዲሆን በአንድነት እንዲመገቡ፣ ልብሳቸው አንድ አይነት እንዲሆንና እነዚህን የመሳሰሉትን ደንቦች አወጣላቸው፡፡ በዚህ መሠረት መነኮሳቱ የዕለት ምግባቸውን የሚያገኙት እየሠሩ ነበር፡፡ ከሴቶችም የምንኩስናን ሕይወት የጀመረች የአባ ጳኩሚስ እህት ማርያም ናት፡፡

ከዚህ በኋላ በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን ጀምሮ ምንኩስና በግሪክ፣ በሮም፣ በሶሪያና በሌሎችም ሀገሮችም እየተስፋፋ ሄደ፡፡

የምንኩስናን ሕይወት ወደ ኢትዮጵያ ያመጡ በ5ኛው መቶ ክፍለ ዘመን በጉባዔ ኬልቄዶን /በሃይማኖት ስደት/ ምክንያት ከቁስጥንጥንያ፣ ከግብፅ፣ ከሶርያ፣ ከሮም፣ ከአንጾኪያ ወደ ኢትዮጵያ የመጡ ዘጠኙ ቅዱሳን መነኮሳት ናቸው፡፡ ምንኩስና ከተመሠረተ ጀምሮ በየጊዜው ሕዝቡ ታላላቆችም ሳይቀሩ ወደ ገዳማቱ እየሄዱ ይመነኩሱ ነበር፡፡

ነገር ግን ከ9ኛው መቶ ዘመን ጀምሮ በማኅበር ከሚኖሩት መነኮሳት መካከል ጥቂቶቹ ቀስ በቀስ ለብቻ በተለየ ቤት መኖር እያንዳንዱ መነኩሴ ለብቻ በፈለገበት ጊዜ መብላትና መተኛት ስለጀመረ በየገዳማቱ የመነኮሳቱ ኑሮ በማኅበር የሚኖሩትና ለብቻቸው የሚኖሩት ለሁለት ተከፈሉ፡፡

የድንግልና መሠረቱ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ «ስለ መንግሥተ ሰማያት ሰውነታቸውን ጃንደረባ ያደረጉ አሉና፤ መፈጸም የሚችል ግን ይፈጽም» ሲል የተናገረው የሕግ ቃል ነው፡፡ ማቴ. 19፡12

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

/ምንጭ፦ ‘የዛሬዋ ኢትዮጵያ በመጽሐፍ ቅዱስ’ በዲ/ን አሐዱ አስረስ፣ ነሐሴ 1992 ዓ.ም/

ashetenKArsema.jpg

ጥንታዊው አሸተን ቅድስት አርሴማ ህንፃ ቤተ ክርስቲያን ህንፃን ለመሥራት ጥሪ ቀረበ።

በወ/ኪዳን  ወ/ኪሮስ
በስድስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን የተመሰረተችው የአሸተን ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን ህንፃ ለማሠራት እየተደረገ ባለው እንቅስቃሴ ምእመናኑን ድጋፍ እንዲያደርጉ ተጠየቀ።
ashetenKArsema.jpg

የቤተክርስቲያኒቱ አስተዳዳሪ አባ ወልደ ነአኩቶ ለአብ እንደገለጡት፤ ግራኝ አህመድ በኢትዮጵያ አብያተ ክርስትያናት የጥፋት ዘመቻ ባወጀ ጊዜ ካጠፋቸው ታላላቅ ገዳማት አንዱ የሆነው ይህ ታሪካዊ ቦታ፣ ቤተክርስቲያኑ ሲፈርስ የተወሰነው ነዋየ ቅዱሳቱ በአሸተን ቅድስት ማርያም ቤተክርስቲያን እንዲቀመጥ ሲደረግ ሌሎችን ቅርሶች ጠላት በማያገኝበት ዋሻ እንደደበቁት ይነገራል፡፡
ሕዳር 6 ቀን 2001 ዓ.ም በቦታው መቃኞ/መቀረቢያ/ ተሰርቶ የቅድስት አርሴማ ታቦት ገብቶ የአካባቢው ምእመን እየተገለገለ ይገኛል።

በአሁኑ ጊዜ የቤተክርስቲያኑን መሰረት ድሮ ቤተክርስቲያኑ ይገኝበት በነበረው ቦታ ላይ የወጣ ሲሆን ቀሪውን ሥራ አጠናቆ ለመጨረስ  በአካባቢው የሚገኘው ምእመናንም በኑሮ ዝቅተኛ ስለሆነ ገንዘብ ቢያዋጡም ቤተክርስቲያኑን ከፍጻሜ ለማድረስ አለመቻሉን አስተዳዳሪው ገልጸዋል፡፡

ashetenKArsema2.jpg

ህንፃ ቤተክርስቲያኑን ሥራ በገንዘብ ለመደገፍ ለምትፈልጉ የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ላሊበላ ቅርንጫፍ የአሸተን ቅድስት አርሴማ ቤተክርስቲያን የሒሳብ ቁጥር 40 ብላችሁ መላክ የምትችሉ መሆኑን ጠቁመዋል። 
 
በሰሜን ወሎ ሃገረ ስብከት ከቅዱስ ላሊበላ አብያተ ክርስቲያናት በኩል በስተመሥራቅ 6 ኪሎ ሜትር የእግር ጉዞ ከተጓዙ በኋላ ይህችን ጥንታዊ ቤተ ክርስቲያን ያገኟታል። አቀማመጧ ጉብታ ላይ ስለሆነ በአካባቢዋ ያሉትን የቅዱስ ላሊበላ አብያተ ክርስቲያናትንና አካባቢውን ለመቃኝት እጅግ የተመቸች ናት።

ashetenKArsema1.jpg

በስድስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን አባ ተክለ ፅዮን በተባሉ ቅዱስ አባት እንደተመሰረት የሚነገርለት ይህ ጥንታዊ ቤተክርስቲያን በ1929 ዓ.ም ጣሊያን ኢትዮጵያን በወረረበት ጊዜ የቤተክርስትያኑ ሊቃውንት ብዙ መከራ እንደደረሰባችው ይነገራል።

hall.jpg

በደብረ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ እና በመካነ ጎልጎታ ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ የእግር ጉዞ ተዘጋጀ።

በኪ/ማርያም ወ/ኪሮስ
 
hall.jpg የደብረ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ እና መካነ ጎልጎታ ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ እያሰራ ላለው የሰንበት ት/ቤት እና የስብከተ ወንጌል ሁለገብ አዳራሽ ታህሳስ 10 ቀን 2003ዓ.ም ከጠዋቱ 3፡30 ጀምሮ መነሻው መስቀል አደባባይ መድረሻው በደብረ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ ቤተክርስቲያን  የሚፈጸም  የእግር ጉዞ አዘጋጅተዋል።
  
 በዕለቱም ብፁአን ሊቃነ ጳጳሳት፣ታላላቅ የቤተክርስቲያን አባቶች፣ መምህራንና ዘማርያን፣ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ ጋዜጠኞች፣ አርቲስቶች እና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ይገኛሉ።

                    
“እርሶዎም እንዳያመልጦዎት አሁኑኑ ቲሸርቱን በ35 ብር በመግዛት ይጓዙ።” በማለት ደብረ ነጎድጓድ ቅዱስ ዮሐንስ እና መካነ ጎልጎታ ቅድስት ድንግል ማርያም ቤተክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ ጥሪያቸውን አስተላልፈዋል።

poster.jpg

“ህንፃው ግን ለእግዚአብሔር ለአምላክ ነው፤ ለሰው አይደለምና ሥራው ታላቅ ነው።”
                                                                    1ኛዜና መዋ 29፡1
ቲሸርቱ በደብሩ ንዋየ ቅዱሳት መሸጫ እና በደብሩ ልማት ጽ/ቤት ያገኛሉ።
ለበለጠ መረጃ
–    011-1-55-62-87
–    0911-15-44-47
–    0911-00-24-99
–    0911-11-69-56 ብለው ይደውሉ

styared.jpg

ቅዱስ ያሬድ በደብረ ታቦር ከተማ ተዘክሮ ዋለ

ደብረ ታቦርና ባህር ዳር ማዕከል
ሰንበት ትምህርት ቤቱ ለግቢ ጉባኤ ተማሪዎች አቀባበል አደረገ

«ዝክረ ቅዱስ ያሬድ» በሚል ርዕስ ከህዳር 11-12 ቀን 2003 ዓ. ም. ለሁለት  ቀናት የቆየ የሥዕል ዓውደ ርዕይና ሲምፖዚየም ተካሄደ፡፡ ዝግጅቱ የተካሄደበት ሰ/ት/ቤት አዲስ ለገቡ የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች አቀባበል አደርጓል። 
styared.jpg
በደብረ ታቦር ከተማ የተካሄደውን መርሐ ግብር ያዘጋጀው በማኅበረ ቅዱሳን የደብረታቦር ማዕከል ሲሆን ኢትዮጵያ በብሉይና በሐዲስ፣ የቅዱስ ያሬድ ማንነት፣ ቅዱስ ያሬድና አፄ ገ/መስቀል፣በመርሐ ግብሩ በመሪጌቶች በዜማ ገለጻ የተደረገባቸው 8ቱ የዜማ ምልክቶችና የዜማ መሣሪያዎች በሥዕል ዓውደ ርዕዩ የተካተቱ ሲሆን የአሁኑን ሐመረ ተዋሕዶ እትም የሽፋን ሥዕል በመጠቀም ያለውን የተሃድሶ እንቅስቃሴ እንዲሁም የማኅበረ ቅዱሳን አርማና እንቅስቃሴ ገለጻ ተደርጐባቸዋል፡፡

በተጨማሪም በከተማው በሚገኘው በቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤት አዳራሽ ተያያዥ መርሐ ግብር ተደርጓል፡፡ በዚህም በሰንበት ት/ቤቱ ሕፃናትና ወጣቶች መዘምራን እንዲሁም በግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች መዝሙሮች ቀርበዋል፡፡ የቅዱስ ያሬድን ሕይወት በተመለከተ፤ ዜማን በተመለከተም በግዕዝ ቋንቋ በሰንበት ት/ቤቱ ወጣቶች ጭውውት ቀርቧል፡፡ በመርሐ ግብሩ በርካታ ምዕመናን፣ የሰንበት ት/ቤቶች ወጣቶችና የግቢ ጉባኤያት ተማሪዎች ተሣታፊ እንደነበሩ ከሥፍራው የደረሠን ዘገባ ያስረዳል፡፡
 
ቀጥሎ ባለው ቀን የቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን ሰንበት ት/ቤት ለግቢ ጉባኤ ተማሪዎች የእንኳን ደህና መጣችሁ መርሐ ግብር በማዘጋጀት ተቀብሏቸዋል፡፡ በዕለቱ ሰንበት ት/ቤቱ ስለ አንዲት ቤተ ክርስቲያን በሕብረት መሥራት ይጠበቅብናል በማለት ለተማሪዎቹ መልዕክቱን አስተላልፏል፡፡
 
በተያያዘም፣ ስብከተ ወንጌልንና አጠቃላይ ሁኔታን በተመለከተ መስከረም 22 ቀን 2003 ዓ.ም. በባሕር ዳር ከተማ ውይይት ተካሂዷል።ውይይቱን ያዘጋጀው በማኅበረ ቅዱሳን የባሕር ዳር ማዕከል ሲሆን ለውይይቱ መነሻ ይሆን ዘንድ በማዕከሉ ስለ ስብከተ ወንጌል አጀማመርና ሂደት እንዲሁም አሁን ያለው ወቅታዊ ሁኔታ በጥናት መልክ ቀርቧል። ተሳታፊዎቹም በጉዳዩ ዙሪያ ጥልቅ ውይይት አካሂደዋል።
 
ተሳታፊዎቹ ስብከተ ወንጌልን በተመለከተ ወደ ፊት ከማዕከሉ ጋር አብረው ለመሥራት ቃል ገብተዋል። የማዕከሉ ሰባክያንም በየዓውደ ምህረቱ እየተገኙ አሁን እየታየ ያለውን ጉድለትና የስብከት መደጋገም ለማስቀረት በስብከት እንዲያገለግሉ ተጠይቀዋል።
 
በዕለቱም የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ሊቀ ጉባኤ ዘላለም ደስታና የወረዳ ቤተ ክህነት ሓላፊ መልአከ ብርሃን ፍስሐ ጥላሁንን ጨምሮ ከሀገረ ስብከቱና ከወረዳው ቤተ ክህነት እንዲሁም የየአድባራቱ ስብከተ ወንጌል ሓላፊዎችና ሰባክያን ተሳታፊ ሆነዋል።

ታቦት

እህተ ፍሬስብሐት

 ልጆች ታቦት ምን እንደሆነ ታውቃላችሁ?

ልጆች ታቦት ማለት የእግዚአብሔር ትዕዛዝ የተፃፈበት ቅዱስ ሰሌዳ ማለት ነው፡፡ በመጀመሪያ ታቦትን ከእግዚአብሔር እጅ የተቀበለው ሙሴ ነበር።

እስራኤላውያን በግብፅ በስደት ከኖሩ በኋላ በሙሴ መሪነት ወደ ሀገራቸው ወደ እስራኤል ጉዞ ጀመሩ፡፡ ብዙ ቀናቶችን ከተጓዙ በኋላ እረፍት አድርገው እግዚአብሔር ሙሴን ሲና  ወደተባለው ተራራ እንዲወጣ አዘው፡፡ ሙሴም ወንድሙ አሮን ህዝቡን እንዲጠብቅ አድርጎ ወደ ተራራው ወጣ፡፡ በተራራውም ላይ 40 ቀንና 40 ሌሊት ከፆመ በኋላ ከእግዚአብሔር እጅ ሁለቱን ታቦቶች ተቀበለ፡፡ በታቦቱ ላይም አስር የእግዚአብሔር ትዕዛዞች ተፅፈውበታል፡፡ እግዚአብሔር ታቦትን የሰጠበት ምክንያት ሌሎች ህዝቦች ጣኦትን ያመልኩ ስለነበር እስራኤላውያን ግን እግዚአብሔርን ስለሚያምኑ ሌሎች ህዝቦችን አይተው ጣኦት እንዳያመልኩ የእግዚአብሔር መንፈስ ያለበትን ታቦት እንዲያመልኩ ታቦትን ለሙሴ ሰጠው፡፡

ሙሴ ከሲና ተራራ ታቦታቱን ይዞ እስከሚመለስ እስራኤላውያኑ 40 ቀን መታገስ አቅቷቸው አሮንን አስገድደው ጣዖት ሠርተው ሲሰግዱ አገኛቸው። በዚህ ጊዜ ሙሴ ህዝቡ እግዚአብሔርን ትተው ጣኦትን በማምለካቸው በጣም ስለተናደደ ታቦቶቹን በጣኦቱ ላይ ጣላቸው እና ታቦቱም ጣኦቱም ተሰባበሩ፡፡ ሙሴ ታቦቶች በመሰባበራቸው በጣም አዘነ፡፡ እግዚአብሔርም የሙሴን ማዘን ተመልክቶ “የሰበርካቸውን አስመስለህ አንተ ራስህ ስራ እኔም እባርክልሃሁ” አለው፡፡ ሙሴም እንደታዘዘው ቅርፁን ከሰራ በኋላ እግዚአብሔርም እንደገና አስሩ ትዕዛዞችን በጣቶቹ ፃፈበት እና ባረከለት፡፡

ልጆች በሌላ ቀን ደግሞ የእግዚአብሔር አስሩ ትዕዛዞች ምን እንደሆነ እንነግራቹሀለን፡፡

የግቢ ጉባኤያት ማስተባበሪያ ክፍል እንቅስቃሴ ተጠናክሮ መቀጠሉ ተገለፀ።

ከማኅበረ ቅዱሳን ሕዝብ ግንኙነት ክፍል
በማኅበረ ቅዱሳን የሀገር ውስጥ ማዕከላትና የግቢ ጉባኤያት ማደራጃና ማስተባበሪያ ዋና ክፍል በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሥር እያስተማራቸው የሚገኙ ተማሪዎችን የክትትል እንቅስቃሴ አጠናክሮ መቀጠሉ ተገለፀ።
አቶ እንዳለ ደጀኔ፥ የግቢ ጉባኤያት ማስተባበሪያና ማጠናከሪያ ክፍል አስተባባሪ እንደተናገሩት፥ ማኅበሩ ተማሪዎችን ለማስተማር ሥርዓተ ትምህርት ቀርጾ 21 የመማሪያ መጻሕፍትን ያዘጋጀ ሲሆን፤ በአሁኑ ሰዓት ሥርዓተ ትምህርቱን ሙሉ በሙሉ በመከለስ የትምህርት አሰጣጥ ሥርዓቱን በማዘጋጀት ላይ ይገኛል።

ማኅበረ ቅዱሳን በግቢ ጉባኤያት የሚያስተምራቸውን ተማሪዎች ከግቢ ከወጡ በኋላ የሚጠበቅባቸውን ግዴታ እንዲወጡ ለማድረግ የክትትል መስመር ዘርግቶ እየተንቀሳቀስ ይገኛል። ተማሪዎች በሥራ ዓለም ላይ እያሉ በታማኝነት ሀገርን ማገልገል፣ ሕዝብና ሀገር የሚፈልጉባቸውን ግዴታዎች በጥሩ ሥነ ምግባር መወጣት፣ ቤተ ክርስቲያንን በሰንበት ትምህርት ቤትና በሰበካ ጉባኤ ተሣትፎ ማገልገል፣ ሀገርንና ቤተ ክርስቲያንን በገንዘብ፣ በዕውቀትና በጉልበት በማገልገል፤ ለሕዝብና ለወገን ጠቃሚ ዜጋ መሆን ከተማሪዎቹ የሚጠበቅባቸው ውጤት እንደሆነ አስተባባሪው ጨምረው ገልጸዋል።
አስተባባሪው አክለውም፥ አባላት በተለያየ ሙያ ላይ ሆነው ቤተ ክርስቲያንን እንዴት ማገልገል እንችላለን ለሚሉ ተማሪዎችም፥ በማኅበረ ቅዱሳን የሙያ አገልግሎትና አቅም ማጎልበቻ ዋና ክፍሉ ምላሽ ለመስጠት ዝግጁ እንደሆነ አስረድተዋል።
ማኅበሩ በአሁኑ ጊዜ ዕውቅና ያገኙ 171፥ በክትትል ላይ የሚገኙ 140፥ በድምሩ 311 ግቢ ጉባኤያትና በሥራቸው የሚገኙ ከ120,000 በላይ ተማሪዎችን እያስተማረ ይገኛል ።

debre_Tsege.jpg

የመነኮሳት አባቶች የጋራ መኖሪያ ቤት ተመረቀ

በደረጀ ትዕዛዙ
 
debre_Tsege.jpgበ ሰሜን ሸዋ ሰላሌ ሀገረ ስብከት በደብር ቅዱስ ደብረ ጽጌ ቅድስት ማርያም ገዳም የተሠራው የአረጋውያን አባቶች መነኮሳት የጋራ መኖሪያ ቤትና መጦሪያ ተመርቆ አገልግሎት መስጠት ጀመረ፡፡መንፈሳዊ ዕውቀት ሀብታቸውን ሲያካፍሉ የኖሩ አባቶችን ለመንከባከብ የተደረገው ጥረት የሚያስመሰግን መሆኑን ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ተናገሩ፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ በገዳሙ ተገኝተው የመነኮሳቱን መኖሪያ ሕንፃ መርቀዋል፡፡

 

በምእመናን፣ በበጎ አድራጊ ግለሰቦችና ድርጅቶች እንዲሁም በገዳሙ ትብብር ተሠርቶ ጥቅምት 21 ቀን 2003 ዓ. ም ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ እና ሌሎችም ብፁአን አባቶች በተገኙበት ለምረቃ የበቃው ይኸው የጋራ መኖሪያ ቤትና መጦሪያ ከአራት መቶ ሰባ ሺሕ ብር (400,000) በላይ ወጪ የተደረገበት ሲሆን ሃያ (20) አረጋውያን አባቶች መነኮሳትን ለመንከባከብ ያስችላል፡፡

መጦሪያ ቤቱን ባርከው የከፈቱት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ጳውሎስ ትርያርክ ርዕሰ ሊቀ ጳጳስ ዘ ኢትዮጵያ ሊቀ ጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለ ሃይማኖት፣ የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት ፕሬዘዳንት፣ የዓለም ሃይማኖቶች ለሰላም የክብር ፕሬዘዳንት እንደተናገሩት፤ «መንሳዊ ዕውቀታቸውን ሲያካፍሉ የኖሩ አባቶች ሲደክሙ ማረፊያና መንከባከቢያ ስፍራ መዘጋጀቱ ተገቢ እና ትውልዱ ሊከተለው የሚገባ ተግባር ነው፡፡» ብለዋል፡፡

ቅዱስ ሲኖዶስ በየጊዜው የሕፃናት ማሳደጊያ፣ የአረጋውያን መጦሪያና የጎልማሶች መማሪያ በየሀገረ ስብከቱ እንዲቋቋም የታዘዘ መሆኑን የጠቀሱት ቅዱስነታቸው፤ ሊቃነ ጳጳሳት ከመንፈሳዊ ልጆቻቸው ጋር በመሆን ይህንኑ ለማከናወን እየጣሩ መሆኑን ተናግረዋል፡፡ ለአረጋውያኑ አስቦ ኮሚቴው የድርሻውን ለመወጣት የሠራው በጎ ሥራ ለሌሎችም አርአያ የሚሆን መሆኑንም አስገንዝበዋል፡፡

የባሌ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ይስሐቅ በበኩላቸው፤ የደቀ መዛሙርት መገኛ በሆነው በዚህ ስፍራ አባቶች መነኮሳትን አስቦ ይህን በጎ ተግባር መፈጸም ቤተ ክርስቲያኒቱ የምትደግፈው የተባረከ ሥራ መሆኑን ተናግረዋል፡፡

አረጋውያኑ በገዳሙ ለረጅም ዘመን መንፈሳዊ አገልግሎት ሲፈጽሙ የነበሩ መሆኑን ጠቅሰው፤ የተደረገላቸው ድጋፍ የጸሎት ተግባራቸውን ለመቀጠል የሚያስችላቸው በመሆኑ ኮሚቴው ምስጋና ይገባዋል ብለዋል፡፡

የገዳሙ አበምኔት መልአከ ሰላም ቆሞስ አባ ገብረ ሥላሴ መስፍን አስተባባሪ ኮሚቴውን በመወከል ባቀረቡት ሪፖርት፤ በቅዱስነታቸው መልካም ፈቃድና መመሪያ መሠረት ሚያዝያ 30 ቀን 2000 ዓ.ም የተቋቋመው ኮሚቴ ዋነኛ ዓላማው የአረጋውያን አባቶች መነኮሳት መኖሪያ ቤት ማሠራት፣የዕለት ምግባቸውን ማቅረብ እና አጠቃላይ ጤንነታቸውን መንከባከብ ነው፡፡

በዚህ መሰረት ኮሚቴው ተግባሩን በአግባቡ እንደተወጣ የገለጡት አበምኔቱ አረጋውያን አባቶች ቀደም ሲል ያጋጠማቸውን ምግብ የማጣት ችግር ከማቃለል ጎን ለጎን አባቶችን የሚከባከብና ንጽሕናቸውን በመጠበቅ የሚያገለግል ሰው በመመደብ ችግራቸውን ለመፍታት ተችሏል ብለዋል፡፡ በዚህ ተግባርም አሁን በገዳሙ የሚገኙ አገልጋይ መነኮሳት አባቶች የበለጠ ተስፋ አግኝተው መንፈሳዊ አገልግሎታቸውን እንዲፈጽሙ እንዳበረታታቸው መገንዘብ እንደተቻለም አስረድተዋል፡፡

የአረጋውያኑ መጦሪያ ከመኖሪያ ክፍላቸው የመመገቢያ፣ የማብሰያ፣የመታጠቢያ የመፀዳጃ እና አዳራሽን ያካተተ መሆኑን በሪፖርቱ ተመልክቷል፡፡አረጋውያኑ እያንዳንዳቸው የየራሳቸው ክፍል ያላቸው ሲሆን አልጋ፣ ፍራሽ፣አንሶላ፣ ብርድልብስ፣ ጋቢ፣ የሌሊት ልብስ እንዲሁም ለመነኮሳት የሚሆን አልባሳት እንደተሟሉላቸው ተገልጧል፡፡

የገዳሙ አበምኔት አረጋውያኑን ለመደገፍ በተደረገው ጥረት ድጋፋቸውን ላደረጉ ለሀገረ ስብከቱ እና በጎ አድራጊ ምእመናን በልዑል እግዚአብሔር ስም ምስጋናቸውን አቅርበዋል፡፡

ወደፊትም አረጋውያኑን በገንዘብ ለመደገፍ ለሚሹ የደ/ቅ/ደብረ/ጽጌ ቅ/ማሪያም የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ አራት ኪሎ ቅርንጫፍ የባንክ ሒሳብ ቁጥር 0173036575400 ቢልኩ እንደ ሚደርስ ተናግረዋል፡፡

ወደ አረጋውያኑ መጦሪያ የገቡ አንዳንድ መነኮሳት አባቶች በሰጡት አስተያየት በጸሎትና በምስጋና ቀሪ ዕድሜያቸውን እንዲያሳልፉ የተመቸ ቦታ ማግኘታቸው እንዳስደሰታቸውም ተናግረዋል፡፡

የ85 ዓመት ዕድሜ ባለፀጋ የሆኑ አባ ወልደ ትንሳኤ በሰጡት አስተያየት፤በገዳሙ ለሠላሳ ሦስት ዓመታት በቅዳሴ መምህርነት ሲያገለግሉ መኖራቸውን ጠቅሰው ዛሬ በደከማቸው ጊዜ ደጋፊ ማግኘታቸው እጅግ እንዳስደሰታቸው ተናግረዋል፡፡ ሌሎች አባቶችም በተሰጣቸው ክብር እግዚአብሔርን ሲያመሰግኑ፣ለሕዝቡና ለሀገሪቱ ሰላም በመጸለይ እነደሚተጉ ተናግረዋል፡፡

ገዳሙ በብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ባስልዮስ በ1938ዓ.ም ከተመሠረተ ጀምሮ በርካታ  ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያንን ማፍራቱ ይታወቃል፡፡

«በአዳም ምክንያት ሁላችን እንደምንሞት፣ እንዲሁም በክርስቶስ በኲርነት ሁላችን እንነሣለን፡፡» 1ኛ ቆሮ. 15፥22

                            ክፍል አራት

በጸጋ እግዚአብሔር አምላኩ የከበረ ይህ ሐዋርያው ጳውሎስ ትምህርቱን የበለጠ ተቀባይነት ያለው ለማድረግ  ብርሃነ እግዚአብሔር ኦሪትን ለሐዲሱ ምስክር እያደረገ ያስተማምናል፡፡ስለሆነም «ነሥአ መሬተ ወገብሮ ለእጓለ እመሕያው ወነፍሐ ላዕሌሁ መንፈሰ ሕይወት፤እግዚአብሔር አዳምን ከምድር ዐፈርን ወስዶ ፈጠረው፡፡ የሕይወትንም እስትንፋስ አሳደረበት፡፡»ብሎ መጽሐፍ እንደተናገረ በዚች ነፍስ ሕይወትነት የሚኖር ሥጋ አስቀድሞ መፈጠሩን ይገልጽና፤ከትንሳኤ ዘጉባኤ በኋላ ግን መንፈስ ቅዱስ ሕይወት ሆኖት የሚኖር ሥጋ እንደሚገኝ /እንደሚነሳ/ ለአጽንዖተ ነገር ደጋግሞ ይናገራል፡፡ ዘፍ 2÷7

ከዚህም አንጻር «በነፍስ ሕያው ሆኖ የሚኖር ቀዳማዊ አዳም አስቀድሞ ተገኝቶአል፡፡ በመለኮታዊ ሕይወት ሕያው ሆኖ የሚኖረው ዳግማዊ አዳም ክርስቶስ ከአምስት ሽሕ አምስት መቶ ዘመን በኋላ በአዳም ባሕርይ ተገኝቶአል፡፡» ብሎ ቅደም ተከተሉን ከአሳየ በኋላ በትንሳኤ ዘጉባኤ የሚነሳ የመጀመሪያው ሰው የአዳም ዘር ሁሉ መሬታዊ እንደሆነ እንደ ሰማያዊው የባሕርይ አምላክ ክርስቶስም ሰማያዊ እንደሚሆን ያረጋግጣል፡፡በትንሳኤ ዘጉባኤ የሰው ልጅ ሁሉ የሚያገኘውን የተፈጥሮ መዓርግ መሬታዊ አዳም መምሰልን በስሕተቱ፣ በኀጢአትና በሞት ሀብቱ፣ ገንዘቡ እንደ አደረገ ሁሉ፤ ሰማያዊ ክርስቶስ መምሰልንም በዘለዓለም ሕይወትና በጸና ቅድስና ሀብቱ ገንዘቡ ያደርጋል፡፡ እያለ በሙታን ትንሳኤ ጥርጥር ያገኘባቸው የቆሮንቶስ ምእመናን ደቀ መዛሙርቱን ልባቸውን በተስፋ ሕይወት ይመላዋል፡፡ምክንያቱም ተስፋ መንግሥተ ሰማያትን ሥርየተ ኀጢአትን ያገኘ ክርስቲያን ክርስቶስን የሚመስልበት ምስጢር ትንሳኤ ዘጉባኤ ነውና ይህም መንግሥተ እግዚአብሔርን ሀገረ ሕይወትን ለመውረስ በክብርና በቃለ ሕይወት ተጠርቶ የሚቆሙበት ዐደባባይ ዳግም ልደት ነው፡፡ፊል 3÷20-22 ፣እርሱን የሕይወት ባለቤት ክርስቶስን የመምሰል ታላቁ ቁም ነገርና የማያልቅ ጥቅም በእርግጥም ይህ እንደሆነ ከሐዋርያው መልእክተ ቃል እነሆ እንረዳለን፡፡ ይህን ለመረዳትም የዕውቀትና የማስተዋል ባለቤቱ እርሱ መድኃኒታችን ስለሆነ ፈቃዱን በተሰበረ ልቡና ዘወትር መጠየቅ ታላቅ ብልኅነት ነው፡፡

እነሆ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ አንደበተ ርቱዕ ጥዑመ ልሳን ሆኖ በትምህርተ ወንጌል ለደከመላቸው ወገኖች በቁጥር 50ኛ መልእክቱ «ወንድሞቻችን ይህ ሥጋዊ ደማዊ ሰው መንግሥተ ሰማያትን አይወርስምና ይህን አውቄ እነግራችኋለሁ፡፡»በማለት ይህ ሟች፣ ጠፊ ኃላፊ፣ ፈራሽ፣ በስባሽ ሥጋ በመቃብር ታድሶ ካተነሳ ሕያው ማሕየዊ መንፈስ ቅዱስን ገንዘቡ ሀብቱ እንዳያደርግ ያውቁ ዘንድ ሳይታክት ያስገነዝባቸዋል፡፡ ሞት ርስተ አበው ሆኖ ለሁሉ የሚደርሰው ይህ ኃላፊ ጠፊ ሥጋና ደም ተለውጦ የማይጠፋ ሕያው ሆኖ ለትንሳኤ ዘጉባኤ እስኪደርስ ነው ስለሆነም የሞትን ኃይል ኀጢአትን እንጂ ሞትን ሳንፈራ ትንሳኤ ሙታንን በጽኑ ተስፋ መጠበቅ ይገባናል፡፡ቅዱስ ጳውሎስ የትንሳኤን ሁኔታ ሲያስረዳ «ናሁ ኅቡአ ነገረ እነግርክሙ ፤ እነሆ ስውር ረቂቅ ሽሽግ አሁን የማይታወቅ ነገርን እነግራችኋላሁ፤የሰው ልጆች ሁላችንም ሞተን በስብሰን ተልከስክሰን የምንቀር አይደለም፡፡» «ወባሕቱ ኲልነ ንትዌለጥ በምዕር ከመ ቅጽበተ ዐይን በደኀሪ ንፍሐተ ቀርን፤በኋለኛው የዐዋጅ ቃል እንደ ዐይን ጥቅሻ ፈጠነን ከዚህ ተፈጥሮአችን ወደ አዲስነት እንለወጣለን፡፡» ብሎ ከአስታወሰ በኋላ የሦስተኛ ደረጃ ዐዋጅ በተነገረ ጊዜ ሙታን ከቁጥራቸው ሳይጐድሉ፤ አንዲት አካል ሳይጐድላቸው እንደሚነሡ ገልጦ ያስረዳል፡፡ ይህ ሓላፊ ጠፊ ሥጋችን የማይጠፋ የማያልፍ ሆኖ በመለወጥ ማለት ሕያው መንፈስ ቅዱስን ገንዘቡ፣ ሀብቱ በማድረግ ለዘለዓለም ሕይወት ይነሳል ማለት ነው፡፡ይህ ጸጋና በረከት ለሰው የተጠበቀው ጥንቱን ለሕይወት በፈጠረው ቸሩ አምላክ እግዚአብሔር ነው፡፡ ሰው ግን ከሕያውነት ኑሮው ወደ ሞት ጐራ ገብቶ ስለነበር በጥንተ ተፈጥሮ ታድሎት የነበረው በሕይወት መኖር ይመለስለት ዘንድ እግዚአብሔር ወልድ በተለየ ስሙ፣ በተለየ አካሉ፣ በተለየ ግብርና ኩነቱ /አካኋኑ ኹኔታው/ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ ክሶ፣ ሙቶና ተቀብሮ በመነሳት እነሆ የዘለዓለም ሕይወትን በትንሳኤ ዘጉባኤ ያድለዋል፡፡

ትምህርቱን አጠናክሮ ለመፈጸም በተገለጠው ምዕ.በቁ. 54 ላይ «ወአመ ለብሰ ዝንቱ መዋቲ ዘኢይመውት፤ ይህ ሟች የሆነ ሥጋ ከትንሳኤ በኋላ ተለውጦ የተነሳ የማይሞት የሆነውን ሥጋ በለበሰ ጊዜ» ከአለ በኋላ እነሆ! ሞት በመሸነፍ ባሕር ጠለቀ ሰጠመ ተብሎ በልዑለ ቃል ነቢይ የተነገረው ቃል ይፈጸማል፣ይደርሳል፡፡ ይህም ሞት ሆይ ድል መንሳትህ ወዴት አለ? መቃብርስ ብትሆን ሰውን ይዘህ ማስቀረትህ ወዴት ነው? አለ የሞትም ኀይሉ ብርታቱ ኀጢአት ሲሆን፣ የኀጢአትም አበረታች ትእዛዛተ ኦሪት ናቸው፡፡ አለ፡፡ ኀጢአት፣ ኀጢአትነቱ የታወቀው በሕገ ኦሪት ደጉ ከክፋው፣ ክፉውም ከደጉ ተለይቶ በመደንገጉ፣ በመገለጡ መሆኑን ሲያመለክት ነው፡፡ ምንጊዜም ሕግ ሥርዐት መውጣቱ በተላላፊው ወገን ላይ የጥፋት ነጥብን አስቆጥሮ ፍርድን ሊያስከትል፣ ከፍርድ በኋላም ቅጣትን ለማምጣት እንደሆነ ይህች ሕግ ልኩንና ተጨባጭ ማሰረጃን አፍሳ በነሲብ ስለምትሰጠን ለልቡናችን ይደምንብናል ማለት አይቻልም፡፡ዕውቅ ነው፡፡ ኢሳ 25÷8፣ ሆሴ 13÷14፣ሮሜ 13÷19 እንዲህ ስለተደረገለን ፣ እንዲህም ስለሚደረግልን «ወለእግዚአብሔር አኮቴት ዘወሀበነ ንማዕ በእግዚእነ ኢየሱስ ክርስቶስ በጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቤዛነት ከሰው ምክንያት ይኸው እንግዲህ በርኅርኅት ሕገ ወንጌል ኦሪትን፣ በጽድቅ በእውነተኛ ንስሐ ኀጢአትን፣በትንሳኤ ሞትን ድል እንነሳ ዘንድ ድል ማድረጉን የሰጠን ሁሉን ያዥ ሁሉን ገዥ እግዚአብሔር አምላክ ይክበር ይመስገን፡፡»በማለት የምግበ መላእክት ስብሐተ እግዚአብሔር ፍጹም ተሳታፊነቱን አንጸባርቆ ገለጠው፡፡በመልእክቱ ማጠቃለይም «እርስ በርሳችሁ የምትዋደዱ እግዚአብሔርን የምትወዱ እርሱም የሚወዳችሁ ወንድሞቻችን ሆይ! ብርቱዎች ሁኑ፤ በማናቸውም ሥራ ሁሉ ዝግጁዎች ሁኑ»ብሎ ሲያበቃ ከላይ እንደታተተው፣እንደተዘረዘረው ከሃይማኖታቸው እንዳይናወጡ፣ እግዚአብሔርን ለማገልገል፣ ሁልጊዜ ከሕጋዊው ሥራ ላይ የትሩፋት ሥራን አብዝተው እንዲሠሩ የትንሳኤ ሙታን ደገኛ የክብር የዋጋ የጽድቅ ማግኛውን ምስጢር ገልጦ ያስረዳቸዋል፡፡»ይልቁንም በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ከማመናቸው የተነሳ የተቀበሉት መከራ ሁሉ ከገለጠላቸውና ከአረጋገጠ በኋላ በሃይማኖታቸው መሠረትነት የጽድቅ መልካም ሥራን አብዝተው እንዲሠሩና ለክብር ትንሳኤ እንዲበቁ እንዲዘጋጁም በፈሊጥ ከልቡ ይመክራቸዋል፣ያስተምራቸዋል፤ ያንጻቸዋል፡፡ 2ኛ ዜና መዋ 15÷7 ፣2ኛ ጴጥ 1÷5፡፡ለባስያነ ኀይለ እግዚአብሔር /የእግዚአብሔር ኀይሉን እንደሸማ የተጐናጸፋችሁ/ ክርስቲያኖች ሆይ! አክሊለ መዋዕ የድል አክሊል ሀብተ መንፈስ ቅዱስን የተቀዳጀው ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስ በቆሮንቶስ ሰዎች አንጻር እንዳስገነዘበን «በአዳም በደል ምክንያት ሁላችን እንደምንሞት፣ እንዲሁም በክርስቶስ ካሳና በኩርነት ሁላችንም እንነሳለን፡፡»በሚል ርእስ «ርእሱ ለአእምሮ፤ የዕውቀት መገኛዋ»የሆነ መድኅነ ዓለም ክርስቶስ በማይመጠን ቸርነቱ በገለጠልን መጠን የምስጢረ ትንሳኤን እሙንነት ይኸው አብራርተን አቅርበናል፡፡ ተስፋው እንደሚፈጸም አምኖ ለመጠባበቅ በርትቶ በማስተዋል ደጋግሞ ማንበቡ ግን የእናንተ ፈንታ ይሆናል፡፡በመሆኑም የሙታን ትንሳኤ መነሳት ወይም አነሳሥ ለተለየ አዲስ ሕይወት ነው፡፡ በዓለመ ሥጋ ምንም ምን አይመስለውም፡፡ይህንም ራሱ ባለቤቱ መድኀኒታችን በዘመነ ሥጋዌው «ወአመሰ የሐይው ምውታን ኢያወስቡ፣ወኢይትዋሰቡ፣ አላ ከመ መላእክተ እግዚአብሔር በሰማያት እሙንቱ፣ ሙታንስ በሚነሡበት ጊዜ አያገቡም፤ አይጋቡም፤ እነርሱ በሰማያት እንደ እግዚአብሔር መላእክት ሆነው ይኖራሉ እንጂ፡፡»በማለት በሕያው ቃሉ የሰጠው ትምህርት በግልጥ ያስረዳናል፡፡ በጌታችን መዋዕለ ሥጋዌ የነበሩ የእምነት መሪዎች፤ በዘመናችንም ብጤዎቻቸው «ሙታን ከተነሡ በኋላ ለዘለዓለም አግብተው እንደሚኖሩ በመስበክ እያስጐመጁ ለያዙት ሃይማኖት ማስፋፊያ አድርገውት ይገኛል፡፡ ይህን አጉልና ከንቱ ሽንገላ ለይቶ በማወቅ ወደ ዕውነት መመለስ፣ ጸንቶ መኖርም በመንፈስ ቅዱስ መቃኘት ነው፡፡ 2ኛ ቆሮ 11÷13-16 ኤፌ 5÷6 ከትንሳኤ ዘጉባኤ በኋላ መብላት መጠጣት የመሳሰለው ሰብአዊ ግብር የለም ጌታችን ከትንሳኤው በኋላ በቅዱሳን ሐዋርያት ፊት የበላው ምግብ አስፈልጐት አይደለም በምትሐት ነው ብለው እንዳይጠራጠሩና ትንሳኤውን እንዲያምኑ ማስረጃ ይሆናቸው ዘንድ ነው፡፡ሉቃ 24÷14-44

መላልሰን እንዳስገነዘብነው ትንሳኤ ዘጉባኤ የክብር የሚሆነው ከዳግም ዘለዓለማዊ ሞት የዳኑ እንደሆነ ብቻ መሆኑ የሚካድ አይደለም፡፡ይህም ዳግም ሞት የሰው ከእግዚአብሔር መለየት እንደሆነ ይታወቃል፡፡ በመጽሐፈ አበው «ሞታ ለነፍስ ርኂቅ እም እግዚአብሔር ፤ የነፍስ ሞቷ ከእግዚአብሔር መለየቷ ነው፡፡» እንደተባለው ነው፡፡

በአስተዋይ ልቡና ሊተኮርበት የሚገባው ምን ጊዜም የሕይወት ባለቤት እግዚአብሔር የባሕርይ ጐዳናው ምሕረትና ቸርነት ብቻ እንደ ሆነ ከምእመናን ንጹሕ ልብ ሊደበቅ አይገባውም፡፡መዝ 24÷10 የክብር ጌታ ኢየሱስ ክርስቶስም ትንሳኤውን ለመላው ዓለም አብርቶ የገለጠው የሰው ሁሉ ትንሳኤ ያለጥርጥር የታወቀ የተረዳ ይሆን ዘንድ ነው፡፡ ግበ.ሐ. 26÷23

ከላይ በመልእክቱ ማእከል እንደተገለጸው በሰው ሁሉ አባት በአዳም በደል የሰው ልጅ በሙሉ ሞተ፡፡ በእርሱ በባሕርይ አምላክ ክርስቶስ ሰው ሆኖ ካሰ እነሆ! መላው የሰው ልጅ ከሞት ከመርገም ዳነ፡፡ የጌታችን ካሳ የራሱ አለማመን ከሚገድበው በስተቀር ማንንም ከማን አይለይም፡፡ዮሐ 3÷36፤ 5÷24 ሮሜ 5÷12-19 በጌታችን ምስጢረ ሥጋዌና ነገረ አድኅኖት አምኖ መጠመቅ ከእርሱ ጋር ተቀብሮ የመነሳት ምስጢር ነው፡፡የትንሳኤ ሙታንም ምልክት ይሆናል፡፡መድኃኒታችንን አምነው ለተቀበሉት ዋጋቸው የሆነ ልጅነትን ይሰጣቸዋል፡፡ በልጅነታቸውም እርሱ እንደተነሳበት ባለ ሥልጣኑ ትንሳኤ ዘለክብርን ያስነሳቸዋል፡፡ በትንሳኤያቸውም የዘለዓለም መንግሥቱ ሀገረ ሕይወትን ያወርሳቸዋል፡፡ ዮሐ. 1÷13፣ ሮሜ 1÷5፡፡

ይህን የትንሳኤ ሙታን ተስፋ ለሰው ሁሉ ተግቶ ያለፍርሃት መመስከር ክርስቲያናዊ ግዳጅ ነውና አምነን በማሳመኑ ሥራ ልንበረታ ይገባናል፡፡ሲራ 4÷20-29፣ 1ኛ ተሰ 4÷18

በገነት በመንግሥተ ሰማያት የማይሰለች ተድላ ደስታ እንጂ ሐዘንና መከራ የለም፡፡ኢሳ 49÷10

ይህን ታላቅ ምስጢር ዐውቀን በሕያው ቃሉ መመራት በእጅጉ ይገባናል፡፡ይህንም በልቡናችን፣ ከመምህራነ ወንጌል፣ ከቅዱሳት መጻሕፍት ተምረን ተመራምረን አምነን ለትንሳኤ ዘለክብር እንድንበቃ በቸርነቱ ይርዳን፡፡