አይቴ ብሔሩ ለግእዝ?

 

ግእዝ የማን ቋንቋ ነው? የካም ወይስ የሴም ቋንቋ የሚለው የብዙዎች ምሁራን ጥናት እና ጥያቄ እየሆነ መጥቷል፡፡ ግእዝን የሴም የሚያደርጉት የሶቢየት ምሁራን ኤቢ ዶጎልስኪ /A.B. Dogopolsky/ እና ኢጎር ዲያኮኖፍት /Igor Diaknoft/ ግእዝ የደቡብ ሴማዊ ልሳን ሳይሆን በዐረብ ምድር የመጀመሪያዎቹ የአፍሪካውያን ወይም የኩሻውያን ቋንቋ ነው ይላሉ፡፡

 

የዚህን ወገን ሐሳብ የሚጋሩት ደግሞ ቸክ አንተ ዲዮፕ /Cheik Anta Diop1919/ «ተርሰሃሌ» ጥበቡ፣ «አቤንጃ»፣ ኃይሉ ሀብቱ /1987/፣ አስረስ የኔሰው፣ ሺናይደር /1976/ እና አየለ በክሪ/1997/ ወዘተ ናቸው፡፡ ለዚህ ከሚጠቀሱት ምክንያቶች ዋና ዋናዎቹ ከአፍሮ እስያ ቋንቋዎች ብዙዎቹ የሚገኙት በኢትዮጵያ ነው የሚል ሲሆን በተጨማሪም በጣም ብዙ ቋንቋዎች በተለያዩ ቡድኖች በተቀራረበ እና በተወሰነ መልከዓ ምድር ስለሚነገሩ ነው፡፡

 

መርቶኔን /A.Murtonen/ ግእዝን ሴማዊ /ከኢትዮጵያ የወጣ/ ቋንቋ ነው የሚል አቋም አላቸው፡፡ ሊኦኔል ቤኤንደርም በተመሳሳይ ሁኔታ፡፡ ከዚህም አልፈው ግእዝን የአዳም ቋንቋ፤ የመላዕክት ቋንቋ የሚሉት አልጠፋም፡፡ ምንም እንኳን የካም ወይም የሴም ብለው ቢከፍሉትም፡፡ ተጠቃሾቹም ሲዲ ጳውሎስና አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ናቸው፡፡

 

«ሴማዊ ነው»፡፡ የሚለውን ሐሳብ ቢቀበሉትም የግእዝ ተናጋሪዎቹ እነማን እንደነበሩ አላውቅም የሚሉት ጌታቸው ኃይሌ ናቸው፡፡

 

በአንጻሩ ካም ወይም ሴም የሚለውን ቃል ከቋንቋ ጋር በማገናኘት የተጠቀመበት የጀርመን መልእክተኛ ጆህን ሊዊድግከፈ /Johunn Luowigkapf1810-1881/ ነው፡፡ ከርል ፍሬድሪክ ሌፐሲየስ /Karl Freidrich Lepsius/ ካምን ሴማዊ አይደለም ይላል፡፡ ከቋንቋ ጥናት በመነሳት ነው ይህን ሊል የቻለው፡፡ ይሁን እንጂ በአሁኑ ሰዓት ያለው የሥነ ልሳን ጥናት ከሐረገ ዘር ይልቅ መልክዐ ምድራዊ በመሆኑ የካምጠሴም ቋንቋ መባሉ ቀርቶ በአፍሮ እስያነት ውስጥ በአጠቃላይ የሚታይ ነው ይላል ዮሴፍ ግሪን በርገ /Joseph Green berg/፡፡ የዮሴፍ ግሪን በርገ /Joseph Green berg/ ሐሳብ የዚህን ጽሑፍ አቅራቢ ሐሳብ የተስማማ ነው፡፡

 

የዚህ ጽሑፍ አዘጋጅ ካለው ግንዛቤ የተነሣ የኢትዮጵያን ቋንቋ ግእዝን አፍሪካዊ የኢትዮጵያ ልሳን ውልደቱን እና እድገቱን ኢትዮጵያ አድርጎ በዘመነ ባቢሎን ሊነገር የሚችል ዓለም ዓቀፋዊና ጥንታዊ ልሳን ነው ብሎ ያምናል፡፡ የግእዝ የመጀመሪያ ጽሑፍ በ500 ቅ.ል.ክ የተጻፈ ሲሆን በአናባቢ መጻፍ የተጀመረው ግን በ4ኛው መቶ ዓ.ም ነው፡፡ ይህንንም በተከታይዮች አርእስተ ነገር ላይ ለማሳየት እንሞክራለን፡፡

የግእዝ ቋንቋ ፡ –

ሀ. የጽሕፈት ዘዴ አቡጊዳ
ለ. የጽሕፈት አቅጣጫ ከግራ ወደ ቀኝ አግድም /ከሳባ የሚለይበት ነው/
ሐ. እያንዳንዱ ፊደል በአናባቢ የተገለጸ እና አናባቢ የሌለው ሆኖ ሊጻፍ የሚችል ዓለማቀፋዊና ጥንታዊ ልሳን ነው ብሎ ያምናል፡፡
   

3 የግእዝ ቋንቋ ፊደላትና ትርጉም፡-
    

የግእዝ ቋንቋ ፊደላት የራሳቸው መለያ ትርጉም ሥዕላዊ መገለጫ ያላቸውና ከጥንት ጀምሮ ከጥቅም ላይ የዋሉ መሆናቸውን ያስረዳሉ፡፡ የግእዝ ቋንቋ መሠረታዊ ድምጾችን ሳይለቅ ከዘመን ዘመን በሚደረገው የሥነ ጽሕፈት ልውጠትም አዳዲስ ፊደላትን ለመፍጠር ያስቻሉ ፊደላትን ይዟል፡፡ እነዚህ ፊደላትም ለአፍሪካ እንደመሠረትነት ያገለገሉ ከመሆናቸውም በላይ ለአሁኑ የሥነ ጽሑፍ ሀብታችን መሠረቶች ናቸው፡፡ ፊደላቱ በአናባቢ ተዋሕደው ቃላትን ሊወልዱ ቋንቋን ሊያበለጽጉ ችለዋል፡፡ የራሳቸው የሆነ ቅርጽ እና ፍቺም ያልተለያቸው ናቸው፡፡

ነዛሪ የጉሮሮ እግድ – አ – አሌፍ አልፍ አብ
ነዛሪ የከናፍር ፈንጂ – በ – ቤት ባዕል
ነዛሪ የትናጋ ፈንጂ – ገ – ጋሜል ገምል
ነዛሪ የጥርስ ፈንጂ – ደ – ዳሌጥ ዳ/ን/ልት
ነዛሪ የጉሮሮ ፍትግ – ሀ – ሆይ ሆይ ሀወይ
 
የከናፍር ትናጋ ደኃራይ – ወ – ዋው ዋዌ ዋሕድ
ነዛሪ የጥርስ ፍትግ – ዘ – ዘይ ዛይ
ኢነዛሪ የማንቁርት ፍትግ – ሐ – ሔት ሐወት ሕያው ሕይወት
ነዛሪ የትናጋ ፍትግ – ኀ – ኀርም ኄር
ኅዩል ኢነዛሪ የጥርስ ፈንጂ – ጠ – ጤት ጠይት ጠቢብ
ቅሩብ የከናፍር ትናጋ ደኃራይ – የ – ዮድ የማን
ኢነዛሪ የትናጋ ፈንጂ – ከ – ከፍ ከሃሊ
ጎናዊ – ለ – ላሜድ ለዊ ልዑል
ከናፍራዊ ወአንፋዊ – መ – ሜም ማይ ምዑዝ
የጥርስ ወአንፋዊ – ነ – ኖን ነሐስ ንጉሥ
ኢነዛሪ የጥርስ ፍትግ – ሠ – ሣምኬት ሣውት
ነዛሪ የማንቁርት ፍትግ – ዐ – ዐይን ዐቢይ
ኢነዛሪ የከንፈር ፈንጂ – ፈ – ፈፍ ፈቁር
ኀዩል ኢነዛሪ የጥርስ ፍትግ  – ጸ – ጻዴ ጸደቅ ጻድቅ
ፀ – ፀጰ

ኀዩል ኢነዛሪ የትናጋ ፈንጂ – ቀ – ቆፍ ቅዱስ
የድድ ተርገብጋቢ – ረ – ሬስ ራእስ
ኀዩል ኢነዛሪ የጥርስ ፈንጂ – ሰ – ሳን ስቡሕ
ኢነዛሪ የጥርስ ፈንጂ – ተ – ታው ተዊ ትጉህ
ነዛሪ የከንፈር ፈንጂ – ጰ – ጰይት ጴት
ኢነዛሪ የከንፈር ፈንጂ – ፐ – ፐ ፌ
    

ከላይ እንዳየነው የግእዝ ፊደላት ቢሆኑም ቋንቋ ምንጊዜም በለውጥ ስለሚሄድ ስለሚወልድ እና ስለሚረባ ሌሎች ልዩ ልዩ ድምጾችን እንደፈጠረ እንረዳለን፡፡ ለዚህም የ «ሰ»ን ድምጽ የመሰለ «ሠ» የ«በ»ን ድምጽ የመሰለ ፐ እና ጰ ሌሎችም በየዘመናቱ ሲፈጠሩ ከመግባቢያነት አልፈው በሥነ ጽሑፍ ደረጃ ታሪክን አስቀምጠዋል፡፡ በተለይም ዛሬ የማይነገሩ «ደ»ን የመሰለ ደ፣ ዘ የጠበቁ.. ወዘተ በየዘመናቱ እንደነበሩ የሥነ ልሳን ጥናቶች ያስረዳሉ፡፡ የግእዝ ፊደላት ትርጉም እና ሃይማኖታዊ ምስጢ ብቻ ሳይሆን ሥዕላዊ መገለጫዎች እንደነበሩት መዛግብት ያስረዳሉ፡፡ ፊደላቱም በሥዕልነት ብቻ ሳይሆን መሠረተ አኀዝ መሆናቸውንም እንመለከታለን፡፡ ምሳሌ አ አልፋ ሲባል የበሬ ቀንድ እንደሚመስል አልፋም በላሕም ተተክቶ በመ.ቅ ይገኛል፡፡ ምሳሌ፡- አባግዐኒ ወኩሎ አልሕምተ ሲል መዝ. 8.7 በዕብራይስጥ ጾጊ ወአላፊም ይላል /ኪ.ክ/፡፡ ጥናት እንደሚያመለክተውም ላሕም ልሔም /እንጀራ/ ከእብራይስጥ ቃል የተወሰደ እና ከአላፊም ቦታ የገባ መሆኑን የሚጠቁም የሥነ ጹሑፍ መረጃ ይገኛል፡፡ ጋሜል ገመል /አባ ገሪማ የሚገኝ ወንጌል እንደ ሚያስረዳው/፡፡ ከፍ የሚለው ቃልም በትንቢተ ሕዝቅኤል ምዕራፍ 1.7 እግሮቻቸው ከፍ ያሉ እግሮች ነበሩ የእግራቸውም ኮቴ እንደ ጥጃ ኮቴ ነበር ሲል ጥጃ ከፍ መሆኑን ያመለክታል፡፡ በተጨማሪም ዮድ በቀኝ እጅ፣ ነ በእባብ፣ መ በውኀ ሞገድ፣ ዐ በዐይን፣ ፈ በአፍ፣ ረ በራስ፣ ተ በመስቀል፣ በ በቤት… መመሰላቸው ፈጣሪ ለሰው ልጅ ራሱን በሚታይ ነገር ከመግለጽም በላይ የፊደላትን ትርጉም ብቻ ሳይሆን ነገረ ድኅነትንም በመስቀል ምልክት በታው/ተ መደምደሙን ያሳየናል፡፡ በግእዝ ፊደላት የድምጽ ለውጥን በማድረጋቸዉ ከጊዜ ብዛት ትርጉማቸዉ ሲዛባ እና ሥዕላዊ መገለጫቸው በተወሰነ ደረጃ ጎድሎ የዘፈቀደ ትርጉም ሊሰጣቸዉ ይችላል፡፡ ምሳሌ «ጥ»ሽ «ት» ወይም «ት»ሽ «ጥ» በመለወጥ ትርጉም ሊሰጥ ይችላል፡፡ በአንጻሩም በቋንቋው የድምጽ ትርጉም ሊሠራላቸው እና ከአንድ በላይ የተለያዩ ትርጉም ሊኖራቸዉ መቻሉ የማይቀር ነው፡፡ የፊደላቱ መለዋወጥ ግን ትርጉም የሚያበላሽ ምስጢር የሚያፋልስ መሆኑ የተረዳ ነው፡፡ ይኽንኑ ለመግለጽ ሊቁ አለቃ ኪዳነ ወልድ «መዝገብ ፊደል» በተባለው መጽሐፋቸው እንዲህ ብለዋል፡፡

እንዳገኙ መጣፍ በድፍረት በመላ
የቋንቋ ደረመን የመጽሐፍ ቢስ ገላ
ንባብ የሚያሳክክ ምስጢር የሚቆምጥ
መልክአ ትርጓሜ የሚለዋውጥ፡፡
   

ይህን ማለታቸውም የፊደል ቁጥር ማጉደሉ፣ ምስጢር ማበላሸቱ ሥርዓተ ልሳን ማፋለሱ አንድና ብዙ ሩቅና ቅርብ ሴትና ወንድ አለመጠንቀቁ ጸያፍነቱና ግዴለሽነትን በማምጣቱ ነው፡፡ ለዚህም መፍትሔ ይሆን ዘንድ ታላቁ ሊቅ መልአከ ብርሃን አድማስ ጀምበሬ በመልእክታቸው ሊቃውንቱ ተስማምተው ጉባኤ ሠርተው ሊወያዩበት ይገባል ብለዋል፡፡ የፊደላቱ ምንነትና ምስጢር ሊጠፋ የቻለው እንደነ መልአከ ብርሃን አባባል የጽሕፈት ትምህርት ቤት ባህልና ትውፊት መረሳቱና ጸሓፍያን ለፊደላት ትርጉም ሳይጨነቁ ለቅርጽ ማማር ብቻ ትኩረት መስጠታቸው ነውና ይኽንኑ ሥርዓት ባለቅኔዎችም ባለማስተዋል ለቤት መምቻ ውበት መጠቀማቸው ነው፡፡

 

የግእዝ ፊደላት ለአኀዝ መሠረት ናቸው ስንል የምናነሳው ዝምድናቸውን ሲሆን ለምሳሌ የግእዝ 6 7 ቁጥሮች «-» ምልክት ሳይኖራቸዉ ይገኛሉ፡፡

የግእዝ ቁጥሮች መሠረታቸው ፊደል ነው፡፡ ስንል እንደ ፊደሎችም ቁጥሮች ከዘመን ዘመን ቅርጻቸዉን መልካቸውን ሲለዋውጡ እና የአሁኑን መልክ ሲይዙ ይታያሉ፡፡ በአጠቃላይም ቋንቋው የራሱ የሆነ ሥርዓተ ነጥብ የሥነ ጸሑፍ አካሄድ የምንባብ አጀማመር እንዳለው ይታወቃል፡፡