ክፉ ለሚያደርጉባችሁ ሰዎች መልካምን አድርጉ::

በአዜብ ገብሩ

በአንድ ወቅት ሳኦል የሚባል የእስራኤላውያን ንጉሥ ነበር፡፡ ይህ ንጉስ በዳዊት ላይ እጅግ ይቀናበት ነበር፡፡ ምክንያቱም ዳዊት ፍልስጤማዊው ጎልያድን ስላሸነፈ እስራኤላውያን በጣም ወደውት ነበር፡፡ ታዋቂም ሆኖ ነበር፡፡ ሳኦልም እግዚአብሔር እርሱን ትቶ ከዳዊት ጋር እንደሆነ ማሰብ ጀመረ፡፡ ስለዚህ በተለያየ ጊዜ ዳዊትን ለመግደል ሙከራ ያደርግ ነበር፡፡

 

አንድ ጊዜ ሳኦል የጦር ሰራዊቱን አስከትሎ ዳዊትን ለመግደል ፍለጋ ጀመረ ሳኦል ሳያውቅ ዳዊት ከሰራዊቶቹ ጋር የሚተኛበትና የሚሸሸግበት ዋሻ ስር ተኛ፡፡ ዳዊት ግን በዋሻው ውስጥ ተደብቆ ነበር፡፡ ሳኦልንም አየው፤ ልጆች እናንተ ዳዊትን ብትሆኑ ምን ታደርጉ ነበር? ዳዊት ግን ሳኦልን ሳይገድለው በተኛበት የልብሱን ጫፍ ቆርጦ ወሰደ፡፡ ሳኦልም ከእንቅልፉ ሲነቃ በተኛበት ጊዜ የተፈጠረውን ነገር ምንም አላወቀም፡፡ ዳዊትም ከኋላው ልብሱን እንደቆረጠበት ነገረው፡፡ ሳኦልም አለቀሰ፤ እጅግም አዘነ፡፡ ምክንያቱም ዳዊት እርሱን መግደል ሲችል ስላልገደለው ነው፡፡ ለዳዊትም እንዲህ አለው ‹‹ከእኔ ይልቅ አንተ ፃድቅ ነህ፤ እኔ ክፉ ሳደርግብህ አንተ ግን ክፉ አላደረግህብኝም፤ ስለዚህ ለእኔ ስላደረግኸው ቸርነት እግዚአብሔር መልካሙን ይመልስልህ’’ አለው:: ከዚህም በኋላ ሳኦልና ዳዊት ይቅር ተባባሉ፡፡

አያችሁ ልጆች እኛም ልክ እንደ ዳዊት የእግዚአብሔር ልጆች ስለሆንን ሁሉንም ሰው መውደድ አለብን፡፡ ክፉ ያደረጉብንን፣ የማይወዱንንና ሊጎዱን ያሰቡ ሰዎች ይቅር ማለት አለብን አንድ ሰው ክፉ ሲያደርግብንም እኛ ግን ያንን ሰው ይቅር ልንለውና ልንወደው ይገባል፡፡ የእግዚአብሔር ልጆች ከሆንን ሰዎችን የምንወድና ለሰዎች የምንራራ መሆን አለብን፡፡