በዓለ ሢመቱ ለሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል

ቅዱስ ኤጲፋንዮስ ሚካኤል ሥዩም በዲበ ኃይላት፤ በኃይላት ላይ የተሾምክ ሚካኤል ሲል ያመሰገነው ቅዱስ ሚካኤል በኃይላት መላእክት ላይ የተሾመ ሊቀ መላእክት እንደመሆኑ በዓለ ሢመቱ ኅዳር ፲፪ ቀን በመላው የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በድምቀት ይከበራል፡፡ (መጽሐፈ አክሲማሮስ)

ኃይላት የተባሉት መላእክትም ሰዎች በዓለም ፈተና ውስጥ ሆነው ሰይጣን ሊያደክማቸው ሲፈልግ ኃይልን ብርታትን የሚሰጡ፣ ይህን ዓለም ንቀው በበርሃ ወድቀው ከሥጋ ምኞት ጋር የሚጋደሉትን፣ በከተማም እየኖሩ መንፈሳዊ ትሩፋት የሚያደርጉትን ደግሞ የሚያበረቱ ናቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ በመልእክቱ እርሱም ወደ ሰማይ ያረገ እግዚአብሔርም ተቀምጦ ያለ መላእክትና ሥልጣናት ኃይላትም የተገዙለት ነው… ሲል  ኃይላትበማለት ያነሣቸው በኢዮር አራተኛይቷ  ከተማ  የሚኖሩትን  ነው፡፡ በእነዚህ ላይ እግዚአብሔር  ቅዱስ ሚካኤልን አለቃቸው አድርጎ ሾሞታል፡፡ (፩ኛጴጥ.፫፥፳፪)

የቅዱስ  ሚካኤል  ሢመት  በነገደ  መላእክት  ላይ ብቻም ግን  አይደለም፤  የእግዚአብሔር  ሕዝብ  በሆኑት  ላይም ጭምር ነው፡፡ ኃያሉ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል የስሙ ትርጓሜ በዕብራይስጥ ‹‹እንደ እግዚአብሔር ያለ ማን ነው!›› ማለት እንደሆነ ቅዱሳት መጻሕፍት ይጠቅሳሉ፤ አለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ በመዝገበ ቃላት መጽሐፋቸው ላይ እንዳሰፈሩት ደግሞ የስሙን ፊደላት በመተንተን እንዲህ ተርጉመውታል፤ ሚ-መኑ፣ ካ-ከመ፣ ኤል-አምላክ፤ ‹‹መኑ ከመ አምላክ፤ እንደ አምላክ  ማን ነው!›› (መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ)

የሰማይ ሠራዊት ሁሉ አለቃቸው  ለፍጥረት ሁሉ የሚማልድ  ይህ ኃያል መልአክ  ቅዱስ  ሚካኤል በብሉይ  ኪዳን  የእግዚአብሔር  ሕዝብ  የተባሉትን  እስራኤል  ዘሥጋን  ሲረዳና  ሲጠብቅ  እንደነበረ ተጽፎልን  እናገኛለን፡፡  ለምሳሌ  መልአኩ  ቅዱስ  ሚካኤል  ለኢያሱ  በኢያሪኮ  ምድረ  በዳ  እንደተገለጠለት  ‹‹… ዐይኑን  አንሥቶ  ተመለከተ፤  እነሆም፥  የተመዘዘ  ሰይፍ  በእጁ የያዘ  ሰው  በፊቱ  ቆሞ አየ፤  ኢያሱም  ወደ  እርሱ  ቀርቦ፥  ከእኛ  ወገን  ወይስ  ከጠላቶቻችን  ወገን  ነህ?  አለው፡፡  እርሱም እኔ  የእግዚአብሔር  ሠራዊት  አለቃ  ነኝ፤  አሁንም  ወደ  አንተ መጥቼአለሁ፡፡ሲል ተናግሯል፡፡ (ኢያ.፭፥፲፫)

እግዚአብሔር አምላክ ሕዝበ እስራኤልን ከግብጽ ባርነት ነፃ ሲያወጣቸው ይመራቸው የነበረ መልአክ ቅዱስ ሚካኤል ነበር፡፡ ‹‹ በመንገድህ ይጠብቅህ ዘንድ፥ ወዳዘጋጀሁልህም ስፍራ ያገባህ ዘንድ፥ እነሆ ፥እኔ መልአኬን በፊትህ እልካለሁ››  እንዲል፤  ሹመቱ  በእግዚአብሔር  ሕዝብ  ላይም  በመሆኑ  ስለ  እነርሱ ከእግዚአብሔር ምሕረትን ይለምንላቸው  ነበር፡፡ (ዘፀአት.፳፫፥፳)

ነገር ግን ኃጢአት ሲሠሩ እግዚአብሔር ኃጢአተኞችን ይቀጣልና ሕዝቡን  ‹‹ራስህን ጠብቅ፤ ስማው፤ እንቢም አትበለው፤ ስሜ በእርሱ ስለሆነ ይቅር አይልምና›› ብሎ  አስጠንቅቋቸው  ነበር፤   ይህም   ቅዱስ  ሚካኤል  በእግዚአብሔር  ሕዝብ  ላይ  መሾሙን  ያስረዳናል፡፡  (ዘፀ.፳፫፥፳፩)

ቅዱስ ገብርኤል በእግዚአብሔር  ሕዝብ  ላይ  ቅዱስ ሚካኤል  ስለመሾሙ ሲመሰክር ‹‹በእውነት   በመጽሐፍ   የተጻፈውን   እነግርሃለሁ፤   በዚህም  ነገር  ከአለቃችሁ  ከሚካኤል  በቀር   የሚረዳኝ  ማንም  የለም›› ብሎአል፡፡  ስለዚህም  ለኢያሱ   የተገለጠውና  እስራኤላውያንንም  የመራው  መልአክ  ቅዱስ  ሚካኤል  መሆኑን እንረዳለን፡፡ (ዳን.፲፥፳፩)

የቅዱስ ሚካኤል አማላጅነት በሐዲስ ኪዳንም እንደነበር ይህ ነቢይ በትንቢቱ ‹‹በዚያም ዘመን ስለ ሕዝብህ  ልጆች  የሚቆመው  ታላቁ  ሚካኤል  ይነሣል›› በማለት  ተናግሮለታል፡፡   ስለዚህም   ቅዱስ  ሚካኤል   እኛን  ከሰይጣን  አሽክላና  ወጥመድ  ይጠብቀንና  በጸሎቱ  በእግዚአብሔር  ፊት  ይቆምልን  ዘንድ  በእኛም  ላይ  ሹም  ነው፡፡ ምክንያቱም  እኛ  የእግዚአብሔር  ሕዝቦችና  የርስቱ ወራሾች ነንና፡፡  (ዳን.፲፪፥፩)

በመጽሐፈ ስንክሳርም ተመዝግቦ እንደምናኘው ቅዱስ ሚካኤል በየወሩ በዐሥራ ሁለት ቀን ለመታሰቢያው በዓል ተሠርቶለታል፤ እርሱ ስለ እኛ የምድሩን ፍሬ ይባርክልን ዘንድ ዝናሙም በጊዜው እንዲወርድልን የወንዙንም ውኃ እንዲመላልን ነፋሱንም የምሕረት ነፋስ እንዲያደርግልን ሁሉንም የተስተካከለ እንዲያደርግልን ወደ እግዚአብሔር በጸሎት ይማልዳልና፡፡ (ስንክሳር ኅዳር ፲፪)

ስለሆነም በኃጢአት ባርነት ተይዘን በችግር እና በመከራ ውስጥ ተዘፍቀን ለምንኖር ሰዎች ስለ  ሕዝበ  እስራኤል  በእግዚአብሔር  ፊት  የቆመው  ሊቀ  መላእክት  ቅዱስ  ሚካኤል  ለእኛም  ያማልደንና ተራዳኢ ይሆነን ዘንድ በጸሎት እንማጸነው።  አምላካችን  እግዚአብሔርም  የምሕረት  ፊቱን  ወደ  እኛ  በመመለስ በጸብና  በጦርነት  ምትክ  ፍቅርን፣  ሰላምንና  መግባባትን፤  በመለያየት  ምትክ አንድነትን እንዲሰጠን በቅዱስ ሚካኤል ስም እንለምን።

የሊቀ መላእክት  ቅዱስ  ሚካኤል  አማላጅነትና ተራዳኢነት  አይለየን፤  አሜን፡፡

ምንጭ፤ መጽሐፈ አክሲማሮስ፣ መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ በአለቃ ኪዳነ ወልድ ክፍሌ ፣መጽሐፈ ስንክሳር ዘወርኀ ኅዳር