«ስለ ሰላም ጸልዩ» (ሥርዓተ ቅዳሴ)

ሰዎች በሕይወታችን ውስጥ እጅጉን ከሚያስፈልገን ነገር ዋነኛው ሰላም ነው፡፡ ያለ ሰላም  መኖር አይቻልንም፡፡ ሰላም  የተረበሹትን ያረጋጋል፤ ያዘኑትን ያጽናናል፤ ጦርነትን ወደ ዕርቅ ይለውጣል፡፡

ሰላም በፍለጋ ብቻ የሚገኝ ሳይሆን በተግባር የሚተረጎም ነውና በሰላም የኖሩት ሰላምን በተግባር ያረጋገጡ ብቻ ናቸው፤ ምክንያቱም ሰላም ተግባራዊ ስለሆነ ነው፡፡ ሰላምን በተግባር ለማዋል ደግሞ ሰላምን መሻት ቅድሚያ የሚሰጠው ነገር ነው፡፡

ሰላም ማለት «ፍጹም፣ ጤና፣ ዕረፍት፣ ዕርቅ፣ ፍቅር፣ አንድነት፣ ደኅንነት፣ ተድላ፣ ገጽታ፣ ሰላምታ፣ የቡራኬ የምርቃት ቃል፣ ሰው ሲገናኝ ሲለያይ የሚለው የሚናገረው ወይም የሚጽፈው ማለት ነው» ብለው ኪዳነ ወልድ ክፍሌ በመዝገበ ቃላቸው ላይ ቃላዊ ትርጉሙን አስቀምጠውታል፡፡ (መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ ገጽ- ፰፻፹፰)

ሰላም ያለው ሰው ፍቅር አለው፤ ዕረፍት ያገኛል፤ ጤነኛም ይሆናል፡፡  እነዚህን ነገሮች ለማግኘት ሰላምን መሻት፣ በሰላም መኖር ያስፈልጋል፡፡ «ቢቻላችሁስ በእናንተ በኩል ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ» በማለት ቅዱስ ጳውሎስ ያስተማረንም ለዚህ ነው፡፡ (ሮሜ ፲፪፥፲፰)

ቅዱስ ጳውሎስ በሮሜ መልእክቱ ሲያስረዳን የሰው ልጅ ከማንኛውም ሰው ጋር በሰላም መኖር ክርስቲያናዊ መገለጫው እና ሥነ ምግባሩ እንደሆነ ገልጿል፡፡ ሰላምን የምናገኘውም ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም መኖር ስንችል ብቻ ነው፡፡ ከሌሎች ጋር ሰላም ከሌለን ሰላማችንን የምናጣው ከሰዎች ጋር ባለን ማኅበራዊ ግንኙነት ብቻ አይደለም፡፡ ከልደታችን እስከ ሞታችን ድረስ አብሮን በሚኖረው ማንነታችንም ውስጥ ነው፡፡ ከሰው ጋር ብቻ ሳይሆን ከራሱ ጋር ተጣልቶ የሚባዝን፣ ለራሱ ሰላምን የነሣ ብዙ ሰው አለና ሰላምን መሻት፣ ሰላማዊ መሆን ከራስ ጋር በመታረቅ ይጀመራል፡፡

በተለያዩ የመገናኛ ብዙኃኖች እንደምንገነዘበው በተለያዩ ጊዜያት ዓለም በሰላም እጦት ስትናጥ ቆይታለች፡፡ በዚህም የተነሣ ብዙ ሰው ሠራሽ ንብረቶች ከማለቃቸው በተጨማሪ እጅግ ክቡሩና በአምሳለ እግዚአብሔር የተፈጠረው የሰው ልጅ እንደ ተራ ነገር በየሜዳው ወድቆ ቀርቷል፡፡ በሀገራችንም በተለያዩ ጊዜያት በሥልጣን፣ በሃይማኖትና በበሽታ እንዲሁም በተለያዩ ምክንያቶች ብዙ የሰው ሕይወት በሰላም ተከፍተው የነበሩ በሮች በሞት ተዘግተዋል፡፡ ምድራችን በደም ታጥባለች፣ አረጋውያን ያለ ጧሪ ቀባሪ ቀርተዋል፤ ሕፃናት ያለ አሳዳጊ ብቻቸውን ሆነዋል፡፡

በየቤታችን በየጓዳችን ስንመለከት ተኳርፎ፣ ተበጣብጦ፣ ፍቅርን አጥቶ የሚያድረው ብዙ ሰው ነው፡፡ ይህ ሁሉ አለመረጋጋትና መባዘን የሚመጣው በሰላም ማጣት ብቻ ነው፡፡ ያለ ሰላም መኖር እንቅልፍ እንኳን ያሳጣል፡፡ ሰላም ያለው ሰው ግን በእግዚአብሔር ተባርኮ መልካም እንቅልፍ መተኛት ይችላል፤ በሰላም ወጥቶ በሰላም ይገባል፡፡ የሰው ልጅ በእምነት ኖሮ፣ ሠርቶ የሚገባው፣ አንቀላፍቶ የሚነሣው ሰላም ሲኖረው ብቻ ነው፡፡ «በእርሱ በሰላም እተኛለሁ፥ አንቀላፋለሁም፤ አቤቱ፥ አንተ ብቻህን በተስፋ አሳድረኸኛልና» እንዲል (መዝ. ፬፥፰)

ሰላምን የምታስተምር ቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ኵላዊት ናትና ለዓለም ሁሉ የሰላም አርአያ መሆኗ የታወቀ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያን ሰላም የሚታየው ደግሞ በእኛ በልጆቿ ነው፡፡ ነገር ግን በውስጣዊም ይሁን በውጫዊ ምክንያት የእኛ የልጆቿ ሰላም ሲደፈርስ የቅድስት ቤተ ክርስቲያንም ሰላም ይደፈርሳል፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የሰላም እመቤት የሰላም ተምሳሌት ናት፡፡ የራሷን ሰላም አስከብራ ለሌሎችም አርአያ በመሆን ዘመናትን አሳልፋለች፡፡ ነገር ግን ዘመናትን ባሳለፈች ቊጥር በሰላም ፈላጊነቷ የማይደሰተው ጠላት ዲያብሎስ ሁልጊዜም ቢሆን ሰላሟን ለመንሳት ተኝቶ አያውቅም «የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዘመኑ የተለያዩ ፈተናዎች የተፈራረቁባት ሲሆን ቤተ ክርስቲያኒቱ የእግዚአብሔር ማደሪያ ናትና የመጣውን የፈተና ጎርፍና ነፋስ ሁሉ ተቋቁማ  አሁን ላለንበት ዘመን ደርሳለች፡፡ የዐላውያን ገዥዎችን ሰይፍ፤ ከውስጥም ከውጭም የነበሩ መናፍቃንን ቅሰጣ ተሻግራ እስከ አሁን የሐዋርያት፣ የቅዱሳን ሊቃውንትን የአትናቴዎስን፣ የቄርሎስን ሃይማኖት ይዛ ተገኝታለች» ተብሎ የተጻፈውም ለዚህ ነው፡፡ ይህ የሚያሳየው ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በተለያዩ የፈተና ወጀቦች ስትታመስ ብትኖርም የሰላም መርከብ ናትና አለመውደቋን ነው፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ሁልጊዜም ቢሆን «ጸልዩ በእንተ ሰላም፤ ስለ ሰላም ጸልዩ» እያለች ለሁሉም ሰላም እንደሚያስፈልግ ለዘመናት ሰብካለች፡፡ ለቤቷም ሰላም እንደሚሻት ስታስተምር «ጸልዩ በእንተ ሰላመ ቤተ ክርስቲያን፤ ስለ ቤተ ክርስቲያን ሰላም ጸልዩ» እያለች ልጆቿን ትመክራለች፡፡ ይሁን እንጂ በሰላም ማጣት ምክንያት እንደ እናት ቤተ ክርስቲያን የችግር ገፈት ስንቀምስ መቆየታችን የቅርብ ጊዜ ትዝታ ብቻ ሳይሆን አሁን ያለው እውነታ ነው፡፡ (ሥርዓተ ቅዳሴ)

ስለ ቤተ ክርስቲያን ሰላም መጸለይ ስለ ምእመናን ስለ ሕዝብ መጸለይ ነው፡፡ ስለ ሕዝብ መጸለይ ደግሞ ስለ ሀገር መጸለይ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያንን ሰላም መሻት የአንድን ምእመን ሰላም መሻት ነው፤ ቤተ ክርስቲያን ማለት የምእመናን ኅብረትና እያንዳንዱን አማኝ የሚመለከት ነውና፡፡ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ለሁሉም ድኅነትና ሰላም ትጸልያለች፡፡ ሌላው ይቅርና ቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስለ እናት ሀገራቸው ሲሉ በየበረሃው ያሉ ሀገር ጠባቂዎችን የማትዘነጋ ርኅሩኅ እናት ናት፡፡ «ዕቀብ ሕዝባ ወሠራዊታ ለሀገሪትነ ኢትዮጵያ፤ የኢትዮጵያ ሀገራችንን ሕዝቦቿንና ሠራዊቷን ጠብቅላት» እያለች በዘወትር የቅዳሴ ሥርዓቷ የምትጸልየው በዚህ ምክንያት ነው፡፡ (ሥርዓተ ቅዳሴ)

እግዚአብሔር አምላክ ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በደሙ ሲመሠርታት ጠብን ጥልን ክርክርን በሞቱ ገድሎ፣ በደሙ አንጽቶ ነው፡፡ ይህ ለዓለም ሰላም የተከፈለ ዋጋ፣ ለድኅነታችን የተሰጠ ስጦታ፣ ለሰላም የተጠራንበት መንገድ ነው፡፡ አይሁድ ክርስቶስን በጥላቻ ሲገርፉትም እርሱም  በትሕትና የተገረፈው ሰላምን ለማምጣት ነው፡፡ የተቅበዘበዘው፣ ሰላም ያጣው፣ በሞት ጥላ ሥር የነበረው ዓለም፤ መዳንንና ሰላምን የሚያገኘው በክርስቶስ ሞት በክርስቶስ መስቀል ነበርና፡፡ የቤተ ክርስቲያን ብርሃን የሆነው ቅዱስ ያሬድ «ገብረ ሰላመ በመስቀሉ፤ በመስቀሉ ሰላምን አደረገ» በማለት የተናገረው ለዚህም ነው፡፡ (መጽሐፈ ድጓ)

ይህ ሁሉ ዋጋ የተከፈለለትን ሰላም በተግባር አለመኖር ዋጋ ያስከፍላል፡፡ በክርስቶስ ሞት የተሰጠንን ሰላም በከንቱ መጣል የክርስቶስን ዋጋ እንደ ማቃለል ይቆጠራል፡፡ ክርስቶስ በመስቀሉ ለዓለም የሰጠውን ሰላም ገንዘብ አለማድረግ የመስቀሉን ስጦታ አለመቀበል ነው፡፡ በቅዱስ መጽሐፍ እንደተገለጠው የተጠራነው በፍቅር በሰላም ልንኖር ነውና ሰላም ገንዘባችን ሊሆን ይገባል፡፡

«ወንድሞች ሆይ፥ በመካከላችሁ የሚደክሙትን፥ በጌታችን የሚቆሙላችሁንና የሚአስተምሩአችሁንም ዕወቋቸው ብለን እንማልዳችኋለን፡፡ እጅግ አክብሩአቸው፤ ስለ ሥራቸውም ውደዱአቸው፤ እርስ በርሳችሁም በሰላም ሁኑ» ብሎ ቅዱስ ጳውሎስ እንደተናገረው ሰዎችን በሥራቸው እያከበርን፣ ግሣጼንና ምክርን እየተቀበልን፣ ከጥፋታችን እየታረምን በሰላምና በፍቅር መኖር ይጠበቅብናል፡፡ ይህንን ስናደርግ በሰላም መኖራችን ዕረፍት ያሳጣቸው አካላት ቢኖሩ እንኳን እኛ የሰላምን ጥሪ ማዳመጥ፣ የሰላምን ደወል መስማት፣ መንገዷንም መከተል ይገባናል፡፡ ራሳችን ሰላማዊ ሁነን ዓለምንም በፍቅር ልናሸንፍ የምንችለው ይህ ሲሆን ነው፡፡ (፩ኛተሰ.፭፥፲፪-፲፫)

በሰዎች ፍቅር እንዲሠርጽ፣ መግባባት እንዲኖር፣ መረዳዳትና መከባበር እንዲመጣ በመንፈሳዊ ተቋማት በኃላፊነት የሚገኙ ሰዎች ሰላምን ማስተማር አለባቸው፡፡ የሀገር መሪዎች የሰላም አስከባሪ ሲሆኑ ተመሪው ሕዝብ ሰላምን ይከተላል፡፡ የሃይማኖት አባቶች የሰላም ሰባኪ ሲሆኑ ምእመናን የሰላም ባለቤት ይሆናሉ፡፡ ተመሪ ሁልጊዜም ቢሆን መሪውን ያያል፡፡ ሰላማዊ መሪ እንደ ሙሴ ባሕር ከፍሎ ሕዝቡን ያሻግራል፡፡ ሰላም የሌለው መሪ ደግሞ እንደ ፈርዖን እስከ ሠራዊቱ ይሰጥማል፡፡ ሕፃን የአባቱንና እናቱን እንዲሁም የታላላቆቹን አርአያ ይዞ እንደሚያድግ ሕዝብም መሪዎቹን፣ አባቶቹን ይከተላል፡፡ የተከፋፈለ መሪ የተከፋፈለ ሕዝብን ያፈራልና፡፡

እግዚአብሔር አምላክ ሰላሙን ይስጠን፤ አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፤ መጽሐፈ ሰዋስው ወግስ ወመዝገበ ቃላት ሐዲስ ገጽ- ፰፻፹፰፣ሥርዓተ ቅዳሴ፣ መጽሐፈ ድጓ፣ ሐመር መጽሔት ፳፭ ዓመት ቊጥር ፭ እና ፳፮ ዓመት ቊጥር