‹‹ሁሉ በአግባቡ እና በሥርዓቱ ይሁን›› ፩ኛ ቆሮ.፲፬፥፵ (ክፍል አንድ)
በዲ/ን ታደለ ሲሳይ
ጊዜ ገቢር ለእግዚአብሔር እንዲል እግዚአብሔር ሁሉንም ነገር የሚሠራበት ጊዜ አለው፡፡ ዓለምን ሲፈጥር፣ ሙታንን ሲያስነሣ፣ ድዉያንን ሲፈውስ፣ የተሰደዱትን ሲመልስ፣ ያዘኑትን ሲያረጋጋ እርሱ ጊዜ አለው፡፡ ሁሉንም በጊዜው ውብ አድርጎ ሠራው እንዲል ለሥራው ሁሉ ጊዜ አለው፡፡ የሰው ልጅም በእግዚአብሔር የተፈጠረ፣ እርሱ የሠራለትን ሥርዓት ተከትሎ የሚኖር እንደመሆኑ ለእንቅስቃሴው ሁሉ ጊዜ አለው፡፡ የሰው ልጅ በጨለማ የኖረበት ጊዜ አለው፤ በብርሃን ውስጥ ያለፈበትም ጊዜ አለው፡፡ የሰው ልጅ በድንቁርና የኖረበት ጊዜ አለ፤ በዕውቀት ብርሃን የተመላለሰበት ጊዜ አለ፡፡ የሰው ልጅ በጥበብ ሰክኖ ፈጣሪውን ያመሰገነበት ጊዜም አለው፡፡ የሰው ልጅ ባልተጻፈ ሕግ የተመራበት ጊዜ አለው፤ በተጻፈ ሕግም የተመራበት ጊዜ አለው፡፡