‘‘እርስ በርሳችሁ ትዋደዱ ዘንድ ትእዛዜ ይህች ናት’’(ማቴ. ፲፭፥፲፪)

በመ/ር ኃይለ ሚካኤል ብርሃኑ

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እውነተኛ የወይን ሐረግ ስለመሆኑና አምነው የተከተሉት ሁሉ ደግሞ ቅርንጫፎች እንደሆኑ በብዙ ምሳሌ ካስረዳ በኋላ ከላይ በርዕስ የተነሣንበትን ቃል ተናግሯል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነግረን ቃል በቃል ስንመለከተው “እኔ እንደወደድኋችሁ እርስ በርሳችሁ እንድትዋደዱ የእኔ ትእዛዜ ይህች ናት፣ ስለ ወዳጆቹ ሕይወቱን አሳልፎ የሚሰጥ ሰው ያለ እንደሆነ ከዚህ የሚበልጥ ፍቅር የለም፤ እናንተስ ያዘዝኋችሁን ሁሉ ካደረጋችሁ ወዳጆቼ ናችሁ” (ዮሐ.፲፭፥፲፪-፲፭) ይላል፡፡

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ እኛ እርስ በእርሳችን እንዋደድ ዘንድ እንደሚገባ ከማዘዙ አስቀድሞ እርሱ እኛን የወደደበትን ፍጹም ፍቅሩ አብነት እንዲሆነን ጠቅሶልናል፡፡ እሱም ፍጹም አምላክ  ሲሆን ፍጹም ሰው ሆኖ በሥጋ የተመላለሰው እኛ የሰው ልጆች በግብራችን (በሥራችን) ደካሞች (ሰነፎች) ብንሆንም በነገር ሁሉ ብርቱ የሆነውን እርሱን ተመልክተን ከድካማችን እንድንበረታ ነው፡፡

ለዚህም ነው ጌታችን በወንጌሉ “እናንተ ደካሞች ሸክማችሁ የከበደ ሁሉ ወደ እኔ ኑ እኔም አሳርፋችኋለሁ፣ ቀንበሬን በላያችሁ ተሸከሙ ከእኔም ተማሩ፤ እኔ የዋህ ነኝና በልቤም ትሑት ነኝና ለነፍሳችሁም ዕረፍት ታገኛላችሁ፤ ቀንበሬ ልዝብ ሸክሜም ቀላል ነውና” (ማቴ. ፲፩፥፳፰) በማለት ያስተማረን፡፡

እኛ ምንም ሳይኖረን ማለትም በበደላችን ምክንያት ከጸጋው ተራቁተን፣ በኃጢአት ተጎሳቁለን፣ ደስታ ርቆን በኀዘን ተውጠን ሳለ እንዲሁ የወደደን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ከእኛ ምንም አገኛለሁ ወይም እጠቀማለሁ ሳይል ሕመማችንን የታመመ፣ ስለ እኛ የቆሰለ፣ ሞታችንን ሞቶ ሕይወቱን ያደለን እርሱ ፍቅር ስለሆነ ነው፡፡ እንግዲህ እንዲህ ያለ ዋጋ እንደ ወደደንና መተኪያ የሌለውን የደም(የሕይወት) ዋጋ ከፍሎልን ፍጹም ፍቅሩን እንዳሳየን ሁሉ እርስ በርሳችን እንዋደድ ዘንድ አዝዞናል፡፡

እርሱ እንደወደደን እርስ በርሳችን መዋደድ ማለትም፡ ጥቅምን፣ ዋጋን፣ ክፍያን፣ ውለታን ምክንያት ሳናደርግ እንዲሁ ያለ ዋጋ፣ ያለ ውለታ፣ ያለ ጥቅም መዋደድ ነው፡፡ ይህም ያለው ለሌለው፣ ያገኘው ላላገኘው፣ የተማረው ላልተማረው፣ የበረታው ለደከመው ነገ ይከፍለኛል ወይም ውለታዬን ይመልስልኛል ብሎ ሳያስብ እንዲሁ ያለ ዋጋ በነፃ የሚደረግ ስጦታ ከእውነተኛ ፍቅር የተገኘ ነው፡፡

እርስ በእርስ መዋደድ፡- ዘርን፣ ብሔርን፣ ቋንቋን ምክንያት ሳያደርግ ድሃ፣ ባለጠጋ ሳይል ሁሉን በእኩል ዓይን መመልከትና መውደድ ነው፡፡ አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር በሲና ተራራ ላይ ለሙሴ ከሰጠው ከዐሥሩ ትእዛዛት መካከልም አንዱ “ባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ” (ዘሌ. ፲፱፥፲፰) የሚል ነው፡፡

ስለዚህ ክርስትና ስለራስ ብቻ የሚኖሩበት፣ ስለራስ ብቻ የሚያስቡበት፣ ስለራስ ብቻ የሚጨነቁበት ሕይወት ሳይሆን ስለ ሌላውም የሚኖሩት፣ የሚያስቡበት፣ የሚጨነቁበት፣ የመረዳዳትና የመተሳሰብ ሕይወት ነው፡፡ ለዚህም ነው ጌታችን ኢሱስ ክርስቶስ በወንጌሉ “ሰዎች ሊያደርጉላችሁ የምትወዱትን ሁሉ እናንተም እንዲሁ አድርጉላቸው፤ ኦሪትም ነቢያትም የሚያዝዙት ይህ ነውና” (ማቴ. ፯፥፲፪) በማለት ያሰተማረን፡፡

የክርስትና ሃይማኖት እርስ በእርስ የሚፋቀሩበት፣ የሚረዳዱበትና የሚተሳሰቡበት ሕይወት  ነው፡፡ ለዚህ ደግሞ እንቅፋት የሚሆኑብንን ክፉ ምግባራት ከሕይወታችን ልናስወግዳቸው ይገባል፡፡ እነዚህ ክፉ ምግባራት ራስን ከመጉዳታቸው በተጨማሪ በማኅበራዊ ኑሮ ውስጥ ክርስቲያናዊ የሆነ መልካም ግንኙነት እንዳይኖረንና እውነተኛ ፍቅር እንዳናሳይ የሚያደርጉ ናቸው፡፡ በመሆኑም እነዚህን የመልካምነት እንቅፋቶች የሆኑትን፣ ከክርስቲያናዊ ሕይወት ሊወገዱ የሚገባቸውን ክፉ ተግባራት ከብዙው በጥቂቱ ስንመለከት፡-

፩ኛ. ራስ ወዳድነት

ራስ ወዳድነት ሲባል ስለ ራስ ምቾትና ጥቅም ሲባል ብቻ በጣም ከማሰብ የተነሣ ስለ ሌሎች ሰዎች ወይም ስለ ማኅበረሰቡ ግዴለሽ መሆንና እንዲያውም ስለ ግል ጥቅም ሲባል የሌላውን ሰው መብት መጋፋት ማለት ነው፡፡ ስለ ሌላው ሰው ማሰብ ሲባል ደግሞ ሰው ለራሱ እንዲሆንለት ወይም እንዲደረግለት የሚፈልገውን ጉዳይ ለሌላም ሰው እንዲደረግለት መመኘት ወይም ለማድረግ ፈቃደኛ መሆን ማለት ነው፡፡ እንዲሁም በራስ ሊደርስ የማይፈለግ ድርጊት በሌላ ሰው ላይ እንዲደርስ አለመመኘት ነው፡፡

ይህንን በጎ ተግባርም የእምነት አባት አብርሃም በመፈጸሙ እንደ ምሳሌ ተጠቃሽ ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ እንደሚነገረን አብርሃምና ሎጥ በቤቴል ሰፍረው ሳለ እግዚአብሔር በብዙ ባረካቸው እጅግ የብዙ መንጎች ባለቤትም ሆኑ ነገር ግን መንጎቻቸው ከመብዛታቸው የተነሳ የማሰማሪያ ስፈራ ስለ ጠበባቸው እረኞቻቸው መጋጨት ጀመሩ፡፡ በዚህን ጊዜ አብርሃም ሎጥን እኛ ወንድማማቾች ነንና በእኔና በአንተ፤ በእረኞቼና በእረኞችህ መካከል ጠብ እንዳይሆን እለምንሃለሁ…አንተ ግራውን ብትወስድ እኔ ወደ ቀኝ እሄዳለሁ አንተም ቀኙን ብትወስድ እኔ ወደ ግራ እሄዳለሁ በማለት የመረጠውን ይወስድ ዘንድ የወንድሙን ምርጫ አስቀደመ፡፡

ምንም እንኳ አብርሃም በታላቅነቱ ቅድሚያና መከበር የሚገባው ቢሆንም እርሱ ግን ምርጫን ለወንድሙ ልጅ ለሎጥ ትቶለት ከራስ ወዳድነት ሸሸ፡፡ ሎጥ ግን በወቅቱ የራሱን ምርጫ በማስቀደም የተሻለ መስሎ የታየውን  አቅጣጫ መረጠ፡፡ ከዚያ በኋላ ሎጥ የመረጠው ሀገር ሰዶምና ገሞራ እንዲጠፉ በተወሰነበት ጊዜ ከዚያች ተሰዶ ተንከራተተ፡፡ አብርሃምን ግን ባለበት ቦታ እግዚአብሔር ባረከው (ዘፍ. ፲፫፥፰)፡፡

ይህንን አስመልክቶ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስም በወንጌል “ሰዎች ሊያደርጉላችሁ የምትወዱትን ሁሉ እናንተም ደግሞ እንዲሁ አድርጉላቸው” በማለት አስተምሮናል (ሉቃ. ፮፥፴፩)፡፡

ብዙዎች መንፈሳውያን ሰዎችም ከራሳቸው ክብርና ጥቅም ይልቅ የሌላውን ሰው ክብርና ጥቅም ያስቀድማሉ፡፡ በዚህ በጎ ተግባራቸውም እንደ አብርሃም ተባርከውበታል፡፡ በመሆኑም ለኔ ብቻ ይመቸኝ እንጂ ስለ ሌላው ምን ገዶኝ ከሚለው ራስ ወዳድነት ይልቅ ጸጋና በረከት የሚገኝበትን ለሌላ ሰው የማሰብን ጠባይ ቅዱሳን አባቶቻችን አብነት አድርገን ፈለጋቸውን እንከተል ዘንድ ያስፈልጋል፡፡

በመሁኑም  ክርስትና ስለ ራስ ብቻ ሳይሆን ስለ ሌላውም የሚኖሩበት ሕይወት ነው፡፡ ነገር ግን በተቃራኒው ስለ ራስ ብቻ በማሰብ፣ እኔን ከተመቸኝ፣ ለእኔ ከሆነልኝ፣ እኔን ከተስማማኝ፣ ለእኔ ከዘነበለልኝ በማለት ግላዊ ጥቅምንና የራስን ድሎት ብቻ በማስቀደም የሚኖሩት ሕይወት መንፈሳዊ ሳይሆን ሥጋዊ (ዓለማዊ) ኑሮ ነው፡፡ ለዚህም የሚጠቀስ አንድ አባባል አለ፡፡ እሱም፡- “እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል አለች አህያ” የሚል ነው፡፡ ይህንን ቃል አህያ አፍ አውጥታ ተናገረች ለማለት ሳይሆን ራሱን ብቻ የሚወድ ሰው ስለራሱ እንጂ ስለ ሌላው ምንም የማይገደው መሆኑንና ይህም ክፉ ጠባይ እንደሆነ ለማሳየት ነው፡፡

ራስ ወዳድ ሰው የራሱን ጥቅም ለማስከበር ሲል በወንድሙ ደም ይረማመዳል፡፡ ሌላውን ገፍትሮ ጥሎ ራሱ ብቻ ለመቆም ይጥራል፡፡ የሌላውን እድል ሰብሮ የራሱን ነገር ብቻ ያደላድላል፡፡ ይህ ደግሞ ከክርስቲያናዊ ሕይወት የማይጠበቅ እኩይ ተግባር ነው፡፡ ከቅዱሳን አባቶቻችን  ሕይወት እንደተማርነው ክርስትና ለራስ እየተራቡ ሌላውን ማብላት፣ ራስ እየሞቱ ሌላውን ማዳን፣ ለራስ እየተቸገሩ ሌላውን ከችግሩ ማውጣት፣ ለራስ ክብርን እያጡ ሌላውን ማክበር፣ ለራስ እየተጠሉ ሌላውን መውደድ፣ ለራስ እየተጨነቁ ሌላውን ከጭንቀት ማውጣት ወዘተ… እንደሆነ እናስተውላለን፡፡

፪ኛ. ስስታምነት

ስስታምነት ባለን ነገር አለመርካት፣ ተመስገን አለማለት፣ ያለንን ነገር ሳይሆን ሁልጊዜ የለኝም የምንለውን ነገር ማሰብ፣ ያለንን ብዙ ነገር ባለማስተዋል የሌለንን ጥቂት ነገር ባለማግኘታችን በእግዚአብሔር ላይ የሚደረግ ማጉረምረም ነው፡፡ አንድ ሰው በፊቱ ያለውን ሳያነሣ የጀርባውን የሚመኝ፣ የቆረሰውን ሳይጎርስ በሚመገበው ላይ ዓይኑን የሚጥል፣ የቀረበለትን ሳይበላ ነገ ስለሚቀርበለት የሚጨነቅ፣ የራሱ እያለው የሌላውን የሚመኝ ከሆነ ስስታም ይባላል፡፡

ስስት ለማኅበራዊ ኑሮም ሆነ ለመንፈሳዊ ሕይወት እንቅፋት ነው፡፡ ምክንያቱም ስስታም ሰው ከእግዚአብሔር ጋር ኅብረት የለውም፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “በዓይኑ ትዕቢተኛ የሆነውና ልቡ የሚሳሳው ከእኔ ጋር አይተባበርም”  (መዝ. ፩፻፩፥፭) ይላልና፡፡

ስስታምነት የሚመጣው ከሆዳምነት ወይም ከአልጠግብ ባይነት ነው፡፡ በመሆኑም መቀበል እንጂ መስጠት፣ መለመን እንጂ መለመን(እባክህ መባል) የማይወድ ሰው ስስታም ይባላል፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ሰው ቢበላም አይጠግብም፣ ቢጠጣም አይረካም፣ ቢለብስም አይሞቀውም፡፡ ምክንያቱም ስስት አንቆ ይዞታልና በጥቂትም ሆነ በብዙው ነገር መርካት አይችልም፡፡

ክርስቲያናዊ ሕይወት ግን ከእንዲህ ዓይነት ነገር የራቀ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ የመንፈስ ልጁ ጢሞቴዎስን ሲመክር “በቃኝ ከማለት ጋር እግዚአብሔርን ማምለክ ታላቅ ረብ ነው፡፡ ወደ ዓለም ያመጣነው የለንምና ከእርሱም ልንወስደው የምንችል የለንም፡፡ ምግባችንን እና ልብሳችንን ካገኘን ይበቃናል፡፡ ባለጸጋ ሊሆኑ የሚወዱ ግን በጥፋትና በመፍረስ ሰዎችን  በሚያሰጥምና በሚያሰንፍ በሚጎዳም በብዙ ምኞትና በፈተና በወጥመድም ይወድቃሉ” (፩ኛ ጢሞ. ፮፥፮) ብሏል፡፡

፫ኛ. ክፉ ቅንዓት

ክፉ ቅንዓት ለክርስቲያናዊ ሕይወት ጠንቅ ነው፡፡ ይህም በሌላው ማግኘት፣ መከበር፣ መበልጸግ፣ ማደግና ወደተሻለ ነገር መሸጋገር መናደድ ለምን እገሌ ተለወጠ? ለምን እገሊት ከፍ አለች? በሚል የክፋት አሳብ መያዝ ነው፡፡ ክፉ ቅንዓት በራስ ሳይሆን በሌላ ማግኘት መበሳጨት ነው፡፡ ምንም እንኳ ያ በክፉ ቅንዓት የተያዘ ሰው የማያገኘው ወይም የማይደርስበት ነገር ቢሆንም እንኳ ሌላው ሰው (አካል)እንዳያገኘው ወይም እንዳይደርስበት መፈለግ ነው፡፡ እንዲህ ዓይነቱ ክፉ ጠባይ ለማኅበራዊ ኑሮም ሆነ ለመንፈሳዊ ሕይወት እንቅፋት ነው፡፡

ይህ ዓይነቱ ክፉ ቅንዓት ቃዔል በወንድሙ በአቤል ላይ እንደቀናበት ያለ ቅንዓት ነው፡፡ እንደምንመለከተው በዚህ ክፉ ቅንዓት ሰበብ ብዙ ወንድማማቾች ተለያይተዋል፣ ወዳጆች ወዳጅነታቸውን ሰርዘውበታልና ከክፉ ቅንዓት መራቅ ያስፈልጋል፡፡

፬ኛ ዘረኝነት

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሕዝብና አሕዛብ የታረቁበት የሰላም ባለቤት ነው፡፡ ለሰው ልጅ ሕይወት እውነተኛ ሰላም ያደለው እርሱ ነው፡፡ ይህንን ያልተረዱ አንዳንድ ግለሰቦች ግን ዛሬም ድረስ የሀገሬ ልጅ፣ የወንዜ ልጅ እየተባባሉ ራሳቸውንም ሆነ ሌላውን የሚጎዱ ጥቂት የሚባሉ አይደሉም፡፡ የክርስትና ሃይማኖት የፀብ ግድግዳ የፈረሰበት ሁሉን በእምነት አንድ ወገን ያደረገ ሃይማኖት መሆኑን ያልተረዱ በየስፍራው አይታጡም፡፡ ዘረኝነትን ከውስጣችን ካላጠፋን ክርስቲያናዊ  ሕይወታችን በማኅበራዊ ኑሮ ውስጥ መገለጥ አይችልም፡፡ ምክንያቱም ዘረኝነት አንዱ ለክርስቲያናዊ ሕይወት እንቅፋት ስለሆነ፡፡

ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን በአሁኑ ሰዓት እየተፈተነች ያለችበት አንዱ የዘረኝነት ጉዳይ ነው፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም የሥጋ ሥራ ብሎ ከዘረዘራቸው መካከል አንዱ ይኸው ዘረኝነት ነው፡፡ “ሕግ ሁሉ በአንድ ቃል ይፈጸማልና እርሱም ባልንጀራህን እንደራስህ ውደድ” የሚል ነው፡፡ ነገር ግን እርስ በርሳችሁ ብትነካከሱ ብትበላሉ እርስ በርሳችሁ እንዳትጠፋፉ ተጠንቀቁ ነገር ግን እላለሁ በመንፈስ ተመላለሱ የሥጋንም ምኞት ከቶ አትፈጽሙ” (ገላ. ፭፥፲፬) እንዲል፡፡ በመሆኑም ዘረኝነትን ከመካከላችን አስወግደን እውነተኛ ፈቅርን ገንዘብ ማድረግ ለማኅበራዊ ኑሮአችን አስፈላጊ ነው፡፡     

፭ኛ. ሐሜት

ሐሜት፡- ስለ አንድ ሰው እርሱ በሌለበት የነቀፋ ወይም የስም ማጥፋት ወሬ መናገር ነው፡፡ ሐሜት በእውነት ወይም በሐሰት ላይ የተመሠረተ ሊሆን ይችላል፡፡ በእውነት ላይ የተመሠረተ በሚሆንበት ጊዜ የሚታማው ሰው የፈጸመውን ክፉ ድርጊት በማንሣት ባለቤቱም ሆነ ሌላው ሰው እንዲማርበት ተብሎ ሳይሆን በድክመቱ ሌላው ሰው እንዲዘባበትበት በማሰብ ሆን ተብሎ ለሌላው ወገን በነቀፋ መልክ መናገር ነው፡፡

ሐሜት በሐሰት ላይ የተመሠረተ በሚሆንበት ጊዜ ደግሞ ‘‘ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ’’  እንደሚባለው ሁሉ ሆን ተብሎ የሰው ስም ለማጥፋት ወይም ለመጉዳት ሲባል የሚወራ ክፉ ወሬ ግን እርስ በርስ በመዋደድ ፍቅርን የሚያደርግ ሰው ከሐሜት ይርቃል፡፡ በመሆኑም ክርስቲያናዊ ሕይወት ያለው ሰው ምንም እንኳ በዙሪያው ያሉ ሰዎች ኢ-ክርስቲያናዊ ተግባር የሆነውን የሐሜትን ቃል ቢናገሩም ሰምቶ እንዳልሰማ ዝም ይላል እንጂ ከእነሱ ጋር ለሐሜት አይተባበርም፡፡

ሐሜት በእግዚአብሔር ዘንድ የተጠላ ተግባር ከመሆኑ ባሻገር ለማኅበራዊ ኑሮ ጠንቅ ነው፡፡  በክርስቲያናዊ ሕይወትም አይፈቀድም፡፡ ለዚህ ነው ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ “እግዚአብሔር ሆይ ወደ መኖሪያህ መግባት የሚችል ማነው? የሌሎች ሰዎችን ስም የማያጠፋ… ጎረቤቶቹን የማያማ… እነዚህን ነገሮች የሚያደርግ ሰው ከማናቸውም ክፉ ነገር ተጠብቆ ይኖራል እንጂ ከቶ አይናወጥም” (መዝ. ፲፭፥፩) በማለት ስለ ሐሜት ነውርነት አስገንዝቧል፡፡

ስለዚህ ከሐሜት መራቅ የክርስያናዊ ሕይወት መገለጫ ሲሆን መልካም ለሆነ ማኅበራዊ ግንኙትም ወሳኝ ነው፡፡ በመሆኑም እነዚህንና መሰል በጎ ተግባራን በመፈጸም ሕይወታችንን ልንመራ ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡

እነዚህንና መሰል የማይገቡ ክፉ ተግባራትን አርቀን መልካምነትን ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ የመልካምነት እንቅፋቶችም ከላይ የዘረዘርናቸው የሥጋ ሥራዎች ከላይ የጠቀስናቸውን እናንሳ እንጂ ፍቅርን ሊያቀዘቅዙ የሚችሉ በርካታ ናቸው፡፡ ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ በማስገዛት የመንፈሳዊነታችን መገለጫ የሆነውን ፍቅርን ልናደርግ ይገባል፡፡ እግዚአብሔር አምላካችን እርስ በእርሳችን የምንግባባበትን እውነተኛ ፍቅር ለሁላችንም ያድለን አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

“ሠናይ ውእቱ ለነ ሀልዎ ዝየ” (ማቴ.፲፯፥፬)

በዲ/ን ዐቢይ ሙሉቀን

የቃሉ ተናጋሪ የሐዋርያት አለቃ ቅዱስ ጴጥሮስ ነው። ቃሉን የተናገረው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በደብረ ታቦር ብርሃነ መለኮቱን ሊገልጥላቸው ከነቢያት ሙሴንና ኤልያስን፣ ከሐዋርያት ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ዮሐንስን ወደ ተራራው ባወጣቸው ጊዜ ነው፡፡ ሙሴና ኤልያስ ከክርስቶስ ጋር ሲነጋገሩ ሰምቶ “በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው፣ ብትፈቅድስ ሦስት ሰቀላዎች እንሥራ አንድ ላንተ፣ አንድ ለሙሴ፣ አንድ ለኤልያስ” በማለት ተናገረ።

በዚህ ጽሑፍ ክርስቶስ ከነቢያት ሙሴንና ኤልያስን፣ ከሐዋርያት ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ዮሐንስን ብቻ ወስዶ ብርሃነ መለኮቱን ለመግለጥ የፈቀደበትን ምክንያት፣ ደብረ ታቦር የምን ምሳሌ እንደሆነ፣ በዚህ እንኑር የሚለው ቃል ምንን እንደሚያመለክት፣ እናያለን።

ሀ. ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃነ መለኮቱን ማሳየት ለምን አስፈለገው?

አንደኛ፡-  “እውነት እውነት እላችኋለሁ የሰውን ልጅ በመንግሥቱ ሲመጣ እስኪያዩት ድረስ እዚህ ቆመው ካሉት ሞትን የማይቀምሱ አሉ” (ማቴ.፲፮፥፳፰) ብሏቸው ነበርና ከዚያ ጋር ለማያያዝ።

ሁለተኛ፡- እሞታለሁ ብሎ ቢናገር ቅዱስ ጴጥሮስ አይሁንብህ (ማቴ.፲፮፣፳፩-፳፫) እያለ ተናግሮ ነበርና የሚላችሁን ስሙ ለማለት።

ሦስተኛ፡- በቂሣርያ ሰብስቦ “የሰውን ልጅ ማን ይሉታል?” ባላቸው ጊዜ “ከነቢያት አንዱ ነው” (ማቴ.፲፮፣፣፲፫-፲፬) ብለውት ነበርና የነቢያት ጌታ መሆኑን እንዲረዱት ነው።

ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክ፣ ወልደ አምላክ መሆኑን ሙሴና ኤልያስም መስክረዋል። ሙሴ እኔ ባሕር ብከፍል፣ ጠላት ብገድል፣ መና ባወርድ፣ ደመና ብጋርድ በአንተ ዕርዳታ ነው። ነገር ግን ይህም ሆኖ እስራኤልን ማዳን አልቻልኩም፤ እስራኤልን ማዳን የምትችል አንተን የሙሴ አምላክ የሙሴ ጌታ ነህ ይበሉህ እንጂ ለምን ሙሴ ይሉሃል ብሎ መስክሯል። ኤልያስም ሰማይ ብለጉም፣ እሳት ባዘንም በአንተ ቸርነት እንጂ እኔማ እንዴት ይቻለኛል? ይህም ሆኖ እስራኤልን ከኃጢአታቸው መልሼ ማዳን አልቻልኩም። ይህን ሁሉ ማድረግ የምትችል አንተን የኤልያስ ጌታ ሊሉህ ይገባል እንጂ እንዴት ኤልያስ ነህ ይሉሃል ሲሉ ተሰምተዋል። እንዲሁም በባሕርይ አባቱ ለማስመስከር ነው። ሐዲስ ኪዳን የአምላክ መገለጥ ወይም ዘመነ አስተርእዮ ነው የሚባለውም ለዚህ ነው። ግራ ሲጋቡ የነበሩ ሐዋርያትም አምላክነቱን ተረድተዋልና።

ለ. ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለምን ከነቢያት ሙሴንና ኤልያስን ከሐዋርያት ጴጥሮስን፣ ያዕቆብንና ዮሐንስን ብቻ ወሰዳቸው?

ይህን ጉዳይ ስንመለከት ሁሉም የየራሳቸው ምክንያት አላቸው። በመጀመሪያ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የመረጣቸው ከብሉይ ኪዳንም፣ ከሐዲስ ኪዳንም፣ ከደናግልም፣ ከሕጋውያንም ነው። ሁሉም መንግሥተ ሰማያትን መውረስ እንደሚችሉ ሲያስረዳ ነው። ይህም በብሉይ ኪዳን ምእመናንም ሆነ በሐዲስ ኪዳን ምእመናን፣ እንዲሁም በድንግልና በኖሩትም ሆነ በጋብቻ ሕይወት በኖሩት ትምክህት እንዳይኖር፣ መንግሥተ ሰማያት በሃይማኖት ጸንቶ፣ መልካም ምግባር ሠርቶ የኖረ ሁሉ የሚወርሳት እንደሆነች ለማስረዳት ነው።

ሌላው ደግሞ ሙሴ በመዋዕለ ዘመኑ ክብርህን አሳየኝ ባለው ጊዜ እኔን አይቶ መቋቋም የሚቻለው የለም (ዘፀ.፴፫፥፲፯-፳፫) ብሎት ነበርና የተመኘውን ሊያሳካለት፣ እንዲሁም በባሕርይው የማይመረመር መሆኑንም ሲገልጽለት ነው። ኤልያስንም ምስክር ትሆነኛለህ ተብሎ ስለነበር። ከዚህም በመነሣት የለመኑትን የማይነሣ፣ የነገሩትን የማይረሳ አምላክ መሆኑን እንድንረዳ፣ እንዲሁም የማያደርገውን የማይናገር የተናገረውንም የማያስቀር እውነተኛ አምላክ መሆኑን እንረዳ ዘንድ መረጣቸው።

ሐዋርያት የተመረጡበትን ምክንያት ሊቃውንቱ በሁለት መንገድ ገልጸውታል። የመጀመሪያው ሦስቱም እንሾማለን ብለው ያስቡ ስለነበር እርሱ ንጉሥነቱ ሰማያዊ እንጂ ምድራዊ እንዳልሆነ፣ ንግሥናው ሰማያዊ መሆኑን አስረድቶ የእነርሱንም ሹመት ሰማያዊ እንጂ ምድራዊ እንዳልሆነ ሊያስረዳቸው። ሌላው ደግሞ እጅግ አብዝተው ይወዱት ስለነበር የፍቅራቸው ዋጋ እንዲሆንላቸው ነው። ሹመት ይመኙ እንደነበር ያዕቆብና ዮሐንስ እናታቸውን ልከው ያስጠየቁ ሲሆን ጴጥሮስ ደግሞ እሞታለሁ ቢለው አትሙትብኝ ብሎ መጠየቁ እርሱ ከሞተ ማን ይሾመኛል ብሎ ነው ብለው መተርጉማኑ ተርጉመውታል። ፍቅራቸውን ግን እኔ የምጠጣውን ጽዋዕ ትጠጣላችሁ ወይ ሲባሉ አዎን ማለታቸው ቢወዱት ነውና፤ ጴጥሮስም አትሙትብኝ ማለቱ ቢወደው ነውና የፍቅራቸው መገለጫ ይሆናቸው ዘንድ ብርሃነ መለኮቱን ገለጠላቸው። በዚህ ምክንያት ከሌሎች ሐዋርያት ተለይተው ብርሃነ መለኮቱን እንዲያዩ ተመርጠዋል።

ሐ. ቅዱስ ጴጥሮስ የሙሴንና የኤልያስን ምስክርነት ከሰማ በኋላ ለክርስቶስ፣ ለሙሴና ለኤልያስ ቤት እንሥራ  ማለቱ ለምንድነው?

ብንታመም እየፈወስከን፣ ብንሞት እያስነሣኸን፣ ብንራብ ባርከህ እያበላኸን፣ ሙሴም የጥንት ሥራውን እየሠራ ባሕር እየከፈለ፣ ጠላት እየገደለ፣ መና እያወረደ፣ ደመና እየጋረደ፣ ኤልያስም ሰማይ እየለጎመ፣ ዝናም እያዘነመ በዚህ እንኑር በማለት ተናግሯል። ቅዱስ ጴጥሮስ ለክርስቶስ፣ ለሙሴና ለኤልያስ ቤት እንሥራ ሲል ለራሱና ለሌሎች ሐዋርያት እንሥራ አላለም። ከዚህና ከሌላውም አገላለጹ የምንረዳው መሠረታዊ ነጥብ አለ። እርሱም፡-

የክርስቶስን፣ የሙሴንና የኤልያስን ተግባር መመስከር ሲሆን፤ እውነተኛ ምስክርነትን እንማራለን። በብሉይ ኪዳን ሲተገብሩት የኖሩትን፣ እንዲሁም ክርስቶስ ሁሉን የሚችል አምላክ መሆኑን አስረድቷል። ከዚህ በተጨማሪ ለራሱ አለመጠየቁ አስቀድሞ የነበረውን የዓሣ ማጥመጃ መረብና አንድ አህያ ትተህ ተከተለኝ ተብሏልና፣ እንዲሁም ብር ወይም ወርቅ አትያዙ ተብሏልና ምድራዊ ገንዘብ፣ ቤት ንብረት ማፍራት እንደሌለባቸው የተማሩትን መሠረታዊ ትምህርት ያስታውሰናል። ሌላው ደግሞ ለራስ አለማለትን ሌላውን ማስቀደም እንዳለብን ያስተምረናል።

መ. ደብረ ታቦር የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ናት የሚባለው ለምንድንነው?

በደብረ ታቦር ብርሃነ መለኮቱ እንደተገለጠባት ቤተ ክርስቲያንም ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያን አዕማደ ምሥጢራት፣ ነገረ እግዚአብሔር ይገለጥባታል። ቅዱስ ጴጥሮስ በደብረ ታቦር እንኑር ማለቱ ዛሬም በቤተ ክርስቲያን መኖር እንዳለብን ያስረዳናል። ደብረ ታቦር በክርስቶስ ሰብሳቢነት ነቢያትና ሐዋርያት የተገናኙበት የተቀደሰ ተራራ ነው። ቤተ ክርስቲያንም “በነቢያትና በሐዋርያት መሠረት ላይ ታንጻችኋልና፤ የሕንጻው ማዕዘን ራስ ድንጋይም ኢየሱስ ክርስቶስ ነው” (ኤፌ.፪፥፳) በማለት ብርሃነ ዓለም ቅዱስ ጳውሎስ እንደገለጸው የብሉይ ኪዳን ምእመናንና የሐዲስ ኪዳን ምእመናን ኅብረት፣ አንድነት ናት።

በደብረ ታቦር በአጸደ ሥጋ ያሉ ሐዋርያትና በአጸደ ነፍስ ያሉት ምእመናን እንደተገናኙ ቤተ ክርስቲያንም በአጸደ ሥጋ ያሉ ምእመናን እና በአጸደ ነፍስ ያሉ ምእመናን አንድነት ናት። በደብረ ታቦት ስውራን እና ሕያዋን እንደተገናኙበት ቤተ ክርስቲያን የእነዚህ ሁሉ ኅብረት አንድነት ናት። በድንግልና የኖሩት ኤልያስና ዮሐንስ በጋብቻ ከኖሩት ሙሴና ጴጥሮስ ጋር አንድ ሆነው ብርሃነ መለኮቱን እንደተመለከቱበት ቤተ ክርስቲያንም በድንግልና ያሉትም፣ በጋብቻ ሕይወት የሚኖሩትም ምእመናን በክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት አምነው ምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያንን የሚሳተፉባት እነዚህን ሁሉ አንድ የምታደርግ የአንድነት ቦታ ናት።

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ይህን ልዩ የሆነ ምሥጢር እንድንረዳው ድክመታችንንም እንኳን ልዩ በሆነው ጥበቡ ሰውሮ ደካማ ነህ ሳይል በልዩ ጥበቡ ሊያስተምረን እንደ ሐዋርያቱ እንደ ነቢያቱ ምሥጢሩን ሊገልጽልን፣ አምላክነቱን ሊያስረዳን፣ ሹመታችን ሰማያዊ እንጂ ምድራዊ እንዳልሆነ ሊያስተምረን ዕለት ዕለት ይጠራናል። ቤተ ክርስቲያን ምድራዊ ሹመት የምንለምንባት ሳትሆን ሰማያዊ ሹመት የምንለምንባት ቅድስት ቦታ ናት። በቅድስና ኑረን ሰማያዊውን ርስት መንግሥተ ሰማያትን ለመውረስ የሚያስችል ሥራ የምንሠራባት የቅድስና ሥፍራ ናት።

እኛም ምንም እንኳን ደካማና ለቤቱ የማንመች ብንሆንም፣ በኃጢአት የረከስን፣ ምድራዊ ሹመትና ሀብት በቀላሉ የሚያታልለን ብንሆንም በጥበብ ያስተምረን ዘንድ ዕለት ዕለት ይጠራናልና ጥሪውን አክብረን እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው ልንል ይገባል። ይልቁንም ሰላም በጠፋበት ዘመን፣ እርስ በእርስ መስማማት በሌለበት ዘመን፣ ወንድም ወንድሙን በሚያርድበት ዘመን፣ የተበላሸ ርእዮተ ዓለም እንደ ወጀብ እየናጠን ባለንበት ዘመን፣ የተሻለ ብቻ ሳይሆን ምርጫ የሌለው መኖሪያችንን ቤተ ክርስቲያን ልናደርግ ይገባል። ምንም እንኳን በክርስትና ሕይወት እንድንፈጽማቸው የምንታዘዛቸው ሁሉ በፈቃዳችን ልንፈጽማቸው የሚገቡ ቢሆኑም አሁን ካለው ውስብስብ ችግር አንጻር ግን ቢበርደንም፣ ቢርበንም፣ ቢጠማንም፣ ብንቸገርም፣ በቤተ ክርስቲያን ጥላ ሥር ተጠልለን መኖር ግድ ይለናል። ግድ ይለናል ሲባል ግን እግዚአብሔር አምላካችን አስፈቅዶና አስወድዶ የሚገዛ አምላክ እንጂ አስገድዶ የሚገዛ አምላክ እንዳልሆነ ልብ ማለት ያስፈልጋል። ከክፉ የሚሰውረንን አምላክ ወደንና ፈቅደን ልንገዛለት፣ እንዲሁም ወደንና ፈቅደን ወደ ቤተ ክርስቲያን በመምጣት በቤተ ክርስቲያን ልንኖር ይገባል።

ቤተ ክርስቲያን መንፈሳዊ የሕክምና ማእከልና የጤና ጣቢያ ናት። በሽተኛ በዝቷል ተብሎ የሕክምና ማእከላት ይስፋፋሉ እንጂ አይዘጉም። እንዲሁ እኛ ሰዎች ምንም ኃጢአተኞችና ደካሞች ብንሆንም፣ ዘመኑም የከፋ ቢሆንም፣ በሽታውም ቢበረታ የሕክምና ቦታችን ናትና የበለጠ ልናስፋፋት፣ የበለጠ ድጅ ልንጸናት እንጂ ልንሸሻት አይገባምና ሁሌም እንደ ቅዱስ ጴጥሮስ በዚህ መኖር ለእኛ መልካም ነው ልንል ያስፈልጋል። በቤቱ ኖረን ንስሓ ገብተን ሥጋውን ደሙን ተቀብለን የስሙ ቀዳሾች የመንግሥቱ ወራሾች እንድንሆን እግዚአብሔር አምላካችን ይፍቀድልን አሜን።

“ጾም ትፌውስ ቊስለ ነፍስ፤ጾም የነፍስን ቁስል ታድናለች” (ድጓ ዘቅዱስ ያሬድ)

በመ/ር ኃይለ ሚካኤል ብርሃኑ

ጾም:- ጾመ፤ ተወ፣ ታረመ፣ ታቀበ ከሚል የግእዝ ግሥ የተገኘ ሲሆን፣ ጾም ከመባልእት መከልከል ማለትም ለተወሰነ ሰዓት ከምግብ ተከልክሎ መቆየት እና ከጥሉላት ምግቦች ለአንድ ቀንም ሆነ ለሦስት ቀን፣ ለሳምንት፣ ለሁለት ሳምንት ለወርና ለሁለት ወር ወዘተ በመታቀብ  ስለ ፍቅረ እግዚአብሔር  ከላመ ከጣመ ምግብ መከልከል ማለት ነው፡፡ በዚህም ሁሉ ፈቃደ ሥጋን ለፈቃደ ነፍስ ማስገዛት ነው፡፡ ጾም ሥጋን አድልበው ለፈቃደ ሥጋ ከሚገፋፋ ስሜት ተላቆ ፍትወተ ሥጋን አጥፍቶ ለፈቃደ ነፍስ ማደር እንዲቻል የመንፈስን ጥንካሬ ገንዘብ ማድረጊያ የጽድቅ መሣሪያ ነው፡፡

የጾም መሠረታዊው ዓላማም ሕዋሳትን ሁሉ ለእግዚአብሔር ፈቃድ እንዲኖሩ ማድረግ ነው፡፡ ለዚህም ነው ቅዱስ ያሬድ፡- “ይጹም ዐይን፣ ይጹም ልሳን፣ እዝንኒ ይጹም፣ እምሰሚዓ ኅሡም፤ ዐይን ይጹም፣ አንደበትም ይጹም፣ ጆሮም ክፉ ከመስማት ይጹም” በማለት የገለጸው (ድጓ ዘቅዱስ ያሬድ)፡፡

ጾምን ፍጹም የሚያደርገው ከምግብ መከልከል በተጨማሪ ዐይን ክፉ ከማየት ተቆጥቦ የክርስቶስን መስቀል በመመልከት የእግዚአብሔርን ማዳን በመጠባበቅ ደጅ መጥናት ሲችል፣ ጆሮም ክፉ ከመስማት ርቆ መልካሙን የእግዚአብሔርን ቃል መስማት ሲችል፣ እጅ ክፉ ከማድረግ ተቆጥቦ ለምጽዋት ሲዘረጋ፣ የደከመውን ሲደግፍ፣ የወደቀውን ማንሣት ሲችል፣ እግር ወደ አልባሌ ስፍራ ከመሄድ ይልቅ በቅድስና ስፍራው ተገኝቶ በእግዚአብሔር ፊት መንበርከክ ሲችል፣ ልብም ክፉ ከማሰብ ይልቅ በጎ በጎውን በማሰብ ለእግዚአብሔር የተከፈተ በር፣ ለኃጢአት ግን የተዘጋ በር ሆኖ ለእግዚአብሔር የሚመች ሲሆን ነው፡፡ እነዚህን ሕዋሳት ስም ጠቅሰን ዘረዘርናቸው እንጂ ሰው እነዚህን ከላይ የዘረዘርናቸውን ሁሉ መጠበቅ፣ ሕዋሳቱን መግዛት፣ ስሜቱን መቆጣጠር ሃይማኖታዊም፣ ተፈጥሮአዊም ግዴታው ወይም ሓላፊነቱ ነው፡፡

ጾም ከእግዚአብሔር ጋር ታስታርቃለች፡፡ “ወታጸምም ኩሉ ፍትወታተ ዘሥጋ፤ የሥጋ ፍላጎትን ሁሉ ታጠፋለች” እንዲል፡፡ የሥጋ ፍላጎት ደግሞ ኃጢአት ነው፡፡ እንዲሁም “ትሜህሮሙ ለወራዙት ጽሙና፤ በወጣትነት ዕድሜ ያሉትን እግዚአብሔርን መፍራት ታስተምራቸዋለች”  እንዲል ቅዱስ ያሬድ፡፡  ጾም በበደል ምክንያት ከእግዚአብሔር የራቀን ሰው ወደ እግዚአብሔር ታቀርባለች፡፡ ምክንያቱም ጾም እንዲሁ በልማድ ከእህልና ከውኃ ለተወሰነ ጊዜ ተከልክሎ መቆየት ብቻ ሳይሆን ልማድነቱ ቀርቶ ፍጹም መፀፀት ያለበት ኃጢአትን፣ በደልን እያሰቡ በጸሎት የእግዚአብሔርን ምሕረት በመጠባበቅ በፍቅሩ ተማርኮ የሚጾሙት መሆን ሲቻል በእውነትም ከእግዚአብሔር ጋር መታረቂያ መንገድ፣ ወደ እግዚአብሔር ለመቅረብ የሚያስችል የንስሓ ጉዞ ነው፡፡

ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የበጎ ምግባር መጀመሪያ ጾም እንደሆነ በመግለጽ በአብዛኛው በዓላቶቿን ከማክበሯ አስቀድማ ጾምን ታውጃለች እነዚህንም ለአብነት ያህል ጠቅሰን እንመለከታለን፡-

የትንሣኤን በዓል(ፋሲካን) ከማክበራችን አስቀድመን ዐቢይ ጾምን፣ ብርሃናተ ዓለም ጴጥሮስ ወጳውሎስን በማሰብ በዓለ ዕረፍታቸውን ከማክበራችን አስቀድሞ ቅዱሳን ሐዋርያት መንፈስ ቅዱስ ከወረደላቸው በኋላ አገልግሎታቸውን ከመጀመራቸው አስቀድሞ ሱባዔ እንደገቡና እንደ ጾሙ እኛም ጾመ ሐዋርያትን፣ የእመቤታችንን በዓለ ፍልሰት ከማክበራችን አስቀድሞ ቅዱሳን ሐዋርያት ዕረፍቷን ዓይተን ትንሣኤዋን እንደ ቅዱስ ዮሐንስ ሳናይ ብለው ሱባኤ እንደ ገቡና እንደ ጾሙ እኛም በዓሏን ከማክበራችን አስቀድመን እንጾማለን፡፡ የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን የልደት በዓል ከማክበራችን አስቀድመን ቅዱሳን ነቢያት ይወርዳል ይወለዳል ብለው ትንቢት እየተናገሩ፣ ቅዱሳን አበው ሱባዔ እየቆጠሩ ሲጠብቁት እንደ ነበረ የተስፋው ፍጻሜ ሲደርስ በገባው ቃል መሠረት ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም መወለዱን እያሰብን ያን ያናገራቸውን የነቢያት ትንቢት እንደተፈጸመ እያሰብን ከበዓለ ልደት አስቀድመን እንጾማለን፡፡ በመሆኑም ጾምን የምግባራት ሁሉ መጀመሪያ ብላ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የምታስተምረው ለዚህ ነው፡፡

ጾም የሕግ መጀመሪያም ነው፡፡ ይህንንም ሊቀ ነቢያት ሙሴ የሥነ ፍጥረትን ነገር በአስተማረበት መጽሐፉ እንደ ጠቀሰው እግዚአብሔር አምላክ በኤዶም በስተ ምሥራቅ ገነትን እንደ ተከለ እና የፈጠረውን ሰው በዚያ እንዳኖረው ገልጾ አድርግ እና አታድርግ ወይም ብላ እና አትብላ የምትል የጾም ሕግን እንደሰጠው ይናገራል፡፡

“እግዚአብሔር አምላክም አዳምን እንዲህ ብሎ  አዘዘው በገነት ካለው ዛፍ ሁሉ ብላ ነገር ግን መልካምንና ክፉን ከሚያሳየውና ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህና”(ዘፍ.፪፥፲፮) እንዲል፡፡  በዚህም ቃል መሠረት ጾም ትእዛዘ እግዚአብሔር፣ ሕገ እግዚአብሔር፣ ፍቅረ እግዚአብሔር እንደሆነና በጾም ሕግ ሕይወትና ሞት እንዳለ ተረዳን፡፡ ማለትም ጾምን ስለ እግዚአብሔር ፍቅር ብለን ደስ ብሎን ብንጾም ሕይወትን እንደምናገኝ ሁሉ ጾምን እንደ ግዳጅ ወይም ግዳጅን እንደመወጣት መጾም ስላለብን ብቻ እና ስለ ታዘዝን ብለን ትእዛዝ ለመፈጸማችን ማረጋገጫ አድርገን ለይስሙላ የምንጾም ከሆነ ዋጋ አናገኝበትም፡፡ በሌላም መንገድ ጭራሽ የጾምን ሕግ በመጣስ ለጾም ያለን አመለካከት ዝቅተኛ ሆኖ ብንገኝ ሞትን እንደምንሞት ከእግዚአብሔር እንደምንለይ ከላይ የተመለከትነው በሙሴ መጽሓፍ የተጻፈው የእግዚአብሔር ቃል ያስረዳናል፡፡

በመጀመሪያ የጾምን አዋጅ ያወጀው የሁሉ ባለቤት የሆነው አምላካችን ልዑል እግዚአብሔር ነው፡፡ ይህም “መልካሙንና ክፉን ከሚያሳየውና ከሚያስታውቀው ዛፍ አትብላ” ያለው ነው፡፡ ከዚህ ተነሥተው አበው ቅዱሳን ነቢያት፣ ካህናት፣ ሐዋርያት ሁሉ ጾምን ሰበኩ፡፡ በኃጢአት ምክንያት ከእግዚአብሔር የተለየውን ሰው በጾም ወደ እግዚአብሔር አቀረቡት፡፡ እግዚአብሔርም በጾም፣ በጸሎት፣ በምጽዋት፣ በስግደት፣ በፍጹም ፍቅር እና ትኅትና ሆነው ለተመለሱት ቁጣውን በትዕግሥት፣ መዓቱን በምሕረት ይመልሳልና አባታችን አዳም በጾም በጸሎት ወደ እግዚአብሔር በመመለሱ ከልጅ ልጁ ተወልዶ እንደሚያድነው ቃል ገብቶለት ጊዜው ሲደርስ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ተወልዶ አዳነው፡፡ “ነገር ግን ቀጠሮው በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ልጁን ላከ፣ ከሴትም ተወለደ የኦሪትንም ሕግ ፈጸመ” (ገላ.፬፥፬)እንዲል፡፡

የነነዌ ሕዝቦችም እንዲሁ በነቢዩ ዮናስ ስብከት በጾም በጸሎት ወደ እግዚአብሔር በመመለሳቸው ከተቃጣባቸው መዓት ዳኑ (ዮና.፫፥፩ )፡፡ ሌሎችም በዚህ ክፍል ያልጠቀስናቸው ብዙዎች በጾም በጸሎት የእግዚአብሔር ምሕረት ተደርጎላቸዋልና ጾም ሰውና እግዚአብሔር የሚታረቁባት ደገኛ ሕግ ናት፡፡ ለዚህም ነው ነቢዩ ኢዩኤል “በጽዮን መለከትን ንፉ ጾምንም ቀድሱ፣ ምሕላንም ዐውጁ”(ኢዩ.፪፥፲፭) በማለት ለጾም ልዩ ፍቅር እንዲኖረን እና ስንጾም በደስታ ሆነን የእግዚአብሔር ፍቅር በልባችን ሞልቶ ምስጋናውን እያቀረብን መሆን እንዳለበት ያስረዳናል፡፡ ጾምን ከጸሎት፣ ከስግደት፣ ከምጽዋት፣ ከፍቅር፣ ከትኅትና ጋር አስተባብረን ብንጾም የኃጢአት ሥርየትን፣ የእግዚአብሔርም ጸጋ ይበዛልናል፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

እንዴት እንጹም?

ክፍል ፪

የተከበራችሁ የግቢ ጉባኤያት ድረ ገጽ ተከታታዮች “እንዴት እንጹም” በሚል ርእስ በክፍል አንድ ዝግጅታችን ከሃይማኖተ አበው መጽሐፍ ስለ ጾም በጥቂቱ አቅርበንላችሁ እንደነበር ይታወሳል፡፡ አሁን ደግሞ ቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ከምትመራባቸው የሥርዓት መጻሕፍት መካከል በፍትሐ ነገሥት ስለ ጾም ከተደነገጉት መካከል በአንቀጽ ፲፭ ያገኘነውን እነሆ፡-

  • ጾምስ በሕግ ውስጥ በታወቀው ጊዜ የሰው ከምግብ መከልከል ነው፤ በደሉን ለማስተሥረይ፣ ዋጋውን ለማብዛት እርሱን ወዶ ሕግን ለሠራለት እየታዘዘ የፈቲውን ኃይል ያደክም ዘንድ፣ ለነባቢት ነፍስም ትታዘዝ ዘንድ፡፡
  • ለክርስቲያን ሁሉ የታዘዘውም ጾም ክብር ምስጋና ይግባውና ክርስቶስ የጾመው ጾመ ፵ ነው፡፡ ፍጻሜዋ ከፍሥሕ (የአይሁድ ፋሲካ) በፊት ባለው ዐርብ የሚሆን ነው፡፡ ከዚህም ቀጥሎ የስቅለት ሳምንት ነው፡፡ እነዚህም እስከ አስራ ሁለት ሰዓት ድረስ ይጾማሉ፣ ደም የሚወጣው እንስሳ፣ ከእንስሳትም የሚገኘው አይበላባቸውም፡፡
  • ዳግመኛም በየሳምንቱ ሁሉ ዐርብና ረቡዕን መጾም ነው፡፡ በዓለ ፶ የልደትና የጥምቀት በዓል የተባበሩባቸው ጊዜ ካልሆነ በቀር እንደተጻፈው እስከ ፱ ሰዓት ድረስ ይጹሟቸው፡፡
  • ጾምስ የሥጋ ግብር ነው፣ ምጽዋት የገንዘብ ግብር እንደሆነ፡፡ ሕግ ጾምን ያስወደደው የፈቲው ጾር ትደክም ዘንድ፣ ለነባቢትም ነፍስ ትታዘዝ ዘንድ ነው፡፡
  • ጾም ይረባናል ብለን ከመጾማችን የተነሣ መንፈሳውያን እንመስላለን፣ ከመሰልናቸውም የሚመስሉትን ለመምሰል ይቻላል፡፡ ዳግመኛም ጸዋሚው የረኃብን ችግር ያውቅ ዘንድ ለተራቡትና ለሚለምኑት ይራራላቸው፡፡ ዳግመኛም በጽኑ ፈቃድ ሁኖ ሊመገበው ሥጋውንና ደሙን ይቀበል ዘንድ ነው፡፡ መቀበሉም በሥጋዊና በነፍሳዊ ትጋት ይሁን፤ ዳግመኛም ከእንስሳዊ ባሕርይ ተለይቶ የጾምን ሥርዓት ጠብቆ ከሰው ወገን ደግሞ በጸሎት የተለየ ሁኖ ስለ አጽዋም በተሠሩት ሕጎች የፀና ሁኖ በሁለንተናው እግዚአብሔርን ያምልከው፡፡
  • ጾመ ፵ በእናንተ ዘንድ የከበረ ይሁን፤ መጀመሪያውም ከሰንበቶቹ ሁለተኛ የሆነው ሰኞ ነው፡፡ መጨረሻውም ከፍሥሕ አስቀድሞ ባለው በዕለተ ዐርብ ነው፡፡ ይህም ከፍሥሕ ሱባዔ በኋላ ያለ ሱባኤ እንደሆነ ያስረዳል፡፡ ከዐቢይ ጾም በኋላ የከበረ ሰሙነ ሕማማትን ትፈጽሙ ዘንድ ትጉ፡፡
  • ዘወትር በዕለተ ሰንበት መጾም አይገባም፤ እግዚአብሔር ከሥራው ሁሉ አርፎበታልና፡፡ ቅዳሜ ስዑርን ብቻ ሊጾሙ ይገባል እንጂ የፍጥረታት ሁሉ ፈጣሪ በመቃብር ውስጥ አድሮበታልና፡፡
  • በሊህ በስድስቱ ቀኖች ከቂጣ፣ ከጨው፣ ከውኃ ብቻ በቀር አይብሉባቸው፤ በሊህ ቀኖች ከወይን፣ ከሥጋ ተለዩ የኀዘን ቀኖች ናቸውና የደስታ ቀኖች አይደሉም፡፡ ዐርብንና ቅዳሜን ግን ሁለቱንም በአንድነት ጹሟቸው፡፡ የሚችል እስከ ሌሊቱ ዶሮ ጨኸት ጊዜ ድረስ ምንም ምን አይቅመስባቸው፣ ሰውየው ሁለቱን ቀኖች በአንድነት መጾም ባይቻለው ግን የቅዳሜን ጾም ይጹም፡፡
  • ዐቢይ ጾምንና ዐርብን፣ ረቡዕን የማይጾም የታወቀ ደዌ ያለበት ካልሆነ በቀር ካህን ቢሆን ይሻር፣ ሕዝባዊ ቢሆን ይለይ፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

እንዴት እንጹም?

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የደነገገቻቸው ሰባት የአዋጅ አጽዋማት እንደአሏት ይታወቃል፡፡ እነዚህም፡- ጾመ ነቢያት፣ ጾመ ነነዌ፣ ዐቢይ ጾም፣ ጾመ ሐዋርያት፣ ጾመ ፍልሰታ፣ ጾመ ድኅነት እና ገሀድ ናቸው፡፡ እያንዳንዱ ኦርቶዶክሳዊም በጾም ወቅት እንዴት መጾም እንዳለበት ቅዱሳት መጻሕፍት በስፋት ይተነትናሉ፡፡ ከእነዚህ መጻሕፍት መካከል ከሃይማኖተ አበው፣ እንዲሁም ከፍትሐ ነገሥት ያገኘናቸውን መረጃዎች በጥቂቱ እናካፍላችሁ፡፡  በቅድሚያ ግን በሃይማኖተ አበው ሠለስቱ ምእት ምዕራፍ ፳፤፲፰-፳፱ ላይ የሰፈሩትን እናስቀድም፡-

  • ጌታ ያዘዘውን ጾም አትሻር፣ እነዚህም ረቡዕ፣ ዐርብ ናቸው፡፡ ደዌ ካላገኘህ በቀር በበዓለ ሃምሳ፣ ልደት፣ ጥምቀት፣ በዋሉባቸው ዕለታት (ረቡዕ፣ ዐርብ) በቀር ይኸውም ኤጲፋንያ(ጥምቀት) ነው፡፡
  • ምእመናን የሚጾሙዋት ጾመ አርብዓ (ዐቢይ ጾም) ከፋሲካ የሚቀድሙ ሰባቱን ዕለታት (ሰሙነ ሕማማትን) ጾምነታቸውን በፍጹም ጥንቃቄ ጠብቅ፡፡
  • አንተ ሰውነትህን ለማድከም በምትጾምባቸው ዕለታት ወንድምህ ሊጠይቅህ ቢመጣ እግዚአብሔርን ደስ በምታሰኝ በበጎ ሕሊና በፍቅር ሆነህ ከእርሱ ጋር ተመገብ፣ ይህንንም የምነግርህ የጌታ ጾም በሆኑበት ዕለታት ትበላ ዘንድ አይደለም፡፡ እሊህም ረቡዕና ዐርብ አርባውም (ዐቢይ ጾም) ቀን ናቸው፡፡ አንተ ብቻ በራስህ ፈቃድ በምትጾምበት ቀን ነው እንጂ ይኸውም ሰኞ፣ ማክሰኞ፣ ሐሙስ ነው፡፡
  • በቅዳሜ ቀን ግን መጾም አይገባም፡፡ በቅዳሜ ቀን ፀሐይ እስኪገባ መጾም የሚገባ ሥራ አይደለም፡፡ የሚገባ ጊዜ አለ እንጂ፡፡ እስከ ስድስት ያም ባይሆን እስከ ሰባት፡፡
  • እሑድ ቀን በጠዋት እጅግ ማልደህ ከሌሊቱ ወደ ቤተ ክርስቲያን ሒድ። ስትሔድም ልቡናህን በማባከን ወዲያና ወዲህ አትይ። በንጹሕ ቅዳሴም ጊዜ ሕማሙን፣ ሞቱን፣ ትንሣኤውን እያሰብክ በፍጹም ፍርሃት ቁም፡፡
  • የዐርብና የረቡዕ ጾም ከቀኑ እስከ ዘጠኝ ሰዓት ይሁን፤ ከዚህ አብልጠህ ብትጾም ግን ለነፍስህ ጥቅም ይሆንሃል፡፡ የማሰናበቻ(ዕትዉ) እስኪፈጸም ድረስ ከቤተ ክርስቲያን አትውጣ፣ ሕማም ቢያገኝህ ነው እንጂ፣ ድንገተኛ መንገድ ቢሆን ነው እንጂ፡፡
  • ሁለት ሁለት ቀን መጾም ቢቻልህ በዚህ ብትጸና ጾምህ በትሕትና ይሁን፣ ልቡናህ አይታበይ፡፡
  • ትዕቢት ሰይጣን ያለማው ጦር ነውና በእርሱም ሰይጣን ከልዑል ማዕረጉ ተዋርዶዋልና በትዕቢቱ አሽከላነትም የሰውን ልጆች ሁሉ ያጠምድበታል፡፡ እንደ እርሱ ወደ ገሀነም ሊያወርዳቸው ይፈቅዳል፡፡
  • በከበረች በእሑድ ቀን መቼም መቼም ትጾም ዘንድ ማንም አያስትህ፡፡ አትስገድባት፣ በዋዜማው(ቅዳሜም) ቢሆን ዳግመኛም በከበረች በፋሲካ ቀኖች (በበዓለ ሃምሳ) አትስገድ፣ ቅዳሴ በሚቀደስበትም ጊዜ ሁሉ ሥጋውን ደሙን ከተቀበልክ በኋላ አትስገድ፣ ይህ ሥርዓት ከቤተ ክርስቲያን የተገኘ አይደለምና፡፡
  • በሰንበት ቀኖችም እንደ ሌሎች ቀኖች አትጹም። ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ስኩብ በመቃብር ከነበረባት፣ ድኅነት በተደረገባትና ከፋሲካ ዋዜማ ካለች ከአንዲት ቅዳሜ ቀን (ቀዳም ስዑር) በቀር፡፡
  • እሑድና ቅዳሜን የሚጾም የመርቅያን ክሕደቱ ልቡናህን አያስትብህ፣ በቅዳሴ ጊዜ ቸል አትበል፣ ሰውነትህን ለከበረ ለሥጋው ለደሙ የበቃ አድርግ። የበቃህ ሳትሆን ከእርሱ እንዳትቀበል ጽኑ ፍዳ እንዳይፈርድብህ፡፡
  • ወንድሞች ወደ አንተ በመጡ ጊዜ እግራቸውን ማጠብን ቸል አትበል፣ ይህችን ሥራ ቸል የሚልዋትን ስለዚህ ትእዛዝ ሥላሴ በፍዳ ይመረምሯቸዋልና ምንም ኤጲስ ቆጶሳትም እንኳ ቢሆኑ እግዚአብሔር አስቀድሞ የደቀ መዛሙርቱን እግር አጥቦ እንዲሁ ያደርጉ ዘንድ አዝዟቸዋልና፡፡

ይቆየን

አርአያነቱን ይሰጠን ዘንድ ጌታችን ጾመ፡፡ (ቅዱስ ያሬድ)

በመጋቤ ሐዲስ ምሥጢረ ሥላሴ ማናዬ

ጾም በብሉይ ኪዳንም፣ በሐዲስ ኪዳንም በፈጣሪ መኖር ለሚያምኑ የፈጣሪያቸውን ስሙን ጠርተው ለሚማጸኑ የተሰጠ አምላካዊ ትእዛዝ መሆኑ ለሁሉም ግልጽ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን በነቢያት የተጾሙ፣ ለሰዎች ከእግዚአብሔር ጋር መገናኘት ያገለገሉ አጽዋማት እንዳሉ መጻሕፍት ይመሰክራሉ፡፡ “ሙሴም ወደ ተራራው ወጣ አርባ መዓልትና አርባ ሌሊት ቆየ” (ዘጸ.፳፬፥፲፰) እንዲል፡፡ ሙሴ በተራራው የቆየው እየጾመ ነበር፡፡

ነቢያት በጾም ከፈጣሪያቸው ጋር ተገናኝተውበታል፡፡ ምንም እንኳን ድህነተ ነፍስን ማግኘት ባይችሉም በመጾማቸው አባር ቸነፈርን ከሕዝቡ አርቀዋል፡፡ በብሉይ ኪዳን ያሉ አጽዋማት በሙሉ በፍጡራን የተጾሙ ናቸው፡፡ የሐዲስ ኪዳን ጾም ግን የተጀመረው በጌታ ጸዋሚነት ነው፡፡ የብሉይ ኪዳን አጽዋማት ረድኤተ እግዚአብሔር የሚገኝባቸው እና የሐዲስ ኪዳን አጽዋማት መነሻና ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ቅዱስ ያሬድ ከላይ በርእሱ የነገረን የጌታችን ጾም የሐዲስ ኪዳን አጽዋማት መጀመሪያ ነው፡፡ ይህ ጾም የአጽዋማት ሁሉ በኵር ነው፡፡ በኃጠአት ብዛት በመርገም በጠወለገ ሰውነት የተጾሙ አጽዋማትን አድሷል፣ ቀድሷልም፡፡ ውኃ ከላይ ደጋውን፣ ከታች ቆላውን እንዲያለመልም የጌታም ጾም ከላይ ከመጀመሪያ የነበረ የአበውን ጾም ቀድሷል፣ ጉድለቱን ሞልቷል፡፡ ከእርሱ በኋላ የተነሡ የሐዋርያትን፣ የጻድቃን፣ የሰማዕታትን፣ የደናግል፣ የመነኮሳትን፣ የምእመናንን ጾም ቀድሶ የሰጠ ነው፡፡ በአጠቃላይ የጌታችን ጾም እንደ በር ነው፡፡ በር ሲከፈት ከውጭ ያለውን እና ከውስጥ ያለውን ያገኛል፡፡ የጌታችን ጾምም ከፊት የነበሩትን የነቢያትን አጽዋማት ኋላ ከተነሡ ከሐዋርያት አጽዋማት ጋር ያገናኘ ነው፡፡ በመርገም ውስጥ የነበሩትንና ከመርገም የተዋጁትን ያስተባበረ ጾም ነው፡፡

ቅዱስ ያሬድ እንደነገረን “ጌታችን የጾመው ለምን ነው?” የሚለውን ትልቅ ጥያቄ መልሶልናል “አርአያነቱን ይሰጠን ዘንድ” በማለት፡፡ ጌታችን የጾመው እንደ ፍጡራን ክብር ለመቀበል ኃጠአት ኖሮበት ስርየት ለማግኘት አይደለም፡፡ የጌታችን ጾም እርሱን ከመጥቀም በታች ነው፤ ለእኛ ጥቅም ጾመ እንጂ፡፡ አርአያነቱን አይተን፣ ፍለጋውን ተከትለን ልንጠቀምበት ጾምን ቀድሶ ሰጠን፡፡ ጾም ዲያብሎስን ድል የምንነሳበት ጋሻ፣ ከኃጢአት የምንሰወርበት ዋሻ፣ የመንግሥተ ሰማያት መውረሻ መሆኗን አርአያ ሆኖ ሊያሳየን ጾመ፡፡ የጾምንም ጥቅም በግብር በትምህርት በሚገባ አስረዳን፡፡

ይህ ዐቢይ ጾም(ታላቁ ጾም) ሁዳዴ፣ አርባ ጾም፣ የጌታ ጾም እየተባለ ይጠራል፡፡ ዐቢይ ጾም ማለት ከግሱ እንደምንረዳው እጅግ ትልቅ ጾም ማለትን ያሳያል፡፡ በእርግጥ የጾም ትንሽ የለውም፤ አንድም ቀን ይሁን ሳምንት ጾም ትልቅ ነው፡፡ ነገር ግን ይህ ጾም ዐቢይ(ትልቅ) የተባለበት ምክንያት፡-

የታላቆች ታላቅ፣ የነገሥታት ንጉሥ፣ የጌቶች ሁሉ ጌታ የፍጥረታት ሁሉ ፈጣሪ ስለጾመው ነው፡፡

የሐዲስ ኪዳን አጽዋማት ሁሉ በኩር በመሆኑ ነው፡፡

ስምንት ሳምንታትን፤ ኀምሳ አምስት ቀናትን በውስጡ የያዘው በቁጥር እጅግ ከፍ ያለ በመሆኑ በቁጥር ከአጽዋማት ሁሉ ከፍተኛ ነው፡፡

ሁዳድ(የመንግሥት እርሻ)፡- በአንድ መንግሥት የሚተዳደሩ ሕዝቦች በሙሉ በግዳጅ ወጥተው የሚያርሱት፣ የሚያጭዱት የሚሠሩት እንደሆነ ሁሉ ይህም ጾም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስን የመንግሥቱን የምስራች በምትነግር ወንጌል ያመኑ ምእመናን በአዋጅ በአንድነት የሚጾሙት በመሆኑ ነው፡፡

አርባ ጾም አያሻማም ግልጽ ነው፡፡ ጌታችን የጾመው አርባ መዓልትና አርባ ሌሊት ነው፡፡ “አርባ መዓልት እና  አርባ ሌሊት ጾመ”(ማቴ.፬፥፪) እንዲል፡፡ ጾሙ ስምንት ሳምንታትን ኀምሳ አምስት ቀናትን ያካተተ ነው ብለናል፡፡ ጌታችን የጾመው አርባ ቀን ነው ለምን ኀምሳ አምስት ቀናትን እንጾማለን? የሚሉ ጥያቄዎች በውስጣችን ሊመላለሱ ይችላሉ፡፡ ጌታችን በጾመው አርባ ቀን ላይ ቅዱሳን ሐዋርያት ከመጀመሪያው አንድ ሳምንት፣ ከመጨረሻው አንድ ሳምንት ጨምረውበታል፡፡ በዚህ ምክንያት ጾሙ ከስድስት ሳምንታት ወደ ስምንት ሳምንታት፣ ከአርባ ወደ ኀምሳ አምስት ቀናት ከፍ ሊል ችሏል፡፡ ለምን ብለን ጥያቄ ማንሳት የለብንም፡፡ ምክንያቱም የጨመሩት ከጌታችን ጋር ፣ በቃልም፣ በተግባርም ከጌታ የተማሩ፣ የምሥጢር ደቀ ማዛሙርት የሕግ ምንጮች እኛ ወደ ክርስቶስ በምናደርገው ጉዞ መሪዎች የሆኑ ቅዱሳን ሐዋርያት ናቸው፡፡ አምነን ከመቀበል ውጭ ምንም ልንል አይቻለንም፡፡ እኛ የክርስትና  ተቀባዮች እንጂ ጀማሪዎች ወይም  መሥራቾች አይደለንም  በቅዱሳን ሐዋርያት  መሠረትነት ላይ የተመሠረትን እንጂ፡፡

“እናንተስ በነቢያትና በሐዋርያት መሠረትነት ላይ ተመሥርታችኋል”(ኤፌ.፪፥፳) እንዲል የብሎኬት ድርድር መሠረት አያስፈልገኝም ሊል አይችልም፡፡ መሠረቱ ከተናደ ድርድሩ የት ሊቆም ይችላል? እኛም የሐዋርያትን ካልተቀበልን የማንን እንቀበላለን?

ቅዱሳን  ሐዋርያት ከመጀመሪያው የጨመሩት የጌታችን ጾም መግቢያ መቀበያ ንጉሥ ሲመጣ በሠራዊት እንዲታጀብ፣ በብዙ ሕዝብ እንዲከበብ፣ ከፊት ከኋላ ተከብቦና ታጅቦ በክብር እንደሚቀበሉትና እንደሚሸኙት ሁሉ የንጉሡ ኢየሱስ ክርስቶስ ጾም ሲመጣ የሚያጅቡ፣ የሚከቡ፣ የሚያከብሩ ዘወረደን ከመጀመሪያው፣ ሕማማትን ከመጨረሻ ጨምረዋል፡፡ ደግሞስ መቀነስ እንጂ መጨመር አያስቀጣ፡፡  በክርስትና ሕይወት የተቀበሉትን መክሊት መቅበር እንጂ አትርፎ ማቅረብ ገብርኄር ያሰኛል፣ ያሾማል፣ ያሸልማል ሐዋርያትም የጨመሩት ገብርኄር ለመሰኘት ነው፡፡

ምንጭ፡- ስምዐ ጽድቅ ጋዜጣ (ከመጋቢት ፩-፲፭ ቀን ፳፻፱ ዓ.ም)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የቅድስና ሕይወት

ለሜሳ ጉተታ

ቅድስና የሚለው ቃል ቀደሰ ፤ አከበረ ፤ አነጻ ከሚለው የግእዝ ቃል የተገኘ ነው ፡፡ የቅድስና ባለቤት ምንጭ እና መሠረት እግዚአብሔር ሲኾን ቅድስናውም የባሕርይ ገንዘቡ ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ ሌሎች ማለትም ሰዎች፣ ቀናት፣ ንዋያት፣ ቦታዎች፣ ምስጋናና የመሳሰሉት ለእግዚአብሔር ሆነው ሲለዩና ሲቀርቡ ቅዱስ ይሆናሉ፡፡ ይህ የተሰጣቸው ቅድስና የእግዚአብሔር ከመሆናቸው የተነሣ የሚያገኙት በመሆኑ የጸጋ ቅድስና ይባላል፡፡ የእግዚአብሔር ቅድስና ግን የባሕርይ ገንዘቡ ነው ፡፡

ከላይ የሠፈሩትን ሀሳቦች መሠረታዊ መልእክት ስንመለከት የቅድስና ሕይወት ባለቤት እግዚአብሔር መሆኑንና ሰዎችም ይቀደሱ ዘንድ ፈቃዱ መሆኑን እንረዳለን፡፡ ለቈላስይስ ምእመናን የተላከው የቅዱስ ጳውሎስ መልእክትም ከተገለጸው መልእክት በተጨማሪ ሰውን ወደ ቅድስና የሚያደርሱ የተጋድሎ መስመሮችን ያሳያል፡፡ እነዚህ ምሕረትና ርኅራኄ፣ ቸርነትና ትሕትና፣ የዋህነት፣ ትዕግሥት፣ ይቅር መባባልና ፍቅር፣ ማመስገንና ቅዱስ ቃሉን መማር፣ ራስን ማስተማርና መገሠጽ ወደ ቅድስና ሰገነት የሚያወጡ/የሚያደርሱ መሆናቸውን ከጥቅሱ እንገነዘባለን ቈላ. 3፥12-18.

በመጽሐፍ ቅዱስ ላይ እንደኛ ወጣቶች ሁነው ኃጢአትን አሸንፈው የኖሩ ለቅድስና ማዕርግም የበቁ ብዙ ወጣቶችን በምሳሌነት ማንሳት ይቻላል፡፡ በእነዚህ ቅዱሳን ዘመን የእምነት እና የሃይማኖት ነጻነት የለም፡፡ እግዚአብሔርን ማምለክ ማመስገን ለእርሱ መገዛት አይቻልም፡፡ በሕግ የተከለከለ እና የተገደበ እርሱን አምልኮ አመስግኖ ለእርሱ ተንበርክኮ የተገኘ ሁሉ ይቀጣ ነበር፤ ይታሰራል፤ ይገረፋል፤ ለእሳትና ለአንበሶች እራትም ይሆናል፡፡ እነርሱ ግን ለእርሱ ካላቸው ፍቅርና ቅንነት በእምነታቸው ጽናት ለጣዖት አልሰገዱም፣ አላመለኩምም፡፡ ይህንን ሁሉ ግን የፈጸሙት በእምነትና በተጋድሎ ነው ፡፡

ይህንንም ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ብሎ ገልጾታል፡- “እንግዲህ ምን እላለሁ? ስለ ጌዴዎንና ስለ ባርቅ ስለ ሶምሶንም ስለ ዮፍታሔም ስለ ዳዊትና ስለ ሳሙኤልም ስለ ነቢያትም እንዳልተርክ ጊዜ ያጥርብኛልና። እነርሱ በእምነት መንግሥታትን ድል ነሡ፤ ጽድቅን አደረጉ፤ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አገኙ፥ የአንበሶችን አፍ ዘጉ፥ የእሳትን ኃይል አጠፉ፥ ከሰይፍ ስለት አመለጡ፥ ከድካማቸው በረቱ፥ በጦርነት ኃይለኞች ሆኑ፥ የባዕድ ጭፍሮችን አባረሩ። ሴቶች ሙታናቸውን በትንሣኤ ተቀበሉ፤ ሌሎችም መዳንን ሳይቀበሉ የሚበልጠውን ትንሣኤ እንዲያገኙ እስከ ሞት ድረስ ተደበደቡ፤ ሌሎችም መዘበቻ በመሆንና በመገረፍ ከዚህም በላይ በእስራትና በወኅኒ ተፈተኑ፤ በድንጋይ ተወግረው ሞቱ፥ ተፈተኑ፥ በመጋዝ ተሰነጠቁ፥ በሰይፍ ተገድለው ሞቱ፥ ሁሉን እያጡ መከራን እየተቀበሉ እየተጨነቁ የበግና የፍየል ሌጦ ለብሰው ዞሩ፤ዓለም አልተገባቸውምና በምድረ በዳና በተራራ፥ በዋሻና በምድር ጉድጓድ ተቅበዘበዙ። እነዚህም ሁሉ በእምነታቸው ተመስክሮላቸው ሳሉ የተሰጠውን የተስፋ ቃል አላገኙም፥ ያለ እኛ ፍጹማን እንዳይሆኑ እግዚአብሔር ስለ እኛ አንዳች የሚበልጥ ነገርን አስቀድሞ አይቶ ነበርና” (ዕብ.11፡23-40)።

ዛሬ እኛ በአንጻራዊነት ሲታይ የእምነትና የሃይማኖት ነጻነት አለን፡፡ ያለ እኛ ፈቃድ ከእግዚአብሔር ሌላ እንድናመልክ የሚያስገድድ አካል የለም፤ ሰሞኑን በሀገራችን እየታዩ ያሉ የአህዛብ ጥቃቶችና የሰማእታቱ ጥብዐት እንደተጠበቀ ሆኖ፡፡ ከዚህም በላይ ግን በራሳችን ፍላጎት እና ምኞት ተስበን ከእርሱ ልጅነት እንዳንወጣ፣ ከዘላለማዊ ሕይወትም እንዳይለየን ጥንቃቄ ልናደርግ ይገባል፡፡ እንጸና ዘንድም እነ ዳንኤልን እና ሠለስቱ ደቂቅን እንደ መልካም አርዓያ ማንሳት ይቻላል፡፡ እምነት ሥራን ይፈልጋል፡፡ ይህም ሲባል ማመን አንድ ጉዳይ ሲሆን እምነትን ወደ ተግባር መለወጥን፣ የምግባር ሰው መሆንን፣ ተጋድሎና ክርስቲያናዊ ግዴታዎችንም መፈጸምን ይፈልጋል፡፡

ለሰላም በሰላም እንሥራ!

 

ለሜሣ ጉተታ

ዛሬ በሀገራችን ሰላም የሚያደፈርሱ ብዙ ችግሮች ያሉ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ የተሳሳቱ የታሪክ ትርክቶች፤ ወገንተኛ መሆን፤ አክራሪነት፣ የኢኮኖሚ፣ የሃይማኖት፣ የፖለቲካና፣ የሥልጣን የበላይነትን መፈለግ፤ የሐሳብ ልዩነትን አለማክበር፣ ያለመደማመጥ፣ ያለመግባባት፣ ጽንፈኛ ብሔርተኛ መሆን፣ ዘረኝነትና የሥልጣን ጥማት ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡ ለዚህ መፍትሔ በዋናነት ታላላቆች  ለትውልዱ አርአያና ምሳሌ ሊሆኑ ይገባል፡፡ ከራሳችን የግልና የቡድን ጥቅም/ፍላጎት በላይ ሕዝብንና ሀገርን ማስቀደም የግድ ይላል፡፡

በተለይም ክርስቲያን ከሁሉም ሰው ጋር በሰላም፣ በአንድት፣ በፍቅር፣ በመግባባት፣ በመደማመጥ፣ በመቻቻል፣ ችግሮችን በውይይት መፍታት ለሌሎችም አርአያና ምሳሌ በመሆን ልዩነትን በማጥፋት የተጣሉትን በማስታረቅ ሊኖር ይገባል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ‹‹የሚያስታርቁ ብዑዓን ናቸው›› ይላልና፡፡ በሌላም በኩል “ቢቻላችሁስ በእናንተ በኩል ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ” (ሮሜ.12፤18) መባላችን ሰላም የሁሉም ነገር መሠረት መሆኑን ያሳያል፡፡ ክርስቲያኖች ሁላችን ባለንበት ቦታ ሁሉ ሰላምን ሊያጠፉ ከሚችሉ ክፉ ተግባራት ሁሉ መራቅ አለብን፡፡ ነገሮችን በትዕግሥት፣ በጥበብና በማስተዋል ልናልፍ ይገባል፡፡ ካላስፈላጊ ክርክርና ሙግትም ልንርቅ ይገባል፡፡ ሰላምን መፈለግ፣ ነገርን መተው፣ ለይቅርታ መሸነፍ ይገባል፡፡ ይቅር ባይነትና ይቅርታን መጠየቅ አስተዋይነት እንጂ ተሸናፊነት አይደለምና፡፡ ይህ ደግሞ የክርስቲያን ቁልፍ መለያው ነው፡፡

እኛ ክርስቲያኖች በትንሹም በትልቁም፣ በሥራ ቦታ፣ በትምህርት ቤት፣ በማኅበራዊ ሕይወታችን ላይ የሰላም፣ የአንድነት፣ የፍቅርና የእርቅ ምክንያት እና ተምሳሌቶች መሆን አለብን እንጂ የግጭት፣ የልዩነት፣ የክርክር፣ የጠብ እና የጥል መንስኤ መሆን የለብንም፡፡ ፍቅር የነበራቸው፣ ታሪክ የነበራቸውና ድሆዎችን ሲረዱ የነበሩ ነገር ግን ዛሬ ስማቸውና ታሪካቸው እንዳልነበረ የሆኑ በርካቶች ናቸው፡፡ በማሳያነት ሶርያን፣ ሊቢያንና ሱዳንን ልናስታውስ ይገባል፡፡ ከምድረ ገጽም ለመጥፋት የተቃረቡም አሉ፡፡ ዜጎቻቸው ሰላምን  በማጣት በየሀገራቱ የተበተኑባቸው አሉ፡፡ የየመንና የሶሪያ ዜጎች በሰላም እጦት ምክንያት ከተደላደለ ሕይወታቸው ወጥተው ብዙዎቹ ሕይወታቸው አልፏል፤ በየሀገራቱ በስደት ተቅበዝባዥ ሁነዋል፣ በአዲስ አበባ ጎዳናዎች ላይ እንኳን ሳይቀር በልመና መሰማራታቸውን ጭምር እያስተዋልን ነው፡፡ ይህ ሁሉ ከሰላም እጦት የመጣ ችግር ነው፡፡  ከዚህ ውጪ የብዙ  ሀገራት ዜጎች ሰላምን በማጣት ሀገራችንን መጠለያ አድርገዋታል፤ ይህ ደግሞ ለእኛ ትልቅ ትምህርት ሊሆነን ይገባ ነበር፡፡

ሰላምን ለማግኘት በጎ ሥራን መሥራት ከክፋት ከተንኮል መራቅ እንዳለብን ብሎም ሰላምን መሻትና መፈለግን ተግባራችን መሆኑን መርሳት የለብንም፡፡ ሰላምን የሚሰጠው እግዚአብሔር ነው፡፡ ይህ የሚሆነው ደግሞ እኛ ሰላማዊ ስንሆን ነው፡፡ ሰላምን የማይፈልጉት ክፉዎች ብቻ ናቸው፡፡ እነርሱ ደግሞ ተንኮለኞች፣ በወንድማማች መካከልም ጥልንና ክርክርን የሚዘሩ፣ በእግዚአብሔር ዘንድም የማይወደዱ፣ የተጠሉም ጭምር ናቸው፡፡ የልዩነትና የጦርነት እንክርዳድን፣ ጥርጣሬንና ሐሜትን የሚዘሩ ናቸው፡፡ የፍቅር፣ የአንድነት እና የሰላም እንቅፋቶች ናቸው፡፡ ከዜጎች መካከል ፍቅርን፣ አንድነትን፣ መቻቻልን፣ መደጋገፍን መደማመጥን የሚያጠፉ ናቸው፡፡ ይህ እኩይ ተግባር ደግሞ በእግዚአብሔር ዘንድ አስጸያፊ ነው፤ በሥጋ መጎዳት ብቻ ሳይሆን በነፍስ ላይም ጭምር ሞትን ያስፈርዳል፡፡

የሀገር ፍቅር ያለው ሰው መገለጫው የሰላም ሰው መሆን ብቻ ነው፡፡ የሀገር ፍቅር ያለው እርቅን የሚፈልግ የይቅርታ ልብ ያለው ሰው ነው፡፡ እግዚአብሔር ጥልን የሚዘሩትን ይጸየፋል፡፡ ፍቅር የሌላቸው ክፉዎች ከእግዚአብሔር መንግሥት የተለዩ፣ ከእርሱም ጋር አንድነት ኅብረት የሌላቸው የጨለማው ልጆች ናቸው፡፡ ለጊዜው ሰላማዊ፣ ደስተኞች ሊመስሉ ይችላሉ፤ ነገር ግን ውስጣቸው ክፋታቸውን ስለሚነግራቸው በሰላም መኖር ወጥቶ መግባት፣ ተኝቶ መነሳት፣ ደስተኛ የሆነ ሕይወትን መኖር አይችሉም፡፡ ‹‹ለክፉዎች ሰላም የላቸውም›› ሊኖራቸውም አይችልም፡፡ በአንጻሩ  ደግሞ ‹‹በጎ ሥራ ለሚያደርጉ ሁሉ ምስጋናና ክብር ሰላምም ይሆንላቸዋል›› ተብሏል (ሮሜ.2፡10)፡፡ እናም ሁላችን ለሰላም በሰላም እንሥራ፤ እንጸልይ፤ ለሀገራችን ሰላምን፣ ፍቅርን፣ አንድነትን፣ መግባባትንና መቻቻልን እንዲያድለን የአምላካችን መልካም ፈቃድ ይሁንልን አሜን !

 

‹‹ሰላምን የሚሹ ሰላምን ያደርጋሉ››

ለሜሣ ጉተታ

ከእናንተ ጥበበኛና አስተዋይ ማን ነው? በመልካም አንዋዋሩ ሥራውን በጥበብ  የዋህነት ያሳይ፡፡ ነገር ግን መራራ ቅንዓትና አድመኛነት  በልባችሁ ቢኖርባችሁ አትመኩ፤ በእውነትም ላይ አትዋሹ፡፡ ይህ ጥበብ  ከላይ የሚወርድ አይደለም ፤ ነገር ግን የምድር ነው ፤ የሥጋም ነው፤   የአጋንንነትም ነው ፤ቅንዓትና አድመኛነት ባሉበት ስፍራ በዚያ ሁከትና ክፉ ሥራ ሁሉ አሉና፡፡ ላይኛይቱ ጥበብ ግን በመጀመሪያ ንጽሕት ናት ፤ በኋላም  ታራቂ ገር እሺ ባይ ምሕረትና በጎ ፍሬ የሞላባት ጥርጥርና ግብዝነት የሌለባት ናት፡፡ የጽድቅም ፍሬ ስላምን ለሚያደርጉት ሰዎች በሰላም ይዘራል፡፡  ያዕ 3፡ 13-18

ሰላም የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ ነው፡፡ ሰላምን ለማግኘት እግዚአብሔርን መፍራት በሕጉና በትእዛዙ መሠረት መሔድ፣ ከክፋት ከተንኮል መራቅ በጎነትን መሥራት ያስፈልጋል፡፡ ሰላም በስብሰባ ፣ በሥልጠና፣ በውይይትና በሰላማዊ ሰልፍ የሚመጣ አይደለም፤ ሰላማዊ በመሆንና በጎነትን በመሥራት ክፋትን በመጠየፍ እንጂ፡፡ በእውነት ከልብ ሰላማዊ ሰው በመሆን የሚገኝ ነው ሰላም፡፡ መጽሐፍም “ሰላምን አጥብቀህ ተከተል፤ “ሰላምን እሻ ተከተላትም” (2ኛ ጢሞ 2፡22፣ መዝ 34፤14) ይለናል፡፡

ክርስቲያን የሰላም ሰው መሆን አለበት፡፡ ሰላምን አንድነትንና ፍቅርን ከሚያደፈርሱ ነገሮች ተግባርና ሐሳብም ጭምር መራቅ አለበት፡፡ ሁል ጊዜም ስለ ሰላም፣ ስለ ፍቅር፣ ስለአንድነት መለመን አለበት፡፡ ሰላምን ከሚያደፈርሱ ነገሮች ከመራቅ በተጨማሪም ሰዎችን መምከር፣ ማስተማር መገሰጽ አለበት፡፡ ክርስትና የሰላምና የፍቅር ሕይወት ነውና ፡፡ ይህን ለማድረግ ግን የግል ፍላጎትን መተው አለብን ፡፡ ዕብ 12፡14 ላይም “ከሰው ሁሉ ጋር ሰላምን ተከታተሉ፤ ትቀደሱም ዘንድ ፈልጉ፤ ያለ እርሱ ጌታን ሊያይ የሚችል የለምና“ መባሉም ለዚህ ነው ፡፡ ስለ ፍቅር፣ ስለ ሕዝብ፣ ስለ ወገን ሰላም የሚመኝ ሰው በቃሉ ሰላማዊ በልቡና በተግባሩ ግን ተቃራኒ ሆኖ መገኘት የለበትም፡፡ የአብዘኞች የዘመናችን ግለሰቦች ችግር ግን ይህ ነው ፡፡ በቃል እና በአፋቸው ሰላምን ይሰብኩሉ፤ ከመጋረጃ ጀርባ ያለው ተግባራቸው ግን እጅግ በጣም አሰከፊ እና አጸያፊም ነው፡፡ አብዘኞቻቸው ሰላምን በሚያደፈርስ ተግባር ውስጥ ናቸውና፡፡

ሰላም ለሰው ልጅ ሕይወት መሠረታዊ ጉዳይ ነው፡፡ ሰላም የሁሉም ነገር መሠረት ነው፡፡ ያለ ሰላም እንኳን ልማትን ማልማት፣ መማርና ሠርቶ መለወጥ ይቅርና  ተኝቶ መነሳት፣ ወጥቶ መግባት እንኳን አይቻልም፡፡ ፈጣሪን ለማምለክ፣ ለመማር፣ ለማደግ ለመለወጥ፣ ቤተሰብን ለመመሥረት ሰላም ያስፈልጋል፡፡ ሰላም ከግል ሕይወትና ከቤተሰብ የሚጀምር የሕይወት መሠረት ነው፡፡ የሰው እድሜው በምድር እጅግ አጭር ነው፡፡ በዚህ አጭር የሕይወት ዘመን የተረጋጋ ሕይወትን በመኖር መልካም ሥራን ሠርቶ ማለፍ አለበት፤ ለዚህ ደግሞ ሰላም ያስፈልጋል፡፡ ሰላም ከሌለ  የማይጎዳ የሕብረተሰብ ክፍል የለም ፡፡ ከጦርነት፤ ከጥል፤ ከሁከት የሚገኝ አንድም ነገር የለም ፡፡ ሰላም ስታጣ ሕይወት ይጠፋል፤ መረጋጋትም አይኖርም፡፡ መተማመን ይጠፋል፡፡ በመካከለችንም ጥርጣሬ ይሰፋል፡፡ በዚህ መሐል እርሰ በእርስ መተላለቅም ይመጣል፡፡

‹‹ቢቻላችሁስ ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ›› ሮሜ. ፲፪፥፲፰

በለሜሳ ጉተታ

ማኅበራዊ ሕይወት የአንድነት፣ የመቻቻል እና የመደጋገፍ ኑሮ ነው፤ የቤተ ክርስቲያን አስተምሮ በማኅበራዊ ሕይወት ውስጥ መተሳሰብ፣ መረዳዳትና መተጋገዝ እንዳለብን ያስረዳል፡፡ ቅዱስ ፓትርያርኩ እንዳሉት ‹‹ማኅበራዊ ሕይወታችን የሰላም፣ የፍቅር፣ የአንድነት፣ የመተሳሰብ፣ የመከባበር፣ የመተጋገዝ፣ ምንጭ ስለሆነ የእርስ በርስ ግጭትን በማራቅ ሰላማዊ፣ የለመለመ አካባቢ፣ የለማ ሀገር እንዲኖረን ትልቅ እና መሠረታዊ አስተዋጽኦ አለው››፡፡ ይህም ኃላፊነትና አደራን መወጣት ነው፡፡ ቅዱሳን አባቶቻችን ሀገርን፣ ቤተ ክርስቲያንን፣ ታሪክን፣ ትውፊትን፣ ሥርዓትን ለእኛ ያስረከቡን የክርስትና ፍቅር፣ ውለታና አደራ ስላለባቸው ባለ ራእይና ሩቅ አሳቢ በመሆናቸውም ጭምር ነው፡፡ ክርስቲያኖች ይህን አደራ ተቀብለው የቤተ ክርስቲያን ሥርዓትን በመጠበቅ በኅብረት ለመኖር ክርስቲያናዊ ምግባሮችን የመፈጸም ኃላፊነት አለባቸው፡፡

ዘረኝነትና ለዝሙት መገዛት፤ ዕርቅ፣ ሰላምና ፍቅርን አለመፈለግ፤ ትዳርና ቤተሰብን መበተን፤ ክርስቲያናዊ ግዴታን አለመፈጸም እና ከክርስትና ሕይወት መራቅ የመንፈሳዊ ሰው ምግባር አይደለም፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ በሮሜ. ፲፪፥፲፰ ላይ ‹‹ቢቻላችሁስ ከሰው ሁሉ ጋር በሰላም ኑሩ›› በማለት መክሯል፤ ክርስትና ፍቅር ነውና፡፡ ያለምንም አድልዎ ሰውን ሁሉ ሳንንቅ በማክበር፣ በሰው ላይም ችግርን ሳንፈጥርና ተንኮልን ሳንሠራ መኖር አለብን፤ ይህ ደግሞ ክርስቲያናዊ መሠረት ነው፡፡

ማኅበራዊ ጉዞ በእምነትና በእውነት ላይ የተመሠረተ ሲሆን ለበረከት ይሆናል፡፡ ሥራችንን በትጋት፣ በቅንነት፣ በታማኝነት እንዲሁም በታዛዥነት ልንፈጽም ይገባል፡፡ ትዳራችን በእግዚአብሔር ፈቃድ ሲጸና፣ መልካም ቤተሰብ ስንመሠርት፣ የታመሙትንና የተቸገሩትን ስንጠይቅና ስናስተዛዝን፣ የተራቡትን ስናበላና ስናጠጣ፣ ለሞቱት ወገኖቻችን ተዝካር ስናወጣ፣ ችግሮቻችንን ለመቅረፍ በአንድነት ውይይት ስናደርግ፣ ቅዱሳንን፣ ጻድቃንና ሰማዕታትን ስንዘክር እንዲሁም መንፈሳውያት በዓላትን በአንድነት ስናከብር፤ ማኀበራዊ ሕይወታችን ጠንካራ ይሆናል፡፡ ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስም የማኀበራዊ ሕይወት ጠቀሜታን ሲገልጽ ‹‹ደስ ከሚለው ጋር ደስ ይበላችሁ፤ ከሚያለቅሰው ጋርም አልቅሱ፡፡›› ብሏል (ሮሜ. ፲፪፥፲፭)

በሐዲስ ኪዳን በሐዋርያት ስብከት ያመኑ ምእመናን በአንድ ልቡናና በአንድ ሐሳብ ተስማምተው ይኖሩ ነበር፡፡ ያላቸውንም ሀብት የሚያስቀምጡት በጋራ እንጂ በግል አልነበረም፡፡ ንብረታቸውን በሙሉ እየሸጡ ገንዘባቸውን ሰብስበው በሐዋርያት እግር ስር ያስቀምጡ ነበር፡፡ ‹‹ያመኑትም ሁሉ አንድ ልብና አንዲት ነፍስ ሆነው ይኖሩ ነበር፤ በውስጣቸውም የሁሉ ገንዘብ በአንድነት ነበር እንጂ ‹ይህ የእኔ ገንዘብ ነው› የሚል አልነበረም››፡፡ (ሐዋ.፬፥፴፪)

ማኅበራዊ ሕይወት የጽድቅ፣ የቅድስና፣ የበረከት ሥራን የምንሠራበት እና ለዘለዓለም ሕይወትና ክብር የሚያበቃንን ሥራ የምንፈጽምበት ነው፡፡ ለስንፍናችን ሰበብ ማቅረብ የእግዚአብሔርን ጸጋና በረከትን ያሳጣል፤ ሰላም የሰፈነበት ሕይወት እንድንኖር አያደርግም፡፡ ሁሉ ጊዜ ሕይወትን በሀሳብ፣ በጭንቀት፤ በጉድለት ለመምራት ይዳርጋልና ወደ ልቦናችን መመለስ አለብን፡፡ ፩ኛ ጢሞቴዎስ ፮፥፳ ላይም ‹‹የተሰጠህን አደራ ጠብቅ›› ማለቱ ማንነትን ያለመርሳት ኃላፊነት እና አደራን መወጣት እና ለሌሎች ሰዎች መድረስ እንዳለብን ስለሚያሳይ ልንማርበትና በሕይወትም ልንኖርበት ይገባል፡፡

ተምረው ማገልገል ያቃታቸው፣ የጠፉ፣ በዓለም ጉያ ሥር የተሸሸጉ፣ ከቤተ ክርስቲያን እና ከንስሓ ሕይወት የሸሹ ሰዎች የክርስትና ክብር ስላልገባቸው ነው፡፡ የክርስትና ክብር የገባው ለሥጋ ምቾት ቦታ አይሰጥም፡፡ ነፍሱን ያስበልጣል፤ ከሁሉም ነገር ይልቅ ለክርስትና ሕይወቱ ቅድሚያ ይሰጣል፤ ራሱን አሳልፎም ለአምላኩ ይሰጣል፡፡ ሆኖም ዛሬ ብዙዎች በዓለም ጠፍዋል፤ ማንነታቸውን ረስተዋል፤ በዚህም ለዲያብሎስ ለሥጋ ፈቃድና አምሮት ተገዝተዋል፡፡ እንኳን በእኛ ቀርቶ በአሕዛብ ዘንድ የማይሠሩ በዐይን ለማየትና በጆሮ ለመስማት አሰቃቂ የሆኑ ሰይጣናዊ ሥራዎችን በመሥራት ላይ ይገኛሉ፤ ስለዚህም ወደ ልቡናችን መመለስ ይኖርብናል፡፡

ዛሬ ሰዎች በኅብረትም ሆነ በግል የረከሰ ሥራ እየሰሩ ይገኛሉ፤ ጫት የሚቅሙ፣ ሲጋራ የሚያጤሱ፣ አብዛኛው በዝሙት የተጠቁ እና የሚተዳደሩ፣ ትዳራቸውን በየፍርድ ቤቱ የሚፈቱ፣ በተለያዩ ሱሶች የተጠመዱ፣ ለተለያዩ ሱሶች የተገዙና በመጠጥ ብዛት የሚሰክሩ፣ በስመ ክርስቲያን የሆኑ ነገር ግን በሕይወት የሌሉ ብዙ ናቸውና፡፡ ችግሩንም ለመፍታት ሁላችንም በጋራ ልንሠራ ይገባል፡፡ በተለያዩ መንገዶች ቃለ እግዚአብሔርን የሰማን፣ የተማርን፣ ለሌላውም መትረፍ የነበረብን ክርስቲያኖች ነበርን፡፡ ነገር ግን ለሥጋ በማድላት የተለያዩ ሥጋዊና ቁሳዊ ምክንያቶችን በመደርደር ኃላፊነትን በመርሳት የእግዚአብሔርንና የቤተ ክርስቲያንን ውለታ በመርሳት አደራችንን መወጣት ያቃተን እና ኃላፊነታችንን የረሳን አለን፡፡ ይህ ከማኅበራዊ ሕይወት ውጪ ነውና ያለብንን አደራ እና ኃላፊነት በማሰብ ልንወጣ ይገባል፡፡