ውጤታማ ለመሆን በውይይት ማመን

መስከረም 10 ቀን 2005 ዓ.ም.

ወልደ ማርያም


የአምስተኛው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ፓትርያርክ ሥርዓተ ቀብር ከተፈጸመ ሳምንታት ተቆጠሩ፡፡ ፓትርያርኩ ዐርፈው መንበረ ፕትርክናው ባዶ መኾኑ ከተረጋገጠበት ዕለት ጀምሮ መንበሩን ለመጠበቅና ለማስጠበቅ ይበቃል ያለውን አካል የመሾም፤ የቤተ ክርስቲያኗን መንፈሳዊና ማኅበራዊ አገልግሎት የማስቀጠል ሓላፊነት የተጣለበት ቅዱስ ሲኖዶስ አምስት ዋና ዋና ተግባራትን ፈጽሟል፡፡

 

የመጀመሪያው ፓትርያርኩ ማረፋቸው እንደተሰማና እንደተረጋገጠ በፓትርያርኩ በኩል ቤተ ክርስቲያኗ የሰበሰበቻቸውን ሀብታት በአግባቡ እንዲጠብቁ ማድረግ ነው፡፡ ለዚህም ፓትርያርኩ ረቡዕ ለሐሙስ አጥቢያ ከንጋቱ 11 ሰዓት አካባቢ ዐርፈው በዕለቱ ወደ 7፡30 አካባቢ ይኖሩበትና በቢሮነት ይገለገሉባቸው የነበሩትን ቤቶች አሽጓል፡፡ ሁለተኛው ሥርዓተ ቤተ ክርስቲያን በሚያዘው መሠረት መንበረ ፕትርክናውን የሚጠብቅ፤ ቀጣዩ የቤተ ክርስቲያኗ ፓትርያርክ እስኪመረጥ ድረስ ሲኖዶሱን በበላይነት የሚመራ፣ /ህየንተ ፓትርያርክ/ ኾኖ የቤተ ክርስቲያኗን መንፈሳዊ አስተዳደር የሚመራ ዐቃቤ መንበር መምረጥነው፡፡ በዚሁም ነሐሴ 11 ቀን 2004 ዓ.ም ብፁዕ አቡነ ናትናኤልን ከያዙት የአርሲ ሀገረ ስብከት ሊቀ ጵጵስና በተጨማሪ ዐቃቤ መንበር ኾነው እንዲያገለግሉ መርጧቸዋል፡፡

 

ሦስተኛው /በይፋ የተገለጠ ነገር ባይኖርም/ ከወቅቱ ቋሚ ሲኖዶስ ጋር ቀጣዩ ፓትርያርክ ከመመረጡ በፊት ሊሠሩ የሚገባቸውን ተግባራት የቤተ ክርስቲያኗን ሁሉን ዐቀፍ አስተዳደራዊ ፈርጆች አጥንቶ የሚታረመውን አርሞ የሌለውን አዘጋጅቶ ለምልዐተ ጉባኤ የሚያቀርብ ሰባት አባላት ያሉት የሊቃነ ጳጳሳት ሥራ አስፈጻሚ ጉባኤ መምረጡ ነው፡፡ ዐራተኛው የቅዱስ ፓትርያርኩ ሥርዓተ ቀብር ቀኖና ቤተ ክርስቲያን በሚፈቅደው መሠረት ለክብራቸውም በሚገባ መልኩ እንዲፈጸም ማድረጉ ነው፡፡ አምስተኛው እግዚአብሔር ለቤተክርስቲያኗ መልካም መሪ ይሰጥ ዘንድ የጸሎት ዐዋጅ ለሕዝበ ክርስቲያኑ ማወጅ ነው፡፡

 

ከላይ ያየናቸው የቅዱስ ሲኖዶሱ ተግባራት አፈጻጸማቸው በይፋ የታየ መግለጫም የተሰጠባቸው ናቸው፡፡ ከእነዚህ ውጭ በአሁኑ ወቅት ቅዱስ ሲኖዶሱ ምን እየሠራ እንዳለ እየተሰጠ ያለ መግለጫ የለም፡፡ ይህ ጽሑፍ ቀጣዩን የቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ አመራረጥ አስመልክቶ ቅዱስ ሲኖዶሱ ሊሔድበት የሚገባውን መስመር በአጭሩና በመጠኑ ይጠቁማል፡፡

 

1. መቅደም ያለበትን ማስቀደም፡- ቤተ ክርስቲያናችን ባለፉት ሁለት ዐሠርት ዓመታት ጥሩ ተጓዘች፣ በአንጻሩም ቢኾን ኢኮኖሚዋ አደገ፣ ወደ ቤተ ክርስቲያን ዕለት ዕለት የሚገሠግሠው ምእመን ቁጥር ጨመረ ቢባልም ሒደቱን በከፍተኛ ችግር ውስጥ የከተተ፣ ቤተ ክርስቲያኗን ለዘመናት አስከብረው ለአገርና ለሕዝብ ጠቃሚ አድርገው ያቆዩዋት ዕሴቶቿን ክፉኛ ሲገዳደር የቆየ አንድ መሠረታዊ ችግር አለ፡፡ ይኸውም የቤተ ክርስቲያኗን አስተዳደር በቅዱስ ሲኖዶስ ደረጃ እንዲከፋፈል ያደረገና በአባቶች መካከል የተከሠተ የመለያየት ችግር ነው፡፡ ይህ ልዩነት ለሃያ ዓመታት ምእመኑን ሲያደናግር የኖረ፣ በሁለቱ ጎራ ያሉ አባቶችም እርስ በርስ ተወጋግዘው ቤተክርስቲያኗ ሲኖዶስ አልባ እንድትመስል አድርጎ ያቆየ፣ ለብዙ ሥጋውያን ሰዎች ዓላማ ማስፈጸሚያነትም ሲያገለግል የኖረ መሠረታዊ ችግር ነው፡፡ ነገር ግን ቤተ ክርስቲያኗ አሁን በዚያ መጠላለፍና አልሸነፍ ባይነት – ስትናጥበት ከቆየችበት ችግር የምትላቀቅበት መልካም አጋጣሚ ላይ ትገኛለች፡፡ በመኾኑም ቤተ ክርስቲያኒቱን ይመራ ዘንድ የተሰየመው ቅዱስ ሲኖዶስ ይህንን ለሃያ ዓመት የዘለቀ ልዩነት አጥብቦ ቤተ ክርስቲያኗን ወደ ቀደመ የአንድነት ጉዞዋ መመለስ አለበት፡፡ ይህን ሲያደርግም የሚከተሉትን ጉዳዮች በጥንቃቄ ሊያጤን ይገባል፡፡

 

ሀ. የችግሩን መንሥኤ ከመሠረቱ ማጥናት፡- ከላይ የገለጽነው የመከፋፈል ችግር የብዙ ትንንሽ ችግሮች ውጤት ነው፡፡ ዝርዝራቸውን ትተን መገለጫቸውን ብናይ ፖለቲካዊ ዓላማ፣ ሀብት የማካበት ዓላማ፣ የግል ክብርና ምቾት ፍለጋ ዓላማና ቤተ ክርስቲያኗን በኑፋቄ የማወክል ዓላማ ናቸው፡፡ እነዚህን ዓላማዎች በየግላቸው ይዘው የሚንቀሳቀሱ አካላት መጠናቸው ቢለያይም በሁለቱም ጎራዎች አሉ፡፡ እነዚህ አካላት ልዩነቱን በመጠቀም ዓላማዎቻቸውን ሲያሳኩና ለማሳካት ሲሞክሩ ታይተዋል፡፡ በመኾኑም በሁለቱም በኩል ያሉ አባቶች ቤተ ክርስቲያኗ የምትናፍቀውን ሰላም አስፍነው በታሪክ ተመዝግቦ የሚኖር ደገኛ ተግባር ለመፈጸም፤ የችግሩን ምንጮች አጥንተው በመለየት እነዚህን አካላት በምክርም በተግሣጽም ማረም ወይም መለየት ይገባቸዋል፡፡

 

ለ. የዕርቁን አስፈጻሚዎች በጥንቃቄ መምረጥ፡- በአባቶች መለያየት ምክንያት ቤተ ክርስቲያኗ ከተከፈለችበት ጊዜ አንሥቶ በኦፊሴል ያልተገለጹትን ጨምሮ ሁለቱንም አካላት በመወከል በሚቀመጡ አባቶች አማካኝነት በርካታ ውይይቶች ተደርገዋል፡፡ ነገር ግን ድካሞቹ ሁሉ ውጤት አላመጡም፡፡ ለዚህ ከሚሰጡት ምክንያቶች አንዱ የሚወከሉት አባቶች ችግሩ እንዲፈታ በማድረግ በኩል የማስፈጸም ብቃት ማነስ ወይም ለማስፈጸም ጠንክሮ አለመሥራት ናቸው፡፡ በቤተ ክርስቲያን መካከል የሚከሠትን ችግር ለመፍታት ምድራዊ ጥበብና ቀመር ቦታ የላቸውም፡፡ «እንዲህ ቢባል እንዲህ በሉ» የሚለው ቅደመ ውትወታም አያስፈልግም፡፡ «እንዲህ ብል እከሌ ምን ይላል?» ወይም «የምናገረውን እከሌን ልጠይቅ» የሚሉት ደካማ አስተሳሰቦችም ሊኖሩ አይገባም፡፡በመኾኑም በቀጣይ ይህንን ሁሉም የሚናፍቀውን አንድነት እውን ለማድረግ ከሁለቱም ወገን የሚመረጡት አባቶች እውነትንና አንድነትን በማስቀደም ራሳቸውን ኾነው የሚወያዩ መኾን ይኖርባቸዋል፡፡ ለዚህም በሁለቱም በኩል ያሉት አባቶች ይወክሏቸው ዘንድ በሚመርጧቸው ሰዎች  ብቃት ላይ ጥንቃቄ ማድረግ ይኖርባቸዋል፡፡

 

ሐ.  የዕርቅ ውይይቱ በሁሉም አካላት በኩል እንዲጀመር ማድረግ፡- ይህ ችግር እንዲፈታ በማድረግ ሥልጣንና ሓላፊነት ያላቸው በሁለቱም በኩል ያሉ አባቶች እንደ ኾኑ ይታመናል፡፡ ይሁን እንጂ ባለፉት ሃያ ዓመታት መሠረታዊው የአባቶች ልዩነት ያቆሰላቸው በርካታ አካላት በሁለቱም በኩል በየደረጃው አሉ፡፡ እነሱም በሁለቱም በኩል ያሉ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ ምእመናን፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶችና ማኅበራት ናቸው፡፡ ምንም እንኳን አባቶች በዕርቅ ከተዋሐዱ እነዚህ አካላት አሻፈረኝ ብለው እንደተለያዩ ይቀራሉ ባይባልም የእነሱም መወያየት ዕርቁን የተሟላ ያደርገዋል፡፡ የአባቶችን መዋሐድ የማይፈልጉ ግለሰቦችንና ድርጅቶችንም ለመለየት ያግዛል፡፡

 

2.    በቀጣዩ የቤተ ክርስቲያን ጉዞ ላይ በጥብዓትና በግልጽ መወያየት መጀመር፡- ባለፉት ሃያ ዓመታት የቤተ ክርስቲያን ችግር ገዝፎ ይታይ የነበረው በኢትዮጵያና በአሜሪካ አብያተ ክህነት መካከል ብቻ አልነበረም፡፡ እዚህ አዲስ አበባም በተለያዩ ጊዜያት በቤተ ክህነቱ አስተዳደርና በቅዱስ ሲኖዶሱ አመራር ላይም ችግሮች ታይተዋል፡፡ ችግሮቹ ገዝፈው የቤተ ክርስቲያኗን ምልዐት እስከ ማወክና ምእመኑን ወደ ቀቢጸ ተስፋ እስከ መክተትም ደርሰው ነበር፡፡ ለቤተ ክርስቲያን ቅድስና የማይስማሟት ዘረኝነት፣ ሙስናና አድሎአዊነት በይፋ ታይተዋል፡፡ የቤተ ክርስቲያኗ አስተዳደርና አገልግሎት የሚጠበቀውን ያህል ዘመናዊ አልሆነም፡፡ አህጉረ ስብከት በልማት አገልግሎት መጓዝ ያለባቸውን ያህል አልተጓዙም፡፡ ለዚህ ሁሉ በብዙዎች እንደ ምክንያት ይጠቀስ የነበረው የቅዱስ ፓትርያርኩ የአስተዳደርና የአመራር ችግር ነው፡፡ አከራካሪ ነው፡፡ የኾነው ኾኖ አሁን ይህ ምክንያት በዜማነት የሚነሣበት ጊዜ አልፏል፡፡ ለሃያ ዓመታት በምክንያትነት ሲነሡ የነበሩት ቅዱስ ፓትርያርክ የሉም፡፡ እንደ ሥራቸው ወደሚከፍላቸው አምላክ ሔደዋል፡፡ ስለዚህ የሲኖዶሱ አባላት ሌላ ምክንያት ፈጥሮ የሚቀጥሉትን ሃያ ዓመታትም ተመሳሳይ ዜማ ሲያዜሙ ላለመኖር በመንበረ ፕትርክናው ስለሚያስቀምጡት አባትና ስለሚቀመጥበት አግባብ እንዲሁም ስለ ቤተ ክርስቲያኗ ቀጣይ አስተዳደራዊ መልክእ መወያየትና ቀጥተኛ መስመር ማስቀመጥ አለባቸው፡፡

 

3.    ችግሮችን አጥንተው ለውሳኔ የሚያቀርቡ ልዩ ልዩ ጉባኤያትን ማቋቋም፡- ሲኖዶስ የቤተክርስቲያኗን መንፈሳዊ አስተዳደር በበላይነት የሚመራ፣ በባለሞያዎች ተጠንቶ በሚቀርብለት መሠረታዊ አስተዳደራዊ ጉዳዮች ላይ የመጨረሻ ውሳኔ የሚሰጥ የቤተ ክርስቲያኒቱ የበላይ አካል ነው፡፡ ይህ እንዲኾን ደግሞ አስፈላጊውን አቅጣጫ ለአስፈጻሚው አካል መስጠት ይጠበቅበታል፡፡ በአሁኑ ሰዓት ቅዱስ ሲኖዶስ ከላይ ከተጠቀሱት ተግባራት በተጨማሪ ማድረግ ያለበት የቤቱን መሠረታዊ ችግሮች ሙያዊ በኾነ መንገድ አጥንተው ከነመፍትሔ ሐሳባቸው  የሚያቀርቡ የባለሞያዎች ቡድኖችን ማቋቋም ነው፡፡ ቡድኖቹም በተወሰነላቸው ጊዜ የቤተ ክርስቲያኗን መሠረታዊ ችግሮች ከመፍትሔ ሐሳቦች ጋር እንዲያቀርቡለት መመሪያና ትእዛዝ መስጠት፣ ለሥራቸው ቅልጥፍናም አስፈላጊው ሎጂስቲክስ እንዲሟላላቸው ማድረግ  ይጠበቅበታል፡፡ የቀደመ አገልግሎቷን ለማስቀጠል 21ኛው መቶ ክፍለ ዘመን ላይ የደረሰች ቤተ ክርስቲያን ዘመኑን የዋጀ አገልግሎት ለመስጠት ሙያዊና አስተዳደርንና አሠራርን መከተል ይጠበቅባታል፡፡ ለዚያ ደግሞ አሁን በመስቀለኛ መንገድ ላይ ያለው ቅዱስ ሲኖዶስ ሓላፊነቱን መወጣት ኖርበታል፡፡ አሁን በሚታየው ሁኔታ ሦስት የባለሙያዎች ቡድኖች እንዲቋቋሙ ግድ ይላል፡፡ እነዚህም የገንዘብና የንብረት አስተዳደር ጥናት ቡድን፣ የሰው ኃይል ጥናት ቡድንና የቤተ ክርስቲያን መዋቅርና አሠራር ጥናት ቡድን ናቸው፡፡ እነዚህ ቡድኖች በየተሰጧቸው አርእስት ያሉትን ጉዳዮች ፈትሸው ችግሮችን ነቅሰው በማውጣት የመፍትሔ ሐሳቦችንና የአሠራር መንገዶችን አጥንተው ያቀርባሉ፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስም በሚቀርቡለት ሰነዶች ዙሪያ ተወያይቶ ይወስናል፡፡

4.    ጣልቃ ገብነትን በጥንቃቄ መከታተል፡- የቤተ ክርስቲያን ፈተናዎች የሚመነጩት ከውስጥም ከውጭም ነው፡፡ በተደጋጋሚ ሲነሡ የቆዩትና በመነሣት ላይ ያሉ የቤተ ክርስቲያን ችግሮች ሙሉ በሙሉ በውስጧ ባሉ አካላት /ምእመናን፣ ካህናት፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ የቤተ ክህነቱ ሠራተኞች፣/ ድካም ብቻ የመጡ አይደሉም፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ ዐውቃም ይሁን ሳታውቅ በገቡባት ባዕዳን እጆች የተነሣ  ችግር ላይ ስትወድቅ ቆይታለች፡፡ እነዚህ የባዕዳን እጆች አሁንም በቤተ ክህነታችን አሠራር ድርሻ እንዲኖራቸው መፈቀድ የለበትም፡፡ ስለዚህ አሁን ሁሉም ዐይኑን አፍጥጦ እንዲኾን የሚጠብቀው ሒደት ከየትኛውም ውጫዊ አካል ተፅዕኖ በጸዳ መልኩ እንዲኾን ሓላፊነት ያለበት ሁሉም የቤተ ክርስቲያኗ ምልዐት መትጋት ይጠበቅበታል፡፡ በዚህ ረገድ ቤተ ክርስቲያኗ በመስቀለኛ መንገድ ላይ በቆመችበት ሰዓት ወደደጉ የመምራት ሓላፊነት ያለባቸው የቅዱስ ሲኖዶስ አባላት ከፍተኛ ድርሻ አለባቸው፡፡ እነሱ ከየትኛውም ጫና ነጻ በኾነ መልኩ እንዲመሩ ደግሞ የሚመለከተን የቤተ ክርስቲያን ልጆች ሁላችን በምንችለው ሁሉ ልናግዛቸው ያስፈልጋል፡፡

 

5. በቤተ ክርስቲያኗ ቀጣይ ጉዞ ላይ ሁሉም የቤተ ክርስቲያኗ ምልዐት በየደረጃው እንዲወያዩ ቢደረግ፡- ወቅቱ ሁሉም የቤተ ክርሰቲያኗ አካላት ስለ እናት ቤተ ክርስቲያናቸው ቀጣይ ጉዞ ስለ መሪዎቿና አመራር ሥልታቸው፣ ስለ አገልግሎቷና አገልጋዮቿ ብቃት በስፋት መወያየት ያለባቸው ጊዜ ነው፡፡ በዘርፉ ምሁራን በቃልም በመጻፍም እንደሚገለጠው ዘመናዊ አመራር የጋርዮሽ ተግባር ነው፡፡ ይህ አባባል ወደ ቤተ ክርስቲያን ሲመጣ ተግባራዊነቱ ወሳኝ በኾኑ ጉዳዮች ዙሪያ ሁሉም አካላት እየተወያዩ ለቤተ ክርስቲያኗ ይበጃሉ የሚባሉ ሐሳቦችን ወደ ዋናው ወሳኝ አካል ቅዱስ ሲኖዶስ እንዲልኩ ሲኾን ነው፡፡ በመኾኑም ቅዱስ ሲኖዶሱ ለውይይቱና ለሚያሳልፋቸው ውሳኔዎች መቃናትና ቀጥተኛነት እሱ የሚመራቸው አካላት /የቤተ ክህነት ሠራተኞች፣ ሰበካ ጉባኤያት፣ ሰንበት ትምህርት ቤቶች፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፣ ምሁራን የቤተ ክርስቲያን ልጆች ወዘተ/ በየመልኩ እንዲወያዩ አቅጣጫ መስጠት አለበት፡፡ እነዚህ አካላትም የቅዱስ ሲኖዶስን አባላት ግብዣ በመቀበል ለተግባራዊነቱ መንቀሳቀስ አለባቸው፡፡

 

ስናጠቃልል፡- በአሁኑ ሰዓት ቤተ ክርስቲያናችን ወሳኝ ምዕራፍ ላይ ትገኛለች፡፡ የምዕራፉ ወሳኝነትም ቤተ ክርስቲያኗ አሁን ያለውን ነባራዊ ሁኔታ ተረድታ ወደ ፊት የምትራመድበትን አቅጣጫ ለማስቀመጥ በጥንቃቄ መራመድ ያለባት ጊዜ ላይ በመኾኗ ነው፡፡ ጥንቃቄው ደግሞ ቤተ ክርስቲያኗን ለመምራት እግዚአብሔር መርጦ ያስቀመጣቸው አባቶች ድርሻ ብቻ አይደለም፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ በጥምቀት ከአብራከ መንፈስ ቅዱስ የወለደቻቸው ልጆቿ ሁሉ ለእናት ቤተ ክርስቲያናቸው ቀጣይ መልካም ጉዞ በሚችሉት ሁሉ መወያየት ይበጃል ያሉትን ሐሳብ ሁሉ ማቅረብ ይኖርባቸዋል፡፡ ሁሉም ይሰምር ዘንድ ደግሞ የእኔ ሐሳብ ብቻ ተቀባይ ይሁን ከሚል መገዳደር ርቆ ሁሉንም በፍቅር ማድረግና የፍቅር አምላክ የመሠረተልንን ቤተ ክርስቲያን በፍቅር ልንኖርባት ያስፈልጋል፡፡ ለሁሉም ቤተ ክርስቲያንን በደሙ የመሠረተ መሥርቶም ያጸና አምላክ ደጉን ሁሉ ያድርግልን፡፡

 

ረድኤተ እግዚአብሔር አይለየን

የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያንን የፖትርያርክ ምርጫ የሚመለከት ረቂቅ ሕግ

መስከረም 10 ቀን 2005 ዓ.ም.

ወልደ ማርያም

ምዕራፍ 1

የዐቃቤ መንበሩን ምርጫ በተመለከተ

 

አንቀጽ 1

  • መንበረ ፓትርያርኩ በሞት ወይም በሌላ ምክንያት በመንበሩ ላይ ባይኖር ቅዱስ ሲኖዶስና ሚሊ ካውንስሉ /የምዕመናን ጉባኤ/ በዕድሜ አንጋፋ በሆነው ጳጳስ በሚጠራው ጉባኤ ሰብሳቢነት ቅዱስ ሲኖዶሱ ተሰይሞ ከ7 ቀን ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ ዐቃቤ መንበር ይሰይማል፡፡ የተመረጠውም አባት ዐቃቤ መንበር በመሆን ያገለግላል፡፡ ብሔራዊ ዐዋጅ /republican decree/ ታውጆ በቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግ፣ ትውፊትና ሥርዓት መሠረት ሕጋዊ የሆነው ፓትርያርክ ሹመት ይፈጸማል፡፡

 

ምዕራፍ 2

ለመንበሩ የሚመጥን ሰው ምርጫ

 

አንቀጽ 2

ለፓትርያርክነት ሹመት የሚወዳደር ሰው የሚከተሉትን ቅድመ ሁኔታዎች ማሟላት ይጠበቅበታል፡፡

  1. በትውልድ ግብጻዊ በሃይማኖቱም የግብጽ ኦርቶዶክስ ክርስትና ሃይማኖት አባል የሆነ፡፡

  2. የቤተ ክርስቲያንን ሕግ፣ ሥርዓትና ትውፊት የሚያዘውን የሚያሟላ፣ መነኩሴ የሆነ በጋብቻ ሕይወት ያልተወሰነ /ሜትሮፓሊታንም ሆነ ጳጳስ/ ይህ ቅድመ ሁኔታ ይጠበቅበታል፡፡

  3. ዕድሜው ከአርባ ዓመት ያላነሠ በገዳም ከ15 ዓመት ላላነሠ ጊዜ የኖረ፡፡

አንቀጽ 3

  • ዐቃቤ መንበሩ የሚመራው 18 አባላት ያሉት ቅዱስ ሲኖዶስ የመረጠው የሜትሮፓሊታን የጳጳስነትና ከሚሊ ካውንስሉ /ከምእመናን ጉባኤ/ የተውጣጣ 18 አባላት ያሉት ጉባኤ ለመንበረ ጵጵስናው የሚወደደሩ እጩዎችን ዝርዝር ይይዛል፡፡

  • ኮሚቴው በመንበሩ ላይ ተቀምጦ የነበረው ፓትርያርክ ሥፍራው በሞት ወይም በሌላ ሁኔታ በለቀቀ በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ መሰየም ይኖርበታል፡፡ የዚህን ኮሚቴ ስብሰባ የሚጠራው ሊቀ መንበሩ ነው፡፡ ሊቀ መንበሩ ከሌለ ወይም ከአቅም በላይ የሆነ ችግር ከተፈጠረበት አስቀድሞ የተመረጠው ሜትሮ ፓሊተን የሊቀ መንበሩን ሥፍራ ተክቶ ይሠራል፡፡ ጉባውንም ይጠራል፡፡

  • ጉባኤው የሚካሄደው የሁለቱም ጥምር ጉባኤ አባላት 2/3ኛው ያህል ሲገኙ ነው፤ ምልዓተ ጉባኤው ካልተሟላ ስብሰባው ለሌላ ጊዜ ይቀጠራል፡፡ ሁለተኛው ምልአተ ጉባኤ ስብሰባውን የሚካፈሉት አባላት ቢሟሉም ባይሟሉም የተገኙት አባላት በአብላጫ ድምጽ የሚወስኑት ውሳኔ ተቀባይነት ይኖረዋል፡፡

 

አንቀጽ 4

  • ለፓትርያርክነት የሚወዳደረው እጩ በሁለት ወር ጊዜ ውስጥ በስድስት ሜትሮ ፓሊታን ጳጳሳትና የገዳማት አስተዳዳሪዎች ወይም በሚሊ ካውንስሉ /የምእመናን ጉባኤ/ አስቀድመው ተመርጠው ያገለገሉ ወይም አሁን እያገለገሉ ያሉ አባላትን ይሁንታ የያዘ የጽሑፍ ድጋፍ ማቅረብ ይኖርበታል፡፡

  • ይሁንታ ያገኙበትን ድጋፍ ሲያቀርቡ የድጋፍ ደብዳቤ የተሰጠበት ቀንና ሰዓት ተመዝግቦ ደረሰኝ ይሰጣቸዋል፡፡

 

አንቀጽ 5

  • የምርጫ አስፈጻሚ ኮሚቴው በአንቀጽ 4 ላይ በተቀመጠው መሠረት በ15 ቀን ውስጥ ተሰብስቦ የድጋፍ ደብዳቤዎችን ይመረምራል፤ ሕጉን የተላለፈውን ያስወግዳል፡፡ በሕጉ መሠረት የመጡለትን ድጋፎች ይቀበላል፡፡

  • ኮሚቴው በተቀመጠው የማስረከቢያ ቀን የእጩዎችን ዝርዝር ካይሮ ለሚገኘው የፓትርያርክ ጽ/ቤትና በሌሎችም ሥፍራዎች ላሉ ጽ/ቤቶች ያስረክባል፡፡ የደረሰበትንም ውሳኔ በአረብኛ ቋንቋ ካይሮ ውስጥ በጋዜጣ እንዲታተም ያደርጋል፡፡

 

አንቀጽ 6

  • ለፓትርያርክነት መንበር የሚወዳደር ማንኛውንም እጩ የነጋሪት ጋዜጣ በወጣ በ15 ቀን ውስጥ ለመንበረ ጵጵስናው የማይመጥን ተወዳዳሪ አለ ብሎ ካመነ ለኮሚቴው ሊቀ መንበር /ሰብሳቢ/ ማስታወሻ ሊጽፍ ይችላል፡፡ አሳማኝ የሆነ ነጥብም ማቅረብ ይጠበቅበታል፡፡ ለአመልካቹ ደረሰኝ ይሰጠዋል፡፡

  • የቀረበውን ቅሬታ ኮሚቴው ተቀብሎ ከመረመረ በኋላ ኮሚቴው ውሳኔውን ያሳውቃል ኮሚቴው በአንቀጽ 2 ላይ የተቀመጡትን ነጥቦች ያላሟላ እጩ ካገኘ የማንንም ውሳኔ ሳይጠብቅ እጩውን የመሰረዝ ሥልጣን አለው፡፡ ለፓትርያርክነት እጩ ለመሆን ሁኔታዎችን ያሟሉ የመጨረሻዎቹን እጩዎች ያሳውቃል፡፡ የመጨረሻዎች ተወዳዳሪዎች የድጋፍ ደብዳቤ ያላቸው ሁነው ቁጥራቸው ቢያንስ አምስት ቢበዛ ሰባት መሆን ይኖርበታል፡፡ ስማቸውም በፊደል ተራ ቁጥር ይቀመጣል፡፡

 

አንቀጽ 7

  • ኮሚቴው የመጨረሻውን የፓትርያርክ ምርጫ ቀን ያሳውቃል፡፡ የመጨረሻውን ዝርዝር በፓትርያርኩ መኖሪያ በር ካይሮና በሌሎች አካባቢዎች ባሉ ጽ/ቤቶች ይለጥፋል፡፡ በዝርዝሩ ግርጌ ኮሚቴው ዕጩው የተመረጠበትን ቀን በማሳወቅ መራጮች ድምጽ እንዲሰጡ ይጋብዛል በተቀመጠው ቀንና ሥፍራ በየቀኑ ታትመው በሚወጡ ሦስት ጋዜጦች ካይሮ ውስጥ የምርጫውን ቀንና ሥፍራ ያሳውቃል፡፡ የምርጫ ቀኑ የእጩዎች ዝርዝር ከተገለጠበት ጀምሮ ከ30 ቀናት ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ ይከናወናል፡፡

 

ምዕራፍ ሦስት

የፓትርያርኩ ምርጫ ድምጽ ሰጪዎች

 

አንቀጽ 8

  • በፓትርያርኩ ጽ/ቤት መራጮች ድምጽ የሚሰጡበት ሳጥን ይዘጋጃል፤ መራጮች በትውልድ ግብጻውያንና የኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች መሆን ይኖርባቸዋል፡፡ ከቤተ ክርስቲያኑ ጋር ባላቸው ግንኙነት በሃይማኖታቸውና በመልካም ግብራቸው የተመሰከረላቸው ሊሆኑ ይገባል፡፡

 

ድምጽ ከሚሰጥበበት ጠረጴዛ የሚቀመጡ አስመራጮች

  1. የፓትርያርኩ መንበር ባዶ ከሆነበት ጊዜ ጀምሮ በጎርጎራውያን ቀመር መሠረት ዕድሜው 35 ዓመት የሞላው፡፡
  2. የዩኒቨርሲቲ ዲግሪ ምሩቅ ወይም በግብጽ መንግሥታዊ ተቋም ተቀጥሮ ያገለገለ ወርሃዊ ገቢው 480 የግብጽ ፓውንድ ያላነሰ ወይም በባንክ፣ በካምፓኒ ተቀጥሮ የሚሠራ፣ ወይም በተመሳሳይ የሥራ ገበታ የተሰማራ፣ ገቢው ከ600 የግብጽ ፓውንድ ያላነሰ፣ ወይም ታክስ የሚከፍል ግብጻዊ ሆኖ ገቢው ከ100 የግብጽ ፓውንድ ያላነሰ መሆን ይኖርበታል፡፡
  3. በአንቀጽ 2 በተቀመጠው መሠረት በአስመራጭ ኮሚቴው ተቀባይነትን ያገኘ፡፡

አንቀጽ 9

  • ሦስት ካህናት፣ ሁለት የጠቅላላ ሚሊ ካውንስሉ/ የምእመናን ጉባኤ/ አባላት ወይም አሁን ወይም አስቀድሞ አባል የነበሩ ተመራጮች ያሉበት ኮሚቴ ድምጽ ሰጪዎች የሰጡትን ድምጽ ለመቁጠር ይሰየማል፡፡ ዐቃቤ መንበሩ የኮሚቴውን አባላት ይመርጣል ከካህናት መካከል በዕድሜ፣ ወይም በሌላ ቅድመ ሁኔታ ከፍ ካለው ጀምሮ ወደታች ያሉትን ሁሉ ሊመለከት ይችላል፡፡

 

ይህ ኮሚቴ በጽሑፍ በቀረበው ዳታ መሠረት የድምጽ ሰጪዎችን ድምጽ ከሚከተሉት ክፍሎች ይወስዳል፡፡

  1. ሜትሮ ፓሊታን፣ ጳጳሳት፣ የገዳማት አስተዳዳሪዎች ተመራጮችና ፍላጎት ያላቸው መራጮች፡፡

  2. ካይሮ ከሚገኙ መንፈሳውያት ማኅበራት ጉባኤ አባላትን፣ የአህጉረ ስብከት ተመራጮችን፣ በከተማዎች ያሉ የክርስቲያናዊ ሕግ አስፈጻሚዎች፣ በከተማ ያሉ ታዋቂ መራጮችን፡፡

  3. ከመላው ካይሮ 24 ቀሳውስት 7ቱ ከአሌክሳንድርያ የሆኑ፡፡

  4. የቀድሞ ጊዜና የአሁን የመጅሊስ አልሚሊስ የኮፕቲክ ፓርላማ አባላት፡፡

  5. የጠቅላላ ሚሊ ጉባኤ የቀድሞና የአሁን አባላት፡፡

  6. የጠቅላላ ሚሊ ጉባኤ የቀድሞና የአሁን አባላት፡፡

  7. በአስመራጭ ኮሚቴው የተመረጡ  ከካይሮ 72 አስመራጮች ከእነርሱም መካከል 24ቱ ከአሌክሳንድርያ የሆኑ፡፡

  8. ከእያንዳንዱ ሀገረ ስብከት የተመረጡ 12 ድምጽ ሰጪዎች ሜትሮፓሊቲኑ ወይም ጳጳሱ በሚመራው ኮሚቴ የተመረጡ፡፡

  9. ወይም የአህጉረ ስብከት ጳጳሳት 5 መራጮች የተካተቱበት አካል፡፡

  10. ዕለታዊ ጋዜጣ አዟሪዎችና ዋና አዘጋጆችም እነርሱም የጋዘጠኞች ማኅበር አባላት የሆኑ፡፡

 

የመጀመሪያወቹ አምስቱ ድምጽ ሰጪዎች /መራጮች/ ዝርዝር ዐቃቤ መንበሩ በሚልከው ዝርዝር ውስጥ የተካተቱ መሆን ይኖርባቸዋል፡፡

በ6ኛው ተራ ቁጥር የተቀመጡ ድምጽ ሰጪዎች ዝርዝር በአስመራጭ ኮሚቴው ይላካል፡፡

በ7ኛ ተራ ቁጥር የተላኩ ድምጽ ሰጪዎች በሜትሮ ፓሊታን አማካኝነት ይላካሉ፡፡

በ8ኛው ምድብ ላይ ያሉ ድምጽ ሰጪዎች በጋዜጠኞች ጉባኤ አማካኝነት ይላካል፡፡

የፓትርያክነት ምርጫ ቅስቀሳው ከተጀመረ በሁለት ወር ጊዜ ውስጥ የመራጮች ዝርዝር ያለምንም ክፍያ ይከናወናል፡፡

 

አንቀጽ 10

  • የመጨረሻውን የመራጮችን ዝርዝር እንደተጠቃለለ በአረብኛ ቋንቋ በሚታተሙ ሦስት ጋዜጦች ካይሮ ውስጥ ይገለጣል፡፡

  • ስማቸው በስህተት በመጨረሻው ዝርዝር ውስጥ ያልተካተተ መራጮች ዝርዝሩ እንዲስተካከል ማመልከት ይችላሉ፡፡ ጉዳዩም ዐቃቤ መንበሩ በሚመራው ኮሚቴ ይታያል፡፡ ከምርጫ አስፈጻሚ መካከል የተመረጡ ሁለት አባላት አብረው ይሆናሉ፡፡ ከሁለቱ አንዱ ካህን ይሆናል፡፡ ይህ ኮሚቴ የሚሰጠው ውሳኔ የመጨረሻው ይሆናል፡፡ ነገር ግን በስድስተኛውና በሰባተኛው ተራ ቁጥር በአንቀጽ 9 የገለጥነውን መራጭ ኮሚቴው አለመቀበሉ አስፈላጊ መስሎ ከታየው የምርጫ አስፈጻሚ ኮሚቴው ተቀባይነት ያላገኙ መራጮችን ተክተው የሚመዘገቡ ሌሎች መራጮችን መውሰድ መብት አለው፡፡

አንቀጽ 11

  • ስማቸው በምርጫው ጠረንጴዛ ላይ የተካተተ መራጮች ስማቸው ሓላፊነታቸው ሥራቸው ዕድሜአቸው ወደ ምርጫ የገቡበት ጊዜ የምርጫ ቁጥራቸውን የሚያሳይ መታወቂያ ይሰጣቸዋል፡፡ ይህንን መታወቂያ የመስጠቱ ሓላፊነት የምዝገባ ኮሚቴው ሰብሳቢ ወይም የአጥቢያ ሜትሮፓሊን ወይም ጳጳስ ይሆናል ይህም መራጩ በሚኖርበት አካባቢ ነው፡፡

  • መራጮች መታወቂያቸውን ለመውሰዳቸው መፈረም ይኖርባቸዋል፡፡ መታወቂያውን የሰጠው ወገን ፊርማውን ያስቀምጣል፡፡ ከምርጫው አስቀድሞ ባሉት 15 ቀናት የሚከናወን ይሆናል፡፡

 

2. የምርጫ ሂደት

አንቀጽ 12

  • አስመራጭ ኮሚቴው ዐቃቤ መንበሩን ሰብሳቢ ሦስት ካህናት በቅዱስ ሲኖዶስ የተመረጡ ሦስት አካላት በሰያሚ ኮሚቴው /nomination committee/ የተመረጡ ከምርጫው ከሦስት ቀን አስቀድሞ ይሠየማሉ፡፡ የቃለ ጉባኤውን ሥራ ሰብሳቢው ደስ ያለውን ሰው በመሰየም ያስይዛል፡፡

  • በኮሚቴው ሰብሳቢ ጥያቄ የምርጫ ሂደቱን የሀገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር እንዲከታተለው ይደረጋል፡፡ ሰብሳቢው ከአቅም በላይ በሆነ ችግር ለመገኘት ባይቻለው ከሜትሮ ፓሊታን መካከል  የሰብሳቢውን ሥራ ተክቶ ይሠራል፡፡ ከኮሚቴው አባላት የጎደለ ቢኖር ከአጠቃላይ ምርጫ ጉባኤው መካከል የሚተካ ሰውን ሰብሳቢው ይመርጣል፡፡

 

አንቀጽ 13

  • ምርጫው በሚካሄድበት ቀን አስቀድመን የገለጥነው ኮሚቴ በፓትርያርኩ ቤት መገኘት ይኖርበታል፡፡ ምርጫው ከ 3፡00 ሰዓት እስከ ቀኑ 11፡00 ሰዓት ድረስ ይከናወናል በቀኑ በ11ኛው ሰዓት ድምጽ መስጠት ያልቻለ መራጭ ቢኖር ኮሚቴው ዝርዝራቸውን ተናግሮ ሁሉንም ድምጽ ይሁንታ እስከሚያገኝ ሥራውን ይቀጥላል፡፡

 

አንቀጽ 14

  • ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ከሚመጡ ድምጽ ሰጪዎች በስተቀር /እነርሱ በራሳቸው ወይም ሕጋዊ በሆኑ ወኪሎቻቸው አማካኝነት የሚፈጽሙት ሆኖ ስም ዝርዝርራቸው በምርጫ ጠረጴዛው ላይ ከሰፈረ ውጪ በሕጉ ላይ እንደተቀመጠው

  1. ሜትሮፓሊቲንና ጳጳሳት፡፡
  2. የንጉሡ ተወካይ፡፡
  3. በመላው ግብጽ የታወቁ 24 ሰዎች ይህም በንጉሡ በፕሬዝዳንቱ የሚሰየሙ ይካተታሉ፡፡

 

አንቀጽ 15

  • በምርጫ ጠረጴዛው ላይ አስቀድሞ የስም ዝርዝርራቸው ባለ መራጮች ቁጥር ልክ ካርዶች ይዘጋጃሉ፤ ካርዶቹ በሊቀ መንበሩ /በምርጫ ኮሚቴ ስብሰባው ማኅተም መታተም  ይኖርባቸዋል፤ ለእያንዳንዱ መራጭም ይሰጣል፤ ወደ ምርጫው አደባባይ ሲመጡ ይዘው ይቀርባሉ፡፡ ካርዱ የመራጩ ስም የምርጫ ቁጥር ይኖረዋል፡፡ ድምጽ ሰጪው ካርዱን ለመውሰዱ ለዚህ ዓላማ በተዘጋጀው መዝገብ ላይ በፊርማው ያረጋግጣል፡፡

  • ድምጽ ለመስጠት ከተመዘገቡት ውስጥ ካርድ ያልወሰዱ ካሉ፣ ካርዱ የሌሉ ሰዎች ካርድ በሚቀመጥበት ኤንቨሎፕ ውስጥ ይቀመጣል፡፡ ለምርጫ ኮሚቴው ሊቀመንበርም ይሰጣል፡፡ ኤንቨሎፑን ካሸገ በኋላ ቀዶ ማኅተም ያደርግበታል፡፡

  • በአስመራጭ ኮሚቴው የተመረጡ 6 ድምጽ ሰጪዎች ያሉበት ኮሚቴ ከምርጫው 3 ቀን አስቀድሞ ካርዶቹን ያስረክባል ምርጫውንም ይቆጣጠራል፡፡

 

አንቀጽ 16

  • ድምጽ ሰጪዎች በአስመራጭ ኮሚቴ ፊት ሲቀርቡ ለጸሐፊው የምርጫ ካርዶቸውን መስጠት ይኖርባቸዋል፡፡ ጸሐፊው ካርዱን አትሞ ለዚህ ዓላማ በተዘጋጀው ሳጥን ውስጥ ይከታል፡፡ መራጮች የምርጫ ወረቀት ይጧቸዋል የመረጡትን ሰው ስም ይይዛል፡፡

  • የዕጣ መጣሉ ሁኔታ በተወሰነ አግባብ ውስጥ የሚካሄድ ነው፡፡ ድምጽ የሚሰጠው ሰው ለድምጽ መስጫ በተከለለ ምስጢራዊ ቦታ ሊመርጥ ያሰበውን ዕጩ ያስቀምጣል፡፡ ድምጽ ሰጪዎች በምርጫ ወረቀቱ ላይ ምልክት ባያስቀምጡ ማንነታቸውን የሚገልጽ ነገር ባይኖረው ወረቀቱ ዋጋ አይኖረውም፡፡

 

አንቀጽ 17

  • የምርጫ ሂደቱ ከተጠቃለለ በኋላ ኮሚቴው የመራጭ ሰዎችን ካርድ ይቆጥራል፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ተወካዮች ቁጥር ከመራጮች ካርድ እና ከቀሪዎች ካርድ ጋር ተደምሮ የተመዝጋቢዎችን አጠቃላይ ቁጥር መስጠቱ ይመሳከራል ይህም የኢትዩጵያ ተወካዮች ቁጥር ጨምሮ ነው፡፡

  • ጸሐፊው ይህንን ሁኔታ በቃለ ጉባኤው ላይ ካሰፈረ በኋላ ኮሚቴው ድምጹን ይለያል ከምርጫው ጋር በተያያዘ ጉዳዮች ላይ ውሳኔውን ያሳልፋል፡፡ እያንዳንዱ መራጭ በሰጠው ድምጽ ላይ ያሰፈረውን አስተያየት ተአማኒነት ይመረመራል፡፡

  • ኮሚቴው የሚሰጠው ይሁንታ አስተያየት ምስጢራዊ ነው፡፡ ውሳኔውንም የሚተላለፈው በሚቆጠረው ድምጽ ይሆናል፡፡ የተሰጠው ድምጽ እኩል ሲሆን ዐቃቤ መንበሩ የሚሰጠው ውሳኔ ተፈጻሚ ይሆናል፡፡

  • የድምጽ ቆጠራው ከተጠናቀቀ በኋላ ሊቀ መንበሩ የመጨረሻዎቹን ሦስት እጩዎች ስም ዝርዝር ያሳውቃል፡፡ እነርሱም የብልጫውን ድምጽ ያገኙ ናቸው፡፡ የኮሚቴው ጸሐፊ ሁለት ኮፒ ቃለ ጉባኤውን ያረቅቃል ዐቃቤ መንበሩ ይፈርምበታል፡፡ የሀገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር ተወካዮችም ይፈርማሉ፡፡

  • ምርጫው በተካሄደበት እሑድ ምዝገባው ይካሄዳል፡፡ ይሄውም ከላይ ለተገለጸው ሚኒስትር መ/ቤት 1 ኮፒ ቃለ ጉባኤ ይላካል/ቀሪው ካይሮ በሚገኘው የመንበረ ፓትርያርክ ጽ/ቤት ይቀመጣል፡፡ የምርጫ ሂደት ወረቀቶች በኤንቨሎፕ ቀይ ማኅተም ታትሞባቸው በፓትርያርኩ ጽ/ቤት ይቀመጣሉ፡፡

 

አንቀጽ 18

  • በቤተ ክርስቲያኒቱ ሕግና ሥርዓት መሠረት ዐቃቤ መንበር ዕጣው የሚጣልበትን ሁኔታ ያመቻቻል፡፡ በዕጣ መጣሉ ሂደት ያሸነፈውን ዕጩ ስም ዐቃቤ መንበሩ ፈርሞበት ሁለት ኮፒ ቃለ ጉባኤ ይጻፋል፡፡ በምርጫ ኮሚቴው ስምና ፊርማ ይጸድቃል፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስ አባላትም ፊርማቸውን ያስቀምጣሉ፡፡ የዕጩ ጥቆማ አስተባባሪ ኮሚቴም እንዲሁ ፊርማቸውን ያስቀምጣሉ፡፡ አንዲ ኮፒ ለሀገር ውስጥ ጉዳዮች ሚኒስትር ይላካል፡፡

  • በቤተ ክርስቲያኒቱ ሥርዓት መሠረት የተሾመው ፓትርያርክ በመላ ሀገሪቱ ይገለጣል፡፡

 

ምዕራፍ 4

ጠቅላላ ደንብና ከጊዜ ጋር የተያያዙ ደንቦች

 

አንቀጽ 19

አስፈላጊ ሆኖ ሲያገኘው የዕጩ አፈላላጊ ኮሚቴው /nomination committee/ በዚህ ሕግ ውስጥ የተቀመጠውን ጊዜ የማሳጠር ሥልጣኑ አለው፡፡ ይህም በጋራ በሚደረግ ውሳኔ ነው፡፡

ሃይማኖታውያን መስለው ከሚመጡ መናፍቃን ተጠንቀቁ ማቴ 7፥15

መስከረም 8 ቀን 2005 ዓ.ም.


አባ ዘሚካኤል

  • የተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለዘመናት ያቆየችውን ትውፊት፣ ቅርስና ሀብት፣ ቋንቋና ዜማ  የመቀራመቱ  ዘመቻ ይቁም!

ትላንት ተዋሕዶን በማናናቅ ምእመናኑን ለማስኮብለል ያልተሳካላቸው መናፍቃን፣ ዛሬ ደግሞ ስልት ቀይሰው የተዋሕዶን ታሪክ፣ ግዕዝ ጠቀሳና ያሬዳዊ ዜማን ያደነቁ በመምሰልየመፈታተናቸው አንድምታው ምን ይሆን? የተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለዘመናት ያቆየችውን ትውፊት፣ ቅርስና ሀብት የመቀራመቱ ድፍረትሳ ተመሳስሎ ተጠግቶ ማንነትዋን ለመጋራት ይሆን?ዓላማው መጀመሪያ ምእመኑን የማዘናጋት ቀጥሎ አንድነን ለማለትና ወደመናፍቅነት ለመሳብ ከዚያም እንደ ሰለጠነው ዓለም ፍጹም ዓለማዊ ለማድረግ ይሆንን?

 

መጽሐፍ ተዓቀቡኬ እምሐሳውያን ነቢያት እለይመጽኡ ሀቤክሙ በአልባሰ አባግዕ፣ የበግ ለምድ ለብሰው ከሚመጡ ሐሰተኞች፣ መናፍቃን፣ መምህራን ተጠንቀቁ፣ ወእንተ ውስጦሙሰ ተኩላት መሰጥ እሙንቱ፡፡በውስጣቸው ግን ነጣቂ ተኩላ ናቸው፣ ቢመረምሩዋቸው ግን ሰውን እየነጠቁ ወደ ገኀነም የሚያወርዱ የሰይጣን ሰራዊት ናቸው፡፡ (ወንጌል አንድምታማቴ 7፥15)

 

ይህን የወንጌል አሳብ እንደሚያስረዳን መናፍቃን ዓለማውያን የሚጠነስሱት ሴራና ፈጠራ ጌታችን መድኀኒታችንኢየሱስ ክርስቶስ ካስተማረው የማስጠንቀቂያ ትንቢት ቃል ውጭ የሆነ ያልታወቀ፣ ያልተረዳአዲስ ነገር ሊሆን አይችልም፡፡አስቀድሞ”በስሜ ይመጣሉ” ብሎ ተናግሯልና፡፡ ለዚህምቀጥሎ የተመለከተውን የበግ ለምድ ምሳሌ ዝርዘር እንመልከት፣

 

  1. የበግ ለምድ ለብሰው የሚመጡ ተኩላ ያላቸውእውነተኛ መስለው የሚመጡ ሐሰተኞች መምህራንን ነው፣ ነገር ግን በእውነተኛ ሃይማኖት ጸንተው ያሉትን ክርስቲያኖች ተመሳስለው ገብተው በተለያየ ዘዴ ምእመኑን በመቀሰጥናከእምነቱ በማናጋት ወደገሃነም ለማውረድ የሚሠሩትን የዲያብሎስንሠራተኞች ነው፡፡

  2. የበግ ለምድ መልበስምሳሌ የሚያሳየውማስመሰያአሠራራቸውን፣ ድራማ መሰል ጥረታቸውን ነው፡፡ተኩላ ለምድ የሚለብስሆኖ አይደለም፣ ተኩላ ለምድን ከሚለበስ ቢበላው ይመርጣልና፡፡ መናፍቃንም የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያን ባትኖር ይመርጣሉ፣ ነገር ግን ሊውጡት ያሰቡትን ምእመን እንደ ተኩላ ለመንጠቅ ያመቻቸው ዘንድ የቤተ ክርስቲያኗን ግእዝና ዜማ የወደዱ መስለው መታየት የጀመሩትምእመኑን ለማዘናጋት የፈጠሩት አዲሱ ዘዴ ነው፡፡ ነገር ግን ግብራቸው የተኩላ ግብርእንዲመስል፣ ለነዚህ ቀሳጥያን ጌታችንአስቀድሞ ሲመስልባቸው የበግ ለምድ ለብሰው የሚመጡ ተኩላ ነጣቂ አላቸው፡፡ ይህም ተኩላ በግን ለመምሰል የበግን ቆዳ ቢለብስ እንዳይዋሐደውና በግን እንዳይመስል እነሱም እንደ ድራማ ትምህርቱን ልስበከው፣ ዜማውን ላዚመው፣ ቅዳሴውን ልቀድሰው፣መዝሙሩን ልዘምረው ወዘተ ብለው ቢጥሩ እውነተኛውን የተዋሕዶ አገልጋይ፣ አማኝእና ክርስቲያን መሆን አይቻላቸውም፡፡

  3. የበግ ለምድ የተባለው ምሳሌ፣ለምድ የበግ አካል የነበረ እንጂ የተኩላ አካል አይደለም፣ተኩላው ከላይ ለምዱን ቢደርበው አካል ሆኖት ደመ ነፍስ እንዳይዘራና ተኩላ በግ እንዳይሆን ሁሉ መናፍቃንም የተዋሕዶን አሠራር ሳያምኑበት በማስመሰልና ማቅረብ ቢሞክሩም እንኳን ውጤቱ ሕይወት አልባ ዳንኪራ፣ በቀቢጸ ተስፋ ያቀረቡት ሙሾ አስመስሎባቸዋል፡፡ በእሁኑ ወቅት የጀመሩት የተዋሕዶ ምእመናን የሚወዱትን ግዕዝ መጥቀስ፣ ያሬዳዊ ዜማን አስመስሎ ለማቅረብ የተሞከረው ሕይወት አልባ እንቅስቃሴየዚህ ማሳያ ነው፡፡የተዋሕዶ ሕዝብ ማስተዋል ያለበትይህን ሕይወት አልባ ሩጫ፣ ክርስቲያን ሳይሆኑ ክርስቲያንን ለማታለል ያደረጉት  የቅስጥ ድራማ መሆኑን ነው፡፡

 

በወንጌል ትርጓሜ እነዚህን ቀሳጥያን በሁለት ዓይነት ይገልጻቸዋል፣

  1. ሃይማኖተኛ የሚመስሉ መናፍቃን መምህራን

  2. መንፈሳውያን የሚመሰሉ ሥጋውያን መምህራን ይላቸዋል፡፡ እነዚህ የተጠቀሱት ሁለቱ በተገቢው ሃይማኖት ላልተረዱ ሰዎች አደገኛ ናቸው፡፡ቅዱስ ጴጥሮስ እንዲህ በማለት ይገልጻቸዋል ስለመናፍቅነታቸው፣ የዋጃቸውን ጌታ ክደው … የሚያጠፋ ኑፋቄ አሾልከው ያገባሉ፡፡ብዙዎችም በመዳራታቸው ይከተሏቸዋል፡፡ ስለ ሥጋዊነታቸው ደግሞ … ይልቁንም በርኲሰት ምኞት የሥጋን ፍትወት እየተከተሉ የሚመላለሱ … ነውረኞችና ርኲሳን … ምንዝር የሞላባቸው ኀጢአትንም የማይተው ዓይኖች አሏቸው የማይጸኑትን ነፍሳት ያታልላሉ፣ መመኘትን የለመደ ልብ አላቸው የተረገሙ ናቸው (1ጴጥ 2፥1-16)ይላል፡፡

 

እነዚህ ሃይማኖተኛና መንፈሳውያን የሚመሰሉ የቤተ ክርሰቲያን ጠላቶችን ከላይ ከቅዱስ መጽሐፍ እንደተገለጸው፣ ምእመናን ማንነታቸውንና ዓላማቸውን መረዳት አለብን፡፡ ማንነታቸው መጽሐፍ እንደጠቀሰው ተኩላነት ነው፣ ማለትም ምንም ግእዝ ቢጠቅሱ ወይም ላላዋቂ ያሬዳዊ ዜማ ያዜምኩ ቢመስሉ እነሱ በልባቸው ከሃዲያን ናቸው፡፡ዓላማቸውም በመመሳሰልአቀራረብ ተቀባይነትን አግኝተው፣ ይህን እግዚአብሔርን የሚያከብር ሕዝብ ከእምነቱ ለማናጋት ነው፡፡

 

በመመሳሰል ”የማይጸኑ ነፍሳትን ያታልላሉ” እንዲል፣ ክርሰቲያን ልብ ሊለው የሚገባው ዋናው ነገር፣ የተዋሕዶ ተጻራሪዎች ሁሉ ሁል ጊዜ የመመሳሰል ስልታቸውን በመቀያየር ያልጸኑትን ምእመንዋን መሻማት የዘመናት አሠራራቸው እንደሆነ ነው፡፡ ለምሳሌ የፖርቱጋል ካቶሊክ ሚሲዮናውያን የካቶሊክ እምነትን ወደ አገራችን ለማስገባት በተለይ ቤርሙዴዝ፣ አንድሬ አብያዶ፣ ጴጥሮስ ፖኤዝና አልፎኑስ ሜንደዝ ወዘተ ተልከው ነበር፡፡ ከእነዚህ አብዛኞቹ ወደ አገራችን ሲመጡ ሆን ብለው አጥንተው ግእዝን መናገርናየያሬዳዊን ዜማ እስከማዜም የደረሱ ነበሩ፡፡ እንዲያውም በሮም ቫቲካን የኢትዮጵያ ኮሌጅ በማቋቋም የኢትዮጵያን ቤተ ክርስቲያንን ቋንቋግእዝን የሚናገሩና ያሬዳዊን ዜማ የሚያዜሙ ነጮችን በመላክ የጎንደርን ቤተ መንግሥት እንዴት ሲያተራምሱት እንደ ነበሩ ታሪክያስረዳናል፡፡ ዛሬም የመመሳሰል ዓላማቸውን እውን ለማድረግ በአገር ውስጥ እንቅስቃሴአቸው የተለያየ ገጽታዎች ሲያሳዩ ይታያል፡፡ ለምሳሌ ይህንኑ ክብር ታቦትና ማኅሌት የሚወድ ህዝብን ለማታለልና ወደራሳቸው ለማስገባት አንድ ነን የሚል ስብከት፣ በዋና ዋና ከተሞች ባላቸው የጸሎት ቤት ታቦት አለን፣ ማኅሌት ይቆማል ሲሉ፣ ፕሮቴስታንት በበዙበት በሚመሰላቸው አካባቢ ደግሞ ፕሮቴስታንትንመመሳሰልይስተዋልባቸዋል፡፡ ሌሎችምየመመሳሰል አባዜ የተጠናወታቸው መናፍቃን እና ሥጋውያን እንደተለመደው ውጫውያንም ሆኑ የአገራችን በተለይ ከተዋሕዶ የወጡ ማለትም በቀሳጢዎች የተበሉ ካፈርኩ አይመልሰኝ እንዲል በቁጭት ሁል ጊዜ ይህንን ሕዝብ በመጎምዠት ለአጋንንት አሳልፈው ለመሰጠት ሲቋምጡና ለመንጠቅ ሲተጉይገኛሉ፡፡

 

ከላይ በግልጽ ለይተን አጽራረ ቤተ ክርስቲያንን ማንነት ባጭሩ ማብራራት እንደሞከርነው ሁሉ፣ ለምን ስልታቸውን መቀያየር አስፈለጋቸው የሚለውን ማየት ግድ ይለናል፡፡ ስልታቸውን መቀያየር ያስፈለገበት ምክንያት የተዋሕዶ እምነትና ሥርዓት አንዳች የማመን ፍላጎት አድሮባቸው አይደለም፡፡ ቤተ ክርስቲያኗን ሲወቅሱና ሲከሱ ነበርና፡፡

 

ለዚህ ምክንያት የደረሰባቸውን ክስረት መመልከት ተገቢ ነው፡፡ ይህም፡-

  1. የኢትዮጵያ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያን ባደረገችው ጸረ ተሐድሶ መናፍቃን ዘመቻ ህዝቡን በማስተማሯ ህዝቡ እኲይ ተግባራቸውን ስለተረዳ

  2. ህዝቡ ራሱ መልስ በመስጠት ራሱን መከላከል ስለጀመረ

  3. በስህተት መንገዳቸው ተጉዞ የነበረው ሕዝብ ወደ ቤቱ መመለስ ስለጀመረ

  4. ቤተ ክርስቲያኗን በማጥላላት ያደረጉት ዘመቻ በመክሸፉ እንደማያዋጣቸው ስለተረዱ

  5. ከቤተ ክርሰቲያኗ ህዘቡን እየደለሉ በማስኮብለል የሚያገኙት ይሁዳዊ ምንደኝነት ስለቀረባቸው

  6. የካሴት ሽያጭ፣ የህዝቡ መዋጮ ወዘተ ገቢ ስለቀረባቸው ፤ ወዘተ ነው፡፡

 

ከላይ የተዘረዘረውና ሌላም የኪሳራ ምክንያቶቻቸውሳይወዱ በግድ ልባቸውን ጸፍቶ አፋቸውን ከፍቶ አነጋግሯቸዋል፡፡ ክርስቲያኑ ሁሉ ይህን ሁኔታ በቀላሉ ማየትናበዝምታ ማለፉ ተገቢ አይደለም፡፡ ይህ ሁሉ ክስረት ያናጋው መናፍቅ ከዚህ የበለጠ ሌላ የድፍረት ዘዴ ለመፍጠር መሞከሩ አይቀሬ ነው፡፡ ሊሰመርበት የሚገባው ጉዳይበግእዝና በያሬዳዊ ዜማ ያዘጋጁት ዝግጅት ገበያ ተኮርያውም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ምእመናንን ማእከል ያደረገ መሆኑን ነው፡፡ልንረዳው የሚገባን አንዳንድ ምእመናን የማስመሰል ተንኮላቸውን ባለመረዳት ካሴታቸውን መግዛትና ማዳመጥ ሁለት አደጋ ያመጣባቸዋል፣ አንደኛው በመናፍቅ መንፈስ የተዘጋጀው ዜማ ማዳመጥ ራሱ ቆይቶ መናፍቅ ሚያደርግ መሆኑን፣ ሁለተኛው የመናፍቃን ከኪሳራቸው አንዱ ገንዘብ በመሆኑ አማኙን ህዝብ የሚያስቱበትን ገንዘብ ለነሱ መገበር ራሱ ከመናፍቅነት አይለይም፡፡

 

የአሁኑየለየላቸው መናፍቃን ወዳጅ የመምስል ስልታቸው ከላይ ለመጥቀስ እንደተሞከረው ተኩላ በግን ለመምሰል ቆዳ ብትደርት ተኩላነቷን እንዳይቀይር ሁሉ ምእመናንን ያታልላሉ መስሎአቸው አንዴ ግእዙን አንዴ ዜማውን ያልኩ ቢመስላቸውም ”ዪህቺ ጠጋጠጋ … ” እንዲሉ ለእውነተኛ ክርስቲያኖች ይህ መሰሪነታቸው ግልጽ ነው፡፡ በመሆኑም ዓላማቸው የቤተክርስቲያን ተቆርቋሪ፣ ታሪኳን ተናጋሪ፣ ዜማዋን ወዳጅ፣ ጥንታዊነቷን አክባሪ ወዘተ በመምሰል የህዝቡን ልብ ለማግኘት የተዘየደ ዘዴ ለማንም አይጠፋውም፡፡ ነገር ግን ዘዴው ጊዜ ያለፈበት ድሮ በነ ዐጼ ሱሱንዮስ ዘመን እነ አልፎኑስ ሜንደዝ የሞከሩት ነገር ግን እነ ዐጼ ፋሲል አውቀውት ምላሽ የሰጡበት፣ የማይረሳ ጠባሳ ጥሎ ያለፈ መሆኑ ወገኔ ትዝ ሊለው ግድ ይለዋል፣ የብዙ ክርስቲያን ደም ተከፍሎበታልና፡፡ አሁንም ይህች መመሳሰልና ቀይ መስመር መጣስ የነ አልፎኑስ ሜንደዝ ድፍረት ጋር አንድ ናትና ከወዲሁ ካልታሰበባት በኋላ ከባድ ዋጋ እንዳታስከፍል ስጋታችን ነው፡፡

 

ዋናው ጉዳይ ባለፈው በተካሄደው የጸረ ተሐድሶ ዘመቻ መናፍቃን የፈራረሰባቸውን ሁለንተናዊ ክስረት ማለት በቤተ ክርሰቲያኗ ውስጥ ምእመኑን መናፍቅ የማድረግ ቅሰጣ ሲመታባቸውና ሴራው ሲከሽፍባቸው፣ ውድቀታቸውን መልሶ ለመገንባት ስፖንሰራቸው የሰጣቸው አዲሱ አሰራር  በግልጽ ውዳሴ ለኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያንቋንቋ ግእዝ፣ ዜማዋ፣ ታሪኳ ወዘተ ማቅረብ ነው፡፡ ይህ የለየላቸው መናፍቃን ደርሶ የቤተ ክርስቲያኗወዳጅ መምሰል ለኛ አዲስ ነገር አይደለም፤ ተሐድሶቹም ሲጠቀሙበት የነበረ ስልት ነው፡፡ የተሐድሶ መናፍቃን ዘመቻ በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ላይ በሚለው መጽሐፍ (በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በሰንበት ትምህርት ቤቶች ማደራጃ መምሪያየማኅበረ ቅዱሳን ዶክሜንቴሽን ክፍል፣ ቁጥር 1፣ ሚያዝያ 2003 ዓም ገጽ 58)  እንደተጠቀሰው ተሐድሶዎች ያቀዱት ዋና ጉዳይ ተሐድሶ እንኳን እንደሆነ የማያውቅ ግን ተሐድሶ የሆነ ትውልድ መፍጠር እና ሳያውቀው የሚደግፍ ቲፎዞ ማፍራት ነበር፡፡ ማለትም በቤተ ክርስቲያኗ ውስጥ ሆኖ የመናፍቅን ዶግማ የተቀበለ የእነሱን ዜማ የሚያዜም ወዘተ ቡድን ማመቻቸት ነበረ፡፡ ስልቶቹን መጽሐፉ እንዲህ ይጠቅሳቸዋል፣

 

  • ተቆርቋሪ መምሰል፣ ገንዘብና እርዳታ በመስጠት፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን ተቋማትና ሕዝቡን መያዝ እና ቲፎዞ እንዲሆን ማድረግ፣

  • ኦርቶዶክስን የማያውቅ፣ ፕሮቴስታንት የሆነ፣ ነገር ግን ተሐድሶ (ፕሮቴስታንት) መሆኑን እንኳ የማያውቅ ምእመን ማፍራት፡፡ ማተብ ያሰረ፣ ነጠላ የሚያጣፋ፣ እምነቱና መንፈሱ ግንፕሮቴሰታንት የሆነ፣ ሆኖም ፕሮቴስታንት ነኝ የማይል (ፕሮቴስታንት መሆኑን ሳያውቅ ስለተለወጠ)፣ ”እኔ ኦርቶዶክስ ነኝ” እያለ የሚናገር(ሀርድ ዌሩ ሳይቀየር ሶፍት ዌሩ የተቀየረ)ትውልድ ማፍራት ነው፡፡

 

እንዲሁም በዚህ ወቅት ፕሮቴስታንቱ በግልጽ መሰደቡንና መወገዙን በውስጥ አድርገው በውጪ ውዳሴ የጀመሩት፣ የኦርቶዶክስ ምእመናንን በመመሳሰል ለመሳብና ቢቻላቸው ፕሮቴስታንት ለማድረግ ባይሆንም ቲፎዞ ለማድረግ፣ እንዲሁም ቲፎዞ በመሆን መካከል  በሚፈጠረው ያለመግባባት ክፍተት ያልጸኑትን ለማግኘት ነው፡፡

 

ባጠቃላይምከላይ እንደገለጽነው መናፍቃን ምን ጊዜም የተወሰነ ሃይማኖታዊ የትውፊት፣ የዶግማ፣ የሥርዓት ወዘተ ገደብ የሌላቸው በመሆኑ የሌላውን መንጋ ለመቀሰጥ ቢቻላቸው በማጥላላት ባይቻላቸው በመመሳሰል ራሳቸውን እየለዋወጡ የተለያየ ስልት እንሚጠቀሙ መረዳት ተገቢ ነው፡፡ ለመመሳሰል በሚያደርጉት ቅሰጣ የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለዘመናት ያቆየችውን ትውፊት፣ ቅርስና ሀብት እንዲሁም ግእዝ ቋንቋና ያሬዳዊ ዜማን ማንም እንደፈለገ አስመስሎ ባልተገባ መንገድ የመቀራመቱ ድፍረት ቤተ ክርስቲያን እንዴት ታየዋለች? ያውም ቤተ ክርስቲያን የማትፈቅደው የመናፍቅ ድርጅት በሀብቷ ላይ ሲፈነጭ፣ ይህስ ጉዳይ ከህግ አንጻር እንዴት ይታያል? አንድ ተቋም ያላትን ሀብት ያለፈቃዷ ማንም መጠቀም ይችላልን? ምእመናን በሙሉ በተለይ የሕግ ባለሙያ ልጆቿ እንዲነጋገሩበት የሚስፈልግ ጉዳይ ነው፡፡ ሌላው ምእመናን መገንዘብ የሚገባን መናፍቅ ያወጣውን የቅስጥ ዜማ ያሬዳዊ መስሎን በመጠቀም የዓላማቸው ሰለባ እንዳንሆን አንዱ ለሌላው ማሳሰብና ማስረዳት ተገቢ ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የበግ ለምድ ለብሰው ማለት እውነተኞች መስለው ከሚመጡ ሐሰተኞች፣ ሃይማኖታውያን መስለው ከሚመጡ መናፍቃን፣ መንፈሳውያን መስለው ከሚመጡ ሥጋውያን መምህራን ተጠንቀቁ ብሎ አስተምሮናልና እንጠንቀቅ፣ እርስ በርሳችንም እንጠባበቅ፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወለወላዲቱ ድንግል ወለመስቀሉ ክቡር አሜን፡፡


አዲስ ዓመት

ጳጉሜን 5 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዳዊት ደስታ

ኢትዮጵያ የወራት ሁሉ መጀመሪያ መስከረም ነው፡፡ ይህ ወር ዘመን መለወጫ፣ ዕንቁጣጣሽ፣ ቅዱስ ዮሐንስ እየተባለ ይጠራል፡፡ ስለ አዲስ ዓመት በተለያየ ስም የመጠራቱ ታሪካዊ አመጣጥና ስያሜ መነሻ አሳቡ ምን እንደሆነ እንደሚከተለው እንመለከታለን፡፡

 

ዘመን መለወጫ

ዘመን መለወጫ መስከረም ወር የሆነበት ምክንያት “ብርሃናት /ፀሐይ፣ ጨረቃ፣ ከዋክብት/ የዓመት ዑደታቸውን በጳጉሜ ወር ጨርሰው በመስከረም ወር ስለሚጀምሩ ነው፡፡ ሌሊቱ ከቀኑ ጋር ይተካከላል፡፡ ዓመቱን ጠንቅቀው ቢቆጥሩ 364 ቀናት ይሆናል፡፡ “ሌሊቱም ከቀኑ ጋራ ይተካከላል፡፡ ዓመቱም ጠንቅቆ ቢቆጥሩት ሦስት መቶ ስልሳ አራት ቀን ይሆናል፡፡ /ሄኖክ.26፥44/ “ዘመናችንን እንደ ቀድሞ አድሱ” /ሰ.ኤር.5፥21/ እንዲል፡፡

በዘመነ ኖኅ ዓለምን ንፍር ውኃ አጥለቅልቆት ከቆየ በኋላ ዳግመኛ ውኃው የጎደለበት በመሆኑ /ኩፋሌ 7፥1/ “በመጀመሪያው ወር መባቻም ምድር ታየች” እንዲል፡፡

 

ዕንቁጣጣሽ

ዕንቁጣጣሽ የተባለበት ምክንያት አንደኛ “ዕንቁ – ዕፅ አመጣሽ” ብሎ የአበባውን መፈንዳት ያመለክታል፡፡ ሁለተኛ ኖኅ ለሦስቱ ልጆቹ አህጉራትን በእጣ ሲያካፍላቸው አፍሪካ ለካም ደረሰችው፡፡ በአፍሪካ ምድርም ሲገባ በመጀመሪያ ያረፈው በኢትዮጵያ ነበር፡፡ ሀገሪቱም በአደይ አበባ አሸብርቃ ነበር፡፡ ወሩ ወርኀ መስከረም በመሆኑ ደስ ብሎት ዕንቁ ዕጣ ወጣሽልኝ ይህችን ወቅት እንቁጣጣሽ ብሏታል፡፡ ሦስተኛው /1ነገ.10፥1-10/ ኢትዮጵያዊቷ ንግሥት ሣባ /አዜብ የንጉሡን ጥበብ ከመስማት ማየትን መርጣ ወደ ንጉሥ ሰሎሞን ከብዙ ሠራዊቶቿ ጋር የእጅ መንሻ በመያዝ ሄደች፡፡ ንጉሡም በደስታ ተቀብሎ እርሱም “እንቁ ለጣትሽ ጌጥ ይሁንሽ” በማለት አራት አይነት ቀለም የሚታይበት በቀንና በሌሊት የምታበራ ቀለበት ሰጥቷታል፡፡ ወሩም ወርኀ መስከረም ነበር፡፡ ከዚህ በመነሣት እንቁጣጣሽ የሚለው ስያሜ ወጥቷል፡፡

 

ቅዱስ ዮሐንስ

ሦስተኛው የአዲስ ዘመን ስያሜ ቅዱስ ዮሐንስ ነው፡፡ የመጥምቁ ዮሐንስ ተግባር ለዘመነ ወንጌል በር ወይም መነሻ እንዲሆን ለኢትዮጵያ ዐውደ ዓመት መስከረም አንድ ቀን እንዲከበር አባቶች ወስነዋል፡፡ /ድርሳነ ዮሐንስ አፈወርቅ ገጽ 1-3/ መጽሐፈ ስንክሳር “የመስከረም ወር የተባረከ ነው፡፡ እርሱም የግብጽና የኢትዮጵያ ዓመቶች መጀመሪያ ነው፡፡ የዚህ ወር ቀኑና ሌሊቱ እኩል 12 ሰዓት ነው፡፡ ከዚህ በኋላ ቀኑ እየጎደለ ይሄዳል” እንዲል፡፡

 

በአጠቃላይ ዘመን መለወጫ ከላይ ባየናቸው የተለያየ ስያሜ ይጠራ እንጂ ዘመኑ አዲስ እየተባለ ቢጠራም አዲስ መሆን ያለበት ወርና ወቅቱ ብቻ ሳይሆን የእኛ የክርስቲያኖች ሥርዓት ነው፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሰውነታችሁን አታርክሱ የእግዚአብሔር ማደሪያ ነውና እያለ በመዋዕለ ሥጋዌው ያስተምር ነበር፡፡ አዲስ ዓመት ሲመጣ በኀጥያት፣ በተንኮል፣ በክፋት የቆሸሸው ሰውነታችን በንስሓ፣ በቅዱስ ቊርባን፣ በመልካም ተግባር አዲስ ልናደርገው ይገባናል፡፡

Kiduse Rufyele

መልአከ ሰላም ወጥኢና

ጳጉሜን 2 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ

Kiduse Rufyele

ጳጉሜን፡- “ጭማሪ፣ ተወሳክ፣ አምስት ቀን ተሩብ” የሚል ትርጉም አለው፡፡ ጳጉሜን 13ኛ ወር ትባል እንጂ በውስጧ የያዘቻቸው ቀናት ቁጥር በአንድ ሳምንት ካሉ ቀናት ያነሱ ናቸው፡፡ እንደዚያም ሆኖ ኢትዮጵያን ብቸኛዋ የዓለማችን ባለ 13 ወራት ሀገር እንድትሆን ያስቻለች ልዩ ወር ናት፡- ወርኀ ጳጉሜን፡፡

 

ጳጉሜን ገዝፋና ጎልታ የምትታየው በመንፈሳዊ  ዓለም ነው ማለት ይቻላል፡፡ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የዓለም ፍጻሜ መታሰቢያ ተደርጋ ትታሰባለች፡፡ በዚህ የተነሣ በርካታ የቤተ ክርስቲያኒቱ ተከታዮች ወርኀ ጳጉሜን በጾምና በጸሎት /በሱባኤ/ ያሳልፏታል፡፡ በተለይም እንደ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ በቅዱስ ሩፋኤል ዕለት ሰማያት የሚከፈቱበት /ተርኅዎ ሰማይ/ መሆኑን በማመን ምእመናን ወደ ፈፍላጋት በመሄድ እንዲሁም በጳጉሜን ቀናት በሚዘንበው ዝናብ በመጠመቅና በረከትን ይሻሉ፡፡ ጸሎታቸውንም ከምንገባም በበለጠ ያቀርባሉ፡፡

 

ወርኀ ጳጉሜን የጌታችን ምጽአት የሚታሰብባት በመሆኗ የሚዘመረው መዝሙር፣ የሚነበቡ ምንባባትና ቅዱስ ወንጌሉ እንዲሁም የሚሰበከው ምስባክ ይህንኑ የሚያሳዩ ናቸው፡፡ ከነዚህም ውስጥ፡-

 

“ከመ ንተ መብረቅ ዘይወፅእ እምጽባሕ ወያስተርኢ እስከ አረብ ከማሁ ምጽአቱ ለወልደ እግዚአብሔር ምስለ ኀይለ ሰማያት በንጥረ መባርቅት/ከ/ ምስለ አላፍ መላእክት /ከ/ ወኲሎሙ ሊቃነ መላእክት /ከ/ አክሊለ አክሊላት ዲበ ርእሶሙ” ይህም ማለት፡-


“መብረቅ ከምሥራቅ ወጥቶ እስከ ምዕራብ እንዲታይ በመባርቅት ፍጥነት፡ – ሰማያውያን ኀይላት ከብዙ መላእክትና የመላእክት አለቆች ጋር በካህናት ራስ ላይ ያሉት አክሊሎች መገኛ የሆነው የሾህ አክሊል ደፍቶ የእግዚአብሔር ልጅ እንዲሁ ይመጣል” ማለት ነው፡፡

 

በየዓመቱ ጳጉሜን ሦስት ቀን የሊቀ መላእክት የቅዱስ ሩፋኤል ዓመታዊ ክብረ በዓልም በመላው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አብያተ ክርስቲያናት፣ በልዩ ልዩ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ይከበራል፡፡ ይህም ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል ከከበሩት ቅዱሳን መላእክት ሦስተኛው ነው፡፡ መጽሐፍ፡-  “ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ” እንዲል፡፡ /ጦቢት 12፥15/

 

መላእክት ሲፈጠሩ የማይሞቱ፣ የማይራቡ፣ ጾታ የሌላቸው ዝንተ ዓለም በቅድስና ጸንተው እንዲያገለግሉና ፈጻምያነ ፈቃድ እንዲሆኑ ነው፡፡ በዚሁ መሠረት ከአንዱ ዲያብሎስና ከተከታዮቹ አጋንንት በቀር ቅዱሳን መላእክት ሁሉ በተፈጠሩበት ዓላማ ጸንተው ያሉና የሚኖሩ ናቸው፡፡ በዚሁ አገልግሎታቸውም የእግዚአብሔርንና የሰውን በጎ ፈቃድ ሲፈጽሙ ይኖራሉ፡፡ ያለማቋረጥ ፈጣሪያቸውን ልዑል እግዚአብሔርን ከሚያመሰግኑ ቅዱሳን መላእክት አንዱ መልአከ ጥኢና ወሰላም /የሰላምና የጤና መልአክ/ የሚባለው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡

 

“ሩፋኤል” የሚለው የስሙ ትርጓሜ ደስ የሚያሰኝ፣ ቸር፣ መሐሪ፣ ቅን የዋህ ማለት ነው፡፡

በሰውነታችን ላይ የሚወጣውን ደዌም ሆነ ቁስል ይፈወስ ዘንድ ከልዑል እግዚአብሔር ሥልጣን ተሰጥቶታል፡፡ “በሰው ቁስል ላይ የተሾመ ከከበሩ መላእክት አንዱ ቅዱስ ሩፋኤል ነው” መጽሐፈ ሄኖክ 6፥3 ይላል፡፡ ለቆሰሉ ፈውስን የሚያሰጣቸው ለማሕጸን ችግር ሁሉ ለሴቶች እረዳታቸው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡ ሴት በፀነሰችበት ወቅት ቅዱስ ሩፋኤል አይለያትም ሕፃኑ አርባ ቀን ሞልቶት፣ በማሕፀን እያለ “ተስእሎተ መልክዕ” /በሥላሴ አርአያ መልኩ መሳል ከጀመረበት ቀን አንሥቶ እስከሚወለድበት ቀን ድረስ/ ቅዱስ ሩፋኤል አይለየውም፡፡ በወሊዳቸው ቀን ሴቶች ከሚደርስባቸው ጭንቀትና ሕመም ስሙን ጠርተው ይማጸኑታል፡፡ ፈታሔ ማሕፀን ነውና ቅዱስ ሩፋኤልም ጭንቀታቸውን ያቀላል፡፡

 

ቅዱስ ሩፋኤል በሰውነት ያለን ረቂቅ ርኩስ መንፈስ ያውቃል፡፡ አስማንድዮስ የተባለ ጋኔን በወለተ ራጉኤል ጭን ላይ አድሮ ባሎቿን እየገደለ ቢያሰቃያት ቅዱስ ሩፋኤል ጋኔኑን አስጨንቆ አስወጥቶላታል፡፡ /ጦቢት.3፥8-17/

 

“ዳግመኛም እግዚአብሔር ሩፋኤልን፣ አዛዝኤልን እጁን እግሩን አስረህ በጨለማ ውስጥ ጣለው አለው” /ሄኖክ 3፥5-7/ በዚህ መሠረት ለቃየን ልጆች ሰይፍና ሾተል መሥራትን፣ የምንዝር ጌጥ ማጌጥን፣ መቀንደብን ያስተማረ አዛዝኤል የተባለውን ጋኔን በእሳት ሰይፍ እየቀጣ በረቂቅ አስሮ ወደ ጥልቁ የጣለው ይኸው መልአክ ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡ /ሄኖክ፤2፥18/ የሰው ልጆች ከተያዙበት የኀጢአት ቁስል ይፈወሱ ዘንድ በአማላጅነቱና በጸሎቱ የማይለይ መልአክ ነው፡፡ “በበሽታ ሁሉ ላይ በሰው ልጆችም ቁስል ላይ የተሾመው ቅዱስ ሩፋኤል ነው፡፡” በማለት ሄኖክ ከእግዚአብሔር መልአክ ያገኘውን የምስክርነት ቃል ጽፏል፡፡ /ሄኖክ.10፥13/

 

የጦቢትን ልጁ ጦቢያን በሰው አምሳል ተገልጦ ከተራዳው በኋላ ወደ ሰማይ በሚያርግበት ጊዜ ራሱን ሲገልጥ “የቅዱሳንን ጸሎት ከሚያሳርጉ ወደ ከበረ ወደገነነ ወደ እግዚአብሔር ጌትነትም ከሚያገቡ ከከበሩ ከሰባቱ አለቆች አንዱ አለቃ እኔ ሩፋኤል ነኝ አላቸው” /ጦቢት.12፥15/

 

የቅዱስ ሩፋኤል በዓሉ የሚከበርባቸው ምክንያቶችም ሁለት ናቸው፡፡ እነርሱም አንደኛው በዓለ ሢመቱን ምክንያት በማድረግ ሲሆን ሁለተኛው የቅዳሴ ቤቱ የተከበረበት ስለሆነ ነው፡፡ ይኸውም በመጽሐፈ ስንክሳር እንዲህ ተመዝግቧል፡፡ ከእስክንድርያ አቅራቢያ በምትገኝ በደሴት የታነጸች ቤተ ክርስቲያኑ በከበረ ሊቀ ጳጳሳት ቴዎፍሎስ ዘመን በውስጧ ተአምር የተገለጸባት የከበረችበት ነው፡፡

 

ይህም እንዲህ ነው፤ ሀብትም ሴት ወደ ሊቀ ጳጳሳት አባ ቴዎፍሎስ መጥታ ሳለ ከእርሷ ጋርም ብዙ ሰው ነበረ፡፡ ከባሏም የወረሰችው ብዙ ገንዘብ አላት፡፡ በሊቀ ጳጳሳቱ ቤት አንጻር ያለውን ኮረብታ አስቆፈረችው በዚያም የወርቅ መዝገብ ተገለጠ፡፡ በዚያም ወርቅ ብዙዎች አብያተ ክርስቲያናትን አነፀ፤ ከእርሳቸውም አንዲቱ የመላአክት አለቃ በሆነ በከበረ መልአክ ቅዱስ ሩፋኤል በስሙ የታነፀች ይህች ናት፡፡ ሥራዋንም በፈጸመ ጊዜ እንደዛሬው በዚች ቀን አከበራት፡፡ ብዙ ምእመናንም በቤተ ክርስቲያን ውስጥ እያሉ ቤተ ክርስቲያኒቱ ፈጽማ ተናወጸች፤ ያቺ ደሴት በታላቅ አንበሪ ጀርባ ላይ የቆመች ናትና፡፡ የሰዎች ብዛትም በከበደው ጊዜ ቤተ ክርስቲያኒቱን ያፈርሳት ዘንድ ሰይጣን አነሣሣው፡፡ ወደ ክብር ባለቤት እግዚአብሔርም በከበረ መልአክ ሩፋኤል ስም ጮሁ፡፡ ያን ጊዜ ይህ የከበረ ሩፋኤል ያንን አንበሪ በጦሩ ወግቶ እንዲህ አለው “እግዚአብሔር አዝዞሃልና ከቦታህ ሳትናወጽ ጸጥ ብለህ ቁም!” አንበሪውም ጸጥ ብሎ ቆመ፡፡ አልታወከም፡፡ በውስጧም ድንቆች ተአምራቶች ተገለጡ ለሕሙማንም ፈውስ ሆነ” ይላል፡፡

 

በቀኖና ቤተ ክርስቲያን በወርኀ ጳጉሜን ከሚታሰቡት እና ከሚከበሩት በዓላት መካከል ጳጉሜን 2 ቀን የሐዋርያው ቅዱስ ቲቶ በዓለ ዕረፍቱ፣ እንዲሁም ጳጉሜን 5 ቀን የነቢዩ አሞጽ ዕረፍት ይጠቀሳሉ፡፡

 

ፈጣሪያችን ከሊቀ መላእክት ቅዱስ ሩፋኤል እና ከቅዱሳኑ በረከት ረድኤት ያሳትፈን፡፡

ቤተ ክርስቲያንና የፓትርያርክ ምርጫ

ነሐሴ 25 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ብርሃኑ አድማስ

ቤተ ክርስቲያን አንዲት፣ ቅድስት፣ ኩላዊትና ሐዋርያዊት መሆኗን ጥንታውያን አብያተ ክርስቲያን ሁሉ ይቀበላሉ፤ በመሠረተ እምነታቸው ውስጥም አካትተው በጸሎትና በአስተምህሮ ይጠቀሙበታል፡፡የዚህ መሠረታዊ ምክንያቱ ደግሞ ከዘመነ ሐዋርያት ጀምሮ ይህ ትምህርት ቢኖርም ነገር ግን መልእክቱን በአግባቡ ካለመረዳት የተነሣ እነ አርዮስና መቅዶንዮስ በትውፊት ከሐዋርያት ጀምሮ የመጣውን የቅዱሳት መጻሕፍት ትርጓሜ መሠረት መቀበልን ቸል ብለው በራሳቸው መንገድ ሔደው ስለሳቱ በጉባኤ ኒቅያ በማያሻማ መንገድ ቤተ ክርስቲያን አንዲት፣ቅድስት፣ ሐዋርያዊት እና ኩላዊት መሆኗን አስቀመጡ፡፡ በኋላ በጉባኤ ቁስጥንጥንያ ደግሞ ሁላችንም እንድንጸልይበት በተዘጋጀው አንቀጸ ሃይማኖት ላይ (ጸሎተ ሃይማኖት) ‹‹ ወነአምን በአሐቲ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን እንተ ላዕለ ኩሉ ጉባኤ ዘሐዋርያት›› የሚለው የጸሎታችን መፈጸሚያ እንዲሆን ተደነገገ፡፡ በዚህም መሠረት እነዚህን ዓለም አቀፍ ጉባኤያት የሚቀበሉ ሁሉ የሚቀበሉትና የሚመሩበት መሠረታዊ ትምህርተ ሃይማኖት /doctrine/ ሆነ፡፡

ይሁን እንጂ እየዋለና እያደረ ሲሔድ ቃላቱን ተርጉመው የሚረዱበት ሁኔታ እንደገና እየተለያየ መጣ፡፡ ለምሳሌ ያህል ከዚሁ አንቀጸ ሃይማኖት የሚነሱትን ሦስት መሠረታዊ ልዩነቶች ማየት ይቻላል፡፡ የመጀመሪያው ራሱ‹‹ቤተ ክርስቲያን›› የሚለውን ጽንሰ ሀሳብ መረዳት ላይ ያለው ልዩነት ነው፡፡ በፕሮቴስታንቱ ዓለም ቤተ ክርስቲያን በአንድ ቦታ የተሰባበሰቡት ሰዎች ኅብረት ብቻ ነው፡፡ ከዚህ አለፍ የሚሉትም ቢሆን በምድር ያለውን የአማኞቻቸውን ኅብረት አንድ መንጋ እንዲሁም በሰማይ ያሉትን ደግሞ ሁለተኛ መንጋ አድርው በአንድ እረኛ ሁለት መንጋ ሀሳብ የሚያራምዱ እንደ ሆኑ የምዕራባውያን ጽሑፎች ያሳያሉ፡፡ በምሥራቃውን ትውፊት ወይም በኦርቶዶክስ ግን ‹ቤተ ክርስቲያን› ማለት በምድር ያሉት ምእመናንና ተጋድሏቸውን የፈጸሙ ቅዱሳን ኅብረት ወይም አንድነት ናት፡፡ “እንተ በምድር ሥረዊሃ ወበሰማይ አእጹቂሃ..” “ሥሮቿ በምድር ቅርንጫፎቿም በሰማይ ያሉ” የሚለው የቅዱስ ያሬድ ትምህርትም ለዚህ ትልቅ አስረጂ ነው፡፡ በሰማይ ያሉት በዚህ በእንግድነት ከምንኖርበት ምድር ተጋድሏቸውን ፈጽመው ሀገራቸው ገብተው ሽልማታቸውን ተቀብለው በድል ዝማሬ ላይ ያሉ ሲሆን በዚህ ያለነው ደግሞ በዕድሜ ዘመናችን እየተጓዝን ያለንና ገና ተጋድሏችን ያለፈጸምን መሆናችን እሙን ነው፡፡ ሆኖም በምሥጢራተ ቤተ ክርስቲያንና ብልቶቹ በሆንለት በቤተ ክርስቲያን ራስ በክርስቶስ አንድ ስለሆንን ቤተ ክርስቲያን አንዲት ብቻ ናት፤ መንጋው አንድ እረኛውም አንድ፡፡ ለምሳሌ በእኛም ሆነ በሌሎቹ ኦርቶዶክሶች ያለውን ቅዳሴ በአስተውሎት ብንመረምረው ይህን ዶግማ ፍንትው አድርጎ ያሳየናል፡፡ ወደ ፊት በደንብ የምናየው ቢሆንም ለቤተ ክርስቲያን አስተዳደር መነሻውና መሠረቱ ይህ ነው፡፡

ታዲያ ይህን ‹‹ ቤተ ክርስቲያን አንዲት ናት›› የሚለውን አንቀጹ ራሱ መጽሐፍ ቅዱሳዊ በመሆኑ ሁሉም ቢቀበሉትም በትርጉም ግን ልዩነት ተፈጥሯል፡፡ የሮማ ካቶሊክ ‹አንድነትን›› በሮማው ፓፓ ሥር በመተዳደር ስትተረጉመው ኦርቶዶክሶቹ ግን አንድነት የሚገለጸው ዓለም በሙሉ በአንድ በመተዳደሩ አይደለም፤በምድር ተጋድላቸውን እያደረጉ ያሉ ምእመናንን በአንድ ምድራዊ ሃይማኖታዊ ተቋም አስተዳደርም የአነድነቱ ምንጭ አይደለም፤ ነገር ግን አማናዊ ሥጋውንና ደሙን ስንቀበልና የክርስቶስ ብልቶች ስንሆን ያን ጊዜ በአንዱ በክርስቶስ አንድ እንሆናለን ግንዱ አንድ ስለሆነ በዚያ የወይን ግንድ ያሉ ምእመናን ሁሉ በዚያው ግንድ ላይ በመሆናቸው ወይም አካሉ በመሆናቸው አንድ ናቸው፤ቤተ ክርስቲያንንም አንድ የሚያሰኛት ይህ የአንዱ ክርስቶስ ብልትነታችንንና አንድ አካል መሆናችን ነው ፡፡ “…ይዌልጦሙ በቅጽበት አባላተ ክርስቶስ ይኩኑ፤ በኃይለ ጥበቡ መንክር ወዕጹብ ኪኑ” “ድንቅና ዕፁብ በሆነ በጥበቡ ኀይል የክርስቶስ አካላት ይሆኑ ዘንድ በቅጽበት ይለውጣቸዋል፡፡” እንዳለ የመልክአ ቁርባን ደራሲ፡፡የኦርቶዶክሳውያን ትርጓሜ ይህን መንፈሳዊነትንና ከክርስቶስ ጋር ያለንን ውሕደት መሠረት ያደረገ ነው፡፡

 

ከዚሁ ጋር በትልቁ መሠረት የሚሆነው ደግሞ ‹‹ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊት ናት›› የሚለው እምነት ነው፡፡ እዚህም ላይ ትልቅ ልዩነቶች አሉ፡፡ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርዊት ናት የምትባለው መቼ ነው የሚለውን ጥያቄ ሲመልሱ ኦርቶዶክሳዊያን ሦስት ነገሮች ሲሟሉ ነው ይላሉ፡፡ የመጀመሪያው ሢመተ ጵጵስና ወፓትርያርክን የሚመለከት ነው፡፡ ይህም አንዲት ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊት የምትባለው ጌታ ከሾማቸው ከሐዋርያት አንሥቶ ያልተቋረጠ ክትትል ያለው የሢመት ሐረግ ሲኖር ነው፡፡ ለምሳሌ የእኛ ከቅዱስ ማርቆስ ወንጌላዊ አንሥቶ ሳይቋረጥ እስከ ቄርሎስ ስድሰተኛ (116ኛው) ፓትርያርክ ከደረስ በኋላ ለእኛ 117ኛ ሆነው አባ ባስልዮስ ኢትዮጵያዊ ተሾሙ፡፡ አሁን 121ኛው አባ ጳውሎስ ሆኑ ማለት ነው፡፡ ሁለተኛው ቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊት የሚያሰኘው ደግሞ ሐዋርያዊ ትዉፊትን ተቀብላ የምትተገብር መሆኗ ነው፡፡ ከእነዚህም አንዱ ጳጳሳትን በተለይም ፓትርያርኮችን የምትመርጥበት ሐዋርያዊ ትዉፊት ወሳኙ ነው፡፡ ሦስተኛው ቤተ ክርስቲያንን ሐዋርያዊ የሚያሰኛት ደግሞ ሐዋርያዊ ክትትሉን የጠበቀ የቅዱሳት መጻሕፍት ትርጓሜ ነው፡፡ ዶግማ የሚባለውም የዚህ ትርጓሜ ውጤት ነው፡፡

 

ከእነዚህ ነጥቦች ተነሥተን የእኛን ቤተ ክርስቲያን ሂደት (Experiance) መዳሰስ ቅድሚያ የሚሰጠው ሆኖ ይገኛል፡፡ ምክንያቱም አንደኛ በታሪካችን ውስጥ ከነበሩት ጠንካራ ጎኖች ብቻ ሳይሆን ከድከመቶቹም የምንወስዳቸውን ጥቅሞች በቅርበት ለመመርመር፤ ሁለተኛም ከዚያ ተነሥተን ወደፊት የምንሔድበትን ለማየት ስለሚጠቅም ነው፡፡

 

ቀደም ብለን እንደገለጽነው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ሐዋርያዊት የምትባለው ቅዱስ ማርቆስ ወንጌላዊ ሲመተ እድ ባለተቋረጠና ክትትል ባለው ሐዋርያዊ ክህነት (Apostolic succession)እስካሁን በመኖሯና ሐዋርያዊ ትውፊትንም ከዚያው ሳትወጣ የምትፈጽም በመሆኗ ነው፡፡ ሆኖም በታሪካችን ሐዋርያዊ ትውፊትና ቀኖና የተፈተኑበት ጊዜ አልነበረም ማለት አይደለም፡፡ ከሁለት ሺሕ ዓመት አገልግሎት አንጻር ሲታይ አጋጣሚዎች ጥቂትና ጊዜዎቹም አጫጭር ቢሆኑም ከትፊዉቱ የመውጣትና የውጤቱንም መከራና ፈተና ማጨድ እንደነበረ ግን ታሪካችን ያስረዳል፡፡ ምንም እንኳ ዘመኑ ትንሽ ዕድሎቹም ጥቂት የነበሩ ቢሆኑም ያስከተሉት ጥፋትና ጉድለት ግን ትንሽ አልነበረም፡፡ሆኖም በየዘመኑ የነበሩ አባቶች ከችግሮቹ እየተማሩ ትውፊታቸውን አጥብቆ ወደመጠበቅ በመመለስ ከችግራቸው ወጥተዋል፡፡ ለመሆኑ ቀኖናውና ትውፊቱ ምንድን ነው?

 

ትውፊቱ

የቤተ ክርስቲያንን የጵጵስናና የፕትርክና ሹመት ታሪክ ጸሐፊዎች መነሻ የሚያደርጉት ጌታችን ሐዋርያትን የመረጠበትን ሁኔታና በሐዋርያት ሥራ ላይ የተገለጸውን የማትያስን ምርጫ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያንን ‹‹ ሐዋርያዊት›› በሚያሰኟት በእነዚህ ሁለት የምርጫ ክስተት ውስጥ ሦስት መሠረታዊ መስፈርቶችን እንደ ምሳሌ ይወስዳሉ፡፡ እነዚህም

 

1ኛ) የሐዋርያት ከተርታው ሰው ውስጥ መመረጣቸው

ታሪክ ጸሐፊዎቹ እንደሚሉት ሁሉን ማድረግ የሚቻለው ጌታ ከምሁራነ ኦሪት ቅኖቹን መምረጥና ማብቃት መለወጥ እየተቻለው እነርሱን ትቶ ከተርታ ሰዎች ምንም ካልተማሩትና ምንም ልምድም ሆነ ዕውቀት የሌላቸውን መርጦና አምጥቶ አስተምሮ ቅዱሳን ሐዋርያትን የሾመው ወደ ፊት ፓትርያርኮች ከአነሥተኛው መዓርግ እየተመረጡ እንዲሾሙ ሲያሰተምረን ነው ይላሉ፡፡ እንዲያውም እንደ ቅዱስ ጳውሎስና እንደ አጵሎስ ያሉትን ምሁራነ አሪት እንደሚመልሳቸው እያወቀና ክብራቸውንም በተለይ ቅዱስ ጳውሎስ ቁጥሩም መዓርጉም ከሐዋርያት ሆኖ ሳለ መጀመሪያ ያልተመረጠው ምርጫው መንፈሳዊነትን እንጂ ዕውቀትን መሠረት ያደረገ እንዳይሆን ሥርዓት ሲሠራልን ነው በማለት ያስረግጣሉ፡፡ ጌታ ሐዋርያትን ከመረጠ በኋላ ግን አስተምሯቸዋል፤ በዚህም መሠረት የቤተ ክርስቲያንን ትምህርት በተገቢው መንገድ ለአገልግሎትና ለምሥጢራት በሚያስችል ሁኔታ ከተማረና በርግጥ መንፈሳዊ ሆኖ ቀኖና ቤተ ክርስቲያን ጠብቆ ከተመረጠ ሌላውን ዕውቀት ከራሱ ከጌታ ሊያገኘው ይችላል ባዮች ናቸው፡፡

2ኛ)የሰዎች ድርሻ

በቅዱስ ማትያስ ምርጫ ሒደት ውስጥ ከተገኙት ሁለት መሠራታዊ ትውፊቶች አንዱ ደግሞ ሐዋርያት መጀመሪያ ሁለት ሰዎችን መርጠው ድርሻቸውን መወጣታቸው ነው፡፡ ስለዚህ አባቶችን በመምረጥ ሒደት ሓላፊነት ያለባቸው አካላት አሉ፡፡ እነዚህ አካላት ግን ልክ እንደ ሐዋርያት ሊሾም ከታሰበው በላይ ቁጥር ያላቸውን መርጠው ማቅረብ አለባቸው፡፡ ሐዋርያት አንድ ሰው በይሁዳ ለመተካት ሲፈልጉ ሁለት እንዳቀረቡት ሁሉ ለመጨረሻው አባትነት ለፓትርያርክም አባቶች መምረጥ ያለባቸው ከአንድ በላይ መሆን አለበት፡፡

3ኛ) የእግዚአብሔር ምርጫ

ቅዱሳን ሐዋርያት ማትያስንና በርናባስን (ዮሴፍን) ከመረጡ በኋላ ከሁለቱ አንዱን የመምረጡ ድርሻ ግን የእግዚአብሔር ነበረ፡፡ ስለዚህ ማንኛችንም ቢሆን ከሐዋርያት ልንበቃ አንችልምና በወደደው መንገድ የእግዚአብሔርን የመምረጥ ዕድል የሰጠ መሆን አለበት፡፡የጥንታዊቷ ኦርቶዶክሳዊት ቤተ ክርስቲያን ትውፊትም በእነዚህ መሠረቶች ላይ የተገነባ የሰውንና የእግዚአብሔርን ድርሻ በግልጽ የሚያስቀምጥ ነበር ይላሉ፡፡

ቀኖናውስ?

‹‹የእግዚአብሔርን መንጋ በእውቀት ለመጠበቅ ፍጹም የሆነ የሰው እጥረት አለ፡፡… ትክክለኛ የቀኖና እውቀትም የለም፡፡ ኃጢአትን ለመሥራት ሙሉ ነጻነት አለ፡፡ ሰዎች በአማላጅ ክህነትና እልቅና በተሾሙ ጊዜ ውልታቸውን ለመመለስ ሲሉ ቀኖናዊ ጥፋቶችን ቸለል ይላሉ፡፡›› ባስልዮስ ዘቂሳርያ /Basil of Caesaria, To the Italians and Gauls, letter 92/

“አንድ ጳጳስ በድርቅና በረሃብ፣ በተሾመባት ከተማ ትንሽ መሆን፣ በሕዝቡ ማነስ፣ በቂ ገቢ በሀገረስብከቱ ባለመኖሩና በመሳሰሉት ምክንያት ከተሾመባት ከተማ ወይም መንደር ተነሥቶ ወደ ሌላ አይሂድ፤ ከዚህ የተሻለ ይሰጠኝ ብሎም አይጠይቅ፤ እያንዳንዱ ከእግዚአብሔር የሚከፈለው ዋጋ አለውና” ይላል፡፡ በዚህ መሠረት

1ኛ) አንድ (ሊቀ) ጳጳስ ወደ ፕትርክና ቢመጣ እንደሚስት የምትቆጠርለትን ሀገረ ስብከቱን በማቅለሉና ሌላ የተሻለች መንበር (ሚስት) በመፈለጉ ምክንያት ብቻ የተነቀፈ ነው፡፡

2ኛ) ለፕትርክና ሲሾምም ጳጳሳቱ እጃቸውን የሚጭኑበት ‹‹ በ…ሀገር እና…ከተማ›› ብለው ስለሆነ ሁለተኛ እንደ ማግባት ተቆጥሮ እንደ ዝሙት ያስቀጣዋል ወይንም ክህነቱን ያሳጣዋል ይላሉ፡፡

3ኛ) ጌታ እንዳደረገው ወደ ላይኛው ሥልጣን የሚመጡት ከታችኛው ከአበ ምኔትነትና በታች ካለው እንደሆነ ትውፊቱ ያስገድዳልና፡፡

ይህንን ሀሳብ በትክክል ለመረዳት ግን የፓትርያርክን መሠረተ ሀሳብ በደንብ መፈተሽና በትክክለኛው ሁኔታ መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ምክንያቱም በሐዋርያት ትውፊት መሠረት ፓትርያርክ ወይንም ፖፕ የሚለው ቃል ራሱ ለመጀመሪያ ጊዜ ጥቅም ላይ የዋለው ከ232-247 ዓ.ም. ድረስ በእስክንድርያ መንበር በተሾመው በአባ ሔራክልዮስ ዘመን ነው፡፡ ይህም ማለት ፓትርያርክነት በክህነት መዓርግ ብልጫ የለውም ማለት ነው፡፡ ልክ በዲያቆንና በሊቀ ዲያቆን ወይም በጳጳስና በሊቀ ጳጳስ ወይም ደግሞ በቄስና በቆሞስ መካከል የሥልጣነ ክህነት ልዩነት እንደሌለው ሁሉ በጳጳስና በፓትርያርክም መካከል የሥልጣነ ክህነት መበላለጥ የለም፡፡ ይህም ማለት ዲያቆንን ሊቀ ዲያቆን በማድረግ ሒደት ድጋሚ የዲቁና ሥልጣን እንደማይሰጠው ሁሉ ወይም ድጋሚ ክህነት ቢሰጠው ውግዘት ያለበት እንደሆነው ሁሉ በፕትርክና ጊዜም የሚሰጠው ክህነት የጵጵስና ከሆነ ድጋሜ ክህነት ተሰጠው ስለሚያሰኝና በሁለተኛ ሀገረ ስብከትም ተሾመ የሚለውን ትርጉም የሚያመጣው ምሥጢር ይህ ስለሆነ ነው ጳጳስ ሀገረ ስብከቱን ትቶ ፓትርያርክ እንዳይሆን ቀኖናው የሚከለክለው፡፡ ይህ ከሆነ ፓትርያርክ ማለት የትክክል የበላይ ( Father among equals) ነው እንጂ የጳጳሳት ሁሉ ፍጹም የበላይ( father above equals) አይደለም፡፡ እንግዲህ ግብጾች እየጠበቁት ነው የሚባለው ይህ ነው፡፡

ሙሉውን እዚህ በመጫን ያንብቡ

 

abuneteklhymanote

ሐዲስ ሐዋርያ ተክለ ሃይማኖት

ነሐሴ 23 ቀን 2004 ዓ.ም.


abuneteklhymanoteጻድቃንን ማሰብ ሥራቸውን መዘከር ክርስቲያናዊ ሕይወታችንን ያጐለምሳል፡፡ የበረከታቸው ተሳታፊ በማድረግ በነፍስ በሥጋ የሚታደገንን የሚረባን፤ የሚጠቅመን ይሆናል፡፡ ስለጻድቁ አባታችን ስለ ቅዱስ ተክለ ሃይማኖትም የምናስበው ከዚህ የተለየ አይደለም፡፡ በመንፈሳዊ አርአያነታቸው፣ በጸሎታቸውና በትምህርታቸው ከከበቡን የነፍስ ጠላቶች፤ ከርኲሳን መናፍስትና ከጨለማው ልጆች፣ ከክፉ ሰዎች ሽንገላና ተንኰል ለመሰወርና ለመጠበቅ ከእግዚአብሔር የተቀበሉት ሥልጣን ምን ጊዜም ይሠራል፡፡ በጻድቃን መኖር ሀገር ከጥፋት ትድናለች፡፡ የጻድቃንን ስም ጠርቶ እግዚአብሔርን በመለመን በረከትና ረድኤት ይገኛል፡፡ ስለጻድቃን ብሎ እግዚአብሔርም ምሕረቱን ያድላል፡፡ ስለዚህ ነው ቤተ ክርስቲያናችን ጻድቃንን እንድናስባቸው፣ በስማቸውም ለድሆችና ለጦም አዳሮች እንድንመጸውት መታሰቢያቸውን እንድናደርግ የምትመክረን፤ የምታስተምረን፡ ጻድቁ ተክለ ሃይማኖትንም የምናስባቸው ከዚሁ የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ በመነሣት ነው፡፡ ማቴ.10፥41-42 ጻድቃንን በሕይወተ ሥጋ ሳሉም ቢሆን፤ ከሞቱም በኋላ በአጸደ ነፍስ በጸሎታቸው ለሚታመኑ፣ በቃል ኪዳናቸው ለሚማጸኑ፣ የድኅነተ ሥጋ፣ የድኅነት ነፍስ ምክንያት ናቸው፡፡

በዚህ መሠረት ከቅዱሳን አባቶች መካከል ለኢትዮጵያ ሐዲስ ሐዋርያ ሆነው የተመረጡና ከጻድቃን መካከል የሆኑትን የቅዱስ ተክለሃይማኖት በዓለ ዕረፍትን መታሰቢያ ምክንያት በማድረግ ዜና ሕይወታቸውን ከዚህ እንደሚከተለው በአጭሩ እናቀርባለን፡፡

 

ጻድቁ አባታችን ተክለ ሃይማኖት በአምላክ ፈቃድ፣ በሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ብሥራት፤ ከአባታቸው ከካህኑ ጸጋ ዘአብና ከእናታቸው ከቅድስት እግዚእ ኀረያ ታኅሣም 24 ቀን 1212 ዓ.ም.  ተወለዱ፡፡ ወላጆቻቸው ስማቸውን ፍሥሐ ጽዮን በማለት አወጡላቸው፡፡ በተወለዱ በሦስተኛውም ቀን እሑድ ከጠዋቱ ሦስት ሰዓት ከእናታቸው ዕቅፍ ወርደው “አሐዱ አብ ቅዱስ፤ አሐዱ ወልድ ቅዱስ፤ አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ፡- አንዱ አብ ቅዱስ ነው፤ አንዱ ወልድ ቅዱስ ነው፤ አንዱ መንፈስ ቅዱስ ቅዱስ ነው፡፡” በማለት የሥላሴን ስም ጠርተው አመስግነዋል፡፡ በተወለዱ በ15 ዓመት ዕድሜያቸው ዲቊናን፣ በ22 ዓመታቸው ቅስናን ከግብፃዊው ጳጳስ ከአባ ጌርሎስ /ቄርሎስ/ ተቀብለዋል፡፡

 

ከዕለታት በአንዱ ቀን አባታችን ወደ ጫካ ለአደን ሄደው ሳለ፤ ሊቀ መላእክት ቅዱስ ሚካኤል ግሩም ድንቅ የሆነ ልብስ ለብሶ ታያቸው፡፡ አባታችንም እንደዚህ ባለ ገናንነት የማይህ ጌታዬ ማነህ?” አሉት፡፡ ቅዱስ ሚካኤልም “ዘወትር የምጠብቅህ ካንተ የማልለይ እናትህንና አባትህንም ስላንተ ከውኃ ስጥመትና ከምርኮ ያዳንኳቸው እኔ ሚካኤል ነኝ፡፡ እንግዲህ አውሬ አዳኝ አትሁን፤ ሰውን ወደ እግዚአብሔር ለመመለስ ሰውን በትምህርት የምታድን ሁን እንጂ፡፡ እነሆ እግዚአብሔር ጽኑዕ ሥልጣን ሰጥቶሀልና፤ ሙት ታስነሣለህ፤ ድውያንን ትፈውሳለህ፤ አጋንንትም አንተን በመፍራት ይሸሻሉ፡፡ ስምህ ፍሥሐ ጽዮን አይሁን፤ ተክለ ሃይማኖት ይሁን እንጂ፡፡ ትርጓሜውም ተክለ አብ፥ ተክለ ወልድ፥ ተክለ መንፈስ ቅዱስ ማለት ነው፡፡” አላቸው፡፡ ቅዱስ ሚካኤል ይህን ሲያነጋግራቸው ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በሥጋ ከደቀ መዛሙርቱ ጋር እንደነበር ሆኖ መልከ መልካም ጎልማሳ መስሎ ታያቸው፡፡ ጌታችንም “ወዳጄ እንዴት ሰነበትክ! ቸር አለህን፤” አላቸው፡፡ ብፁዕ ተክለ ሃይማኖትም “ጌታዬ ሆይ አንተ ማነህ? ብለው ጠየቁ፡፡ ጌታም “እኔ የዓለም መድኀኒት ኢየሱስ ነኝ፤ በናትህ ማኅፀን ፈጥሬህ ያከበርኩህ እኔ ነኝ፡፡ በተወለድክ በሦስተኛው ቀን አሐዱ አብ ቅዱስ፥ አሐዱ ወልድ ቅዱስ፥አሐዱ ውእቱ መንፈስ ቅዱስ፥ብለህ ታመሰግነኝ ዘንድ የምስጋና ሀብት ያሳደርኩብህ እኔ ነኝ፡፡ በረሃብ ዘመን በቤት የሚያሻው ምግብ ሁሉ ቅቤው፣ የስንዴው ዶቄት በእናት በአባትህ ቤት ይመላ ዘንድ በእጅህ ሀብተ በረከት ያሳደርኩብህ እኔ ነኝ፡፡ ያንን ሰው አንተን በተጣላ ጊዜ በነፋስ አውታር የሰቀለኩት በመዓት ጨንገር የገረፍኩት እኔ ነኝ፡፡ ውኃ ጠምቶህ በለመንከኝ ጊዜ ከደረቅ መሬት የጣፈጠ ውኃ ያመነጨሁልህ አኔ ነኝ፡፡ ከልጅነትህ ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ ብዙ ተአምራት እያደረግሁ በአንተ እጅ የታመሙትን ያዳንኳቸው እኔ ነኝ፡፡ ወደ ፊትም አደርግልሃለሁ፡፡ ይህንን ብሎ ንጹሓት ክቡራት በሆኑ እጆቹ ባረካቸው “ንሣእ መንፈስ ቅዱስ” ብሎ የሹመትን ሀብት አሳደረባቸው፡፡ በምድር ያሰርከው በሰማይ የታሰረ ይሁን፡፡ በምድርም የፈታኸው በሰማይ የተፈታ ይሁን፤ አንተን የሰማ እኔን መስማቱ ነው፤ የላከኝ አባቴንም መስማቱ ነው፡፡ አንተን እንቢ ያለ እኔን እንቢ ማለቱ ነው፡፡ የላከኝ አባቴንም እንቢ ማለቱ ነው፡፡ ይህን ሥልጣን ቀድሞ ለሐዋርያት ሰጥቻቸው ነበር፡፡ ከሐዋርያትም ሹመትን የተቀበለ ጳጳሱ ትሾምና ትሽር ትተክልና ትነቅል ዘንድ ሥልጣንን ሰጠህ፡፡ ይህንንም ያደረኩልህ የጳጳሱን ቃል በመናቅ አይደለም፡፡ የፍቅሬን ጽናት ባንተ እገልጽ ዘንድ ነው እንጂ፡፡ ሐዋርያት ወደአልደረሱበት ሕዝብ በመምህርነት እልክህ ዘንድ በሚካኤል ቃል አዲስ ስም አወጣሁልህ፡፡ አንተም በማናቸውም ሥራ ከነሱ አታንስም፡፡ ሐዲስ ሐዋርያ አድርጌሃለሁና፡፡ ሰውን ሁሉ በእኔ ስም እያስተማርክ ታሳምን ዘንድ፤ ሚካኤልም ባሰብከው ሥራ ሁሉ ረዳት ይሁንልህ፡፡ ሁል ጊዜ ካንተ አይለይም፡፡ በምትሄድበትም ጎዳና ሁሉ እርሱ መሪ ይሁንህ፡፡ እኔም ባለ ዘመንህ ሁሉ አልለይህም” ብሎ ሰላምታ ሰጥቷቸው ዐረገ፡፡ ብፁዕ አባታችንም እጅ ነስተው “ለእኔ ለኀጥኡ የማይገባኝ ሲሆን ይህን ሁሉ ጸጋ የጠኸኝ ስምህ በሰማይ በምድር የተመሰገነ ይሁን” አሉ፡፡ ከዚያች ቀን ጀምሮ ሀብተ ኀይልን የተመሉ ሆኑ፡፡ ከዚያም ወደቤታቸው ተመልሰው ያላቸውን ንብረት ሁሉ ለቤተ ክርስቲያንና ለነዳያን ሰጥተው ጨረሱ፡፡ ከዚያም “አቤቱ ጌታዬ ኢየሱስ ክርስቶስ ሆይ! የመንግሥተ ሰማያትን በር ትከፍትልኝ ዘንድ እነሆ ቤቴን እንደተከፈተ ተውኩልህ” ብለው ቤታቸውን እንደተከፈተ ትተው ወንጌልን ለማስተማር ፈጥነው ወጡ፡፡ /ገድለ ተክለሃይማኖት ዘሠሉስ ምዕ.28 ገጽ 116/

 

ከ1219-1222 ዓ.ም. በከተታ ሦስት ዓመት፣ ወንጌልን አስተማሩ፡፡ ቀጥለውም ዘጠኝ ወር በዊፋት አገልግሎታቸውን ፈጽመዋል፡፡ ከ1223-1234 ዓ.ም. ዳሞት በተባለው ስፍራ ወይም በወላይታ ሀገር ለ12 ዓመታት ከአምልኮተ ጣዖት ወደ አምልኮተ እግዚአብሔር፤ ከገቢረ ኀጢአት ወደ ገቢረ ጽድቅ ትምህርት በመስጠት ተአምራት አድርገው፤ መልሰዋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንንም አንፀዋል፡፡ በዚህ ሀገር ዲያብሎስ በዛፍ ላይ አድሮ አምላክ ነኝ እያለ ለረጅም ዘመናት ሕዝቡን በማሳት የሚጠቀምበትን ዛፍ በተአምራት ከሦሩ ነቅለው አፍልሰዋል፡፡

 

በዚህ ተግባራቸው ጌታችን በቅዱስ ወንጌል “የሰናፍጭ ቅንጣት የሚያህል እምነት ቢኖራችሁ፤ ይሄንን ሾላ ተነቅለህ ወደ ባሕር ተተከል ብትሉት ይታዘዝላችኋል፡፡” ሉቃ.17፥6 ያለውን አምላካዊ ቃል በተግባር አስመስክረዋል፡፡ ከዚህም በኋላ በእግዚአብሔር ፈቃድና ትእዛዝ ወደ አማራ ሳይንት ወሎ በመሄድ ሥርዓተ ምንኲስናን ከአባ በጸሎተ ሚካኤል ገዳም ገብተው ከ1234-1244 ዓ.ም. ለዓሥር ዓመታት የእርድና ሥራ በመሥራትና ገቢረ ታምራትን በማሳየት ጌታ በቅዱስ ወንጌል “ማንም ከእናንተ ታላቅ ሊሆን የሚወድ ለእናንተ አገልጋይ ይሁን፤ ከእናንተ ማንም ፊተኛ ሊሆን የሚወድ የእናንተ ባሪያ ይሁን፡፡ እንዲሁም የሰው ልጅ /ወልደ እጓለ እመሕያው ክርስቶስ/ ሊያገለግል ነፍሱንም ለብዙዎች ቤዛ ሊሰጥ እንጂ እንዲያገለግሉት አልመጣም፡፡ ማቴ.20፥26-28 ያለውን መለኮታዊ ትእዛዝ በተግባር አሳይቷል፡፡ ከ1244-1254 ዓ.ም. አባ ኢየሱስ ሞዓ ወደሚገኙበት ገዳም ሐይቅ እስጢፋኖስ በቅዱስ ሚካኤል መሪነት ሐይቁን በእግራቸው እንደ ደረቅ መሬት በመርገጥ ወደ ደሴቲቱ በመግባት የምንኲስናን ተግባራቸውን በመቀጠል በግብረ ሐዋርያትና በወንጌል የተነገረውን የእርድናን ተግባር ፤የአገልግሎትና ትሩፋት/ሥራ ከፍጻሜ አድርሰዋል፡፡ በአባ ኢየሱስ ሞዓ እጅም የንጽሕና ምልክት የሆነውን የምንኲስናን ቀሚስ ተቀብለዋል፡፡

 

ከ1254-1266 ዓ.ም. ለዐሥራ ሁለት ዓመታት አቡነ አረጋዊ ወዳቀኑት ገዳም በትግራይ ሀገረ ስብከት ወደሚገኘው ደብረ ዳሞ ገዳም በመግባትDebre libanos Monastary. በጊዜው ከነበሩት አበምኔት ከአባ ዮሐኒ ቆብና አስኬማ ተቀብለው በገድል በትሩፋት መንፈሳዊ ተጋድሎአቸውን ቀጠሉ፡፡ ከደብረ ዳሞ ገዳም ወደሌላ ለመሄድ ሲነሡ፤ ክቡር አባታችን ተክለሃይማኖት አበምኔቱና መነኰሳቱ ሲሸኟቸው ሳለ፤ አርባ ክንድ ርዝመት ባለው ገመድ ገደሉን ለመውረድ እንደጀመሩ፤ ገመዱ ከካስማው ሥራ በመቆረጡ እንዳይወድቁ በተሰጣቸው ስድስት የብርሃን ክንፎች እየበረሩ፤ ክንፎቻቸውን እያማቱ ሦስት ምዕራፍ ሄደው ዐርፈዋል፡፡ ከዚያም ወደ ገዳመ ዋሊ ገብተዋል፡፡ በዚህም ጊዜ ነቢዩ ኢሳይያስ የተናገረው ትንቢት “ለደካማ ኀይልን ይሰጣል፤ ጉልበት ለሌለው ብርታትን ይጨምራል፡፡ ብላቴኖች ይደክማሉ፤ ይታክቱማል፡፡ ጐበዛዝትም ፈጽመው ይወድቃሉ፡፡ እግዚአብሔርን በመተማመን የሚጠብቁ ግን ኀይላቸውን ያድሳሉ፤ እንደ ንስርም በክንፍ ይወጣሉ፤ ይሮጣሉ፤ አይታክቱም፡፡ “ኢሳይያስ 40፥29-31 ያለው ቃል በጻድቁ በቅዱስ ተክለ ሃይማኖት ሕይወት ሊተረጐም ችሏል፡፡ ከ1266-1267 ዓ.ም. አንድ ዓመት ሙሉ ገዳማተ ትግራይን በመጐብኘት ኢየሩሳሌምንና ግብፅ ያሉ ቅዱሳት መካናትን ሲጎበኙ ቆይተዋል፡፡ ከዚህ በኋላ አንድ ወር ሙሉ “ዳዳ” በተባለ ስፍራ ይመለክ የነበረውን 75 ክንድ ዘንዶ በጸሎት ኀይል በተአምራት ገድለውታል፡፡ አርባዓቱ እንስሳ /በኪሩቤልና በሱራፌል/ ስም ቤተ ክርስቲያን አንፀው፤ ታቦተ ሕግ /ጽላተ ሕግ/ አስገብተዋል፡፡ ከሴቶችና ከልጆች ሌላ፤ ሦስት ሺህ በጣዖት የሚያመልኩ ወንዶችን መልሰው፤ አጥምቀው አቊርበዋል፡፡ በዚህም ተግባራቸው መድኀኒታችን “እነሆ እባቡንና ጊንጡን ትረግጡ ዘንድ በጠላትም ኀይል ሁሉ ላይ ሥልጣን ሰጥቻችኋለሁ፥ የሚጎዳችሁም ምንም የለም” ሉቃስ 10፥19 ያለው ቃል ተፈጽሞላቸዋል፡፡ ክቡር ዳዊት በመዝሙር 90፥13-14 “በተኲላና በእባብ ላይ ትጫማለህ፤ አንበሳውና ዘንዶውን ትረግጣለህ፡፡ በእኔ ተማምኗልና አስጥለዋለሁ፤ ስሜንም ዐውቋልና እጋርደዋለሁ፡፡” የተባለው ትንቢት ተፈጽሞላቸዋል፡፡ ከ1267-1289 ዓ.ም. በደብረ ሊባኖስ ካለችው ገዳመ አስቦ ዋሻ በመግባት፤ ስምንት ጦሮችን /ሁለቱን በፊት፣ ሁለቱን በኋላ ሁለቱን በቀኝ፣ ሁለቱን በግራ አስተክለው  እጆቻቸውን በትእምርተ መስቀል በመዘርጋት የክርስቶስን ሕማምና ሞት፣ ነገረ መስቀልን በማሰብ በተመስጦ ሌትና ቀን ያለማቋረጥ በጾምና በጸሎት በአርምሞ ተወስነው ሲጋደሉ፤ ከቊመት ብዛት የተነሣ ጥር 4 ቀን 1289 ዓ.ም. አንዲቱ የእግራቸው አገዳ ተሰብራለች፡፡ ደቀ መዛሙርቱም የመንፈሳዊ አባታቸውን ስባረ ዐፅም አክብረው በሥርዓት አኑረውታል፡፡ እግራቸው እስኪሰበር የቆዩባቸው ዓመታት በቊጥር ሃያ ሁለት ናቸው፡፡ በመዓልትና በሌሊት በትጋትና በቊመት በተጋድሎ ብዛት፤ አንዲት የአገዳ እግራቸው ስትሰበር፤ ዕድሜያቸው 92 ዓመት ሆኗቸው ነበር፡፡

 

ከ1289-1296 ዓ.ም. ለሰባት ዓመታት በአንድ እግራቸው በመቆም ያለምግብና ያለውኃ በትኅርምት ሌትና ቀን እንቅልፍ በዓይናቸው ሳይዞር እንደ ምሰሶ ጸንተው፤ በተመስጦ በትጋት ለሰው ዘር ሁሉ ድኅነትን ሲለምኑ ኖረዋል፡፡ ከሰባቱ ዓመታት ውስጥ ጥቂት ውኃ የቀመሱት በአራተኛው ዓመት ብቻ ነበር፡፡ ማቴ.4፥4 የሐ.14፥22፣ 2ቆሮ.11፥26፤ በዚህ ጊዜ ውስጥ ጌታችን ተገልጾ፤ “በሰው እጅ የማይለካውን ይህንን የመንግሥት አዳራሽ ውሰድ” በማለት የመለኮትን ነገር የሚናገር የእሳት አንደበት ያላቸው የመንግሥት ልብስ አልብሷቸዋል፡፡ በመስቀል ምልክት የተጌጡት ሰባት የሕይወት አክሊላት “ስለ ቀናች ሃይማኖትህ፤ ሃይማኖትን ለማስተማር መላዋን ኢትዮጵያን ስለመዞርህ፤ ከአረማውያን ሕዝብ ጋር በሃይማኖት ስትታገል ደምህን ስለማፍሰስህ፤ ወደ ኢየሩሳሌም ወርደህ ልዩ ልዩ የቅዱሳን ቦታዎች ስለመሳለምህ፤ በሰባት ዓመታት ቊመት የአንዱ አገዳ እግርህ ስለመሰበሩ፤ ስለብዙ ጾም ጸሎትህ ስግደትህ፤ ስለልብህ ንጽሕናና ቅድስና” ብሎ አቀዳጅቷቸዋል፡፡ ዝክራቸውን በማዘከር መታሰቢያቸውን የሚያደርጉ ሁሉ በዚህ ዓለምም ሆነ በወዲያኛው ፍጹም ዋጋና ፍጹም ክብር እንደሚሰጣቸው ጌታ ቃል ኪዳን ገብቶላቸዋል፡፡ ያዕ.1፥12፣ ራእ.14፥1213፣ 2ጢሞ.4፥6-8 በመጨረሻም ለዐሥር ቀናት በሕመም ቆይተው፤ ፈጣሪያቸው የገባላቸውን ቃል ኪዳን ለመነኰሳት መንፈሳውያን ልጆቻቸውና ለደቀ መዛሙርቶቻቸው ከነገሩ በኋላ ነሐሴ 24 ቀን በክብር ዐርፈዋል፡፡ በከበረች ዕረፍታቸው ከዚህ የሚከተለውን የሃይማኖት ኑዛዜ አውርሰውናል፡፡

 

“ልጆቼ! አታልቅሱ፤ ነገር ግን የሽማግሌውን የአባታችሁን ቃል ስሙ፡፡ መጀመሪያ እምነታችሁ በእግዚአብሔር ላይ ይሁን፡፡ በዚህ ዓለም እንደተያዙ እንደ ዓለም ሰዎች ስለ ልብስና ስለምግብ አሳብ አታብዙ፡፡ በየጊዜው ሁሉ መጸለይን አታቋርጡ ለቤተ ክርስቲያንም ሌትና ቀን አገልግሉ፡፡ እግዚአብሔር በሚወደው ገንዘብ ንጽሐ ሥጋንና ጾምን ውደዱ፡፡ ውዳሴ ከንቱም የሚቀረውንም የዚህን ዓለም ክብር አትውደዱት፤ እናንተስ የቀደሙትን አባቶች በመከራና በድካም ብዛት ከዓለም የወጡትን በመጋደላቸውም ክፉውን ዐሳብ ድል የነሡትን ምሰሏቸው፡፡

 

ፍለጋቸውንም ካልተከተላችሁ፤ ልጆቻቸው አትባሉምና፤ በመከራቸው ካልመሰላችኋቸው በደስታቸው አትመስሏቸውም፤ በድካማቸውም ካልተባበራችሁ ወደ ቤታቸው አትገቡም.. እነሱን መስላችሁ ኀጢአተኛ አባታችሁን እኔን ደግሞ ምሰሉ፤ ስለትኅርምቱም በመብል በመጠጥ ልባችሁ እንዳይከብድ፣ ሥጋ ከመብላትና ጠጅ ከመጠጣት ተጠበቁ፡፡ ለመመካትም በዓለማዊ ልብስ አታጊጡ፡፡ የመላእክት አስኬማ ከዓለማዊ ሥራ ጋር አይስማማምና፤ ዓለምንም በዓለም ላይ ያለውን ሁሉ አትውደዱ፡፡ ዓለሙም ፈቃዱም ሓላፊ ነውና፡፡ የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚያደርግ ግን ለዘለዓለም ይኖራል፡፡

 

ልጆቼ ሆይ! ትሩፋትን ሁሉ በችኮላ ሠርታችሁ በጎይቱን ሃይማኖታችሁን አስከትሏት፡፡ ለነፍሳችሁ እንጂ ለሆዳችሁ አትገዙ፡፡ ሁላችሁ ወንድማማች ሁኑ፡፡ እርስ በርሳችሁም ተፋቀሩ፤ ከመንፈስ ቅዱስ የሚገኝ ፍቅር ኀጢአትን ያጠፋልና፤ የነፍስና የሥጋን ርኲሰት ያነጻልና፡፡ ይህንንም ብትጠብቁ በእውነት ልጆቼ ናችሁ፡፡ የሕይወትንም ፍሬ የምታፈሩ ትሆናላችሁ፡፡ ወደ እግዚአብሔር ፊት በክብር ትደርሳላችሁ፤…

 

ልጆቼ ሆይ! ሰላም ለእናንተ ይሁን፡፡ እንግዲህ ወዲህ ተሰናበትኳችሁ የእግዚአብሔር ፍቅሩ የክብሩም ባለሟልነት፣ የረዳትነቱም ሀብት ዘወትር ከእኔና ከሁላችሁ ጋር ይኑር ለዘላለም በእውነት ይኑር፡፡” /ገድለ ተክለ ሃይማኖት ዘቀዳሚት ምዕ.54/

 

ጌታችን ለደቀ መዛሙርቱ እናንተን የሚቀበል እኔን ይቀበላል፥ እኔንም የሚቀበል የላከኝን ይቀበላል፡፡ ነቢይን በነቢይ ስም የሚቀበል የነቢይን ዋጋ ይወስዳል፥ ጻድቅንም በጻድቅ ስም የሚቀበል የጻድቁን ዋጋ ይወስዳል፡፡ ማንም ከእነዚህ ከተናናሾቹ ለአንዱ ቀዝቃዛ ጽዋ ብቻ በደቀ መዝሙር ስም የሚያጠጣ፥ እውነት እላችኋለሁ፥ ዋጋው አይጠፋበትም፡፡” /ማቴ.10፥40-42/ ብሎ የተናገረውን መለኮታዊ ቃል ኪዳን ኦርቶዶክሳዊ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ተቀብላ፤ መጋቢት 24 ፅንሰታቸውን፣ ታኅሣስ 24 ቀን ልደታቸውን፣ ጥር 24ን ሰባረ ዐፅማቸውን /የዕረፍታቸውን ቀን ይዞ በዚሁ ወር 24 ይከበራል ሰባረ ዐፅማቸው ከላይ እንደተገለጸው በጥር 4 ነው፡፡/ በግንቦት 12 ቀን ፍልሰተ ዐፅማቸውን ነሐሴ 24 ቀን ዕረፍታቸውን በትላቅ ደስታ ታከብራለች፡፡ ጸሎታቸውና በረከታቸው ረድኤታቸውና ምልጃቸው በመላው ሕዝበ ክርስቲያንና በቅድስት ኦርቶዶክሳዊት ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አገልጋዮች ሁሉ አድሮ ይኑር ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

 

አርኬ፡-

ሰላም እብል እንበለ አርምሞ በጽዋዔ፡፡ ኪያከ አበ ወኪያከ ረዳኤ፡፡ ተክለ ሃይማኖት መዋዒ እንዘ ትጸንሕ ተስፋ ትንሣኤ፡፡ አጽናዕከ ለቀዊም አእጋረ ክልኤ፡፡ ወእምስቴ ማይ አሕረምከ ጒርዔ፡፡


አሸናፊ የሆንህ ተክለ ሃይማኖት! አባት አንተን ረዳት፥ አንተን ያለዝምታ በጥሪ ሰላም እላለሁ፡፡ የትንሣኤ ተስፋን ስትጠብቅ፤ ሁለት እግሮችን ለቊመት አጸናህ፤ ጒሮሮህንም ውኃ ከመጠጣት አረምኽ፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ምንጭ፡- መለከት መጽሔት 18ኛ ዓመት ቁጥር 9

“ኅርየተ ፓትርያርክ በቤተ ክርስቲያን ዘግብጽ ኦርቶዶክሳዊት፤ የፓትርያርክ ምርጫ ታሪክና አፈጻጸም በኮፕት ቤተ ክርስቲያን”

ነሐሴ 23 ቀን 2004 ዓ.ም.

ወልደ ማርያም

የዚህ አጭር ጽሑፍ ዋና ዓላማ በትምህርተ ሃይማኖትና ከሞላ ጎደል በሥርዓተ እምነት ከሚመስሉን አኀት አብያተ ክርስቲያናት መካከል አንዷ የሆነችው የኮፕት ቤተ ክርስቲያን በ2000 ዘመን ታሪኳ የሚመሯትን ፓትርያርኮች እየመረጠች የሄደችበትን ቀኖና ታሪክና ሥልት ጠቅለል ባለ መልኩ ማቅረብ ነው፡፡ ከሌሎቹ አኀት አብያተ ክርስቲያናት የኮፕት ቤተ ክርስቲያንን የምርጫ ቀኖናና ሂደት ዳስሰን ለማቅረብ የፈለግንበት ምክንያት የቤተ ክርስቲያኗ መንበረ ፕትርክና ለ1600 ዘመናት የቤተ ክርስያናችንም መንበረ ፕትርክና ሆኖ የቆየ ከመሆኑ አንጻር በጽሑፉ የሚወሳው ታሪክ የሚቀርበን በመሆኑ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያኗ መንበረ ፕትርክናዋ በመጀመሪያው መቶ ክፍለ ዘመን ወንጌላዊው ማርቆስ ከተመሠረተበት ጊዜ ጀምሮ እስከ አሁን ድረስ በድምሩ 117 ፓትርያርኮችን እየመረጠች አስቀምጣለች፡፡ ፓትርያርኮቹም የተቀበሉትን ሰማያዊ ሓላፊነት በመያዝ ቤተ ክርስቲያኗ ክፉውንና ደጉን ዘመን አልፋ ዛሬ ካለችበት ደረጃ እንድትደርስ አድርገዋታል፡፡ አሁን ባለችበት ሁኔታ ቤተ ክርስቲያኗ በግብጽና በመላው ዓለም ከ15 እስከ 18 ሚልዮን የሚደርሱ ምእመናን ያሏት ሲሆን እነዚህንም ምእመናን በእረኝነት የሚጠብቁ ከ150 በላይ ሊቃነ ጳጳሳት አሏት፡፡ እነዚህ ሊቃነ ጳጳሳት በመንበረ ፕትርክናው ማእከላዊ አስተዳደር በሚመሩ 54 ያኽል አኅጉረ ስብከት በሊቃነ ጳጳስነት ተመድበው ያገለግላሉ፡፡ ከእነዚህ አኅጉረ ስብከት 15 የሚሆኑት ከግብጽ ውጪ በተለያዩ ክፍላተ ዓለም ተቋቁመው በማገልገል ላይ የሚገኙ ናቸው፡፡

 

ቤተ ክርስቲያኗ በአሁኑ ወቅት ከ41 ዓመታት የፕትርክና አገልግሎት በኋላ መጋቢት 17 ቀን 2012 ዓ.ም. /በዚህ ጽሑፍ የተሰጡት የቀናትና የዓመታት ቁጥር በሙሉ እንደ አውሮፓውያኑ አቆጣጠር ነው/ ከዚህ ዓለም የተለዩትን 117ኛውን ፓትርያርክ ብፁዕ አቡነ ሲኖዳ 3ኛን ለመተካት በከፍተኛ ዝግጅት ላይ ትገኛለች፡፡ በመሆኑም ቤተ ክርስቲያኗ እ.ኤ.አ. ከ1975 ዓ.ም. ጀምሮ ባላት ቀዋሚ የፓትርያርክ ምርጫ ደንብ መሠረት ሦስት ዕጩዎች ተለይተው አንዱ በዕጣ የሚመረጥበት የመጨረሻ ሥነ ሥርዓት ለመስከረም ቀጠሮ ተይዟል፡፡ ለመሆኑ ይህ ቀዋሚ የፓትርያርክ ምርጫ ደንብ ተረቆ በመጽደቅ ሥራ ላይ ከመዋሉ በፊት ያገለገሉት ፓትርያርኮች እንዴት ተመረጡ? የአመራረጣቸው ሂደትና ቀኖናስ ምን ይመስል ነበር? እያንዳንዱ ሂደትና ቀኖና ተመሳሳይ ነበር ወይስ ልዩነት ነበረው? ይህ ጽሑፍ ለእነዚህ ጥያቄዎች መልስ ይሰጣል፡፡

 

በቤተ ክርስቲያኗ ታሪክ የፓትርያርኮች ምርጫ ምንም እንኳን በመሠረታዊ የተመራጮቹ መመዘኛዎች በአብዛኛው ልዩነት ባይኖርም፤ የምርጫ አፈጻጸም ቀኖናዎች ላይ የሚስተዋሉ ልዩነቶች ነበሩ፡፡ በጉዳዩ ላይ የተጻፉ ጥናቶችንና የፓትርያርኮቹን የሕይወት ታሪክ በማጥናት በቤተ ክርስቲያኗ የ2000 ዘመናት ታሪክ ዘጠኝ ዓይነት የምርጫ ቀኖናዊ ሥልቆች ነበሩ ማለት ይቻላል፡፡ እነዚህን ሥልቶች ከነ አፈጻጸማቸውና ከተመረጡባቸው ፓትርያርኮች ዝርዝር ጋር እንደ ሚከተለው እንመለከታለን፡፡

 

1.    የካህናት ብቻ ምርጫ /Election by Presbyterians of Alexandria/

ይህ ቀኖና ፓትርያርክ የመምረጡን ሓላፊነትና መብት ለካህናት ብቻ የሰጠ ቀኖና ነው፡፡ በተለይ በቤተ ክርስቲያኗ የመጀመሪያዎቹ ዘመናት ያገለገለው ይህ የምርጫ ቀኖና መሠረት ያደረገው በወቅቱ ቤተ ክርስቲያኗ የነበራትን አስተዳደራዊ መዋቅር ነበር፡፡ በተለያዩ መዛግብት ተገልጾ እንደሚገኘው በመጀመሪያዎቹ የአገልግሎት ዘመናቷ ቤተ ክርስቲያኗ ስትመራ የነበረው አባላቱ 12 በሆነ የካህናት ጉባኤ /Presbyterian Council/ አማካይነት ነበር፡፡ በ12ቱ ሐዋርያት ምሳሌነት በቅድስናቸውና በአገልግሎት ልምዳቸው ከማኅበረ ካህናቱ ተመርጠው የሚሾሙት እነዚህ 12 ካህናት ከመካከላቸው የበለጠ የተሻለ ነው ያሉትን አንድ አባት መርጠው በአስራ አንዱ አንበሮተ እድ ሊቀ ጳጳስ አድርገው ይሾሙታል፡፡ ይህ ሊቀ ጳጳስ ጉባኤውን በበላይነት ይመራል፤ ካህናትን ይሾማል፤ አንድ ፓትርያርክ ያለውን ሓላፊነት ሁሉ ይፈጽማል፡፡ በዚህ ዓይነቱ ምርጫ እስከ 12ኛው ፓትርያርክ ዲሜጥሮስ ቀዳማዊ /189-231 ዓ.ም./ ድረስ ቤተ ክርስቲያኗ አንድ ጳጳስ ብቻ ነበራት፡፡

 

በዚህ የምርጫ ሥልት የተመረጠው ሊቀ ጳጳስ በእርግናም ይሁን በጤና መታወክ የተነሣ ኅልፈተ ሕይወቱ በደረሰ ጊዜ ከአስራ አንዱ ውስጥ ብቃት አለው ያለውን መርጦ ያለፈበት አካሄድ ነበር፡፡ ምርጫውንም የሚያውጀው ካህናትና ምእመናን በተሰበሰቡት ጉባኤ ነበር፡፡ ነገር ግን ምንም እንኳን ይሁን ብሎ መርጦት ቢሄድ ተመራጩ በመንብረ ፕትርክናው የሚቀመጠው በካህናት ጉባኤው ታምኖበት ሲጸድቅና በአንብሮተ እዳቸው ሲሾም ብቻ ነበር፡፡ በዚህ ዓይነት ስድስተኛው ፓትርያርክ በቴኦናስ /282-300 ዓ.ም./ እና ሰባተኛው የግብጽ ፓትርያርክ ጴጥሮስ ቀዳማዊ /300-311 ዓ.ም./ ተመርጠው አገልግለው አልፈዋል፡፡

 

ይህ ፓትርያርኮችን የመምረጡ ሥልጣንና ሓላፊነት ካህናት ብቻ የሆነበት ቀኖና እስከ 19ኛው ፓትርያርክ አባ እስክንድር /312-326 ዓ.ም./ ድረስ ሲያገለግል ቆይቶ መንበረ ፓትርያርኩ ከአሌክሳንድርያ ተነሥቶ ወደ ካይሮ ከመዛወሩ ጋር ተያይዞ ተግባራዊነቱ እየቀነሰ መጥቶ በሌላ ቀኖና ተተክቷል፡፡

 

2.    የምእመናን ብቻ ምርጫ / Election by Laity Acting Alone/

ይህ የምርጫ ሥልት በተለይ ቤተ ክርስቲያኗ በእስልምና ወረራ የተነሣ ካህናቷን አጥታ በነበረችበት ዘመን ይፈጸም የነበረ ሲሆን፤ የፓትርያርክ ምርጫ መብት የምእመናን ብቻ የነበረበት ሥልት ነው፡፡ በመሆኑም በዚህ ሥልት ከተመረጡት አምስት ፓትርያርኮች ምእመናንና ዲያቆናት የነበሩ ይገኙባቸዋል፡፡

 

3.    የኤጲስ ቆጶሳት ብቻ ምርጫ /Election by Bishops Acting Alone/

በአፈጻጸሙ ከሮም ካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን ጋር ተመሳሳይነት ያለው ይህ ሥልት በፓትርያርኮች ምርጫ ምእመናንና ካህናት ቦታ ሳይኖራቸው በኤጲስ ቆጶሳት ብቻ የሚከናወን ነበር፡፡

 

በዚህ ሥልት በድምሩ አራት ፓትርያርኮች ብቻ የተመረጡ ሲሆን እነሱም 19ኛው ፓትሪያርክ አባ እስክድር /312-326 ዓ.ም./፣ 35ኛው ፓትርያርክ አባ ዳምያን /569-605 ዓ.ም./፣ 52ኛው ፓትርያርክ አባ ዮሳብ /830-849 ዓ.ም./ እና 112ኛው ፓትርያርክ አባ ቄርሎስ 5ኛ /1874-1927 ዓ.ም./ ናቸው፡፡

 

4.    በጠቅላላ ስምምነት /Election by General Consensus/

ይህ የምርጫ ቀኖና አፈጻጸሙ ከሊቃነ ጳጳሳት፣ ከካህናት ተወካዮችና ከሌሎች መሪዎች የተውጣጡ መራጮች ካሉት ሊቃነ ጳጳሳት አንዱን በሙሉ ስምምነት መርጠው የሚሾሙበት ቀኖና ነበር፡፡ በዚህ ቀኖና ሠላሳ አምስት ፓትርያርኮች ተመርጠው አገልግለው አልፈዋል፡፡ የፓትሪያርኮችን ዝርዝር ከጽሑፉ መጨረሻ ከሚቀርበው ሠንጠረዥ ይመለከቷል፡፡

 

5.    በሓላፊው ፓትርያርክ ምርጫ /Election through the Appointment of the Predecessor/

በዚህ የምርጫ ቀኖና በዕድሜ መግፋትም ይሁን በጤና መታወክ የተነሣ ኅልፈተ ሕይወቱን በሚጠባበቅበት አልጋ ላይ /Death bed/ ሆኖ የሚጠብቀው ፓትርያርክ ካሉት ጻጳሳት ወይም መነኮሳት ውስጥ የበለጠ ይመጥናል ያለውን መርጦ የሚያስቀምጥበት ቀኖና ነው፡፡ ይህንን ቀኖናዊ የምርጫ ሥልት ቤተ ክርስቲያኗን ያጠኑ ሊቃውንት የፓትሪያርክ የመጨረሻ ምኞት /patriarchal Death bed wish/ ይሉታል፡፡ እንደ ቤተ ክርስቲያኗ ሊቃውንት ትረካ የዚህ ቀኖና መሠረቱ የመጀመሪያው የቤተ ክርስቲያኗ መሥራችና ፓትርያርክ ቅዱስ ማርቆስ በእሱ መንበር ተቀምጦ ቤተ ክርስቲያኗን ይመራ ዘንድ ሁለተኛውን ፓትርያርክ አባ አንያኖስን /68-85 ዓ.ም./ መርጦ ያለፈበት ታሪክ ነው፡፡ በዚህ ቀኖናዊ የምርጫ ሥልት በድምሩ ሰባት ፓትርያርኮች ተመርጠዋል፡፡ ይህ ሥልት በብቃት ሳይሆን ለፓትርያርኩ ካላቸው ቅርበት የተነሣ እንዲመረጡ ያደረጋቸው አንዳንድ አባቶች እንዳሉ በቤተ ክርስቲያኗ ታሪክ ይወሳል፡፡ በዚህ ረገድ በምሳሌነት የሚጠቀሰው ሠላሳ ስምንተኛው ፓትርያርክ አባ ቢንያም ቀዳማዊ /622-661 ዓ.ም./ ነው፡፡ ይህ ፓትርያርክ ሲመረጥ በቅድስናም ይሁን በአገልግሎት ልምድ ከእነሱ የተሻሉ የነበሩ ቢሆንም በዘመነ ፕትርክናው ያገለግለው የነበረው ሓላፊ ፓትርያርክ ስለመረጠው እንደተሾመ ተጽፏል፡፡

 

6.    መለኮታዊ ምርጫ ወይም ራእይ /Election by Divine Appointment or vision/

እንደ ቤተ ክርስቲያኗ ሊቃውንት አስተምህሮ ይህ ሥልት የተወሰደው የመጀመሪያው ፓትሪያርክ ቅዱስ ማርቆስ ወንጌላዊ በመለኮታዊ ጥበብ ከተሾመበት አካሄድ ነው፡፡ ይህ ሥልት በተለይ በሓላፊው ፓትርያርክ ወይም ለእሱ ለሚቀርቡና በፓትርያርክ ምርጫው ተሳትፊ በሆኑ አካላት በሚታይ ራእይ ተመሥርቶ ፓትርያርክ የሚመረጥበት ዘዴ ነበር፡፡ ለምሳሌ በእርግና አልጋው ላይ የነበረው 11ኛው ፓትርያርክ አባ ዩልየስ /189-231 ዓ.ም./ መልአኩ ተገልጦ “ነገ ወደ መንበረ ፕትርክናው መጥቶ ዕቅፍ ወይን የሚያበረክትልህ እሱ በመንበርህ ይተካል” እንዳለውና በወቅቱ በግብርና የገዳም ማኅበሩን ሲያገለግል የነበረው ዲሜጥሮስ ባልተለመደ ሁኔታ ማሳው ላይ የወይን ተክል በማግኘቱ “ይህስ ለቅዱስ ፓትርያርክ ይገባል” ብሎ ቆርጦ በዕቅፉ ወስዶ ስላበረከተለት መንበረ ፓትርያርኩን ተረክቦ ቤተ ክርስቲያኗን ለ42 ዓመታት /189-231 ዓ.ም./ እንዳገለገለ መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡ በተመሳሳይም 46ኛውን ፓትርያርክ ለመምረጥ ኤጲስ ቆጶሳት ካህናትና ምእመናን ተሰብስበው ሦስት ዕጩዎችን ቢያቀርቡም በመራጮቹ መካከል ከፍተኛ ልዩነትና ጭቅጭቅ በተነሣ ጊዜ ከመካከላቸው አንዱ የሆነው ሊቀ ዲያቆን፤ አባ ኽኢል የተባለው ሰው ለመንበሩ ብቃት እንዳለው ራእይ በማየቱ በእሱ ሕልም ተመርተው በሙሉ ስምምነት እንደሾሙት ተጽፏል፡፡

 

7.    ዕጣ የማውጣት ምርጫ /Election through Casting of Lots/

ይህ ቀኖና አስራ አንዱ ሐዋርያት በይሁዳ ምትክ ከእነሱ ጋር ይደመር ዘንድ ማትያስን የመረጡበትን አካሄድ በሞዴልነት በመጠቀም በቤተ ክርስቲያኗ የታሪክ ዘመናት እንደታየው ይህ ዘዴ ተግባር ላይ ሲውል የነበረው በዕጩዎች መካከል እኩል ተቀባይነትና ቅድስና ኖሮ አንዱን ከሌላው ለመለየት አስቸጋሪ ሲሆን ወይም ዕጩዎች ያገኙት ድምጽ አንድ ዓይነት ሲሆንና /ምሳሌ ሰባ አንደኛው ፓትርያርክ አባ ሚካኤል /1145-1146 ዓ.ም/ እና በዕጩዎቹ ደጋፊዎች መካከል ከፍተኛ ሽኩቻና ጸብ ሲኖር /ምሳሌ 48ኛው ፓትርያርክ ዮሐንስ አራተኛ /775-799 ዓ.ም./ ነው፡፡ የዕጣ አወጣጥ ሥርዓቱም በሰንበት ቀን የዕጩዎቹ ስም በታሸገ ኢንቨሎፕ ከመንበሩ ላይ ይቀመጥና ጸሎተ ቅዳሴ እንዲሁም ቀኖና የሚያዝዘው ጸሎት ሁሉ ተደርጎ ሲያበቃ አንድ ሕጻን ከአስቀዳሾች መካከል ቀርቦ ዓይኑን በጨርቅ ከታሰረ በኋላ አንዱን ያወጣል፡፡ ስሙ የወጣውም ቀጣዩ የቤተ ክርስቲያኗ ፓትርያርክ ሆኖ ይሾማል፡፡ በዚህ ቀኖናዊ ሥልት በአጠቃላይ አሥር ያህል ፓትርያርኮች ተመርጠው አገልግለው አልፈዋል፡፡

 

ከዚህ በታች የምናያቸው ሁለት የምርጫ ሂደቶች በቤተ ክርስቲያኗ ታሪክ በቀኖናዊ ሥልትነት የተመዘገቡ ሳይሆኑ፤ ፓትርያርኮች ተመርጠው ያለፉባቸው አካሄዶች ናቸው፡፡

 

8.    የመንግሥት ጣልቃ ገብነት /Strong Intervention by Government/

የኮፕት ቤተ ክርስቲያን ዛሬ ድረስ ዘልቀው ከሚያስቸግሯት ፈተናዎች አንዱ በሀገሪቱ መንግሥት ያለባት ጫና ነው፡፡ ይህ የገዥዎች ቀንበር በቤተ ክርስቲያኗ ጫንቃ ላይ የወደቀው ሀገሪቱ በአረብ እስላሞች እጅ ከወደቀችበት 640 ዓ.ም. ጀምሮ ነው፡፡ ሀገሪቱን የሚመራው ኢስላማዊ መንግሥት በቤተ ክርስቲያኗ ላይ ከሚያሳድረው ተጽዕኖ መገለጫዎች አንዱ በቤተ ክርስቲያኗ የፓትርያርክ ምርጫ ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖና የወሳኝነት ሚና ነበር፡፡ እሱም ቢሆን ከመንግሥቱ ጣልቃ ገብነት ሳይወጣ፤ ቤተ ክርስቲያኗ በራሷ አካሄድ ይሆነኛል ያለችውን ብትመርጥም ተመራጩ አባት ፓትርያርክ ሆኖ የሚሠየመው ስሙ ወደ ሀገሩ ገዥ ተልኮ ሲጸድቅ ብቻ ነበር፡፡ በዚህ ዓይነት በቤተ ክርስቲያኗ ታሪክ ስድስት ያህል ፓትርያርኮች ተመርጠው አገልግለው አልፈዋል፡፡ በእርግጥ ቤተ ክርስቲያኗ በፓትርያርክ ምርጫ ከፍተኛ የመንግሥት ተጽዕኖ ነበረባት ቢባልም፤ በወቅቱ የነበሩት አባቶችና ምእመናን ተጽዕኖውን በመቋቋም የቤተ ክርስቲያናቸውን ክብር ለማስጠበቅ ሞክረዋል፡፡ በዚህ ረገድ ከሊቃነ ጳጳሳቱ፣ ማኅበረ ካህናቱና ምእመናኑ ፈቃድና ይሁንታ ውጭ በወቅቱ ለነበሩት ገዥዎች በነበረው ቀረቤታና አገልግሎት በመንግሥት ቀጥተኛ ምርጫና ትእዛዝ እንዲመረጥ የቀረበውን ሰባ አምስተኛውን ፓትርያርክ አባ ቄርሎስ 3ኛ /1235-1243 ዓ.ም./ እንዳይመረጥ ከፍተኛ ተጋድሎ አድርገዋል፡፡ በዚህ የተነሣም ምንም እንኳን የኋላ ኋላ መንግሥት አሸንፎ አባ ቄርሎስ ፓትርያርክ ሆኖ ቢመረጥም፤ ለ19 ዓመታት መንበሩ ባዶ ሆኖ ታግለዋል፡፡

 

9.    በአጋጣሚ /Election by Coincidence or Chance/

ይህ የምርጫ ሂደት መራጮቹም ይሁኑ ተመራጩ ባላሰበበት ሁኔታ በአጋጣሚ ያልታሰቡ መነኮሳት ተመርጠው ለከፍተኛው ሥልጣን የበቁበት ሂደት ነው፡፡ ለዚህ ሂደት በምሳሌነት በተደጋጋሚ ተጠቅሶ የሚገኘው የ64ኛው ፓትርያርክ አመራረጥ ሂደት ነው፡፡ 63ኛው ፓትሪያርክ ከዚህ ዓለም በሞት እንደተለየ ሲሰማ፤ አንድ ባዕለ ጸጋ በዘመኑ ለነበረው ኸሊፋ /የግብጽ ገዥ/ ብዙ ገንዘብ ከሰጠው በኋላ ባለፈው ፓትርያርክ መንበር እንዲሾመው ይጠይቀዋል፡፡ ኸሊፋውም የባዕለ ጸጋውን ገንዘብና ጥያቄ ተቀብሎ በካይሮ ያሉት አባቶች ትእዛዙን ይፈጽሙ ዘንድ ደብዳቤ አስይዞ ይልከዋል፡፡ በዚህ ተጨንቀው የተቀመጡ አባቶችም ነጋዴውን በመጠባበቅ ላይ ሳሉ አንድ በቅድስናውና በአገልግሎት ትጋቱ የታወቀ መነኩሴ የሸክላ ድስት ይዞ አባቶች ተሰባስበው ወደ ተቀመጡበት አዳራሽ ይገባና እየጮኸ ድስቱን ከደረጃ ላይ በኀይል ይጥለዋል፡፡ ደጋግሞም እያነሳ ይጥለዋል፡፡ ነገር ግን ባልተለመደ ሁኔታ ድስቱ ሳይሰበር ቀረ፡፡ ይህንን ያዩና በጭንቀት ውስጥ የነበሩ አባቶች ባዕለ ጸጋው ከመድረሱ በፊት ቶሎ ብለው አባ ዘካርያስ /1004-1032/ ብለው መነኩሴውን እንደ ሾሙት በቤተ ክርስቲያኗ የታሪክ መዛግብት ሰፍሮ ይገኛል፡፡

 

ከላይ ባየናቸው ቀኖናዊ የምርጫ ማስፈጸሚያ ሥልቶችና ሂደቶች በእያንዳንዱ የተመረጡትን አባቶች ዝርዝር በሚከተለው ሠንጠረዥ ማየት ይቻላል፡፡

 

ተ.ቁ

ቀኖናዊ የምርጫ ሥልት

ወይም ሂደት

በሥልቱ ወይም በሂደቱ የተመረጡ አባቶች ብዛት

የተመረጡት ፓትሪያርኮች

ተራ ቁጥር

1

የካህናት ብቻ ምርጫ

16

4፣5፣6፣7፣8፣9፣10፣11፣12፣13፣14፣

15፣16፣17፣18፣

2

የምእመናን ብቻ ምርጫ

5

44፣70፣74፣77፣101

3

የኤጲስ ቆጶሳት ብቻ ምርጫ

4

19፣35፣52፣112

4

በጠቅላላ ስምምነት

35

20፣22፣24፣28፣36፣37፣43፣45፣

47፣51፣53፣54፣55፣61፣62፣67፣

68፣69፣72፣73፣76፣80፣81፣83፣

87፣95፣100፣106፣107፣109፣

110፣111፣113፣114፣115

5

በሓላፊው ፓትርያርክ ምርጫ

7

2፣21፣38፣39፣49፣50፣88

6

መለኮታዊ ምርጫ ወይም ራእይ

4

1፣12፣46፣82

7

ዕጣ የማውጣት ምርጫ

10

3፣48፣71፣102፣103፣104፣

105፣108፣116፣117

8

የመንግሥት ጣልቃ ገብነት

6

27፣31፣33፣41፣75፣78

9

በአጋጣሚ

3

42፣63፣64

 

በየትኛው ሥልት ወይም ሂደት እንደተመረጡ የማይታወቁ

27

 

 

ድምር

117

 

 

የፓትርያርክ ምርጫ ሥርዓትና አፈጻጸም በግብጽ ቤተ ክርስቲያን ዛሬ

ከላይ ባየናቸው ሥልቶች ፓትርያርኮቿን እየመረጠች 2000 ዓመታት የተጓዘችዋ ቤተ ክርስቲያን ዛሬ በቅርቡ ያለፉት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሲኖዳ 3ኛና እሳቸው የተኳቸው አባ ቄርሎስ ምርጫ ወቅት ሥራ ላይ ውሎ የተፈተነ ቀዋሚ የፓትርያርክ ምርጫ ደንብ አላት፡፡ የዚህን ደንብ ትርጉም ተግባር ላይ ከመዋሉ በፊትና ከዋለ በኋላ ያጋጠሙትንና እያጋጠሙት ካሉት ተግዳሮቶች ጋር በሚቀጥለው አቀርባለሁ፡፡

 

ምንጭ:-

Atiya, Aziz S.ed., The Coptic Encyclopedia.8 vols. New York:macmillan,1991.

E l- Masri, Iris Habib. The Story of the Copts: The true Story of Christian in Egypt. Cairo: Coptic Bishopric of African Affairs.1987.

Evetts. B. ed “History of the patriarchs of the Coptic Church of Alexandria” Patrologia Orientalis I.4, Paris,1984

Meinardus, O.F.A. Christian Egypt: Faith and Life. Cairo: American University in Cairo Press, 1970.

Saad Michael Saad and Nardine Miranda Saad. “Electing Coptic Patriarchs: A Diversity of Tradition”

Bulletin of St. Shenouda the Archimanrite Coptic Society 6,1999-2000, pp.20-32.

Emebetachin-Eriget

“ወልድኪ ይጼውአኪ ውስተ ሕይወተ ወመንግሥተ ክብር” ልጅሽ ወደ ሕይወትና ክብር መንግሥት ይጠራሻል፡፡

ነሐሴ 15 ቀን 2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ዮሴፍ ይኲኖ አምላክ
 

እንኳን ለወላዲተ አምላክ ለቅድስት ድንግል ማርያም የትንሣኤ በዓል በሰላም አደረሳችሁ እያልን ፈጣሪያችን በዓሉን የበረከት፣ የረድኤት ያድርግልን፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዓመቱ ነሐሴ 16 ቀን የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምን ትንሣኤ በታላቅ መንፈሳዊ ሥነ ሥርዓት ታከብራለች፡፡

ቅዱስ ያሬድ የእመቤታችንን ፍልሰተ ሥጋ አስመልክቶ ዝማሬ በተባለው ድርሰቱ “በስብሐት ውስተ ሰማያት መላእክት ወሊቃነ መላእክት ወረዱ ለተቀብሎታ፣ እብለኪ ወእሙ ለእግዚእየ እብለኪ ዳዊት አቡሃ ምስለ መሰንቆሁ ሙሴኒ እንዘ ይፀውር ኤፉደ መጽኡ ሃቤሃ ጴጥሮስ ወጳውሎስ ሐዋርያት አጠኑ ሥጋሃ በማዕጠንተ ወርቅ፣ ሱራፌል ወኪሩቤል ሰፍሑ ከነፊሆሙ ላዕሌሃ፣ ወረደ ብርሃን እምሰማያት ወመብረቀ ስብሐት እምውስተ ደመናት፣ ተለዓለት እምድር ውስተ አርያም በስብሐት ወበህየ ነበረት ዘምስለ ወልዳ በየማነ አብ ወመንፈስ ቅዱስ” ብሏል፡፡ ይኸውም “መላእክትና ሊቃነ መላእክት ቅዱስ ሥጋዋን ለማሳረግ በታላቅ ምሥጋና ከሰማይ ወረዱ፤ አባቷ ዳዊት ከመሰንቆው ጋር ሙሴም የአገልግሎት ልብሱን ለብሶ፣ ሐዋርያት ጴጥሮስና ጳውሎስም ወደ እርሷ መጡ ሥጋዋንም በወርቅ ማዕጠንት አጠኑ፡፡ ሱራፌልና ኪሩቤልም በላይዋ ክንፎቻቸውን ዘረጉ /ጋረዱ/፡፡ ከሰማያት ብርሃን የምስጋና መብረቅም ከደመናት ውስጥ ወጣ፡፡ ከምድር ወደ ሰማያት በምስጋና ከፍ ከፍ አለች ከልጇ ጋርም በአብና በመንፈስ ቅዱስ ቀኝ ተቀመጠች” ማለት ነው፡፡ ይህም “በወርቅ ልብስ ተጎናጽፋና ተሸፋፍና ንግሥቲቱ በቀኝህ ትቆማለች፡፡” መዝ.44፥9 ተብሎ የተነገረላትን ቃለ ትንቢት የተፈጸመላት መሆኑን ያመለክታል፡፡

 

የዚህም ጥንተ ነገሩ እንደምን ነው ቢሉ ታሪኩ ይህን ይመስላል፡-

እሑድ ጥር 21 ቀን እመቤታችን አርፋለች፡፡ ሐዋርያት ባጎበር አድርገው ወደ ጌቴ ሴማኒ ይዘዋት ሲሄዱ አይሁድ “ቀድሞ ልጇን ሰቅለን ብንገድለው ደቀ መዛሙርቱ ተነሣ፣ ዐረገ” እያሉ ሲያውኩን ኖሩ፤ ዛሬ ደግሞ እርሷን ተነሣች፣ ዐረገች እያሉ ሊያውኩን አይደለምን? በእሳት እናቃጥላታለን” ብለው ተነሡ፡፡ ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊ ተራምዶ አጎበሩን ጨበጠው፡፡ መልአኩ ቅዱስ ሩፋኤል የታውፋንያን ሁለት እጁን በሰይፍ መትቶ ቀጣው፡፡ በዚህም የታውፋንያ ሁለት እጁ ከአጎበሩ ተንጠልጥሎ ቀረ፡፡ ከዚያ በኋላ መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ወንጌላዊውን ቅዱስ ዮሐንስ ጨምሮ በደመና ነጥቆ ከገነት በዕፀ ሕይወት ሥር አኖራት፡፡ ሐዋርያት ዮሐንስን “እንደምን ሆነች” አሉት፡፡ እርሱም፡- “በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አለች” አላቸው፡፡ “ዮሐንስ አይቶ እኛ ሳናይ” ብለው፤ በነሐሴ መባቻ ጾም ጀመሩ፤ ሰኞ ነሐሴ 1 ቀን ጀምረው እሑድ ነሐሴ 14 ቀን ፈጽመዋል፡፡ በዚሁ ቀን ጌታችን ትኩስ በድን አድርጎ የእመቤታችንን ሥጋ ሰጥቷቸው ቀብረዋታል፡፡ እርሷም እንደ ልጇ በተቀበረች በሦስተኛው ቀን /ማክሰኞ/ ተነሥታ አርጋለች፡፡ “ከመ ትንሣኤ ወልዳ” ያሰኘውም ይህ ነው፡፡ በዚሁ ጊዜ ከሐዋርያት ወገን የሆነው ቅዱስ ቶማስ አልነበረም፡፡ ደመና ጠቅሶ ከሀገረ ስብከቱ /ከሕንድ/ ሲመጣ ስታርግ አገኛት፡፡ “ወፈቀደ ይደቅ እምደመናሁ” ይላል፤ ተበሳጨ፡፡ “ቀድሞ የልጅሽን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ፤ ዛሬ ደግሞ ያንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁኝ” አለ፡፡ በዚህ ጊዜ የልቡናን ሐዘን የምታቀል እመቤታችን፡- አይዞህ አትዘን እኒያ ትንሣኤዬን ዕርገቴን አላዩም፡፡ አንተ አይተሃል፡፡ ተነሣች፣ ዐረገች ብለህ ንገራቸው፡፡” ብላEmebetachin-Eriget የያዘችውን ሰበን ሰጥታ ሰደደችው፡፡ ከዚህ በኋላ ሄዶ፤ “የእመቤታችን ነገር እንደምን ሆነ?” አላቸው “ሥጋዋን አግኝተን ቀበርናት” አሉት፡፡ እርሱም “ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር ተዉ ይህ ነገር አይመስለኝም” አላቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ “አንተ እንጂ ልማድህ ነው፡፡ አንተ ብቻ ተጠራጥረህ አትቀርም፤ አንተ እየተጠራጠርህ ሰውን ሁሉ ስታጠራጥር ትኖራለህ” አለው፡፡ እርሱም የያዘውን ያውቃልና ጸጥ ብሎ ይሰማቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ ቅዱስ ጴጥሮስ ተቆጥቶ ሂዶ መቃብሩን ቢከፍተው የእመቤታችን ሥጋዋን አጥቷል፡፡ በዚህም ምክንያት ደንግጦ ቆመ፡፡ ይህን ጊዜ ቅዱስ ቶማስ “አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ተነሣች ዐረገች” አላቸው፡፡ የያዘውንም ሰበን እያሳያቸው፡- “ቅዱስ ሥጋዋን የገነዛችሁበት ጨርቅ /ሰበን/ ይህ አይደለምን” ብሎ ሰበኑን ሰጣቸው፡፡ ይህንንም ለበረከት ተካፍለውታል፡፡ ከዚህ በኋላ በዓመቱ “ቶማስ ትንሣኤሽን ዕርገትሽን አይቶ እኛ ሳናይ በማለት ጾም ጀመሩ፡፡ በ16ኛው ቀን እመቤታችንን መንበር ቅዱስ ጴጥሮስን ንፍቅ ቄስ፣ እስጢፋኖስን ሠራዒ ዲያቆን አድርጎ ራሱ ቀድሶ አቁርቦአቸዋል፡፡

 

እመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያም በእናት አባቷ ቤት 3 ዓመት፣ በቤተ መቅደስ 12 ዓመት፣ ጌታችንን ከወለደችበት ጊዜ አንሥቶ ለ33 ዓመት ከ3 ወር ከተወዳጅ ልጇ ጋር፣ ለ15 ዓመት ከ9 ወር ከቅዱስ ዮሐንስ ጋር፣ በአጠቃላይ በዚህች ምድር ለ64 ዓመታት ቆይታ በተነገረላት ተስፋ ትንሣኤና ትንቢት መሠረት እርሷም እንደ ልጇ ወደ መቃብር በወረደች በሦስተኛው ቀን በልጇ ፈቃድ ከሙታን ተለይታ ተነሥታለች፡፡

 

“አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ፥ አንተና የመቅደስ ታቦት” /መዝ.131፥8/ የሚለው የነቢየ እግዚአብሔር የቅዱስ ዳዊት ቃልም ፈጻሜውን አግኝቷል፡፡

እግዚአብሔር አምላካችን ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በረከት ረድኤት ያሳትፈን፡፡

Debre_Tabor

ደብረ ታቦር

ሐሴ 13 ቀን 2004 ዓ.ም.

በመ/ር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

“ወኮነት ደብረ ታቦር አምሳለ ቤተ ክርስቲያን እስመ አስተጋብአት እም ብሉይ ወሐዲስ”

 

ደብረ ታቦር የቤተ ክርስቲያን ምሳሌ ነች፤ ከብሉይና ከሐዲስ ሰብስባለችና፡፡ ከብሉይ ኪዳን ነቢያት ሙሴና ኤልያስን ከሐዲስ ኪዳን ሐዋርያት ጴጥሮስን ያዕቆብን፣ ዮሐንስን ከመምህራቸው ከክርስቶስ ጋር ሰብስባለችና፡፡ ቤተ ክርስቲያን በነቢያትና በሐዋርያት መሠረትነት ላይ ተመሥርታለች “እስመ ተሐነጽክሙ ዲበ መሠረተ ነቢያት ወሐዋርያት እንዘ ክርስቶስ ርዕሰ ማዕዘንተ ሕንጻ”  “በነቢያትና በሐዋርያት መሠረት ላይ ታንጻችኋል፤ የማዕዘኑም ራስ ደንጋይ ክርስቶስ ነው” እንዲል፡፡ኤፌ. 2፥20

የታቦር ተራራ

፩. የቤተ ክርስቲያን

፪. የወንጌል

፫. የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው፡፡

 

አንደኛውን ምሳሌ ከላይ የተመለከትን ሲሆን ሁለተኛው ምሳሌ አበው መተርጉማን በትርጓሜአቸው እንዲህ አብራርተውታል፡፡ ተራራ ሲወጡት አድካሚ ነው ከወጡት በኋላ ግን ሁሉንም ቁልጭ አድርጎ ሲያሳይ ደስ ያሰኛል፤ ወንጌልም ሲማሯት፤ ሲያስተምሯት ታደክማለች፤ ከተማሯት በኋላ ግን ጽድቅና ኀጢአትን ፤እውነትንና ሐሰትን ለይታ ስታሳውቅ ደስ ታሰኛለችና”፡፡ “በሌላ መልኩ ከተራራ ላይ ያለ ሰው ጠላቱን በቀላሉ በአፈር በጠጠር ድል መንሣት፣ ፍትወታት እኩያትን ማሸነፍ ይችላል፡፡ ከተራራ ላይ ያለ ልሰወር ቢል እንዳይችል በወንጌል ያመነ ሰውም ተሰውሮ አይቀርም በመልካም ሥራው ለሁሉም ይገለጣል፡፡ በሦስተኛውም ተራራው የመንግሥተ ሰማያት ምሳሌ ነው፡፡ ከነቢያት ሁለቱ ከሐዋርያት ሦስቱ በተራራው ላይ መገኘታቸው መንግሥተ ሰማያት ነቢያትም ሐዋርያትም አንድ ሆነው የሚወርሷት መሆኑን ያስረዳል፡፡ ከደናግ ኤልያስዮሐንስ ከመአስባን (በሕግ ጋብቻ ኖረው ሚስቶቻቸው የሞቱባቸው ወይም ትዳራቸውን የተው) ሙሴ ጴጥሮስ በተራራው ላይ መገኘታቸውም መንግሥተ ሰማያት ደናግም መአስባንም መልካም ሥራ ሠርተው በአንድነት የሚወርሷት እንደሆነ ይገልጻል፡፡

እንዲሁም ተራራ ሲወጡት አድካሚ ነው መንግሥተ ሰማያት በብዙ ድካም ትወረሳለችና “እስመ በብዙህ ጻማ ሐለወነ ንበአ ውስተ መንግሥተ እግዚአብሔር” ወደ እግዚአብሔር መንግሥት በብዙ መከራ እንገባ ዘንድ አለን” እንዲል ሐዋ.14፥23 ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ብርሃነ መለኮቱን በደብረ ታቦር የገለጸበት ምክንያት ምሥጢር በብዙ ድካም እንጂ ምንም ሳይደክሙ እንደማይገኝ ሲገልጽ ነው፡፡ ለደቀ መዛሙርቱ ብዙዎቹን ምሥጢራት የገለጠላቸው ከከተማ ውጭ ነው፡፡ ቀደም ሲልም ለሙሴ የቃል ኪዳኑን ጽላት ሲሰጠው ወደ ሲና ተራራ በመጥራት ነበር፡፡ ነገረ ሥጋዌውንም በነበልባልና በእሳት አምሳል የገለጠለት በኮሬብ ተራራ በጎቹን አሰማርቶ በነበረበት ጊዜ እንደሆነ መጻሕፍት ይመሰክራሉ ዘፀ.3፥1 ምሥጢር ይገለጽልን ባላችሁ ጊዜ ወደ ቤተ ክርስቲያን ገስግሱ ቤተ ክርስቲያንን ደጅ ጽኑ ለማለት ነው፡፡ ወደ ተራራውም ሲወጣ ስምንቱን ደቀ መዛሙርቱን ከይሁዳ ጋር ከተራራ እግር ስር ትቶ ሦስቱን አስከትሎ ወጥቷል፡፡ ለሦስቱ በተራራው ላይ የተገለጠው ድንቅ ምሥጢርም ከእግረ ደብር ላሉት በሳምንቱ ተገልጿል፤ ከይሁዳ በቀር፡፡ ለዚህ ምሥጢር ብቁ ያልነበረው ይሁዳ ብቻ ነው፡፡ ይህም የሚያስተምረን ተገቢውን ምሥጢር ለተገቢው ሰው መንገር እና ለማይገባው ከመንገር መቆጠብ ተገቢ መሆኑን ነው፡፡ “እመኒ ክዱን ትምዓርትነ ክዱን ውእቱ ለህርቱማን ወለንፉቃን” ወንጌላችን የተሰወረ ቢሆንም እንኳን ፥ የተሰወረባቸው ለሚጠፉት ነው፡፡ እግዚአብሔርን የሚመስለው የክርስቶስ የክብሩ ወንጌል ብርሃን እንዳያበራላቸው የዚህ ዓለም አምላክ ልባቸውን አሳውሯልና፡፡ 2ቆሮ.4፥3-5 ያለው የሐዋርያው ትምህርት ይህን መሰል ምሥጢር ለሚገባው እንጂ ለማይገባው መግለጽ ተገቢ አለመሆኑን ነው፡፡

 

በዓለ ደብረ ታቦር

እንደሚታወቀው በቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮ ከጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ዘጠኙ ዐበይት /ታላላቅ/ በዓላት አንዱ በዓለ ደብረ ታቦር ነው፡፡ ከዐበይት በዓላት የተመደበበትም ምክንያት በደብረ ታቦር የተገለጸው ምሥጢር ድንቅ በመሆኑ ነው፡፡ ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችን አምላካችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ለደቀ መዛሙርቱ አንድ አንድ ጊዜ ለሁሉም፤ አንድ አንድ ጊዜ ደግሞ በከፊል ምሥጢራትን ገልጾላቸዋል፡፡ ከእነዚህም ምሥጢራት የሚከተሉት ተጠቃሾች ናቸው ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንን በቤተ አልዓዛርና በቤተ ኢያኤሮስ፣ ምሥጢረ ቊርባንን እንዲሁ በአልዓዛር ቤት፣ ነገረ ምጽአትን በደብረ ዘይት ገልጿል፡፡ ማቴ.9፥23፣ 26፥26፣24፥3፣ ዮሐ.11፥43 ከእነዚህ ከላይ ከተዘረዘሩት ምሥጢራት ምሥጢረ ትንሣኤ ሙታንና ምሥጢረ ቊርባንን ሁሉም ደቀ መዛሙርት ያዩ ሲሆን ነገረ ምጽአትን ግን በከፊል ከደቀ መዛሙርቱ ጴጥሮስ፣ ያዕቆብና ዮሐንስ አራተኛ እንድርያስን ጨምረው ተረድተዋል፡፡ ደብረ ታቦርን ከዚህ ልዩ የሚያደርገው ከሐዋርያት ጴጥሮስ፣ ዮሐንስና ያዕቆብ ያሉ ሲሆን ከነቢያት ሙሴና ኤልያስ መጨመራቸው ነው፡፡ ከጌታችን ዘጠኝ በዓላት አንድ አንዶቹ በተፈጸመው ድርጊት የተሰየሙ ሲሆን ከፊሎቹ ድርጊቱ በተፈጸመባቸው ቦታዎች ተሰይመዋል፡፡ በድርጊቱ የተሰየሙት ጽንሰት፣ ልደት፣ ጥምቀት፣ ስቅለት፣ ትንሣኤ፣ ዕርገት ሲሆኑ ሁለቱ ሆሳዕናና  ጰራቅሊጦስ ደግሞ ድርጊቱንና ስምን አስተባብረው የያዙ ሲሆን ከእነዚሁ ሁሉ ተለይቶ ደብረ ታቦር ድርጊቱ በተፈጸመበትDebre_Tabor ቦታ ተሰይሟል፡፡

 

ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከሁሉም ምሥጢራት ነገረ ምጽአቱንና ምሥጢረ መንግሥቱን በተራራ ላይ ገልጿል፡፡ ነገረ ምጽአትን በደብረ ዘይት የገለጸበትን ምክንያት ጠቢቡ ስሎሞን ለሁሉም ጊዜ አለው እንዳለ ለጊዜው ትተነው ወደ ደብረ ታቦር እንመለስ ፡፡ጌታችን ብርሃነ መለኮቱን ለደቀ መዛሙርቱ የገለጠበት ነቢያት ሊያዩት የተመኙትን ያዩበት ነቢያትና ሐዋርያት በአንድነት የተገናኙበት፣ ተገናኝተው እንደ አንድ ልብ መካሪ እንደ አንድ ቃል ተናጋሪ ሆነው የክርስቶስን የባህርይ አምላክነት የመሰከሩበት፤ እግዚአብሔር ወልድ በክበበ ትስብዕትና በግርማ መለኮት የተገለጠበት፣ እግዚአብሔር አብ በደመና የምወደው ለተዋሕዶ የመረጥኩት በዕርሱ ህልው ሆኜ የምመለክበት ልጄ ይህ ነው እርሱን ስሙት ብሎ የመሰከረበት፣ መንፈስ ቅዱስም በአምሳለ ርግብ የወረደበት፣ እግዚአብሔር አንድነቱን ሦስትነቱን የገለጠበት እነ ቅዱስ ጴጥሮስ ለመኖር የተመኙት ደብረ ታቦር ነው፡፡ በዓሉ የጌታችን ሲሆን በስሙ ደብረ ታቦር ተብሏል፡፡ ይህን በዓል ስናከብር ያን ጊዜ ጌታችን ደቀ መዛሙርቱን አስከትሎ ወደ ተራራው ሲወጣ በተራራው ራስ ላይ ምሥጢሩን ሲገልጥላቸው አእምሮአቸውን ሲከፍትላቸው ከግርማው የተነሣ ፈርተው ሲወድቁ ሲያነሣቸው በዐይነ ሕሊና የምንመለከትበት ነው፡፡

 

ለዚህ ምሥጢር ደብረ ታቦር ለምን ተመረጠ?

1.    ደብረ ታቦር የድል ተራራ ነው፡፡

የእስራኤል ነቢይት ዲቦራ ለባርቅ የእስራኤል ጠላት የነበረው የኢያቢስን የሠራዊት አለቃ ሲሣራን ለመውጋት ወደ ደብረ ታቦር አስር ሺ ሰዎችን አስከትሎ እንዲወጣ ነግራዋለች፤ “የአቢኒኤምን ልጅ ባርቅ ጠርታ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ሔደህ ወደ ታቦር ተራራ ውጣ ከአንተም ጋር ከንፍታሌምና ከዛብሎን ልጆች አስር ሺ ሰዎች ውሰድ” መሳ.4፥6፡፡ በዚህ መልኩ ባርቅ አስር ሺ ሰዎችን አሰልፎ ዲቦራን አስከትሎ በደብረ ታቦር ሰፍሮ የነበረውን የሲሣራን ሠራዊት ድል ነሥቶበታል፡፡ ሲሣራ ዘጠኝ መቶ የብረት ሠረገላ እንዲሁ ብዙ ሠራዊትም በታቦር ያሰለፈ ቢሆንም ድል ግን ረድኤተ እግዚብሔርን ጥግ ላደረገ ለባርቅ ሆነ፤ በዚህ ጊዜ ዲቦራ በታቦር ተራራ የሙሴ እኅት ማርያም በኤርትራ ባሕር የዘመረችውን መዝሙር የመሠለ ምስጋና አቅርባለች፡፡ ሁሉም እስራኤላውያን የድል መዝሙር ዘምረውበታል ፈጣሪአቸውን አመስግነውበታል፡፡ ጌታችንም የባሕርይ አምላክነቱን ገልጾ ከደቀ መዛሙርቱ ልቡና አጋንንትን የሚያባርርበት ዲያብሎስን ድል የሚነሳበት ስለሆነ ከሌሎች ተራሮች ተመርጧል፡፡

 

2.    ትንቢት ተነግሮለታል

“ታቦር ወአርሞንዔም በስመ ዚአከ ይትፌስሑ ወይሴብሑ ለስምከ” መዝ. 88፥12 ታቦርና አርሞንዔም በስምህ ደስ ይላቸዋል” ብሎ ቅዱስ ዳዊት ከክርስቶስ ሰው ሆኖ መገለጥ በፊት አምላካችን ክርስቶስ ብርሃነ መለኮቱን በደብረ ታቦር እንደሚገልጽ ብርሃኑ ከደብረ ታቦር እስከ አርሞንዔም ድረስ እንደሚታይ ይህም መለኮታዊ ብርሃን በታቦርና በአርሞንዔም ዙሪያ ለነበሩ ሕዝቦች ደስታ እንደሚሆን ተናግሯል፡፡ እንደሚታወቀው ታቦር የተባለው ተራራ ከገሊላ ባሕር በምዕራብ በኩል 10 ኪ. ሜትር ርቆ የሚገኝ ተራራ ሲሆን ተራራው እስከ 572 ሜትር ከባሕር ጠለል/ወለል ከፍ ይላል፡፡ ቀደም ሲል እንደገለጽነው ባርቅ ሲሣራን ድል ነሥቶበታል፤ የመጀመሪያው የእስራኤል ንጉሥ ሳዖል በሳሙኤል እጅ ተቀብቶ ሲመለስ ሦስት ሰዎች ታገኛለህ አንዱ ሦስት የድል ጠቦቶች ሁለተኛው ሦስት ዳቦ ይዟል፤ ሦስተኛውም የወይን ጠጅ አቆማዳ ይዟል፡፡ ሠላምታ ይሰጡሀል ብሎ ሳሙኤል ነግሮት ነበር፡፡ በነገረው መሠረት ሦስት ሰዎችን አግኝቶበታል፡፡ “ከዚያም ደግሞ ወደፊት ትሔዳለህ ወደታቦር ወደትልቁ ዛፍ ትደርሳለህ” 1ሳሙ.10፥3-5፡፡

 

ስለዚህ ተራራ ቅዱስ ዳዊት በድጋሜ እንዲህ በማለት ትንቢት ተናግሮለታል፡፡ “የእግዚአብሔር ተራራ የለመለመ ተራራ ነው፡፡ የጸና ተራራ የለመለመ ተራራ ነው፡፡ እግዚአብሔር ይህን ተራራ ያድርበት ዘንድ ወደደው” መዝ.67፥15 ብሎ እግዚብሔር ብርሃነ መለኮቱን እንደሚገልጥበት ዘምሮአል፡፡ በእነዚህ ከላይ በአየናቸው ሁለት ምክንያት ደብረ ታቦር ለዚህ ተመርጧል፡፡ወንጌላዊያኑ ቅዱስ ማቴዎስና ቅዱስ ማርቆስ ጌታችን ወደ ደብረ ታቦር የወጣው ደቀ መዛሙርቱን በቂሣርያ “ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል” ብሎ በጠየቃቸው በሰባተኛው ቀን ነው ብለው በቅዱስ ወንጌል የጻፉ ሲሆን ቅዱስ ሉቃስ በስምንተኛው ቀን ነው ይላል፡፡ ማቴ.17፥1-8፣ ማር.9፥2-8፣ ሉቃ.9፥28 ነገሩ እንዴት ነው? “እምድኅረ ሰዱስ መዋዕል ነሥኦሙ እግዚእ ኢየሱስ ለጴጥሮስ ወለ ያዕቆብ ወለ ዮሐንስ ዕሁሁ ወአፅረጎሙ ደብረ ነዋኅ እንተ ባህቲቶሙ” ከስድስት ቀን በኋላ ኢየሱስ ጴጥሮስንና ያዕቆብን ወንድሙንም ዮሐንስን ወደ ረጅም ተራራ ብቻቸውን አወጣቸው” ማቴ. 17፥1፣ ማር.9፥2፣ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ነገሩ እንደ ማቴዎስ ነው ብለው በሰባተኛው ቀን መሆኑን በትርጓሜያቸው አስቀምጠዋል፡፡ ታዲያ ስለምን ስምንት አለ? የሚለውን ሲያትቱ /ሲያብራሩ/ ስምንት ያለው ሰባት ሲል ነው ብለው ተርጉመውታል ምክንያቱም አንድ ሳምንት የሚባለው ሰባት ቀን ነው፡፡ ሊቁ ቅዱስ አትናቴዎስ ስለ ዕለተ ሰንበት ሲናገር ኦ ቅድስት ንዒ ኀቤነ ለለሰሙኑ ከመንትፈሣህ ብኪ ለዓለመ ዓለም” ቅድስት ሆይ በየሳምንቱ ወደኛ ነዪ በአንቺ ደስ ይለን ዘንድ ለዘለዓለሙ”  በማለት ሰሙን ማለት ስምንት ማለት ቢሆንም ሊቁ ግን ሳምንት ብሎት ይገኛል፤ ሳምንት ማለት ደግሞ ሰባት ቀን ነው ከዚህ የተነሣ ሉቃስ በሰባተኛው ቀን ያለው በሰባተኛው ሲል ነው፡፡ በሌላ መልኩ ማቴዎስ በሰባተኛው ቀን ሲል ሉቃስ በስምንተኛው ቀን ማለቱ የወጡበትንና የተመለሱበትን ቆጥሮ ነው፡፡ ከዚህ ባለፈ መጽሐፍ የጎደለውን ሞልቶ የሞላውን አትርፎ መናገር ልማዱ ነው ይህንም በሚከተሉት ማየት እንችላለን፡፡

 

ሰሎሞን “ወነበርኩ ውስተ ከርሰ ዕምየ አሠርተ አውርሀ ርጉኦ በደም” ጥበ.7፥2 “በእናቴ ማኅፀን በደም ረግቼ አሥር ወር ነበርኩ ብሏል ይህን ያክል ረጅም ቀን የመጨመር ልማድ ያለው መጽሐፍ በስምንተኛ ቀን ቢል ብዙ የሚደንቅ አይደለም የሚጣረስም አይደለም፡፡ የሚጣረሰው ወይም የሚጋጨው የእኛ አእምሮ ነው ከዕውቀት ማነስ ስለሆነ፡፡

 

ወበጽሐ ወርሀ ለኤልሳቤጥ” የኤልሳቤጥም የመውለጃዋ ወራት ደረሰ ሲል ቀን አልዘረዘረም ሰው የሚወለድበት ቀኑ የታወቀ ስለሆነ ነው፡፡ ሉቃ.1፥57 ስለ እመቤታችንም ሲናገር “በዚያ ሳሉም የመውለጃዋ ወራት ደረሰ የበኩር ልጅዋንም ወለደች” ሉቃ.2፥6 ወራት ሲል ከአንድ በላይ ሁለትም ሦስትም ወራት ይባላሉ አሁን ከዚህ የምናየው መጽሐፍ ጠቅልሎ ሲፈልግ ዘርዝሮ አስፈላጊ ሲሆን በአኀዝ ወስኖ ሲልም ጎድሎ አስፈላጊ ሲሆን ሞልቶ ሊናገር እንደሚችል ያስረዳናል፡፡ “ተፀውረ በከርሣ ፱ተ አውራሀ” ዘጠኝ ወር በማኅፀኗ አደረ” ወደ ማርያም በማኅፀኗ ያደረው ዘጠኝ ወር ከአምስት ቀን ሲሆን አምስት ቀን አጉድሎ ሲናገር እናገኘዋለን ከዚህ አንጻር ሉቃስም አንድ ጨምሮ ነው ስምንት ያለው መጨመር ማጉደል የመጻሕፍት ልማድ ነውና፡፡

 

ጌታችን በደብረ ታቦር ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠው እንዴት ነው?

ይህንን ከማየት አስቀድሞ መገለጡ በምን ምክንያት ነው የሚለውን ማየቱ የተሻለ ነው፡፡ ብርሃነ መለኮቱን የገለጠው በሦስት ምክንያቶች ነው ነሐሴ ሰባት ቀን በቂሳርያ ደቀ መዛሙርቱን “ሰዎች የሰውን ልጅ ማን ይሉታል? ” ብሎ በጠየቃቸው ጊዜ ኤርምያስ ነው፣ ኤልያስ ነው፣ ዮሐንስ መጥምቅ ነው፣ ከነቢያት አንዱ ነው፣ ይሉሀል የሚል የተለያየ መልስ ተሰጥቶት “እናንተስ ማን ትሉኛላችሁ?” ባላቸው ጊዜ ቅዱስ ጴጥሮስ “አንተ ክርስቶስ የሕያው እግዚአብሔር ልጅ ነህ” ብሎ መስክሯል፡፡

 

  1. በፍጡር ቃል የተመሰከረውን በባሕርይ አባቱ ለማስመስከር

  2. ከነቢያት አንዱ ነው ብለውት ነበርና እግዚአ ነቢያት /የነቢያት ጌታ/ እንደሆነ ለማስረዳት

  3. እሞታለሁ እሰቀላለሁ ሲል ጴጥሮስ “ሀሰ ለከ” ልትሞት አይገባህም ብሎት ነበርና እርሱን ስሙት ለማለት፡፡

 

በፍጡር በጴጥሮስ የተመሠከረውን ምስክርነት የባሕርይ አባቱ “ይህ የምወደው ልጄ ነው እርሱን ስሙት” ማለት እሞታለሁ እሰቀላለሁ ቢላችሁ አይገባህም አትበሉት ዓለም የሚድነው በእርሱ ሞት ነውና ተቀበሉት ለማለት ነው፡፡  ለጴጥሮስ መልስ እንዲሆን ይህ ሊሆንብህ አይገባም ብሎት ነበርና ያዕቆብና ዮሐንስም አንዳችን በቀኝህ አንዳችን በግራህ እንሾም ብለው ነበርና ፍቅረ ሲመትን ሊያርቅላቸው የእርሱን የባሕርይ ክብሩን አይተው የመጣለት ዓላማ ልዩ መሆኑን እንዲረዱ እነዚህን ሦስቱን ይዞ ወደ ተራራው ወጥቷል፡፡ ከነቢያት አንዱ ነው ብለውት ነበርና ከነቢያት ሙሴንና ኤልያስን በተራራው ተገኝተው እንዲመሰክሩ አድርጓል፡፡ ሙሴ ምነው የኔን የሙሴን አምላክ÷ አምላከ ሙሴ፣ እግዚአ ሙሴ ይበሉህ እንጂ ማነው ሙሴ የሚልህ፤ ኤልያስም የኔን የኤልያስን አምላክ÷ ኤልያስ የሚልህ ማነው? አምላከ ኤልያስ፣ እግዚአ ኤልያስ ይበሉህ እንጂ በማለት መስክረውለታል እንዴት ነው ምሥጢረ መለኮቱን የገለጠው የሚለውን ለማብራራትም ሆነ ለመተንተን ዕውቀትም ቃላትም ያጥረናል፡፡ ወንጌላውያን መግለጥ በሚችሉት መጠን ከገለጹት ያለፈ ልናብራራው የምንችለው አይደለም፡፡ ማቴዎስ እንዲህ ይገልጸዋል “ወተወለጠ ራዕዩ በቅድሜሆሙ ወአብርሀ ገጹ ከመ ፀሐይ ወአልባሲሆኒ ኮነ ፀአዳ ከመ በረድ” “በፊታቸውም ተለወጠ ፊቱም እንደ ፀሐይ በራ ልብሱም እንደ ብርሃን ነጭ ሆነ” ማቴ.17፥2 ብሎ ወንጌላዊው በዚህ ዓይነት ገለጾ የተናገረው ምሳሌ ስለ አጣለት ነው፡፡ ማርቆስም ይህንኑ ተጋርቶ “ልብሱን አንፀባረቀ አጣቢም በምድር ላይ እንደዚያ ሊያነጣው እስከማይችል በጣም ነጭ ሆነ” ማር.9፥2-4 “የፊቱ መልክ ተለወጠ ልብሱም ተብለጭልጮ ነጭ ሆነ” ሉቃ.9፥29-30፡፡ ከዚህ ወንጌላውያን ከገለጹበት የሚሻል ምሳሌ አናገኝለትም፡፡ በደብረ ታቦር ሐዋርያት ካዩት በተጨማሪ አብ በደመና ሆኖ የምወደው ልጄ ነው እርሱን ስሙት ሲል ተሰምቷል መንፈስ ቅዱስም በአምሳለ ርግብ ታይቶ አንድነት ሦስትነት ተገልጿል፡፡

 

ይህንን ኢትዮጵያዊቷ የቅኔ መምህርት እማሆይ ገላነሽ እንዲህ በማለት በቅኔአቸው ገልጸውታል፡፡

“በታቦርሂ አመቀነፀ መለኮትከ ፈረስ

ኢክህሉ ስሂቦቶ ሙሴ ወኤልያስ”

መለኮት ፈረስ በደብረ ታቦር በዘለለ ጊዜ ሙሴና ኤልያስ ሊስቡት አልቻሉም”

ብለው በምን አይነት ግርማ እንደተገለጸ ተቀኝተዋል፡፡

የደብረ ታቦር ባሕላዊ አመጣጥና ከመንፈሳዊው ሥርዓት ጋር ያለው ተዛምዶ፡-

ብፁዕ አቡነ ጎርጎርዮስ፣ “የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ታሪክ” በሚል ርዕስ ባሳተሙት መጽሐፋቸው የደብረ ታቦር በዓል አከባበርን አስመልክቶ በሀገራችን ያለውን ሥርዓትና የትመጣነት እንደሚከተለው ጽፈውታል፡-

አስቀድመን እንደተመለከትነው ጌታችን በዚህ ዓለም እየተመላለሰ በሚያስተምርበት ጊዜ በደብረ ታቦር ብርሃነ መለኮቱን፣ ክብረ መንግሥቱን መግለጡን በማሰብ በየዓመቱ ነሐሴ 13 ቀን በዓሉ ይከበራል፡፡ ይህ በዓል በኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን በተለይም በምእመናን ዘንድ የተለየ ስም አለው፤ ይኸውም “ቡሄ” የሚለው መጠሪያ ስም ነው፡፡ ቡሄ ማለት /መላጣ ፣ ገላጣ/ ማለት ነው፡፡ በሀገራችን ክረምቱ፣ አፈናው ተወግዶ የብርሃን ወገግታ የሚታይበት በዚሁ በዓል አካባቢ ስለሆነ “ቡሄ” ያሉት ለዚሁ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ድርጊቱ በተፈጸመበት በፍልስጥኤም ግን የደመና መልክ የማይታይበት ፍጹም የበጋ ወራት ነው፡፡ በሀገራችን ሕፃናቱ ይህ በዓል ከመድረሱ በፊት ቀደም አድርገው ጅራፍ ሲገምዱና ሲያጮሁ /ሲያኖጉ/ ይሰነብታሉ፡፡ እናቶችም ለዚህ በዓል የሚሆን ዳቦ ለመጋገር /የሚከበረው በዓል ነውና/ ስንዴያቸውን ሲያጥቡ፣ ሲፈትጉ ይሰነብታሉ፡፡ በዓሉ እንደነገ ሊሆን እንደ ዛሬ በዋዜማው /ነሐሴ 12/ የሠፈር ሕፃናት በየቤቱ እየዞሩ “ቡሄ ቡሄ” እያሉ ይጨፍራሉ፡፡ የሚገጥሙትም ግጥም አላቸው፡፡ “ቡሄ ና ቡሄ በሉ፤ ቡሄ መጣ፣ ያመላጣ ቅቤ ቀቡት እንዳይነጣ” እዚህ ላይ ቡሄ ያሉት ዳቦውን ነው፡፡ በዚህ ጊዜ እናቶች ካዘጋጁት ዳቦ እያነሱ ይሰጧቸዋል፡፡ ሄደው ዳቧቸውን እየገመጡ ሲጋረፉ ይውላሉ፡፡ ለግርፊያው ተምሳሌት ባይገኝለትም የጅራፉ መጮህ የድምፀ መለኮት ፣ጅራፉ ሲጮህ ማስደንገጡ የሐዋርያትን /የጴጥሮስን፣ የያዕቆብንና የዮሐንስን/ በድምፀ መለኮት መደንገጣቸውንና መውደቃቸውን ያስተውላል፡፡

በአንዳንድ ቀበሌዎች የቡሄ ዕለት ማታ ችቦ ያበራሉ፡፡ በደብረ ታቦር ለታየው ብርሃነ መለኮት ምሳሌ ነው፡፡ በዚያውም ላይ በኢትዮጵያችን የፀዓተ ክረምት ዋዜማ ስለሆነ ቡሄን ብርሃን ቢሉት ይስማማዋል፡፡ “ቡሄ ከዋለ የለም ክረምት ዶሮ ከጮኸ የለም ሌሊት” እንዲሉ፡፡ የቡሄ ዕለት ለዘመድ ለአዝማድ ለእያንዳንዱ ቤተሰብ በልጆቹ ልክ ዳቦ ይሰጣል፡፡ በተጨማሪም ለክርስትና ልጅ፣ ለአማች ለምራት፣ የቅርብ ዕውቂያ ላለውም ሁሉ የቡሄ ዳቦ ይሰጣል፡፡ በተማሪ ቤት ደግሞ ተማሪዎች ቀደም አድርገው “ስለደብረ ታቦር” እያሉ እህሉን፣ ጌሾውን ብቅሉን ይለምናሉ፤ ሕዝቡም ባሕሉን ስለሚያውቅ በገፍ ይሰጣቸዋል፡፡ የደብረ ታቦር ዕለት ጠላውን ጠምቀው ቆሎውን ቆልተው ዳቦውን ጋግረው ሊያስቀድሱ የመጡትን ምእመናን ሁሉ ከቅዳሴ በኋላ ይጋብዛሉ፡፡ ይህ እስከ አሁን በትምህርት ቤቶች የሚሠራበት ነባር ትውፊት ነው፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር