ጸሎት (ክፍል 2)

ሚያዚያ 3/2004 ዓ.ም.

በመ/ር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

“አንትሙሰ ሶበት ጸልዩ ስመ ዝበሉ፡፡” ማቴ.6፥

እናንተስ በምትጸልዩበት ጊዜ እንዲህ በላችሁ ጸልዩ “አባታችን ሆይ በሰማያት የምትኖር ስምህ ይቀደስ መንግሥትህ ትምጣ ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነ እንዲሁ በምድር ይሁን….

በዚህ የጸሎት ክፍል ክብር ምስጋና ይግባውና ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ከ81 መጻሕፍት የተገኙ አምስት ቁም ነገሮችን አስተምሯል፡፡

  1. ሃይማኖት

  2. ተስፋ

  3. ፍቅር

  4. ትሕትና

  5. ጸሎት

1.   ሃይማኖት፡- ሃይማኖት ማለት በዐይናችን ያላየነውን አምላክ አባታችን ሆይ ሲሉ መኖር ነው ቀደም ሲል የነበሩ አበው ነቢያት ሲጸልዩ እግዚእነ አምላክነ ንጉሥነ እያሉ ይጸልዩ ነበር፡፡ ይህም ከግብርናተ ዲያብሎስ /ለዲያብሎስ ከመገዛት/ እንዳልዳኑ ለማጠየቅ ነው፡፡ እኛን ግን ከግብርናተ ዲያብሎስ ነጻ አውጥቻችኋለሁ ሲል አባታችን ሆይ ብላችሁ ጸልዩ ብሎ አስተማረን፡፡ “ልጆች እንደመሆናችሁ መጠን እግዚአብሔር አባ አባቴ ብላችሁ የምትጠሩትን የልጁን መንፈስ በልባችሁ አሳደረ” /ገላ.4፥6፣ ሮሜ.8፥15/፡፡ አባትነቱንም በሁለት ነገር ከምድራዊ አባት ለይቶታል፡፡

በመውለድና በመግቦት ከምድራዊ አባት ይለያል፡፡ ምድራዊ አባት በዘር በሩካቤ ይወልዳል፡፡ በማር፣ በወተት፣ በፍትፍት ያሳድጋል፤ ኋላም በሞት ሲያልፍ የምታልፍ ርስትን ያወርሳል፡፡ እርሱ ግን ሲወልደን በርቀት ሲያሳድገንም በሥጋውና በደሙ ነው፡፡ “ከሥጋ የተወለደ ሥጋ ነው፥ ከመንፈስ የተወለደ መንፈስ ነው ዮሐ. 3፥6፡፡ ኋላም የማታልፍ ርስት መንግሥተ ሰማያትን “በክርስቶስ ደግሞ ርስትን ተቀበልን” ኤፌ.1፥11፣ 1ኛጴጥ.3፥5፡፡ በአበው ነቢያት ሐዋርያትን፣ በሐዋርያትም እኛን አቅርቦ አባታችን ሆይ ብለን እንድናመሰግነው አዞናል፡፡

ምድራዊ አባት የሚመግበው እግዚአብሔር ስለሚሰጠው ለልጁ በመስጠት ተቀብሎ በማቀበል ነው፡፡ እርሱ ግን መመገብ የባሕርዩ ስለሆነ ከሌላው ነስቶ አይደለም፡፡ ምድራዊ አባት ሲያጣ አጣሁ ይላል እርሱ ግን አያጣም፡፡ ምድራዊ አባት ሰጥቶ ሲያልቅ አለቀ ይላል፡፡ የእርሱ ግን ስጦታው አያልቅም፡፡ “በሰማያት የማያልቅ መዝገብ የሚሆኑትን የሚያረጁትን ኮረዶች ለራሳችሁ አድርጉ” ሉቃ.12፥33፡፡ ምድራዊ አባት ከትልቁ ልጁ ይልቅ ለትንሹ የደላል እርሱ ግን ዓለምን በእኩል ምግብና ይመግባል፡፡ ምድራዊ አባት ትዕዛዙን ካልተጠበቀለት ልጁን ከቤት ያስወጣል፣ ያባርረዋል እርሱ ግን ሁል ጊዜ በትዕግስት ይመለከተናልና፡፡ “በጻድቃንና ለኀጥአንም ዝናምን ያዘንማልና” ማቴ.5፥45፡፡  እኛ አባትነቱን አምነን አባታችን ሆይ ብንለው እኛ ልጆቹ መሆናችን የልጅነት ሥልጣን እንዳገኘን እንመሰክራለን፡፡ “ለተቀበሉት ሁሉ ግን በስሙ ለሚያምኑት ለእነርሱ የእግዚአብሔር ልጆች ይሆኑ ዘንድ ሥልጣንን ሰጣቸው፡፡ እነርሱም ከእግዚአብሔር ተወለዱ እንጂ ከደም ወይም ከሥጋ ፈቃድ ወይም ከወንድ ፈቃድ አልተወለዱም” እንዲል ዮሐ.1፥12፡፡ “የእግዚአብሔር ልጆች ተብለን ልንጠራ አብ እንዴት ያለውን ፍቅር እንደሰጠን እዩ 1ዮሐ.3፥1፡፡

ከላይ ያየናቸው የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች የሚያስረዱን የእግዚአብሔር ፍቅር ከምድራዊ አባት የተለየ መሆኑን ነው፡፡ ምድራዊ አባት ልጁን ቢወደውም ሥልጣን አይሰጠውም፡፡ እግዚአብሔር ግን ለልጆቹ አጋንንትን እንዲያወጡ ድውያንን እንዲፈውሱ ለምጽ እንዲያነጹ ሙታን እንዲያስነሡ ሥልጣን ሰጥቷል፡፡ “አሥራ ሁለቱን ደቀመዛሙርቱን ወደ እርሱ ጠርቶ እንዲያወጡአቸው በርኩሳን መናፍስት ላይ ደዌንና ሕማምንም ሁሉ እንዲፈውሱ ሥልጣን ሰጣቸው” እንዲል ማቴ.10፥1፡፡

በመኖሪያው /በሰማያት/ በመኖሩ ከምድራዊ አባት ይለያል፡፡ በሰማያት የምትኖር ብሎ በመኖሪያው ከምድራዊ አባት ለይቶታል፡፡ አሁን እግዚአብሔር በምድር የሌለ በሰማይ ብቻ የተወሰነ ሆኖ አይደለም በሰማይም በምድርም የመላ አምላክ ነው፡፡ “ከመንፈስ ወዴት እሔዳለሁ? ከፊትህስ ወዴት እሸሻለሁ? ወደ ሰማይ ብወጣ አንተ በዚያ ነህ ወደጥልቅም ብወርድ በዚያ አለህ፡፡ እንደንስር ክንፍን ብወስድ /ቢኖረኝ/ እስከባሕር መጨረሻም ብበርር በዚያ እጅህ ትመራኛለች፡፡” መዝ.139፥7 በማለት ቅዱስ ዳዊት እግዚአብሔር የሌለበት ቦታ እንደሌለ ገልጿል፡፡

በሰማያት የምትኖር በሉኝ ያለን ብዙ ጊዜ መገለጫው፣ መቀመጫው፣ ለቅዱሳን እርሱ በወደደ እነርሱ በሚችሉት መጠን የተገለጠና የታየ በሰማይ ስለሆነ ነው፡፡

“ንጉሡ ዖዝያን በሞተበት ዓመት እግዚአብሔርን በረጅምና ከፍ ባለ ዙፋን ላይ ተቀመጦ አየሁት የልብሱን ዘርፍ መቅደሱን መልቶት ነበር” ኢሳ.6፥1-6፡፡

“እግዚአብሔር እንዲህ ይላል ሰማይ ዙፋኔ ነው ምድርም የእግሬ መርገጫ ናት” ኢሳ.66፥1፡፡

ኢሳይያስ ምልአቱን፣ ክብሩን፣ ልዕልናውን በአየው መጠን ነገረን፡፡ ይህን የአገልጋዩ የኢሳይያስን ምስክርነት ሳይለውጥ ነቢያት የተናገሩልኝ የስተማሩልኝ፣ የሰበኩልኝ እኔ ነኝ በማለት እነ “ኢሳይያስ ሰማይ ዙፋኔ ነው” ያለውን እንደአስተማሩ እርሱም በሰማያት የምትኖር ብላችሁ አመስግኑኝ አለን፡፡ ስለ ልዕልናው ስለ ክብሩ በሰማይ አለ ይባላል፡፡ “በእንተ ዕበይከ ትትሜሰል በደመናት” እና ትርጓሜ ወንጌል “ስለ ልዕልናህ በደመናት ትመሰላለህ” ከዚህም የተነሣ ጌትችን ሲያስተምር “በሰማያ አትማሉ የእግዚአብሔር ዙፋን ነውና በምድርም አትማሉ የእግሩ መረገጫ ናትና” ማቴ.5፥32 ብሏል፡፡ ቅዱስ እስጢፋኖስ ጌቶችን ኢየሱስ ክርስቶስን በአየው ጊዜ እንዲህ መስክሯል “ወደሰማይ ትኩር ብሎ ሲመለከት የእግዚአብሔርን ክብር ኢየሱስንም በእግዚአብሔር ቀኝ ቆሞ አየና እነሆ ሰማያት ተከፍታው የሰው ልጅም በእግዚአብሔር ቀኝ ቆሞ አያለሁ አለ” ሐዋ.7፥55፡፡

ስለዚህ ብዙ ጊዜ በሰማይ ለወዳጆቹ ከመገለጡ የተነሣ አባታችን ሆይ በሰማያት የምትኖር ብላችሁ አመስግኑኝ አለን፡፡

2.    ተስፋ፡- ተስፋ ማለት የወደፊት አለኝታ እናገኘዋለን ብለን የምንጠብቀው መከራ የምንቀበልለት፣ በዚህ ዓለም ባይመቸን መከራ ቢጸናብን፣ ብንገፋ ብንከፋ ብናዝን ብንጨነቅ ያልፋል ብለን የምንጽናናበት ነው፡፡ ይህን ተስፋ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ብሎ ገልጾታል፡፡ “በእግዚአብሔር ክብርም ተስፋ እንመካለን፡፡ ይህም ብቻ አይደለም ነገር ግን መከራ ትዕግሥትን እንዲያደርግ ትዕግሥትም ፈተናን ፈተናም ተስፋን እንዲያደርግ እያወቅን በመከራችን ደግሞ እንመካለን፡፡ በተሰጠንም በመንፈስ ቅዱስ የእግዚአብሔር ፍቅር በልባችን ስለፈሰሰ ተስፋ አያሳፍርም” ሮሜ.5፥2-5 ተስፋ ከላይ ቅዱስ ጳውሎስ እንደነገረን ሰማዕታት ከነደደ እሳት ገብተው፤ የተሳለ ስዕለትን ታግሰው፤ የዓላውያን ነገሥታትን ግርማ አይተው ሳይደነግጡ፣ ሃይማኖታቸውን ሳይለውጡ፣ ሹመቱን ሽልማቱን ወርቁን ብሩን ምድራዊ ክብራቸውን ትተው መከራ የተቀበሉት ለተስፋ መንግሥተ ሰማያት ነው፡፡ ጻድቃንም ድምጸ አራዊትን ግርማ ሌሊትን ፍትወታት እኩያትን ታግሰው፣ በምናኔ በተባሕትዎ ከዘመድ ባዳ ከሀገር ምድረ በዳ ይሻለናል ብለው የኖሩት ለዚሁ ተስፋ ነው፡፡ ይህንንም ቅዱስ ጴጥሮስ በሃይማኖት ምክንየት ተበትነው ለነበሩ ምዕመናን ሲጽፍ እንዲህ ብሎአል፡፡ “እስመ በእንተ ዝንቱ ተጸዋእክሙ ከመ በረከተ ትረሱ በእንተ ዛቲ ተስፋክሙ” ለዚች ተስፋችሁ መከራን ትቀበሉ ዘንድ ተጠርታችኋልና 1ጴጥ.2፥22 የህ ተስፋ መጻሕፍት የተባበሩበት ነው” በተስፋ ያጽናናልና ነገር ግን ተስፋ የሚደረግበቱ ነገር ቢታይ ተስፋ አይደለም፡፡ የሚያየውንማ ማን ተስፋ ያደርገዋል? የማናየውን ግን ተስፋ ብናደርገው በትዕግስት እንጠባበቃለን” ሮሜ. 8፥24፡፡ ስለዚህ ተስፋ የምንለው የማናየውን መንግሥተ ሰማያትን ነው፡፡ ይህን ተስፋ በጸሎታችን ውስጥ መንግሥትህ ትምጣ ብለን እንድንለምን ጌታችን አስተማረን፡፡ አሁን መንግሥትህ ትምጣ ስንል መንግሥተ ሰማያት ክንፍ ኖሯት በራ፣ እግር ኖሯት ተሽከርክራ የምትመጣ ሆኖ አይደለም ትሰጠን በሉኝ ሲል ተስፋ የምናደርጋት መንግሥትን እንዲያወርሰን ለምኑ አለን፡፡

3.    ፍቅር ፡- ፍቅር ማለት አንዱ ለሌላው መጸለይ ነው፡፡ ይኸውም “የዕለት ምግባችንን ዛሬ ስጠን” የሚለው ነው፡፡ ሰው ሁሉ አባታችን ሆይ የሚለውን ጸሎት ሲጸልይ የዕለት እንጀራዬን ሰጠኝ ብሎ”  አይጸለይም ለጠላቶቹም ለወዳጆቹም ጠቅላላ ሰው ሆኖ የተፈጠረ የተፈጥሪሮ ወንድምና እኅት ሁሉ ነው፡፡ ምክንያቱም ለእገሌ የሚል አደለም፡፡ ጠቅል አድርጎ የዕለት ምግባችንን ስጠን የሚል ነውና፡፡ ይህ ፍቅር ነው ሊቃውንት በትርጓሜያቸው ይህን ሲተረጉሙት ዕለት ዕለት እንድንማር፣ ሥጋውን ደሙን እንድንቀበል፣ ንሰሓ እንድገባ አድርግ ማለት ነው ይላሉ፡፡ ከምግበ ሥጋ ያለፈ ጸሎት ነው፡፡ ይህም ጸሎት ለሕዝቡ ለአሕዛቡ ለጠላት ለወዳጅ ለዘመድ ለባዕድ ሳይባል ለሁሉም የሚጸለይ ጸሎት ሲሆን እግዚአብሔር እኛን እንደወደደን እርስ በእርሳችንም እንዋደድ ዘንድ ተዋደዱ “ጠላቶቻችሁንም ውደዱ ለሚያሳድዷችሁ ጸልዩ” ብሎ አስተምሮኗል፡፡  ለሁሉም የሚሆን የጸሎት ፍቅርን የሚገልጽ ጸሎት “የዕለት ምግባችንን ስጠን” በሉኝ አለን፡፡

4.    ትሕትና፡- ትሕትና ማለት ራስን ዝቅ ማድረግ ማዋረድ ከሁሉ በታች ማድረግ ትዕቢትን ኩራትን ትዝህረትን ማስወገድ ነው፡፡ “ትዕቢትን ግን አታስቡ ራሲን የሚያዋርደውን ሰው ምሰሉ ሮሜ.12፥16፡፡ ይህም “ኀጢአታችንን ይቅርበለን” የሚለው ነው ይህን ጸሎት የበቃውም ያልበቃውም ይጸልየዋል፡፡ የበቃው የነጻው ከኃጢአት አልፎ ከአስረኛው መዓርግ የደረሰው ሁሉ ይጸልየዋል፡፡ ይህንን ሲጸልይ ግን ራሱን ዝቅ አድርጎ ከእኛ መደብ ውስጥ አስገብቶ ኀጢአታችንን ይቅር በለን ይላል፡፡ እርሱ ግን ከኀጢአት አልፎአል ስለትሕትና እኛን መስሎ እንደኛ ሆኖ ይጸልየዋል፡፡ ጌታችን ብዙ ጊዜ ስለትሕትና አስተምሯል፣ “እንግዲህ እንደዚህ ሕፃን ራሱን የሚያዋርድ ሁሉ በመንግሥተ ሰማያት የሚበልጥ እርሱ ነው” ማቴ 18፥4 “ማንም ከእናንተ ታላቅ ሊሆን የሚወድ የእናንተ አገልጋይ ይሁን ከእናንተ ማንም ፊተኛ ሊሆን የሚወድ የእናንተ ባሪያ ይሁን” ማቴ 20፥26-28፡፡

“ራሱን ከፍ የሚያደርግ ሁሉ ይዋረዳል ራሱንም የሚያዋርድ ሁሉ ከፍ ይላል” ማቴ 23፣11 እነዚህና ጌታችን ያስተማራቸውን በተግባር የሚያውሉ ቅዱሳን በቅተው ሳለ እንዳልበቁ ራሳቸውን ዝቅ በማድረግ ይጸልያል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ ከጌታው ከኢየሱስ ክርስቶስ እንደተማረው የትሕትና ጥቅምን ጽፎአል “እንግዲህ በጊዜው ከፍ እንዲያደርጋችሁ ከኀይለኛው ከእግዚአብሔር እጅ በታች ራሳችሁን አዋርዱ” 1ጴጥ 5፥6፡፡ በዚህ ጸሎት ውስጥ ይህ ጠቃሚ የሆነ ጸሎት ተአምኖ ኀጣውእ (ኀጢአትን ማመን) ያለበት በደላችንን ይቅር በለን የሚለው ትሕትና ነው፡፡

5.    ጸሎት ፡- ጸሎት አባታችን ሆይ ብሎ እስከ መጨረሻው ያለው ነው አባችን ሆይ ስምህ ይቀደስ መንግሥት ትምጣ ፈቃድ ይሁንልን ይደረግልን የዕለት እንጀራችንን ስጠን በደላችንን ይቅር በለን ጸሎት ነው ታዲያ ይህን በንባብ አጭር በምሥጢር ጌታ መጻሕፍት ያጠቃለለ ታላቅ ጸሎት አፍ ንባብ ይነዳ ልብ ጓዝ ያስናዳ እንዲሉ አበው ኅሊናን በማባከን ሳይሆን በንቃት፣ በትጋት ሆነን ብንጸልይ እንጠቀማለን፡፡ ስለዚህ ነው ክብር ምሥጋና ይግባውና አባታችን ሆይ ብላችሁ ጸልዩ ያልን፡፡

ጸሎታችን ይቀበልልን፡፡

ጸሎት

መጋቢት 18/2004 ዓ.ም.

በመ/ር ምሥጢረ ሥላሴ ማናየ

ጸሎት ጸለየ፡- ለመነ፣ ጠየቀ አማለደ፣ ማለደ ካለው የግዕዝ ቃል የወጣ ቃል ነው፡፡ ጸሎት ማለት ጠቅለል አድርገን ስንመለከተው ከእግዚአብሔር ጋር መነጋገር እግዚአብሔርን ማመስገን መለመን፣ መጠየቅ፣ መማለድ፣ መማፀን ነው፡፡ “ጸሎት ብሂል ተናግሮ ምስለ እግዚአብሔር፡፡” አባታችን አዳምም ከመላእክት ተምሮ በየሰዓቱ ይጸልይ ያመሰግን ነበር፡፡ ዲያብሎስ በእባብ አድሮ ወደ አዳም በመጣ ጊዜ ጸሎት እያደረገ ስለነበር ዲያብሎስን ድል ነሥቶታል ሔዋንን ግን ሥራ ፈትታ እግሯን ዘርግታ ስለአገኛት ድል ነስቷታል፡፡

ጸሎት ሰማእታት ከነደደ እሳት፣ ከተሳለ ስለት፣ ከአላውያን መኳንንት፣ ከአሕዛብ ነገሥታት ከዲያብሎስ ተንኮል እና ሽንገላ ዲያብሎስ በእነርሱ ላይ ከአጠመደው አሽከላ የዳኑበት ጋሻ ነው፡፡ ኤፌ.6፥10 21 ጸሎት፣ ሰው አሳቡን ለእግዚአብሔር የሚገልጥበት እግዚአብሔርም የሰውን ልመና ተቀብሎ ፈቃዱን የሚፈጽምበት ረቂቅ ምስጢር ነው፡፡

የጸሎት መሠረቱ “ዕሹ ታገኛላችሁ ለምኑ ይሰጣችኋል ደጁ ምቱ ይከፈትላችኋል” የሚለው የጌታችን ትምህርት ነው ማቴ.7፥7

ጸሎት፡- በሦስት ክፍል ይከፈላል

  1. ጸሎተ አኰቴት

  2. ጸሎተ ምህላ

  3. ጸሎተ አስተብቊዖት

  1. ጸሎተ አኰቴት፡- ማለት እግዚአብሔርን ከሁሉም አስቀድሞ ስለተደረገልን ነገር በማመስገን የሚጀመር ጸሎት ነው ይህም ዓይነት ጸሎት የቅዱስ ባስልዮስን የምስጋና ጸሎት የመሰለ ነው፡፡

“ነአኲቶ ለገባሬ ሠናያት ላዕሌነ እግዚአብሔር መሐሪ”

“ለእኛ በጎ ነገርን ያደረገ ይቅርባይ እግዚአብሔር አምላካችንን እናመሰግነዋለን” ይልና ምክንኀያቱን ሲገልጥ ጠብቆናልና፥ አቅርቦናልና፥ ወደ እርሱም ተቀብሎናልና፥ እስከዚችም ሰዓት አድርሶናልና” ይላል፡፡ /ሥርዐተ ቅዳሴ/ ይህ ጸሎት የምስጋና ጸሎት /ጸሎተ አኰቴት/ ይባላል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም ይህንን የምስጋና ጸሎት ለፊልጵስዮስ ክርስቲያኖች ሲጽፍላቸው “ነገር ግን በሁሉ ነገር ጸልዩ ማልዱም እያመሰገናችሁም ልመናችሁን ለእግዚአብሔር ግለጡ” ይላል፡፡ ፊል.4፥6 ዳግመኛም “ስለእናንተ በኢየሱስ ክርስቶስ ከእግዚአብሔር ዘንድ ለእናንተ ስለተሰጣችሁ ጸጋ ዘወትር እግዚአብሔርን አመስግነዋለሁ” 1ቆሮ.1፥4 ብሎ ከመለመን አስቀድሞ እግዚአብሔርን ማመስገን አስፈላጊ መሆኑን አስተምሯል፡፡ በዚህ መሠረት ሰው የተደረገለትን በጎ ነገር ሁሉ በማሰብ ፈጣሪውን ማመስገን ከማመስገንም ቀጥሎ የሚያስፈልገውን ከፈጣሪው መለመን አስፈላጊ ነው፡፡

ከቅዱስ ጳውሎስ የምንማረው ለእኛ ስለተደረገልን ብቻ ማመስገንን አይደለም፤ ሌሎች ስለተደረገላቸውም ማመስገን ተገቢ መሆኑን እንጂ፡፡ “ለእናንተ ስለተሰጣችሁ ጸጋ ዘወትር እግዚአብሔርን አመሰግናለሁ” ሲል ለወገኖቹ ስለተደረገላቸው በጎ ነገር በደስታ ማመስገኑ ነው፡፡ ክርስትና ማለት ለእኔ ብቻ ማለት ሳይሆን ለሌሎችም መኖር፣ ለሌሎች በተደረገው የእግዚአብሔር ስጦታም ደስ መሰኘት ነው፡፡ ይህን የምስጋና ጸሎት /ጸሎተ አኮቴት/ ብዙ አባቶች፣ እናቶች ተጠቅመውበታል፡፡ ለምሳሌም ያህል ዘካርያስንና ኤልሳቤጥን መመልከት እንችላለን፡፡ ቅድስት ኤልሳቤጥ እግዚአብሔር ያደረገላትን በጎ ነገር ስትመሰክር “እግዚአብሔር በዚህ ወራት ከሰው ስድቤን ያርቅ ዘንድ በጎበኘን ጊዜ እንዲህ አደረገልኝ” ብላለች፡፡ ሉቃ.1፥25 እግዚአብሔር ጎበኘኝ ብላ ቸርነቱን አደረገለኝም በማለት የተደረገላትን መልካም ስጦታ ዮሐንስን መጽነሷን ገልጣ አመስግናለች፡፡ ዘካርያስም እንዲሁ አመስግኗል፡፡ “ያን ጊዜም አፉ ተከፈተ አንደበቱም ተናገረ እግዚአብሔርንም አመሰገነ” ሉቃ.1፥65 “ከዚህ ጊዜ ያደረስከኝ፥ ከደዌ የፈወስከኝ፥ ዮሐንስን የሰጠኸኝ ብሎ ፈጣሪውን አመስግኗል በመቀጠልም ይቅር ያለን ለወገኖቹም ድኅነትን ያደረገ የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ይመስገን ከባሪያው ከዳዊት ቤት የምንድንበትን ቀንድ አስነሣልን፡፡” ሉቃ.1፥68 በዘካርያስ ጸሎት ውስጥ ምስጋናውን አስቀድሞ ትንቢቱን አስከትሎ እናገኘዋለን፡፡ በዚህ ምስጋናውና ትንቢቱ አምላክ ለእኛ ያደረገው የቤዛነቱን ሥራ በመግለጥ ሲያመሰግን እንመለከታለን፡፡

2. ጸሎተ ምህላ፡- ጸሎተ ምህላ ስለፈውሰ ሕሙማን …… ስለ ሀገርና ስለነገሥታት ስለ ጳጳሳት፣ ካህናት ዲያቆናት፣ ምዕመናን ሕይወት ቸነፈር፣ ጦርነት፣ ረሀብ፣ ድርቅ ወይም ሌላ አስጊ ነገር በሆነ ጊዜ በብዛት፣ በማኅበር የሚጸለይ ጸሎት ነው፡፡ የምህላ ጸሎት ሲጸለይ በእስራኤል ላይ ቸነፈር በተነሣ ጊዜ አሮን በሽተኞን ባንድ ወገን ጤነኞችን ባንድ ወገን አድርጎ የክህነት ልብሱን ለብሶ ማዕጠንተ ወርቁን ይዞ በራስህ የማልክላቸውን አብርሃምን፣ ይስሐቅን፣ ያዕቆብን አስበህ የወገኖችህን ኀጢአት ይቅር በል”  እንደጸለየላቸው ነው፡፡ ዘኁ.16፥46-50

ዛሬም ካህናት ከጠቀስናቸው አስጊ ነገሮች ማንኛውም በሀገር ላይ ቢመጣ ወደ ሀገር እንዳይገባ ገብቶ ቢሆን ከፍ ያለ ጉዳት እንዳያመጣ የክህነት ልብስ ለብሰው ማዕጠንቱ ይዘው ሥዕለ ማርያም፣ መስቀል አቅርበው ማኅበረ ክርስቲያንን ሰብስበው፣ ኢየሱስ ክርስቶስን “ስለእኛ ከድንግል ማርያም መወለድህን ስለእኛ መሠቀል መሞትህን አስበህ የህዝብን ኀጢአት ይቅር በል ከመዓት ወደ ምሕረት ተመለሰ” እያሉ በምህላ ይጸልያሉ፡፡

የምህላ ጸሎት መአትን መቅሰፍትን ይመልሳል ጦርን፣ ቸነፈርን ያስታግሳል መሠረቱም፡፡
“ጾም ለዩ ምህላ ስበኩ” ያለው ቃል ነው፡፡ ይህ ጸሎት በሰላም ጊዜ ሰላሙ ዘላቂ እንዲሆን በጦርነት ጊዜ ለመከላከያነት ዋና መሣሪያ ነው፡፡ ስለዚህ አጥብቀን ልንከተለው ይገባል፡፡

የምህላ ጸሎት ነገሠታት ከዙፋናቸው ወርደው ወንድ ሙሽራ ሴት ሙሽራ ከጫጉላቸው፣ ከመጋረጃቸው ለምግብ የደረሱ ልጆች ከምግብ ለምግብ ያልደረሱ ከጡት ተከልክለው ሕዝብ ሁሉ ምንጣፍ ለብሰው አመድ ነስንሰው የሚጸልዩት ከፍተኛ ጸሎት ነው ኢዩ.2፥12-18፣ ዮና.3፥5

3.    ጸሎተ አስብቊዖት

ይህ ጸሎት አንድ ሰው ስለሚፈልገው ነገር ቦታ ለይቶ ሱባኤ ገብቶ የሚጸልየው ጸሎት ነው፡፡ ይህ ጸሎት በተለይ ጣዕመ ጸጋን በቀመሱ በተባሕትዎ፣ በምናኔ በገዳም በሚኖሩ አበው ዘንድ የተለመደና የሚደረግ ጸሎት ነው፡፡ ወጣንያን እግዚአብሔርን ጠይቀው አድርግ አታድርግ የሚል መልስን አይጠብቁም፡፡ ፍጹማን አባቶች ግን እግዚአብሔር ጠይቀው አድርግ ወይም አታድርግ የሚል ፈቃደ እግዚአብሔርን ሳይቀበሉ የሚያደርጉት ነገር የለምና ቦታ፣ ጊዜ ወስነው ፈቃደ እግዚአብሔር ይጠይቃሉ፡፡ ይህ ጸሎተ አስተብቊዖት ይባላል፡፡ ይህም ማለት መላልሶ ደጋግሞ ያለ ዕረፍት ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ የሚደረግ ጸሎት ነው፡፡ ለምሳሌ ትልቁ መቃርስ ዓለምን ዞሮ ለመጎብኘት ለተከታታይ አምስት ዓመታት እግዚአብሔርን ከለመነ በኋላ እየዞረ መካነ ቅዱሳንን እንዲጎበኝ ከእግዚአብሔር ፈቃድ አግኝቷል በዚህም ከእርሱ ከገድል በትሩፋት የሚበልጡ መናንያን በማግኘቱ መነኮሳትማ እነርሱ እንጂ እኔ ምንድን ነኝ? እያለ ራሱን እየወቀሰ እንደተመለሰ በመጽሐፈ መነኮሳት ተጽፎ እናገኛለን፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን “መስተበቊዕ” የሚባል የጸሎት ክፍል፡፡ አለ ይህ ጸሎት በካህናት አባቶቻችን ስለሙታን፣ ስለሕያዋን፣ ስለነገሠታት፣ ስለ ጳጳሳት ስለ ንዑሰ ክርስቲያን፣ ስለ ምእመናን መባዕ ስለሚያቀርቡ ስለነጋድያን፣ ስለዝናም ስለ ወንዞች የሚጸለይ ትልቅ ቦታ የሚሰጠው የጸሎት ክፍል ነው፡፡

ጠቅላላውን በቤተ ክርስቲያን የሚጸልዩ ጸሎታት ጸሎተ ፍትሐት፣ ጸሎተ ተክሊል፣ ጸሎተ ህሙማን፣ ጸሎተ ቅዳሴ፣ ጸሎተ ሰዓታት፣ የግል ጸሎት፣ የማኅበር ጸሎት እነዚህ ሁሉ ከላይ ከዘረዘርዓቸው ሦስቱ የጸሎት ክፍሎች አይወጡም፡፡ ከጸሎተ አኰቴት ከጸሎተ ምህላ፣ ከጸሎተ አስተበቊዖት ይመደባሉ፡፡ እነዚህን ጸሎታት በሰቂለ ኅሊና በአንቃዕድዎ /ዐይንን ወደ እግዚአብሔር በማንሳት/ መጸለይ ታላቅ ዋጋ የሚያሰጥ ከሰይጣን ወጥመድ የሚታደግ ሕይወትን የሚስተካከል ከእግዚአብሔር ጋር የሚያስታርቅ አጋንንትን የሚያርቅ ኀይለ እግዚአብሔርን ለሚጸልየው የሚያስታጥቅ መላእክትን የሚያስመስል ነው፡፡

እኛም ሰውነታችን ከበደል ልቡናችን ከቂም ከበቀል እንዲሁም ከተንኮል ንጹሕ አድርገን ብንጸልይ እንጠቀማለን ጸሎታችን ተሰሚ ልመናችንና ጩኸታችን ግዳጅ ፈጻሚ ይሆናል፡፡ የአባቶቻችን ጸሎት የተቀበለ እግዚአብሔር አምላካችን ጸሎታችንን ይቀበለናል፡፡

ይቆየን

ትምህርተ ጦም በሊቃውንት

ሰኔ 24/2003 ዓ.ም.

 በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
 
በዚህ ጽሑፍ ጦምን አስመልክቶ የቅዱሳን አባቶችን አስተምህሮ እንመለከታለን
 
አንድ የገዳም አበምኔት  አንድ ወቅት አባ ጳይመን የሚባሉትን አባት “እግዚአብሔርን መፍራት እንዴት ገንዘቤ ማድረግ ይቻለኛል” ብለው  ይጠይቋቸዋል፡፡ እሳቸውም ሲመልሱ “እንዴት ሰው በላመና በጣፈጠ መብልና መጠጥ ሆዱን እየሞላ እግዚአብሔርን መፍራት ገንዘቡ ሊያደርግ ይችላል? ስለዚህም ጦም እግዚአብሔርን ወደመፍራት ይመራል፡፡ የጦም የመጨረሻ ግቡ እግዚአብሔርን ወደመፍራት ማምጣት  ነው”  ብለው ይመልሱላቸዋል፡፡
 
አንድ ወቅት አንድ ጠዋሚ በጦም ወቅት ማልዶ ይርበዋል፡፡ እናም ከሦስት ሰዓት በፊት ላለመመገብ ከፍላጎቱ ጋር ይሟገታል፡፡ ሦስት ሰዓትም ሲሆን እንደምንም ብሎ እስከ ስድስት ሰዓት ሊቆይ ይወስናል፡፡ ስድስት ሰዓት ደርሶ ሊመገብ ማዕዱን በቆረሰ ጊዜ እንደገና ለራሱ እስከ ዘጠኝ ሰዓት ልቆይ ብሎ በመናገር ምግቡን ከመመገብ ይከለከላል፡፡ ዘጠኝ ሰዓት ላይ ጸሎቱን አድርሶ ሊመገብ ሲል ሰይጣን ልክ እንደጭስ ከሰውነቱ ሲወጣ ታየው ወዲያው ረሃቡ ጠፋ፡፡
 

እየጦምክ ነውን? ለተራበ አብላ ፣ለተጠማም አጠጣ፣ ሕመምተኞችን ጎብኝ፣ የታሰሩትን ጠይቅ፣ በመከራ ላሉት እራራላቸው፣ በጭንቀት ወድቀው የሚያለቅሱትን አጽናናቸው፣ ርኅሩኅ፣ ትሑት፣የዋህ፣ ሰላማዊ፣ አዛኝ፣ይቅር ባይ፣ እውነተኛ እና ታማኝ ሁን፡፡ እንዲህ ከሆንክ እግዚአብሔር ጦምህን ይቀበልልሃል፡፡ ስለንስሐም ብዙ የንስሐ ፍሬን ይሰጥሃል፡፡ ጦም ለነፍስ ምግብ ነው፡፡

 ቁጣ መቼም ቢሆን የሚመከር አይደለም፤በተለይ በጦም ሰዓት ከቁጣ መራቅ ተገቢ ነው፡፡ ትሕትናንና ፣የዋሃትን ገንዘብህ አድርግ፤ክፉ ፈቃዶችንና አሳቦችን ተቃወማቸው፤ ራስህን መርምር በየእለቱ ወይም በሳምንት ውስጥ ምን መልካም እንደሠራህ አእምሮህን ጠይቀው፡፡ እንዲሁም ምን ስሕተትን ፈጽመህ እንደነበርና ስሕተትሕን ደግመህ እንዳትፈጽም የመፍትሔህ እርምጃዎች ምን ሊሆኑ እንዲገባቸው አሰላስል፡፡ ጦምህ እንዲህ ሊሆን ይገባዋልና፡፡

ምግብ ሰውነትን እንደሚያሰባ እንዲሁ ጦም ነፍስን ከሥጋ አስተሳሰብ ተላቃ ወደ ላይ በመነጠቅ ሰማያዊ ነገሮችን ለመመርመርና ከምድራዊ ደስታ ይልቅ እጅግ ግሩም የሆነ ደስታን ለማግኘት ጥንካሬን ይሰጣታል፡፡

 አርባ ቀን ሙሉ ከምግብ ተከልክዬ ጦምኩ አትበለኝ፡፡ ይህንና ያንን አልበላሁም ወይንም ከአፌ አልገባም አትበለኝ፡፡ እኔ ይህንን ካንተ አልሻም፣ ነገር ግን ከቁጣ ርቀህ ታጋሽ መሆንህን አሳየኝ፤ ከጭካኔህ ተመልሰህ አዛኝ ወደመሆን እንደመጣህ አሳየኝ፡፡ ነገር ግን ቁጣ የሞላብህ ከሆነ ስለምን ሥጋህን በጦም በከንቱ ትጎስማታለህ ? ሰዎችን ሁሉ የምትጠላና ስስታም ከሆንክ ለአንተ ከምግብ ተከልክለህ ውሃ ብቻ መጠጣትህ ምን ትርፍ ያመጣልሃል?

ጦም እጅግ ግሩም የሆነ ነገር ነው፡፡ ኃጢአታችንን እንደማይጠቅም አረም ከውስጣችን ይነቅለዋል፡፡  እውነተኛው የጽድቅ ተክልም  በውስጣችን ልክ እንደ አበባ እንዲያብብ ይረዳዋል፡፡ (ቅዱስ ባሲልዮስ)

ጸሎት፣ ጦም ፣ትጋህ ሌሊት እና ሌሎችም አንድ ክርስቲያን የሚተገብራቸው ክርስቲያናዊ ተግባራት ምንም መልካሞች ቢሆኑ የክርስቲያናዊ ሕይወት ግቦች ግን አይደሉም፡፡ ነገር ግን ወደ ትክክለኛው ክርስቲያናዊ ሕይወት ለመድረስ የሚያገለግሉን መንፈሳዊ ትጥቆች ናቸው፡፡ትክክለኛው የክርስቲያን ግብ መንፈስ ቅዱስ በእርሱ ሰውነት ውስጥ ሥራ እንዲሠራ በመፍቀድ የመንፈስ ቅዱስ ፍሬዎችን አፍርቶ መገኘት ነው፡፡በዚህ ምድር የመንፈስ ቅዱስ ፍሬዎች ማፍራት እስካልቻልን ድረስ የእግዚአብሔርን መንግሥት መውረስ አይቻለንም፡፡ (ቅዱስ ሱራፊ)

የአዋጅ ጦም ሲገባ መንፈሳዊ የበጋ ወራቱ እንደገባ ልብ እንበል፡፡ ስለዚህም የጦር መሳሪያችንን እንወለውለው  ከእርሻቸው አዝመራውን የሚሰበሰቡትም ገበሬዎች ማጭዳቸውን ይሳሉ፤ ነጋዴዎችም በከንቱ ገንዘባቸውን ከማባከን ይከልከሉ፣ መንገደኞችም ወደ እግዚአብሔር መንግሥት ለመግባት መንገዳቸውን ያቅኑ፡፡ ወደ እግዚአብሔር መንግሥት የምትወስደው ጎዳና ቀጭንና ጠባብ ናትና በጥንቃቄ እያስተዋላችሁ ተጓዙ፡፡

እንዲያው በልማድ ሰዎች እንደሚፈጽሙት ዓይነት ጦም ትጦሙ ዘንድ አልመክራችሁም፡፡ ነገር ግን ከምግብ ስለምንከለከልባት ጦም ብቻ ሳይሆን ከኃጢአት ስለምንከለከልባት  እውነተኛይቱ ስለሆነችው ጦም እጽፍላችኋለሁ፡፡ ጦም በባሕርይዋ በሕግ ካልተመራች  ለሚተገበሩዋት ሰዎች ዋጋን አታሰጥም፡፡ ስለዚህም ጦምን ለመጦም ስንዘጋጅ የጦም ዘውድ የሆነውን ነገር መዘንጋት የለብንም፡፡ ስለዚህ ስለምን ያ በእግዚአብሔር ቤተመቅደስ ደጅ ሆኖ ጸሎቱን ያደረሰው ፈሪሳዊ ከእግዚአብሔር ዘንድ ስለጦሙ አንዳች ዋጋ ሳያገኝ በባዶው እጁ እንደተመለሰ መረዳት ተቀዳሚ ተግባራችን ሊሆን ይገባዋል (ሉቃ. ፲፰፥፱-፲፬(18፡9-14))፡፡ ቀራጩ አልጦመም ነገር ግን ጸሎቱ ተሰምቶለታል፡፡ ጦም ሌሎች አባሪ የሚሆኑ መልካም ሥራዎች ካልታከሉበት በቀር ልክ እንደዚኛው ፈሪሳዊ ዋጋ አያሰጠንም፡፡

ጦም ማለት መድኃኒት ማለት ናት፡፡ እንደ ሌሎቹ መድኃኒቶች ሁሉ ጦምን እንዴት እንደሚጠቀምበት የሚያውቅ ሰው ዋጋ ያገኝበታል፡፡ በጥበብ ላልተጠቀመበት ሰው ግን የማይረባና የማይጠቅም ይሆንበታል፡፡ ከጦም የሚገኘው ክብር ከምግብ በመከልከላችን ምክንያት የምናገኘው ብቻ አይደለም፡፡ ከኃጢአት ሥራዎችም ፈጽመን በመከልከላችን ምክንያት የምናገኘው ክብር ጭምር ነው ፡፡ ጦም ሰይጣን ወደ እኛ እንዳይቀርብ እንደጋሻ የሚያገልግለን መሣሪያ ነው፡፡ ነገር ግን በጦም ሰዓት ኃጢአትን ፈቅደን የምንሠራት ከሆነ ሰይጣን አጥሩን ጥሶ እንዲገባና በእኛ ላይ እንዲሠለጥን ምክንያት እየሆንነው ነው፡፡ ጦማችን ከምግብ በመከልከል ብቻ የተወሰነ ከሆነ ጦምን እናስነቅፋታለን፡፡

እየጦምክ ነውን ? መጦምህን በሥራህ ገልጠህ አሳየኝ፡፡ ድሃው እርዳታህን ፈልጎ እንደሆነ ቸርነትን አድርግለት፡፡ ጠላት ያደረግኸውን ካየኸው ከእርሱ ጋር ፈጥነህ ታረቅ፡፡ ጓደኛህ ተሳክቶለት ካየኸው በእርሱ ላይ ቅናት አይደርብህ፡፡ አፍህ ብቻ አይጡም ዐይንህም ጆሮህም እግርህም እጅህም የሰውነትህ ሕዋሳቶች ሁሉ ክፉ ከማድረግ ይጡሙ፡፡

እጆችህ ከዝርፊያና ከሕግ ውጪ ለመክበር ሲባል ትርፍን ከማጋበስ ይጡሙ፡፡ እግሮችህ የኃጢአት ሥራን ለመፈፀም ከመፋጠን ይጡሙ፡፡ ዐይኖችህም ውጫዊ በሆነ ውበት ምክንያት ከመቅበዝበዝ ይጡሙ፡፡ የሚታዩ ነገሮች ለዐይን ምግቦች ናቸው፡፡ ነገር ግን ከእግዚአብሔር ሕግ ጋር የሚጣረሱ ምልከታዎች ጦምን ያፈርሳሉ፡፡ነፍስንም እንድትነዋወጥ ያደርጉአታል፡፡ የምናያቸውን ነገሮች ከእግዚአብሔር ሕግ ጋር የሚስማሙ ከሆኑ ጦማችንን ያስጌጡዋታል፡፡ በጦም ምክንያት በጦም ሰዓት መመገብ የተከለከሉትን ምግቦች መመገብ የሚያስነቅፍ ከሆነ ፤ እንዴት ታዲያ በዐይናችን እንድንመለከተው በሕግ የተከለከልነውን ነገር መመልከታችን ይበልጥ አያስነቅፈን ? ምግብን ከመብላት ተከልክለሃልን? እንዲሁ ለሰውነትህ ጎጂ የሆኑ ነገሮችን በዐይንህም በጆሮህም ከመመገብ ተከልከል፡፡ ጆሮ የምትጦመው ለኃጢአት ከሚጋብዙ ክፉ ወሬዎችና ሐሜትን ከመስማት ነው፡፡ “ሐሰተኛ ወሬን አትቀበል ሐሰተኛ ምስክርም ትሆን ዘንድ ከኃጢአተኛ ጋር እጅህን አታንሣ፡፡”እንዲል(ዘጸአ.፳፫፥፩(23፡1))

አፍህም ከከንቱ ንግግር ይጡም ፡፡ ከአሣና በጦም ሰዓት መመገብ ከተከለከልናቸው የፍስክ ምግቦች ተከልክለን ወንድሞቻችንንና እኅቶቻችንን በክፉ ቃላችን ሕሊናቸውን የምናቆስልና በሐሜት ሥጋቸውን የምንበላ ከሆነ ከጦማችን ምን ዋጋን እናገኛለን? ክፉ ተናጋሪ የወንድሙን አካል ያቆስላል ሥጋውንም ይበላል፡፡ ስለዚህም ቅዱስ ጳውሎስ ይህን አስመልክቶ  እጅግ የሚያስደነግጥ ንግግርን ተናገረ “ሕግ ሁሉ በአንድ ቃል ይፈጸማልና እርሱም፡- ባልንጀራህም እንደ ራስህ ውደድ  የሚል ነው፡፡ ነገር ግን እርስ በእርሳችሁ ብትነካከሱና ብትበላሉ እርስ በእርሳችሁ እንዳትጠፋፉ ተጠንቀቁ፡፡(ገላ.፭፥፲፭(5፡15))ብሎ አስጠነቀቀን፡፡

ስለታሙ የሐሜት ጥርስህ የሚያርፈው በወንድምህ ሥጋ ላይ ሳይሆን ነፍስ ላይ ነው፡፡ በዚህም ጥርስህ ወንድምህን በእጅጉ ትጎዳዋለህ፡፡ እንዲህ በማድረግህ አንተም እርሱንም ሌሎችንም ብዙ ሺህ ጊዜ ትጎዳቸዋለህ፡፡ በሐሜትህ አንተን የሚሰማህ ባልንጀራህ የሐሜት ተባባሪ ይሆናል፡፡ በዚህም ምክንያት እርሱንም በደለኛ ታደርገዋለህ፡፡ እርሱም በእርሱ ላይ ከነገሠበት ኃጢአት የተነሣ ለሌላ ለወዳጁ ምን መርጦ ማውራት እንዳለበት ሳያውቅ ከሐሜተኞች ጎራ ይቀላቀላል፡፡እንዲህ ዓይነት ሰው ጻድቅ ልንለው እንችላለንን? እንዲህ ዓይነት ሰው  በመጦሙ ትልቅ የጽድቅ ሥራን እንደፈጸመ ቆጥሮ ይኩራራል፡፡ ሰዎችን ወደ ኃጢአት እየመራ ትልቅ ሥራን እንደሠራ ሰው ራሱን በከንቱ ያስኮፍሳል፡፡ ከዚህ ጎን ለጎን ሊታይ የሚገባው ትልቁ ቁም ነገር ስለቤተክርስቲያን ጥቅም ሲባል የእንዲህ ዓይነቱን ሰው ንግግር ከመስማት መከልከል እንደሚገባ ነው፡፡ ምክንያቱም የዚህ ሐሜተኛ ወሬ እርሱን ብቻ ኃጢአተኛ የሚያሰኝ ጉዳይ ሳይሆን ቤተክርስቲያንንም ጭምር የሚያሰድብ ነውና፡፡

ስለዚህ በጦም ሰዓታችሁ ጊዜም ይሁን አይሁን  ሦስት ነገሮችን በሕሊናችሁ ትይዙ ዘንድ እመክራችኋለሁ፡፡ እነርሱም ክፉ ከመናገር መከልከልን፣ ማንንም ሰው እንደጠላት ከማየት መቆጠብንና እንደልምድ አድርጋችሁ ከያዛችሁት መሐላ ትርቁ ዘንድ እመክራቸኋለሁ፡፡

በአጨዳ ላይ ያለ ገበሬ እህሉን ከእርሻው ላይ በአንዴ እንዳይሰበስብ ነገር ግን ጥቂት በጥቂት እንዲሰበስብ እኛም እነዚህን ምክሮች ተግባራዊ በማድረግ በዚህ የጦም  ወቅት ልንለማመዳቸው እና መልካም ልምዶቻችን ልናደርጋቸው ይገባናል፡፡ እንዲህም በማድረጋችን በቀላሉ መንፈሳዊ ጥበብን ገንዘባችን ማድረግ ይቻለናል፡፡ በዚህም ዓለም ሳለን መልካም ተስፋ ያለውን አዝመራ እናፈራለን፡፡በሚመጣውም ዓለም በክርስቶስ ፊት ያለፍርሃት በደስታ ተሞልተን እንድንቆም ይረዱናል፡፡ ለእግዚአብሔር መንግሥት የሚያበቃንን ጸጋ አግኝተን የክብሩ ወራሾች ያድርገን፤ ለአብ ለወልድ ለመንፈስ ቅዱስ ክብር ምስጋና ይሁን ዛሬም ዘወትርም እስከዘላለሙ አሜን፡፡

 ጦም የጤንነት እናት፣ የፍቅር እኅት፣ የትሕትና ወዳጅ ናት፡፡ ሕመሞች አብዛኛውን ጊዜ ያለቅጥ ከመመገብ የሚመነጩ ናቸው፡፡ (ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ)

ከምግባራት ሁሉ ታላቁ ጸሎት ነው ነገር ግን የእርሱ መሠረቱ ጦም ነው፡፡የምንጦምበት ምክንያት ርኩስ የሆነውን የሰይጣንን መንፈስ በነፍሳችን ውስጥ እንዳያድር ለመጠበቅ ነው፡፡ ሥጋችንን ለጦም ባስገዛነው ጊዜ ነፍሳችን ነፃነትን፤ ጥንካሬን ሰላምን ፣ንጽሕናን እንዲሁም እውቀትን ለመለየት እንድትበቃ ትሆናለች፡፡ (ጻድቁ ዮሐንስ ዘክሮስታንድ)

እውነተኛ ጦዋሚ ራሱን ከክፉ ምግባራት የከለከለ፤ ከንቱ የሆኑ ንግግሮችን ከመናገር የተቆጠበ፣ ሐሰትን የማይናገር፣ ሐሜተኛ ያልሆነ፣ በማንም ላይ የማይፈርድ፣ሽንገላን የማይወድና እኒህንም ከመሰሉ ነገሮች ራሱን የተጠበቀ ፣የማይቆጣ፣ የማይበሳጭ ፣ተንኮለኛ ያልሆነ ፣ ቂመኛ ያልሆነና፣ እነዚህን ከመሳሰሉ ክፋቶች ሁሉ የራቀ ሰው ነው፡፡

ሕሊናህ ኃጢአትን  ከማሰብ ይጡም፡ አእምሮህም ኃጢአትን ከማስታወስ ይከልከል፡፡ ክፉን ከመመኘት ሁሉ ጡም፡፡ ዐይኖችህ ከንቱ የሆኑ ነገሮችን ከመመልከት፣ ጆሮህም ከንቱ ከሆኑ ዘፈኖችና ከሐሜተኞች ሹክሹክታዎች ጠብቅ፡፡ አንደበትህ ከሐሜት፣ በሌላው ላይ ከመፍረድ ፣ከስድብ፣ ከውሸት ፣ከማታለል፣ከሽንገላ ንግግሮች እንዲሁም ከማይጠቅሙና አጸያፊ ከሆኑ  ቃላት ይጡሙ፡፡ እጆችህም ሰውን ከመግደልና የሌላውን ንብረት ከመዝረፍ ይጡሙ፡፡ እግሮችህም ኃጢአትን ለመፈጸም ከመሄድ ይጡሙ፡፡ ከክፉ ተመለስ መልካምንም ፈጽም፡፡ (ቅዱስ ኤፍሬም)

 ጦም ምን እንደሚያደርግ ትመለከታለህን? ሕመምን ይፈውሳል ፣አጋንንትን ያስወጣል፣ ክፉ አሳቦችን ከአእምሮ ያስወግዳቸዋል፣ ልብንም ንጹሕ ያደርጋታል፡፡ አንድ ሰው በክፉ መንፈስ የተያዘ ቢሆን  እንዲህ ዐይነት መንፈስ በጦምና በጸሎት እንደሚወጣ ያስተውል፡፡ ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ “ይህ ዓይነት ግን ከጸሎትና ከጦም በቀር አይወጣም” እንዳለው (ማቴ. ፲፯፥፳፩(17፡21)) (ቅዱስ ቲክሆን)

የአርባ ቀን ጦም የሥጋ ፍትወታትን ይገድላቸዋል፣ቁጣንና ብስጭትን ከሰውነታችን ያስወግዳቸዋል፣  ከሆዳምነት ከሚመነጩ የትኞቹም ነገሮች ሁሉ ነፃ ያወጣናል፡፡ በበጋ ወራት ፀሐይ ከነሙሉ ኃይሉዋ እንድትወጣና ምድርንም በሙቀቱዋ እንደምታግል በላዩዋም የበቀሉ አትክልቶችን እንደምታደርቅ፤ ከሰሜን የሚነፍሰውም ነፋስ የደረቁትን ሳሮች እንደሚጠርጋቸው፤  እንዲሁ በጦም ወቅትም አብዝቶ በመመገብ የበቀሉትን የሥጋ ፍትወታት ይወገዳሉ፡፡ (ቅዱስ አትናቴዎስ)

ቅዱሳን ጠዋሚዎች ጽኑ ወደሆነው የጦም ሥርዓት የገቡት ወዲያው አይደለም፡፡  በጥቂት ምግብ ወደ መጥገብ የመጡት ቀስ በቀስ ነው፡፡ እነዚህ ቅዱሳን ኃጢአትን ፈጽመው አያውቋትም፡፡ ሁልጊዜ ለመልካም ሥራ እንደተፋጠኑ ነው፡፡ በእነርሱ ዘንድ ሕመም አይታወቅም እድሜአቸውም  ከሰው ሁሉ በተለየ የረዘመ ነው፡፡ (ቅዱስ አግናጢዎስ)

ጦም  የሰውን እድሜ አያሳጥርም ፣ ቅዱስ ቄርሎስ ዘአንኮራይት በ108 እድሜው አረፈ፡፡ ቅዱስ እንጦስም 105 ዓመት ሙሉ ኖሮአል፡፡ ቅዱስ መቃርስ ዘእስክንድሪያ የኖረበት እድሜ 100 ዓመት ነበር ፡፡ (ቅዱስ አውግስጢኖስ)

አርባውን ቀን መጦምን ቸል አትበሉ፡፡ ምክንያቱም ክርስቶስን የምንመስልበት ሕይወት ከዚህ ጦም እናገኛለንና፡፡ (ቅዱስ እንጦስ)

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

 

 

አባታችን ሆይ(የመጨረሻው ክፍል)

 ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
አቤቱ ወደፈተና አታግባን÷ ከክፉ አድነን እንጂ÷ መንግሥት ያንተ ናትና÷ ኃይል ክብር ምስጋና ለዘለዓለሙ አሜን።
ግንቦት 19/2003 ዓ.ም.

ጌታችን በዚህ ቃል የእኛን ደካማነት በማሳወቅና መታበያችንን በማጥፋት ፣ ፈተናዎች በእኛ ላይ ከመሠልጠናቸው በፊት  በትሕትና በመገኘት ልናርቃቸው እንደምንችል በግልጽ አስተማረን ፡፡ በዚህ ምክንያት ድላችን እጅግ ታላቅ ይሆናል ፡፡ ሰይጣን ከፊት ይልቅ በታላቅ ፍርሃት ውስጥ ይወድቃል ፡፡ እንዲህ ስል ለጸሎት በእግዚአብሔር ፊት ስንቀርብ በማስተዋል ልንሆን ይገባናል ሲል ነው  ፡፡ ልቡናችንን ሰብስበን መጸለይ ከተሣነን ግን ዝም ማለትን በመምረጥ የፈተናው ጊዜ እስኪያልፍ ድረስ በትዕግሥት ልንጠባበቀው ይገባናል ፡፡  እንዲህ ካደረግን ከከንቱ ውዳሴና ከትዕቢት ነጻ እንደወጣን ማስተዋል ይቻለናል ፡፡

በዚህ ቦታ ሰይጣንን “ክፉ” እንዳለው እናስተውላለን ፡፡ በዚህም ያለ ዕረፍት እኛን ለመጣል በሚፋጠነው ሰይጣን ላይ ጦርነትን ልንከፍት እንዲገባን አሳሰበን ፡፡ ነገር ግን ሰይጣን ክፉ ሲባል ከፍጥረቱ ክፉ ሆኖ የተፈጠረ ነበር ማለቱ ግን አይደለም ፡፡ በተፈጥሮ ክፉ ሆኖ የተፈጠረ ፍጥረት የለም “ብርሃን ከሌለ ጨለማ እንደሚሆን ደግ ሥራ ከሌለ ክፉ ሥራ ይነግሳልና፡፡ ነገር ግን  እኛው ነን ክፋትን  በፈቃዳችን ከተፈጥሮአችን ጋር የምንደባልቀው ፡፡ ስለዚህም እኛን በኃጢአት ስላሰናከለን ቅድመ ጠላታችን ተባለ ፡፡ እንዲሁም ያለ አንዳች ምክንያት እኛ ላይ ጦርነትን በመክፈቱ ጠላታችን ተሰኝቶአል ፡፡ ስለዚህም “ ከፈተና አድነን” ብለን እንድንጸልይ ሳይሆን “ከክፉ አድነን አንጂ” ብለን እንድንጸልይ አዘዘን ፡፡ እንዲህም ሲል በወዳጆቻችን ክፉ ሥራ ደስ ባንሰኝም ፤ በእነርሱ እጅ ማንኛውንም በደል ብንቀበል ፤ ለክፋታቸው  ምክንያት እርሱ ነውና  እነርሱን ጠላት ከማድረግ ተቆጥበን  ጠላትነታችንን በሰይጣን ላይ ሊሆን ይገባል ፡፡

ወደ ፈተና እንዳንገባ ጠላታችን ማን እንደሆነ ለይቶ በመጠቆም ፣ በእርሱ ተግባር እንድናዝን በማድረግ ፣ ባለማስተዋል የምንፈጽማቸውን ክፉ ተግባራትን ከእኛ ቆርጦ በመጣል ፣ እንዲሁም መንፈሳችንን በማነቃቃትና በማትጋት የጽድቅ ዕቃ ጦርን የሚያስታጥቀን ንጉሥ ማን እንደሆነ በማስታወስ እንዲሁም እርሱ ከሁሉ በላይ ኃያል እንደሆነ በማመልከት “መንግሥት የአንተ ናትና ኃይል ክብር ምስጋና ለዘለዓለሙ አሜን” እንድንል አዘዘን ፡፡

እናም በእርሱ ታምነን ያዘዘንንም ወደ ተግባር መልሰን ለመፈጸም እንትጋ ፡፡ እርሱ ንጉሣችን ከሆነ ማንንም ልንፈራ አይገባንም ፡፡ ጌትነቱን ማንም ሊቃወምና ሊያጠፋ የሚችለው የለም ፡፡ አርሱ  “መንግሥት የአንተ ናትና” ሲለን እኛን የሚዋጋውን ለጊዜው ፣ እግዚአብሔርን የሚቋቋም የሚመስለውን ሰይጣንን ለእኛ እንዲገዛ አሳልፎ እንደሚሰጠን ሲያመላክተን ነው ፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ እርሱ ከእግዚአብሔር ባሪያዎች አንዱ ነው ፤ ምንም እንኳ ከተዋረዱትና ለመተላለፋችን ምክንያት ከሆኑት ወገን ቢሆንም ፡፡ እርሱ ከላይ ከእግዚአብሔር ዘንድ ፈቃድ ካላገኘ በቀር በእግዚአብሔር ባሮች ላይ የማደር መብቱ የለውም ፡፡ ስለምን  እኔ “ በባሮቹ ላይ” ለምን እላለሁ ፣ በእሪያዎች ላይ ስንኳ በማደር እነርሱን አስቻኩሎና አጣድፎ ለማጥፋት ሰይጣን ከእግዚአብሔር ፈቃድን መቀበል የግድ አለበት (ማቴ.7፥31) በእንስሳት መንጋ ላይ ከላይ ያለው እርሱ ካልፈቀደለት በቀር ከቶ ሊያድር አይቻለውም ፡፡

“ኃይል” አለ ፡፡ ስለዚህም ድክመቶችህ እጅግ ብዙ ቢሆኑም ያለሥጋት በድፍረት ለመቆም እንድትችል ሁሉን በቀላሉ መፈጸም  የሚቻለው እርሱ በአንተ ላይ መንገሡን አሳወቀህ ፡፡ በአንተም ሥራውን መከወን ለእርሱ አይሳነውም  ፡፡

“ክብር ምስጋና ለዘለዓለሙ አሜን”  በዚህ ወደ አንተ ከቀረቡ መከራዎች ሁሉ ነጻ ሊያወጣህ እንደሚችል ብቻ አልገለጸልህም ፡፡ ነገር ግን አንተን ማክበርና ማላቅ እንደሚቻለው አሳወቀህ ፡፡ የእርሱ ኃይል እጅግ ታላቅ እንደመሆኑ መጠን እንዲሁ ክብሩም እንዲሁ በቃላት ሊገለጽ የማይችል እጅግ ታላቅ ነው ፡፡ ለእርሱ የሆኑ ጸጋዎች ሁሉ ወሰን አልባና ፍጻሜ የሌላቸው ናቸው ፡፡  እርሱ ኃይሉ ታላቅ ክብሩም በቃላት ሊነገር የማይችል ፣ ወሰን አልባዎች እንዲሁም ፍጻሜ የሌላቸው ናቸው ፡፡ ድል አድራጊው እርሱ የእርሱ የሆኑትን እንዴት ባለ ክብር እንደሚያከብራቸውና ፍጹም በሆነ በራስ መተማመን እንዲሞሉ እንደሚያደርጋቸው ታስተውላለህን ?

ስለዚህም አስቀድሜ  ለማብራራትም እንደሞከርኩት በእርሱ ዘንድ  የተጠላውንና የማይወደደውን ቂምና ጥላቻን ከልባችን አስወግደን  ከንቱዎች ከሆኑት ከእነዚህ  ክፉ ጠባያት ርቀን በሁሉ ዘንድ መልካም የሆነውን መፈጸም እንዲገባን አበክሮ ሲያሳስበን ፣ እንዴት መጸለይ እንዳለብን ካስተማረን በኋላ በድጋሚ መልካም የሆነው ምግባር ምን እንደሆነ ያስታውሳል ፡፡ ስለዚህም ይህን ብንፈጽም በእኛ ላይ የሚመጣብንን ቅጣትና በብድራት የምንቀበለውን በመጠቆም ሰሚዎቹ ቃሉን አክብረው መታዘዝ እንዲሻላቸው ማሳሳቡን እንመለከታለን ፡፡

“ለሰዎች ኃጢአታቸውን ይቅር ብትሉ” ካለ በኋላ “የሰማዩ አባታችሁ እናንተን ደግሞ ይቅር ይላችኋልና ፣ ለሰዎች ግን ኃጢአታቸውን ይቅር ባትሉ አባታችሁም ይቅር አይላችሁም” (ማቴ.6፥14) አለን ፡፡

በዚህም ኃይለ ቃል “ሰማይ”ና “አባት” የሚለውን ቃል በድጋሜ መጠቀሙን እናስተውላለን ፡፡ ይህም ሰሚዎቹ ትሕትናን ገንዘባቸው እንዲያደርጉ ለመርዳት ነው ፡፡ በዚህ ቃል አስቀድመው እንደ አውሬ ክፉ ምግባር ይመላለስ የነበረው ሕዝብ እርሱን የመሰለ አባት ማግኘቱንና ከተራና ከተናቀ ምድራዊ አስተሳሰብ አውጥቶ በሰማያት መኖሪያውን እንዳደረገለት ሊያሳየው እንዲህ አለው ፡፡ ይህን ሲፈጽምልን በጸጋው እንዳው በከንቱ ሳይሆን እኛም የእርሱ ልጆች እንባል ዘንድ የእኛም ሥራ እንደሚያስፈልግ ሲያስታውሰን አይደለምን ?  እግዚአብሔርን ለመምሰል የበደሉንንና በእኛ ላይ ክፋት የፈጸሙትን ይቅር ከማለት በቀር የበለጠ ነገር የለም ፡፡ እርሱም አስቀድሞ “እርሱ በክፉዎችና በበጎዎች ላይ ፀሐይን ያወጣል” በማለት በእርግጥ ስለዚህ አስተምሮናል ፡፡

ይህም እንዲሆን ፈቃዱ እንደሆነ ሊያሳየን በእያንዳንዱ ኃይለ ቃል ላይ  “አባታችን ሆይ” “ፈቃድህ በሰማያት እንደሆነች እንዲሁም በምድር ትሁን” “የዕለት እንጀራችንን ስጠን ዛሬ” “በደላችንን ይቅር በለን” “ ወደፈተና አታግባን” “ከክፉ አድነን እንጂ” በማለት የጋራ ጸሎት እንድንጸልይ ማዘዙን እናስተውላለን ፡፡ በወንድሞቻችን ላይ እንዳንቆጣና በእነርሱ ላይ በጠብ ከመነሣሣት እንድንቆጠብ ሲል  በእያንዳንዱ የጸሎታችን ክፍል ላይ እነዚህን የብዙ ቁጥር ግሶችን እንድንጠቀም አዞናል ፡፡

ከዚህ ሁሉ ማሳሰቢያ በኋላ የበደሏቸውን ይቅር ከማለት እንቢ ብለው እግዚአብሔር ተበቅሎ እንዲያጠፋላቸው የሚለምኑት በእጥፍ ሕጉን በመተላለፋቸው እንዴት የባሰ ቅጣት አይጠብቃቸው ይሆን !  እርሱ እግዚአብሔር ሁሉን እንዲህ አስማምቶ መፍጠሩ አንዱን ከአንዱ እንዳይለያይ በመሻቱ አይደለምን ? ለመልካም ነገር ሁሉ ፍቅር መሠረት ነው ፡፡ እርሱ ፍቅርን የሚያፈርሱ ነገሮችን ሁሉ ከእያቅጣጫው እንዲወገዱ ያደርጋቸዋል ፡፡ ሁላችንንም ወደ አንድ በማምጣት ፍቅርን እንደሲሚንቶ በመጠቀም እርስ በእርሳችን እንድንያያዝ ነው የፈጠረን ፡፡ አባትም ይሁን እናት ጓደኛም ይሁን ሌላ እንደ ፈጣሪያችን እግዚአብሔር እኛን የሚወደን የለም ፡፡ ከዚህ በላይ በተጠቀሱት ሁሉ እርሱ እግዚአብሔር  በየቀኑ ለእኛ የሚያደርገውን መግቦትና የእርሱን ሥርዓት ወዳድነት አሳይቶናል ፡፡ ነገር ግን ስለ ሕመሞቻችሁና ስለኀዘኖቻችሁ እንዲሁም በሕይወታችሁ ዘመን ስለገጠሟችሁ መከራዎች የምትነግሩኝ ከሆነ በየቀኑ እናንተ እርሱን ምን ያህል ጊዜ በክፉ ሥራችሁ እንደምታሳዝኑት ልብ በሉ ፡፡ ከዚህ በኋላ በደረሰባችሁ መከራ ሁሉ መገረምና መደነቃችሁን ታቆማላችሁ ፡፡ ነገር ግን በየቀኑ ስለምንፈጽማቸው ኃጢአቶች ምክንያት በእኛ ላይ ስለመጣው ከፉ ነገር ሁሉ ልብ የማንል ከሆነ ግራ መጋባት ውስጥ ልንገባ እንችላለን ፡፡ በቀን ውስጥ ብቻ የምንፈጽማቸውን በደሎች በጥንቃቄ ብንመረምራቸው ስለመተላለፋችን እንዴት ያለ ታላቅ ቅጣት ሊታዘዝብን እንዲገባ መገንዘብ እንችላለን ፡፡              

ስለዚህም በቀን ውስጥ የፈጸምናቸውን በደሎች አንዱ ለአንዱ በመናዘዝ ፣ በደላችንን በማሰብ  የበደሉንን ይቅር ልንል ይገባናል ፡፡ በእርግጥ እያንዳንዳችን ምን በደል እንደበደልን ማወቅ ባንችልም ፣ በደሎቻችን እጅግ የበዙ መሆናቸውን መገንዘብ እችላለሁ ፡፡ ከእነዚህ ከፈጸምናቸው በደሎች መካከል ከእኛ መካከል አንዱ  የሚያውቃቸው ቢሆን እንኳን ከእነዚህ መካከል አንዱን መምረጥ ይሳነዋል ፡፡ ለምሳሌ ፡- ከእኛ በጸሎቱ ቸልተኞች አይደለንምን ? ከእኛ መካከል በትዕቢት ተሞልቶና ከንቱ ውዳሴን ሽቶ የሚጸልይ የለምን ?  ወንድሙን በክፉ የማይናገረው፣ ክፉውን የማይመኝ ፣ ወገኑን በንቀት ዐይን የማይመለከተው ፣ልብን የሚያቆስል ግፍን ቢፈጽምበት እንኳን የወንድሙን መተላለፍ ይቅር የሚል አለን ?

ነገር ግን እኛ በቤተክርስቲያን ለአጭር ጊዜ በቆየንባት ሰዓት ውስጥ እጅግ ታላቅ ክፋትን እንፈጽማለን ፡፡ ከቤተክርስቲያን ወጥተን ወደ ቤት ስንመለስ ምን ያህል የከፉ በደሎችን እንፈጽም ይሆን ? በወደቡዋ (በቤተክርስቲያን) ታላቅ የሆነ ወጀብ ካለ ወደ ኃጢአት መተላለፊያው ባሕር ስናመራ ማለትም ወደ ገበያ ሥፍራ ወሬዎች ፣ወደ የቤቶቻችን ስንመለስ በሥጋ ምቾቶቻችን ተስበን የከፉ ኃጢአቶቻችን እንዴት አንፈጽም ይሆን ?

ነገር ግን እግዚአብሔር ከእነዚህ ሁሉ መተላለፎቻችን እንድንድን ያለምንም ድካም አጭርና ቀላል መንገድን ሠርቶልናል ፡፡ የበደለንን ይቅር ማለት ምን ዐይነት ድካም አለው ?  ይቅር ለማለት ምንም ዐይነት ድካም የለውም ፤ ነገር ግን እርስ በእርሳችን በጠላትነት ተፋጠን እንገኛለን ፡፡ በውስጣችን ከተቀጣጠለው ቁጣ ለመዳንና መጽናናትን ለማግኘት ፈቃዳችን ብቻ በቂ ነው ፡፡ ይቅርታ ለማድረግ ባሕር ማቋረጥ ፣ ረጅም መንገድ መጓዝ ፣ ወይም ተራራን መቧጠጥ ወይም ብዙ ገንዘብ ማጥፋት ወይም ሥጋችንን ማጎሳቆል አያስፈልገንም ፤ ነገር ግን ፈቃደኛ መሆን ብቻ በቂ ነው ፡፡ እንዲህ ከሆነ ኃጢአታችን ሁሉ አንድ ሳይቀር ይወገድልናል ፡፡

ነገር ግን እርሱን ወንድምህን ይቅር ማለት ትተህ እርሱ እግዚአብሔር ያጠፋልህ ዘንድ የምትለማመን ከሆነ ፣ ምን ዐይነት የመዳን ተስፋ ሊኖርህ ይችላል? አስቀድመህ ከእግዚአብሔር ጋር በፈቃድ አልተስማማህም ፤ ከዚህ አልፈህ የጠላትህን ጥፋት በመጠየቅህ ምክንያት እግዚአብሔርን  ታስቆጣለህን ? እርሱን ትለማመነው ዘንድ የኀዘን ማቅን ደርበሃል ፤ ነገር ግን የአውሬ ጩኸት ወደ እርሱ እየጮኽ በኃጥእ ላይ የሚመዘዙትን የጥፋት ፍላጻዎችን በራስ ላይ ታመጣለህን? ስለዚህም ቅዱስ ጳውሎስ ስለጸሎት ሥርዓት ባስተማረበት ወቅት ከበቀል ነጽተን ጸሎታችንን ማቅረብ እንዲገባን “… በስፍራ ሁሉ አለቁጣና አለክፉ አሳብ የተቀደሱትን እጆች እያነሡ እንዲጸልዩ እፈቅዳለሁ ፡፡” ብሎ አስተምሮናል ፡፡ (1ኛ ጢሞ.2፥20) አንተ ምሕረትን ለራስህ የምትሻ ከሆነ ከቁጣ መቆጠብ ብቻውን ለአንተ በቂ አይደለም ፤ ነገር ግን ለዚህ ነገርም እጅግ አስተዋይ ልትሆን ይጠበቅብሃል ፡፡ አንተ በራስ ፈቃድ ራስህ ላይ የጥፋት ሰይፍን የምትመዝ መሆንህን ከተረዳህ ለአንተ መሐሪ ከመሆንህና የክፋት መርዝ የሆነውን ቁጣ ከሰውነት ከማስወገድ የበለጠ ለአንተ ምን የሚቀልህ ነገር አለ?

•    ነገር ግን ይቅር ባለማለትህ በአንተ ላይ ሊመጣ የሚችለውን የእግዚአብሔርን ቁጣ ያላስተዋልክ እንደሆነ አንድ ምሳሌ ልስጥህ፡፡ አንድ ወቅት በሰዎች መካከል ጠብ ይነሣና እርስ በእርሳቸው ክፉኛ ይነቃቀፋሉ፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ አንድ ሰው ከአንተ ምሕረትን ያገኝ ዘንድ ከእግርህ ሥር ወድቆ ይለማመንሃል፡፡ ነገር ግን የእርሱ ጠላት የሆነው መጥቶ አንተን እየተለማመነህ ያለውን ሰው ከወደቀበት መደብደብ ቢጀምር አንተ ከበደለህ ሰው ይልቅ አንተን የሚለማመንህን በሚመታው ሰው ላይ ይበልጥ አትቆጣምን? እንዲሁ የጠላቱን ጥፋት የሚለምን ሰው እግዚአብሔርን እንዲህ እንዲያስቆጣው ተረዳ ፡፡ አንተም እግዚአብሔርን ስለመተላለፍህ እየተለማመጥከው ሳለ ድንገት ልመናህን ከመሃል አቋርጠህ በቃልህ ጅራፍ ጠላትህን ልትገርፈው ብትጀምርና እግዚአብሔር ለአንተ የሠራልህን ሕግ ብታቃልል ፣ አንተን የበደሉህን ሰዎች ሁሉ በደል ትተህ ከቁጣ እንድትርቅ ያዘዘህን አምላክህን እርሱ ከአዘዘህ ትዕዛዛት ወጥቶ በተቃራኒው በአንተ ላይ ቁጣው እንደሚነድ አታደርገውምን? እግዚአብሔር አንተን ተበቅሎ ለማጥፋት የገዛ ኃጢአትህ በቂው ነው፡፡  ነገር ግን  በዚህ ተግባርህ ይህን እንዲፈጽምብህ እርሱን ታነሣሣዋለህን? ምንድን ነው? እርሱ ለአንተ የሰጠውን ትዕዛዝ ይዘነጋዋልን? እርሱ ሁሉን የሚያውቅ እግዚአብሔር ነው፡፡ እርሱ ሕግጋቶቹ ሁሉ በፍጹም ጥንቃቄ ይፈጸሙ ዘንድ የሚሻ እግዚአብሔር ነው፡፡ ከአንተ እንደሚጠብቀው አድርገህ ሕግጋቶቹን ከመፈጸም ርቀህ እንደፈቃድህ በጥላቻና ሕግጋቶቹን  የምትጥሳቸው ከሆነ እጅግ የከፋ ቅጣት እንደሚጠብቅህ በአርግጥ እወቅ፡፡ አጥብቆ ትጠብቀው ዘንድ ያዘዘህን ትእዛዝ ካቃለልክ በኋላ ከእርሱ ዘንድ ምን በጎነትን አገኛለሁ ብለህ ትጠብቃለህ?

ከዚህም አልፈው እጅግ ቆሻሻ ወደ ሆነው ወደዚህ ምግባር የሚመለሱ ግን አሉ፡፡ እነዚህ ወገኖች ለጠላቶቻቸው ጥፋትን የሚለምኑ ብቻ አይደሉም፤ የገዛ ልጆቻቸውን በመርገም የገዛ ሥጋቸውን የሚያጠፉ ወይም ከእርሱ የሚመገቡ ናቸው፡፡ በጥርሶቼ የልጄን ሥጋ መች በላሁ ብለህ አትንገረኝ፡፡ ይህንን በእርግጥ አድርገኸዋል፡፡ ከእግዚአብሔር ቁጣ ወጥቶ በልጅህ ላይ እንዲወድቅና ለዘለዓለማዊ ቅጣት ተላልፎ እንዲሰጥ እንዲሁም ከነቤተሰቡ ተነቃለቅሎ እንዲጠፋ ከመለመን የበለጠ ምን አስከፊ የሆነ ጸሎት አለ?

ለምን እንዲህ ይሆናል ፡፡ከዚህስ የከፋ ጭካኔ ምን አለ ? እንዲህ በክፋት ተጨማልቀህ በልቡናህ ውስጥ ይህን ክፉ መርዝ አስቀምጠህ እንዴት ከቅዱስ ሥጋው ልትቀበል ትቀርባለህ ? የጌታንስ ደም እንዴት ትቀበላለህ ? አንተ “ ሥጋውን በሰይፍ ከፋፍለህ ቤቱንም ገልብጠህ አጥፋው ፣ ያለውን ሁሉ እንዳልነበር አድርገህ አጥፋቸው” የምትል ፣ እልፍ ጊዜ ሞትን እንዲሞት የምትለማመን አንተ ሰው ሆይ ፣ አንተ ከነፍሰ ገዳዮች ፈጽሞ የምትለይ አይደለህም? ወይም ሰዎችን እንደሚመገብ እንደክፉ አውሬ ነህ ፡፡

ስለዚህ ከዚህ ክፉ ሕመምና እብደት ራሳችንን እንጠብቅ ፡፡ እርሱ እንዳዘዘን እኛን ለሚያሳዝኑን ርኅራኄን በማሳየት “የሰማዩ አባታችንን”  እንምሰለው ፡፡ የገዛ ኃጢአታችንን በማሰብ ከዚህ ክፋት እንመለስ ፡፡ በቤታችንም  ከቤታችንም  ውጭ በገበያ ቦታ ፣ በቤተክርስቲያን የምፈንጽመውን ኃጢአት በጥንቃቄ በመመርመር ከዚህ ክፋት እንራቅ ፡፡

ለዚህ ትእዛዝ ተገቢውን ትኩረት ካለመስጠት የተነሣ ካልሆነ በቀር ለከፋ ቅጣት የሚዳርገን ሌላ ትእዛዝ የለም ፡፡ ነቢያት ሲዘምሩ ፣ ሐዋርያት በመንፈሳዊ ቅኔ ሲቀኙ ፣ እግዚአብሔርም ሲያስተምር  እኛ ግን በዓለም ተጣብቀን እንባክናለን፡፡ ራሳችንን በምድራዊ ነገሮች አሳውረናል ፡፡ በተዋንያን መድረክ ላይ የሚነበበውን የንጉሥ ደብዳቤ ለመስማት በጸጥታ እንድንቆም የእግዚአብሔርን ሕግ በጸጥታ ለመስማት አንተጋም ፡፡  በዚያ የንጉሡ ደብዳቤ ሲነበብ አማካሪዎች፣ ገዢዎች የመንግሥት ልዑካኑና ሕዝቡ ሁሉ ቃሉን ለመስማት  ይቆማል ፡፡ በዚያ ጸጥታ ውስጥ አንድ ሰው ቢንቀሳቀስና ጩኸት ቢያሰማ ንጉሡን እንዳቃለሉ ተቆጥሮበት ከባድ ቅጣትን ይቀበላል ፡፡  በዚህ ግን ሰማያዊ ደብዳቤ በተነበበ ጊዜ በሁሉ አቅጣጫ ታላቅ የሆነ ሁከት ይቀሰቀሳል ፡፡ ነገር ግን ደብዳቤውን የላከው ንጉሥ ከዚህኛው ምድራዊ ንጉሥ እጅግ የሚልቅ ነበር ፡፡ ታዳሚዎቹም የተከበሩ ናቸው ፡፡ ሰዎች ብቻ አይደሉም የሚገኙበት መላእክት ፣ ሊቃነ መላእክት የሰማይ ሠራዊቶች ሁሉ ይገኙበታል ፡፡ አኛም በምድር ያለነው ምስጋናን እናቀርብ ዘንድ ከጉባኤው ታድመናል ፡፡ “ሥራዎቹ ሁሉ እግዚአብሔርን ያመሰግኑታል” ተብሎ እንደተጻፈ ፡፡ አዎን እርሱ ለእኛ የፈጸማቸው ሥራዎቹ ከቃላት ፣ እኛ ከምናስበውና ከምንረዳው በላይ ናቸው ፡፡

ይህን ጉዳይ ነቢያት ሁል ጊዜ የሚያውጁት ነው፡፡ እያንዳንዳቸው በተለያየ መንገድ ይህን የእግዚአብሔርን ድል አድራጊነት ለእኛ ጽፈውልናል፡፡ ንጉሥ ዳዊት “ወደ ላይ ዓረግህ ፣ ምርኮን ማረክህ ስጦታህን ለሰዎች ሰጠህ”(መዝ.67፥18) እንዲሁም  “እግዚአብሔር ነው በሰልፍ ኃያል”(መዝ.23፥8)  ሌላውም ነቢይ “የኃይለኛውን ምርኮ ይበዘብዛል” ብሎአል ፡፡ የተማረኩትን ሊያስለቅቅ፣ ለእውራን ብርሃንን ሊሰጥ÷ ለሃንካሳን ምርኩዝ ሊሆናቸው ነው ጌታችን ወደዚህ ምድር መምጣቱ ፡፡

 ሌላው ደግሞ በሞት ላይ ያገኘነውን ድል አሰምቶ በመናገር እንዲህ ይላል “ ሞት ሆይ መውጊያህ የት አለ? ሞት ሆይ ድል መንሣትህ የታለ? (ኢሳ.25፥8) በሌላ ቦታ ደግሞ ሰላምን ስለሚሰጠን ስለምሥራቹ ቃል  ሲመሰክር “ሰይፋቸውንም ማረሻ ፣ ጦራቸውንም ማጭድ ለማድረግ ይቀጠቅጣሉ”(ኢሳ.4፥4) ሲል ፤ ሌላኛው ነቢይ ደግሞ  ኢየሩሳሌምን እየተጣራ  “አንቺ የጽዮን ልጅ ሆይ እጅግ ደስ ይበለሽ አንቺ የኢየሩሳሌም ልጅ ሆይ እልል በዪ አነሆ ንጉሥሽ ጻድቅና አዳኝ ነው ፡፡ ትሑትም ሆኖ በአህያም በአህያይቱ ግልገል በውርንጫይቱ ላይ ተቀምጦ ወደ አንቺ ይመጣል ፡፡” ብሎ አስተምሮአል፡፡ ( ዘካ.9፥9) ሌላኛውም ነቢይ “እናንተ የምትፈልጉት ጌታ ይመጣል ::  በዚያች ቀን በእርሱ ፊት ማን ይቆማል? በእርሱ ከእስራቶቻችሁ በመፈታታችሁ  እንደ ጥጃ ትዘላላችሁ፡፡” በዚህ ነገር የተደነቀው ሌላ ነቢይም “እርሱ የእኛ ጌታ ነው ከእርሱ ጋር የሚስተካከል ጌታ ፈጽሞ  የለም” ብሎአል ፡፡

ነገር ግን እነዚህንና ከእነዚህም ከጠቀስናቸው በላይ የተነገረለትን የእርሱን ቃል ለመስማት በመንቀጥቀጥ በጸጥታ መቆም ሲገባን ፣ እኛ በምድር እንዳለን ሳንረዳ አሁንም ራሳችንን በአንድ የስብሰባ አዳራሽ ውስጥ እንዳለን በመቁጠር እንጮኸለን ፣ እናወካን፣ ሰላማዊ የሆነውን ጉባኤያችንን ሁል ጊዜ ምንም በማይጠቅሙ ንግግሮች ስንረብሸው እንገኛለን ፡፡

ስለዚህ በትንሹም ፣ በትልቁም ጉዳይ ፤ በመስማትም ፣ በመሥራትም በውጭም ይሁን ፣ በቤታችን እንዲሁም በቤተክርስቲያን እጅግ ቸልተኞች ሆነናል ፡፡ እነዚህ ክፋቶቻችንን እንደያዝን የጠላቶቻችንን ነፍስ በመለመን ከባድ ኃጢአትን በራሳችን ላይ እንጨምራለን ፡፡  ከዚህ ኃጢአታችን ጋር የሚስተካከል ምን ኃጢአት አለ? በዚህ ባልተገባ ጸሎታችን ምክንያት ለእኛ ስለመዳን የሚቀርልን ምን ተስፋ አለን?

 ከእኛ የማይጠበቅ ሥራን እየሠራን በእኛ ላይ በደረሰው ውድቀትና ሕመም ልንደነቅ ይገባናልን ?  ልንደነቅ የሚገባን እነዚህ በእኛ ላይ ባይመጡብን ነው ፡፡ የመጀመሪያው ተፈጥሮአዊ ከሆነው ባሕርያችን መንጭቶ ነው ፡፡ ለሁለተኛው በደላችን ግን ምንም ምክንያት የምናቀርብለት አይደልም ፡፡ ለፍጥረት ሁሉ ፀሐይን በሚያወጣውና ዝናብን በሚሰጠው እንዲሁም ሌሎችንም በጎ ሥጦታዎችን በሚሰጠን በእግዚአብሔር ላይ በጠላትነት መነሣትና እርሱን በቁጣ ተሞልቶ መናገር ፣ ምንም ምክንያት ልናቀርብለት የማንችልበት በደላችን ነው ፡፡ ከቆረቡና እጅግ ታላቅ የሆነውን ጸጋ ተቀብለው ካበቁ በኋላ ፣ ከአውሬ ይልቅ ከፍተው ፣ እርስ በእርሳቸው በጠላትነት ተፋጥጠው የሚኖሩና ጎረቤቶቻቸውን  በምላሳቸው እያቆሰሉና አፋችን በእነርሱ ደም እያራሱ በቁጥር እጅግ የከፋ ቅጣት ለራሳቸው የሚያከማቹ አሉ ፡፡

ስለዚህም ይህን መተላለፋችንን አስበን ይህን ክፉ መርዝ ከውስጣችን አስወግደን ልንጥለው ይገባናል ፡፡ አንዳችን በአንዳችን ላይ ያለንን ጠላትነት እናቁም ፡፡ ለእኛ እንደምንጸልይ አድርገን ለሰው ልጅ ሁሉ ጸሎትን እናድርግ ፡፡ እንደአጋንንት ጨካኞች ከመሆን ይልቅ እንደ ቅዱሳን መላእክት ርኅሩኀን እንሁን :: ምንም ዐይነት ጥቃት በእኛ ላይ እንዳይደርስ የራሳችንን ኃጢአትና የጌታ ትእዛዝን በመፈጸማችን የምናገኘውን ብድራት አስበን ፣ ከቁጣ ይልቅ የዋህነትን ገንዘባችን እናድርግ ፡፡ ከዚህች ምድር በምናልፍበት ጊዜ እኛ ለወንድማችን እንዳደረግንለት ጌታችን ለእኛም እንዲያደርግልን  ምንም የማይጠቅመንን ጠብን በትዕግሥት በማሳለፍ ጥለናት በምንሄዳት በዚህች ዓለም ሰላማውያን ሆነን እንመላለስ ፡፡ በሚመጣው ዓለም የምንቀበለው ቅጣት የሚያስፈራን ከሆነ ሕይወታችንን በጠብ ያልተሞላ ቀላልና ሰላማዊ እናድርገው ፡፡ ወደ እርሱም የምንገባበትን የምሕረትን በር እንክፈተው ፡፡ ከኃጢአት ለመራቅ አቅሙ ያነሰን ቢሆን እንኳ እኛን የበደሉንን ይቅር በማለት በጥበብ እንመላለስ ፡፡ ይህን ማድረግ የሚያስጨንቅ ወይንም የሚከብድ አይደለም ፡፡ ጠላቶች ላደረጉን ቸርነትን በማድረግ ለራሳችንን ታላቅ የሆነውን ምሕረት ከአምላክ ዘንድ እናከማች ፡፡

በዚህ ዓለም በሁሉ ዘንድ ተወዳጆች እንድንሆን እንዲሁም እግዚአብሔር እኛን ወዳጆቹ በማድርግ ፣ የክብሩን አክሊል እንዲያቀዳጀን ለሚመጣውም ዓለም የተገባን ሆነን እንድንገኝ እግዚአብሔር ይርዳን ፤ ለሰው ልጆች ሁሉ ታላቅ ፍቅር ባለው በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል ለእርሱ ክብር ምስጋና ለዘለዓለሙ ይሁን አሜን ፡፡               

        

     

 

Picture.jpg

‹እንግዲህ አንተና ዘርህ በሕይወት ትኖሩ ዘንድ ሕይወትን ምረጥ› ዘዳ 30፥19

በዲ/ን ሄኖክ ኃይሌ
 
Picture.jpgአምላካችን እግዚአብሔር በሥልጣኑ ገደብ የሌለበት ሁሉን ማድረግ የሚችል አምላክ ነው፡፡ ከሥልጣኑ ማምለጥ የሚችልም የለም፤ ሁሉ በእርሱ መግቦት፣ ጥበቃና እይታ ሥር ነው፡፡ በምድር ላይ ያሉ ባለሥልጣናት ሥልጣናቸው በድንበር፤ በጊዜ፤ በሕግ የተገደበ ነው፡፡ እንዲህም ሆኖ በቦታና በጊዜ የተገደበ ሥልጣናቸውን ያለገደብ ለመጠቀም ይሞክራሉ፡፡ ሥልጣናቸውና ኃይላቸው የፈቀደላቸውን ያህል ኅብረተሰቡን እንደ ሰም አቅልጠው፤ እንደገል ቀጥቅጠው በግርፋት፣ በቅጣት፣ እየተጠቀሙ ልክ ሊያስገቡት ያም ባይሆን ሊያዳክሙት መሞከራቸው የምድራዊ ገዢዎች ጠባይ እንደሆነ በመጽሐፍ ቅዱስና በታሪክ የምንረዳው ሀቅ ነው፡፡ እግዚአብሔር ግን ገደብ የሌለው ሥልጣኑን በራሱ መግቦት ቸርነት፣ ምሕረት ገድቦ ሁሉን የሚያኖር አምላክ ነው፡፡
የሰው ልጅን ታሪክ ስንመረምርም ይህን እውነት መረዳት እንችላለን፡፡ አዳም የእግዚአብሔርን ሥልጣን (አምላክነትን) ሽቶ በዲያብሎስ ምክር ሕገ እግዚአብሔርን በጣሰ ጊዜ እግዚአብሔር ‹ሥልጣኔን ልትጋፋ አሰብህን? ብሎ በአዳም የፈረደበትን ፍርድ በራሱ ላይ አድርጎ ለመቀበል የፈጠረውን ሥጋ ተዋሕዶ በመከራው፣ በሞቱ አድኖታል፡፡ ይህም እግዚአብሔር የሰውን ልጅ በግድ ሳይሆን በነፃነት የሚገዛ አምላክ መሆኑን ያስረዳል፡፡ ከአዳምም በኋላ የሰው ልጆች እርሱን ከማምለክ ወደኋላ ሲሉና ለፍቅር አገዛዙ ሊመለስ የማይገባ ያለመታዘዝና የአመጽ አጸፋን ሲመልሱ የነጻነት እርምጃውን አልተወም። ሰውን ሁሉ እርሱን ወደ ማምለክና ለእርሱ ብቻ መገዛት የሚችልበት ችሎታ ሲኖረው ‹እሳትና ውኃን አቀረብኩልህ ወደ ወደድኸው እጅህን ስደድ› የሚል የነፃነት ጥሪን ከማቅረብ በቀር ምንም አላደረገም፡፡ ዛሬም ድረስ “እግዚአብሔር የለም” እስከማለት፤ በእርሱ ላይ እስከማፌዝና እስከመዘበት የሚደርሱ ብዙዎችን እየተመለከተ ዝም ማለቱ ማንም ሰው በፍላጎቱ ብቻ እርሱን እንዲመርጥ ስለሚፈልግ ነው፡፡ ‹ወደ እኔ ኑ! ወደ እኔ ቅረቡ› እያለ መጣራቱን ወደንና መርጠን በፈቃደኝነት ወደ እርሱ እንድንሄድ፤ ነፃነታችን ላለመንፈግ እንጂ እኛን ወደ እርሱ ማቅረብ ተስኖት የሚያደርገው የልምምጥ ጥሪ አይደለም፡፡ ይህን ሁኔታም አሁን ከምንረዳው በላይ በእግዚአብሔር ፊት በሞት እጅ ተይዘን በምንቀርብበት ጊዜ በይበልጥ የምንረዳው ነው፡፡
አንባብያን ሆይ! እግዚአብሔር አባታችን አዳምን በገነት ሳለ ዕፀ በለስን እንዳይበላ መከልከሉ ከሞላ ዛፍና ፍሬ አንዲት ዕፅ ተበልታ እርሱ የሚጎድልበት ሆኖ ነው? ወይስ ዲያቢሎስ ለሔዋን እንደነገራት አምላክ እንዳይሆን ነው? እንዲህ እንዳንል ደግሞ አዳም ዕፅዋን ሲበላ እንኳን አምላክነት ሊጨመርለት የነበረው ፀጋ ተገፍፎ ዕርቃኑን ቀርቶአል፡፡ ታዲያ ለእግዚአብሔር አንዲት ቅጠል ምን ልትረባው ነው አትብላ ብሎ የከለከለው? በንባብና በትምህርት ከምንደርስባቸው በርካታ ምክንያቶች በተጨማሪ የአዳም ነጻ ፈቃድ እንዲታወቅ ነው፡፡
እግዚአብሔር ለአዳም ያለውን ፍቅር በመፍጠር፤ ሁሉን በመስጠት ከገለጠ አዳም ለእግዚአብሔር ያለውን ፍቅርስ በምን መለካት ይቻላል? አዳም ለእግዚአብሔር ሊሰጠው የሚችለው እግዚአብሔር ከሰጠው ነገር ሌላ አዲስ ነገር ምን አለ? ምንም የለም! አዳም ለአምላኩ ያለውን ፍቅር የሚገልጠው በምንም ቁስ አይደለም የመታዘዝና ያለመታዘዝ ነጻ ፈቃዱን ለእግዚአብሔር በመስጠት (በመታዘዝ) ብቻ ነበር፡፡ ዕፀ በለስም የዚህ ነጻ ፈቃድ መመዘኛ ነበረች፡፡ አዳም ግን ነጻ ፈቃዱን ለእግዚአብሔር ሊሰጥ አልፈቀደም። በነጻነት ከሚገዛው ፈጣሪ ይልቅ ረግጦ የሚገዛውን የዲያብሎስን አገዛዝ መረጠ፡፡
አንዳንዶች ‹ፈጣሪ የሰው ልጅ ኃጢአተኛ እንደሚሆነ እያወቀ፤ እያየ ለምን ኃጢአት እንዳይሠራ አላደረገውም? ይላሉ፡፡ ይሁንና እግዚአብሔር የሰውን ልጅ ነጻ ፈቃድ የማይነካ የነጻነት ገዢ ነው፡፡ ደግሞም ሰው በበጎው መንገድ ብቻ እንዲሔድ ቢያስገድደው ኖሮ ‹ነጻነቴን ተነፈግሁ› ባለ ነበር፡፡ እንኳን ዕድሜያችንን ሙሉ በመንፈሳዊው አኗኗር ለመኖር በዕለተ ሰንበት በቤተ ክርስቲያን መጥተን ሥርዓተ ቅዳሴ እስከሚጠናቀቅ ለመታገስ ፈቃደኛ ያልሆንን ብዙዎች ነን፡፡
ወደ ሲኦል ወይንም ወደ ገነት መግባታችን የነጻነት አገዛዙ አካል ነው፡፡ አንዳንዴ ‹እግዚአብሔር እንዴት ሰው ወደ ሲኦል እንዲገባ ያደርጋል? ለምን ይጨክናል?› ብለን ባላወቅነው ልንፈርድ እንችላለን፡፡ እግዚአብሔር  በምድር ሳለን ‹ይህን ብትፈጽሙና ብታደርጉ ገነትን ትወርሳላችሁ፤ ይህንን ብታደርጉ ደግሞ ሲኦል ትገባላችሁ ብሎ ሁለት አማራጮችን ሰጥቶናል፡፡ የምንመርጠው መንገድ የምንወርሰው ርስት ምን እንደሆነ ይወስነዋል፡፡ እግዚአብሔር ሁሉም ሰው ቢድን (ወደ ገነት ቢገባ) የሚወድ አምላክ መሆኑን ራሱ በቃሉ ተናግሯል፡፡ ይሁንና በምድር ሳሉ ሲኦል ለመግባት የሚያበቃቸውን መንገድ የመረጡ ሰዎችን ግን ከምርጫቸው ለይቶ ወደ ገነት መውሰድን የነጻነት አገዛዙ አይፈቅድም፡፡ ስለዚህም ማንንም ማስገደድ የማይወድ አምላክ የሰው ልጅ በተሰጠው ነጻ ፈቃድ በምድር ሳለ የመረጠውን ርስት እንዲወርስ ያደርገዋል፡፡
የዚህ ጽሑፍ መሪ ጥቅስ የሆነው ቃልም ከላይ ለጠቀስነው ሀሳብ ምሳሌ የሚሆን የነጻነት ጥሪ ነው፡፡ ‹በፊታችሁ ሕይወትና ሞትን፤ በረከትና መርገምን እንዳስቀመጥኩ እኔ ዛሬ ሰማይና ምድርን ባንተ ላይ አስመሰክራለሁ፡፡ እንግዲህ ‹አንተና ዘርህ በሕይወት ትኖሩ ዘንድ ሕይወትን ምረጥ› ዘዳ 30፥19
እግዚአብሔር ሕይወት የተባለች ሃይማኖትንና ምግባርን በእርስዋ ከሚገኘው በረከት ጋር፤ ሞት የተባለች ኃጢአትንና ርኩሰትን በእርስዋ ከሚመጣው መርገም ጋር በፊታችን አስቀምጧል፡፡ የምንወደውን የምንመርጥበት ነጻ ፈቃድ አለንና፡፡
choose.jpg
የዚህ ምርጫ ታዛቢዎች ሰማይና ምድር ናቸው፡፡ ሰማይና ምድር ደግሞ በየትኛውም ዘዴ የማይታለሉና ንቁ ታዛቢዎች ናቸው፡፡ ወደ ሞት መንገድ እየሄድን የመረጥኩት ሕይወትን ነው ብሎ ማታለል አይቻልም፤ ሰማይና ምድር ይመለከታሉና፡፡ ኃጢአትን አብዝተን እየፈጸምን በመላ ሰውነታችን ርኩሰትን እየመረጥን የመረጥኩት ሕይወት ነው ብንል ከሰማይና ከምድር ዕይታ ውጪ የሰራነው ኃጢአት ስለሌለ እግዚአብሔር እነርሱን ምስክር ያደርግብናል፡፡ ብሎም በምድር በሰው ልጆች በሰማይ በመላእክት ያስመሰክርብናል፡፡ መላእክቱም ጠባቂዎቻችን ፤ የሰው ልጆችም አብረውን የሚኖሩ ናቸውና ሥራችንና ምርጫችን ምን እንደሆነ ለመታዘብ አይቸገሩም። እግዚአብሔር ታዛቢዎች አቁሞ ምረጡ ሲለን ምንም ነጻ ፈቃዳችንን ባይነካም፤ ብንሰማውም ባንሰማውን እንደ አባትነቱ የቱን ብንመርጥ እንደሚሻለን ይመክረናል ‹እንግዲህ አንተና ዘርህ በሕይወት ትኖሩ ዘንድ ሕይወትን ምረጥ› በማለት፡፡
 
ሕይወትን ምረጡ ሲል ወደ ሞት የምትወስደውን የኃጢአት መንገድ ትታችሁ ወደ ዘላለማዊ ሕይወት የምትወስደውን የሃይማኖትና የጽድቅን መንገድ ተከተሉ ማለት ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ቤት መራቅና ዓለማዊ ተድላ ደስታን ብቻ ማሳደድ ሕይወትን አለመፈለግ ነው፡፡ ወደዚህች ቅድስት ስፍራ የሚመጣ ሁሉ ሕይወት የሆነ አምላክን ከእርሱም የሚገኘውን መንፈሳዊ ስጦታ ሁሉ ያገኛል፡፡ እግዚአብሔር ሕይወትን ምረጡ ማለቱ በሌላው ምርጫችን የሚደርስብንን ክፉ ነገር ሁሉ እንዳናይ በማሰብ ነው፡፡
ውድ አንባብያን! ቀጣዩን አንቀፅ ከማንበባችን በፊት እስቲ ቆም ብለን ‹ባለፈው የሕይወት ዘመናችን መርጠን የነበረው መንገድ የሕይወት ነው? ወይስ የሞት?› በማለት ራሳችንን እንጠይቅ የብዙዎቻችን ሕሊና የሚነግረን ምርጫችን የጥፋት መንገድ እንደነበረ ነው፡፡ ከነፍሳችን ይልቅ ለሥጋችን፤ ከሕይወታችን ይልቅ ለሞታችን፤ከልማታችን ይልቅ ለጥፋታችን ስንደክም መኖራችን ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ የደጋግ ቅዱሳን አባቶች መፍለቂያ የሃይማኖትና የምግባር መነኻሪያ በነበረችው ቅድስት ሀገራችን ያለአንዳች እፍረትና ፍርሃት  ተከፍሎ የሚያልቅ፤ የማይመስል የኃጢአት ዕዳ ሲከማች እንደዋዛ መታየቱ ምንም እንኳን መጽሐፍ ቅዱስ ‹ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች› ቢል የብዙ ኢትዮጵያውያን እጅ ግን ወደ ሌላ አቅጣጫ መዘርጋቱን የሚያመለክት ነው፡፡ ለመንፈሳዊ አገልግሎትና ለሥራ ዳተኛ የሆነ ሁሉ ለዝሙትና ለዳንኪራ ያለስስት ገንዘቡን፣ ጊዜውንና ጉልበቱን ሲሰጥ በመንፈሳዊ ዓይን ለሚመለከተው ሰው እጅግ የሚያሳዝን ነበር፡፡
ክርስቲያኖች፣ በዚህ ዲያብሎስና የዓለም ጠባይ ሰውን ሁሉ ከሃይማኖትና ከምግባር ለማውጣት፤ የተቀደሰ ኢትዮጵያዊ ባሕሉን፤ ማንነቱንና ሥርዓቱን ለማጥፋት ታጥቀው በተነሱበት ጊዜ ‹ሕይወት ምረጡ› የሚለው አዋጅ እጅግ ተገቢ አይደለም ትላላችሁ? ስለዚህ ነው ፈጣሪ እያንዳንዱ ክርስቲያን ‹ወደ ሌላው ሰው በደል መጠቆምና ማመካኘት ትተህ አንተና ዘርህ በሕይወት ትኖሩ ዘንድ ሕይወትን ምረጥ› በሚለው ቃል ራስን ለመመርመር ወደ ቤተ ክርስቲያን መቅረብ ነው፡፡
ቤተ ክርስቲያን ሕይወትን የሚመርጡ ሁሉ የሚገቡባት በር ናት፡፡ ምንም እንኳን በቤተ ክርስቲያን ስላሉ ሰዎች መጥፎ ወሬን ቢሰሙ እንኳን እንደ ተራ እንቅፋት ቆጥረው በጽናት መቀጠል ለክርስቲያኖች ይገባቸዋል፡፡ ያለፉት የኃጢአትና የርኩሰት ዓመታት በንስሐ በማጠብ ወደ ሥጋ ወደሙ መቅረብ ፤ ሕይወትን መምረጥ ፤ብሎም በሕይወት መኖር ነው፡፡
የእግዚአብሔርን ጥሪ ተቀብሎ ይህንን የሕይወትና የሞት ምርጫ ለመምረጥ ልዩ መሥፈርት የለውም ክርስቲያንነት ብቻ በቂ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም መንፈሳዊውን መንገድ መርጠን መኖር ጀምረን በድክመታችን ያቋረጥነው ሰዎችም አሁን ዳግመኛ ሕይወትን መርጠን በሕይወት ከመኖር አንከለከልም፡፡ አውራጣታችንን ይዞ ቀለም እየቀባ ‹እናንተ ከዚህ በፊት መርጣችኋል ድጋሚ መምረጥ አትችሉም!..›የሚል ከልካይ በቤተ ክርስቲያን የለም፡፡ ዲያብሎስ ግን «ጠፍቼ ጠፍቼ እመለሳለሁ?» እንድንል ወደ ኋላ ሊስበን ይሞክራልና ሕይወትን በመምረጥ የክርስቶስን መንገድ በመያዝ እናሳፍረው፡፡
 
የእግዚአብሔር ሁሉን የመቀበል፣ ይቅር የማለት ባህርይ የእኛን ድኅነት ከመሻቱ ነውና የተዘረጋልንን የምሕረት እጅ ቸል ብንል እንቀጣለን። ነገሩም እንዲህ ያለውን መዳን ቸል ብንል የሚብስ ቅጣት የሚገጥመን አይመስላችሁም? እንዳለው ነው። እርሱ ይቅር ማለት ሳይታክተውና እኛ ይቅር መባልና ይቅር በለኝ ማለትን ልንጠላ አይገባንም።
እግዚአብሔር መጪውን ጊዜ የንስሐ፤ የስምምነት፣ የፍቅርና መደማመጥ የሞላበት የአገልግሎትና የመንፈሳዊነት ዘመን ያድርግልን! አሜን!
 
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ እና የ«ተሐድሶዎች» ቅሰጣ

                                    በእደማርያም ንርአዩ

ምድራችን እስከ ዕለተ ምጽአት ከመልካም ስንዴው ጋር እንክርዳዱን ማብቀሏ፤ ከየዋሁ በግ ጋር ተኩላውን ማሰለፏ፤ ከንጹሐን ሐዋርያት መካከል ይሁዳን ማስገኘቷ አይቀርም፡፡ እንክርዳዱ እንዳይነቀል ከስንዴው ጋር አብሮ በቅሎ፣ ተኩላው እንዳይጋለጥ በግ ይመስል ዘንድ ለምድ ለብሶ ከስንዴው ጋር ልዘናፈል፣ ከበጉም ጋር ልመሳሰል ብለው ያልሆኑትን ለመሆን እየታገሉ ለዓላማቸው መስለው የሚሠሩ ተቆርቋሪም ሆነው የሚቀርቡ በማባበል ቃል የሚጎዱ ከፍጥረት ጅማሬ እስከ ዘመን ፍጻሜ፤ ከመላእክት ከተማ እስከ ደብረ ዘይት ተራራ ጌታችን እስከሚገለጥበት ቦታ ከገነት እስከ ዛሬዋ መቅደስ ስተው እያሳቱ ክደው እያስካዱ ከዚህ ዘመን ደርሰዋል፡፡

ለዚህም ነው ሄሬኔዎስ /ከ 130-200 ዓ.ም/ የተባለ ሊቅ «በእውነቱ የስኅተት ትምህርት ወዲያው ታይቶና ታውቆ እንዳይገለጥ እርቃኑን ከቶ አይቆምም፡፡ ነገር ግን መስሕብነት ያለውን ልብስ በብልሃት ለብሶ በውጭ አምሮ ይገኛል፡፡ የሚሞኝ ሰው ካገኘ ለማታለል ከእውነትም የበለጠ እውነት መስሎ ይታያል፡፡» በማለት የገለጸው፡፡

ቅድስት ቤተክርስቲያን ከምሥረታዋ ጀምሮ ጠላት ዲያብሎስ በግብር የወለዳቸውን በመጠቀም እውነቱን ሐሰት በማለት ማሩን በማምረር ወተቱን በማጥቆር የዋሃንን በረቀቀ ስልቱ ተመሳስሎ የጸኑትን ደግሞ እርቃኑን ገልጦ      ጭንብሉን አውልቆ፤ ሲሆን ኃይለ ቃል አጣምሞ ሳይሆንለት ደግሞ ሰይፍ ስሎ ስንዴውን ለማጥፋት እንክርዳዱን    ለማብዛት ያለማቋረጥ ይሠራል፡፡ ያለ ድካም ይተጋል፡፡

ሰማዕታቱም ሞት በእጅጉ በሚፈራበት ዘመን ሞትን እየናቁ ወደ መገደያቸው በዝማሬ ሲሄዱ ያዩ      ሃይማኖታቸው ምንኛ እውነት ቢሆን ነው በማለት ብዙዎችን በሞታቸው ወለዱ የካርታጎው ጠርጠሉስ «አሠቃዩን፣ ስቀሉን፣ ንቀፉን፣ ኮንኑን፣ አቃጥሉን የእናንተ ክፋት ግፍና ጭካኔ የእኛ ንጽሕና ማረጋገጫ ነው፡፡ እናንተ በወገራችሁንና በቆረጣችሁን ልክ ቁጥራችን እልፍ ይሆናል፤ ደመ ሰማዕታት የክርስቲያኖች ዘር ነው፡፡» እንዳለው እንደ ሐሰተኛ ተቆጠሩ እንደ አበደ ውሻ ተወገሩ፤ እንደ ጥራጊ ቆሻሻ ተቃጠሉ፡፡ ስንዴ ስትርስ እንደምታፈራ ሁሉ ሲሞቱ ሌሎችን እያፈሩ ስብከተ ወንጌል ካጸናቸው መከራው የሳባቸው እየበዙ «ሞት ምንም አይደለም ክርስቶስ ተነሥቶአልና» እያሉ በሰማዕትነት ቀናቸው ለዘላለማዊ ሕይወት እየተወለዱ ያረፉበት ዕለትም እንደ ልደት ቀናቸው የሚከበር ሆነ፡፡

መከራ መገለጫቸው ስደት ኑሯቸው ቢሆንም እንኳን በትንሣኤ ተስፋ እየ ተጽናኑ መከራውን እንደ ኢምንት እየቆጠሩ ሳይጠራጠሩ ንግግር የማያውቁ ሲሆኑ ንግግር አዋቂዎችን በክርክር እየረቱ የተረቱትንም ሞትን እንዲንቁ ዘላለማዊ ሕይወትን እንዲናፍቁ አደረጉ፡፡

ገንዘው ሊቀብሯት ስም አጠራሯንም ሊያጠፏት መስሏቸው ለጊዜውም ቢሆን ላይ ታች ቢሉ «እኔ ዓለምን    አሸንፌአለሁ» ያለ አምላክ እንዴት ይሸነፋል ? ቀላያት ተነድለው፣ ምድርንና በውስጧ ያለው ሁሉ በውኃ በጠፋበት በኖኅ ዘመን ኖኅና ቤተሰቦቹን የያዛቸውን መርከብ ይሰብራትና ያጠፋት ዘንድ ውኃው መች ተቻለው ? መጽሐፍ «ውኃውም በምድር ላይ አሸነፈ» ቢልም የኖኅን መርከብ ያሸንፋት ዘንድ ግን አልቻልም፤ እግዚአብሔር ደጆቿንና መስኮቶቿን ራሱ ዘግቷቸዋልና፡፡ እግዚአብሔር የዘጋውንስ ማን ሊከፍተው ይችላል ? ውኃው ሌላውን ሁሉ ሲያሰጥምም መርከቢቷን ግን ከፍ ከፍ እያደረጋት ወደ ተራራው ጫፍ አደረሳት እንጂ መቼ አሰጠማት ?

ኦርቶዶክሳዊት ቤተክርስቲያን በዚህ ሁሉ መከራ የምትሰጥም ለሚመስላቸው ደጆቿን ለመስበር ለሚታገሉ በዙሪያዋ እንደ አንበሳ ለሚዞሩ «ከሠሪው ጋር ለሚታገል ወዮለት» /ኢሳ. 45/ ከማለትስ ሌላ ምን እንላለን ? መሠረቷ ዐለት ነውና ብትወድቁበት ትሰበራላችሁ ቢወድቅባችሁ ትፈጫላችሁ ከማለት ሌላስ ምን እንናገራለን ? / ኢሳ 8/፡፡

ቤተክርስቲያንን በመከራ እየገፏት ወደ ተራራው ጫፍ ወደ ዘላለማዊ ዕረፍት ወደ ፍጹም ጽናት ያደርሷታል እንጂ መቼ ከአምላኳ ይለይዋታል ?

በዚህ ሁሉ ግን ስለ ጥርጥር ጥያቄአቸው ስለ ክህደት አቋማቸው ስለ ነቀፋና ትችታቸው በብርቱ ያለ ዕረፍት ቢዘበዝቡንም ነገር ሁሉ ለበጎ በሆነ በአምላካችን ፊት ወደ በለጠ ጽናት ወደ በለጠ ምርምር ወደ ጥልቅ ንባብ ወደ ታላቅ የሥራ በር መርተውናልና አናማርራቸው፡፡ ቅዱስ አውግስጢን «መናፍቃንን ስለ ጥርጥር         ጥያቄዎቻቸው ሁሉ እናመሰግናቸዋለን፤ የበለጠ እንድናጠና፣ በጥልቀትም እንድንመራመር አድርገውናልና» እንዳለው፡፡ የመናፍቃን መነሣት ለቤተክርስቲያን ትልቅ ጥቅም ነው፡፡ ታላቁ ሐዋርያ ቅዱስ ጳውሎስም «ሥራ የሞላበት ታላቅ በር ተከፍቶልኛል ተቃዋሚዎች ግን ብዙ ናቸው» ብሏል፡፡

በዚህ ጽሑፍ «ተቃዋሚዎች» በከፈቱልን የሥራ በር ጥቂት መቆየት ፈለግን፤ በሩ… እነሆ

ከአባቶች ትምህርት የራቀው ማን ነው ?

ራሱን እንደ «ለውጥ» አራማጅ እንደ «ተሐድሶ» ፋና ወጊ አንዳንዴም እንደ «ተሳዳጅ» አንዳንዴም እንደ «ሰማዕት» የሚቆጥረው ቡድን «ዛሬ ያለችው ቤተ ክርስቲያን ከጥንቶቹ አባቶች ትምህርት የራቀች ናት» በማለት ራሱን ከአባቶቿ የሚያገናኛት ሐዋርያ አድርጎ አስቀምጧል፡፡ ለእግሮቹ ማረፊያ ፍለጋ ማነህ ለሚለው ጥግ መያዣ ሲሻው የጥንታዊያን አበውን ትምህርት ይጠቅሳል ስማቸውን በማንሣት የትምህርታቸውን ጫፍ በመጠንቆል በስማቸው ይሸፈናል፡፡ ክንብንብ ጭንብሉን ሲያወልቁበት ደግሞ «አባቶቼ» እንዳላላቸው ዞር ብሎ ደግሞ ይሰድባቸዋል፡፡ በቅዱሳን ሐዋርያት፣ በሐዋርያውያን አበው በሊቃውንት ትምህርት ተስቦ ሳያምን ትምህርታቸውን እየሳበ ወደ ራሱ ሃሳብ ሊያገባቸው እየሞከረ በስማቸው እንድንቀበለው ይፈልጋል፡፡

መጽሐፍ ቅዱስ አንድ ወይም ጥቂት ጥቅሶች ብቻ እስኪመስል እንዳደረጉት ፕሮቴስታንት ወላጆቻቸው አንዲት መሥመር ትምህርታቸውን ብቻ፣ አንዲት ቃላቸውን ብቻ ይዘው ብዙውን ከራሳቸው ጨምረው የአበው ልጆች መስለው እንደተማሩ፣ የእነርሱ ወራሽ መስለው እንደተረከቡ ብዙዎችን ያደናግራሉ፡፡ ልባቸው ሰፊ አይደለምና ታግሰው አይመረምሩም፣ ጥቂት እንኳን ዝቅ ብለው አያነቡም፤ ብቻ «የአይሁድ ንጉሥ» የምትለዋን ቃል ከሰብአ ሰገል ሲሰማ ብዙ የማይመለስ ጥፋት እንዳጠፋ ሄሮድስ «ሊቀ ካህናት» «አስታራቂ» የሚለውን ቃለ ሲሰሙ ይደናበሩና ራሳቸውን ሌሎችንም ይዘው ለጥፋት ይፋጠናሉ፡፡ የአበውን ሙሉ ቃል የድምጻቸውንም ለዛ እየሰሙ እንደመከተል የተገላቢጦሽ እየመሩ ሊወስዱአቸው ይከጅላሉ፡፡ ታዲያ እንዴት «አባቶቼ» ይሏቸዋል? «አባቴ» ለማለት «ልጅ» ሆኖ መገኘት ግድ ይላል፡፡ እውነተኛ ልጅ ለመሆን ደግሞ በአባቱ ትምህርት ፍጹም መወለድን ይጠይቃል፡፡   

ይህ ቡድን «አባት» ብሎ ትምህርቱን እንደወረሰ ቃሉን እንደታጠቀ የሚናገርለት ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን ደጋግሞ ከአፉ አይለየውም ከብዕሩ አይነጥለውም፡፡ እውነት ይህ ቡድን «አባቴ» የሚለው ይህ ታላቅ     የቤተክርስቲያን አባት የዚህ ቡድን አባት ነው ? እስኪ ልጅ ነኝ የሚለውን ቡድን አባቴ ከሚለው ታላቅ አባት ትምህርት ጋር እያነጻጸርን «ልጅ» አይደለህምና፤ እርሱም አባትህ አይደለም፤ ሌላ አባትህን ፈልግ እንበለው፡፡

መናፍቃን በሚያሳትሙት መጽሔት ላይ ቃለ መጠይቅ የሰጠው የዚሁ ቡድን አባል መሪጌታ ጽጌ ስጦታው     በተለመደው የአበውን ትምህርት ድጋፍ ለማድረግ በሚያደርጉት ጉድፈራ አንዲት መሥመር እንኳን የማትሞላ ቃል በመምዘዝ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅን «ክርስቶስ አማላጅ ነው» ? ለሚለው ፕሮቴስታንታዊ ትምህርቱ ታኮ ለማድረግ ይፈልጋል፤ እንዲህ በማለት «ዮሐንስ አፈወርቅ ደግሞ በክርስቶስ በተገኘው እርቅ ካልሆነ በቀር በሌላ በማንም በኩል ጸሎትና ምልጃን ማቅረብ አልተቻለም…፡፡» /ትሪኒቲ ቁ.4 ገጽ 3/ የሚል ቃል በመጥቀስ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ጌታችንን «አማላጅ» ብሎታል በማለት ሊቁን  የስሕተት ትምህርታቸው ተባባሪ ሊያደርጉት ይፈልጋሉ፡፡ በዚህም ፍጹም የአበውን ፈለግ የተከተሉ የእነርሱን ሃይማኖት ያነገቡ መስለው ለመታየት ይከጅላሉ፡፡ እውነቱን ለመናገር ግን በዚህ በፕሮቴስታንት መጽሔት ቃለ መጠይቅ የሰጠው ግለሰብ የሊቁን ትምህርት ቆንጽሎ ለስኅተቱ መደገፊያ ያድርገው እንጂ የሊቁን ሙሉ ጭብጥ ትምህርት ያላገናዘበ አንዲት መስመርን እንኳ ያልፈተሸ መሆኑ ይገልጽበታል፡፡

ቆንጽሎ የጠቀሰውን ቃል ብቻ እንኳን ብናየው አንድም ጌታችንን «አማላጅ» የሚል ትምህርት ከሊቁ አናገኝም፡፡

በክርስቶስ በተገኘው እርቅ ካልሆነ በቀር…

ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ «እግዚአብሔርም አየ ፍርድም ስለሌለ ተከፋ፡፡ ሰውም እንደ ሌለ አየ፤ ወደ እርሱ    የሚማልድ እንደሌለ ተረዳ፤ ተደነቀም፤ ስለዚህ የገዛ ክንዱ መድኃኒት አመጣለት ጽድቁም አገዘው፡፡» /ኢሳ. 59÷16/ የሚለውን መሠረት አድርጎ ሰው ሁሉ በአንዱ በአዳም በደል ተጠያቂ ሆኖ፣ ባሕርይው ጎስቁሎ፣ ሕያውነትን አጥቶ፣ ባለ ዕዳ ሆኖ በኖረበት ዘመን የካህናቱ ጸሎት፣ የነቢያቱ ምልጃ፣ የቅዱሳኑ ልመና የሰውን ልጅ ከሲኦል ማውጣት፤ ገነትን መክፈት፤ ጎስቋላ ባሕርይውን ማደስ፤ የሰውን ጥንተ ተፈጥሮ ሳይወድቅ በፊት ወደ ነበረበት ንጽሕና መመለስ አልቻለምና ነቢዩ ኢሳይያስ እንዳለው ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ «በክርስቶስ በተገኘው እርቅ ካልሆነ በቀር» አለ፡፡

ጌታችን መገለጥ ያስፈለገበት መንገድ እንደ ነቢያቱና ካህናቱ ምልጃና ጸሎት አይደለም፡፡ ዕርቁ ኃጢአት የተዋሐደውን የሰው ልጅ ከኃጢአት ነጻ ማውጣት የተፈረደበትን የሞት ፍርድ በደሙ መፍሰስ፣ በሥጋው መቆረስ ማስወገድ፣ ገነትን መክፈትን ባሕርይውን ማደስ ነው፡፡ ለዚህም ደግሞ ከሰው ወገን ይህንን ሊፈጽም የሚችል አልተገኘምና «ሰው እንደሌለ አየ» ተባለ፤ ራሱ የሰው ልጅ ገነትን መክፈት አልቻለም፤ ገነት ተዘግታበታለችና፡፡ ሞትን ማስወገድ አልቻለም፤ ሕያውነትን አጥቷልና፡፡ ከኃጢአት ነጻ አይደለም፤ ባለዕዳ ነውና፡፡ ታዲያ ለዚህ የሚያስፈልገው ሰው ሆኖ የሚክስለት ሰው የሆነ በሐዲስ ተፈጥሮ ይቅር ብሎ የሚታረቀውም አምላክ መሆን አለበትና ይህንን የሚያሟላ ቢጠፋ «የሚማልድ እንደሌለ ተረዳ» አለ፡፡ ስለሆነም «የገዛ ክንዱ መድኃኒት አመጣለት» እንዲል ክንዱ የተባለ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በተለየ አካሉ ተገልጦ እንደ ነቢያቱ «እግዚአብሔር እንዲህ ይላል» እያለ ሳይሆን « እኔ ግን እላችኋለሁ» በማለት ተገለጠ፡፡ ነቢያት ምሳሌውን እየመሰሉት ትንቢት እየተናገሩለት ሱባኤ እየቆጠሩለት ኖሩ ጌታችን ግን እርሱ መሆኑን ስለ እርሱ መነገሩን… እንደ ተፈጸመ እየነገረን መጣ፡፡ መጽሐፍ ቅዱስም «በአምላካቸው በእግዚአብሔር አድናቸዋለሁ» ይላል፡፡ /ሆሴ 1÷3/ የተገለጠው እግዚአብሔር  ነው፤ ያለ እግዚአብሔር ይህ ሁሉ ሊሆን አይችልምና፡፡ በትምህርታቸው እየገሠጹ በኃይለ ቃላቸው እየመከሩ መጻኢያቱን እየተናገሩ በጸሎትና በምልጃ ሕዝቡን እየተራዱ የኖሩት ነቢያት /ቅዱሳን/ ይህን ፍጹም እርቅ ማምጣት አልተቻላቸውምና ነው ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ «በክርስቶስ በተገኘ እርቅ ካልሆነ በቀር» ያለው እንጂ ሊቁ ክርስቶስን «አማላጅ» የሚል አሳብ የለውም፡፡

በሌላ በማንም በኩል ጸሎትና ምልጃን ማቅረብ አልተቻለም

ይህ ከላይ የዘረዘርነው የጌታችን ሥራ አገልግሎት በራሱ በእግዚአብሔር ካልሆነ የሚሠራ ባለመሆኑ በፍጡር ሳይሆን በፈጣሪ ብቻ የሚሠራ በመሆኑ ፍጡራን በሆኑ በማናቸውም ይህን እርቅ ማምጣት አልተቻለምና «..በሌላ በማንም በኩል ጸሎትንና ምልጃን ማቅረብ አልተቻለም፡፡» በማለት ገለጸው፡፡ በአዳም የሞት ፍርድ የፈረደው እግዚአብሔር ነውና እግዚአብሔር የፈረደውን እንዴት ፍጡራን ያነሣሉ? ስለዚህ «በክርስቶስ በተገኘው እርቅ ካልሆነ በቀር» አለ፡፡ እግዚአብሔርም ያስወጣውን ፍጡራን /ነቢያት፣ መላእክት፣ ካህናት/ ሊያስገቡት አይችሉምና «በሌላ በማንም በኩል» አለ እንጂ ሊቁ «ጸሎትንና ምልጃን» ሲያቀርብ የሚኖር «አማላጅ» አላለውም፡፡

ጽድቃችን ፍሬ፣ ጸሎታችን ተሰሚ፣ ደጅ ጥናታችን ግዳጅ ፈጻሚ እንዲሆን ዳግመኛ ሕይወት እንድናገኝ ለማድረግ ኃጢአትን አስወግዶልን ወደ ጥንት ክብራችን መልሶን አንድ ጊዜ ክሶ ያስታረቀንን እና የታረቀንን አምላክ ሁሌ «አማላጅ» በማለት ደጋግሞ እንደሚሠራ አድርጎ ማቅረብ የቃለ መጠይቅ ሰጪው የ«ጽጌ ስጦታው» እንጂ የቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ትምህርት አይደለም፡፡ ደጋግሞ መሥራት ከፍጡራን የሚጠበቅም እንጂ ከፈጣሪ የሚጠበቅም አይደለም፡፡

የነቢያት፣ የካህናት፣ የቅዱሳኑ ጸሎትና ምልጃ ፍጹምን ዕርቅ አምጥቶ ሰውንም አድኖ ከሲኦል ወደ ገነት ማግባት የማይቻለው በመሆኑ ለሰው ልጅ ደጋግመው መጸለይ ዘወትር መሥዋዕት መሠዋት ሲያገለግሉ መኖርን ጠይቋቸው ነበር፡፡ ደጋግመው በማድረጋቸውም ድካም ስላለባቸው ፍጹም መፈወስ /ማዳን/ አለመቻላቸው ይታወቃል፡፡ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ግን ድካም የሌለበት የባሕርይ አምላክ በመሆኑ አንዴ ሠርቶ የሚያድን አንዴ ተናግሮ የሚያጸና በመሆኑ እንደ እነርሱ ዘወትር ምልጃን ሲያቀርብ አይኖርም፡፡ ሊቁ ዮሐንስ አፈወርቅ «..በክርስቶስ በተገኘው እርቅ» አለ እርቁን አንዴ አስገኝቷልና «በተገኘው» አለ የሚያስገኝልን እርቅ የለምና፤ «በተገኘው» የሚለው ቃል ጌታችን በመስቀል ላይ የሰጠንን ፍጹም እርቅ የሚያመለክት እንጂ «ሲያስታርቅ» ስለመኖሩ በማስታረቅ ሥራን እየደጋገመ ስለመፈጸሙ የሚያሳይ አይደለም፡፡ ሊቁ ይህንን ቃል ከሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ ትምህርት አግኝቶታል፤ «ነገር ግን አሁን መታረቁን ባገኘንበት በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ በኩል በእግዚአብሔር እንመካለን፡፡» ከሚለው /ሮሜ. 5÷11/ መታረቁን አንድ ጊዜ በመስቀል ላይ አግኝተናልና «..በልጁ ሞት ታረቀን» እንዲል፡፡ /ሮሜ. 5÷10/

ዳግመኛም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ «ብርቱ መድኃኒት አንድ ጊዜ በመደረጉ ጽኑውን ደዌ ያድናል፡፡ ብዙ ጊዜ የሚደረግ መድኃኒት ደካማ እንደሆነ ይታወቃልና፡፡» እንዳለው /ድርሳ 17 ቁ 96 -97/ የቀደሙት /የነቢያቱ ጸሎት የካህናቱ መስዋዕት /ደካማ ነበሩና/ በኃጢአት በባለዕዳነት/ ብዙ ጊዜ መሥዋዕት እየሰሠዉ ምልጃ እያቀረቡ ኖሩ፡፡ ጌታችንን ግን «ብርቱ መድኃኒት» ነውና አንድ ጊዜ ባደረገው የመስቀል ዕርቅ ጽኑ ደዌአችንን አስወገደልን፡፡ አሁን /መታረቁን ካገኘን በኋላ/ «አማላጅ ነው» «ሁልጊዜም በማያቋርጥ ሁኔታ… የምልጃ ተግባሩን ይፈጽማል፡፡» ማለት /በንስሐ የመታደስ አገልግሎት በጎ ፈቃደኛ ገጽ 69 ቁ.1 2002 ዓ.ም/ በየትኛውም አቀራረብ ጌታችንን ያለ ጥርጥር «ደካማ መድኃኒት ማድረግ» ነው፡፡ እንደ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ትምህርት፡፡      «ሁልጊዜም ሳያቋርጥ» ይፈጽማል ማለት አንዴ ማዳን የማይችል ነው ማለት ነው፡፡ ይህም በቅዱሳት መጻሕፍት ተደጋግመው ከተጠቀሱት «አንድ ጊዜ»  ከሚሉት ኃይለ ቃላት ጋር መላተም ነው፡፡

ይቆየን
ምንጭ፡ ሐመር ጥር 2003 ዓ.ም.

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር

የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት ተወለደ ፡፡ ገላ 4፣4

በመምህር ሳሙኤል

እግዚአብሔር አምላክ ዓለምንና በውስጧ ያሉትን ፈጠረ ዘፍ 1፡1 ሌሎች ፍጥረታት ለአንክሮ ለተዘክሮ ሲፈጠሩ ሰውና መላእክት ግን ፍቅሩን ክብሩን ይወርሱ ዘንድ ተፈጠሩ፡፡

የሰው ልጅን /አዳምን/ፈጥሮ የሚያስፈልገውን አዘጋጅቶ፣ዕውቀትንና ሥልጣን ሰጥቶ፣ በጸጋ አምላክነትን ሾሞ ፣መመሪያ ሰጥቶ፣በክበር እንዲኖረው ፈቀደለት  በመጀመሪያው ዕለትና ሰዓት ከተፈጠሩት መላእክት መካከል በክብር ይልቅ የነበረው ሳጥናኤል /የኋላ ስሙ ዲያብሎስ /አምላከነት በመሻቱ ተዋርዶ ሳለ አዳምንም በተዋረደበት ምኞትና ፍላጎት እንዲወድቅ ክብሩን እንዲያወጣ ከአምላኩም እንዲለይ አደረገው፡፡  እግዚአብሔርን ፣ጸጋውን፣ሹመቱን፣ወዘተ አጣ /ኃጥአ/፡፡ ኃጢአት የሚለው ከዚህ ጽንሰ ሐሳብ የተወሰደ ነው፡፡
አዳም ከእግዚአብሔር በመለየቱና ክብሩን በማጣቱ ተጸጽቶ ንሰሐ በመግባቱ ለሥርየተ ኃጢአት የሚሆን መስዋእትም በማቅረቡ፤እግዚአብሔር አምላክ ልመናውንና መስዋእቱን ተቀብሎ እርሱንና ዘሩን ለማዳን እንደሚመጣ ቃል ኪዳን ገባለት “መልዓትንና ዓመታትን በዚህ ምድር ላይ ሠራሁልህ፡፡ይኸውም እነርሱ እስኪፈጸሙ ድረስ በምድር ላይ ትኖርና ትመላለስ ዘንድ ነው፡፡ የፈጠረችህና የተላለፍካት ከገነት ያወጣችህና በወደቅህም ጊዜ ያነሳችህ ዳግመኛም አምስት ቀን ተኩል ሲፈጸም የምታድንህ ቃሌን እልክልሃለሁ” ገድለ አዳም ብሎ እግዚአብሔር ለአዳም ነገረው እዳምም አምስት ቀን ተኩል የሚለውን ቃል ከእግዚአብሔር በሰማ ጊዜ የእነዚህን ታላላቅ ነገሮች ትርጓሜ ሊያስተውል አልቻለም፡፡ ስለዚህም እግዚአብሔር አምስት ቀን ተኩል ማለት አምስት ሺህ አምስት መቶ ዓመታት መሆናቸውን ገልጾ አርያውና አምሳያው ለሆነው ለአዳም በቸርነቱ ተረጎመለት ያንጊዜ እርሱንና  ዘሩን ለማዳን እንደሚመጣ ተስፋ ሰጠው፡፡

አዳምም ይህንን ተስፋ ለልጆቹ አስተማራቸው ልጆቹም ተስፋው የሚፈጸምበትን ጊዜ ለማወቅ በፀሐይ ፣በጨረቃና በክዋክብት /ዛሬም ቤተክርስቲያናችን ይህንን አቆጣጠር ትጠቀምበታለች/ዘመናትን እየቆጠሩ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንኃለሁ ያለውን አዳኝ ጌታ መወለድ በትንቢታቸው ይናገሩ ይጠብቁም ነበር፡፡ ከእነርሱም ውስጥ:-

1 ሱባኤ ሔኖክ
ሔኖክ ሱባኤውን ሲቆጥር የነበረው በአበው ትውልድ ሲሆን ሰባቱን መቶ ዓመት አንድ እያለ ቆጥሯል። በስምንተኛው ሱባኤ ኢየሱስ ክርስቶስ እንደሚወለድ ትንቢት ተናግሯል። አቆጣጠሩም ከአዳም ጀምሮ ነው። 8×700=5600ዓመት ይሆናል። 5500ዓመተ ዓለም ሲፈጸም ኢየሱስ ክርስቶስ እንደተወለደ ያጠይቃል።

ትንቢቱም እንዲህ ይላል። “ስምንተኛይቱ ሰንበት ጽድቅና ኩነኔ የሚታወቅባት ሱባኤ ናት፡፡ ሰይፍም ለርሰዋ ይሰጣታል ታላቁ ንጉሥ የሚመሰገንበት ቤትም በርሰዋ ይሰራል፡፡ ምሥጋናውም ዘላለማዊ ነው፡፡” ሔኖክ 35፡ 1-2 ክፍል 91 በማለት ሲተነብይ መተርጉማን እንዲህ ይመልሱታል ለርሰዋ ሰይፍ ይሰጣታል ማለቱ ጽድቅና ኩነኔ የሚታወቅበት ወንጌል ያን ጊዜ በዓለም ሁሉ ትሰበካለች ማለት ነው፡፡ የታላቁን ንጉሥ ቤት ይሠራል ማለቱ የነገሥታት ንጉሥ ኢየሱስ ክርስቶስ የሚመሰገንበት ቤተክርስቲያን ትሰራለች ማለት ነው፡፡ ምስጋናውም ዘላለማዊ ነው ማለቱ ሰውና መላእክት በአንድነት ሆነው “ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ወሰላም በምድር” እያሉ ዘወትር ያመሰግናሉ ማለት ሲሆን ስምንተኛይቱ ሰንበት ለክርስቲያኖች የተሰጠችበትን ዕለት ልደተ ክርስቶስ ናት ይሏታል፡፡

2 ሱባኤ ዳንኤል
ስለ ጌታችን ሰው መሆን ጊዜ ወስኖ ሱባኤ ቆጥሮ የተናገረው ዳንኤል ነው፡፡ የዳንኤል ሱባኤ የሚቆጠረው በዓመት ነው ፡፡ ዳንኤል ሰባው ዘመን በተፈጸመ ጊዜ እጐበኛችኋለሁ ተብሎ በኤርምያስ የተነገረውን ትንቢት እያስታዋሰ ሲጸልይ መልአኩ ቅ/ገብርኤል በሰው አምሳል ተገልጾ እንዲህ ብሎታል፡፡ “እግዚአብሔር ልምናህን ሰምቶሃልና እነግርህ ዘንድ መጥቻለሁ፡፡ አሁንም ነገሩን መርምር ራዕዩንም አስተዋሉ ኅጢአት የሚሰረይበትን ቅዱሰ ቅዱሳን ጌታም የባህርይ ክብሩን ገንዘብ የሚያደርግበት ባለው ሰባው ሊደርስ ሊፈጸም ነው ብለህ ወገኖችህን ቅጠራቸው ብሎታል፡፡” /ዳን 9፡22- 25 ኤር 29፡1ዐ/
ሰባ ሱባኤ አራት መቶ ዘጠና ዓመት ነው /7ዐX7= 490/ ይህ ጊዜ ከሚጠት እስከ ክርስቶስ መምጣት ያለው ጊዜ ነው /ትርጓሜ ሕዝ፡4፡6/

3 ሱባኤ ኤርምያስ
ኤርምያስ ከባቢሎን እንደተመለሰ በፈረሰው ቤተ መቅደስ ውሰጥ ሆኖ ሲጸልይ ሳለ ራዕይ አየ በሦስተኛው ቀንም እንዲህ ብሎ ትንቢት ተናገረ፡፡ “ፈጣሪያችንን በአንድ ቃሉ አመስግኑ የአብ የባሕርይ ልጅ ኢየሱስ ክርስቶስን አመስግኑ ከዚህ በኋላ ሰው ሊሆን ሥጋ ሊለብስ ወደዚህ ዓለም ሊመጣ የቀረው 333 ሱባኤ ዕለት ነውና እርሱ ወደዚህ ዓለም ይመጣል ዐሥራ ሁለት ሐዋርያትንም ይመርጣል…፡፡” ተረፈ ኤር 11፤37 ፣38፣42-48 ኤርምያስ ሱባኤውን የጀመረበትን ትንቢቱን የተናገረበት ራዕዩን ያየበት ዘመን ዓለም በተፈጠረ በ5 ሺህ እና 54  ዓመት ነው፡፡ ስለዚህ ትንቢቱ ከተነገረበት እስከ ክርስቶስ ልደት ያለው ጊዜ 446 ዓመት ነው፡፡

ይኸውም በኤርምያስ ሱባኤ አንዱ 49ዐ ዕለት ነው መላው ሱባኤ 49ዐX333 = 163,170 ዕለት ሲሆን ወደ ዓመት ሲለወጥ 163, 170÷365 =446 ዓመት
ኤርምያስ ሱባኤውን መቁጥር የጀመረበት ዘመን …….. 5ዐ54 ዓመተ ዓለም
ትንቢቱ ከተነገረበት ዓመት እስከ ክርስቶስ ልደት …….  446 ዓመት
በተነገረው ትንቢት በተቆጠረው ሱባኤ መሠረት 55ዐዐ ዓመት ሲፈጸም ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መወለዱ በዚህ ይታወቃል፡፡

                                                     
4 ዓመተ ዓለም የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንት በእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱሳት መጻሕፍትን መርምረው ሱባኤያትንና ሰንበታትን አውቀው ከአዳም እስከ ክርስቶስ ያለውን ዘመን ቁጥር 55ዐዐ ዓመት መሆኑን አረጋግጠዋል፡፡
ይኸውም ከአዳም አስከ ኖኅ …… 2256 ዓመት
ከኖኅ እስክ ሙሴ ……… 1588 ዓመት
      ከሙሴ እስከ ሰሎሞን ….  593 ዓመት 
ከሰሎሞን አስከ ክርስቶስ 1063 ዓመት
                55ዐዐ ዓመት
ጌታችን ኢየሱስ በተነገረው ትንቢት በተቆጠረው ሱባኤ መሠረት /ዓመተ ዓለም ፣ዓመተ ኩነኔ ፣ዓመተ ፍዳ/ አምስት ቀን ተኩል /55ዐዐ ዓመት/ ሲፈጸም /በእግዚአሔር ዘንድ 1ዐዐዐ ቀን  እንደ አንድ ቀን ናት፡፡ 2ኛ ጴጥ 3፤8 / በ5501 ዓመት ማክሰኞ ታኀሣሥ 29 ቀን ተወለደ፡፡ “ስብሐት ለእግዚአብሔር በሰማያት ስምረቱ ለሰብእ” አምላካችን እየሱስ ክርስቶስ የዘመኑ ፍጻሜ /የገባው ቃል ኪዳን፣ የተነገረው ትንቢት፣ የተቆጠረው ሱባዔ/ ሲደርስ ከእመቤታችን ቅድስተ ቅዱሳን ድንግል ማርያም የተወለደው ያጣነውን ልጅነት ሊመልስልን፣ ከተቀማነው ርስት ሊያስገባን፣ የገባንበትን እዳ ሊከፍልልን እንደሆነ ሁሉ በየዓመቱ የአምላካችንን የኢየሱስ ክርስቶስን የልደት በዓል ስናከብር ፍቅሩን እያሰብን በኃጢያታችን ምክንያት ከልባችን ያወጣነውን የሁላችንንም አምላክ ዛሬም በልባችን እንዲወለድ ያስፈልጋል፡፡
   “የተወለደው የአይሁድ ንጉሥ የት አለ?” ማቴ. 2÷1       
                                                             
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

‹ትውልድ ሁሉ የእግዚአብሔርን ቃል ተመልከቱ› /ኤር 2፥31/

ዲ/ን ብርሃኑ አድማ
‹አንድ ምድራዊ ንጉሥ ወይም ጠቅላይ ሚኒስቴር ወይም ሌላ ታላቅ ባለሥልጣን ደብዳቤ ቢጽፍልን በደስታ አናነበውምን? በእርግጠኝነት በታላቅ ደስታ የማያነበውና በልዩ ትኩረት የማይመለከተው አይኖርም፡፡ ይሁን እንጂ ከምድራዊ ባለሥልጣን እንዲህ ያለ ደብዳቤ የተጻፈለት ሰው የለም፤/ለሥራ፣ ለሹመት፣…ካልሆነ በቀር/ ከሰማያዊው ንጉሥ ግን ያልተጻፈለት የለም፣ በምድራዊ ዋጋ የማይታመን ለሕይወት መድኃኒት የሆነ ደብዳቤ ተጽፎልን ነበር። ይሁን እንጂ ለአንድ ምድራዊ ንጉሥ ደብዳቤ የምንሰጠውን ያህል ክብርና ትኩረት እንኳን አልሰጠነውም፡፡
 
መጽሐፍ ቅዱስን ማንበብ ምን ማለት እንደሆነ አልገባንምና፡፡ ወንጌልን ስናነብ እኮ ክርስቶስ ራሱ እያነጋገረን እኛም ከእርሱ ጋር እየተነጋገርንና ወደ እርሱ እየጸለይን ነበር፡፡ አንድ አባት መጽሐፍ ቅዱስን አስመልክተው የተናገሩት ነበር፡፡ በርግጥም መጽሐፍ ቅዱስ ለእያንዳንዳችን የተጻፈና የተነገረ የእግዚአብሔር ቃል ነበር፡፡ ነገር ግን እንደ ሳሙኤል ‹ባሪያህ ይሰማልና ተናገር›እንደ ኢሳይያስም ‹እኔ አለሁ› የሚል እግዚአብሔርን ሰምቶ ለመታዘዝ የተዘጋጀ ብዙም ያለ አይመስለኝም፡፡ /1ኛ ሳሙ 3፥10፣ ኢሳ 6፥8/

የእግዚአብሔር ቃል /መጽሐፍ ቅዱስ/
በመጽሐፍ ቅዱስ የተመዘገበው የእግዚአብሔር ቃል ፍጹም እውነትና ከእርሱ የተገኘ ቃል ነው፡፡ ይህም ማለት በጸሐፊዎቹ ሥጋዊ ዕውቀት ወይም አመለካከት ተጽእኖ ሥር የወደቀ አይደለም፡፡ የተጻፈው በመንፈስ     ቅዱስ መሪነት ወይም መንፈስ ቅዱስ በአደረባቸው አበው ብቻ ነውና ፡፡ «ትንቢት ከቶ በሰው ፈቃድ አልመጣምና..ዳሩ ግን በእግዚአብሔር ተልከው ቅዱሳን ሰዎች በመንፈስ ቅዱስ ተነድተው ተናገሩ» ተብሎ እንደጻፈ። ጸሐፊዎቹ በመንፈስ ቅዱስ የተመረጡ  /መንፈስ ቅዱስ ያደረባቸው/ ሰዎች ብቻ ናቸው፡፡ /2ኛ ጴጥ 1፥21/ ቅዱስ ጳውሎስም ‹የእግዚአብሔር መንፈስ ያለባቸው መጻሕፍት› በማለት ይጠራቸዋል፡፡ /2ኛ ጢሞ 3፥16/ ስለዚህ መቼም ቢሆን ትክክል ናቸው፡፡

 
ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ‹በምድር ላይ እንደተፈተነ ሰባት ጊዜ እንደተጣራ ብር የእግዚአብሔር ቃላት የነጹ ቃላት ናቸው› /መዝ1፥16/ ሲል እንደተናገረው ልንጠራጠረው ወይም ስህተት ሊኖርበት ይችላል ተብሎ የሚገመት ቃል የለም፡፡ የእግዚአብሔር ቃል ፍጹም፣ ጽሩይ ፣ንጹሕ ፣እውነተኛ ቃል ነውና፡፡ እግዚአብሔር ለሙሴ ‹ከወንድሞቻቸው መካከል እንደ አንተ ያለ ነቢይ አስነሣላቸዋለሁ፤ ቃሌንም በአፉ አደርጋለሁ፤ ያዘዝሁትንም ቃል ሁሉ ይነግራቸዋል፤ በስሜም  የሚናገረውን ቃሌን የማይሰማውን ሰው እኔ እበቀልለታለሁ› ሲል የተናገረው ቃል የነቢያቱ ወይም የሐዋርያቱ ሳይሆን የእግዚአብሔር ቃል ብቻ ስለሆነ ነው፡፡ /ዘዳ18፥18-19/ ስለዚህም በመጽሐፍ ቅዱስ የተጻፈው ሁሉ የእግዚአብሔር ቃል ብቻ ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስም ‹ቃሌን ሰምቶ የማይጠብቀው ቢኖር የምፈርድበት እኔ አይደለሁም!…እኔ ተናገርሁት ቃል እርሱ በመጨረሻው ቀን ይፈርድበታል፡፡› ያለን ቃሉ ንጹሕ የራሱ ብቻ ስለሆነ ነው፡፡ /ዮሐ 12፥47-48/ የሰው ቃል ቢሆን ሊፈርድብን አይችልምና፡፡
ቃለ እግዚአብሔር ለሕይወታችን
ያለምንም ቅድመ ሁኔታና ያለ ተጨማሪ ዓላማ የእግዚአብሔርን ቃል የምንሰማው ለነፍሳችን ድኅነት ነው፡፡ ይህም ማለት ሰማዕያኑ /ሰሚዎቹ ወይም አንባቢዎች/ የእግዚአብሔርን ቃል የምናነብበት፣ የምንሰማበት ተቀዳሚ ዓላማ ድኅነት ብቻ መሆን አለበት ለማለት ነው፡፡ ‹አስቀድማችሁ ጽድቁንና መንግሥቱን ፈልጉ፤ ሌላው ሁሉ ይጨመርላችኋል› /ማቴ 6፥33/ መባላችንን መዘንጋት የለብንም፡፡ እኛ ለነፍሳችን ድኅነት ስንሰማው ከእግዚአብሔር የምንቀበለው እጅግ ይበዛል፡፡ ‹ይጨመርለችኋል› ያለን አምላካችን ይጨምርልን ዘንድ የታመነ ነው፡፡ በዚህም መሠረት ጥቂቶቹን ጥቅሞች እንመልከትና እንዴት ማንበብና መማር እንዳለብን እንመልከት፡፡
ሀ/ ለሕይወተ ነፍስ፡- ‹ሲሳያ ለነፍስ ቃለ እግዚአብሔር ውእቱ፤ የነፍስ ምግቧ የእግዚአብሔር ቃል ነው› እንደተባለ ያለ እግዚአብሔር ቃል ለድኅነት የምትበቃ ነፍስ የለችም፡፡ ጌታ በወንጌል ‹እውነት እውነት እላችኋለሁ፤ ቃሌን የሚጠብቅ ቢኖር ለዘለዓለም ሞትን  አያይም/ ዮሐ8፥51/ ያለው ድኅነት ነፍስን የሚያስገኝ ስለሆነ ነው፡፡ በዚሁ ምዕራፍ ላይ ‹ከእግዚአብሔር የሆነ የእግዚአብሔርን ቃል ይሰማል› ያለውም ያለ ቃለ እግዚአብሔር የእግዚአብሔር መሆን ስለማይቻል ነው፡፡ / ዮሐ 8፥47/ ቃሉን የሚሰሙ፤ እንደሰሙም የሚኖሩት ግን በሰላምና በሕይወት ይኖራሉ፡፡ ራሱ ጌታም ‹እኔ የነገርኋችሁ ቃል መንፈስ ነው፤ ሕይወትም ነው፡፡› ብሏልና፡፡ /ዮሐ 6፥63/ ቅዱስ ጳውሎስም ቅዱሳት መጻሕፍት ሰውን ለፍፁምነት የሚያበቁ፣ በጎ የሚያደርጉ፣ በተግሣጽ ልብን የሚያጸኑና በትምህርት እያነጹ በጽድቅ ላለው ምክር እንደሚጠቅሙ አስረግጦ ያስተምራል፡፡ /2ኛ ጢሞ 3፥16-17 ፣ ሮሜ 15፥3-4/ ነቢየ እግዚአብሔር ቅዱስ ዳዊትም ሕጉን /መጻሕፍትን/ በቀንም በሌሊትም የሚያነብ ሰው ቢኖር ቅጠሎቿ እንደማይረግፉና ፍሬዋን በየጊዜው እንደምትሰጥ በወንዝ ዳር እንደተተከለች ዛፍ ይሆናል፤ ይላል፡፡ /መዝ 1፥2-3/
ለ/ ለሕይወተ ሥጋ፡- ጌታችን በወንጌል ‹ሰው በእንጀራ ብቻ አይኖርም፤ በእግዚአብሔር ቃልም ጭምር ነው እንጂ› እንዳለ ቃለ እግዚአብሔር ለሥጋዊ ሕይወታችንም ይጠቅመናል፤ /ማቴ 4፥4/፡፡ ነቢየ እገዚአብሔር ቅዱስ ዳዊት ‹ቃልህ (ሕግህ) ለእግሬ መብራት ለመንገዴም ብርሃን ነው› እንዳለ ቅዱሳት መጻሕፍትን የሚያነቡ ሰዎች መንገዳቸው ሁሉ የተቃና ይሆንላቸዋል፡፡ /መዝ118፥105/ ሳምራዊቷ በእርሷ ተሰውሮ አምስት ባሎቿን ከገደለባት መንፈስ ርኩስ ነጻ የወጣችው የእግዚአብሔርን ቃል በመስማት ነው፡፡ /ዮሐ4፥7-40/  መቶ አለቃው ‹ቃል ብቻ ተናገር ብላቴናዬም ይፈወሳል› በማለቱ እንደ እምነቱ ተደርጎለታል፡፡ ይህም ብቻ አይደለም ዓለሙ ሁሉ የተፈጠረው በእግዚአብሔር ቃል ነውና የእግዚአብሔር ቃል የጎደለብንን ሁሉ ይሞላል፡፡ ቅዱስ ዳዊት «የቃልህ ፍቺ ያበራል ፤ሕጻናትንም ጠቢባን /አስተዋዮች/ ያደርጋል፤ አፌን ከፈትሁ አለከለክሁም፤ ወደ ትእዛዝህ ናፍቄአለሁና» እያለ ናፍቆቱን የሚናገረው ከቃለ እግዚአብሔር የማይገኝ ዕውቀትና ጥበብ ስለሌለ ነው፡፡ /መዝ 118፥129-131/

እግዚአብሔር ይነግሮሙ ለሕዝቡ በመጽሐፍ /መዝ 86፥6/

ቅዱስ ዳዊት ‹እግዚአብሔር ለሕዝቡ በመጽሐፍ ይነግራቸዋል› ይላል፡፡ ስለዚህም እግዚአብሔር እንዲነግረው የፈለገ ሁሉ ቅዱሳት መጻሕፍትን ማንበብ ይጠበቅበታል፡፡ ነቢየ እግዚአብሔር ኤርምያስም ‹ትውልድ ሁሉ የእግዚአብሔርን ቃል ተመልከቱ› የሚለን ቅዱሳት መጻሕፍትን በማንበብና በማድመጥ እንድንጠቀም ነው፡፡ ለመሆኑ አንድ ሰው መጽሐፍ ቅዱስን ለማንበብ አስቀድሞ መገንዘብ ያለበት ጉዳይ ምንድ ነው?  የሚለውን መረዳት ያፈልጋል፡፡

ሀ/ መጽሐፍ ቅዱስን በቤተ ክርስቲያን መንፈስ መረዳት

በመጀመሪያ ደረጃ መጽሐፍ ቅዱስን ከቤተ ክርስቲያን እንደተቀበልነው ወይም እነዳገኘነው መረዳት ያስፈልጋል፡፡ ቤተክርስቲያን ስንልም ክርስቶስ መሠረቷ ጉልላቷ የሆነላት /1ኛ ቆሮ 3፥6፣ ዕብ 6፥1፣ ኤፌ 5፥22/ በምድርም፣ በገነትም፣ በብሔረ ብፁአንና በብሔረ ሕያዋን ያሉት የቅዱሳን ሰዎችና የማኅበረ መላእክት አንድነት ማለታችን ነው፡፡ ቅዱስ የሆነው ትውፊት ወይም ቅብብል እስከ ዘመነ ሊቃውን ካደረሳቸው በኋላ በቤተ ክርስቲያን ቀኖና ተወስነዋል፡፡ ስለዚህ አንድ አማኝ መጽሐፍ ቅዱስን እንደሌላ የፍልስፍና መጽሐፍ በፈለገው መንገድ ሊተነትነው አይችልምም፣ አይገባምም፡፡ ከቤተ ክርስቲን የተቀበለው ከሆነ በቤተ ክርስቲያን /በኅብረቱ በአንደነቱ መንፈስ/ ሆኖ መረዳት ይገባዋል፡፡ ኢትዮጵያዊው ጃንደረባ «የሚተረጉምልኝ ሳይኖር ይህ እንዴት ይቻለኛል?» /ሐዋ 8፥31/ ያለው ራሱን በኅብረቱ ውስጥ አድርጎ ስለሚያኖርና የእነርሱንም ርዳታ ስለሚሻ ነበር፤ አገኘም፡፡ ሉቃስና ቀልዮጳ ‹በመንገድ ሲናገረን መጻሕፍትንም ሲከፍትልን /ሲተረጉምልን/ ልባችን ይቃጠል አልነበረምን?› የተባባሉት መጻሕፍትን መረዳት የሚቻለው በቤተ ክርስቲያን መንፈስ /ትምህርት፣ ትርጓሜና ሥርዓት መሠረት /ማንበብና ማጥናት ስንችል ብቻ ስለሆነ ነው፡፡ /ሉቃ 24፥32/ ቅዱስ ጴጥሮስም «በመጽሐፍ ያለውን ትንቢት ሁሉ ማንም ለገዛ ራሱ ሊተረጉም አልተፈቀደው….» የሚለው ለዚህ ነው፡፡ /2ኛ ጴጥ 1፥20/ ያለ ትርጓሜ መንፈስ የምናነብ ከሆነ ከቤተ ክርስቲያን የመውጣት ዕድላችን ሰፊ ነውና እንጠበቅ፡፡

ለ/ በመታዘዝ ማንበብ፡-

መጻሕፍቱ በመንፈስ ቅዱስ መሪነት ተጽፈዋል ብሎ የሚያምን ሰው ሲማር የሚሰማው፤ ሲያነብም የሚያዳምጠው በመታዘዝ መንፈስ ነው፤ ቃሉ በሰው ቋንቋ  የተጻፈ የእግዚአብሔር ድምጽ ነውና፡፡ ስለዚህ አንድ አማኝ በሚያነብበት ጊዜ ራሱን አስገብቶ ከመጻሕፍቱ ባለቤት ከእግዚአብሔር በትሕትና መንፈስ በማድመጥ ያነብባል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ‹ከጥንት ጀምሮ እግዚአብሔር በብዙ ዓይነትና ጎዳና ለአባቶቻችን በነቢያት ተናግሮ….›› ስለሚል መንገዱ ቢለያይም ነገሩ ሁልጊዜም ለእኛ ሁሉ ነው፡፡ /ዕብ1፥1/ ስለዚህ በመታዘዝ ማንበብ ማለት አንደኛ በማድነቅ/በተመስጦ/ ሁለተኘ ለራስ በማድመጥ ማንበብ ነው፡፡ ይህም ቅድስት ድንግል ማርያም ‹‹ይኩነኒ በከመ ትሌበኒ፣ እነደ ቃልህ ይሁንልኝ ›› እንዳለችው ቃሉን በእምነት በመቀበልና በመታዘዝ ማንበብ ነው፡፡

ሐ/ ለእኔ ብሎ ማንበብ፦

እውነት የመጽሐፍ ቅዱስ አንባቢ ለራሱ ብሎ ያነባል፡፡ ለምሳሌ አንድ ሰው በዝሙት የተከሰሰችውን ሴት ታሪክ ቢያነብ ያን ጊዜ እርሷን ወክሎ መናዘዝ፣ራሱን መክሰስ ይገባዋል፡፡ ‹‹በሰላም ሒጂ›› የሚለው ቃል ላይ ሲደርስም ክርስቶስ ለራሱ እንደተናገረው እየሰማ ሥርየተ ኃጢአት ማግኘትን እየተቀበለ ያነባል፡፡ /ንስሐ አያስፈልግም ማለት አይደለም/፡፡ ይህንኑ አለፍ ብሎም ‹‹ዳግመኛም ኃጢአት አትሥሪ›› የሚለውን አድምጦ ዳግም ኃጢአት ላለመሥራት እየታዘዘ ማንበብ አለበት፡፡ በዚህ መንገድ ካልሆነ የሌሎች ሰዎች ታሪክን የሚያነብ ይመስለውና ሳይጠቀም ይቀራል፡፡ ስለዚህ የአዳምን ታሪክ ሲያነብ የወደቀው፤ የእግዚአብሔርንም ድምጽ ለራሱ አድርጎ ይሰማል፡፡ ‹‹አዳም አዳም ወዴት ነህ›› የሚለውን ‹‹ እኔ ወዴት ነኝ›› እያለ ያነበዋል፡፡ እግዚአብሔር ለቃየል ‹‹ወንድምህ አቤል ወዴት ነው?›› ሲል የጠየቀው የእኔ ወንድሞች /ክርስቲያኖች፣ ደቂቀ አዳም…/ ወዴት ናቸው? እያለ ያነባል እንጂ አርቆ አያነብም፡፡ በዚህም የእግዚአብሔርን የምሕረት ድምጽ ይሰማል፡፡ ስለጠፋው በግ፣ ስለጠፋው ልጅ፣ ስለፈሪሳውያን ፣….. ስለሌሎችም ሲያነብ የሚያስበው ራሱን ነው፣ወይም እራሱን ከእነዚያ እንደ አንዱ በመቁጠር ያነባል፤ ያን ጊዜ በትክክል እግዚአብሔር ለእርሱ የሚለውን ይሰማል፡፡

ማጠቃለያ

በሊቃውንት ዘንድ ቅዱሳት መጻሕፍት ለማንበብ ከዚህ በላይ ግንዛቤና ዝግጅት የሚያስፈልገው ቢሆንም እኛ ለመጀመር ያህል እንኳን መጽሐፍ ቅዱሳችንን በዚህ መንገድ እንቅረበው፡፡ በዚያን ጊዜ ‹‹እኔ ስጸልይ ለእግዚአብሔር እየተናገርኩ ነው፡፡ መጻሕፍትን ሳነብ ደግሞ እግዚአብሔር ለእኔ የሚናገረውን እሰማለሁ›› ያሉት ሊቅ ሕይወትን ገንዘብ ማድረግ እንችላለን፡፡የአሁን ዘመን የእግዚአብሔርን ቃል የምንራብበትም ዘመን ነው፡፡ ‹‹ እነሆ በምድር ላይ ራብን የምሰድበት ዘመን ይመጣል? ይላል ጌታ እግዚአብሔር፡፡ እርሱም የእግዚአብሔር ቃል ከመስማት እንጂ እንጀራን ከመራብና ውኃን ከመጠማት አይደለም፡፡ ከባሕርም እስከ ባሕር ድረስ፤ ከሰሜንም እስከ ምሥራቅ ድረስ ይቅበዘበዛሉ፤ የእግዚአብሔርን ቃል ለመሻት ይሯሯጣሉ፤ አያገኙትምም፡፡ በዚያ ቀን መልካሞች ደናግል ጎበዛዝትም በጥም ይዝላሉ››ተብሎ እንደተጻፈ ነፍሳት በርግጥም ተጠምተዋል፡፡/አሞ 8፥11-14/
ረሀብ የተፈጠረው ግን በመጻሕፍት ወይም በመምህራን አለመኖር አይደለም፡፡ በሰው ወይም በሰማዕያንና በአንባብያን አለመዘጋጀት ነው ማለት ይቻላል፡፡ ምእመናን ስንሰማም ሆነ ስናነብ መንፈሳችንን ከሥጋዊ ዓላማ ‹‹ የእግዚአብሔር ልጅስ ከሆንክ ይህንን ድንጋይ ዳቦ አድርግ›› በማለት ሰይጣን ከሚያቀርበው ፈተና ማለትም መንፈሳዊ ነገርን ለምድራዊ ጥቅም ከማዋል ርቀን በቤተ ክርስቲያን መንፈስ፣ ለእኔ እግዚአብሔር ምን ይለኛል? ቤተ ክርስቲያን ምን ትላለች? በማለት በመታዘዝ መንፈስ ተዘጋጅተን ከመጣን እግዚአብሔር ይናገረናል፡፡ ‹‹ የልብ መዘጋጀት ከሰው ነው የምላስ /የጸሎትና የዝግጅት/ መልስ ግን ከእግዚአብሔር ዘንድ ነው›› ተብሎ ተጽፎአልና /ምሳ 16፥1/
ስለዚህ ከስሜት፣ ከእልህ፣ ከመብለጥና ከመፎካከር ስሜት ወጥተን እናንብበው፤ ያን ጊዜ በግጥም ‹‹ የእግዚአብሔርን ቃል ተመልከቱ›› የሚለውን ትእዛዝ እንፈጽማለን፤ እግዚአብሔርም ምስጢሩን ይገልጽልናል፤ ለድኅነትም ያበቃናል፡፡
                                                
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ታቦት

ትምህርት ሃይማኖት (የሃይማኖት ትምህርት) በሁለት ይከፈላል፡፡ ይኸውም፦
1ኛ፡- ዶግማ   2ኛ፡- ቀኖና በሚል ነው፡፡
ዶግማ፡- ቃሉ የግሪክ ሲሆን ፍችውም እምነት ማለት ነው፡፡

ቀኖና፡- ደግሞ ቃሉ የግሪክ ሲሆን ሥርዓት ማለት ነው፡፡ ከእነዚህ ከሁለቱ ዶግማ ወይም እምነት አይጨመርበትም፤ አይቀነስበትም፤ አይሻሻልም፤ ችግርና ፈተናም ቢመጣ እስከ ሞት ድረስ አጥብቀን የምንይዘው ነው፡፡ ለምሳሌ ያህል ይህን ዓለም ካለመኖር ወደ መኖር አምጥቶ የፈጠረ፤ ቢመረምር እንጂ የማይመረመር ሁሉን ቻይ አምላክ፤ የሚሳነው ነገር የሌለ ፈጣሪ፤ የሰማይና የምድር ባለቤት የሠራዊት ጌታ ሕያው እግዚአብሔር ነው፡፡

እግዚአብሔር (ፈጣሪ) የአካል ሦስትነት አለው፡፡ በመለኮት፣ በመፍጠር፣ በሥልጣን፣ በአገዛዝ፣ በፈቃድ ግን አንድ ነው፡፡ በሦስትነቱ አብ፤ ወልድ፤ መንፈስ ቅዱስ ሲባል በአንድነቱ አንድ መለኮት አንድ እግዚአብሔር ይባላል፡፡ በአዳም ምክንያት ከመጣው የዘለዓለም ሞትና ከዲያብሎስ ባርነት ነጻ የወጣነው ከሦስቱ አካላት በአንደኛው አካል ማለትም በወልድ በኢየሱስ ክርስቶስ ነው፡፡ ይህ ዶግማ ወይም እምነት ይባላል፡፡

ቀኖና ግን በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ አምነው ያደጉ ክርስቲያኖች የሚመሩበት ሥርዓት ስለሆነ፤ በሃይማኖት አባቶች ወይም በቅዱስ ሲኖዶስ አማካኝነት እንደጊዜው ሁኔታ የሚሻሻል በመሆኑ የሚጨመርበት፤ የሚቀነስለት ነው፡፡ ለምሳሌ ያህል እኛ ኦርቶዶክሳውያን የምንጠመቀው ሴት በሰማንያ ወንድ በአርባ ቀናችን ነው፡፡ የተወለዱ ሕጻናት ሴቷ ሰማንያ ወንዱም አርባ ቀን ሳይሞላቸው ቢታመሙና በሽታው አስጊ ከሆነ በ10፣ በ20፣ በ30…ቀናቸው መጠመቅ ይችላሉ ቀኖና ነውና፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን የቀዳስያን ብዛት መነሻው አምስት ነው፡፡ ምናልባት ከአምስቱ አንዱ፤ ሁለቱ፤ ሦስቱ ቢታጡና ሌላም ተፈልጎ እስከ መጨረሻ የማይገኝ ከሆነ ከአቅም በላይም የሆነ ችግር ከገጠመ ሁለቱ ወይም አንዱ ብቻ ቀድሰው ማቁረብ ይችላሉ፡፡ ቀኖና ነውና፡፡ በቤተ ክርስቲያናችን ታቦት ሲከብር ቤተ ክርስቲያኑን የሚዞረው ሦስት ጊዜ ነው ችግር ካለ አንድ ጊዜ ብቻ ዑደት ተፈጽሞ ሊገባ ይችላል። ቀኖና ነውና፤ ስለቀኖና (ስለሥርዐት) ቅዱስ ጳውሎስ በመልእክቱ እንዲህ ሲል ጽፏል።

1. ‹‹ነገር ግን ሁሉን በአግባብና በሥርዐት አድርጉ፡፡›› 1ኛ ቆሮ. 14፥40፡፡
2. ‹‹ወንድሞች ሆይ በሠራንላቸው ሥርዐት ሳይሆን በተንኮል ከሚሄዱት ወንድሞች ሁሉ ትለዩ ዘንድ በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም እናዝዛችኋለን፡፡ እኛን ልትመስሉ እንደሚገባችሁ እኛም በእናንተ መካከል ያለ ሥራ እንዳልኖርን ራሳችሁ ታውቃላችሁ›› 2ኛተሰ. 3፥6-7›› ቀኖና (ሥርዐት) የሚወሰነው በሃይማኖት አባቶች እንደሆነና ወንጌልን የሚስተምር ሰው ለሚያስተምራቸው ክርስቲያኖች በሃይማኖት አባቶች የተወሰነ ቀኖና ማስተማርና መሰጠት እንዳለበት መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ሲል ያስረዳል፡፡

በየከተማውም ሲሄዱ፥ ሐዋርያትና ቀሳውስት በኢየሩሳሌም ያዘዙትን /የወሰኑትን/ ሥርዐት አስተማሯቸው፡፡ አብያተ ክርስቲያናትም በሃይማኖት ጸኑ ዕለት ዕለትም ቁጥራቸው ይበዛ ነበር፡፡›› ይላል የሐዋ. 16፥4-5፡፡ በዚህ የእግዚአብሔር ቃል መሠረት ቅዱስ ጳውሎስ ደርቤንና ልስጥራን በተባሉ ቦታዎች ለነበሩ ክርስቲያኖች ወንጌልን ከሰበከ በኋላ ሐዋርያት የወሰኑትን ቀኖና (ሥርዐት) እነደሰጣቸው እንረዳለን፡፡ ስለዚህ ቀኖና ወይም ሥርዐት ቤተክርስቲያንን ይጠቅማል እንጂ አይጎዳም፡፡ በመሆኑም ዶግማንና ቀኖናን ወይም እምነትንና ሥርዓትን ጎን ለጎን ይዞ መጓዝ ሐዋርያትን መከተል እንጂ ወደ ኋላ ተመልሶ አይሁድን መከተል አይደለም፡፡ እንግዲህ ሥርዐተ ቤተ ክርስቲያንን የሚቃወሙ ሰዎች ሁሉ፤ የሚቃወሙት በቀኖና (በሥርዐት) የሚመሩትን ክርስቲያኖች ሳይሆን የእግዚአብሔር ቃል የሆነ መጽሐፍ ቅዱስን በመሆኑ እንዳይሳሳቱ አደራ እንላለን፡፡

አሁን እንግዲህ የዶግማንና የቀኖናን ልዩነት ከተረዳን በቀጥታ ወደ ታቦቱ ጥያቄ እንሄዳለን፡፡

ጥያቄ፡-1 ዛሬ በእኛ ቤተክርስቲያን ያለው ታቦት ነው? ወይስ ጽላት በታቦትና በጽላት መካከል ልዩነት አለና፡፡

መልስ፡- ታቦት የጽላት ማደሪያ ነው፡፡ ዘዳ 40፥20፡፡ ጽላት ደግሞ ቅዱስ ቃሉ የተጻፈበት ሰሌዳ ማለት ነው፡፡ ዘዳ 34፥27-28፡፡ ስለዚህ እነዚህ ሁለት ነገሮች ዛሬም በሐዲስ ኪዳን አሉ። ሆኖም ግን አሠራሩ ሙሉ በሙሉ በዘጸ 25፥10-18 ያለውን የሙሴን ሕግ የተከተለ አይደለም፡፡ ምክንያቱም፤

1ኛ፡- ታቦት እንደሙሴ ሕግ የሚዘጋጀው ከግራር እንጨት ሆኖ ርዝመቱ ሁለት ክንድ ተኩል፤ ወርዱም አንድ ክንድ ተኩል ቁመቱም አንድ ተኩል ይሁን ይልና በውስጥና በውጭም በጥሩ ወርቅ ለብጠው፤ በዙሪያውም የወርቅ አክሊል አድርግለት ይላል፡፡ ደግሞም ታቦቱን የሚሸከሙት ከወርቅ በተሠሩ መሎጊያዎች አራት ሰዎች እንደሆኑ እንረዳለን፡፡ በአጠቃላይ የብሉይ ኪዳን የታቦት አሠራር እጅግ ከባድ በመሆኑ በሁሉም ዘንድ አይቻልም ነበር፡፡ ምናልባት አንዳንድ የቤተክርስቲያን ፍቅር የነበራቸው ነገሥታትና ዛሬም ፍቅረ ቤተክርስቲያን ያላቸው አንዳንድ ምዕመናን ይችሉት እንደሆነ ነው እንጂ፡፡

2ኛ፡- ጽላት፤ ጽላትም እንደሙሴ ሕግ ከሆነ መዘጋጀትና መጠረብ ያለበት ከከበረ ድንጋይ ነው፡፡ በአንድ ታቦት ውስጥም መቀመጥ ያለባቸው ሁለት ጽላቶች ናቸው፡፡ ዘዳ 34፥1፡፡ በአጠቃላይ እንደ ብሉይ ኪዳኑ ሕግና ሥርዐት ከባድ ነው፡፡ የብሉይ ኪዳኑ ሥርዐትም ለሐዲስ ኪዳኑ ሥርዓት ጥላ ሆኖ አልፏል፡፡ 2ኛ ቆሮ 3፥7-11 ፤ ቆላ 2፥17፤ ዕብ 10፥1፡፡

እንግዲህ እዚህ ላይ የሐዲስ ኪዳኑ ታቦትና ጽላት የብሉይ ኪዳኑን የታቦት አሰራርና ሥርዐት ጠንቅቆና ተከትሎ የማይሄድ ከሆነ፤ ይህ የብሉይ ኪዳኑን የታቦትና የጽላት አቀራረጽ ሥርዐት ጠንቅቆ ያልሄደ የሐዲስ ኪዳን ታቦትና ጽላት ከየት መጣ የሚል ጥያቄም ሳይነሳ አይቀርም፡፡

አንባብያን ሆይ በቀጥታ ወደ ጥያቄው ከመግባታችን በፊት በዚህ ጽሑፍ ዶግማ ላይ ስለዶግማና ቀኖና ማብራሪያ የሰጠነው ይህን ለመሰለው ጥያቄ እንዲጠቅም ነው፡፡ አሁን ወደ ሐዲስ ኪዳን ታቦትና ጽላት ስንሄድ ቁም ነገሩ እንደሚከተለው ነው፡፡

የሐዲስ ኪዳን የታቦትና የጽላት አቀራረጽም ሆነ አጠቃቀሙ የተወሰነውና የሚወሰነው በቀኖና ነው፡፡ ቀኖና ደግሞ እንደ ሁኔታው የሚሻሻል ነው፡፡ ሲቻል ይጨመርበታል ሳይቻል ደግሞ ይቀነስለታል፡፡ እንግዲህ በቤተክርስቲያናችን ቀኖና ካበረከታቸው ነገሮች አንዱ የሐዲስ ኪዳን የታቦትና የጽላት አቀራረጽንና አጠቃቀምን ነው፡፡

ስለዚህ በሐዲስ ኪዳን ታቦትን ለመቅረጽ የግራር እንጨት ባይገኝ በዘፍ 1፥31 ላይ ‹‹ እግዚአብሔርም የፈጠረውን (ያደረገውን) ሁሉ እጅግ መልካም እንደሆነ አየ›› ስለሚልና እግዚአብሔር የፈጠረውን ስለማይንቅ ከግራር ሌላ ከማይነቅዝ እንጨት መቅረጽ እንችላለን፡፡ ቁመቱ ወርዱና ዙሪያውም እንደችሎታችን ይሆናል፡፡ በውስጥና በውጭ ስለሚሆነው የወርቅ ክብርም እንደችሎታችን ይወሰናል፡፡ ከሌለንም ወርቁ ይቀራል ቀኖና ነውና፡፡

ስለጽላቱም እንደዚሁ ነው ከቻልን ከከበረ ድንጋይ፣ ከዕብነ በረድ መቅረጽ እንችላለን፤ ካልቻልን ጽላቱን ከማይነቅዝ እንጨት መቅረጽ እንችላለን፡፡ በሌላ በኩልም ከቻልን እንደ ብሉይ ኪዳኑ በአንድ ታቦት ሁለት ጽላት ማስቀመጥ እንችላለን፤ ካልቻን በአንድ ታቦት አንድ ጽላት ብቻ ይሆናል፡፡ በተጨማሪም የጽላቱን ማስቀመጫ ታቦት ባይኖረን ጽላቱን ታቦት ብለን በመጥራት በጽላቱ ብቻ መጠቀም እችላለን ቀኖና ነውና፡፡

በተጨማሪም በኤር 31፥31፤ 2ኛ ቆሮ 3፥1-3፤ በዕብ 8፥8-13፡፡ የእኛ አካልና ልቡና የእርሱ ታቦትና ጽላት አልሆነም ወይ? በሐዲስ ኪዳን ለምን ታቦትና ጽላት አስፈለገ? ለምንስ ይህ ሁሉ ተፈጠረ የሚሉ አሉ፡፡ የክርስቲያኖች  አካልና ልቡና በክርስቶስ ደም ታቦት፤ ጽላት፤ ቤተ መቅደስ መሆኑን እናምናለን፡፡ ቢሆንም በሐዲስ ኪዳን ታቦትና ጽላት ያስፈለገበት ምክንያት ስለአምላካችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አምላክነትና ክብር ሲባል ነው፡፡ ምክንያቱም በብሉይ ኪዳን ክብሩን የገለጠበት፤ ቃሉን ያሰማበት፣ ሙሴን እንደባልጀራ ያነጋገረበት፣ የክብሩ ዙፋን ሆኖ ጽላቱ በውስጡ ለታቦቱ ማደሪያ በመሆኑ፤ በሐዲስ ኪዳንም የሥጋውና የደሙ የክብር ዙፋን እንዲሆን ሲሆን ስለእኛ በዚህ ዓለም መከራ የተቀበለውን መድኅኔዓለም ክርስቶስን ለማክበር ሲባል ነው፡፡

ጥያቄ2፡- በዘዳ 31፣18፣32፣15፣134፣1-5፡፡2ኛዜና 5፣10 ያሉትን ጥቅሶች በመጥቀስ እግዚአብሔር ለሙሴ የሰጠው ሁለት ጽላቶችን ብቻ ነው፡፡ ነገር ግን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን እነዚህን እልፍ አእላፋት ጽላቶች ከየት አመጣቻቸው? አራብታችሁ ቅረጹ የሚል አለ ወይ?

መልስ፡- በዘዳ 32፥19፡፡ ስንመለከት እግዚአብሔር ራሱ አዘጋጅቶ ለሙሴ የሰጠውን ሁለቱን ጽላቶች እሥራኤል ጣዖት ሲያመልኩ ስላገኛቸው ሙሴ ተበሳጭቶ ሰብሯቸዋል፡፡ነገር ግን ቸርነቱ ለዘለዓለም የሆነ እግዚአብሔር አምላክ  ለሙሴ የመጀመሪያዎቹን አስመስሎ እንዲሰራ ነገረው፤ ሙሴም አስመስሎ ሠራ፡፡ ዘዳ 34፥1-5 መሥራት ብቻ ሳይሆን ዐሥሩን የቃል ኪዳን ቃላትም በጽላቶቹ ላይ እንዲጽፍ ሙሉ ሥልጣን ከእግዚአብሔር ተሰጠው፡፡ ሙሴም ተፈቅዶለታልና አሥሩን ቃላት በጽላቶቹ ላይ ጻፈ፡፡ ዘዳ 34፥27-28 ከዚህ ጊዜ ጀምሮ ጽላትንም ሆነ ታቦትን እያስመሰሉ ለመሥራት ሙሉ ሥልጣንን አግኝተናል፡፡ ይህን በተመለከተ አንዳንድ አባቶች እንዲህ ይላሉ፤

‹‹አዳም እንኳን በደለ አዳም ባይበድል ኖሮ አምላክ ሰው ሆኖ በቀራንዮ ስለእኛ የመሰቀሉን፤ ስለኛ የመሞቱን የፍቅር ምስጢር አናውቀውም ነበር፡፡››

እስራኤልም በጥጃ ምስል ጣኦት አምልከው እንኳን በደሉ እሥራኤል ባይበድሉ ሙሴ በእግዚአብሔር የተዘጋጁት ሁለቱ ጽላቶች’ የሰው ልጅም እግዚአብሔር የሠራቸውን የፊተኞቹን አስመስሎ ለመሥራት ስልጣን ባልኖረውም ቢሠራም ለምን ሠራህ ለሚለው መረጃ ባላቀረበም ነበር›› ይላሉ፡፡ ያም ሆነ ይህ ጽላትን አስመስለን፤ አባዝተን፤ አራብተን ለመሥራት መሠረታችን ሥልጣኑ ለኛ ለልጆቹ የተላለፈልን ከአባታችን ከሙሴ ነው፡፡››

ሙሴ የተሰበሩትን አስመስለህ ሁለት ጽላቶች ቅረጽ ከሚል በቀር ጽላቶችን አብዝታችሁ፤ አራብታችሁ ተጠቀሙ የሚል ቀጥተኛ ቃል አምጡ ለሚለው ግን ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ በብሉይ ኪዳን የጽላትም ሆነ የቤተ መቅደስ ሥርዐት፤ የመስዋዕቱ የዕጣኑ አገልግሎት፤ በኢየሩሳሌም ብቻ ስለነበረና፤ የሌላውም አገር ሕዝብ የሚከተለው የጣዖትን ሥርዓት እንጂ የሙሴን ሥርዐት ባለመሆኑ ጽላቱ ተባዝቶ ተራብቶ ለሌላው አገር ሕዝብ አልተሰጠም፡፡ እግዚአብሔርም ከኢየሩሳሌም ውጭ አልፈቀደም የተቀደሰውን ጣዖታውያኑ አሕዛብ ያረክሱታልና ስለዚህ ስግደቱም የቤተመቅደስ ሥርዐቱም በኢየሩሰሳሌም ብቻ ነበር። /ዮሐ 4፥18-24/

በኢየሩሳሌም ይኖሩ የነበሩ አሕዝቦችም ሠሎሞን ያሠራው ታላቁ ቤተ መቅደስና ሁለቱ ጽላቶች አንሰውናል፤ በርቀት የምንገኝ እኛ የመንገድ ድካም በዝቶብናልና፡፡ ስለዚህ በያለንበት ቤተ መቅደስ ሠርተን ጽላቱን አክብረን መገልገል እንፈልጋለንና ይፈቀድልን ብለው ሙሴም ከሁለቱ ጽላቶች በቀር ሌላ አልተፈቀደም ብሎ መልስ የሰጠበት ቦታ የለም፡፡

ያም ሆነ ይህ በሐዲስ ኪዳንም በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ አምነው በአብ፤ በወልድ፤ በመንፈስ ቅዱስ ስም ተጠምቀው ፤ሁለተኛ የድኅነት ልደት ተወልደው የእግዚአብሔር ልጆች እንዲሆኑ ሥልጣን ሰጣቸው። ለክርስቲያኖችም ከፀሐይ መውጫ እስከ ፀሐይ መግቢያ ድረስ እንደሚበዙና በአዲስ ኪዳን በአምላካችን በኢየሱስ ክርስቶስ ስም ንጹሕ የሆነውን ቁርባን ከኢየሩሳሌም ውጭ በየቦታው ለእግዚአብሔር ማቅረብ እንደሚችሉ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፡፡

1. ‹‹ ከፀሐይ መውጫ ጀምሮ እስከ መግቢያዋ ድረስ ስሜ በአሕዛብ ዘንድ ይከበራልና፤ በየስፍራው ለስሜ ዕጣን ያጥናሉ፤ ንጹሕንም ቁርባን ያቀርባሉ፤ ስሜ በአሕዛብ ዘንድ ታላቅ ይሆናልና ይላል ሁሉን የሚችል እግዚአብሔር›› ሚል 1፥11፡፡
2. ‹‹ ቤቴ ለአሕዛብ ሁሉ የጸሎት ቤት ትባላለች ተብሎ ተጽፎ የለምን? እናንተ ግን የወንበዴዎች ዋሻ አደረጋችኋት ብሎ አስተማራቸው›› ማር11፥17፤ ኢሳ 56 ፥ 7፤ ኤር 7፥11 ፡፡

ይህ ትንቢት በቀጥታ ለሐዲስ ኪዳን ክርስቲያኖች መሆኑ ግልጥ ነው፡፡ ምክንያቱም በብሉይ ኪዳን ቤተ መቅደስም ሆነ የዕጣን፤ የቁርባን አገልግሎት እንኳን ከፀሐይ መውጫ እስከ ፀሐይ መግቢያ ድረስ ላሉ አሕዛብ በኢየሩሳሌም ከሚኖሩ የእግዚአብሔር ሕዝቦች በቀር ለእስራኤል ጎረቤት አገሮች እንኳ አልተፈቀደምና፡፡ ነቢዩ ሚልክያስ ንጹሕ ዕጣን ያለው በማቴ 2፥11፡፡ ወንጌል እንደተናገረው ከአሕዛብ ወገን የሆኑ ሰብአ ሰገል በቤተልሔም ዋሻ ለክርስቶስ ካቀረቡት ጀምሮ እስከ ዛሬ ድረስ በዓለም ያለን ክርስቲያኖች በክርስቶስ ስም ለክርስቶስ የምናቀርበው ቅዱስ ዕጣን ነው፡፡

ንጹሕ ቁርባን የሚለውንም በማቴ 26፥26፤ ጌታ ኅብስቱን አንሥቶ ነገ የሚቆረሰው ሥጋዬ ይህ ነው፤ ወይኑንም አንሥቶ ነገ ስለብዙዎች ሀጢአት የሚፈሰው ደሜ ይህ ነው ብሎ ለሐዋርያት የሰጣቸው የክርስቶስ ሥጋና ደም ነው፡፡ ንጹሕ የተባለው እርሱ በባሕርዩ ንጹሕ ሆኖ የእኛን የኃጢአት እድፍ ስለሚያነጻ ነው፡፡

በብሉይ ኪዳን በኢየሩሳሌም ብቻ መሆን የሚገባቸው ቤተ መቅደሱ፤ ዕጣኑ፣ ቁርባኑ፣ በክርስቶስ ደም በአዲስ ሕይወት፣ በአዲስ ተፈጥሮ፤ በአዲስ ሥርዓት፣ ክርስቲያኖች ለሆንን ለዓለም ሕዝቦች በየሥፍራው (በያለንበት) እንድንጠቀምባቸው ከተፈቀዱልን በኢየሩሳሌም ይኖሩ የነበሩት ሁለቱ ጽላቶች ከፀሐይ መውጫ እስከ ፀሐይ መግቢያ ተባዝተው በዓለም ያለን ክርስቲያኖች በያለንበት በየቤተ መቅደሳችን ለሥጋውና ለደሙ የክብር ዙፋንነት ብንገለገልባቸውና የአምላካችን የኢየሱስ ክርስቶስን ስም ብናከብርባቸው ምን የሚጎዳ ነገር ተገኘ? የሚያስደነግጠውስ ምኑ ነው? ስህተቱስ የቱ ላይ ነው?
   
እንዲሁም ዐሠርቱ ትእዛዛት የተጻፉባቸው ሁለቱ ጽላቶች መባዛት መራባት የለባቸውም ከተባለ በጽላቶቹ ላይ የተጻፉት ዐሠርቱ ትእዛዛት መባዛት የለባቸውም፡፡ ከኢየሩሳሌምም መውጣት የለባቸውም ማለት አይደለም? ትእዛዛቱም ተከለከሉ ማለት ነውና፡፡

በጽላቶች ላይ የተጻፉት ትእዛዛት በእግዚአብሔር ፈቃድ በፀሐይ መውጫ እስከ ፀሐይ መግቢያ ድረስ በሚገኙ ክርስቲያኖች እጅ ገብተዋል፡፡ ይህም ያስደስታል እንጂ አያሳዝንም፡፡ ይህ ከሆነ ለሥጋውና ለደሙ (ለክርስቶስ) ክብር ሲባል በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ውስጥ የሚገኙ ጽላቶች ምን በደል አስከተሉ፥ እግዚአብሔር ለቀደሙ አባቶቻችን በታቦቱ አድሮ የሠራላቸውን ድንቅ ሥራ እያስታወስን እግዚአብሔርን ከማመስገን ውጭ ደግሞም ጌታ ስለ ጸሎት ሲያስተምረን ‹‹አባታችን ሆይ በሚለው ጸሎት ውስጥ ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች እንዲሁም በምድር ትሁን›› በሉ ብሏል፡፡ በዚህ መሠረት በዮሐንስ ራዕይ 11፥19 ላይ ታቦቱን በሰማይ አሳይቶናል፡፡ ስለዚህ የሙሴ የቃል ኪዳኑ ታቦት በሰማይ እንዲገኝ፤ በሰማይ እንዲሆን፤ በሰማይ እንዲታይ ፈቃዱ ከሆነ፤ በምድርም እንዲሆን ፈቃድህ ይሁን ብለን ብንጠቀምበት ስህተቱ ምን ይሆን?

ጥያቄ3፡- የሰሎሞን ቤተ መቅደስ እስኪሠራ ድረስ በእርግጥ ታቦቱ ከቦታ ወደ ቦታ ይዘዋወር ነበር፤ ቤተ መቅደሱ ተሠርቶ ታቦቱ ወደ ቤተ መቅደሱ ከገባ በኋላ ግን ካህናቱ ታቦቱን ተሸክመው ስለመውጣታቸው መጽሐፍ ቅዱስ አይናገርም፡፡ ታዲያ ዛሬ ክርስቶስ ደሙን ካፈሰሰ በኋላ፤ በብሉይም ሆነ በሐዲስ ኪዳን መመሪያ ሳይኖር፤ ከየት አምጥታችሁ ነው ታቦትን በየጊዜው በማውጣት የክርስቲያኖች ህሊና ሁሉ ወደተሰቀለው ክርስቶስ መሆኑ ቀርቶ ወደ ታቦቱ የሆነው?

መልስ፡- በብሉይ ኪዳን እንኳን አይወጣም ነበር ማለት አንችልም ምክንያቱም በችግራቸው ጊዜ ለችግራቸው መፍትሔ ያገኙ ዘንድ ከነበረበት ከድንኳኑም ቢሆን ያወጡት ነበርና ለምሳሌ፦

1. በሙሴ ምትክ  የተመረጠ ኢያሱ ሕዝበ እስራኤልን እየመራ ወደ ምድረ ርስት ሲሄድ ድንገት የዮርዳኖስ ወንዝ ሞልቶ ባገኘው ጊዜ ወንዙን ከፍሎ አሕዛብን ለማሻገር ከእግዚአብሔር በተነገረው መሠረት ካህናቱ ታቦቱን ከነበረበት ቦታ ተሸክመው ወደ ወንዙ በመሄድ ታቦቱን የተሸከሙት ካህናት እግር ወንዙን ሲረግጥ ወንዙ ተከፍሎ ሕዝቡ ሁሉ በሰላም መሻገራቸውን እናገኛለን፡፡ ኢያሱ 3፥1-17፡፡
 
2. እስራኤል ምድረ ርስት በደረሱ ጊዜ ምድረ ርስት (ኢያሪካ) በጠላት እጅ በጽኑዕ ግንብ ታጥራ አገኟት፡፡ በዚህም ጊዜ ይህን የጠላት የግንብ አጥር ለማፍረስና ርስታቸውን በእጃቸው ለማድረግ እግዚአብሔር የገለጠላቸው ጥበብ ካህናቱ ታቦቱን ተሸክመው ሕዝቡም እየተከተሉ ሰባት ጊዜ ግንቡን እንዲዞሩት ነው፡፡ የታዘዙትን አደረጉ ግንቡም ፈረሰላቸው፡፡ ኢያሱ 6፥1-17፡፡

3. እስራኤል ጠላት በበረታባቸው ጊዜ ጠላትን ለማሸነፍ ካህናቱ ታቦቱን ተሸክመው ይወጡ ነበር፡፡ 1ሳሙ 5፥1-ፍ፡፡ ስለዚህ በብሉይ ኪዳን ካህናቱ ታቦቱን ከቦታ ወደ ቦታ ሲንቀሳቀሱ ካልሆነ በቀር ለሚፈልጉት ዓላማ ታቦቱን ካለት ቦታ ተሸክመው አያወጡትም ነበር ማለት አንችልም፡፡ ሰሎሞን ቤተ መቅደሱን ሠርቶ ካስገባው በኋላ ቢሆንም ካህናቱ ታቦቱን ተሸክመው እንዳያወጡ የሚል ሕግም የለም፡፡ እግዚአብሔር የሠራው ሥራ በብሉይ ኪዳን የተፈጸመው አገልግሎት ሁሉ ሙሉ በሙሉ በመጽሐፍ ቅዱስ አልተጻፈም፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስም ያልተጻፈ ብዙ ነገር እንዳለ እናምናለን ከዚህ በመነሳት ነው እኛ በሐዲስ ኪዳን ታቦትን ተሸክመን የምናወጣው፤

በብሉይ ኪዳን በእግዚአብሔር ቸርነት (ትእዛዝ) ካህናቱ ታቦታቱን ተሸክመው እንዲወጡ ተደርጎ ካህናቱም ታቦታቱን ተሸክመው በመውጣት በታቦቱ ያደረ ኃይለ እግዚአብሔር ለሕዝበ እስራኤል ያደረገው ድንቅ ሥራ ለማሰብና እግዚአብሔርን ለማመስገን ነው፡፡ዛሬም ለሥጋና ለደሙ የክብር ዙፋን የሆነውን ቅዱስ ስሙም የተጻፈበትን ቅዱስ ታቦት በምናወጣበት ጊዜ በደሙ የባረከን መድኅነ ዓለም ክርስቶስ አሁንም የሥጋውና የደሙ ዙፋን በሆነው በታቦቱ ረቂቅ ኃይሎች በማስተላለፍ በረከቱን ያበዛልናል ብለን በማመን ነው፡፡

የተሰቀለው አምላክ መክበሩና መንገሡ ቀርቶ በየጊዜው ታቦት ወጣ እየተባለ ታቦቱ ብቻ ነገሠ ከበረ ሕዝቡም ወደ አምልኮ ባዕድ ኮበለለ ስለሚለው ግን አንድ ሕዝብ የንጉሡን ዙፋን ሲያከብርና ሲፈራ ንጉሡን ማክበሩና መፍራቱ እንደሆነ መዘንጋት የለበትም፡፡

እኛ የምናምነው ቅዱስ ስሙ የተጻፈበትን የክርስቶስ ሥጋና ደም የክብር ዙፋን የሆነውን ታቦት ማክበራችን በኪሩቤል ዙፋን የሚቀመጥ መድኅነ ዓለም ክርስቶስን ማክበራችን መሆኑን ነው፡፡ በታቦቱ ፊት መስገዳችንም በታቦቱ ለተጻፈው ለቅዱስ ስሙ ነው፡፡ በታቦት ፊት ለእግዚአብሔር ስም ይሰግዱ የነበሩ ኢያሱና የእስራኤል ሽማግሌዎች በረከት አገኙበት እንጂ አልተጎዱበትምና ነው፡፡ ኢያ 7፥6፣ ዘዳ 33፥10፡፡

በሐዲስ ኪዳንም ‹‹ድል ለነሣው ስውር መናን እሰጠዋለሁ፤ የብርሃን መጽሐፍንም እሰጠዋለሁ፤ በዚያ መጽሐፍ ውስጥ ላይ ከተቀበለው በቀር ማንም የሚያውቀው የሌለ አዲስ ስም ተጽፎበታል›› ራእ 217፡፡ ለዚህ ስም ደግሞ ጉልበት ሁሉ መንበርከክ እንደሚገባ መጽሐፍ ቅዱስ እንዲህ ይላል፤

‹‹ይህም በሰማይና በምድር በቀላያትና ከምድርም በታች ያለ ጉልበት ሁሉ ለኢየሱስ ክርስቶስ ስም ይሰግድ ዘንድ ነው። አንደበትም ሁሉ ኢየሱስ ክርስቶስ በእግዚአብሔር አብ ክብር ጌታ እንደሆነ ያምን ዘንድ ነው›› ፊልጵ 2፥10-11፡፡ በዚህ መሠረት ቅዱስ ስሙ በተጻፈበት ከነጭ ድንጋይ (ከዕምነ በረድ፣ከእንጨት) በተሠራው በጽላቱ ፊት ለቅዱስ ስሙ መስገድ ታላቅ የመንፈስ ጥበብ እንጂ ሞኝነት አይደለም፡፡ ምናልባት ስለታቦት፣ ስለጽላት ባለማወቅ ባጠቃቀሙ በኩል የሚሳሳቱ አባቶችን፤ እናቶችን ወንድሞችንና እህቶችን በተገቢው መንገድ ማስተማር ተገቢ ነው፡፡

ከዚህ በላይ ስለ ታቦት ከቤተ መቅደስ መውጣትና አለመውጣት መጽሐፍ ቅዱሳዊ ከመሆኑም በተጨማሪ ቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሆኑ መታወቅ አለበት፡፡

ብዙዎች በሐዲስ ኪዳን ታቦትን ለመቃወም በኤር 3፥16፡፡ የተጻፈውን ጠቅሰው “በዚያ ዘመን ፦የ እስራኤል ቅዱስ እግዚአብሔር የቃል ኪዳኑ ታቦት እነኋት እያሉም በአፋቸውም አይጠሯትም ከእንግዲህ ወዲህ አይሿትም።” ተብሏልና ታቦት አያስፈልግም በማለት ያስተምራሉ፡፡

እንደተባለው ታቦት ብሎ መጥራት ካላስፈለገ በኤርምያስ 31፥34፤ ደግሞ “እያንዳንዱ ሰው ባልንጀራውን፣ እያንዳንዱም ወንድሙን፦ እግዚአብሔርን ዕወቅ ብሎ አያስተምርም” ተብሎ ስለተጻፈ እንግዲህ ሰው ሁሉ በየዘመኑ እግዚአብሔርን እንዲያውቅ ማስተማር አያስፈልግም ማለት ነዋ! ደግሞም ጌታችን በማቴ 28፥19 “እንግዲህ ሂዱና በአብ በወልድና በመንፈስ ቅዱስ ስም እያጠመቃችኋቸው አሕዛብን ሁሉ አስተምሩ” ብሎ መናገሩ ስህተት መሆኑ ነዋ! በአጠቃላይ እንዲህ ነው ብሎ ከመናገር አስቀድሞ በመጽሐፍ የተጻፈው ነገር ለምንና እንዴት ባለ ሁኔታና ጊዜ መጻፉን ማጥናትና መልእክቱን (ምስጢሩን) መመርመር ይገባል እንላለን፡፡

በመጨረሻ ግን በኢትዮጵያ ኦርቶኮክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የማርያም፣ የቅዱሳን፣የሰማዕታት፣ የመላዕክት ወዘተ…. ታቦት እየተባለ የተሰየመበት ምክንያቱና የዚህ ስያሜ ከየት ነው የመጣው ምንድን ነው የሚሉ ጥያቄዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ እርግጥ ነው፡፡

እንዲህ ተብሎ መሠየሙ በትንቢተ ኢሳይያስ 56፥46 በተገለጸው መሠረት የእግዚአብሔርን ሰንበቱን ለሚጠብቁ ደስ የሚያሰኘውንም ለሚመርጡ ቃል ኪዳኑንም ለሚይዙ ጃንደረቦች (ስለእግዚአብሔር መንግሥት ራሳቸውን ጃንደረባ ያደረጉ ቅዱሳን) ማቴ 19፥12 በእግዚአብሔር ቤትና በቅጥሩ የዘለዓለም መታሰቢያ እንደሚደረግላቸው የተገለጠ በመሆኑ ይህን አብነት በማድረግ ጌታ ሥጋው፣ ደሙ የሚከብርበት ሆኖ ለቅዱሳኑም መታሰቢያ ለማድረግ ነው፡፡ /መዝ 111፥7/ እንዲሁም የጻድቅ መታሰቢያ ለበረከት ነውና ምሳ 10፥7፡፡ በዚህ ምክንያት እንጂ በታቦታቱ የሚከብረው መድኃኒተ ዓለም ክርስቶስ መሆኑ ግልጽ ሊሆን ያስፈልጋል፡፡

እግዚአብሔር አስተዋይ ልቡና ይስጠን።
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
አሜን።

/ምንጭ፦ ሐመር መጽሔት ሚያዝያ 1985 ዓ.ም/

የክርስትና መሠረተ እምነት በጸሎተ ሃይማኖት (አራተኛ መጽሐፍ)

በሊቀ ጉባኤ አባ አበራ በቀለ
 
የሕይወት ብርሃን የሚያጠፋው ሞት የተባለው ጠላታችን በመጨረሻው ዘመን በእግዚአብሔር ኃይል አንዲጠፋና ሰውም የማይጠፋና ሰውም የማይጠፋውን የዘላለም ሕይወት እንደሚያገኝ ፣ ተድላ ደስታ ያለበትን መንግሥተ ሰማያትንም እንደሚወርስ በቅዱሳት መጻሕፍት ተገልጿል ፤ በወንጌሉ የምሥራች ቃል ተረጋግጧል፡፡