ርእሰ ዓውደ ዓመት ዮሐንስ

ክፍል ሁለት

በዓሉ እንዴት ይከበራል?

በማኅበረ ቅዱሳን ዐቢይ ማዕከል መምህር የሆኑት ሊቀጠበብት ሐረገወይን አገዘ «ቤተ ክርስቲያን በዓሉን በመንፈሳዊና ማኅበራዊ ክንውኖች ታከብረዋለች» በማለት እንደሚከተለው ያስረዳሉ፡፡
 

መንፈሳዊ ክንውኖች

የቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ጽላት ባለባችው አብያተ ክርስቲያናት ከዋዜማው /ጳጉሜን 5/6/ ከሰዓት/ ጀምሮ በሌሎቹ ደግሞ ከምሽት ጀምሮ ማኅሌት ይቆማል፡፡ በዕለቱ ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅን እና የአዲስ ዓመትን መግባት በሚያነሱ ያሬዳዊ ዜማዎች ምስጋና ሲቀርብ ያድራል፡፡

በበዓሉ ዕለት ጠዋት /ረቡዕ እና ዓርብ ከሆነ ከሰዓት/ ቅዳሴ ይቀደሳል፤ ካህናትና ምዕመናንም ሥጋ ወደሙ ይቀበላሉ፤ ቤተ ክርስቲያን በዓላትን የምታከብርበት ዋና ምክንያትም ይኸው ነውና፤ ምዕምናን ሥጋ ወደሙ የሚቀበሉበት የዕረፍት ቀን ያገኙ ዘንድ፡፡

አይሁድ የዘመን መለወጫ በዓላቸው የሆነውን ሮስ ሆሻና /በዓለ መጥቅዕ/ በሚያከብሩበት ዕለት ሊቀ ካህናቱ የአገልግሎት አልባሳቱን ለብሶ ቆሞ የዓመቱ በዓላት የሚውሉበትን ቀን ያውጅ ነበር፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ይህንን ትውፊት በመከተል ከቅዳሴ በኋላ /ቅዳሴው ከሰዓት ከሆነ ከቅዳሴው ቀደም ብሎ ሊሆን ይችላል/፡፡ የባሕረ ሀሳብ አዋቂ የሆኑ አባቶች የዓመቱ ተለዋዋጭ በዓላትና አጽዋማት የሚወሉባቸውን ቀናት በባሕረ ሃሳብ ቀመር እያሰሉ ያውጃሉ፡፡ 

በዚህም መሠረት መስከረም አንድ ቀን 2002 . የሚከተለው ይታወጃል፡፡ ዘመኑ ዘመነ ማርቆስ ነው፡፡

 

በዓላት /አጽዋማት

የሚውሉበት ቀን

ጾመ ነነዌ

ጥር 17

ዐቢይ ጾም

የካቲት 1

ደብረ ዘይት

የካቲት 28

ሆሣዕና

መጋቢት 19

ስቅለት

መጋቢት 24

ትንሣኤ

መጋቢት 26

ርክበ ካህናት

ሚያዝያ 20

ዕርገት

ግንቦት 5

ጰራቅሊጦስ

ግንቦት 15

ጾመ ሐዋርያት

ግንቦት 16

ጾመ ድኅነት

ግንቦት 18

 

ከዚህ በኋላ በዓመቱ የሚቀርቡ መስዋዕቶችን ሁሉ ወክለው ስንዴ /መገበሪያ/ ወይን /ዘቢብ/ ዕጣን፤ ጧፍ፣ወዘተ ይቀርቡና ይባረካሉ፡፡ በመጨረሻም ሠርዎተ ሕዝብ ይደረጋል፤ ሕዝቡ ይሰናበታል፡፡

ማኅበራዊ ክንውኖች

«ከዚህ በኋላ ማኅበራዊ ክንውኑ ይቀጥላል» ይላሉ ሊቀ ጠበብት ሐረገ ወይን፡፡ በዓሉን ምክንያት አድርገው ሰዎች ወዳጆቻቸውን፣ ዘመዶቻቸውን እንዲሁም የተቸገሩትና የሚበሉት የሚጠጡት ያጡ ወገኖችን በመጥራት ይጋብዛሉ፡፡ እነርሱም ይጋበዛሉ፡፡

«ይህ በበዓላት ላይ በእምነት ከማይመስሉን ጋር ሳይቀር የሚደረገው መተሳሰብና የፍቅር ግንኙነት ማኅበረሰቡን አንድ አድርጎ ይዞ የኖረ ገመድ ስለሆነ ልንጠብቀው ይገባል፡፡» ይላሉ ሊቀጠበብት፡፡

ከዚህም በተጨማሪ «በዓሉን ስናከብር የተቸገሩ፣ የሚበሉትና የሚጠጡት ያጡ ነዲያን ወገኖቻችንን ልናስብና «ብራብ አብልታችሁኛል» የሚለውን አምላካዊ ምሥጋና ለመስማት የሚያበቃ ሥራ ለመሥራት ልንተጋ ይገባናል» በማለት ያሳስባሉ፡፡

የበዓሉ መንፈሳዊ ትርጉም /ፋይዳ

የአዲስ ዓመት በዓል ለእኛ ለመንፈሳዊያን ሁለት ዋና ዋና መንፈሳዊ ትርጉሞች /ፋይዳዎች/ አሉት፡፡

  1. የምስጋና ዕለት ነው

በእርግጥ እግዚአብሔርን ማመስገን የዘወትር ተግባራችን መሆን አለበት፡፡ እርሱ ኅልፈት የሌለበት ዘመናትን ግን የሚያሳልፍና የሚለዋውጥ እግዚአብሔር ያለፈውን ዓመት አሳልፎ ለአዲስ ዓመት ሲያደርሰን ደግሞ ቢያንስ ለሚከተሉት ሁለት ምክንያቶች ልናመሰግነው ይገባል፡፡

. ቅዱስ ዳዊት «ወትባርክ አክሊለ ዓመተ ምሕረትከ፤ የምህረትህነ ዓመት ትባርካለህ» /መዝ.64.11/ እንዳለው ያለፈውን ዓመት ሙሉ በመግቦቱ ከምንተነፍሰው አየር ጀምሮ የሚያስፈልገንን ነገር ሁሉ ስላዘጋጀልንና በጠብቆቱም እኛ ከምናውቃቸውና ከማናውቃቸው ነገሮች ጠብቆ ወደ አዲሱ ዓመት ስላደረሰን ልናመሰግነው ይገባናል፡፡

. ቅዱስ ዳዊት «አንተ ኃጢአትን ብታስብ፤ አቤቱ በፊትህ ማን ይቆማል» እንዳለው እግዚአብሔር ኃጢአታችንን ቢያስብብን እና እንደ ኃጢአታችን ቢፈርድብን አንዲት ደቂቃ እንኳን መኖር አንችልም ነበር፡፡ እርሱ ግን ኃጢአታችንን እየታገሰ፤ አይቶ እንዳላየ እየሆነ በንስሃ እንድንመለስ ዕድሜ ይጨምርልናል፡፡ ሰዎች ወደ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሔደው ጲላጦስ ስለገደላቸውና ደማቸውን በመስዋዕታቸው ጋር ስለቀላቀለው ሰዎች የነገሩት፡፡ እርሱም መልሶ እንዲህ አላቸው «ይህች መከራ ስላገኘቻቸው እነዚህ ገሊላውያን ከገሊላ ሰዎች ይልቅ ተለያይተው ኃጢአተኞች የሆኑ ይመስሉአችኋልን? አይደለም፡፡ እላችኋለሁ፤ እናንተም ንስሓ ካልገባችሁ እንዲሁ ትጠፋላችሁ፡፡» አላቸውና የሚከተለውን ምሳሌ ነገራቸው፡፡

«አንድ ሰው በታወቀች በወይኑ ቦታ ውስጥ በለስ ነበረችው፤ ፍሬዋን ሊወስድ ወደ እርስዋ ሔዶ አላገኘም፡፡ የወይኑን ጠባቂም፡– «የዚችን በለስ ፍሬ ልወስድ ስመላለስ እነሆ ሦስት ዓመት ሆነኝ አላገኘሁም፤ እንግዲህስ ምድራችንን እንዳታቦዝን ቁረጣት» አለው፡፡ እርሱም መልሶ እንዲህ አለው «አቤቱ አፈር ቆፍሬ በሥሯ እስካስታቅፋት ፍግም እስከ አፈስባት ድረስ የዘንድሮን ተዋት፡፡ ምናልባት ለክረምት ታፈራ እንደሆነ ያለዚያ ግን እንቆርጣታለን» /ሉቃ.131-9/

ስለዚህ የዘመን መለወጫን በዓል የምናከብረው እግዚአብሔር በዕድሜያችን ላይ ሌላ ዓመት የጨመረልን በቸርነቱ ኃጢአታችንን ታግሶ የንስሐ ጊዜ ሊሰጠን መሆኑን በማስተዋልና ለዚህም ምስጋና በማቅረብ፤ እንዲሁም ቀጥለን እንደምንመለከተው የተጨመረልንን ዓመት ተጠቅመን ለከርሞ አፍርተን እንድንገኝ ለንስሐ እና ለለውጥ በመነሣት መሆን አለበት፡፡

2. ንስሐ እና ለውጥ

ንስሐ ማለት በኃጢአት መጸጸት፤ ኃጢአትን ለመተውና አዲስ ሕይወት ለመጀመር መወሰን ማለት ነው፡፡

ሐዋርያው ቅዱስ ጴጥሮስ እንዲህ ይላል፤ «የአህዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት፤ በመዳራትና በሥጋ ምኞትም፣ በስካርም፣ በዘፈንም ያለ ልክም በመጠጣት ነውርም ባለበት በጣዖት ማምለክ የተመላለሳችሁት ያለፈው ዘመን ይበቃል» /1ጴጥ. 4.3/

መንፈሳዊ ሕይወትና የክርስትና ጉዞ ሁል ጊዜ ራስን መመርመርና የቆሙበትን ማወቅ፤ ከዚያም የተሻለ ነገር ለማድረግ መወሰንን ይጠይቃል፡፡ ይህ ሁል ጊዜ መደረግ ያለት ቢሆንም የዘመን መለወጫ ወቅት ደግሞ ይህን ለማድረግ የሚያስችል የተሻለ የሥነ ልቡና ዝግጅት ያለበት መልካም አጋጣሚ ነው፡፡

ስለዚህ የዘመን መለወጫ በዓልን ስናከብር ከበዓሉ አስቀድሞ ወይም በኋላ ባሉት ቀናት ውስጥ ይህንን ለማድረግ ጊዜ መመደብና ቁጭ ብለን በዕርጋታና በጥሙና ያለፈውን ዓመት መገመግም፣ የነበሩትን ደካማ ጎኖች /ችግሮች/ እና ጠንካራ /መልካም/ ነገሮች ነቅሰን ማውጣት ከነበሩት ችግሮች ውስጥ በአዲሱ ዓመት ልንፈታቸው የሚገቡ ችግሮችን ለይተን ማስቀመጥ ይገባናል፡፡ ከዚያም ቅዱስ ያዕቆብ በመልእክቱ «እግዚአብሔር ቢፈቅድና ብንኖር ይህን ወይም ያንን እናደርጋለን ማለት ይገባችኋል» /ያዕ.4.15/ እንዳለው፡፡ እያንዳንዳቸውንም እንዴት አድርገን እንደምንቀርፋቸው አስበን ስልት መቀየስና ዕቅድ ማውጣት ዕቅዳችንን ለመፈጸምም መወሰን ይገባናል፡፡

ሊቀጠበብት ሐረገወይን «የምንቀበለው ዓመትአዲስሊባል የሚችለው እኛ መታደስ ከቻልን ብቻ ነው» ይላሉ፡፡

ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ሐዲስ ኪዳንን ሲመሠርት በብሉይ ኪዳን የነበሩ ነገሮችን አድሷቸዋል፡፡ ደካማ የነበሩትንም ነገሮች አጠንክሯቸዋል አበርትቷቸዋል፡፡ በብሉይ ኪዳን የነበሩትን ክህነት፣ መስዋዕት፣ ሕግ፣ በኃጢአት የተበላሸውን የሰው ልጅ ባሕርይ እና ሌሎቹንም ሁሉ መቅረት ያለባቸውን አስቀርቶ፣ መስተካከል ያለባቸውን አስተካክሎ፣ ሐዲስ ኪዳንን ሠርቷል፡፡ ጌታችን ይህንን ካደረገ በኋላ ያለውን ዘመን «ዘመነ ሐዲስ» ያስባለው የእነዚህ ነገሮች መስተካከል ነው፡፡

«ይህ በእያንዳንዳችን ሕይወት መደረግ አለበት፡፡ መጪው ዓመት አዲስ ዓመት፣ አዲስ ዘመን የሚሆንልን ዓመቱ ችግሮቻችንን ቀርፈን፣ ጥንካሬዎቻችንን አጎልብተን የተሻለ ሕይወት የተሻለ አመለካከት የተሻለ ሥራ የምንጀምርበት ከሆነ ነው፡፡ ይህ ካልሆነና አምና የነበረውን ችግር ሁሉ መልሶ መድገም ካለ ግን ዓመቱ ለእኛ አዲስ ዓመት አይደለም» ይላሉ ሊቀጠበብት፡፡

ይህ ነገር በግለሰብ ብቻ ሳይሆን በቤተሰብም በአገልግሎታችንም ሁሉ መደረግ አለበት፤ ያን ጊዜ እውነትም ወደ አዲሱ ዓመት እንሸጋገራለን፡፡

«የዘመን መለወጫ በዓል የአዲስ ሕይወት መጀመሪያ እንዲሆንልን የአምላካችን ቅዱስ ፈቃድ ይሁንልን፡፡ የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም፣ የጻድቃን፣ የሰማዕታት፣ የመላእክት፣ የቅዱሳን ሁሉ አማላጅነትና ተራዳኢነት ከእኛ ጋር ይሁን፡፡

 ወስብሐት ለእግዚአብሔር

adye abeba 2006

ርእሰ ዐውደ ዓመት ዮሐንስ

ጳጉሜን 5 ቀን 2006 ዓ.ም.

ዲ/ን ዘላለም ቻላቸው

“የአሕዛብን ፈቃድ ያደረጋችሁበት ያለፈው ዘመን ይበቃል” /1ኛ.ጴጥ.4.3/

adye abeba 2006መስከረም 1 ቀን የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስቲያንና የኢትዮጵያውያን የዘመን መለወጫ በዓል ነው፡፡ ይህንን ምክንያት አድርገን በዚህ ጽሑፍ የዘመን አቆጣጠርን ምንነትና ታሪክ፣ የኢትዮጵያን የዘመን አቆጣጠር እንዲሁም የዘመን መለወጫ በዓልና አዲስ ዓመት ሊኖራቸው የሚገባውን መንፈሳዊ ትርጉምና ፋይዳ አስመልክተን አንዳንድ ነገሮችን እንመለከታለን፡፡ እግዚአብሔር ማስተዋሉን ያድለን፤

የዘመን አቆጣጠርን መጀመር አስፈላጊ ያደረጉ ሁለት ዋና ዋናምክንያቶች ነበሩ፡-

1. አዳም በበደሉ ምክንያት ከገነት ተባሮ ወደዚች ምድር ሲመጣ በመጸሐፈ ቀሌምጦስ እንደተጠቀሰው እግዚአብሔር «ከአምስት ቀን ተኩል በኋላ ከልጅ ልጅህ ተወልጄ አድንሃለሁ» ብሎት ነበር፡፡ በእግዚአብሔር ዘንድ አንድ ቀን አንድ ሺሕ ዓመት መሆኑንና ይህ አምስት ቀንተኩል የተባለው ጊዜ 5500 ዓመት መሆኑን አዳምም ፣ ቀደምት አበውም ያውቁ ነበር እግዚአብሔር ዕፀ በለስን እንዳይበላ አዳምን ሲያዘው «ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞትለህ» ብሎት ነበር /ዘፍ.2.17፡፡ ይሁን እንጂ አዳም የሞተው በሰው አቆጣጠር 970 ዓመት ኖሮ ነው፡፡ይህ እግዚአብሔር ቀን ብሎ የገለጸው ምን ያህል እንደሆነ ለአዳም የሚያሳውቅ ነበር፡፡

 

ክቡር ዳዊትም “ሺሕ ዓመት በፊትህ እንዳለፈች እንደ ትናንት ቀን እንደ ሌሊትም ሰዓት ነውና” /መዝ.89.4/ በማለት መናገሩ ደግሞ ቀደምት አበው ስሌቱን እንደሚያውቁት የሚጠቁም ነው፡፡እንግዲህ አበውና ነቢያት ይህንን በተስፋ ሲጠብቁት የነበረውን የእግዚአብሔርን የማዳን ቀን የሚቆጥሩት የዘመን አቆጣጠር አስፈለጋቸው፡፡

2. የሰው ልጆች ወደ ምድረ ፋይድ ከወረዱ በኃላ “በሕይወትህ ዘመን ሁሉ በድካም ከእርስዋ ትበላለህ.. ወደ መጣህባት መሬት እስክትመለስ ድረስ በፊትህ ወዝ እንጀራን ትበላለህ » /ዘፍ.2 .16-17/ በሚለው አምላካዊ ቃል መሠረት የሚበሉትን ለማግኘት የግብርና እንቅስቃሴዎችን ማድረግ ጀምረው ነበር፡፡በዚህ ጊዜ አየሩ የሚሞቅበትንና የሚቀዘቅዝበትን፣ ዝናም የሚኖርበትንና የማይኖርበትን፣ ቀኑ የሚረዝምበትንና የሚያጥርበትን ጊዜ ለማወቅና ሥራን ከዚህ አንጻር ለማቀድና ለመተግበር የዘመን መቁጠሪያና የጊዜ መስፈሪያ አስፈልጓቸዋል፡፡

በእነዚህ ምክንያቶች የሰው ልጆች የተለያዩ መስፊሪያዎችን /መለኪያዎችን/ በመጠቀም ጊዜን / ዘመንን ሰፍረዋል፡፡ በሁሉም ቦታ የነበሩትና ዐበይት የሚባሉት የዘመን መስፈሪያዎች እግዚአብሔር «ቀንና ሌሊትን ይለዩ ዘንድ ፣ ለዕለታት፣ ለዘመናትና ለዓመታት ምልክት ይሆኑ ዘንድ» / ዘፍ.1. 14- 15/ የፈጠራቸውን የፀሐይንና የጨረቃን እንቅስቃሴ መሠረትያደረጉት መስፈሪያዎች ናቸው፡፡ እነዚህም፡-

ሀ. ዕለት- አንድ ዕለት አንድ ቀንን /የብርሃን ክፍለ ጊዜን / እና አንድ ሌሊትን /የጨለማ ክፍለ ጊዜን/ ያካተተ ፀሐይ አንድ ጊዜ ከወጣች በኋላ ተመልሳ እስክትወጣ ድረስ ያለውን ጊዜ የያዘ ነው፡፡ በአሁኑ ዕውቀታችን አንድ ዕለት ምድር በራሷ ዛቢያ አንድ ጊዜ የምትሸከረከርበት ጊዜ ነው፡፡

ለ. ውርኅ- ወርኅ ማለት በግእዝ ጨረቃ ማለት ነው፡፡ አንድ ወርኅ የሚባለው ጊዜ ሙሉ ጨረቃ ከወጣች በኋላ ድጋሚ እስከምትወጣ ድረስ ያለው ጊዜ ነው፡፡ በአሁኑ ዕውቀታችን / በጥንቱም ጨምሮ/ ይህ ጨረቃ መሬትን አንድ ጊዜ ዙራ ለመጨረስ የሚፈጅባት ጊዜ ነው፡፡ አንድ ወር ሃያ ዘጠኝ ተኩል ዕለታትን ይፈጃል፡፡

ሐ. ዓመት- አንድ ዓመት ማለት መሬት አንድ ጊዜ በፀሐይ ዙሪያ ለመዞር የሚፈጅባት ጊዜ ነው፡፡ ይህም 365 ከ1/4 / ሦስት መቶ ስድሳ አምስት ቀን ከሩብ/ ዕለታት ይፈጃል፡፡ይህ ከመታወቁ በፊትም ግን የዓመት ጽንሰ ሓሳብ ነበር፡፡

 

ፕሮፊሰር ጌታቸው ኃይሌ የፅንሰ ሐሳቡን አመጣጥ እንዲህ ያስረዳሉ፡-

ሰዎች ርዝመታቸው እኩል የሆኑ ሁለት ሻማዎችን ሠሩና ልክ ፀሐይ ስትወጣ /ቀኑ ሲያልቅና ሌሊቱ ሲጀምር/ አንዱን ሻማ አበሩት፡፡ ልክ ፀሐይ ስትወጣ እሱን አጠፋናሌላውን / ሁለተኛውን/ ሻማ አበሩት፤ ጧት ፀሐይ እንደገና ስትወጣ / ሌሊቱ አልቆ ሌላ ቀን ሲጀምር/ ሻማውን አጠፉት፡፡ አሁን እንግዲህ ከየሻማዎቹ /ከሁለቱ ሻማዎች/ ምን ያህል እንደተቃጠለላቸው ሲያስተያዩት ከሁለቱ ሻማዎች የተቃጠለው እኩል አለመሆኑን ተመለከቱ በዚህም የቀኑና የሌሊቱ ርዝማኔ እኩል አለመሆኑን ተረዱ፡፡ ቀደም ብለውም የቀኑና የሌሊቱ ርዝማኔ በተለያዩ ወቅቶች የተለያየ መሆኑን ልብ ብለው ነበርና ይህንን ሙከራቸውን ሲቀጥሉ በቀኑና በሌሊቱ ርዘማኔ /በሚቃጠለው የሻማዎቹ መጠን/ መካከል ያለው ልዩነት ከወቅት ወቅት የተለያየ እንደሆነ ተመለከቱ፡፡ ይህን ሙከራቸውን ሲቀጥሉ ግን በየ182 /ተኩል/ ዕለቱ ቀኑና ሌሊቱ እኩል የሚሆኑባቸው ሁለት ዕለታት በዓመት ውስጥ እንዳሉ ተገነዘቡ፡፡ እነዚህ ዕለታት አንዱ የሙቀት ወራት ከመጀመሩ በፊት የሌላው ደግሞ የቅዝቃዜው ወራት ከመጀመሩ በፊት የሚመጡ ናቸው፡፡ ስለዚህ የቀኑና የሌሊቱ ርዝመት አንድ ጊዜ እኩል ሁኖ ደግሞበዚያው ወቅት እኩል እስከሚሆን ድረስ ያለውን ጊዜ ማለትም /182 ተኩል +182=365/ ዕለት አንድ ዓመት አሉት፡፡ አሁን ባለን ግንዛቤ ምድር በራሷ ዛቢያ እንደተሽከረከረች በፀሐይ ዙሪያ ትዞራለች፡፡ ምድር በፀሐይ ዙሪያ የምትዞረው ወደ ጎን 23 ተኩል ዲግሪ ያህልአጋድላ ነው፡፡ ይህ የቀንና የሌሊት ርዝመት መለያየትም የሚከሰተው በዚህ ማጋደል ምክንያት ነው፡፡

 

እንግዲህ በአጠቃላይ ዋናዎቹ የጊዜ / የዘመን/ መስፊሪያዎች ዕለት፣ ወር እና ዓመት ናቸው፡፡ ሦስትቱም ተመላላሽ ክስተቶችን / ለምሳሌ የፀሐይን መውጣት/ መሠረት ያደረጉ ናቸው፡፡ እነዚሀ ተመላላሽ ክስተቶች አንድ ጊዜ ከተከሰቱ በኋላ ደግመው እስኪከሰቱ የሚፈጁት ዘመንnወይም ጊዜ ዓውድ ይባላል፡፡ ዓውድ ማለት ዙሪያ፣ ክብ፣ እንደ ቀለበት ዙሮ የሚገጥም ማለት ነው፡፡ ስለዚህዓውድ ማለት ክስተቶቹ አንድ ጊዜ ከተከሰቱ በኋላ ደግመው እስኪመጡ ድረስ ያለው ጊዜ ማለት ነው፡፡ በዚህ መሠረት ከላይ ያየናቸው ሦስት መስፈሪያዎች/ ዕለት፣ ወርኀ፣ ዓመት/ ዓዕዋዳት / ዓውዶች/ የሚወጡበት ጊዜ ዓውደ ዕለት፣ ዓውደ ወርኀ፣ ዓውደ ዓመት ይባላሉ፡፡

መጀመሪያ ላይ ሰዎች እነዚህን ሦስቱን መስፈሪያዎች /ዓዕዋዳት/ /በተለይም ቀንና እና ወርን/ለየብቻቸው ይጠቀሙባቸው ነበር፡፡ ከዚህን ያህል ቀን፣ከዚህን ያህል ወር በኋላ /በፊት/ እያሉ ጊዜን ይለኩ ነበር፡፡ እነዚህ ሦስቱን በቅንብር/በቅንጅት/ ለመጠቀም ሲፈለግ ግን የዘመን አቆጣጠር ስሌት ያስፈልጋል፡፡ምክንያቱም አንድ ወር 29 ከግማሽ ቀን ነው፡፡ እንዲሁ እንዳለ ለመቁጠር ቢፈለግ የመጀመሪያው ወር ጠዋት ላይ ቢጀመር ሁለተኛው ወር ምሽት ላይ ይጀምራል፣ ሦስተኛው ደግሞ ድጋሚ ጠዋት ላይ ይጀምራል፤ ይህን ለመቅረፍ ወሩን ሙሉ ሰላሳ ቀን ቢያደርጉት ከትክክለኛው ወር /የጨረቃ ዐውድ/ ግማሽ ቀን ይተርፋል፤ 29 ቀን ብቻ ቢያደርጉት ደግሞ ግማሸ ቀን ይጎድላል፡፡

አንድ ዓመት 365 ከሩብ ዕለታት አሉት፡፡ ዓመትን በወራት ለመቁጠር ቢፈለግ፤ዓመቱን 12 ወር ቢያደርጉት የዓመቱ /የዕለታት ቁጥር /29.5X12=354/ ብቻ ይሆናል፡፡ይህም ከትክክለኛው ዓመት /365-354=11/ ዕለታት ያህል ያንሳል፡፡13 ወር ቢያደርጉት ዓመቱ /365X13=385.5/ ቀናት ይሆናል ይህም ከትክክለኛው ዓመት /383.5-365=19/ ቀናት ያህል ይበልጣል፡፡ ስለዚህ እነዚህን መስፈሪያዎች በቅንጅት ለመጠቀምይህንን አለመጣጣም የሚፈታ ቀመር /የዘመን አቆጣጠር ሥርዓት/ ያስፈልጋል፡፡ በተለያዩ አካባቢዎች የተለያዩ የዘመን አቆጣጠሮች ተዘጋጅተዋል፡፡ ከእነዚህ መካከል የአይሁድን፣የሮማውያንን እና የሀገራችንን አቆጣጠሮች በአጭሩ እንመለከታለን፡፡ የአይሁድ ዘመን አቆጣጠር የአይሁድ ዘመን አቆጣጠር እያንዳንዳቸው 29 እና 30 ዕለታት ያሏቸው 12 ወራት አሏቸው፤

 

 

.

የአይሁድ ወራት

የዕለታት ብዛት

ወራቱ በእኛ

1

ኒሳን

30

መጋቢት/ ሚያዝያ

2

ኢያር

29

ሚያዝያ/ ግንቦት

3

ሲዋን

30

ግንቦት/ ሰኔ

4

ታሙዝ

29

ሰኔ/ ሐምሌ

5

አቭ

30

ሐምሌ/ ነሐሴ

6

አሉል

29

ነሐሴ/ መስከረም

7

ኤታኒም

30

መስከረም/ ጥቅምት

8

ቡል

29/30

ጥቀምት/ ኅዳር

9

ከሴሉ

30/29

ኅዳር/ ታህሳስ

10

ጤቤት

29

ታህሳስ/ ጥር

11

ሳባጥ

30

ጥር/ የካቲት

12

አዳር 1

29

የካቲት/ መጋቢት

 

 

እነዚህ የዓመቱ 12 ወራት በአጠቃላይ 354 ያህል ብቻ ዕለታት ይኖሯቸዋል፡፡ ይህም በትክክለኛው ዓመት በ11 ዕለታትያህል ቢያንስም አዲስ ዓመት ይጀምራሉ፡፡ ልዩነቱ በሁለት ዓመታት 22 ዕለታት፣ በሦስት ዓመት ደግሞ 33 ዕለታት ያህል ይሆናል፡፡ስለዚህ በየሦስት ዓመቱ ከአስራ ሁለተኛው ወር ጳጉሜን በፊት አንድ ሌላ ወር ይጨምሩና የዓመቱን የወራት ቁጥር ዐሥራ ሦስትያደርጉና ልዩነቱንያስተካክሉታል፡፡

የኢትዮጵያውያንና የግብጻውያን ዘመን አቆጣጠር

የሀገራችን ኢትዮጵያ እና የጥንት ግብጻውያን /ዛሬም ድረስ የግብጽ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን Yየምትጠቀምበት/ የዘመን አቆጣጠር ተመሳሳይ ነው፡፡ ሁለታችንም እኩል ሰላሳ ቀናት ያሏቸው12 ወራት አሉን፡፡ እነዚህ 12 ወራት / 12X30=360/ ቀናት አሏቸው፡፡ እነዚህ ቀናት በትክክለኛው ዓመት በ/365.25-360=5.25/ ቀናት ያንሳሉ፡፡ይህንንም 5 ቀናት/ በ4 ዓመት አንድ ጊዜ 6 ቀናት/ ያሏትን 13ኛ ወር በመጨመር ያስተካክሉታል፡፡የኢትዮጵያውያን እና የግብጻውያን ወሮች ስም እንደሚከተለው ነው፡፡

 

 

ተ.ቁ

የግብጽ ወሮች

የኢትዮጵያ ወሮች

1

ቱት/ዩት

መስከረም

2

ባባ/ፓከር

ጥቅምት

3

ሀቱር

ኅዳር

4

ኪሃክ/ከያክ

ታኅሣሥ

5

ጡባ/ቶቢር

ጥር

6

አምሺር/ሜሺር

የካቲት

7

በረምሃት

መጋቢት

8

በርሙዳ

ሚያዝያ

9

በሸንስ

ግንቦት

10

ቦኩሩ

ሰኔ

11

አቢብ

ሐምሌ

12

መስሪ

ነሐሴ

13

ኒሳ/አፓጎሜኔ

ጳጉሜን

/ባሕረ ሐሳብ፣ፕ/ ጌታቸው ኃይሌ ፣ገጽ.65/

የሮማውያን ዘመን አቆጣጠር

የጥንት ሮማውያን የመጀመሪያው የዘመን መቁጠሪያ 30 እና 31 ቀናት ያሏቸው 10 ወራት ብቻ ነበሩት፡፡ በአንድ ዓመት ያሉት ቀናት ቁጥር 304 ብቻ ነበር፡፡ሮማውያን ይህን ያዘጋጀው የሮማ ከተማን የመሠረተው ሮሙለስ እንደሆነ ይናገራሉ፡፡
በ713 ዓመት ቅ.ል.ክ ኑማ ፓምፒለስ /Noma Pompilos/ የተባለ የሮማ ንጉሥ ሌሎች ሁለት ተጨማሪ ወራት ጨመረበት፡፡

ጁሊያን የዘመን አቆጣጠር /Julian Calander/ የሮማው ንጉሥ ጁልየስ ቄሳር ለሲጃነስ የተባለ እስክንድርያዊ ሥነ ከዋክብት ተመራማሪን አማክሮ ጥንታዊውን የሮማውያን ዘመን አቆጣጠር አሻሽለው 30 እና 31 ቀናት ያላቸው11 ወራትና 28 ቀናት የአራት ዓመቱ 29 ቀናት ያሉት አንድ ወር ያለው የዘመን አቆጣጠር አዘጋጀ፡፡

አሁን ምዕራባውያን የሚጠቀሙበት የጎርጎርዮሳዊ አቆጣጠርም በ16ኛው መቶ ክፍለ ዘመን መጨረሻ አካባቢ ከተደረጉበት የቀናት ማስተካከያ በስተቀር ይኸው የጁልያን አቆጣጠር ነው፡፡እነዚህ ሁሉ ልዩ ልዩ አቆጣጠሮች መኖራቸው እንደ እውነቱ ከሆነ የሚያስከፋ አይደለም፤ ሁሉምዓላማቸው አንድ ነውና፤ ሦስቱን የጊዜ መስፈሪያዎች ማጣጣም፡፡ ጥያቄ ሊሆኑ የሚገባቸው የሚከተሉት ሁለት ነጥቦች ናቸው፡፡

1. የዘመን ቁጥር ልዩነት

ፕ/ር ጌታቸው ኃይሌ የዘመን አቆጣጠር መለያየትን መነሻ እንዲህ በማለት ያብራራሉ፤ «ክብ የሆነ ነገር ሲከብ ከየትኛውም ቦታ መጀመር ይቻላል፤ የዘመን አቆጣጠር /ዓውደ ዓመትም/ ይኸው ነው፡፡ ዋናው ነገር አንድ ታላቅ ታሪካዊ ድርጊት ፈልጎ እርሱን መነሻ ማድረግ አንድ ታላቅታሪካዊ ድርጊት ፈልጎ እርሱን መነሻ ማድረግ ነው፤ የዘመን አቆጣጠሮቹም ልዩነት መንስኤው ይኸው ነው» ይላሉ፡፡

ባሕረ ሐሳብ፣ ጌታቸው ኃይሌ፣ ገጽ.65/ ለምሳሌነትም ሮማውያን የሮም ከተማ የተቆረቆረችበትን ጊዜ መነሻ ማድረጋቸውን/ በኋላም ታላቁ እስክንድር የነገሠበት ዘመን የዘመን ቆጠራ መነሻ ሆነው እንደ ነበር ይጠቅሳሉ፡፡ መሐመድና ተከታዮች ከመካ ወደ መዲና ያደረጉትን ስደት መነሻ የሚያደርገው ኢስላማዊ የዘመን አቆጣጠርም ሌላው ተጠቃሽ ነው፡፡ የአይሁድን አቆጣጠር ትተን ከላይ ያየናቸው ሁለቱ የዘመን አቆጣጠሮች /የምዕራባውያኑ የጁልስ ጎርጎርዮሳዊ አቆጣጠርና የኢትዮጵያና የግብጽ አቆጣጠር/ ሁለቱም ዘመንን የሚቆጥሩት ከክርስቶስ ልደት መነሻ አድርገው ነው፡፡ይሁን እንጂ እኛ ዛሬ 2002 ዓ.ም ነው ስንል እነርሱ ደግሞ 2009 ዓ.ም ነው ይላሉ፡፡

በመካከሉ የ7/8 ዓመታት ልዩነት አለ፡፡እንግዲህ ጥያቄው ትክክለኛው የትኛው ነው? የሚለው ነው። ጉዳዩ መጻሕፍትን ሊያጽፍ የሚችልና በእርግጥም የተጻፉበት ቢሆንም ለማሳያ ያክል ሁለት ነገሮች እንመልከት፡-

 

  1. አሁን ባለው የምዕራባውያን አቆጣጠር ሄሮድስ የሞተው 4 ዓመት ቅ.ል.ክ ነው። ሄሮድስ የሞተው ጌታ ተወልዶ በስደት ሦስት ዓመት ያህል በግብጽ ከቆየ በኋላ ነው፡፡ይህ ማለት በእርሱ አቆጣጠር ጌታ የተወለደው በ7 ዓመት ቅ.ል.ክ ነው ማለት ነው።እንግዲህ ጌታ በትክክል በተወለደበት በአንድ ዓ.ም እነርሱ ጌታ ሰባት ዓመት ሆኖታል ይላሉ ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ትክክለኛውን ቁጥር ለማግኘት አሁን ካላቸው ቁጥር ላይ ሰባት ዓመት መቀነስ አለባቸው፡፡

  2. ፍላቪየስ ጆሴፈስ የተባለው የአይሁድን ታሪክ የጻፈው ሊቅ እንደ መሰከረው ጌታ የተወለደበት ዓመት ነው ተብሎ በወንጌል ላይ የተጻፈው የቆጠራ ዓመት /ሕዝቡ ሁሉ የተቆጠረበትን ዘመን /ሉቃ.2.1/ በጎርጎሪያን ዘመን አቆጣጠር «7 ዓመተ እግዚአ /A.D/ ላይ ነው፡፡» በማለት መረጃ ትቶልናል ይህ ማለት ደግሞ ከምዕራባውያኑ ዘመን አቆጣጠር ላይ 7 ዓመቶች የግድ መቀነስአለበት ማለት ነው፡፡ ያ ሲደረግ ደግሞ የኛን ዘመን አቆጣጠር ያመጣል፡፡

 

2. የዘመን መለወጫ ቀን ልዩነት

ሁለተኛው ጉዳይ የዘመን መለወጫ ወርና ዕለት ልዩነት ነው፡፡ እኛ መስከረም 1 አዲስ ዓመት ስንጀምር እነርሱ በ January 1 / በእኛ ታኅሣሥ 23/ አዲስ ዓመት ይጀምራሉ፡፡ ይህ ከየት የመጣ ልዩነት ነው? የእኛ እና የግብጻውያን አቆጣጠር እዚህ ጉዳይ ላይ ከአይሁድ አቆጣጠር ጋር ይስማማል፡፡በአይሁድ አቆጣጠር የመጀመሪያው ወር ኒሳን የሚባለው /በእኛ መጋቢት/ ሚያዝያ/ ነው፡፡«ይህ ወር የዓመቱ የመጀመሪያ ወር ይሁናችሁ፣ በዚህም ወር በዐሥራ አራተኛው ቀን የአንድ ዓመት ተባዕት ላይ ወስደው ይረዱ፡፡ /ዘፀ.12.1-14/ ተብሎ የተሰጣቸውን የፋሲካ በዓል የሚያከብሩት በዚህ ወር ነው፡፡ ይሁን እንጂ አዲስ የዓመት በዓል አድርገው የሚያከብሩት «የሰባተኛው ወር የመጀመሪያ ቀን ዕረፍት ይሁናችሁ፡፡ በዚሁ በመለከት ድምጽ የሚከበር የተቀደሰ ጉባኤ ይኑራችሁ መስዋዕት ለእግዚአብሔር አቅርቡ እንጂ የተለመደ ተግባራችሁን አታከናውኑበት» /ዘሌ.13.23-25/ ተብሎ የተሰጣቸው የሮሽ ሆሻና፣/የመለከት በዓል ወይም በዓለ መጥቅዕ/ ተብሎ የሚጠራው በዓል ነው፡፡ ይህም ማለት አዲስ ዓመት የሚያከብሩት በሰባተኛው ወር በኢታኒም ወር /በእኛ መስከረም ጥቅምት/ ነው፡፡

በቤተ ክርስቲያናችንም ትምህርት ዓለም የተፈጠረው መጋቢት 29 ቀን ነው፡፡ መስከረም ደግሞ ከመጋቢትጀምሮ ሲቆጠር ሰባተኛው ወር ነው ይህም ከአይሁድ ዘመን አቆጣጠር ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ አይሁድስ ቢሆኑ የመጀመሪያው ወር እያለ አዲስ ዓመትን ለምን በሰባተኛው ወርያከብራሉ ለሚለው ጥያቄ ሁለት ዓይነት ምላሾች /ምክንያቶች/ ይሰጣሉ፡፡

የመጀመሪያው ምክንያት «ሰባተኛው ወር ኖኅ ከመርከብ የወጣበት ወር በመሆኑ ይህ የአዲስ ዓመት መጀመሪያ ተደርጎ መከበር በመጀመሩ ነው» የሚል ነው፡፡ በዘመን መለወጫ ዕለት ልጃገረዶች አበባ እና ለምለም ሣር መያዛቸው ርግቢቱ ለኖኅ ካመጣችው ለምለም ወይራ /ቄጠማ/ ጋር ተያይዞ የተጀመረ መሆኑን ይናገራሉ፡፡

ሁለተኛው ደግሞ መስከረም የቀንና የዕለቱ ርዝመት እኩል የሚሆኑበት ወር በመሆኑ ነው የሚል ነው፡፡ የመስከረም1 ቀን ስንክሳር «የተባረከ የመስከረም ወር የግብጽና የኢትዮጵያ ዓመታት ወሮች ርእስ ነው፤ የቀኑ ሰዓትም ከሌሊቱ ሰዓት የተስተካከለ ዐሥራ ሁለት ነው» ይላል፡፡ እዚህ ላይ ማስተዋል የሚገባው ሌላው ጉዳይ በቤተክርስቲያናችን ትምህርት እመቤታችን ጌታን የጸነሰችው መጋቢት 29 ቀን ነው፡፡ይህም ቅዱስ ጳዉሎስ ፣የዘመኑ ፍጻሜ በደረሰ ጊዜ እግዚአብሔር ከሴት ተወለደ» /ገላ.4.4/ እንዳለው የ5500 ዘመኑ ፍጻሜ /ዓለም ከተፈጠረ ጀምሮ/ ነው፡፡ ጽንሰትን መጋቢት 29 ካልን በኋላ ልደትን ታህሣሥ 29 ቀን እናከብራለን፡፡ ከመጋቢት 29 እስከ ታህሣሥ 29 ድረስ 9 ወር ከ5 ቀን ነው፡፡ /ጳጉሜን ጨምሮ/፡፡ ጳጉሜ 6 በምትሆንበት ጊዜ ደግሞ ታህሣሥ 28 ቀን ልደት ስለሚከበር አሁንም በመሐሉ ያለው ጊዜ 9 ወር ከአምስት ቀን ይሆናል፡፡

የዘመን ቆጠራ ለቤተ ክርስቲያን

የዘመን ቆጠራ ከጌታችን ልደት በፊት የነበረው ሃይማኖታዊ ፋይዳ የሰው ልጆች ሁሉ /በተለይ አበውና ነቢያት/ በተስፋ ይጠብቁት የነበረውን የጌታችንን መምጣት የቀረውን ጊዜ ለማወቅ ነበር፡፡ተስፋው ከተፈፀመ በኋላ ደግሞ የዘመን ቆጠራ ዋና አገልግሎቱ በዓላትና አጽዋማት በዓመቱ የሚወሉበትን ዕለት ለማወቅ ነው፡፡ እነዚህ በዓላት እግዚአብሔር በተለያዩ ዘመናት ለሰው ልጆች ያደረጋቸው ድንቅ ነገሮችና ውለታዎች የሚታሰቡባቸው ናቸው፡፡ በመጀመሪያ እነዚህ በዓላት ሁሉ መጀመሪያ በተደረጉባቸው ቀናት ይከበሩ ነበር፡፡ ለምሳሌ ስቅለት መጋቢት 27፣ ትንሳኤ መጋቢት 29፣ ልደት ታኅሣስ 29፣ የቅዱስ ሚካኤል በዓል ኅዳር 12፣ ወዘተ. . . ማለት ነው፡፡ አጽዋማቱም እንዲሁ፡፡

የእስክንድርያ ሊቀ ጳጳሳት የነበረው ዲሜጥሮስ ግን አንዳንድ በዓላትና አጽዋማት መጀመሪያ በተፈጸሙባቸው ዕለታት እንዲውሉ ይመኝ ነበር፡፡ በተለይም ነነዌ የዐቢይ ጾም መጀመሪያ፣ እና የጾመ ሐዋርያት መጀመሪያ ሁል ጊዜ ሰኞ እንዲውሉ፤ ደብረ ዘይት፤ ሆሳዕና፤ ትንሳኤ ጰራቅሊጦስ ከእሁድ እንዳይወጡ፣ ርክበ ካህናት፣ ጾመ ድኅነት፣ ከረቡዕ፤ ዕርገት ከኀሙስ ስቅለት ከዓርብ እንዳይወጡ ይመኝ ነበር፡፡ ከዚህ በኋላ ከእግዚአብሔር የታዘዘ መልአክ መጥቶ «ዲሜጥሮስ ሆይ ይህ ሁሉ በሐሳብ አይፈጸምም፤በተግባር ቢያደርጉት ካልሆነ» ብሎ ሱባኤ እንዲገባ ነገረው፡፡

 

ዲሜጥሮስም ሱባዔ ገባና የተመኘውን ሊያደርግበት የሚችል ቀመር ተገለጠለት፡፡ ቀመሩን በመጠቀምም ግብጻውያን እነዚህ በዓላት የሚውሉቸውን ቀናት በየዓመቱ እየወሰኑ ማክበር ጀመሩ፡፡በ325 የተደረገው የኒቅያ ጉባኤም ትንሳኤ ሁል ጊዜ እሁድ እንዲከበርና በዓሉ የሚከበርበትን ዕለት የግብጽ ቤተ ክርስቲያን እንድታስታውቅ በመወሰኑ ይህ ቀመር ተስፋፍቷል፡፡ቀመሩ ወደ ሃገራቸንም መጥቷል፡፡ ስሙም ባሕረ ሐሳብ ይባላል፡፡

ቀመሩን እኛ ለመጀመሪያ ጊዜ ያገኘነው ትምህርቱን በድጋሚ ካስፋፋው 13ኛው መቶ ክፍለ ዘመን አካባቢ ከነበረው ከግብጻዊው ዲያቆን ከዮሐንስ አቡሻክር በመሆኑ የአቡሻክር ትምህርትም ተብሎ ይጠራል፡፡ /ባሕረ ሐሳብ፣ፕ/ር ጌታቸው ኃይሌ ፣ገጽ 19/ የእኛ ሀገር ሊቃውንትም አስፋፍተውታል፤አራቀውታልም፡፡ ስለዚህም ቤተ ክርስቲያናችን ይህንን ቀመር በመጠቀም በየዓመቱ የሚውሉትን ተለዋዋጭ በዓላት እና አጽዋማት መቼ እንደሚውሉ ትወስናለች፡፡

ስለ ዘመን አቆጣጠር ይህንን ያህል ካልን ቀጥለን ደግሞ ዐቢይ ትኩረታችን ስለሆነው ስለ ዘመን መለወጫ በዓል እንነጋገር፡፡

 

የዘመን መለወጫ በዓል የበዓሉ ስያሜዎች

 

ይህ በዓል “የዘመን መለወጫ”፤ “አዲስ ዓመት” ከሚሉት በተጨማሪ ሌሎች ስሞችም አሉት፡፡

 

ሀ. ቅዱስ ዮሐንስ-

a st.john 2006ቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ ተብሎ ከጌታችን ስብከት አስቀድሞ እንደሚመጣና ጥርጊያውን እንደሚያዘጋጅ በነቢዩ ኢሳይያስ ተነግሮለት ነበር /ኢሳ.40.3/፡፡ በዚህም መሠረት በዘመነ ብሉይ መጨረሻና በዘመነ ሐዲስ መጀመሪያ ተነስቶ «መንግሥት ሰማያት ቀርባለችና ንስሐ ግቡ» «እነሆ የዓለሙን ኃጢአት የሚያስወግድ የእግዚአብሔር በግ» በማለት ስለ ጌታችን አዳኝነት መስክሯል፤ሕዝቡን ስለ ኃጢአታቸው እየገሰፁ ንስሐ እንዲገቡ አድርጓል፡፡ ጌታችንንም በዮርዳኖስ ወንዝ አጥምቋል፡፡

የቅዱስ ዮሐንስ ዕረፍት/ምትረት ርእስ/ የሚታሰበው መስከረም ሁለት ቀን ቢሆንም እንኳን ተግባሩ በዘመነ ወንጌልና በዘመነ ሐዲስ መካከል የነበረ መሸጋገሪያ በመሆኑ የቅዱስ ዮሐንስ መጥምቅ መታሰቢያ በዓል የብሉይ ኪዳን ምሳሌ ከሚሆነው ካለፈው ዓመት የሐዲስ ኪዳን ምሳሌ ወደሚሆነው አዲሱ ዓመት መሸጋገሪያ በሆነው በመስከረም አንድ ቀን እንዲከበር፤ በዓሉም በእርሱ ስም እንዲሰየም አባቶ ወስነዋል፡፡

ለ. ርእሰ ዓውደ ዐመት

ዓውድ ማለት ዙሪያ፣ ክብ፣ ክስተቶች አንድ ጊዜ ከተከሰቱ በኋላ ደግመው የሚመጡበት ጊዜ ማለት መሆኑን ተመልክተናል፡፡ ስለዚህ ዓውደ ዓመት ማለት ዓመቱ አንድ ጊዜ ከተጀመረ በኋላ ሁለተኛ ዓመት እስኪጀመር ያለው ጊዜ ማለት ነው፡፡ ዓመትን መቁጠር ከየትኛውም ወር እና ቀን መጀመር ይቻላል፡፡ኅዳር 13 ብንጀምር አንድ ዓውደ ዓመት ማለት እስከሚቀጥለው ኅዳር 12 ቀን ያለው ጊዜ ማለት ነው፡፡ ነገር ግን መደበኛው ዓውደ ዓመት የሚጀምረው መስከረም አንድ ቀን ነው፡፡ ይህ ቀን ርእሰ ዓውደ ዓመት የተባለውም «የሁሉም ዓውደ ዓመት መጀመሪያዎች ቁንጮ ነው» ለማለት ነው፡፡

ሐ. ዕንቁጣጣሽ

ሐጎስ ዘማርያም ለምለም በቀለን ለመጀመሪያ ዲግሪ ማሟያ ያቀረበችውን ጽሑፍና ሌሎች የቃል ማስረጃዎችን ጠቅሶ በሐመር መጽሔት የ1997 ዓ.ም መስከረም/ ጥቅምት ዕትም ላይ በቀረበው ጽሑፍ «ዕንቁጣጣሽ» ለሚለው የዚህ ስያሜ ሁለት ዋና ዋና መነሻዎችን እንዳሉት ገልጿል፡፡

 

  1. ዕንቁጣጣሽ የሚለው ቃል ሁለት ቃላት ካሉት ጥምር ቃል የተገኘ ነው፡፡ ዕንቁ እና ጣጣሽ ከሚሉ ዕንቁ የከበረ ዋናው ውድ የሆነ አብረቅራቂ ድንጋይ ነው፡፡ ጣጣሽ የሚለው ቃል ፃዕ ፃዕ ከሚለው የግእዙ ቃል የተወረሰ ሲሆን ትርጉሙ ግብር፣ ጣጣ፣ ገጸ በረከት፣ ማለት ነው፡፡ለምሳሌ በሸዋ አካባቢ ግብር አለብኝ ሲል «ጣጣ አለብኝ» ይላል፡፡ይህ ስያሜ ለበዓሉ የተሰጠው ከንግሥተ ሳበ /ንግሥት ማክዳ/ ጋር በተያያዘ ነው፡፡ንግሥተ ሳባ ንጉሥ ሰሎሞንን ለመጎብኘት ሔዳ ሳለ የጸነሰችውንቀዳማዊ ምኒልክን በወለደች ጊዜ ሕዝቡ ንጉሥ ተወለደ ብሎ እልል እያሉ «አበባ እንቁ ጣጣሽ» እያለ ገጸ በረከት ለንግሥቲቱ አበረከቱ፡፡ያ የዘመን መለወጫ በዓልም ልጃገረዶች የአበባ ገጸ በረከት የሚያቀርቡበት ስለሆነ ዕንቁጣጣሽ ተባለ፡፡

  2. ዕንቁጣጣሽ ግጫ ማለት ነው፤ ግጫ ደግሞ የሣር ዓይነት ነው፡፡የአበባ፣ የእርጥብ ስጦታ መስጠት የተጀመረው በኖኅ ዘመን ነው፡፡ ኖኅ የጥፋት ውኃ በጎደለ ጊዜ መጉደሉን ለማረጋገጥ ርግብን ልኳት የወይራ ቅጠል አምጥታለች ይህ የሆነበት ወቅት የመስከረም ወር በመሆኑ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ የዘመን መለወጫ ሆነ፡፡በርግቧ አምሳልም ልጃገረዶች የተለያየ ዓይነት ሣርና አበባ በመያዝና በማደል በዓሉን ያከብራሉ፡፡ በሣሩ ስምም በዓሉ ዕንቁጣጣሽ ተባለ፡፡

ምኩራብ

ሦስተኛው ሰንበት ምኩራብ ተብሎ የተሰየመበት ምክንያት በዚሁ ዕለት የሚዘመረው ጾመ ድጓ ከዋዜማው ጀምሮ እስከ ሰላሙ ድረስ በዕለተ ሰንበት «ቦአ ኢየሱስ ምኩራበ አይሁድ»

«ኢየሱስ በሰንበት ቀን ወደ አይሁድ ምኩራብ ገባ» እያለ ኢየሱስ በአይሁድ ምኩራብ ማስተማሩን እየጠቃቀሰና እያነሣሣ ስለሚዘምር ይህን ሰንበት ለዚህ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ በምኩራብ እየገባ ለማስተማሩና በምኩራብ የሚሸጡ የሚለውጡ ነጋዴዎችን ለማስወጣቱ ቤተ መቅደሱን ለማስከበሩ መታሰቢያ ሆኖ ስለተሰጠ ነው፡፡ የዚህም በዓል ታሪክ ዝርዝር ሁኔታው በማቴዎስ ወንጌል ምዕ 21፡12-13 ተጠቅሷል፡፡

ቆላስ 2፡16-23 «እንግዲህ በመብል ወይ በመጠጥ ወይም ስለ በዓል ወይም ስለ ወር መባቻ ወይም ስለሰንበት ማንም አይፍረድባችሁ እነዚህ ሊመጡ ያሉት ነገሮች ጥላ ናቸውና፣ አካሉ ግን የክርስቶስ ነው፡፡ ትሕትናንና የመላእክትን አምልኮ እየወደደ፣ ባላየውም ያለፈቃድ እየገባ፣ በሥጋዊም አእምሮ በከንቱ እየታበየ ማንም አይፍረድባችሁ፤ እንደዚህ ያለ ሰው ራስ ወደሚሆነው አይጠጋም፣ ከእርሱም አካል ሁሉ በጅማትና በማሰሪያ ምግብን እየተቀበለ እየተጋጠመም፣ እግዚአብሔር በሚሰጠው ማደግ ያድጋል፡፡ ከዓለማዊ ከመጀመሪያ ት ምህር ት ርቃችሁ ከክርስቶስ ጋር ከሞታችሁ፣ እንደሰው ሥርዓትና ት ምህር ት፡- አትያዝ አትቅመስ፣ አትንካ ለሚሉት ትእዛዛት በዓለም ሁሉ እንደምትኖሩ ስለምን ትገዛላችሁ) እነዚህ ሁሉ በመደረግ ሊጠፉ ተወስነዋልና፡፡ ይህ እንደገዛ ፈቃድህ በማምለክና በትሕትና ሥጋንም በመጨቈን ጥበብ ያለው ይመስላል፣ ነገር ግን ሥጋ ያለ ልክ እንዳይጠግብ ለመከልከል ምንም አይጠቅምም፡፡»

ያዕ 2፡14-26 « ወንድሞቼ ሆይ፣ እምነት አለኝ የሚል፣ ሥራ ግን የሌለው ሰው ቢኖር ምን ይጠቅመዋል) እምነቱስ ሊያድነው ይችላልን) ወንድም ወይም እኅት ራቁታቸውን ቢሆኑ የዕለት ምግብንም ቢያጡ፣ ከእናንተ አንዱም በደህና ሂዱ፣ እሳት ሙቁ፣ ጥገቡም ቢላቸው ለሰውነት ግን የሚያስፈልጉትን ባትሰጡአቸው ምን ይጠቅማቸዋል) እንደዚሁም ሥራ የሌለው እምነት ቢኖር በራሱ የሞተ ነው፡፡
 
ነገር ግን አንድ ሰው አንተ እምነት አለህ እኔም ሥራ አለኝ፤ እምነትህን ከሥራህ ለይተህ አሳየኝ፣ እኔም እምነቴን በሥራዬ አሳይሃለሁ ይላል፡፡ በእግዚአብሔር አንድ እንደሆነ አንተ ታምናለህ፤ መልካም ታደርጋለህ፤ አጋንንት ደግሞ ያምናሉ ይንቀጠቀጡማል፡፡ አንተ ከንቱ ሰው፣ እምነት ከሥራ ተለይቶ የሞተ መሆኑን ልታውቅ ትወዳለህን) አባታችን አብርሃም ልጁን ይስሐቅን በመሠዊያው ባቀረበ ጊዜ በሥራ የጸደቀ አልነበረምን) እምነት ከሥራው ጋር አብሮ ያደርግ እንደ ነበረ፣ በሥራም እምነት እንደተፈጸመ ትመለከታለህን) መጽሐፍም አብርሃምም እግዚአብሔር አመነ ጽድቅም ሆኖ ተቈጠረለት ያለው ተፈጸመ፤ የእግዚአብሔርም ወዳጅ ተባለ፡፡ ሰው በእምነት ብቻ ሳይሆን በሥራ እንዲጸድቅ ታያላችሁ፡፡ እንደዚሁም ጋለሞይቱ ረዓብ ደግሞ መልእክተኞቹን ተቀብላ በሌላ መንገድ በሰደደቻቸው ጊዜ በሥራ አልጸደቀችምን) ከነፍስ የተለየ ሥጋ የሞተ እንደሆነ እንዲሁ ደግሞ ከሥራ የተለየ እምነት የሞተ ነው፡፡»
 
የሐዋ.ሥራ 1ዐ፡1-9 « በቂሣርያም ኢጣሊቄ ለሚሉት ጭፍራ የመቶ አለቃ የሆነው ቆርኔሌዎስ የሚሉት አንድ ሰው ነበር፡፡ እርሱም ከቤተ ሰዎቹ ሁሉ ጋር እግዚአብሔርን የሚያመልክና የሚፈራ ለሕዝብም እጅግ ምጽዋት የሚያደርግ ወደ እግዚአብሔርም ሁልጊዜ የሚጸልይ ነበረ፡፡ ከቀኑም ዘጠኝ ሰዓት ያህል፡- ቆርኔሌዎስ ሆይ የሚለው የእግዚአብሔር መልአክ ወደ እርሱ ሲገባ በራእይ በግልጥ አየው እርሱም ትኩር ብሎ ሲመለከተው ደንግጦ ጌታ ሆይ ምንድር ነው) አለ፡፡ መልአኩም አለው፡- ጸሎትህና ምጽዋትህ በእግዚአብሔር ፊት ለመታሰቢያ እንዲሆን ዐረገ፡፡ አሁንም ወደ ኢዮጴ ሰዎችን ልከህ ጴጥሮስ የሚባለውን ስምዖንን አስመጣ፡፡ እርሱ ቤቱ በባሕር አጠገብ ባለው በቁርበት ፋቂው በስምዖን ዘንድ እንግድነት ተቀምጦአል፤ ልታደርገው የሚገባህን እርሱ ይነግርሃል፡፡ የተናገረውም መልአክ በሄደ ጊዜ ከሎሌዎቹ ሁለቱን፣ ከማይለዩትም ጭፍሮቹ እግዚአብሔርን የሚያመልክ አንዱን ወታደር ጠርቶ፣ ነገሩን ሁሉ ተረከላቸው ወደ ኢዮጴም ላካቸው፡፡ እነርሱም በነገው ሲሄዱ ወደ ከተማም ሲቀርቡ፣ ጴጥሮስ በስድስት ሰዓት ያህል ይጸልይ ዘንድ ወደ ጣራው ወጣ፡፡
 
መዝ 68፡9
እስመ ቅንዐተ ቤትከ በልዐኒ
ትዕይርቶሙ ለእለ ይትዔየሩከ ወድቀ ላዕሌየ
ወቀጻዕክዋ በጾም ለነፍስየ፡፡
 
የቤትህ ቅንዓት በልታኛለችና
የሚሰድቡህም ስድብ በላዬ ወድቆአልና
ነፍሴን በጾም አስመረርሁአት፡፡
 
ዮሐ 2፡12-25 «ከዚህ በኋላ ከእናቱና ከወንድሞቹ ከደቀመዛሙርቱም ጋር ወደ ቅፍርናሆም ወረደ፣ በዚያም ጥቂት ቀን ኖሩ፡፡ የአይሁድ ፋሲካም ቀርቦ ነበር ኢየሱስም ወደ ኢየሩሳሌም ወጣ፡፡ ወደ መቅደስም በሬዎችንና በጎችን ርግቦችንም የሚሸጡትን ገንዘብ ለዋጮችንም ተቀምጠው አገኘ፤ የገመድም ጅራፍ አበጅቶ ሁሉን በጎችንም በሬዎችንም ከመቅደስ አወጣቸው፣ የለዋጮችንም ገንዘብ አፈሰሰ፣ ገበታዎቻቸውንም ገለበጠ፣ ርግብ ሻጪዎችንም ይህን ከዚህ ውሰዱ፡፡ የአባቴን ቤት የንግድ ቤት አታድርጉት አላቸው፡፡ ደቀ መዛሙርቱም የቤትህ ቅናት ይበላኛል ተብሎ እንደተጻፈ አሰቡ፡፡ ስለዚህ አይሁድ መልሰው ይህን ስለምታደርግ ምን ምልክ ት ታሳየናለህ) አሉት፡፡ ኢየሱስም መልሶ ይህን ቤተመቅደስ አፍርሱት በሦስት ቀንም አነሣዋለሁ አላቸው ስለዚህ አይሁድ ይህ ቤተ መቅደስ ከአርባ ስድስት ዓመት ጀምሮ ይሠራ ነበር፣ አንተስ በሦስት ቀን ታነሣዋለህን) አሉት፡፡ እርሱ ግን ስለ ሰውነቱ ቤተመቅደስ ይል ነበር፡፡ ስለዚህ ከሙታን ከተነሣ በኋላ ደቀመዛሙርቱ ይህን እንደተናገረ አሰቡና መጽሐፍንና ኢየሱስ የተናገረውን ቃል አመኑ፡፡
 
በፋሲካ በዓልም በኢየሩሳሌም ሳለ፣ ያደረገውን ምልክት ባዩ ጊዜ ብዙ ሰዎች በስሙ አመኑ ነገር ግን ኢየሱስ ሰዎችን ሁሉ ያውቅ ነበር፤ ስለ ሰውም ማንም ሊመሰክር አያስፈልገውም ነበርና አይተማመናቸውም ነበር፣ ራሱ በሰው ያለውን ያውቅ ነበርና፡፡»
 

                        ወስብሐት ለእግዚአብሔር