Gubae_Qana

እነሆ እኔ በእናንተ ደስ ይለኛል፡፡ ፊል. 2፡17

ቤተ ክርስቲያን ከተመሠረተችበት ጊዜ አንሥቶ የቀና እውነተኛና መልካም ጉዞዋን የሚፈታተኑ በዙሪያዋ ጠፍተው አያውቁም፡፡ ከሰው መፈጠር በፊት በመላእክት ዘንድ የነበረችው የመላእክት ማኅበር በክፉው መልአክ /በዲያብሎስ/ እና እርሱን በመሰሉ ጭፍራዎቹ መካከል Gubae_Qanaያለ ነውርና ነቀፋ በመገኘቷ የተመረጠች ነበረች፡፡

 

በጥንተ አበው ታሪክም የምናየው ይህንኑ ነው፡፡ ከአቤል ጀምሮ እስከ ዮሴፍ ያሉ አበው በክፉዎች ብዙ መከራ የደረሰባቸው፣ በዚህች ምድር ላይ እንግዶችና መጻተኞች ሆነው የኖሩ ናቸው፡፡ጌታችን ወደዚህ ምድር በሥጋ እስከመጣበት ድረስ የነበሩት የእስራኤል ልጆች ታሪክም በክፉና መልካም ነገሮች ከሚጎረብጠው ትውልድ መካከል የነበረ ውጣ ውረድ የበዛበት ነው፡፡

የአበው ተስፋ ተፈጽሞ ጌታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ መወለዱን፤ በሞቱና በትንሣኤው ዓለምን ማዳኑን የምሥራች አምነው፤ በሐዋርያት ስብከት የተሰበሰቡ እግዚአብሔር ደስ የሚሰኝባቸው ማኅበረ ምእመናንም በዚሁ ታሪክ እንደኖሩ መጽሐፍ ቅዱስ ምስክር ነው፡፡
ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመጀመሪያዎቹ ክፍለ ዘመናት ብዙ መከራ ስትቀበል ነውርና ነቀፋ የሌለባቸውንም ብዙ ቅዱሳን አፍርታለች፡፡ ቤተ ክርስቲያን በሰማዕታት ዘመን ክርስቶስን እንዲክዱ ከክፉና ጠማማው ትውልድ ብዙ መከራ ደርሶባቸው በእምነታቸው በመጽናት ያለነቀፋና ነውር ሕይወታቸውን ለእግዚአብሔር ያቀረቡ “እነሆ በእናንተ ደስ ይለኛል” ፈል.፪፥፲፯ ብሎ እግዚአብሔር የተናገረላቸው አሁን የምንዘክራቸው ብዙ ቅዱሳን ሰማዕታትን አግኝታለች፡፡

የመከራው ዘመን ለጊዜውም ቢሆን ሲያልፍ የቀጠለው መናፍቃን በቤተ ክርስቲያን ላይ ያመጡት መከራ ነበር፡፡ ቤተ ክርስቲያንን እስከ መከፋፈል የደረሱ ሰዎች በአሕዛብ መንደር የሊቃቀሙትን የሐሰት ትምህርት ከቤተ ክርስቲያን ንጹሕ አስተምህሮ ጋር ለማቀያየጥ በሞከሩ ጊዜ በትምህርታቸው ነውርና ነቀፋ የሌለባቸው ሊቃውንት አበው ብዙ መከራ ተቀብለው እውነተኛውን አስተምህሮ አጽንተዋል፡፡
ከዚያም በኋላ እስካሁን የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ለመበረዝ አልፎም ለማጥፋት የሚታትር ትውልድ ጠፍቶ አያውቅም፡፡ ያለንበትም ዘመን ከምንጊዜውም የበለጠ ለቤተ ክርስቲያን አስቸጋሪ ዘመን መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ክፉ አሳቢነት በአብዛኛው ተንሰራፍቶ እና ተደላድሎ የሚታይበት ዘመን ነው፡፡

 

ዘመኑ የክርስቲያኖችን ልቦና ለመክፈል በሚችሉ አያሌ እንግዳ እና አደገኛ አስተሳሰቦች በተለይ በወጣቱ ዘንድ የተናኙበት ዘመን ነው፡፡ በነዚህ ሁሉ ከክርስትና ጋር የማይስማሙ የእንግዳ አስተሳሰቦች ማዕበል መካከል ደግሞ ከኃጢአት ርቆ ለመኖር የሚታገሉ የቤተ ክርስቲያን ልጆችን የሚፈታተን ልቅ ዓለማዊነት በስፋት የሚሰበክ የዓለም ሥርዓት መሆን ጀምሯል፡፡

 

በዚህ ሁሉ መካከል የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስን ምክር ሁል ጊዜም በልቦናችን መያዝ እና ማስታወስ አስፈላጊ ነው፡፡ “በመጥፎና በጠማማ ትውልድ መካከል ያለነቀፋ የዋሆችም ነውርም የሌለባቸው የእግዚአብሔር ልጆች እንድትሆኑ ሳታንጎራጉሩ ክፉም ሳታስቡ ሁሉን አድርጉ፤ በእነርሱም መካከል የሕይወትን ቃል እየሰበካችሁ እንደብርሃን ትታያላችሁ” /ፊል.፪፥፲፬-፲፮/፡፡ ምንም እንኳ ክፉና ጠማማ ትውልድ መኖሩ የማይፈለግ ቢሆንም ከኖረ ዘንድ ግን ክፉን ለመልካም ማዋል የሚችል እግዚአብሔር ብዙ ቅዱሳን የሚገኙበት፣ የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ እንደማለዳ ፀሐይ እየደመቀ እንዲሔድ ማድረጊያ መንገድ አድርጎታል፡፡ በእኛ ዘመንም እግዚአብሔርን ይህን ከማድረግ የሚከለክለው የለም፤ የሚፈለገው “በክፉና በጠማማ ትውልድ” መካከል ሆኖ እንደ ቤተ ክርስቲያን ትእዛዝ ለመኖር መጣር እና መጋደል ነው፡፡

 

ውድ ወንድሞችና እኅቶች ቤተ ክርስቲያን በብዙ ፈተና በተከበበችበት ዘመን ያለ ነቀፋ በየዋህነትና ያለ ነውር” ለመኖር እና ልዑል እግዚአብሔር በእኛ ደስ እንዲለው ክፋትን በመልካምነት ለማሸነፍ ልንጋደል ይገባል፡፡ ሁላችንም ከቤተሰቦቻችን ርቀን በዓለማዊ የትምህርት አዝመራ ፍሬአማ ለመሆን በምንጥርበት ወቅት ከቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ውጪ መንፈሳዊ ዕሴቶቻችንን ሊፍቁ ከሚሯሯጡ ቀሳጢዎች እራሳችንን መጠበቅ አስፈላጊ ነው፡፡ በዚህም በሁለት በኩል የተሳለ ሰይፍ ሆኖ ለመገኘት መትጋትን የዕለት ተዕለት ጥረታችን ሊሆን ይገባል፡፡ ለዚህም የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም እና የቅዱሳን ጸሎትና ረዳትነት አይለየን፡፡አሜን፡፡

 

ምንጭ፡ 4ኛ ዓመት ቁጥር 1 ጉባኤ ቃና ጥቅምት 2004 ዓ.ም