ዘመነ አስተምህሮ

ኅዳር 6/2004 ዓ.ም

በቤተ ክርስተያናችን የዘመን አቆጣጠር /አከፋፈል/ መሠረት ከኀዳር 6 ጀምሮ እስከ ታኀሣሥ 13 ድረስ ያለው ወቅት ዘመነ አስተምህሮ ይባላል፡፡

መሀረ ማለት ይቅር አለ ማለት ሲሆን፤ ዘመነ አስተምህሮ ማለት ይቅርታ የመጠየቅ /የምልጃ/ ዘመን ማለት ነው፡፡ ዘመኑ ቤተ ክርስቲያን ስለ ልጆቿ ይቅርታ የምትጠይቅበት፤ ምዕመናንንም ስለ በደላቸው ይቅርታ የሚጠይቁበት፤ ስለዚህም በስፋት ትምህርት የሚሰጥበት ዘመን ነው፡፡

በዚህ ዘመን ያሉት አምስት እሑዶችና በእነዚህ እሑዶች የሚጀምሩት ሳምንታት አስተምህሮ፣ ቅድስት፣ ምኩራብ፣ መጻጉዕ፣ እና ደብረ ዘይት በመባል ይጠራሉ በየሳምንቱ ቤተ ክርስቲያን የምታቀርበውን ትምህርት በየጊዜው እናከብራለን የመጀመሪያውን ሳምንት /የአስተምህሮ/ ትምህርት እነሆ: –

እኛ የበደሉንን ይቅር እንደምንል፤ በደላችንን ይቅር በለን /ማቴ.6-12/

ይህ ቃል የተወሰደው ጌታችን በደቀ መዛሙርቱ በኩል እስከ ዓለም ፍጻሜ ድረስ ለሚኖሩ /ዛሬም ላለን/ ክርስቲያኖች እንዲህ ብላችሁ ጸልዩ ብሎ ካስተማረው ፀሎት ነው፤

በሰማይ የምትኖር አባታችን ሆይ ስምህ ይቀደስ መንግሥትህ ትምጣ ፈቃድህ በሰማይ እንደሆነች እንዲሁ በምድር ትሁን፤ የዕለት እንጀራችንን ዛሬ ስጠን፤ እኛም ደግሞ የበደሉንን ይቅር እንደምንል በደላችንን ይቅር በለን፤ ከክፉም አድነን እንጂ ወደ ፈተና አታግባን፤ መንግሥት ያንተ ናትና ኃይልም ክብርም ለዘለዓለም አሜን/ ማቴ.6. 9-14/

ይህ ጸሎት በጥንታውያን የቤተ ክርስቲያን አባቶች እና ሊቀውንት «የጌታ ጸሎት» ተብሎ ይጠራል፡፡ በእኛ ቤተ ክርስቲያን የጸሎቱን የመጀመሪያ ሐረግ በመያዝ «አባታችን ሆይ» ወይም በግእዝ «አቡነ ዘበሰማያት» እንለዋለን፡፡

ይህ ጸሎት ጌታችን ራሱ ያስተማረው በመሆኑ በቤተ ክርስቲያን ትልቅ ቦታ ይሰጠዋል፡፡ የሌሎች ጸሎታት ሁሉ ማሰሪያ /ማሳረጊያ/ ሆኖም ያገለግላል፡፡ በውስጡም «አባታችን ሆይ» ከምትለው ከመጀመሪያዋ ሀረግ ጀምሮ እስከ መጨረሻው ድረስ እጅግ ጥልቅ የሆኑና ነፍስን የሚያጠግቡ ወደ ሰማይ ከፍ የሚያደርጉ መንፈሳዊና ነገረ መለኮታዊ መልእክቶችን ያዘለ ነው፡፡

ይህ የዘመነ አስተምህሮ የመጀመሪያው ሳምንት ስለ ይቅርታ የሚሰበክበት ነውና በጸሎቱ ውስጥ ስለዚህ የሚናገረውን አንቀጽ መሠረት አድርገን እንማራለን፤

«እኛ የበደሉንን ይቅር እንደምንል በደላችንን ይቅር በለን» ከዚህ ቃል በርካታ ነገሮችን እንማራለን፤

1. እግዚአብሔር ኃጢአታችንን ይቅር ሊለን እንደሚወድ

አምላካችን ኃጢአታችንን ይቅር ሊለን ባይወድ ኖሮ ይቅርታን እንድንጠይቅ አይነግረንም ነበር፡፡ አዎ እኛ ከተመለስን ምንም ያህል በደለኛ ብንሆን ይቅር ሊለን፤ ምንም ያህል ብንቆሽሸ ሊያድነን ዝግጁ ነው፡፡ እንዲህ እያለ ይጠራናል፤ «እናንተ ሸክማችሁ የከበዳችሁ፤ ወደ እኔ ኑ፤ እኔም አሳርፋችኋለሁ»፡፡ ስለዚህ በዚሀ ጸሎትም ላይ «በደላችንን ይቅር በለን» ብለን እንድንጠይቀው አስተማረን፤ ይቅር ይለን ዘንድ፡፡

2. ይቅር ለመባል ምን ማድረግ እንዳለብን፤

ይቅር ሊለን ስለ ወደደም ይቅርታን ለማግኘት ምን ማድረግ እንዳለብን በዚሁ ቃል ነግሮናል፤ ማድረግ ያለብን ምንድን ነው?

– ኀጢአታችንን ማወቅ፣ ማመን፣ ማስታወስ

– የበደሉንን ይቅር ማለት

– ይቅርታን መለመን

ኅጢአታችንን ማወቅ /ማመን/

ጌታ «በደላችንን ይቅር በለን» ብለን እንድንጸልይ ሲነግረን በመጀመሪያ ደረጃ በደለኛ እንደሆንን እያስታወስን /እንድናስታውስ እያደረገን/ ነው፡፡

ሁልጊዜም በማሰብ፣ በመናገርና በማድረግ የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ የሆነውን ልባችንን /ኅሊናችንን/ እና ሰውነታችንን እናቆሽሻለን፤ መድኃኔዓለም ክርስቶስ የሞተለትን ማንነታችንን እናጎድፋለን፡፡ ይህም የሰው ልጆች በቅድስና እርሱን መስለን እንድንኖር በኋላም የተዘጋጀልንን የዘለዓለም መንግሥት እንድወርስ ብቻ ፈቃዱ የሆነውን እግዚአብሔርን ያሳዝናል፤ በአርአያውና በአምሳሉ ለክብር የፈጠረው ሰውነታችን መጉደፍ ያስቆጣዋል፤ ንጹሐ ባሕርይ የሆነ እርሱ ኀጢአት አይስማማውምና፡፡

እንግዲህ ይቅር ለመባል በመጀመሪያ እንዲህ ኀጢአት እየሠራን መሆኑን ማወቅና ማመን ያስፈልገናል፡፡ ወደዚህ ዕውቀት ለመድረስም የቅዱሳት መጻሕፍትን ቃል መማር የግድ አስፈላጊ ነው፡፡ ምክንያቱም ስህተት የሚታወቀው ያለውን ሁኔታ /ድርጊታችንን ንግግራችንን፣ ሀሳባችንን.. / መሆን ከነበረበት /ከትክክለኛው/ ጋር በማነጻጸር በሚዛን ላይ በማስቀመጥ ነው፡፡ የማነጻጻሪያ ሚዛኖቻችን ደግሞ በቅዱሳት መጻሕፍት የተጻፉ ሕግጋትና ትዕዛዛት ናቸው፡፡ እነዚህን ስናውቅ ጉድለቶቻችን፣ ድካሞቻችን ፍንተው ብሎ ይታዩናል፡፡ አሊያ ግን እየበደለን ያልበደልን ሊመስለን ይችላል፡፡

የበደሉንን ይቅር ማለት

ጌታ በዚህ ጸሎት ይቅርታ እንድንጠይቀው በማስተማር ይቅር ሊለን እንደሚወድ ዝግጁም እንደሆነ ቢነግረንም ይቅር ለመባል ግን እኛ የበደሉንን ይቅር ማለታችን የግድ እንደሆነ በግልጽ አስቀምጦልናል፤

«በደላችንን ይቅር በለን» ከማለታችን በፊት «እኛ የበደሉንን ይቅር እንደምንል» እንድንል ያዘዘን እኛ ይቅርታ የምናገኘው ሌሎችን ይቅር ስንል ብቻ መሆኑን ለማመልከት ነው፡፡

ጌታችን ይህንን ጉዳይ በሌሎች የተለያዩ ቦታዎችም በተደጋጋሚ አስተምህሮናል፤ በዚሁ በተራራው ስብከት ይኸው ጉዳይ ሁለት ጊዜ በጌታችን ትምህርት ተሰጥቶበታል፡፡


«እንዳይፈረድባችሁ አትፍረዱ በምትፈርዱበት ፍርድ ይፈረድባችኋልና በምትሰፍሩበትም መስፈሪያ ይሰፈርባችኋል፡፡ » /ማቴ.7-2/

በሌላ ቦታም እንዲህ ሲል ይህንኑ ጉዳይ በምሳሌ አስተምሯል፤

መንግስተ ሰማያት ባሮቹን ለመቆጣጠር የወደደን ንጉሥ ትመስላለች መቆጣጠርም በጀመረ ጊዜ እልፍ መክሊት ዕዳ ያለበትን አንድ ሰው ወደ እርሱ አመጡ፡፡ ባለ እዳው ሰው የሚከፍለው ስላጣ እርሱና ሚስቱ ልጆቹም ያለውም ሁሉ እንዲሸጥና ዕዳው እንዲከፈል ንጉሡ አዘዘ፡፡ በዚህም ጊዜ ባርያው ወድቆ ሰገደለትና ጌታ ሆይ ታገሰኝ፤ ሁሉንም እከፍልሃለሁ አለው፡፡ የዚያም ባርያ ጌታ አዘነለትና ለቀቀው፡፡ ይህ ባርያ ግን ወጥቶ ከባልጀሮቹ /እንደርሱ ባርያ ከሆኑት/ መቶ ዲናር ዕዳ ያለበትን አንዱን አገኘና ዕዳህን ክፈለኝ ብሎ ያዘና አነቀው፡፡ ባልንጀራው ባርያም ወድቆ ታገሰኝ፤ ሁሉንም እከፍልሃለሁ፤ ብሎ ለመነው፡፡ እርሱ ግን ሊተወው አልወደደም፡፡ ዕዳውን እስኪከፍልም በወኅኒ አኖረው፡፡ ይህንን ያዩ ሰዎችም አዘኑ፤ ሄደውም የሆነውን ሁሉ ለንጉሡ ተናገሩ፡፡


«ከዚህ ወዲያ ንጉሡ ጠርቶ፣ አንተ ክፉ ባርያ ስለ ለመንከኝ ያን ዕዳ ሁሉ ተውሁልህ፤ እኔ እንደ ማርሁህ ባልንጀራህን የሆነውን ባርያ ልትምረው ለአንተስ አይገባህምን አለው፡፡ ጌታውም ተቆጣና ዕዳውን ሁሉ እስኪከፍለው ድረስ ለሚያሰቃዩት አሳልፎ ሰጠው፡፡»

ጌታ ይህንን ምሳሌ ከተናገረ በኋላ የምሳሌውን ትርጉም እንዲህ ሲል ገልጦታል፤ ብሏል፤ «ከእናንተ እያንዳንዱ ወንድሙን ከልቡ ይቅር ካላለ እንዲሁ ደግሞ የሰማዩ አባቴ ያደርግባችኋል»/ማቴ.18. 23- 35/

በአጠቃላይ ይቅር ለመባል ይቅር ማለት የግድ ነው፡፡ በእኛ ላይ የሚፈረድብን ፍርድ በእኛው እጅ ላይ ነው፡፡ ጌታችን በእነዚህ ትምህርቶች እንዲህ እያለን ነው «እኔ እናንተ ላይ የምፈርደው እናንተ በራሳችሁ ላይ በፈረዳችሁበት መንገድ /መልኩ ነው/»፡፡

ይቅርታ መጠየቅ

ኀጢአታችንን ካወቅንና ካመንን፣ የበደሉንንም ከልብ ይቅር ካልን በኋላ ይቅር እንድንባል መጠየቅ /መለመን/ አለብን ፡፡

«ይቅር በለን» ብላችሁ ጸልዩ ብሎ በማስተማሩ ይህንን እንረዳለን፡፡ ወደ ንስሐ አባት መሄድና ኀጢአትን ተናዞ ቀኖና መቀበል የሚገባው መጀመሪያ በዚህ መልኩ ስለ ኀጢአት ካለቀሱ በኋላ ነው፡፡ ከዚያም ቀኖና ተቀብለን ስንፈጽምም ሆነ ከዚያ በኋላ ይኸው ስለ ኀጢአት ይቅርታ መጠየቁ ይቀጥላል፡፡

በእርግጥም ይቅርታ የምንጠይቀው አዳዲስ ስለ ሠራናቸውና ንስሐ ገና ስላልገባንባቸው ኀጢአቶቻችን ብቻ ሳይሆን ንስሐ ስለ ገባንባቸው ስለ ቀደሙት በደሎቻችንም ጭምር ነው፡፡ እንደ ቅዱስ ዳዊት «የቀደመ በደላችንን አታስብብን ምሕረትህ በቶሎ ታግኘን» /መዝ.78-8/ እያልን ሰለ ቀደሙ በደሎቻችንንም እያሰብን በሕይወታችን ዘመን ሁሉ መጠየቅ አለብን፡፡

ይቅርታ የምንጠይቀው ስለምናውቃቸው /ስለምናስተውላቸው/ ኀጢአቶቻችን ብቻ ሳይሆን ስለ ማናስተውላቸውም መሆን አለበት፡፡ ስለዚህ «ይቅር ብለን» ስንል እኛ ካስተዋልናቸው መንገዶች ውጪ በብዙ መልኩ እርሱን እንደምንበድል አስበን ተማጽኗችን ስለነዚህም መሆን አለበት፡፡

ስለዚህ ለጸሎት ከመቆማችንና የጌታን ጸሎት ከመጸለያችን በፊት የበደሉንን ይቅር እንዳልን እርግጠኛ መሆን አለብን እኛ የበደሉንን ይቅር እንዳልን ልንል ነውና፡፡

«እኛንም በደላችንን ይቅር በለን» ስንልም ከላይ ያየናቸውን ነገሮች ሁሉ እያሰብን፤ ይቅር ሊለን የወደደ አምላካችንንም እያመሰገንን መሆን አለበት፡፡ በእውነት ይህንን ጸሎት የምንጸልየው በዚህ መልኩ ነውን? ካልሆነ ልምምዱን ዛሬውኑ እንጀምረው፡፡ ይህንን ማድረግ እንችል ዘንደ የእግዚአብሔር ቅዱስ ፈቃዱ ይሁንልን አሜን፡፡

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

Gubae_Qana

እነሆ እኔ በእናንተ ደስ ይለኛል፡፡ ፊል. 2፡17

ቤተ ክርስቲያን ከተመሠረተችበት ጊዜ አንሥቶ የቀና እውነተኛና መልካም ጉዞዋን የሚፈታተኑ በዙሪያዋ ጠፍተው አያውቁም፡፡ ከሰው መፈጠር በፊት በመላእክት ዘንድ የነበረችው የመላእክት ማኅበር በክፉው መልአክ /በዲያብሎስ/ እና እርሱን በመሰሉ ጭፍራዎቹ መካከል Gubae_Qanaያለ ነውርና ነቀፋ በመገኘቷ የተመረጠች ነበረች፡፡

 

በጥንተ አበው ታሪክም የምናየው ይህንኑ ነው፡፡ ከአቤል ጀምሮ እስከ ዮሴፍ ያሉ አበው በክፉዎች ብዙ መከራ የደረሰባቸው፣ በዚህች ምድር ላይ እንግዶችና መጻተኞች ሆነው የኖሩ ናቸው፡፡ጌታችን ወደዚህ ምድር በሥጋ እስከመጣበት ድረስ የነበሩት የእስራኤል ልጆች ታሪክም በክፉና መልካም ነገሮች ከሚጎረብጠው ትውልድ መካከል የነበረ ውጣ ውረድ የበዛበት ነው፡፡

የአበው ተስፋ ተፈጽሞ ጌታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም በሥጋ መወለዱን፤ በሞቱና በትንሣኤው ዓለምን ማዳኑን የምሥራች አምነው፤ በሐዋርያት ስብከት የተሰበሰቡ እግዚአብሔር ደስ የሚሰኝባቸው ማኅበረ ምእመናንም በዚሁ ታሪክ እንደኖሩ መጽሐፍ ቅዱስ ምስክር ነው፡፡
ቅድስት ቤተ ክርስቲያን በመጀመሪያዎቹ ክፍለ ዘመናት ብዙ መከራ ስትቀበል ነውርና ነቀፋ የሌለባቸውንም ብዙ ቅዱሳን አፍርታለች፡፡ ቤተ ክርስቲያን በሰማዕታት ዘመን ክርስቶስን እንዲክዱ ከክፉና ጠማማው ትውልድ ብዙ መከራ ደርሶባቸው በእምነታቸው በመጽናት ያለነቀፋና ነውር ሕይወታቸውን ለእግዚአብሔር ያቀረቡ “እነሆ በእናንተ ደስ ይለኛል” ፈል.፪፥፲፯ ብሎ እግዚአብሔር የተናገረላቸው አሁን የምንዘክራቸው ብዙ ቅዱሳን ሰማዕታትን አግኝታለች፡፡

የመከራው ዘመን ለጊዜውም ቢሆን ሲያልፍ የቀጠለው መናፍቃን በቤተ ክርስቲያን ላይ ያመጡት መከራ ነበር፡፡ ቤተ ክርስቲያንን እስከ መከፋፈል የደረሱ ሰዎች በአሕዛብ መንደር የሊቃቀሙትን የሐሰት ትምህርት ከቤተ ክርስቲያን ንጹሕ አስተምህሮ ጋር ለማቀያየጥ በሞከሩ ጊዜ በትምህርታቸው ነውርና ነቀፋ የሌለባቸው ሊቃውንት አበው ብዙ መከራ ተቀብለው እውነተኛውን አስተምህሮ አጽንተዋል፡፡
ከዚያም በኋላ እስካሁን የቤተ ክርስቲያንን አስተምህሮ ለመበረዝ አልፎም ለማጥፋት የሚታትር ትውልድ ጠፍቶ አያውቅም፡፡ ያለንበትም ዘመን ከምንጊዜውም የበለጠ ለቤተ ክርስቲያን አስቸጋሪ ዘመን መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ክፉ አሳቢነት በአብዛኛው ተንሰራፍቶ እና ተደላድሎ የሚታይበት ዘመን ነው፡፡

 

ዘመኑ የክርስቲያኖችን ልቦና ለመክፈል በሚችሉ አያሌ እንግዳ እና አደገኛ አስተሳሰቦች በተለይ በወጣቱ ዘንድ የተናኙበት ዘመን ነው፡፡ በነዚህ ሁሉ ከክርስትና ጋር የማይስማሙ የእንግዳ አስተሳሰቦች ማዕበል መካከል ደግሞ ከኃጢአት ርቆ ለመኖር የሚታገሉ የቤተ ክርስቲያን ልጆችን የሚፈታተን ልቅ ዓለማዊነት በስፋት የሚሰበክ የዓለም ሥርዓት መሆን ጀምሯል፡፡

 

በዚህ ሁሉ መካከል የሐዋርያው የቅዱስ ጳውሎስን ምክር ሁል ጊዜም በልቦናችን መያዝ እና ማስታወስ አስፈላጊ ነው፡፡ “በመጥፎና በጠማማ ትውልድ መካከል ያለነቀፋ የዋሆችም ነውርም የሌለባቸው የእግዚአብሔር ልጆች እንድትሆኑ ሳታንጎራጉሩ ክፉም ሳታስቡ ሁሉን አድርጉ፤ በእነርሱም መካከል የሕይወትን ቃል እየሰበካችሁ እንደብርሃን ትታያላችሁ” /ፊል.፪፥፲፬-፲፮/፡፡ ምንም እንኳ ክፉና ጠማማ ትውልድ መኖሩ የማይፈለግ ቢሆንም ከኖረ ዘንድ ግን ክፉን ለመልካም ማዋል የሚችል እግዚአብሔር ብዙ ቅዱሳን የሚገኙበት፣ የቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ እንደማለዳ ፀሐይ እየደመቀ እንዲሔድ ማድረጊያ መንገድ አድርጎታል፡፡ በእኛ ዘመንም እግዚአብሔርን ይህን ከማድረግ የሚከለክለው የለም፤ የሚፈለገው “በክፉና በጠማማ ትውልድ” መካከል ሆኖ እንደ ቤተ ክርስቲያን ትእዛዝ ለመኖር መጣር እና መጋደል ነው፡፡

 

ውድ ወንድሞችና እኅቶች ቤተ ክርስቲያን በብዙ ፈተና በተከበበችበት ዘመን ያለ ነቀፋ በየዋህነትና ያለ ነውር” ለመኖር እና ልዑል እግዚአብሔር በእኛ ደስ እንዲለው ክፋትን በመልካምነት ለማሸነፍ ልንጋደል ይገባል፡፡ ሁላችንም ከቤተሰቦቻችን ርቀን በዓለማዊ የትምህርት አዝመራ ፍሬአማ ለመሆን በምንጥርበት ወቅት ከቤተ ክርስቲያን አስተምህሮ ውጪ መንፈሳዊ ዕሴቶቻችንን ሊፍቁ ከሚሯሯጡ ቀሳጢዎች እራሳችንን መጠበቅ አስፈላጊ ነው፡፡ በዚህም በሁለት በኩል የተሳለ ሰይፍ ሆኖ ለመገኘት መትጋትን የዕለት ተዕለት ጥረታችን ሊሆን ይገባል፡፡ ለዚህም የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያም እና የቅዱሳን ጸሎትና ረዳትነት አይለየን፡፡አሜን፡፡

 

ምንጭ፡ 4ኛ ዓመት ቁጥር 1 ጉባኤ ቃና ጥቅምት 2004 ዓ.ም

weddingpic

ሰርግ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ትምህርት

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

ኅዳር 06/2004 ዓ.ም.

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ቅዱስ ጳውሎስ ለቈላስይስ ሰዎች በላከው መልእክት ም.፬፥፲፪ ላይ ያለውን ኃይለ ቃል በተረጎመበት ፲፪ኛው ድርሳኑ በዘመኑ የሚፈጸመውን የሰርግ ሥርዐት መሠረት በማድረግ ሰርግን አስመልክቶ ሰፋ ያለ ትምህርትን ሰጥቶአል ፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ በሰርግ ምክንያት የሚወጡትን ወጪዎችና ግርግርና ሁካታ አጥብቆ የሚቃወም አባት ነው ፡፡ በዚህም ጽሑፍ ይህን ወደማስተዋል ልንመጣም እንችላልን ፡፡ መልካም ንባብ

ስለዚህ እንዲህ ብሎ ያስተምራል ፡- ትዳር ምንድን ነው? ትዕይንት(ትያትር) ነውን ? አይደለም፡፡  ምንም እንኳ እናንተ ለትዳርና ለምሳሌውweddingpic አክብሮት ባይኖራችሁ ትዳር ግሩም ምሥጢርና የታላቅ መንፈሳዊ ምሥጢር ምሳሌ ነው ፡፡ ቅዱስ    ጳውሎስ ስለዚህ ሲያስተምር “ይህ ምሥጢር ታላቅ ነው”   ይልና ጨምሮ “እኔ ግን ስለ ክርስቶስና    ስለ  ቤተ ክርስቲያን እላለሁ” ይላል   ፡፡(ኤፌ.፭፥፴፪) ጋብቻ የቤተ ክርስቲያንና   የክርስቶስ ምሳሌ ነው ፤  እንዲህ በከበረ    ምሥጢር ላይ ዳንኪረኞችን በመጋበዝ   ዝሙትን ታስተዋውቁበታላችሁን ? ነገር   ግን  ከእናንተ መካከል አንዱ እኔን፡- እንዲህ ስትል ደናግል ወይም ያገቡት አይጨፍሩ እያልክ ነው ፤  እንግዲያ እነርሱ በዚህ ሰርግ ላይ ካልጨፈሩ ማን ሊጨፍር ነው ? ብሎ ሊጠይቅ ይችላል ፡፡ ማንም  አይጨፍር ነው መልሴ ፡፡

በአሕዛብ ዘንድ ይህን በመሰሉ ሥርዐቶቻቸው ዳንኪረኞች ዳንኪራቸውን ያቀርባሉ፡፡ በእኛ ግን ማንኛውም ምሥጢራት ሲከናወኑ በጸጥታ፣ በትሕትናና  በጥሩ ሥነምግባር እንዲሁም በመልካም ሥርዐት ነው፡፡ ይህ የጋብቻ ሥርዐት አመንዝሮች ከተጠሩበት እግዚብሔርን የማይፈሩ ከተጋበዙበት እንዴት ብለን ነው መንፈሳዊ ጋብቻ ብለን ልንጠራው የምንችለው ? እንዲህ ከሆነ እንዴት ተብሎ ነው ሁለቱ አካላት አንድ ሆነዋል ልንል የምንችለው ?

ክርስቶስ በተገኘበት ጋብቻ ግን ዳንኪራ የለም የእምቢልታም ድምፅ አይሰማበትም፡፡ ነገር ግን ግሩም የሆነ ጸጥታ የሰፈነበት፣ በታላቅ መንፈሳዊ ሥርዐት የሚከናወን ነው፡፡ በዚህ ሥርዐት  አንድ አካል ወደመሆን ሲመጡ አንድነታቸው ሕይወት አልባ ፍጥረታት እንደሚኖራቸው አንድነት ወይም በዚህ ምድር የሚታየውን ዓይነት አንድነት አይደለም፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሔር አርዓያና አምሳል ሆነው አንድ ይሆናሉ፡፡ ይህ ታላቅ የሆነ ምሥጢር በሚከናወንበት ሥፍራ እንደ አራዊት ታላቅ ሁካታና ረብሻ እንዲሁም ነፍስን የሚያሳድፉ ታላቅ የሆነ በደል ይፈጸማልን ?

ሁለቱ አንድ አካል በመሆናቸው በዚህ ያለውን የፍቅርን ምሥጢር አስተውል ፡፡ እነዚህ ሁለት አካላት ሁለትነታቸውን ይዘው የሚቀጥሉ ከሆነ ብዙ ሊሆኑ አይችሉም ፡፡ ነገር ግን አንድ ወደመሆን ሲመጡ ብዙዎች ይሆናሉ ፡፡ ከዚህ ምን እንማራለን ? የትዳርን ታላቅነት አይደለምን ? ሥላሴ ሁለት የሆነው አካል አንድ አድርጎ ፈጠረው ስሙንም ሰው አለው፡፡ ይህን አንድ የሆነው አካልንም ሁለት በማድረግ ገለጠው ፡፡ ምንም እንኳ እነዚህ አካላት ሁለት ቢሆኑ የእግዚአብሔር ፈቃድ  ግን አንድ ይሆኑ ዘንድ ነበር ፡፡

በዚህም ምክንያት አንዱ አምሳሉን ለመውለድ ብቻውን ብቁ እንዲሆን አላደረገውም ፡፡ ስለዚህ ከተቃራኒው አካል ጋር አንድነትን ላልመሠረተ ሰው አንድ አካል የሚባለው ስያሜው አይሰጠውም ነገር ግን የሌላኛው ግማሽ አካል ይባላል ፡፡ ለዚህም ምስክሩ ልጅን መውለድ አለመቻሉ ነው ፡፡ ይህ እግዚአብሔር አስቀድሞ የሠራው ሥርዐት ነው፡፡ የጋብቻን ምሥጢር አስተዋላችሁን ? አስቀድሞ አንድ አድርጎ ፈጠራቸው በኋላም ነጣጠላቸው ፤ እንደገና ሁለት የነበሩትን እነዚህን ወገኖች ወደ አንድነት አመጣቸው ፡፡ እንዲህም አድርጎ ስለሠራው ሰው በትዳር አንድ ከሆኑ ወገኖች እንዲፈጠር ሆነ ፡፡

ባልና ሚስት ሁለት አካላት አይደሉም ነገር ግን አንድ አካል ናቸው ፡፡…. ይህን “ሰውን በአርዓያችንና በአምሳላችን እንፍጠር …ወንድና ሴት አድርጎ ፈጠራቸው” (ዘፍ.1፡27) በሚለው ቃል ማረጋገጥ ይቻላል  ፡፡ ባል ራስ ነው ፤ ሚስት ደግሞ ቀሪው አካል ናት ፡፡ ስለዚህ አንዱ የደቀመዝሙርነት ማዕረግ ሲኖረው አንዱ የመምህርነት ቦታ ይይዛል አንዱ መሪ ሲሆን ሌላው ደግሞ ታዛዥ አደረገው ፡፡ ሔዋን ከአዳም ጎን ትገኝ እንጂ ወደ ኋላ መለስ ብለን የእርሱዋን ልደት ስንመረምረው አንድ አካል እንደነበሩ ማስተዋል እንችላለን  ፡፡በዚህ ምክንያት አንድ አካል እንደሆኑ ለማስረዳት ሲል እግዚአብሔር አምላክ ሴቲቱን ረዳት አላት፡፡ (ዘፍ.2፡18) በአንድነት ከመኖራቸውና አባትና እናት ከመሆን ባለፈ አንድ አካል በማድረግ አከበራቸው፡፡ (ዘፍ.2፡24)

በሌላ መልኩ ደግሞ አባት ወንድ ልጁ ወይም ሴት ልጁ የራሳቸውን አካል አግኝተው በመጣመራቸው እጅግ ደስ ይሰኛል፡፡ አባት ምንም ሀብት የተረፈው ባለጠጋ ቢሆን ወንድ ልጁ ወይም ሴት ልጁ ያላገቡ  ከሆኑ ውስጡ ምንም ዓይነት መረጋጋት አይኖረውም፡፡ ይህን ታግሶ መኖርም አይቻለውም፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ ምንም ልጅ ከእናቱ አካል ተከፍሎ የተወለደ ቢሆን በዚህ ምድር ዘሩ እንዲቀጥል ብቻውን በቂ አይደለም፡፡ ስለዚህም በራሱ ሙሉ አይደለም ማለት ነው፡፡ ስለዚህም ነቢዩ ሚልክያስ “እግዚአብሔር የሕይወትን መንፈስ አንድ አድርጎ ጠብቆልን የለምን? እርሱም የሚፈልገው ምንድን ነው? ዘር አይደለምን? (ሚል.፪፥፲፭) ይለናል፡፡

እንዴት ነው ታዲያ አንድ ሥጋ ወደ መሆን የሚመጡት ? እጅግ ንጹሕ የሆነን ወርቅን ማግኘት ከፈለግህ ወርቅህን ከሌላ ወርቅ ጋር ትቀይጠዋለህ፤ ከእነዚህም አንድነት ልዩ የሆነ ወርቅ ይገኛል፡፡ በዚሁ መልክ እናት በደስታ ዘርን ተቀብላ ከራሱዋ ጋር በማዋሐድ፣ ፅንሱን በመመገብና እንክብካቤ በማድረግ ሰው ሆኖ ወደዚህ ዓለም እንዲመጣ የራሱዋን ድርሻ ትወጣለች፡፡ልጅ እንደ ድልድይ ነው ፡፡ በእርሱም ምክንያት ሦስቱ አንድ ሥጋ ይባላሉ ፡፡ ልጅ ሁለቱ አካላት ፍጹም አንድ እንዲሆኑ ያደርጋቸዋል ፡፡ በመካከላቸው ባለው ታላቅ ወንዝ ምክንያት የተለያዩ ከተሞች በወንዙ ላይ በሚሠራው ድልድይ ምክንያት ሁለት መሆናቸው ቀርቶ አንድ እንዲሆኑ እንዲሁም ልጅም እንዲህ ነው ፡፡

ልጅ በፊት በባልና በሚስት መካከል የተፈጠረውን አንድነት ይበልጥ ያጠናክረዋል ፡፡ ለባልና ሚስት ድልድይ የሆነው ልጅ የሁለቱ ተዋሕዶ ውጤት ነውና ፡፡ ራስና ቀሪው አካል በአንገት አንድ እንዲሆን ፣ እንዲሁ ልጅም በባልና በሚስት መካከል ሆኖ በእነርሱ መካከል ያለውን አንድነት ይበልጥ ያጠብቀዋል ፡፡ ከልዩነታቸው ይልቅ አንድነታቸውን በልጅ ምክንያት ይበልጥ እየጠበቀ ይመጣል ፡፡

እንዲሁም ዘማርያን በአንድነት ሲዘምሩ ዝማሬው አንድ ሆኖ ይወጣል ፡፡ ወይም ሁለት ወገኖች እጃቸውን እርስ በእርሳቸው ቢያቆላልፉ ከእንግዲህ አንድ እንጂ ሁለት አይደለንም ማለታቸው እንደሆነ እንዲሁ ባልና ሚስትም በአንድነታቸው በሚፈጠሩት በልጅ በኩል ፍጹም የሆነ አንድነትን ይመሠርታሉ ፡፡ ስለዚህ ጌታችን ግሩም በሆነ ቃሉ “ሁለቱም አንድ ሥጋ ይሆናሉ አለ” በተለይ በልጆቻቸው ፡፡ እንዲህ ሲባል ባልና ሚስት ልጅ ካልወለዱ ሁለት እንደሆኑ አይቀጥሉም ማለት ነውን ? በፍጹም አይደለም ፤ ሁለቱ በሥጋ ሲተባበሩ አንድ አካል ወደ መሆን ይመጣሉ ፡፡ የሽቶ ዘይትን ከሌላ የሽቶ ዘይት ጋር ሲደባልቁት አንድ እንዲሆኑ ከተቀየጡም በኋላ አንድ የሽቶ ዘይት እንዲሆኑ እንዲሁ በዚህም እንዲሁ ነው ፡፡

እኔ አሁን እንዲህ በግልጽ ስለዚህ ጉዳይ በመናገሬ አንዳንዶች ነውር ነው በማለት ትምህርቴን እንደሚጠየፉት እረዳለሁ ፡፡ ለዚህ ምክንያቱ ምንድነው ? ይህን አሁን የምናገረውን እንደ ብልግና ንግግር ስለሚቆጥሩት ነው ፡፡እነዚህ ወገኖች በትዳር ውስጥ የሚፈጠረውን እንደዚህ ላለው አንድነት ልዩ የነቀፋ ስም ይሰጡታል (ብልግና ይሉታል) ፡፡ ነገር ግን ቅዱስ ጳውሎስ “መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር መኝታውም ንጹሕ ይሁን”(ዕብ.፲፫፥፬) ብሎ አስተምሮናል ፡፡

ስለምን እናንተ ክቡር የሆነውን እንደ ነውር ፣ ንጹሕ የሆነውን እንደ ርኩስ ትቆጥሩታላችሁ ? ይህ ጋብቻን እንደ ርኩሰት የሚቆጥሩትና በራሳቸው አካል ላይ ዝሙትን የሚፈጽሙ የከሃድያን አመለካከት ነው፡፡ ስለዚህም ነው ይህን ክፉ አስተሳሰብ ለማጥራትና ወደ ቀድሞው ክብሩ ለመመለስ ስል በዚህ መልክ ያስተማርኩት፡፡ በዚህም እስተምህሮ የከሃድያን አፍ ይዘጋል፡፡

እነርሱ የእግዚአብሔርን ድንቅ ስጦታንና የልደታችን መሠረት የሆነውን ተራክቦን ሲነቅፉት ይሰማሉ፡፡

ይህን የመገኛችን ምንጭ የሆነውን ተራክቦ እንደ ቆሻሻና እንደማይጠቅም ረብ የለሽ ከንቱ ነገር አድርገው ይቆጥሩታል፡፡ ስለዚህ እኛ ይህን አስተምህሮ ከዚህ ዓይነት አመለካከት ንጹሕ ልናደርገው ይገባናል፡፡ተወዳጆች ሆይ ይህ ጉዳይ ሲነሣ እንደሚጠየፉት ከሃዲያን እንድንሆን አልሻም፤ ይልቁንስ ከእነርሱ አጸያፊ ሥራ ትሸሹ ዘንድ እመክራችኋለሁ፡፡ ነገር ግን በዚህ እነርሱን የምትመስሉዋቸው ከሆነ በቀጥታ እግዚአብሔርን እየተሳደባችሁ ነው፡፡

ትዳር ለቤተ ክርስቲያን የተፈጸመላት ምሥጢር ምሳሌ እንደሆነ ላስረዳችሁን? ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያንን የራሱ ሲያደርጋትና በመንፈሳዊ ተዋሕዶ ከእርሱዋ ጋር አንድ ሲሆን ቅዱስ ጳውሎስ “እንደ ንጽሕት ድንግል” ይልና “እናንተን ለክርስቶስ ላቀርብ ለአንድ ወንድ አጭቻችኋለውና” ይለናል፡፡ (፪ቆሮ.፲፪፥፪) ታዲያ እኛ ምን ሆንን ? የእርሱ የአካል ሕዋሳቶችና “ሥጋው” ሆንን፡፡ ይህን ሁሉ በማስተዋል ታላቅ ምሥጢር የሆነውን ትዳርን ከማቃለል እንቆጠብ፡፡ ሰርግ ማለት የክርስቶስ በሰዎች መካከል ሰለመገኘቱ የሚመሰልበት ታላቅ ምሥጢር ነው፡፡ ታላቅ የሆነው ይህ ምሥጢር በሚፈጸምበት ቦታ ስካር የሚገባ ነውን? ንገረኝ  የንጉሥ ምስል በቆመበት ስፍራ ሆነህ እርሱን ማዋረድ ትጀምራለህን? ይህን ፈጽሞ አታደርገውም፡፡

አሁን ግን ሰርግ ሲሲረግ  ሰርጉ ለተመሰለበት ምሳሌ ተገቢውን አክብሮት ከመስጠት ይልቅ ቦታውን የኃጢአት መፍለቂያ ምንጭ አድርገነዋል፡፡ ሥርዐቱ ሙሉ ለሙሉ ተለውጦ ሕገወጥ ሥራዎች የሚፈጸሙት ሥርዐት ሆኗል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ “የሚያሳፍር ነገርም የስንፍና ንግግርም ወይም ዋዛ የማይገቡ ናቸው” አላለንምን? እንዲሁም “ለሚሰሙት ጸጋን ይሰጥ ዘንድ እንደሚያስፈልግ ለማነጽ የሚጠቅም ማናቸውም በጎ ቃል እንጂ ክፉ ቃል ከአፋችሁ ከቶ አይውጣ፡፡” (ኤፌ.፭፥፬፤፬፥፳፱) ብሎ አላስተማረንምን? አሁን ግን በዚህ ታላቅ በሆነ ምሥጢር ላይ የስንፍና ንግግር፣ ዋዛ ፈዛዛ ነገሮች፣ ፌዝና ቀልዶች ሞልተውበታል፡፡

እነዚህ ከንቱ ነገሮች በቀላሉ የሚቀርቡም አይደሉም  እኮ እነዚህ ከንቱ ነገሮች እንደ ጥበብ ተቆጥረው በአቅራቢዎቻቸው ተቀናብረው በሰርጉ ለታደሙት ይቀርባሉ፡፡ ይህንንም ለሚያቀርቡ ሰዎችም ታላቅ ክብርና  ምስጋና ይሰጣቸዋል፡፡ ይገርማል  ኃጢአት እንደ ጥበብ ተቆጠረ፡፡ ከዚህም በላይ ኃጢአትን ለእኛ የሚያስተዋውቁንን ወገኖች ትዕይንት የምንከታተለው  ትኩረት ሰጥተንና በጸጥታ ነው፤ ከአንደበታቸው የሚያወጡትንም ቃል በአጽንዖት በመስማት ጭምር እንጂ እንዲያው በከንቱ አናዳምጣቸውም፡፡ ስለዚህ ዲያብሎስ በዚህ የሰርግ ቤት ለእርሱ ወታደሮች ይሆኑ ዘንድ ሠራዊቶችን ይመለምላል፡፡ ስካር ባለበት ቦታ ዝሙት አለ፡፡ ከንቱ ንግግር ባለበት ቦታ ሰይጣን የራሱን አስተዋጽኦ ለማድረግ ይመቸዋል፡፡ እስቲ ንገረኝ እንዲህ በሆነ ቦታ ሰይጣን እንዲገኝ እየጋበዝህ ክርስቶስ የሚገኝበትን ምሥጢር እየፈጸምኩ ነው ትላለህን?

አንተ እኔን ለዚህ ነገር ጠንካራ ተቃዋሚ እንደሆንኩ አድርገህ ትቆጥረኛለህ ፡፡ ከዚህ ጥመትህ ትድን ዘንድ አንተን በጽኑ የሚገሥጽህንም ሰው እንዲህ እንድትመለከተው አውቃለሁ ፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ አንተን “የምትበሉም የምትጠጡም ብትሆኑ ወይም ማናቸውም ተግባር ብታደርጉ ሁሉን ለእግዚአብሔር ክብር አድርጉት”(፩ቆሮ.፲፥፴፩) አላለህምን ? አንተ ግን ሥራዎችህን ሁሉን ራስህን ለማዋረድና የሰውን ልጅ ለሚጎዱ ነገሮች ታውላዋለህ ፡፡ ነቢዩስ “ለእግዚአብሔር በፍርሃት ተገዙ በረዓድም ደስ ይበላችሁ”(መዝ.፪፥፲፩) አላለህምን ? አንተ ግን ሥርዐት አልባ ሆነህ ትመላለሳለህ ፡፡

በአንድ ጊዜ ደስታውንና ጥንቃቄውንም ማስኬድ ትፈልጋላችሁን? አጥንትን የሚያለመልም መዝሙርን መስማትስ ትሻላችሁን? በእርግጥ ከመዝሙሮች ሁሉ የሚልቅ መዝሙርን ልትሰሙ ትችላላችሁ፡፡ እናንተ ግን አትፈቅዱም፤ ብትፈቅዱ ግን  ሰይጣናዊ ዘፈኖች ከመስማት ይልቅ መንፈሳዊ ዝማሬን ለመስማት ትበቃላችሁ፡፡ የመዘምራንን ግሩም የሆነ መጓደድ መመልከት ትሻላችሁ? እነሆ የመላእክት ዝማሬና መጓደድ፡፡ እንዴት ሆኖ ነው የእነርሱን ዝማሬን መስማት በልዑል ፊት መጓደዳቸው መመልከት የሚቻለው ብሎ የሚጠይቀኝ ካለ “እነዚህን ግሳንግሶችን ከነአካቴው ከተውክና በሰርግህ ክርስቶስ እንዲገኝ ከፈቀድክ ይህ ይሆናል፡፡  ክርስቶስ በሰርግህ የታደመ ከሆነ መላእክትም ከእርሱ ጋር በሰርግህ ይገኙልሃል፡፡

ከአንተ ዘንድ ፈቃዱ ካለ እርሱ በአንተ ሰርግ መገኘት ብቻ አይደለም  ውኃውን ወደ ወይን ጠጅነት በመቀየርም ሰርግህን ያደምቅልሃል፡፡ እንደ ውኃ ቀዝቃዛና ወራጅ የሆነውን የዚህን ዓለም ደስታና ፈንጠዝያ አጥፍቶ መንፈሳዊ ደስታን ከሚያጎናጽፈው ከዚህ ተአምር በላይ ምን ድንቅ ተአምር አለ!! ይህ ነው ውኃውን ወደ ወይንነት የመቀየሩ ትርጉም፡፡ እንቢልታ ነፊዎች ባሉበት ክርስቶስ ፈጽሞ አይገኝም፡፡ እርሱ በዚህ ሰርግ ቢገኝ እንኳ መጀመሪያ ይህንን አስወግዶ ነው፡፡ ከዚያም የራሱን ተአምርን ይፈጽማል፡፡ ከዚህ የሰይጣን መሳሪያ ከሆነ እቢልታ በላይ ምን የሚጠላ ነገር አለ? ሁሉ በሥርዐት ካልሆነ ምንም ነገር ያለጥቅም ይሆናል፡፡ ድካማችን ሁሉ ያለፍሬ ይቀራል እኛንም ወደ ውርደት ይጥለናል፡፡

ከመልካም ሥነምግባር የበለጠ አስደሳች ነገር የለም፣ ሥርዐት ወዳድ ከመሆን የበለጠ ጣፋጭ የሆነ ነገር የለም፣ ጽድቅ ለመፈጸም ቆራጥ ከመሆን የበለጠ ተወዳጅ ነገር የለም፡፡ ሁሉም ሥርዐቶቻችን ልክ እኔ ስለጋብቻ ሥነ ሥርዐት ባስተማርኩት መልክ ይሁኑ፡፡ እንዲህ ከሆነ ደስተኛ ልንሆን እንችላለን፡፡

ነገር ግን ጋብቻን ሊያደርግ የሚሻ ሰው ከማን ጋር ጋብቻውን መፈጸም እንዳለበት ይጠንቀቅ፡፡ ሴት ልጅ ያለችው ሰው   አስቀድሞ እውነተኛና እርሱዋን ሊንከባከባት የሚችል ባልን ሊፈልግላት ይገባል፡፡ እንዲህ ዓይነት ወንድ ለአካል ራስ እንዲሆን ሊመረጥ ይገባዋል፡፡ ለእርሱ ስትሰጥም እንደ ባሪያ አድርጎ ሊይዛት ሳይሆን እንደ ልጁ ሊያያት ሊሆን ይገባል፡፡

ሀብት ስላለው ወይም ከከበረ ቤተሰብ በመሆኑ ወይም ሰፊ ግዛት ስላለው እርሱን ለልጃችሁ ባል ይሆን ዘንድ አትምረጡ፡፡ ነገር ግን በነፍሱ ትሑት፣ አስተዋይ፣ ቅንነት ያለውና እግዚአብሔርን የሚፈራ የሆነን ሰው ለልጃችሁ ባል ይሆን ዘንድ ምረጡ፡፡ እንዲህ ከሆነ የምታፈቅሩዋት ልጃችሁ በደስታ ልትኖር ትችላለች፡፡ ባለጠጋ ሆኖ በምግባሩ ግን ብልሹ የሆነን ሰው ለልጃችሁ ባል ይሆን ዘንድ ያጫችሁት ከሆነ እርሱዋን አለመጥቀማችሁ ብቻ ሳይሆን እርሱዋን ነጻ ሰው ከማድረግ ይልቅ የእርሱ ባሪያ በማድረግ ትጎዱአታላችሁ፡፡ ልጃችሁ የእርሱ ሚስት በመሆኑዋ ምክንያት በምታገኛቸው ሀብት ደስ ከመሰኘት ይልቅ እርሱዋን እንደ ባሪያ ቆጥሮ በእርሱዋ ላይ የሚያደርስባት በደል የከፋ ይሆናል፡፡

እንዲህ ዓይነት ድርጊትን ከመፈጸም ትቆጠቡ ዘንድ እለምናችኋለሁ ፡፡  ነገር ግን ከእርሱዋ ጋር ተቀራራቢ ኑሮ ያለውን ለልጃችሁ ባል ይሆን ዘንድ ታጩ ዘንድ እመክራችኋለሁ ፡፡ ይህ ባይሆን ምንም ሀብት ለሌለው ነገር ግን በጎ ሕሊና ላለው ሰው ትድሩዋት ዘንድ አሳስባችኋለሁ ፡፡ እንዲህ በማድረጋችሁ ልጃችሁን ሌላው ቢቀር ለአንድ ጌታ ልጃችሁን እንደባሪያ ከመሸጥ ተቆጥባችሁ በትክክለኛው ትርጉም እንደ ባል ሊሆናት ለሚችል ሰው መስጠት ይቻላችኋል ፡፡

ለልጅህ ባል የሚሆናትን ጥሩ ሥነ ምግባር የተላበሰውን ሰው በጥንቃቄ መርምረህ በማግኘት  ልትድራት ስትዘጋጅ ክርስቶስ ኢየሱስ በጋብቻው ሥነ ሥርዐት ላይ  እንዲገኝልህ ጥራው፡፡  በዚህ የደስታ ቀንህ እርሱን በእንግድነት እንዲገኝ  ስለጋበዝከው ቅር አይሰኝም፡፡ ምክንያቱም እርሱ የሚገኝበት ምሥጢር ነውና፡፡ አዎን ከዚሀ ይልቅ ግን አስቀድመህ ለልጅህ ባል አድርገህ ያጨኸውን ሰው  እርሱ እግዚአብሔር ተወዳጅ ባል ያደርገው ዘንድ ለምነው፡፡

የአብርሃም ባሪያ እንኳ ያላደረገውን አስከፊ ድርጊት ከማድረግ ግን ራስህን ጠብቅ፡፡ እርሱ በጌታው በአብርሃም በተላከ ጊዜ እግዚአብሔርን መንገዱን ያቀናለት ዘንድ ለምኖት ነበር፡፡ እንዲህ በማድረጉም ሁሉን ነገር ሰመረለት፡፡ እንዲሁ አንተም ለልጅህ ባልን በመፈለግ አእምሮ ቢባክን ወደ እግዚአብሔር  “ጌታ ሆይ አንተ የፈቀድከውን አድርግ”  ብለህ ጸልይ፡፡ ለእርሱን እንዲህ በማለት ፈቃድህን አሳልፈህ ስጠው፡፡ በዚህ መልክ ለእርሱ ክብርን ስጥ፤ እርሱም በምላሹ ፈቃድህን በመፈጸም ያከብርሃል፡፡ በእርግጥ አንተን ሁለት ሥራዎች ይጠብቁሃል፡፡ እነርሱም ፈቃድህን ለእርሱ ሙሉ ለሙሉ መስጠትና፣  እርሱ የመሰከረለትን በጥሩ ሥነ ምግባር የታነጸውን ሰው መሻት ናቸው፡፡

የልጅህን ሰርግ ለመሰረግ በምትዘጋጅበትም ጊዜ እቃዎችንና ልብሶችን ለመዋስ ስትል ቤት ለቤት አትዙር፡፡ ምክንያቱም ሰርጉ የሚፈጸመው ትዕይንትን ልታቀርብ ወይም የልጅህን ቁንጅና ልታሳይበት አይደለምና፡፡ በመሆኑም ሰርግህን ልትፈጽም በምትዘጋጅበት ጊዜ ባለህ ነገር ብቻ ቤትህ ለማስዋብ ሞክር፡፡ በመቀጠል ጎረቤቶችህን ወዳጆችህንና የቅርብ ዘመዶችህን ጥራ፡፡ እንዲሁም ጥሩ ባሕርይ አላቸው የምትላቸውን ሰዎች በሰርጉ እንዲታደሙልህ ጋብዝ፡፡ ሙዚቀኞችን ግን ፈጽመህ አትጥራ ለእነርሱ የምታወጣው ወጪ በራሱ ከፍተኛና ሊሆን የማይገባ ነው፡፡

ከእነዚህ ሁሉ አስቀድሞ ግን ክርስቶስን በሰርግህ እንዲገኝ ጋብዘው፡፡ እርሱን እንዴት አድርገህ እንደምትጋብዘው ታውቃለህን ? “ንጉሡም መልሶ፡- እውነት እላችኋለሁ ከሁሉ ከሚያንሱት ከእነዚህ ወንድሞቼ ለአንዱ እንኳ ስላደረጋችሁት ለእኔ አደረጋችሁት ይላቸዋል”(ማቴ.፳፭፥፵) እንዲል ድሆችን በሰርግ እንዲገኙ በማድረግ ክርስቶስን በሰርግህ እንዲገኝ ማደረግ ይቻልሃል፡፡ ስለክርስቶስ ብለህ ድሆች በሰርግህ እንዲገኙ ስላደረግህ ሰርግህ የተበላሸ አድርገህ አትቁጠር፤ ነገር ግን ሴሰኞችን በሰርግህ ብትጋብዝ ሰርግህ በእርግጥ የረከሰ ይሆናል፡፡ ድሆችን ወደ ሰርግህ መጥራትህ ሀብት ወደ ቤትህ እንዲገባ መጥራትህ ነው፡፡ ቅምጥሎችን ከሰርጉ እንዲታደሙ የጠራህ እንደሆነ ግን ውርደትን እየጠራህ ነው፡፡

ሙሽሪትን በወርቅ ጌጣ ጌጦች አታስጊጣት ነገር ግን በጥሩ ሥነ ምግባርና በጭምትነት አስጊጣት እነዚያን ነገሮች ፈጽመህ አትፈልጋቸው፡፡ ግርግርና ሁካት በሰርግህ ፈጽሞ አይኑር፡፡ ሙሽራውን ጥራና ሚስቱን ይዞ ወደ ቤቱ ይግባ፡፡ በምሳና በራት ግብዣህ ላይ አስካሪ  መጠጦች አይገኙ፡፡ ነገር ግን ሰርግህ በደስታ የሞላበት ይሁን፡፡

እንዲህ አድርገህ ሰርግህን በመከወንህ ምን ያህል ተጠቃሚ እንደሆንክ ለማስተዋል እንድትችል በዘመኑ ሰርግ ተብለው ከሚቆጠሩት ጋር ያንተን የሰርግ ሥነ ሥርዐት አስተያይ፡፡ ሌላው ይቅርና ያንተን ሰርግ የተመለከተ ሰው ሁሉ የቁንጅና ውድድር ሳይሆን በእውነተኛ ትርጉም ሰርግን እንዳየ ምስክርነትን ይሰጥሃል፡፡ በዘመኑ ሰርግ ተብለው ከሚጠሩት ውስጥ ግን እጅግ የበዙ ክፋቶች ታጭቀው ይገኙበታል፡፡ በአዳራሽ የሚፈጸመው ሰርግ በጥንቃቄና እግዚአብሔርን በመፍራት ከሚደረገው ጋር ሲነጻጸሩ በቶሎ የሚጠናቀቁ ሰርጎች አይደሉም ፡፡ ከዚህም ባለፈ በውሰት የመጡት እቃዎች ሊጠፉም ስለሚችሉ ፍጻሜው ከደስታ ይልቅ ሊቋቋሙ ከማይችሉት ከባድ ሃዘን ውስጥ ሊጥል ይችላል ፡፡ ይህ የከበደ ሃዘን በአማች ላይ የሚታይ ነው ፡፡ ነገር ግን ሙሽሪትም ከዚህ ሃዘን ነጻ ልትሆን አትችልም ፡፡ በሰርጉም ፍጻሜም የቤቱ ውበቱ ጠፍቶ በሃዘን ታወሮ ይታያል ፡፡

በጥንቃቄና እግዚአብሔርን በመፍራት በሚከናወነው ሰርግና በአሕዛብ ልማድ በሚፈጸመው ሰርግ መካከል ሰፊ የሆነ ልዩነት አለ፡፡ በዚህ ክርስቶስ ሲገኝ በዚያ ግን ሰይጣን ነግሦ ይታይበታል ፡፡ በዚህ ፍጽም የሆነ ፍስሐ ሲታይ በዚያ ደግሞ ጥቅ ያጣ አለባበስ ይተዋወቅበታል ፡፡ በዚህ ፍጹም ደስታ ሲኖር በዚያ ግን ሕማምና ሰቆቃ ይተርፈዋል ፡፡ በዚያ የወጣው ወጪ ታላቅ ሲሆን በዚህ ግን እዚህ ግባ የማይባል ወጪ ብቻ ያስተናግዳል ፡፡ በዚያ ግርግርና ሁካታ ሲታይ በዚህ ግን ግብረ ገብነት ጎልቶ ይንጸባረቅበታል፡፡ በዚያ ኃጢአት ሠልጥና ስትታይ በዚህ ግን ኃጢአት ፈጽማ አትኖርም ፡፡ በዚያ ስካሮች ሲኖሩባት በዚህ ግን ሰላም ወዳዶች ይታዩባታል ፡፡ በዚያ ሁካታና ጠብ ሲኖር በዚህ ግን እርጋትና ሰላም ሰፍነው ይታዩበታል ፡፡

እነዚህን ሁሉ ልብ በሉ ፡፡ እግዚአብሔርን ደስ በማሰኘት እርሱን ለሚያፈቅሩት ካዘጋጀው ከመንግሥቱ ተካፋዮች እንድንሆን ከዚህ ቀን ጀምረን ይህን ክፉ ልማድ ከራሳችን አርቀነው እናስወግደው ፡፡ የሰውን ልጅ ከመውደዱ የተነሣ ሰው በሆነው በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ለእግዚአብሔር አብ ከእግዚአብሔር መንፈስ ቅዱስ ጋር ክብር ምስጋና ዛሬም ዘወትርም እስከዘለዓለሙ ይሁን አሜን !!

የቅዱስ ኤፍሬም ቅኔያዊ መዝሙራት

ጥቅምት 30/2004 ዓ.ም

ዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

መግቢያ

የሶርያዊው ቅዱስ ኤፍሬም አጭር የሕይወት ታሪክ

ቅዱስ ኤፍሬም 299 ዓ.ም ገደማ ንጽቢን በምትባለው ታላቅ ከተማ ተወለደ፡፡ ንጽቢን በጥንታዊቱ የሮም ግዛት በምሥራቅ የምትገኝ ከተማ ነበረች፡፡ አብዛኞቹ የታሪክ ጸሐፍት እንደሚስማሙበት ቅዱስ ኤፍሬም ከክርስቲያን ቤተሰብ የተገኘ ሲሆን በተወለደባት ከተማ በድቁና ሲያገለግል ረጅም የእድሜ ዘመኑን ያሳለፈ ቅዱስ ነው፡፡ አንዳንድ የታሪክ ጸሐፍት ግን የቅስና ማዕረግ አንዳለውም ይተርካሉ፡፡ ነገር ግን በአብዛኛዎቹ የሶርያ የታሪክ ጸሐፊያን ዘንድ ቅዱስ ኤፍሬም ዲያቆን እንደነበረ ተጽፎ እናገኛለን፡፡ ስለዚህም እስካሁን ድረስ በሶርያውያን ክርስቲያኖች ዘንድ የድቁና ማዕረግ በቅዱስ ኤፍሬም ምክንያት ትልቅ ቦታ የሚሰጠው ማዕረግ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡

ቅዱስ ኤፍሬም በንጽቢን ከተማ ሳለ በቤተ ክርስቲያን በሴቶች ዘማሪያን የሚቀርቡ ብዙ የመዝሙር ድርሰቶችን ደርሶአል፡፡ ቢሆንም በ363 ዓ.ም የሮም መንግሥት በመዳከሙ ምክንያት የፋርስ ንጉሥ ንጽቢን ለእርሱ ተላልፋ እንድትሰጥና በውስጡዋም የሚኖሩ ክርስቲያኖች ከከተማዋ ለቀው እንዲወጡ ባቀረበው የመደራደሪያ ነጥብ የተነሣ ንጽቢን ለፋርስ መንግሥት ተሰጠች፤ ክርስቲያኖችም ከከተማዋ ወጥተው ተሰደዱ፡፡ ቅዱስ ኤፍሬምና ደቀመዛሙርቱም ወደ ዑር ወይም ኤዲሳ ወደምትባለው ከተማ አመሩ፡፡ በዚያም የእድሜውን ዐሰርት ዓመታት አሳለፈ፡፡ ዑር የምትባለው ከተማ በአሁኑ ጊዜ ኡርፋ በመባል የምትታወቀው በደቡባዊ ቱርክ የምትገኝ ከተማ ናት፡፡ በዚህም ሳለ በከተማይቱ የተነሡትን ከሃዲያንን በመቃወም ታላላቅ ሥራዎችን ሠርቶ ነበር፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም በሚገርም ሁኔታ የግሪካውያንን ፍልስፍና ጠንቅቆ የሚያውቅ ስለመሆኑ ከጽሑፎቹ መረዳት ይቻላል፡፡ ነገር ግን ድርሰቶቹን ሲደርስ ሴማዊውን የአጻጻፍ ስልት ሳይለቅ ነበር፡፡ ቅዱስ ኤፍሬም በሕይወቱ ክርስቶስን መስሎ ሲያገልግል ሳለ በተወለደ በ67 ዓመቱ ገደማ (በኤዲሳ) ዑር ተቀስቅሶ በነበረው ወረርሽኝ የተጎዱትን ሕመምተኞችን ሲረዳ ቆይቶ በመልካም ሽምግልና ግንቦት 29 በ366 ዐረፈ፡፡ (ዘመን አቆጣጠሩ በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር ነው)

 

ቅዱስ ኤፍሬም  ከጻፋቸው የመዝሙር ድርሰቶች መካከል

1.ስለክርስቶስ ሥጋዌ 59 መዝሙራት
2.ጾምን አስመልከቶ 67 መዝሙራት
3.ንጽቢንን አስመልክቶ 77 መዝሙራት
4.ስለክርስቶስ ሙሽራ አይሁድን በመቃወም የጻፈው 66 መዝሙራት
5.ስለቤተ ክርስቲያን 52 መዝሙራት እንዲሁም ሌላ ስለ ቤተ ክርስቲያን የሚያወሳ 52 መዝሙራት
6.ስለእምነት 87 መዝሙራት
7.አሮኒየስ ለሚባለው ከሃዲ የሰጠው መልስና ስለ ገነት 56 እና 15 መዝሙራት
8.ንስሐ ስለሚገቡ ክርስቲያኖችና በሞት ለተለዩ የሚቀርቡ መዝሙራትን አዘጋጅቶአል፡፡

ከዚህ በተጨማሪ  ዘፍጥረትን፣ ዘጸአትን፣ ዐራቱ ወንጌላትን፣ የጳውሎስ መልእክታትን ተርጉሟል፡፡ የቅዱስ ኤፍሬም ጸሎቱና በረከቱ በእኛ ላይ ይደርብንና ከዚህ በማስከተል ከመዝሙር ድርሰቶቹ መካከል አንዳንዶቹን እንመለከታለን፡፡
ስለገነት የደረሰው መዝሙር

በዚህ መዝሙር ቅዱስ ኤፍሬም እስራኤላውያንን በምድረ በዳ ይከተላቸው የነበረውን ዓለት በመጥቀስ እግዚአብሔር ፍጥረታትን እንዴት እንደፈጠራቸውና ሌሎችም ስለገነት ያለውን አስተምህሮዎቹን እናገኝበታለን፡፡

1. እስራኤላውያንን በምድረ በዳ ይከተላቸው የነበረውን አለትን አስታውሼ፤

ዓለማትን የፈጠረውን የእግዚአብሔርን ቃል ልብ አልኩ፤
እንደ ታላቅ ወንዝ ለእነርሱ ከአለቱ ውስጥ የፈለቀው ውኃ፤
በውስጡ ካለው የውኃ ቋት የተገኘ አልነበረም፤
በአለቱ ውስጥ አንድም ጠብታ ውኃ የለም፤
ነገር ግን ልክ የእግዚአብሔር ቃል ፍጥረትን ከምንም እንዳስገኛቸው፤
አንዲሁ ታላቅ የውኃ ጅረት ከደረቅ ድንጋይ ውስጥ ፈለቀ፡፡

2.ሙሴ በመጽሐፉ ስለ ሥነ ተፈጥሮ ገልጦ ጽፎልናል፤

ስለዚህም ተፈጥሮና መጽሐፍ ቅዱስ ስለፈጣሪ ምስክሮች ሆኑ፤
የሰው ልጅ ተፈጥሮን ለራሱ ጥቅም ሲገለገልባት እንደሚያውቃት፤
እንዲሁ መጽሐፍ ቅዱስን በማንበብ በውስጡ የያዘውን መረዳት ይቻለናል፤
እነዚህን ሁለቱን ምስክሮች በሁሉ ስፍራ እናገኛቸዋለን፡፡
እግዚአብሔር የለም የሚሉትን ኢአማንያንን ለማሳፈር፣
እነዚህ ሁለቱ በሁሉም ጊዜና ሰዓት የሚገኙ የእግዚአብሔርን መኖር አዋጅ ነጋሪዎች ናቸው፡፡

3.ጌታ ሆይ የመጽሐፍህን መግቢያ ባነበብኩ ጊዜ ልቤ በሃሴት ተሞላ፤

የምንባቡ ቁጥሮችና ኃይለ ቃላት እኔን ለመቀበል እጆቻቸውን ዘረጉ፤
ይዘውኝም በፍቅር አቀፉኝ ሳሙኝም ወደ ወዳጃቸውን መርተው አደረሱኝ፡፡
የገነት ታሪኩዋ እኔን ወደ ላይ ወደ ሰማይ እንድነጠቅና ወደ ውስጥ እንድገባ አሸጋገረኝ፤
ከመጽሐፉ እቅፍ ወደ ገነት እቅፍ ተሸጋገርኩ፡፡

4.ዐይኔና ልቤ ቃሎቹ በሰፈሩበት መስመር ላይ ተጓዙ፤

በድልድይ እንደሚሸጋገር ሰው በገነት ታሪክ ወደ ላይ ተነጠቅሁ፡፡
ዐይኖቼ  ምንባቡን  ሲያነቡ አእምሮዬ ያርፍ ነበር፤  
አእምሮዬ በምሥጢር ሲነጠቅ ዐይኔ ደግሞ በተራው ከማንበብ ያርፋል፤
ከንባብ በኋላ ዐይኖቼ ሲያርፉ አእምሮዬ ምሥጢራትን በመመርመር ተጠመደ፡፡

5.ወደ ገነት መሸጋገሪያ ድልድዩንና መግቢያ በሩን በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ አገኘሁት፤

ስለዚህም በድልድዩ ተሸጋግሬ በበሩ በኩል ወደ ውስጥ ዘልቄ ገባሁ፤  
በእርግጥ ዐይኖቼ በውጭ ነበሩ አእምሮዬ ግን ወደ ውስጥ ዘልቆ ገብቶአል፤
በቃላት ሊገለጡ በማይችሉት መካከል ቆሜ መደነቅ ሞላብኝ፤
ስፍራው ታላቅ፣ ፀጥታ የሰፈነበት፣ ፍጹም ንጹሕና በክብር ከፍ ከፍ ያለ ግሩም ነበር፡፡
በረከቶች ሁሉ የሚገኝበትን ይህን ስፍራ መጽሐፍ ቅዱስ ኤደን ብሎ ሰየመው፡፡

 

6.    በዚያም ለቅዱሳን የሆነ አጸድና የተንጣለለ ለምለም መስክ አየሁ፤

በላዩም መዓዛው እጅግ ማራኪ የሆነ ሽቱ ተርከፍክፎበታል፤
አጸዱም በፍራፍሬዎች የተጌጠ፣ የፈኩ አበቦቹም አክሊሎች የሆኑለት ነው፤
መስኩ ርስት ሆኖ ለእያንዳንዱ እንደ ሥራው መጠን የሚሰጥ ሲሆን፤  
በጽድቅ ሕይወት ላልተጋው ውበቱ ማራኪ ያልሆነ ያልተጌጠ መስክ ይሰጠዋል፤  
ለተጋው ግን ውበቱ ዐይንን አፍዝዞ የሚያስቀር እጅግ ማራኪ የሆነ መስክ ያገኛል፡፡

7.    በአጸድ ውስጥም ሳለሁ ገነት ለቅዱሳን ማረፊያነት ትበቃቸዋለችን? ብዬ ጠየቅሁ፤

መሠረቴን መጽሐፍ ቅዱስ አድርጌ በመጽሐፍ ውስጥ ያልሰፈሩትን ለመመርመር ሞከርኹ፡፡
ሌጌዎን የተባለው የአጋንንት ሠራዊት በአንድ ሰው ሰውነት ውስጥ ሰፍሮ እንደነበር አስተዋልሁ፤(ማር.5፡9-10)
በቁጥራቸው እጅግ የበዙ ቢሆንም ከርቀታቸው(ከጥቃቅንነታቸው) የተነሣ እንደ አንዲት ነፍስ እንኳ ጎልተው መታየት አልተቻላቸውም፡፡

8.     በአንድ አካል ውስጥ የአጋንንት ሠራዊት ከትሞ እንዳለ ነገር ግን እጅግ ረቂቃን እንደሆኑ፤

እንዲሁ በትንሣኤ የተነሡ ቅዱሳን በገነት ውስጥ መቶ ሺኽ እጥፍ ረቀው ይኖሩባታል፡፡   
ገነት በአእምሮ ፣ ቅዱሳንም በአእምሮ የማሰብ አቅም ይመሰላሉ ፤
አንድ ሰው እንደ ፈቃዱ በአሳቡ እጅግ ሊራቀቅና ሊመጥቅ ይችላል፤
ቢፈልግ አመለካከለቱን በአንድ ነገር ላይ ብቻ ሊወስነው ይችላል፡፡
አንድ ሰው አመለካከቱን በቦታ ሊወሰን ወይም በቦታ ላይወስነው ይችላል፤

9.     መብራት ሲበራ እጅግ የብዙ ብዙ ሺኽ ጨረሮች በአንድ ቤት እንዲኖሩ ፤


ከብዛታቸው የተነሣ ቤቱ እንደማይጠባቸው፣  ከአንድ ከፈካ አበባ የሚወጣው መዓዛ አካባቢውን እንዲያውደው ነገር ግን በቦታ እንዲወሰን እንዲሁ በገነትም የሚኖሩ፤ ቅዱሳንም እንደ ብርሃኑ ጨረሮችና እንደ አበባው መዓዛ ናቸው ፡፡

ምንም እንኳ የብርሃኑ ጨረሮችና የአበባው መዓዛ በጠባብ ቦታ ላይ የተወሰኑ ቢሆንም፣
የስፍራው ውሱንነት ግን እንደልባቸው እንዲዋኙ እንዳይከለክላቸው ፤ ገነትም እንዲሁ ለቅዱሳን ናት ፡፡
ስለዚህም ገነት በውስጡዋ በመንፈሳዊ ፍጥረታት የተሞላች ብትሆንም፤
ወደ እርሱ የፈለሱትን ለማኖር ከበቂ በላይ የሆነ ሥፍራ አላት፡፡

10.     በቁጥር እጅግ የበዙ አሳቦች በመጠን ካነሱት የሰውነት ክፍሎቻችን አንዷ በሆነችው በልባችን ውስጥ ይኖራሉ ፤

የአካሉዋ ማነስ አንዱ በአንዱ እንዲወሰን ወይም አሳቦቻችንን እንደልባቸው እንዳንሸራሽር አይከለክለንም፤
ይህ እንዲህ ከሆነ እንዴት ገነት በመጠናቸው እጅግ ረቂቃን ለሆኑት ቅዱሳን ሰውነት የበቃች አትሆን !!
የቅዱሳንን ነፍሳት ርቀትን(ረቂቅነትን)ፈጽሞ በአእምሮአችን ተመራምረን የምንደርስበት አይደለም ፡፡

11.    በገነት መካከል ሆኜ እንደ ችሎታዬ መጠን ምስጋናዬን ለአምላኬ ላቀርብ ሞከርኩ፤

ድንገትም በገነት ውስጥ እንደ ነጎድጓድ የመሰለ ጥሙም የምስጋና ድምፅ ተሠማ ፤
ድምፁም ልክ በአንድ የጦር ሰፈር እንደሚነፋ መለከት ድምፅ ዓይነት ነበር፤
ቅዱስ ቅዱስ ቅዱስ የሚል የምስጋና ዝማሬ ሦስት ጊዜ ተደጋግሞ ተሰማ፤
ይህን ስሰማ አምላክ ከቅዱሳኑ ምስጋናን ለእርሱ እየቀረበለት መሆኑን ተረዳሁ ፡፡
እስከዛ ጊዜ ድረስ ግን ገነት ባዶ መስላኝ ነበር፤
ነገር ግን እንደ ነጎድጓድ የሆነውን ይህን ድምፅ ስሰማ ቅዱሳን በዚያ ከትመው እንዳሉ ተማርኹ፡፡

12.    ስለዚህም ገነት በጸጥታዋና በውበቱዋ እጅግ ማረከችኝ ደስም አሰኘችኝ፤

በውስጡዋ ያለው  አጸድ ውበት አንዳች እንከን የለበትም፤  
በውስጡዋ ከሰፈነው ጸጥታ የተነሣ አንዳች ፍርሃት የለም፡፡
ገነትን ለመውረስ የተገባው ቅዱስ እንዴት ብፁዕ ሰው ነው፤
ይህችን ስፍራ እንደ ቅድስናችን መጠን ሳይሆን እንደ እርሱ ጸጋ፤
እንደ እኛ ድካም ሳይሆን እንደ እርሱ ቸርነት የምንወርሳት ናት፡፡

13.     የገነትን ድንበሮችን አልፌ ወደ ውስጡዋ ስገባ በውበቱዋ እጅግ ተደመምኩ፤

በዙሪያው ያሉትን ወዳጆቼን ወደኋላ ትቼ በደኅንነት ወደሚኖሩባት ገነት ዘለቅሁ፤
ነገር ግን ከእርሱዋ ተመልሼ የሾኽና የአሜካላ እናት ወደሆነችው ምድር ስመለስ፤
ልዩ ልየ ዓይነት ሕማማትንና  ስቃዮችን ተቀበልኩ፤
ስለዚህም ገነትን ከምድር ጋር ሳነጻጽራት ልክ እንደወ¬ህኒ ቤት ሆና አገኘኋት፤
ነገር ግን በውስጡዋ ያሉ እስረኞች እርሱዋን ትተው ሲለዩዋት ያነባሉ፡፡ (ይህ ደግሞ የሚደንቅ ነው)

14.    ሕፃናት ከእናታቸው ማኅፀን ሲወጡ ማልቀሳቸው ይገርመኝ ነበር ፤

እኚህ ሕፃናት የሚያነቡት ከጨለማ ወደ ብርሃን በመውጣታቸው ነበር ፤
ከተጨናነቀው ሥፍራ ወደ ሰፊይቱ ዓለም በመምጣቸው ነበር የሚያለቅሱት፡፡
ልክ ከእናታችን ማኅፀን ስንወጣ እንደሚሆነው በሞት ከዚህ ዓለም ስንለይም እንዲሁ እናነባለን፤
ነገር ግን ሰዎች የሚያነቡት የስቃይ እናት ከሆነችው ከዚህች ዓለም ተወልደው እጅግ ግሩም ወደ ሆነችው ገነት ሲገቡ መሆኑ ይደንቃል፡፡

15.    የገነት ጌታዋ የሆንኽ ቸሩ ፈጣሪዬ ሆይ ለእኔ ራራኝ፤

ወደ ገነት ለመግባት ምናልባት እንኳ የበቃሁ ባልሆን፤
ከአንተ ጋር ያሉ ቅዱሳን ከገነት ፍሬዎች ተመግበው ሲጠግቡ፤   
በአንተ ቸርነት ከፍርፋሬአቸው ተመግበን ሕያዋን እንድንሆን፤
በገነት  ባለው አጸድ ዙሪያ እንድንሰፍር ፍቀድልን፡፡

ይቀጥላል ….

«ወአድኀነ ሕዝቦ በመስቀሉ»

ክፍል ሁለት

 

3. ክብረ መስቀል

እኛ ኦርቶዶክሳውያን የመስቀልን መንፈሳዊ ትርጉም ከመረዳትና በልባችን ከመያዝ በተጨማሪ ለመስቀል ያለንን ክብር እና ፍቅር ለመግለፅ የምናደርጋቸው በርካታ ነገሮች አሉ፤ ከእነዚህ መካከል ጥቂቶቹን እንጠቁማለን፡-

3.1 መስቀልን በቤተ ክርስቲያን፣ በንዋያተ ቅዱሳት፣ በሰውነት ላይ ማድረግ

ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ የመስቀልን በዓል አስመልክተው ባስተማሩት ትምህርት ላይ እንዲህ ይላሉ፤

«መስቀል ባሉት መንፈሳዊና ትምህርተ ሃይማኖታዊ ትርጉሞች ምክንያት ክርስቲያኖች ሁሉ የሙጥኝ ብለን እንይዘዋለን፡፡ በአብያተ ክርስቲያናት ላይ እናደርገዋለን፤ በተለያየ መስክ እንቀርፀዋለን፤ በደረታችን ላይ እናንጠለጥለዋለን፣ በምልክቱ እናማትባለን፤ ፀሎታችንን እንጀምርበታለን፤ ካህናትም በእጃቸው ይይዙታል፣ ሰዎችንም ይባርኩበታል፣ የሐዲስ ኪዳን በረከቶች ሁሉ ምንጭ መስቀል እንዲሆን በማመን መስቀል በሁሉም ምስጢራተ ቤተ ክርስቲያን አፈጻጸም ላይ እንጠቀምበታለን፤ በካህናቱ ልብሶች ላይ እናደርገዋለን ይኸውም ለጌጥ ሳይሆን ስለ ኃይሉ እና ስለ ቡራኬው ነው፡፡»

3.2. መስቀልን በመሳለም መባረክ

በጥንት ጊዜ መስቀል የመርገም ምልክት ነበር፡፡ ነገር ግን ጌታችን በመስቀል ላይ መርገማችንን ሁሉ ተሸክሞ ከእግዚአብሔር ጋር የመታረቅንና የአዲስ ሕይወትን በረከት ሰጥቶናል፡፡ ስለዚህም የሐዲስ ኪዳን ታላላቅ ነገሮች ሁሉ የተገኙት ከመስቀል ነው፡፡

ስለዚህ ካህናት ቡራኬን ለመስጠት መስቀልን ይጠቀማሉ፤ ይህም በረከቱ የሚመጣው /የሚመነጨው/ ከራሳቸው ሳይሆን በረከትን እንዲሰጡበት የሰጣቸው ጌታችን ከተሰቀለበት መስቀል መሆኑን እና በሐዲስ ኪዳን ያሉ በረከቶች ሁሉ ምንጭ መስቀል መሆኑን ላይ ለማመልከት ነው፡፡

እግዚአብሔር የማይታዩ ፀጋዎችን ለሰዎች የሚሰጠው በሚታዩ አገልግሎቶች ነው፡፡ ይኸውም ነገሮችን ለሰው ልጅ ህሊና በሚረዳ መልኩ ለማድረግ ነው፡፡ ለምሳሌ ከተወለደ ጀምሮ ዓይን ያልነበረውን ዓይን የፈጠረለት በሚታይ መልኩ በምድር አፈርና በምራቁ ጭቃ ሰርቶ ነው፡፡ ጥምቀትንም በውሃ ውስጥ በመነከር አድርጎታል፡፡ በዚሁ መሰረት በመስቀልን በመባረክ የማይታዩ በረከቶች እና ፀጋዎችን እናገኛለን፡፡ እነዚህ በረከቶችም ደስታ፣ የመስቀሉ ፍቅር፣ ጥብአት /ድፍረት/ እና የመሳሰሉት ናቸው፡፡

3.3. ማማተብ

አተበ ማለተ አመለከተ ማለት ነው፡፡ ማማተብ ማለት ደግሞ ማመልከት ማለት ነው፡፡ ማማተብ ማለት ከአውራ ጣት ቀጥሎ ባለው ጣትና በቀሪዎቹ ሦስት ጣቶች የመስቀል ምልክት ሰርቶ እጅን ከግንባር ጀምሮ ከላይ ወደ ታች ከዚያም ከግራ ወደ ቀኝ «በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ» እያሉ ስመ ሥላሴን እየጠሩ ሰውነትን ማመልከት ማለት ነው፡፡

እጃችንን ከላይ ወደታች ማውረዳችን እግዚአብሔር ወልድ ከሰማየ ሰማያት ወረዶ ከድንግል ማርያም ተወልዶ ሰው መሆኑን እንዲያሳስበን ነው፡፡

ከግራ ወደ ቀኝ ማድረጋችን በመከራውና በሞቱ ከግራ /ከሞት/ ወደ ቀኝ / ወደ ሕይወት / እንዳሸጋገረን እንዲያሳስበን ነው፡፡ የመስቀል ቅርጹ ደግሞ መከራ መስቀሉን ያሳስበናል፡፡

ስናማትብ ራሳችንን እንባርካን፣ አጋንንት እኩያት መናፍስት ይርቁልናል፣ መከራ መስቀሉንም እናስባለን፤ መስቀሉን እንሸከማለን፡፡ ስለዚህ ጠዋት ስንነሳ፣ በፀሎታችን ወቅት፣ ክፉ ሀሳብ ሲመጣብን፣ የማያስፈራ ነገር ሲገጥመን፣ ደስ ሲለን፣…. እናማትባን፡፡

3.4. ለመስቀል መስገድና መገዛት

እኛ ኦርቶዶክሳውያን በመስቀል ፊት እንሰግዳለን፡፡ በመስቀል ፊት የምንሰግደው ስግደት ከሁለቱ የመስቀል ትርጉሞች አንጻር ሁለት ዓይነት መልኮች አሉት

ሀ. መስቀል የክርስቶስ መከራ ስቅለት እና ሞት የሚወክል አርማ እንደመሆኑ መጠን በመስቀለ ፊት ስንሰግድ ጌታችንን እያሰብን ለአምላክ ብቻ የሚገባውን የአምልኮ ስግደት ለአምላካችን እንሰግዳለን፤ ይህም ልክ በጌታችን ስዕለ አድኅኖ ፊት እንደመስገድ ያለ ነው፡፡

ለ. መስቀል የተከበረ ንዋይ ስለሆነ ለመስቀሉ ያለንን ፍቅር እና አክብሮት ለመግለጽ የፀጋ የአክብሮት ስግደት እንሰግድለታን፡፡ እንገዛለታን /እናከብረዋለን/ ቅዱስ ያሬድ ይህንን ሁለተኛውን ስግደት አስመልክቶ እንዲህ ይላል፡፡ «ሀለው እለ ይቤሉ ለዕፅኑ ታመልኩ፣ ለለዕፅኑ ትገብሩ በዓለ፣ አቀደሶኑ በደሙ ክቡር ለዕፀ መስቀሉ፣ ወእንተዝ ንሕነ ናመልኮ» «የምታመልኩት ዕፅን/ የምትገዙት ለዕፅ/ ነውን? በዓልስ የምታደርጉት ለዕንጨት ነውን? የሚሉ አሉ፡፡ በክቡር ደሙ መስቀሉን ቀድሶት የለምን? ስለዚህ እኛ እናመልከዋለን /እንገዛለታለን/»

መለከ ማለት ገዛ ማለት ነው፡፡ ናመልከ ማለት እንገዛለታለን፤ እናከብረዋለን፣ ከፊቱ ራሳችንን ዝቅ እናደርጋለን ማለት ነው፡፡ ክቡር መስቀል ክርስቶስ ማዳኑን የፈፀበት፣ በደሙ ያከበረው ንዋይ ቅዱስ ስለሆነ የፀጋ ስግደት እንሰግድለታለን፡፡ እንገዛለታለንም፡፡

ከዚህም በተጨሪ በመስቀል ስም ታቦታትን በመቅረጽና አብያተ ክርስቲያናትን በማነጽ፣ የመስቀልን በዓላት በማክበር፣ ስመ ክርስትናን ወልደ መስቀል፣ ወለተ መስቀል፣ ገብረ መስቀል እያልን በመሰየም ለመስቀሉ ያለንን ክብር እና ፍቅር እንገልጣለን፡፡

እነዚህን ነገሮች ከማድረግም በተጨማሪ መስቀልን እንዲህ እያልን በቅዱስ ያሬድ ድርሰቶች እናመሰግነዋለን፡-

– «መስቀል ኃይልነ ወፀወንነ መድኃኒተ ነፍስነ ፍጽምን ወከዋላን ምጽንአተ ቅጽርነ መስቀል ቤዛነ ኃይልነ ወፀወንነ ዮም ፍስሓ ለነ» «መስቀል ኃይላችን፣ መመኪያችን፣ የነፍሳችን መድኃኒት ነው፡፡ የአጥራችን መጽኛ፣ ቤዛችን ነው፡፡ ዛሬ ለእኛ ደስታ ሆነ»

– «ወሀለወት አሐቲ ሀገር ብርሐት ከመ ፀሐይ ሕንፄነ ወሱራሬሃ አዳም የዓውደ ሐጹር በትእምርተ መስቀል» «አንዲት እንደ ፀሐይ የምታበራና ህንጻዋና አስራሯ ያማረ ሀገር አለች /ቤተ ክርስቲያንን ነው/፡፡ በመስቀል ምልክት የሆነ አጥር ይከባታል»

– «መስቀልከ ተስፋ ቅቡጻን መስቀልከ ልብስ ለዕሩቃን አንቅዕት ለፅሙዓን መርሶ መድኃኒቶሙ ለአሕዛብ» «መስቀልህ ተስፋ ለቆረጡ ተስፋ፣ ለተራቆቱ ልብስ፣ ለተጠሙ ምንጭ፣ ለአህዛብ ደግሞ የመድኃኒታቸው ወደብ /መጠጊያ/ ነው»

– «መስቀል ዘኀኑ ለባሕር፣ መርሶሙ ለአሕማር መስቀል ብርሃን ወሃቤ ሰላም ብርሃነ ዓለም» «መስቀል የባሕር ፀጥታ፣ የመርከቦች ወደብ፣ የዓለም ብርሃን እና ሰላምን ሰጪ ነው፡፡»  

4. የመስቀሉ ኃይል

ቅዱስ ጳውሎስ ለቆሮንቶሳውያን በላከው የመጀመሪያ መልዕክቱ እንዲህ ይላል፡- «የመስቀሉ ቃል ለሚጠፉት ሞኝነት ነው፤ ለእኛ ለምንድነው ግን የእግዚአብሔር ኀይል ነው፡፡» /1ኛ ቆሮ.1-18/

መስቀል ከሁለቱ ትርጉሞቹ /መልዕክቶቹ/ አንጻር ኃይልነቱም በሁለት መልኩ ሊታይ ይችላል፤

ሀ/ መስቀል ኀጢአታችንንና በኀጢአታችን ምክንያት የደረሰብንን ሞት፣ የጌታችንን ሕማማት፣ መስቀል እና ሞት፣ ትንሳኤውንና ዳግም ምፅአቱንና እኛም ከሞት ተነስተን ለፍርድ የምንቆም መሆናችንንና ሌሎች ተያያዥ ነገሮችን የሚወክልና የሚያስታውሰን ምልክት ነው፡፡

እነዚህን ነገሮች ማሰባችንና ማስታወሳችን ሁል ጊዜ በመንፈሳዊ ሃሳብ ውስጥ እንድንሆንና ዓለምንና የዓለም የሆነውን በሚያስንቅ የክርስቶስ ፍቅር፣ እንድንሞላ ስለሚያደርገን መስቀል ኃይላችን ነው፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ስለ ሚደርስብን ፈተና እና ስለ እግዚአብሔር ብለን ስለምንተወው ነገር ሁሉ የምንቀበለውን አክሊልም እያስታወሰ ብርታት ስለሚሆነን መስቀል ኀይላችን ነው፡፡

ለ/ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ ይህንን ሁለተኛውን የመስቀል ኀይልነት ሰያብራሩ እንዲህ ይላሉ፣ «የመስቀል ምልክት ሰይጣናት ሁሉ የሚፈሩት ኀይል እንደሆነ እናያለን፤ ሰይጣን የሰው ልጆችን ለማጥፋት ያደረገው ጥረትና የደከመው ድካም የከሸፈው በመስቀል ላይ በተደረገው ነጻ ማውጣት ነው፡፡ ስለዚህ ሰይጣን የመስቀልን ምልክት ይፈራል፤ ስለዚህ በእምነት ከተደረገ በመስቀልና በመስቀል ምልክት እጋንንትን ማራቅ፣ ማውጣትና ማሳደድ ይቻላል፡፡ እኛም የእግዚአብሔር ልጆች የድል ምልክት አድርገን እንይዘዋለን፤ አጋንንትን ድል ለማድረግ እንጠቀምበታለን፡፡

ስለዚህ በዘወትር ጸሎታችን «መስቀል ኃይላችን ነው» እንላለን፤ ስለ መስቀሉና ስለ አምላካችን ውለታና ስለ ዘለዓለማዊ ህይወታችን በማሰብ ክፉ ሃሳብና ፍትወታትን ድል እናደርግበታለን፤ በመስቀል ምልክት በማማተብና በዕፀ መስቀል በመባረክ /ባ ይጠብቀል/ እና በመባረክ /ለካህናት/ አጋንንትን እናርቃለን፤ ከሰዎችም እናስወጣለን፡፡

5. ጌታችን የተሰቀለበት ዕፅ መስቀል መገኘት

ጌታችንና መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የተሰቀለበት መስቀል ተአምራትን ማድረግ ሙታንን ማስነሣት፣ በሽተኞችን መፈወስ፣ አጋንንትን ማውጣት ስለጀመረ በቅንአታቸውና ባለማወቃቸው ጌታን የሰቀሉት አይሁድ መስቀሉ በኢየሩሳሌም አካባቢ ባለው የቀራንዮ ተራራ ላይ ቀብረው ቦታውን የቆሻሻ መጣያ አደረጉት፡፡ ሁሉም የኢየሩሳሌም ነዋሪዎች ቆሻሻቸውን በዚያ መጣል ጀመሩ፡፡ በጊዜ ብዛትም የቆሻሻው ክምር አድጎ ትልቅ ኮረብታ አከለ፡፡

ክርስቲያኖች መስቀሉ ያለበትን ቦታ ቢያውቁም ሊያወጡት ግን አልቻሉም ነበር፡፡ ነገር ግን በ70 ዓ.ም የሮማው የጦር ጀነራል /በኋላ ንጉሠ ነገሥት/ ቬስፓስያንና ልጁ ጥጦስ ኢየሩሳሌምን ሊያጠፋ ጥቂት ጊዜ ሲቀራቸው ክርስቲያኖች ከተማውን ለቀው ስለወጡና የነበሩት አይሁድ ስለተገደሉ፣ የቀሩትም ስለሸሹና ከተማዋ ባዶ ስለሆነችና ከዚያ በኋላ የነበረውም ዘመን ለክርስቲያኖች የሰማእትነት፣ የስደትና የመከራ ዘመን ስለነበር መስቀሉን ማውጣት አልተቻለም ነበር፡፡ መስቀሉ የተቀበረበት ቦታ ሳይቀር ተረሳ /ጠፋ/፡፡

ከ300 ዓመታት ያህል በኋላ እግዚአብሔር ንጉሥ ቆስጠንጢኖስን አስነሣ፡፡ ቆስጠንጢኖስ መክስምያኖስ ከሚባል ጠላቱ ጋር አስጨናቂ የሆነ ጦርነት ላይ በነበረበት ወቅት በሰማይ ላይ ብርሃናዊ የመስቀል ምልክት ታየው፤ «ከዚያም በዚህ ምልክት ጠላትህን ታሸንፋለህ፡፡» የሚል ድምፅ ከሰማይ ሰማ፡፡ /ይህ የሆነው ቆስጠንጢኖስ ለብቻው ሁኖ በተመስጦ እያሰበ ሳለ ነው፡፡/ ወዲያውም የክርስትናን እምነት ተቀበለ፡፡ /የተጠመቀው ግን ሊሞት ጥቂት ሲቀረው ነው፡፡ መስቀልን የመንግሥቱና የሠራዊቱ አርማ አደረገ፡፡ በሠራዊቱ ልብሶች፣ የጦር ዕቃዎች፣ ፈረሶች ሁሉ ላይ የመስቀልን ምልክት አድርጎ ጠላቱን በመዋጋት ድል አደረገ፤ ለክርስቲያኖች ነጻነትን ሰጠ የዘመነ ሰማዕታት ፍጻሜ ሆነ፤ ክርስቲያናዊ መንግሥት መሠረተ፡፡

የቆስጠንጢኖስ እናት ቅድስት እሌኒ ትባላለች፡፡ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ሺኖዳ ስለ ቅድስት እሌኒ ሲናገሩ እንዲህ ብለዋል፡- «ልጇ ንጉሠ ነገሥት ቆስጠንጢኖስ ንግሥት በማድረግ አከበራት፤ በቤተ መንግሥቱ ንዋይም ሁሉ ላይ ሥልጣን ሰጣት፤ እርሷም ይህንን ገንዘብ በደግነት በርካታ አብያተ ክርስቲያናትን ሠራችበት፤ ድሆችንና የተቸገሩትንም ረዳችበት፡፡ ከቦታ ቦታ ስትዘዋወርም ሰዎችን ትረዳና ከባርነት ነጻ ታወጣ ነበር፡፡

«በጣም ሃይማኖተኛም ነበረች፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያን የምትሔደው ንግሥት ብትሆንም እንኳን ቀላል እና ተራ ልብሶችን ለብሳ ነበር፡፡ ጸሎቷን ያለ ማስታጐል /ያለማቋረጥ/ ትጸልይ ነበር፡፡ ከመንፈሳዊ መርሐ ግብሮችንም አትቀርም ነበር፡፡ እንደ ንግሥት ከኖረችው በላይ እንደ አማኝ ኖራለች፡፡ ቅዱሳት መካናትን ትጎበኝና በእርጅናዋ ወራት የረጅም ጉዞን ድካም ትቀበል ነበር፡፡ ከዚህም በኋላ እግዚአብሔር ወደ ኢየሩሳሌም ሔዳ መስቀሉን እንድታወጣ በራእይ ነገራት፡፡ እሌኒም የታዘዘችውን ለመፈጸም ወደ ኢየሩሳሌም ብትሔድም መስቀሉን ግን ማግኘት አልቻለችም፡፡ በኢየሩሳሌም የሆነውን ነገር ቅዱስ ያሬድ በድጓው ጽፎታል፤

«ሖረት ዕሌኒ በሰላም ከመ ትኀስስ ዕፅ መስቀል ወረከበት መሐይምናነ እምዘመደ ዕብራውያን ወትቤሎሙ በአይቴ ሰቀሉ ወልደ ዋህደ ወይቤልዋ በቀራንዮ በበህየ ሰቀልዎ፤ ዕሌኒ መስቀሉን ትፈልግ ዘንድ በሰላም ሔደች፤ ከዕብራውያን ወገኖች መካከል ምዕመናንን አገኘችና ጌታን የሰቀሉት የት ነው ብላ ጠየቀቻቸው፤ እነርሱም በቀራንዮ ነው የሰቀሉት አሏት፡፡» ከጠየቀቻቸው ሰዎች መካከልም ኪራኮስ አሚኖስ የሚባሉ ሰዎች እንዳሉበት ቅዱስ ያሬድ እንዲህ እያለ ይነግረናል፡፡

«ትቤሎ ዕሌኒ ለኪራኮስ ምዕመን ንግረኒ አፍጥን ኀበ ሀሎ መስቀሎ ለኢየሱስ ክርስቶስ፤ ዕሌኒ ኪራኮስን የኢየሱስ ክርስቶስ መስቀል የት እንዳለ ቶሎ ብለህ ንገረኝ አለችው፡፡»

ትቤሎሙ ዕሌኒ ለኪራኮስ ወለ አሚኖሰ ንግሩኒ ኀበ ሰቀሉ ወልደ ዋህደ፤ ዕሌኒ ኪራከስንና አሚኖስን አይሁድ ጌታን የት እንደሰቀሉት ንገሩኝ አለቻቸው፡፡»

ኪራኮስም እንዲህ አላት፡- እኔ ዘመኑ ሩቅ ስለሆነ አላውቀውም፤ አባቴ ግን የቦታው ስም ቀራንዮ መሆኑን ነግሮኛል፡፡»

ይሁን እንጂ በቀራንዮ ተራራ ላይ ቁፋሮ ቢጀመርም መስቀሉ ሊገኝ አልቻለም፡፡ በኋላ አባ መቃርስ የተባለው የኢየሩሳሌም ኤጲስ ቆጶስ አይሁድ መስቀሉን አስቀብረው ቦታውን የቆሻሻ መጣያ እንዳደረጉትና ቦታውም በተራራው ላይ ባሉት ኮረብታ መሰል ክምሮች አንዱ እንደሆነ ነገራት፡፡ ይሁን እንጂ በቀራንዮ ተራራ ላይ በርካታ ትናንሽ ኮረብታዎች ክምሮችን በመኖራቸው መስቀሉ ያለበት ሊታወቅ አልቻለም፡፡

ከዚህ በኋላ «ወትቤ ዕሌኒ አንሰ ኢይለብስ አልበሰ መንግሥትየ ለእመ ኢተረክበ ዕፅ መስቀል ወፀርሐት ኀበ እግዚአብሔር በዐቢይ ቃል፤ ዕሌኒም ዕፅ መስቀሉ ካልተገኘ የመንግሥቴን ልብስ አልለብስም አለች፤ በታላቅ ቃልም ወደ እግዚአብሔር ጮኸች» እንዳለው ዕሌኒ ሱባኤ ገብታ ጸሎት ማድረግ ጀመረች፡፡ በሱባኤዋም ወቅት መልአክ ተገልጦ ደመራ አስደምራ ዕጣን ብትጨምርበት ጢሱ መስቀሉ ያለበትን እንደሚያመለክታት ነገራት፡፡

በዚህም መሠረት መስከረም 16 ቀን ታላቅ ደመራ አስደምራ እሳት አስለኩሳ በጣም ብዙ ዕጣን ጨመረችበት የዕጣኑ ጢስም ወደ ሰማይ ወጥቶ ተመልሶ መስቀሉ ወዳለበት ኮረብታ ተመለሰና መስቀሉ ያለበትን አመለከተ፡፡ ቅዱስ ያሬድ ይህንን አስደናቂ ክስተት «ዘዕጣን አንዳረ ሰገደ ጢስ»፣ «ዕጣኑ መስቀሉ ያለበትን አመለከተ፣ ጡሱም ለመስቀል ሰገደ» በማለት ገልጾታል፡፡

ወዲያውም ቁፋሮ ተጀመረ፡፡ ከስድስት ወራት በኋላም በመጋቢት 1ዐ ቀን ስንክሳር እንደተገለጠው ሦስት መስቀሎች /የጌታችንና አብረውት የተሰቀሉት ሁለት ወንበዴዎች/ ተገኙ፡፡ የጌታችን መስቀል ሙት በማስነሣቱና ድውያንን በመፈወሱ ተለይቶ ታውቋል፡፡ ከመስቀሉ ጋርም አክሊለ ሶኩና ጌታችን የተቸነከረባቸው ችንካሮች እንደተገኙ መጽሐፈ ስንክሳርና መጽሐፈ ድጓ ይናገራሉ፡፡

ዕሌኒም በጣም ተደሰተችና በቀራንዮ ተራራ ላይ በመስቀል ስም ቤተ ክርስቲያን አሠራች፡፡ ቤተ ክርስቲያኑም መስከረም 16 ቀን ቅዳሴ ቤቱ ተከብሮ መስከረም 17 ቀን ተቀደሰበት፡፡ የጌታችን መስቀልም በወርቅ ሳጥን ውስጥ በዚያው ቤተ ክርስቲያን ውስጥ ተቀመጠ፡፡ ቤተ ክርስቲያንም በዚህ ምክንያት የመስቀሉን በዓል ቅዳሴ ቤቱ በተከበረበት መስከረም 16 ቀን ዳመራ ደምራ ታከብራለች፡፡ መጋቢት 1ዐ ቀንም መስቀሉ የተገኘበትን ዕለት ታስባለች፡፡

የመስቀሉ በረከት ይደርብን፤ አሜን፡፡

«ወአድኀነ ሕዝቦ በመስቀሉ»

መስከረም 2002 ዓ.ም.

ክፍል አንድ

«ሕዝቡን በመስቀሉ አዳነ»
ዲ/ን ዘላለም ቻላቸው

በቤተክርስቲያናችን መስከረም 17 ቀን የመስቀል በዓል ይከበራል፡፡ እኛም በዚህ ትምህርት የመስቀሉን ነገር እና የበዓሉን ታሪክና አከባበር እንመለከታለን፡፡ ከዚያ በፊት ግን የነገረ መስቀሉ መነሻው ነገረ ድኅነት ነውና ጥቂት ነገሮችን ስለዚያ እንበል፡፡

1.ነገረ ድኅነት

ነገረ ድኅነት አምላካችን እግዚአብሔር ከሰማየ ሰማያት ወርዶ ሰው ሆኖ ተወልዶ እንዳዳነን የምንማርበት የትምህርት ክፍል ነው፡፡ ይህ ትምህርት በውስጡ አራት ዋና ዋና ነገሮች አካቷል፡፡በአጭር በአጭሩ እንመልከታቸው፤

1. እግዚአብሔር በቸርነቱ አዳምንና ሔዋንን ከፍጥረቱ ሁሉ አልቆ በራሱ አርአያና አምሳል ፈጥሮ ገነትን ያህል ቦታ አዘጋጅቶ በተድላ በደስታ እንዲኖሩ ሌሎችንም ፍጥረታት ሁሉ እንዲገዙ ሥልጣንንም ጭምር ሰጣቸው፡፡ /ዘፍ.1.25/፡፡ አዳምና ሔዋንም በገነት በነበሩባቸው ዓመታት ከእግዚአብሔር ጋር እየተነጋገሩ በፍጥረታት ላይ ነግሠው አዳም ካህን ሆኖ በደስታ ይኖሩ ነበር፡፡ ሙሴ ከእግዚአብሔር ጋር ለ40 ቀናት ተነጋግሮ ሲመጣ እስራኤል «ፊትህን ሸፍንልን» እስኪሉት ድረስ ፊቱ ካበራ ዘወትር ከእግዚአብሔር ጋር ይኖሩ የነበሩት አዳምና ሔዋን ምን ያህል ብርሃናዊ ነበሩ ይሆን? አባቶቻችን «ከፀሐይ ሰባት እጅ ያበሩ ነበር» በማለት ክብራቸውን ይገልጡታል፡፡

2. አዳምና ሔዋን አትብሉ የተባሉትን ዕፅ በልተው የእግዚአብሔርን ሕግ በማፍረስ በደሉ፡፡ ከፈጣሪያቸው ጋር ራሳቸውን ለማስተካከል /አምላክ ለመሆን/ በማሰብና በመመኘታቸው ይቅርታ የማይገባውን ዓመጽ ፈፀሙ፡፡ በዚህም ምክንያት «ከእርሱ በበላህ ቀን ሞትን ትሞታለህ» /ዘፍ. 2:18 / ተብሎ አስቀድሞ በተነገራቸው ሕግ መሠረትም «በፀነሰሽ ጊዜ ጭንቅሽን አበዛዋለሁ፣ በጭንቅ ትወልጃለሽ፣ . . .  ምድር ከአንተ የተነሣ የተረገመች ትሁን፣ በሕይወት ዘመንህ ሁሉ በድካም ከእርስዋ ትበላለህ፤ እሾህና አሜከላ ታበቅልብሃለች. . . »/ዘፍ.3.15-19/ ተብለው ተረገሙ፤ ከእግዚአብሔር ጋር ተጣሉ፤ ከገነት ተባረሩ፤ የሞት ሞት ተፈረደባቸው፤ ሞት ሰለጠነባቸው፡፡ አዳምና ሔዋን ከእግዚአብሔር የተለዩና የተዋረዱ ባሕርይ ያላቸው ስለነበሩ የሚወልዷቸው ልጆችም እንዲሁ ከእግዚአብሔር የተለዩና ባሕርያቸው የተዋረደ እነዚህ መከራዎች ሁሉ የሚደርሱባቸው ሆኑ፡፡

3. አዳምና ሔዋንም ሆኑ ልጆቻቸው ከዚህ ውድቀት ራሳቸውን ማዳን አልቻሉም ነበር፤ ምክንያቱም   አዳም፣ ሔዋንና ልጆቻቸው እንዲድኑ የበደሉን ካሣ በሞት የሚከፍል ሰው ያስፈልግ ነበር፡፡ ምክንያቱም የእግዚአብሔር ፍርድ እውነተኛና ትክክለኛ ስለነበር ካሣ ሳይከፈል ፍርዱ ስለማይሻር ነው፡፡ ከአቤል ጀምሮ የፈሰሰው የሰዎችና የነቢያት ደምም ካሣ መሆን አልቻለም፤ ምክንያቱም እነዚህ ሰዎች ሁሉ ራሳቸው የተዋረደ ባሕርይ ያላቸውና ለመስዋዕትነት የማይበቁ በመሆናቸው ነው፡፡

4. እግዚአብሔር ቸርና ሩህሩህ ስለሆነ የፍጡሩ የሰው ሥቃይ ስላሳዘነው ከራሱ ጋር የሚታረቅበትን መንገድ አዘጋጀ፡፡ እግዚአብሔር በመለኮታዊ ባሕርይው መሞት ስለማይችል ሁኖና ሙቶ ካሣውን ለመክፈል ወስኖ ለአዳምና ለሔዋን ቃል ኪዳን ገባላቸው፡፡ ቀጠሮ ሰጣቸው፡፡ የዘመኑ ፍጻሜ /የቀጠሮው ቀን/ በደረሰ ጊዜ ከሦስቱ አካላት አንዱ አካል የእግዚአብሔር ቃል /ወልድ/ መጣ፤ ከነፍሷ ነፍስ ከሥጋዋ ሥጋ ነሥቶ ከእመቤታችን ከቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን አደረ፡፡ ሰው ሆኖ ተወለደ፡፡ ነቢዩ አሳይያስ «በሰዎች ዘንድ የተናቀና የተጠላ የሕማም ሰውና ሥቃይ ያልተለየው ነበር፤ በእርግጥ እርሱ ደዌአችንን ወሰደ፤ ሕማማችንንም ተሸከመ. . »/ኢሳ.53.3-4/ እንዳለው ከልደቱ እስከ ስቅለቱ እና ሞቱ ድረስ በርካታ መከራዎችን በመቀበል የበደላችንን ዋጋ ከፈለ፡፡ በመስቀል ላይ የሕይወት መሥዋዕትነት በመክፈል የሰው ልጆችን ከራሱ ከአብና ከመንፈስ ቅዱስ ጋር አስታረቀ፡፡

ከዚህም በኋላ ቅዱስ ያሬድ «ወሪዶ እመስቀሉ ቀጥቀጠ ኃይሎ በፀላኢ አርአየ ሥልጣኖ ለዕለ ሞት፤»  «ከመስቀሉ ወርዶ የጠላትን ኃይል ቀጠቀጠ፤ በሞትም ላይ ሥልጣኑን አሳየ» በማለት እንደተናገረው በሲኦል ለ5500 ዘመናት ተይዘው የነበሩ ነፍሳትን ነጻ አወጣቸው፡፡

 

2.ነገረ መስቀል

ከላይ እንደተመለከትነው ዓለም የዳነው ጌታችን ወደዚህ ምድር መጥቶ በተቀበለው ጸዋትወ መከራ እና በሞቱ የበደላችንን ዋጋ በመክፈሉ ከሆነ መስቀል ቤዛችን ነው፤መስቀል የነፍሳችን መድኅኒት ነው፤ ሕዝቡን በመስቀሉ አዳነ፤ በመስቀሉ ዳንን ስንል ምን ማለታችን ነው? ይህንን የምንለው ከሁለት ነገሮች አንጻር ነው፤

2.1. መስቀል እንደ ነገረ ድኅነት ዓርማ /ምልክት/

በመጀመሪያ ደረጃ መስቀል የክርስቶሰ የማዳኑ ሥራ እና የክርስቶስ መከራ ዓርማ ነው፡፡ ቅዱስ ያሬድ «. . . መስቀል የህማም ምልክት ነው. . .» እንዳለው መስቀል የክርስቶስን ሕማም፣ መከራ ሞት እና የማዳን ሥራ የሚወክል ዓርማ ነው፡፡

ይህንን ለመረዳት ከሌላ ቀላል እና ግልጽ ከሆነ ነገር እንነሣ፡፡ ሀገር የሚለው ቃል /ጽንሰ ሐሳብ/ በጣም ሰፊና በርካታ በዓይን የሚታዩና በዓይን የማይታዩ ነገሮች የተካተቱበት ነው፡፡ ይህ እጅግ ሰፊና ረቂቅ የሆነ ነገር ግን በአንድ ነገር ይወከላል፤ በባንዲራ፡፡ ባንዲራ ሀገር በሚለው ጽንሰ ሐሳብ ውስጥ የተካተቱትን ነገሮች ሁሉ ይወክላል፡፡ እንደ ቁብ ጨርቅ ቢሆንም ትርጉሙ ግን ሀገር ማለት ነው፡፡ ባንዲራን መውደድ፣ ለንዲራ መሞት ስንልም እንዲሁ ሀገርን መውደድ፣ ለሀገር መሞት ማለት ነው፡፡ ድርጅቶችም እንዲሁ ከዚህ ጋር ተመሳሳይ በሆነ ሁኔታ ዓርማ አላቸው፡፡

በተመሳሳይ ሁኔታ በመጀመሪያ ደረጃ መስቀል የክርስቶስ የማዳኑ ሥራ የመከራው፣ የመስቀሉ፣ የመሞቱ ወካይ ዓርማ ምልክት ነው፡፡ መስቀሉን ስናየው፣ ስናማትብ፣ ስሙን ስንሰማው እነዚህ የጌታችንን መከራዎች የሚያስታውሰን ምልክት፣ ሁሉንም በመስቀል ላይ የተደረገውን ነገር ሁሉ የሚወክል ዓርማ ነው፡፡ በመስቀሉ አዳነን ስንልም በመስቀሉ ላይ በፈጸመው ቤዛነት አዳነን ማለታችን ነው፡፡

 

ይህ ምልክት እንዲኖር ያስፈለገበት ምክንያት ሰዎች እግዚአብሔርን ማምለክ ይችሉ ዘንድ ለመርዳት ነው፡፡ እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን የነበሩትን የመሥዋዕት ሥርዓቶች ያዘጋጀው፤ በሕዝቡ መካከል ለመገኘቱ ምልክት የሆነውን ታቦት የሰጠው. . . ሰዎች አምልኮታቸውን ለመፈጸም የሚታይ የሚዳሰስ ነገር ስላስፈለጋቸው ነው፡፡

በሐዲስ ኪዳንም በቤተክርስቲያን ያሉት ልዩ ልዩ ሥርዓቶች፣ ንዋያተ ቅዱሳት፣ ከዚሁ አንጻር የተዘጋጁ ናቸው፡፡ ምስጢራተ ቤተክርስቲያን የሚገኘው የማይታይ ጸጋም በሚታይ አገልግሎት የሆነው በዚህ ምክንያት ነው፡፡ በአጠቃላይ እግዚአብሔርን የምናመልከው ሰዎች ነንና ሁሉም የተደረገው ለሰዎች በሚሆን፣ ለሰዎች በሚረዳ መልኩ ነው፡፡

 

የመስቀሉም ነገር እንዲሁ ነው፡፡ የጌታችንን መከራ ስቅለት እና ሞት ክርስቲያኖች ሁል ጊዜ ማሰብ አለብን፡፡ ይህንን እንድናደርግ የሚያስችል፣ የረቀቀውን ጉልህ፣ የራቀውን ቀረብ የሚያደርግ እና ህሊናችንን የሚሰበስብ ዓርማ ተዘጋጀ፤ ይኸውም መስቀል ነው፡፡

ጌታም «መስቀሌን ተሸክማቸሁ ተከተሉኝ» ሲልም ከዚህ አንጻር ነው፤ መከራዬን፣ ስቃዬን፣ ሞቴን ተጋርታችሁ ማለቱ ነው፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ይላል «ጥልን በመስቀሉ ገደለ» /ኤፌ. 2.16/ እኛም «መስቀል ቤዛነ፣ መስቀለ ጽንዕነ፣ መስቀል መድኀኒተ ነፍስነ አይሁድ ክህዱ፣ ንሠነሰ አመነ፣ እለ አመነ በኀይለ መስቀለ ደኀነ» ስንል የክርስቶስን መከራውን፣ መስቀሉን፣ ሞቱን እናምናለን፤ በዚህም ድነናል ማለታችን ነው፡፡

ቅዱስ ያሬድም ከዚሁ አንጻር እንዲህ ይላል፡-

–    «መስቀል ብርሃን ለኩሉ ዓለም መሠረተ ቤተ ክርስቲየን» «መስቀል ለዓለሙ ሁሉ ብርሃን ነው፤ የቤተ ክርስቲያንም መሠረት ነው»

–    «በቀራንዮ ሐፍረተ መስቀል  ተዓገሰ ፣ ጊዜ ተፀልበቱ አዕረቅዎ ልብሰ በአፈ ኩናት ረገዝዎ  ከርሠ በዕፀ መስቀሉ……. መርዔተ ሐደሰ» «በቀራንዮ የመስቀል ሀፍረት ታገሰ፣ በስቅለቱ ጊዜ ከልብሱ ራቁቱን አደረጉት፣ በጦር ጐኑን ወጉት፣ በመስቀሉ መንጋውን አደሰ /አዲስ አደረገ/»

–    «በመስቀሉ አርሃወ ገነተ፤ መተሞዓ ኃይለ ሥልጣኑ ለሞት» «በመስቀሉ ገነትን ከፈተ፤ የሞተ ኃይልም ድል ተደረገ»

 

–    «ትዌድሶ መርዓት ቤተ ክርስቲያን እንዘ ትብል በመስቀልከ አብራህከ ሊተ እንዘ ግድፍተ ወኀድግት አነ ምራቀ ርኩሳን ተዓገስከ በእንቲአየ ሕይወተ ርከብኩ በትንሳኤከ ጸጋ ነሣዕኩ ወደቂቅየኒ ገብኡ ውስተ ህጽንየ በመስቀልከ አብራኀከ ሊተ በመስቀልከ አድኅንከ ኩሎ ዓለመ» «ሙሽሪት ቤተ ክርስቲያን /ጌታን/ እንዲህ እያለች ታመሰግነዋለች የተተውኩና የተጣልኩ ሁኜ ሳለ አብርተህልኛል፤ ስለ እኔ ብለህ የርኩሳንን ምራቅ ታግሰሃል፤ ከትንሳኤህ ህይወት አገኘሁ፤ ፀጋንም አገኘሁ፤ ልጆቼም ወደ እቅፌ ገቡ፤ በመስቀልህ አበራህልኝ፤ በመስቀልህም ዓለምን ሁሉ አዳንህ»

በእነዚህ ሁሉ ‹‹… በመስቀልህ…›› ስንል ‹‹… መከራ በመቀበልህ፣ በመሰቀልህ፣ በሞትህ…›› ማለታችን ነው፡፡

መስቀል ምንን ያስታውሰናል?

መስቀልን ስናይ፣ መስቀልን ሰናስብ፣ ስሙንም ስንጠራ የሚከተሉትን ነገሮች እናስታውሳለን፡-

ሀ. በመስቀል አምላክን ለእኛ ያለውን ፍቅር እናስታውሳለን

 

ነቢዩ ኢሳይያስ «እኛ ሁላችን እንደ በጎች ተቅበዝብዘን ጠፋን፤ እያንዳንዳችንም በየመንገዳችን ነጎድን» /ኢሳ. 53-6/ እንዳለው እኛ የሰው ልጆች በሀጢአታችን ምክንያት ከእግዚአብሔር ተለይተን፣ በሞት ጥላ ስር በመከራና በችግር እንኖር ነበር፡፡

 

«በእርሱ የሚያምን ሁሉ የዘለዓለም ህይወት እንዲኖረው እንጂ እንዳይጠፋ እግዚአብሔር አንድያ ልጁን እስኪሰጥ ድረስ ዓለሙን ወዷል» /ዮሐ. 3-16/ እንደተባለው አምላካችን እኛን ለማዳን አንድያ ልጁን ወደዚህ ምድር ልኮና የሞት መስዋዕትነት ከፍሎ አድኖናል፡፡ «ይህም እግዚአብሔር ለእኛ ያለውን የራሱን ፍቅር ያሳያል» /ሮሜ. 5.8/ ምክንያቱም «ስለ ወዳጆቹ ህይወቱን አሳልፎ ከመስጠት የሚበልጥ ፍቅር ለማንም የለውም፡፡» /ዮሐ. 15-13/

ስለዚህ መስቀል ስለ እኛ ሲል በመስቀል ላይ የሞትን ጽዋ የተቀበለው አምላካችን ለእኛ ያለውን ፍቅር የሚያስታውሰን ምልክት ነው፡፡

 

ለ. በመስቀል ኀጢአታችንን እናስታውሳለን፤

ጌታችን በመስቀል የተሰቀለው እኛ ኃጢአተኞች በመሆናችን ነው፡፡ ስለዚህ መስቀል ኀጢአታችንን የሚያስታውሰን ምልክት ነው፡፡ ይህንን ስናስብም ቅዱስ ጳውሎስ «በዋጋ ተገዝታችኋልና የራሳችሁ አይደላችሁም፤» እንዳለው /1ኛ ቆሮ.6-20/ ከኀጢአት ባርነት ነጻ የወጣነው ዋጋ ተከፍሎብን እንደሆነ አስበን እግዚአብሔርን በማመስገን፣ በትህትና እና ራስን ዝቅ በማድረግ እንሞላለን፡፡

 

ሐ. መስቀል የእግዚአብሔርን ቅን ፈራጅነት ያስታውሰናል፤

መስቀል የእግዚአብሔር ፍቅር እና ቅን ፍርድ በአንድ ላይ የተደረጉበት አደባባይ ነው፡፡ አዳም በበደለ ጊዜ አስቀድሞ በተነገረው መሠረት ሞት ተፈረደበት፤ እግዚአብሔር የሰው ልጆች ወዳጅ ስለሆነ ሊያድነው ቢወድም፣ ፍርዱ ሁል ጊዜ ትክክለኛ ስለነበረ ደግሞ ስለ በደሉ ካሳ ሳይከፈል አላዳነውም፡፡ ስለዚህ ራሱ መጥቶ መስዋዕት በመሆን የበደሉን ሳካ በመስቀል ላይ ከፈለ፤ ፍቅሩና ቅን ፍርዱ በአንድ ላይ ተገለጠ፡፡

መ. መስቀል የጌታችንን ሕማማትና ሞት ያስታውሰናል፤

ጌታችን መድኀኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የበደላችንን ዋጋ የከፈለው ሊነገሩ የማይችሉ ሕማማትን ተቀብሎ፣ ተሰዶ፣ ተሰድቦ፣ ተዋርዶ፣ ተገርፎ፣ የሃጢአተኞች ምራቅ ተተፍቶበት፣ መስቀል ተሸክሞ ተራራ ወጥቶ፣ እጆቹና እግሮቹ ተቸንክረው ከመስቀል ላይ በሕይወቱ ለ3 ሰዓታት በሞቱ ለ2 ሰዓታት ቆይቶ፣ የሞትንም ጽዋ ቀምሶ ነው፡፡

መስቀል እነዚህን ሁሉ የጌታችንን ሕማማትና ሞቱን የሚያስታውሰን ምልክት ነው፡፡

 

ሠ. መስቀልን ስናይ ይቅር መባላችንን እና ድኅነታችንን እናስባለን፡፡

መስቀልን ስንመለከት ኀጢአቶቻችን እንዴት ይቅር እንደተባሉና ጌታችን በመስቀል ላይ ሳለ «አባት ሆይ የሚያደርጉትን አያውቁም ይቅር በላቸው» ማለቱን እናስታውሳለን፡፡ /ሉቃ.13-34/

ዳግመኛም መስቀልን ስንመለከት ጌታችን በነፍሱ ወደ ሲኦል ወርዶ በዲያብሎስ አገዛዝ ስር የነበሩ ነፍሳትን ነጻ እንዳወጣቸው፣ እኛንም በአዳም በደል ምክንያት ከመጣብን የባሕርይ ድካም እንዳዳነን እናስባለን፡፡

አሁንም መስቀልን ስንመለከት በጌታ ቀኝ ተሰቅሎ የነበረውንና ድኅነትን ያገኘውን ወንበዴ፤ ጌታችን በፍቅሩ ወደ እርሱ እንደሳበው፣ በቸርነቱ በደሉን ሁሉ ይቅር ብሎ ወደ ገነት እንዳስገባው እናስባለን፣ እኛም በተስፋ እንሞላለን፡፡

ረ. መስቀል የኀጢአት ደመወዝ ሞት መሆኑን ያስታውሰናል፤

«በበደላችን ሙታን ሆነን ሳለ በክርስቶስ ህያዋን ሆንን» /ኤፌ.2-51/ እንደተባለው ጌታችን እኛን ከሞት ለማዳን በመስቀል ተሰቅሎ ለመሞት ያበቃው እኛ በመበደላችን፣ የበደል /የኀጢአት/ ደመወዝ ደግሞ ሞት በመሆኑ ነው፡፡ መስቀል ይህንን ያስታውሰናል፡፡

 

ሰ. መስቀል ትንሳኤንና ዳግም ምጽአትን ያሳስበናል፤

የጌታችን መስቀልና ሞት ስናስታውስ አብረን ትንሳኤውን እናስባን፤ በእርሱ ትንሳኤ ደግሞ የእኛን ትንሳኤ እናስባለን፡፡

መስቀል ዳግም ምጽአትንም ያስታውሰናል፡፡ ጌታችን ስለ ህልፈተ ዓለምና ዳግም ምፅአት ሲያስተምር እንዲህ ብሏል «የዚያን ጊዜ የሰው ልጅ ምልክት /መስቀል/ በሰማይ ይታያል…. የሰው ልጅም በሰማይ ደመና ሁኖ በኀይልና በታላቅ ክብር ሲመጣ ያዩታል» /ማቴ.24-30/ ዳግም ምጽአትን ስናስብ ለፍርድ በፊቱ እንደምንቆምም እናስታውሳለን፡፡

 

ሸ. መስቀል መስቀልን እንድንሸከም መታዘዛችንን ያስታውሰናል፤

መስቀል ጌታችን «ሊከተለኝ የሚወድ ራሱን ይካድ፣ መስቀሉንም ተሸክሞ ይከተለኝ» /ማቴ.16-24/፣ «የራሱንም መስቀል ተሸክሞ የማይከተለኝ ደቀመዝሙሬ ሊሆን አይችልም» /ሉቃ.14-27/ ብሎ ያስተማረንን ትምህርት ያስታውሰናል፡፡

2.2. መስቀሉ እንደ የማዳኑ ሥራ መሣርያ

በሁለተኛ ደረጃ መስቀል ስንል ጌታችን ዓለሙን ባዳነበት ጊዜ እንደ መሣሪያ የተጠቀመበትን ዕፀ መስቀል /የእንጨት መስቀል/ ማለታችን ነው፡፡ በዚህ ሥር ሁለት ዓይነት መስቀሎችን እንመለከታለን፡፡

2.2.1 በቀራንዮ የተተከለው ጌታ የተሰቀለበት የመጀመሪያው መስቀል

 

በዓለም ታሪክ የተለያዩ አስደናቂ ታሪኮች የተሰሩባቸው ቁሶች /የነገስታት የጦር ዕቃዎች፣የታላላቅ ሰዎች አልባሳት፣ መኪናዎች፣ ዙፋኖች፣ የቴክኖሎጂ ውጤቶች፣…./ በክብር በቤተ መዘክሮች ይቀመጣሉ፤ ከበድ ያለ ዋጋም አላቸው፡፡

ዕፀ መስቀል ጌታ የሰው ልጆችን ያዳነበት መሳርያ፤ ክርስቶስ የተሰዋበት መሠዊያ፣ ድኅነት የተፈፀመበት አደባባይ ነው፡፡ የጌታችን ደም የፈሰሰበትና በደሙ የተቀደሰ፣ የከበረ፣ የተለየ ንዋይ /ሃብት/ ነው፡፡ እንግዲህ በዓለም ታሪክ የተሰራባቸው ዕቃዎች ከተከበሩ ይህ ድኅነት ነፍስ የተገኘበት ንዋይ ምን ያህል ይከብር?

ስለዚህ ዕፀ መስቀሉ ድኅነት የተፈፀመበት መሣሪያ ነውና እናከብረዋለን፣ እንሳለመዋለን፡፡ይህ መስቀል በክርስቶስ ደም የተባረከና የከበረ ስለሆነ የበረከት ምንጭ ሆኗል፡፡ በመጽሐፈ ስንክሳር /በመጋቢት 10 ቀን/  እንደተጻፈውም ድውያንን ፈውሷል፤ ሙታንን አስነስቷል፡፡

2.2.2 ዛሬ ከእንጨት /ዕፅ/፣ ከወርቅ፣ ከብር፣ ከብረት እና ከተለያዩ ነገሮች የሚዘጋጁ መስቀሎች

 

እግዚአብሔር ለሙሴ የሰጠው አንድ ታቦት ብቻ ነው፡፡ ሌሎች ታቦታትን እንዴት እንደሚሠራና እንደሚባርካቸው ግን ነግሮታል፡፡ ይኸውም ሰዎች እየበዙ ሲሄዱ በተለያዩ ቦታዎች ታቦታት ማስፈለጋቸው ስለማይቀር ለሁሉም የሚሆን ይሆን ዘንድ ነው፡፡ ዛሬም በዚሁ መሠረት እንሰራለን፡፡

የመስቀልም ነገር እንዲሁ ነው፡፡ ጌታ የተሰቀለበትን የመጀመሪያ መስቀል ሁሉም ሊያገኘው አይችልም፤ ስለዚህ በየቦታው ያሉ ምዕመናን ከመስቀል የሚገኙ ጥቅሞችን ያገኙ ዘንድ መስቀሎች በየቦታው የሚገኙበት መንገድ ተፈጠረ፡፡

 

በዚህ መሠረት መስቀሎች ከተለያዩ ቁሳቁሶች ይዘጋጃሉ፡፡ ጌታችን የተሰቀለበት መስቀል የተቀደሰው በላዩ ላይ በፈሰሰው ደመ መለኮት ነው፡፡ ዛሬ ያሉት መስቀሎች ደግሞ ይህንን ነገር መስቀል በሚያወሱ ጸሎቶች ይበረኩና ይከብራሉ፡፡ ስለዚህ የመጀመሪያው መስቀል የሚሰጣቸውን አገልግሎቶች ይሰጣሉ፡፡ ማለትም አንድም የመከራ መስቀሉና ዓመቱ አርማ ይሆናሉ፤ አንድም የበረከት ምንጭ ይሆናሉ፤ አጋንንትን ያወጣሉ፤ ድውያንን ይፈውሳሉ፡፡

“አባታችን ሆይ” ክፍል አንድ

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

መግቢያ

አንባቢያን ሆይ ይህ ጽሑፍ የትርጉም ሥራ ሲሆን ትምህርቱም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የማቴዎስን ወንጌል ሲተረጉም ከጻፈው ላይ የተወሰደ ነው፡፡ የዚህ ቅዱስ አባት ሥራዎች ብዙ ከመሆናቸው የተነሣ ታላቁ ጸሐፊ /The great author/ ተብሎ ነው በሥነ መለኮት ምሁራን የሚታወቀው፡፡ “አባታችን ሆይ” የሚለውን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረውን የጸሎት ሥርዐት ይህ ቅዱስ እንዴት አድርጎ ድንቅ በሚባል መልኩ እንደተረጎመው ትመለከቱ ዘንድ እነሆ ብለናል፡፡


ግብዞችን አትምሰሉአቸው

ግን ስትጸልይ ወደ እልፍኝህ ግባና መዝጊያህንም ዘግተህ በሥውር ላለው አባትህ ጸልይ በሥውር የሚያይህ አባትህ በግልጽ ይከፍልሃል፡፡” /ማቴ.6÷1-6/

በዚህ ቦታ ላይ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጻፎችንና ፈሪሳውያንን ግብዞች ማለቱ አግባብነት ነበረው፡፡ ምክንያቱም ወደ እግዚአብሐር ቤት ለጸሎት በሚመጡበት ጊዜ የሰዎችን ቀልብ ለመሳብ ሲሉ ከሥርዓት የወጣ አለባበስን ይለብሱ ነበር እንጂ ለጸሎት ተስማሚ የሆነውን የትሕትና አለባበስን አይለብሱም ነበርና ነው፡፡

ለጸሎት ወደ አምላኩ የሚቀርብ ሰው ሌሎች ጉዳዮቹን ሁሉ ወደ ኋላ ትቶና ከሰው ዘንድም ምስጋናንና ክብርን ሳይሻ ጸሎቱን ተቀብሎ ወደሚፈጽምለት አምላኩ ብቻ ትኩረቱን ሊያደርግ ይገባዋል፡፡ ይህን መፈጸም ትተህ ዐይኖችህን የትም የምታንከራትት ከሆነ ከእግዚአብሐር ቤት በባዶ እጅህ ምንም ሳታገኝ እንድትመለስ ዕወቅ፡፡ ከእግዚአብሔር አምላክ ዘንድ ዋጋ ማግኘትና ማጣት በእጅህ የተሰጠ የአንተ እድል ፈንታህ ነው፡፡ ስለዚህ ከንቱ ውዳሴን የሚሹ ሰዎች ከእኔ ዘንድ አንዳች አያገኙም አላለም፡፡ ነገር ግን “ዋጋቸውን ተቀብለዋል” አለ፡፡

በእርግጥ ከእግዚአብሐር ዘንድ ሳይሆን እነርሱን ከመሰሉ ሰዎች ምስጋናና አድናቆትን አግኝተው ይሆናል፡፡ ይህ ለእነርሱ ዋጋቸው ነው፡፡ ነገር ግን ከእግዚአብሐር ዘንድ አይደለም፡፡ ምክንያቱም ለጸሎታቸው ብድራትን የጠበቁት ከእግዚአብሔር ሳይሆን ከሰዎች ነውና፡፡ ነገር ግን በዚህ ኃይለ ቃል እግዚአብሔር አምላክ ማንኛውንም እንደ ፈቃዱ ልመናና ጸሎት ብናቀርብ ልመናችንን ሊሰማን ጸሎታችንን ሊቀበል ቃል ኪዳን መግባቱም እናስተውላለን፡፡ ጌታችን ጻፎችና ፈሪሳውያን ለጸሎታቸው የመረጡት ሥፍራ ለከንቱ ውዳሴ የሚያጋልጥ መሆኑን ካስረዳ በኋላ እኛ ስንጸልይ ምን ማድረግ እንዳለብን አስተምሮናል፡፡
እንዲህም አለን “አንተ ግን ስትጸልይ ወደ እልፍኝህ ግባ መዝጊያህንም ዘግተህ በሥውር ላለው አባትህ ጸልይ፡፡” ምንድን ነው ታዲያ? እንዲህ ሲለን በቤተ ክርስቲያን ጸሎትን አታድርጉ ሲለን ነውን? አይደለም ነገር ግን እንዲህ ማለቱ በየትኛውም ቦታ ሆነን ጸሎትን ብናደርግ በፍጹም ተመስጦ ሆነን ማቅረብ እንዳለብን ሲያሳስብ ነው፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር በየትም ቦታ ማንኛውንም መልካም ሥራ ብንፈጽም ሁልጊዜም በማስተዋል ሆነን ብንፈጽማቸው የእርሱ ፈቃድ ነውና፡፡ ምንም እንኳን አንተ የእልፍኝህን በር ዘግተህ ብትጸልይ ይህን በማድረግህ ከሰው ዘንድ ምስጋናን ሽተህ ከሆነ የእልፍኝህን በር ዘግተህ በመጸለይህ ከእግዚአብሔር ዘንድ አንዳች ዋጋን አገኛለሁ ብለህ አትጠብቅ፡፡

ይህንን ግልጽ ለማድረግም “ለሰው ትታዩ ዘንድ” የሚለውን ቃል ጨመረበት፡፡ ስለዚህም አንተን የእልፍኝህን ደጅ ዘግተህ ትጸልይ ዘንድ ማዘዙ ልቡናህን ሰብስበህ ትጸልይ ዘንድ ነው እንጂ በርህን ዘግተህ መጸለይ ዋጋ ያሰጥሃል እያለህ አይደለም፡፡ የእግዚአብሐር ፈቃድ የቤትህን ደጅ ዘግተህ ትጸልይ ዘንድ ሳይሆን የልብህን ደጆች በመዝጋት ትጸልይ ዘንድ ነው፡፡

ማንኛውንም የትሩፋት ሥራዎችን ስትሠራ ከከንቱ ውዳሴ ነፃ መሆን መልካም ነው፡፡ በተለይ ደግሞ ስትጸልይ ራስህን ከከንቱ ውዳሴ መጠበቅ ይገባሃል፡፡ ከዚህ ውጪ ግን በጸሎታችን ሰዓት የምንቅበዘበዝና የምንባክን ከሆነና ከልባችን የማንጸልይ ከሆነ ለዚህ ክፉ ለሆነ በሽታ ማለትም ለከንቱ ውዳሴ እንጋለጣለን፡፡ እኛ በተመስጦ ሕሊናችንን ሰብስበን ካልሆነ የምንጸልየው እንዴት ጸሎታችንን እግዚአብሔር እንደሚሰማን እርግጠኛ እንሆናለን?

እንዲያም ሆኖ አንዳንድ ምዕመናን ከሥርዓት የወጣ ጩኸት በማሰማትና ያልተገባ ጠባይን በማሳየት የሌላውን ሰላም የሚያውኩ ከዚህም ባለፈ ራሳቸውን ለከንቱ ውዳሴ የሚያጋልጡ አሉ፡፡ በገበያ ቦታ እንኳ አንድ የእኔ ቢጤ ባልተገባ ጠባይ እና ለመስማት በማይመች ጩኸት ለአንዱ ባለጸጋ ልመና ቢያቀርብ ፈጥኖ ከፊቱ እንዲያባርረው በትሕትና በመሆን ቢለምነው ግን የባለጸጋውን ሆድ አባብቶ ያለውን እንዲሰጠው እንደሚያደርገው አትመለከትምን?

እኛም ስንጸልይ በማይገባና ፈር በለቀቀ ከሥርዐት በወጣ መልኩ አብዝተን በመጮኽ ሊሆን አይገባም፡፡ ነገር ግን በውጭ የምናሰማው አንዳች ጩኸት ሳይኖር ለከንቱ ውዳሴ ከሚያጋልጡ ያልተገቡ ጠባያት ርቀን አጠገባችን ያሉትን ሰዎች  ሳናውክ በፍጹም ትሕትና በውስጣዊ ማንነታችን ማለትም በነፍሳችን ወደ እግዚአብሐር ልንጮኽና ልመናችንን ልናቀርብ ይገባል፡፡

እንዲህ ስንል ሰው ከደረሰበት ታላቅ ኅዘን የተነሣ አምርሮ ሊጮኽ አይችልም ማለታችን ግን አይደለም፡፡ ቢሆንም አንድ ሰው ምንም እንኳ እጅግ ያዘነና የተከዘ ቢሆንም ይህን ታላቅ ኅዘን በነፍሱ ወደ እግዚአብሔር በመጮኽ ሊገልጸው ይችላል፡፡ ለምሳሌ ሙሴ ወደ እግዚአብሐር አምላኩ በነፍሱ አብዝቶ ቃተተ ጮኸም፤ ጩኸቱም ከእግዚአብሐር ዘንድ ተሰማች፤ በዚህም ምክንያት እግዚአብሐር ሙሴን “ለምን ትጮኽብኛለህ” አለው፡፡ /ዘጸአ.14÷15/ የነቢዩ ሳሙኤል እናት ሐና ከከንፈሩዋ የወጣ አንዳችን ድምፅ ሳይኖር በነፍሷ ግን የልቧን ኅዘን ወደ እግዚአብሐር ታመለክት ነበር፡፡ ልመናዋንም እግዚአብሐር ተቀበላት የልቧንም መሻት ሁሉ ፈጸመላት፡፡ አቤል እንኳን በሞቱና በደሙ ከእግዚአብሐር አምላክ ዘንድ ከመለከት ድምፅ ይልቅ ጠርታ የምትሰማ ጩኸትን ወደ እግዚአብሐር ጮኾ ነበር፡፡ /ዘፍ.4÷10/

ነቢዩ ኢዩኤልም በእግዚአብሔርም ፊት የልባችንን ኅዘን ለመግለጽ ልብሳችንን ሳይሆን ልበችንን ለጸሎት ልናዋርድ እንዲገባን ሲያስረዳ “ልባችሁን እንጂ ልብሳችሁን አትቅደዱ” /ኢዩ.2÷13/ ብሎናል፡፡

መዝሙረኛውም “አቤቱ አንተን ከጥልቅ ጠራሁ” /መዝ.129፥1/ ብሏል፡፡ ከልባችን ጥግ ከጥልቁ የሚወጣው ጩኸታችን ድንቅ የሆነ ምላሽን ይዞልን ይመጣል፡፡ በምድራዊው ቤተ መንግሥት ትንሽ የሆነ ኮሽታ ወይንም ሹክሹክታ የግቢውን ጸጥታ ምን ያህል እንደሚያውከው አትመለከትምን? እንዴት ታዲያ ምድራዊ ባልሆነው እጅግም አስፈሪ በሆነው ሰማያዊው ቤተ መንግሥት ስትገባ የበለጠ ፀጥታን ገንዘብህ ማድረግ ይጠበቅብህ ይህን!!

አንተ አሁን በምስጋና ከትጉሃን መላእክት ጋር ተቆጥረሃል፡፡ ከሊቃነ መላእክት ጋርም ማኅበርተኛ ሆነሃል፡፡ ከሱራፌል ጋር ዝማሬን ለእግዚአብሐር ለማቅረብ ታድመሃል፡፡ በሰማያት ያሉ መላእክት ሁሉ በመልካም ሥርዓት በመሆን ለእግዚአብሔር ይገዛሉ፡፡ እርሱንም በመፍራት ሆነው ድንቅ የሆነ ዝማሬአቸውንና ቅዳሴአቸውን ለፍጥረት ሁሉ ገዢ ለሆነው አምላክ ያለማቋረጥ ያቀርባሉ፡፡

አንተም ከእነርሱ ጋር እግዚአብሐርን በማመስገን ስሙን በመቀደስ እነርሱን ትመስሏቸው ዘንድ ከእነርሱ ጋርም በጥምቀት ማኅበርተኛ ሆነሃል፡፡ ስለዚህም በምትጸልይበት ጊዜ ለሰዎች ትታይ ዘንድ አትጸልይ ነገር ግን ወደ እግዚአብሐር ጸልይ፡፡ እርሱ በሁሉ ቦታ ይገኛልና እይታን ከፈለግህ በሁሉ ቦታ ያለ እርሱ ከሰው ይልቅ ያስተውልሃል፡፡ እርሱ በልብህ የታሰበውን እንኳ ያውቃል፡፡

በሥውር የሚያይህ አባትህ በግልጥ ይከፍልሃል፡፡” እንዲህ ሲል /Shall freely give thee “but shall reward thee”/  በነጻ ይሰጣሀል አላለም ነገር ግን እንደሚገባ ሆነህ በመጸለይህ ምክንያት በብድራት በግልጽ ይከፍልሃል ማለት ነው፡፡ አዎን እርሱ በአንተ ዘንድ እንደ ተበዳሪ ሆኖ ታየ፡፡ በዚህም አንተን ምን ያህል እንደወደደህና እንዳከበረህ አስተውል፡፡ እርሱ የማይታይ አምላክ እንደመሆኑ መጠን እንዲሁ እኛም ስንጸልይ በሥውር ላለው አባት ብለን እንጂ ከሰው ምስጋናን ለመቀበል ሽተን ሊሆን አይገባውም፡፡

በጸሎታችሁ አሕዛብን አትምሰሉአቸው

በመቀጠል ጸሎታችንን አንዴት ማቅረብ እንዳለብን ያስተምረናል፡፡ “አሕዛብም በመናገራቸው ብዛት እንዲሰሙ ይመስላቸዋልና ስትጸልዩ እንደነርሱ በከንቱ አትድከሙ” /ማቴ.6÷7/ አለ፡፡
ትመለከታለህ! አስቀድሞ ስለምጽዋት ሲያስተምር ወደ ከንቱ ውዳሴ የሚካተቱንን ነገሮች በማውጣት ከእነርሱ እንድንጠበቅ አዝዞን ነበር፡፡ ከእነዚህም ሌላ ግን ጨምሮ አላስተማረንም ወይንም ከድካማችን ካገኘነው እንጂ በአመፃ ካገኘነው ገንዘብ እንዳንመጸውት አስተማረን እንጂ ምጽዋቱ መቼ መፈጸም እንዳለበት ጊዜውን ለይቶ አላስተማረንም፡፡ ምክንያቱም “ስለጽድቅ የሚራቡ ብፁዓን ናቸው” በማለት ምጽዋታችን ምን መምሰል እንዳለበት አስቀድሞ አስተምሮ ነበርና ነው፡፡

ጸሎትን በተመለከተ ግን ደግሞ ደጋግሞ ነበር ያስተማረው፡፡ አስቀድሞ ጻፎችና ፈሪሳውያንን እንደወቀሳቸው ሁሉ “በከንቱ አትድከሙ” በማለት አሕዛብን ወቀሳቸው፡፡ እንዲህ የሚያደርጉ ወገኖችንም አሳፈራቸው፡፡ጌታችን በትምህርቱ የምንሳብባቸውንና እኛም ልንፈጽማቸው የምንጓጓላቸውን ነገሮች ጎጂነት ነቅሶ በማውጣት ደጋግሞ አስተምሮናል፡፡ ምክንያቱም እኛ ሰዎች ስንባል በውጫዊ ገጽታቸው አምረውና አሽብርቀው በሚታዩ ነገሮች በቀላሉ ስለምንሳብ በውጭ ሲታዩ ጻድቃን የሚመስሉን ግብዞች መስሎ መመላለስን ስለምንመርጥ ነው፡፡

“በከንቱ አትድገሙ” በማለት እንዲህ የሚያደርጉ ሰዎች እጅግ የዘቀጠ አስተሳሰብ እንዳላቸው ገለጠ፡፡ እኛ ከእግዚአብሔር ፈቃድ ውጭ ሥልጣንን፣ ክብርን፣ የጠላት ነፍስን ባለጸግነትን እንዲሁም ሌላም እኛን የማይመለከቱን ነገሮችን በጸሎት ብንጠይቅ በከንቱ እንደመድገም ይቆጠርብናል፡፡

ስለዚህም “አትምሰሏቸው ሳትለምኑት አባታችሁ የሚያስፈልጋችሁን ያውቃልና” አለን፡፡ እዚህ ላይ ጌታችን እንዲህ ሲል ጸሎታችሁን አታርዝሙት ማለቱ አይደለም የጌታችን ዋናው የትምህርቱ ትኩረት ጊዜን በተመለከተ አይደለም ነገር ግን አስቀድመን እንዳስቀመጥነው የማይገቡ ጸሎታትን በማድረግ በከንቱ መድከም አብዝተንና አርዝመን የምንጸልየውን ጸሎት ነው፡፡

የሚገባ ጸሎት ከሆነ ደጋግመን መጸለይ እንዲገባ “በጸሎት ጽኑ” ተብለን ታዘናል፡፡ በኤፌ.6÷18 ላይም በጸሎት መጽናት እንዳለብን ተቀምጦልናል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም “ፊታችሁን ልናይ በእምነታችሁም የጎደለውን ልንሞላ ሌሊትና ቀን ከመጠን ይልቅ እንጸልያለን” /1ኛተሰሎ.3÷9-10/ በማለት በተግባር እየፈጸመ እንደነበር እናስተውላለን፡፡

ጌታችን ከጨካኙ ዳኛ ዘንድ ፍርድ ተጓደለብኝ በማለት በተደጋጋሚ ደጅ የጠናችውን መበለት ምሳሌ በማድረግ /ሉቃ.18÷1/ እንግዳ ስለመጣበት እንጀራ በእኩለ ሌሊት ከወዳጁ ይለምን ዘንድ የሄደውን ሰው ትጋት በማውሳትና ያም ወዳጁ የተጠየቀውን የሰጠበት ምክንያት ስናስተውል ስለወዳጅነቱ ሳይሆን ስለንዝነዛው ብዛት እንደሆነ አብራርቶ ገልጾልናል፡፡ በዚህም ያለማቋረጥ መጸለይ እንደሚገባ አስትምሮናል፡፡ በእርግጥ አጭር ስንኞችን ደጋግሞና አርዝሞ መጸለይ ይገባል አንልም ይህም እንደማይገባ ሲያስረዳ “በጸሎታቸው ብዛት የሚሰሙ ይመስላቸዋልና እነርሱን አትምሰሉአቸው” ብሎናልና፡፡

“ባትለምኑትም አባታችሁ የሚያስፈልጋችሁን ያውቃል” ይላልና እርሱ የሚያስፈልገንን ካወቀ የእኛ መጸለይ ለምን አስፈለገ? ብሎ የሚጠይቅ ከእኛ መካከል አይጠፋም፡፡ አምላክን እንዲህ አድርግ ብለን አናዘውም ነገር ግን ከእርሱ ጋር የፍቃድ አንድነት ይኖረን ዘንድ ስለሚገባን ነው፡፡ /እግዚአብሔር ያለፈቃዳችን አንዳች ነገር ሊያደርግብን አይፈቅድም እርሱ ፈቃዳችንን ይጠይቃል/ ከዚህም በተጨማሪ ከእርሱም ጋር በጸሎት በምንመሠርተው የጠበቀ ግንኙነት ተጠቃሚዎች እንድንሆንና እንዲሆን የገዛ ኃጢአታችንን ዘወትር በማሰብ በትሕትና እንመላለስ ዘንድ ነው፡፡

“እናም ስትጸልዩ እንዲህ ብላችሁ ጸልዩ አባታችን ሆይ በሰማይ የምትኖር”/ማቴ.6÷9/

ይቀጥላል…

ቅዱስ እሰጢፋኖስ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ አስተምህሮ

ቀን ጥቅምት 17/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ሽመል መርጊያ

 

(የሐዋ.6፡8-ም.7፡53)

መግቢያ

በሐዋርያት ስብከት ቤተ ክርስቲያን ስትስፋፋ በትምህርታቸውና በተዐምራታቸው ተስበው ወደ ክርስትና እምነት የተመለሱ ከአይሁድና ከአሕዛብ ወገን የሆኑ ክርስቲያኖች መሬታቸውንና ጥሪታቸውን በመሸጥ  ያላቸውን ሀብት አንድነት በማድረግ በኢየሩሳሌም የአንድነት ኑሮን ይኖሩ ነበር፡፡ በሕብረትም የሐዋርያት ትምህርትን በመስማትና  በጸሎት ይተጉ እንዲሁም ማዕድን በመባረክ በጋራ ይመገቡ ነበር፡፡ መጽሐፍ ቅዱስም “አንድ ልብና አንዲትነፈስ አላቸው በማለት (የሐዋ.4፡32) ስለአንድነታቸው ፍጹምነት ይነግረናል፡፡

 

ነገር ግን በቁጥር እየበዙ ሲመጡ በመካከላቸው በማዕድ ምክንያት ልዩነት ተፈጠረ፡፡ ከይሁዲነት ወደ ክርስትና የተመለሱ ክርስቲያኖች በምግብ ክፍፍል ወቅት ከግሪክ የመጡትን ይጸየፉዋቸው፣ በተለይ ባልቴቶቻቸውን ቸል ይሉባቸው ስለነበር በማኅበሩ መካከል አለመስማማት ተፈጠረ፡፡ ይህም በሐዋርያት ዘንድ ተሰማ፡፡

 

ሐዋርያትም “የእግዚአብሔርን ቃል ትተን ማዕድን እናገለግል ዘንድ የሚገባ አይደለም”የሐዋ.6፡2) በማለት ማዕዱንና በውስጥ ያለውን አገልግሎት ያስተናብሩ ዘንድ ሰባት ሰዎች እንዲመረጡ የክርስቲያኑን ኅብረት ጠየቁ፡፡ ምዕመናኑም በአሳቡ ደስ ተሰኝተው መንፈስ ቅዱስና ጥበብ የሞላባቸውን ሰባት ክርስቲያኖችን መረጡ፡፡ ሐዋርያትም እጆቻቸውን ጭነው ረድእ ይሆኑአቸው ዘንድ ዲያቆናት አድርገው ሾሙአቸው፡፡

 

ከእነዚህም ዲያቆናት መካከል በቅድስና ሕይወቱ ለክርስቲያኖች ዓብነት የሆነው ሰማዕቱ ቅዱስ እስጢፋኖስ ይገኝበታል፡፡ እስጢፋኖስ የሚለው ቃል የግሪክ ቃል ሲሆን ትርጉሙም “አክሊል” ማለት ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስን ወደ ግእዝ በኋላም ወደ አማርኛ የመለሱት አባቶች በቀጥታ የግሪኩን እስጢፋኖስ የሚለውን ቃል ተጠቅመዋል፡፡ ቅዱስ እስጢፋኖስ ምንም እንኳ ስሙ የግሪክ ስም ይሁን እንጂ በትውልዱ አይሁዳዊ ነው፡፡ ወላጆቹ ይህንን ስም ሊሰጡት የቻሉት በፍልስጤም ጠረፋማ ከተሞች ይኖሩ ስለነበር የግርክ ባሕልና ቋንቋ ተጽእኖ አድሮባቸው ይሆናል ተብሎ ይገመታል፡፡

 

ቅዱስ እስጢፋኖስ በሐዋርያት ጥበቃ የነበረችውን ቤተ ክርስቲያን ከአምላክ ዘንድ ባገኘው የማስተማርና የፈውስ ሀብት ያገለግል ነበር፡፡ በእርሱም ታላላቅ ተኣምራት ይፈጸሙ ነበር፡፡ ስለዚህም ሕዝቡ ከፊት ይልቅ እጅግ እየበዛና በትምህርት እየጠነከረ መጣ፡፡ አይሁድም ይህን ተመልክተው በቅዱስ እስጢፋኖስ ላይ በቅናትና በጠላትነት ተነሡበት፡፡ ነገር ግን ከመንፈስ ቅዱስ ባገኘው ጥበብና ኃይል እነርሱን በቃልም በድርጊትም ይቃወማቸው ነበርና ሊረቱት አልተቻላቸውም፡፡ ስለዚህም እግዚአብርሔርን፣ ሙሴ ሲሳደብ ሰምተነዋል፣. ሙሴ የሠራልንን ሥርዐት ይለውጣል፣ በዚህ ቤተ መቅደስና በሕጉ ላይ የስድብን ቃል ይናገራል፣ ይህንንም ቤተ መቅደስ የናዝሬቱ ኢየሱስ አፍርሱ ብሎአል እያለ ያስተምራል አያሉ፣ ሕዝቡን፣ ሽማግሌዎችንና ጸሐፍትን በማናደድ ይዘው ከሸንጎ ፊት አቆሙት፡፡

 

ቅዱስ እስጢፋኖስን በሸንጎ ፊት ባቆሙት ጊዜም ፊቱ ልክ እንደ መልአክ ፊት ሆኖ በርቶ ነበር፡፡ እርሱም ለተከሰሰበት ነጥብ መልስ ሰጠ፡፡ ከአብርሃም እስከ ክርስቶስ ለእነርሱ የተሰጣቸውን በረከት በመቃወማቸው ከተስፋ ቃል እርቀው እንደተወገዱ ገለጠላቸው፡፡ ክርስቶስንም ባለመቀበላቸው ወቀሳቸው፡፡ በዚህም ምክንያት በቁጣ ተነሣስተው ከከተማ ውጭ በመውሰድ በድንጋይ ወግረው ገደሉት፡፡

 

ቅዱስ እስጢፋኖስ አይሁድ በድንጋይ እየወገሩት ሳለ ሰማያት ተከፍተው ክርስቶስን በአብ ቀኝ ቆሞ ተመለከተ፡፡ ይህንን ራእይ የክርስቶስን ትንሣኤን ለማይቀበሉት አይሁድ አሰምቶ ተናገረ፤ እነርሱ ከፊት ይልቅ በእርሱ ጨከኑ በድንጋይም ወገሩት፡፡ ነገር ግን ቅዱስ እስጢፋኖስ ጌታውን ክርስቶስን መስሎ ነበርና ልክ እንደ መምህሩ ክርስቶስ “አቤቱ ይህን ኀጢአት አትቁጠርባቸው” ብሎ በታላቅ ድምፅ ጮኾ  ነፍሱን ሰጠ፡፡ በቤተክርስቲያንም ታሪክ ስለክርስቶስ መስክሮ ሰማዕትነትን የተቀበለ የመጀመሪያው ዲያቆን ሆኖአል፡፡

 

በደማስቆ መንገድ ላይ ክርስቲያኖችን ያሳድድ የነበረ ሳውል በኋላም ቅዱስ ጳውሎስ ተብሎ ስያሜ የተሰጠው ሐዋርያ  ቅዱስ እስጢፋኖስ በድንጋይ በሚወግሩበት ወቅት በእርሱ ሞት ተስማምቶና ድንጋይን በእስጢፋኖስ ላይ ያነሡትን የአይሁድ ልብስ ይጠብቅ የነበረ ብላቴና ነበር፡፡ ነገር ግን ቅዱስ ጳውሎስ ሐዋርያ ከሆነ በኋላ የእስጢፋኖስን ቤተሰቦች አጥምቆአቸዋል፡፡ ይህ ደግሞ ድንቅ ነው፡፡  ቅድስት ቤተክርስቲያናችንም ይህን ቅዱስ የመታሰቢያ ቀን በመስጠት  ጥቅምት 17 የድቁና ማዕረግን በአነብሮተ ዕድ በሐዋርያት የተቀበለበትን፥  ጥር 1 ደግሞ ዕረፍቱን ታስባለች፡፡

 

ከዚህ በመቀጠል ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የሐዋርያት ሥራን በተረጎመበት በ15ኛው ድርሳኑ የሐዋ.6.8-ም.7፡53  ያለውን መሠረት አድርጎ የሰጠውን ትምህርት እንመለከታለን፡፡

 

ድርሳን 15 የሐዋርያት ሥራ ትርጓሜ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ትምህርት

 

ከሰባቱ ዲያቆናት መካከል አንዱ ብቻ የክብሩን አክሊል እንደደፋ ትመለከታለህን? ምንም እንኳ ለሁሉም የተሰጠው ሥልጣን አንድ ዓይነት ቢሆንም ታላቅ የሆነን ጸጋን ለራሱ እንዴት ገንዘቡ እንዳደረገ አስተውል፡፡ አንድም ተአምር ወይም ድንቅ ሳያደርግ በዛን ዘመን እንዴት በምዕመናኑ ዘንድ ታዋቂ እንደሆነ ተመልከት፡፡ ነገር ግን ሕዝቡን ወደ መምራት አልመጣም፡፡ ይህ የሚያሳየን በጥምቀት የምናገኘው ጸጋ ብቻውን ሕዝቡን ለመምራት በቂ እንዳልሆነ ነው፡፡ ምንዕመኑን ለማገልገል የሚነሣ ሰው አስቀድሞ ከጸጋው ጋር ሥልጣኑም ሊኖረው ይገባዋል፡፡ ምንም እንኳ በጥምቀት መንፈስ ቅዱስን የተቀበልን ብንሆንም  የእግዚአብሔርን መንጋ ለማገልገል ሌላ አጋዥ የሆነ የመንፈስ ቅዱስ ድጋፍ ያስፈልገናል፡፡ ከዚህም የምንረዳው ይህንኑ ነው፡፡

 

“የነጻ ወጪዎች ከተባለችው ምኩራብም ከቀሬናና ከእስክንድርያም ሰዎች ከኪልቅያና ከእሲያም ከነበሩት አንዳንዶቹ ተነሥተው እስጢፋኖስን ይከራከሩት ነበር”(ቁ.9) “ተነሥተው” የሚለው ቃል የሚያሳየው የእነርሱ ቁጣ ነው፡፡ እኛ በዚህ ብዙ ሆነን እንደተሰባሰብነው እንዲሁ የእስጢፋኖስ ጉባኤም  ነበር፡፡ በዚህ ቦታ የአይሁድን ሌላ ሴራ እናስተውላለን፡፡ ገማልያል በሐዋርያት ላይ ስህተትን እንዳይፈላልጉ ቢያስጠነቅቃቸውም በዚህ ቦታ ዘዴያቸውን ቀይረው እንደገና  በሐዋርያት ላይ በጠላትነት መነሣታችን በዚህ ቦታ ላይ እናስተውላለን፡፡

 

እናም “የነጻ ወጪዎች ከተባለችው ምኩራብም ከቀሬናና ከእስክንድርያም ሰዎች ከኪልቅያና ከእሲያም ከነበሩት አንዳንዶቹ ተነሥተው እስጢፋኖስን ይከራከሩት ነበር፡፡ ይናገርበት የነበረውንም ጥበብና መንፈስ ይቃወሙ ዘንድ አልቻሉም፡፡ በዚያን ጊዜ፡-በሙሴ ላይ በእግዚአብሔርም ላይ የስድብን ነገር ሲናገር ሰምተነዋል የሚሉ ሰዎችን አስነሡ፡፡”(ቁ.9-12)አለን፡፡ በዚህ እነዚህ ወገኖች  “በሙሴና በእግዚብሔር ላይ የስድብን ቃል ሲናገር ሰምተነዋል” ብለው በቅዱስ አስጢፋኖስ ላይ መነሣታቸውን እናስተውላለን፡፡ እንዲህም ማድረጋቸው ከእርሱ ስህተትን ለማግኘት እንዲመቻቸው ሊያናገሩት ስለፈለጉ ነበር፡፡

 

እርሱ ግን ከፊት ይልቅ በግልጥ ስለክርስቶስ ሰበከላቸው፡፡ በሚሰብክበትም ወቅት የእግዚአብሔርን ሕግ መሠረት አድርጎ ነበረ ወይም ሕጉን እየጠቀሰ ነበር የሰበከው፡፡ እርሱ በግልጥ በመስበኩ ምክንያትም እርሱን ለመወንጀል ሲባል የሐሰት ምስክሮችን ማሰባሰባቸውን ከንቱ አደረገባቸው፡፡ወደ ምኩራቡ የመጡት አይሁዳውያን አመጣጣቸው ከተለያየ ቦታ ነበር፡፡ እንደ አመጣጣቸውም የተለየዩ ምኩራቦችም የነበራቸው ይመስላሉ፡፡ አንዳንዶች ግን  ምልልሱ አሰልችቶአቸው መኖሪያቸውን በዚያው በኢየሩሳሌም አድርገው የሚኖሩም ናቸው፡፡ ምኩራቡዋም የነጻ ወጪዎች ምኩራብ መባሉዋ ከሮማውያን አገዛዝ ነጻ የሆነች ምኩራብ በመሆኑዋ ነበር፡፡ በዚህች ምኩራብ ብዙ የውጭ ሀገር ሰዎች ከትመውባት ይኖሩ ነበር፡፡ ስለዚህ በዚህች ከተማ ሕጉ የሚነበብባት ምኩራብ ይህቺ  ነበረች፡፡

 

“እስጢፋኖስን ተከራከሩት” አለ ወንጌላዊው፤ ተወዳጆች ሆይ በዚህ ኃይለ ቃል አይሁድ  ቅዱስ እስጢፋኖስን በግልጽ አስተማሪነቱ አይገባህም እያሉ ሳይሆን ይከራከሩት የነበሩት እኔ መምህር ልባል አይገባኝም እንዲል ነበር ጫና ይፈጥሩበት የነበሩት፡፡ በእርሱ የሚፈጸሙ ተአምራቶች በእርሱ ላይ በክፋት እንዲነሣሡበት ምክንያት ሆኖአቸው ነበር፡፡ ነገር ግን ከእርሱ ጋር በቃል ወደ መሟገት ሲመጡ አሳፍሮ ይመልሳቸው ነበር፡፡ ስለዚህም ሐሰተኛ ምስክሮችን ወደማሰባሰብ ተመለሱ፡፡

 

ነገር ግን “እስጢፋኖስን ይከራከሩት ነበር ይናገርበት የነበረውንም ጥበብና መንፈስ ይቃወሙ ዘንድ አልቻሉም፡፡” ተብሎ እንደተጻፈው  ለክርክራቸው ምላሽ ስላሳጣቸው ይህ ምክንያት ሆኖአቸው በቁጣ በመነሣሣት እርሱን ለመግደል አልሞከሩም፡፡ ነገር ግን ሐዋርያትን በመተው በእርሱ ላይ ብቻ ውንጀላዎችን በማቅረብ በዚህ መንገድ በሐዋርያትና በተከታዮቻቸው ላይ ሽብርን በመዝራት ጉባኤውን መበታተንን ነበር ዓላማቸው፡፡

 

ስለዚህም ሲከሱት “እንዲህ ብሎ ተናገረ” አላሉትም ነገር ግን  “ሕዝቡንና ሽማግሌዎችም ጻፎችም ቀርበውም ያዙት ወደ ሸንጎም አመጡትና፡- ይህ ሰው በዚህ በተቀደሰ ስፍራ  በሕግም ላይ የስድብን ነገር ለመናገር አይተውም”(ቁ.12-13) በማለት ነበር የከሰሱት፡፡” “የስድብን ነገር ለመናገር አይተውም” ሲሉም እንዲህ ማወክ የእለት ከእለት ተግባሩ አድርጎታል ሲሉ ነው፡፡

 

“ይህ የናዝሬቱ ኢየሱስ ይህን ስፍራ ያፈርሰዋል ሙሴም ያስተላለፈልንን ሥርዐት ይለውጣል ሲል ሰምተነዋልና የሚሉ የሐሰት ምስክሮችን አቆሙ፡፡”(ቁ.14)ሲሉም ክርስቶስን ሊነቅፉት ሽተው የናዝሬቱ ማለታቸውን እናስተውላለን ፡፡ እነዚህ ወገኖች “ቤተመቅደስን የምታፈርስ በሦስትም ቀን የምትሠራው ራስህን አድን”(ማቴ.27፡40) በማለት በክርስቶስ ላይ ሲሳለቁ የነበሩ ወገኖች ናቸው፡፡እነዚህ ወገኖች ምንም እንኳ አገራቸውን ጥለው የሚኖሩ ቢሆኑም ለሙሴና ለቤተመቅደሱ ያላቸው ክብር የተለየ ነበር፡፡ የእነርሱ ክስ ሁለት ገጽታ ነበረው፡፡ እርሱ ሥርዐቱን የሚለውጠው ከሆነ በእርሱ ምትክ ሌላ ሥርዐት ይተካልና ብለው ስለሰጉ ነበር፡፡ ለውጡ እንዴት ከቀደመው የተሻለና ከዕንቊ ይልቅ የከበሩ ጸጋዎች የሞሉት እንደሆነ አስተውል፡፡

 

“በሸንጎ የተቀመጡት ሁሉ ትኩር ብለው ሲመለከቱት እንደ መልአክ ፊት ሆኖ ፊቱን አዩት ፡፡”(ቁ.15) በቤተክርስቲያን አነስተኛ ማዕረግ ላይ ላለው ክርስቲያን እንኳ የፊት መልክ እንደ ፀሐይ አብርቶ መታየት የተለመደ መሆኑን ነው ከዚህ ምንባብ  የምናስተውለው፡፡ አንድ የምጠይቀው ጥያቄ አለኝ ይህ ዲያቆን ከሐዋርያት የሚያንስበት ነገ አለውን? ተአምራት ከመፈጸም አልተቆጠበም፣ በድፍረት ነበር ሲያስተምር የነበረው፡፡ መጽሐፉም “በሸንጎ የተቀመጡት ሁሉ ትኩር ብለው ሲመለከቱት” ይልና “እንደ መልአክ ፊት ሆኖ ፊቱን አዩት”ይላል (ዘጸአ.34፡30) ይህ የእርሱ ጸጋ ነው፤ ይህ የሙሴ ክብር ነው፤ እርሱ የሚናገረውን ሁሉ በመታዘዝ ይፈጽሙት ዘንድ እግዚአብሔር አምላክ ይህን ክብር ሰጥቶት ነበር፡፡ አዎን ዛሬም በሚወዱአቸውም በሚጠሉአቸውም ፊት አስገራሚና አስደናቂ  መንፈሳዊ ብርሃንን ከፊታቸው የሚፈልቅላቸው ቅዱሳን አሉ፡፡

 

በዚህ ቦታ የቅዱስ እስጢፋኖስን ቃል መስማት ለምን እንዳስፈለገ አስቀድሞ ተገልጦአል፡፡ ስለዚህም ከዚህ በመቀጠል “ሊቀ ካህናቱም ይህ ነገር እንዲህ ነውን አለ? (የሐዋ.7፡1) እንዲህ ዓይነት ጥያቄ ውስጥ አንዳች ታላቅ ተንኮል እንዳለ ማስተዋል ይቻላል፡፡ ስለዚህም ቅዱስ እስጢፋኖስ መልሱን ታላቅ በሆነ ብስለት ጀመረ “ወንድሞችና አባቶች  ሆይ ስሙ የክብር አምላክ ለአባታችን ለአብርሃም በካራን ሳይቀመጥ ገና በሁለት ወንዝ መካከል ሳለ ታየና ከአገርህና ከዘመዶችህም ወጥተህ ወደማሳይህ ወደ ማንኛውም ምድር ና አለው፡፡” አለ፡፡(ቁ.2-3) በዚህ መልሱ የእነርሱን ተንኮል ነቅሎ አጠፋው፡፡ በዚህም ስለምን ቤተመቅደሱ  ከእንግዲህ ምንም እንደማይጠቅም ገለጠላቸው፡፡ ሥርዐታቸውም ከእነርሱ ግምት ውጪ ምንም ጥቅም እንደሌለው በተዘዋዋሪ አስረዳቸው፡፡ እንዲሁም ስብከቱን ምንም የማስቆም ኃይሉ እንደሌላቸውና ደካማ በሆነው አካል ተጠቅሞ እግዚአብሔር ብርቱ የሆነውን ኃይሉን እንደሚገልጥ አሳየበት፡፡

 

ይህ የመግቢያ ንግግሩ ማግ ጠቅላላ የንግግሩን ይዘት እንዴት እንዲታታው አስተውል፡፡ ከዚህ በላይ ደግሞ እነዚህ ወገኖች እንዴት ታላቅ ደስታና ታላላቅ በረከቶችን ያመጡላቸውን አስካሁንም እየተቃረኑዋቸው እንደመጡ፣ አሁንም ድል ሊነሡት የማይችሉትን አምላክ እየተፈታተኑ እንደሆኑ መግለጡንም ልብ እንላለን፡፡

 

“የክብር አምላክ ለአባታችን ለአብርሃም በካራን ሳይቀመጥ ገና በሁለት ወንዝ መካከል ሳለ ታየና ከዚህ  ከአገርህና ከዘመዶችህም ወጥተህ ወደማሳይህ ወደ ማንኛውም ምድር ና አለው “ አለው፡፡ በዚያን ዘመን ቤተመቅደስ፣ መሥዋዕትም አልነበረም ነገር ግን የእግዚአብሔር ራእይ ብቻ ለአብርሃም የተገለጠለት ነበር፡፡ የእርሱም ቅድመ አያቶቹ ፋርሶች እንደነበሩ እርሱም በተቀመጠባትም ምድር እንግዳ ሆኖ እንደኖረ ያስረዳቸው፡፡በንግግሩ መጀመሪያ ላይ ቅዱስ እስጢፋኖስ “ የክብር አምላክ” ማለቱ መልካም ነበር፡፡ በዚህም እግዚአብሔር ለሰዎች ከሰጠው ክብር ውጪ እንዳደረጋቸው አስረዳቸው፡፡ “የክብር አምላክ” ሲል   “አብርሃምን ያከበረው አምላክ እኛም ይህን ክብር በእምነት እንድናገኝ  አበቃን” ሲላቸው ነው፡፡

 

ቅዱስ እስጢፋኖስ ከሥጋዊ ሥርዐትና ለቦታ ከሚሰጡት ክብር አውጥቶ እንዴት በውስጣቸው ጥያቄን እንደፈጠረባቸው አስተውል፡፡ “የክብር አምላክ” አለ እንዲህ ሲል እርሱ ከእኛ ዘንድ፣ ከመቅደሱም ለእርሱ የሚቀርበው ክብር፣ ክብሩን እንደማይጨምርለት፣ ይልቁኑ እርሱ ራሱ የክብራቸው ምንጭ እንደሆነ ለማሳየት በመፈለጉ ነበር እንዲህ ያላቸው፡፡ በተጨማሪም  ሴራ ሠርታችሁ እኔን ለዚህ ሸንጎ በማቅረባችሁ እግዚአብሔርን ያከበራችሁት እንዳይመስላችሁም እያላቸው ነበር፡፡

 

“ከዘመዶችህ” አለ፡፡ ስለምን የአብርሃም አባት ታራ ከካራን ወጣ ብሎ መጽሐፍ ቅዱስ ተናገረ? (ዘፍ.11፡1) ከዚህ የምንማረው ለአብርሃም በተገለጠለት ራእይ መሠረት የአብርሃምም አባት ከካራን ወጥቶ ከንዓን መግባቱን ነው፡፡ በዚህ ቦታ ደግሞ አብርሃምን  “ከዚህ  ከአገርህና ከዘመዶችህም ወጥተህ ወደማሳይህ ወደ ማንኛውም ምድርና አለው”  በአብርሃም ታላቅ መታዘዝ  የእነርሱን አለመታዘዝ በመግለጥ  የአብርሃም ልጆች ለመባል ምንም እንደማይበቁ ገለጠላቸው፡፡  “ከዘመዶችህ” በማለት ለእግዚአብሔር የማይመቹ ክፉዎች፣ ክፋታቸውንም ሊታገሥ ካልቻላቸው ትውልድ እንደሆኑ፣  አብርሃምም በዚያ ቢቆይ  ከክፋታቸው የተነሣ መልካም ፍሬን ሊያፈራ እንደማይችል ሲገልጥለት ነው፡፡

 

“በዚያን ጊዜ ከከለዳውያን አገር ወጥቶ በካራን ተቀመጠ፡፡ ከዚያም አባቱ ከሞተ በኋላ እናንተ ዛሬ ወደምትኖሩበት ወደዚች አገር አወጣው፡፡ በዚህችም የእግር መረገጫ  ጫማ ስንኳ የሚያህል ርስት አልሰጠውም ”(ቁ.4) እንዲህ በማለቱ በአእምሮአቸው ርስታችን ናት ብለው ከሚመኩባት አውጥቶ እንደሰደዳቸው እናስተውላለን፡፡ ሰጠው ቢላቸው ኖሮ ፍርዱ በእነርሱ ላይ ሳይሆን በእርሱ ላይ ይወድቅ ነበር፡፡ ስለዚህም ዘመዶቹንና ሀገሩን ጥሎ ከወጣ በኋላ ወደዚህ መጣ አላቸው፡፡  ከዛስ በኋላ ከንዓንን ለአብርሃም ርስት አድርጎ አልሰጠውምን? ሰጥቶታል ነገር ግን ይህ የሌላይቱ ርስት ጥላ ነበር፡፡

 

ቅዱስ እስጢፋኖስ ትምህርቱን “ርስት አልሰጠውም” ብቻ ብሎ ለማጠናቀቅ አልፈለገም “ነገር ግን ልጅ ሳይኖረው ለእርሱ ከእርሱም በኋላ ለዘሩ ይሰጠው ዘንድ ተስፋ ሰጠው፡፡” (ቁ.5) አለ፡፡ ከዚህ በመቀጠል የማይቻለው ሁሉ ለእርሱ የሚቻለው እግዚአብሔር ምን እንዳደረገ ገለጠላቸው፡፡ ከሩቁ አገር የሆነ ሰው እነሆ እግዚአብሔር እንዲህ አለው፡- አንተን የከንዓን አገር ገዢ አደርግሃለሁ፡፡ ነገር ግን ስለ እርሱ የተነገረውን መልሰን እንመርምረው፡፡ ተወዳጆች ሆይ እጠይቃኋለሁ በቅዱስ እስጢፋኖስ ላይ የጸጋው ብርሃን የታየው በምን ምክንያት ነው? ጸሐፊው ስለእርሱ ማንነት አስቀድሞ ሲጽፍ “ጸጋና ኃይል የተሞላ”(የሐዋ.6፡8)በማለት ማረጋገጫውን ሰጥቶአል፡፡

 

ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ መገለጥን ለእያንዳንዱ ለጥቅም ይሰጠዋል ለአንዱ ጥበብን መናገር ይሰጠዋልና፣ ለአንዱም በዚያው መንፈስ እውቀትን መናገር ይሰጠዋል፣ ለአንዱም በዚያው መንፈስ እምነት፣ ለአንዱ የመፈወስ ስጦታን …” (1ቆሮ.12፡8፣9)እንዲል አንድ ሰው የመፈወስ ጸጋ ያይደለ ሌላ ጸጋ ሊሰጠው ይችላል፡፡ “በሸንጎ የተቀመጡት ሁሉ ትኩር ብለው ሲመለከቱት እንደ መልአክ ፊት ሆኖ ፊቱን አዩት፡፡”(ቁ.15) ብሎ መናገሩ እንደእኔ ለቅዱስ እስጢፋኖስ  በመንፈስ ቅዱስ የተሰጠውን “ጸጋና ኃይሉን” ይመስለኛል፡፡ ልክ በርናባስን “ደግ ሰውና መንፈስ ቅዱስ እምነትም የሞላበት ነበረና፡፡” (የሐዋ.11፡24) እንደተባለው ዓይነት ማለቴ ነው፡፡ እውነተኞችና ንጹሐን ሰዎች ከምንም ነገር በላይ ሰዎች ይድኑ ዘንድ ይፈልጋሉ ፡፡ ይህ ጸጋም እጅግ ታላቅ የሆነ ጸጋ ነው፡፡

 

“በዚያን ጊዜ፡- በሙሴ ላይ በእግዚአብሔርም ላይ የስድብን ቃል ሲናገር ሰምተነዋል የሚሉ ሰዎችን አስነሡ፡፡”(ቁ.11) አለ፡፡ አስቅድመው ሐዋርያትን ሲከሷቸው ትንሣኤውን ይሰብካሉ ሕዝቡን ወደ ራሳቸው ስበዋል ብለው ነበር፡፡ በዚህ ግን ሕመማቸውን ከእነርሱ ላይ ባራቀላቸው ቅዱስ ላይ ክሳቸውን ያቀረቡት፡፡ (ቁ.4፡ 2) እነዚህ ወገኖች በተደረገላቸው ፈውስ የተነሣ ምስጋናን ሊያቀርቡ  እንጂ እርሱ ላይ በጠላትነት እንዲነሡ የሚያበቃቸው አልነበረም፡፡ እንዴት ታላቅ እብደት ነው! በዚህ ቦታ በሥራ የረታቸውን  በቃላቸው ሊረቱትን ሲሟገቱት እናስተውላለን፡፡ በክርስቶስ ላይ የፈጸሙትን በቅዱስ እስጢፋኖስም ላይ የደገሙት በቃል ብቻ ጉልበታቸውን ማሳየት ነው፡፡

 

እነዚህ ወገኖች ምንም ወንጀል ሳያገኙባቸው ያለምንም መረጃ ምንም የሚከሱበት ነጥብ ሳይኖራቸው ክርስቲያኖችን ሲይዙዋቸው አያፍሩም፡፡ እነርሱ ላይ ምስክር ኖሮት እነርሱን ወደ ፍርድ ወንበር የሚያመጣቸው እንዳልነበር አስተውሉ፡፡ ከሆነ ግን እነርሱ ተከራክረው ይረቱዋቸው ነበር፡፡ ነገር ግን ሐሰተኛ ምስክሮችን በእነርሱ ላይ ያስነሡባቸዋል፡፡ ምክንያቱም ሥራቸው ሕገወጥ እንዳይመስልባቸው ነበር፡፡ እነዚህ ወገኖች ክርስቶስን ሕግን ሽፋን አድርገው የሰቀሉት ወገኖች ናቸው፡፡

 

ቢሆንም የሐዋርያትን እንዲሁም የቅዱስ እስጢፋኖስን ስብከት ሰውን  እንዴት እየለወጠ እንደነበር አስተዋላችሁን? በዚህም ምክንያት ነው እነርሱ ላይ በቁጣ ከመነሣት አልፈው በድንጋይ እስከመውገር ደደረሱት፡፡ አሁንም እንዲሁ ናቸው፡፡ እንዲህም በሚፈጽሙበት ወቅት አንዱ ወዳጁን ወደ አንድ ቦታ ወስዶ አንደሚደረገው ዓይነት በየግላቸው የሚያደርጉት ዱለታ አይደለም፡፡ ነገር ግን  ከየአቅጣጫው ተሰባስበው ነበር ሴራቸውን ይጠነስሱ ይነበሩት፡፡ በሴራቸው ጠላቶቻቸውን ሳይቀር ያሳትፉ ምስክር ይሆኑላቸው ዘንድ ያግባቡ ነበር፡፡ ይህን ያህልም ደክመው የእስጢፋኖስን ጥበብ መቃወም አልተቻላቸውም፡፡(ቁ.10)

 

ከኢየሩሳሌም ብቻ ያሉት አይደሉም እርሱን ለመቃወም የተሰለፉት ነገር ግን ከሌሎችም አገራት የመጡትም ጭምር  ነበሩ፡፡ እኒህ ወገኖች “በሙሴ ላይ በእግዚአብሔርም ላይ የስድብን ቃል ሲናገር ሰምተነዋል”አሉ (ቁ.11) እናንተ በድርጊታችሁ እፍረትን የማታውቁ አይሁድ ሆይ የእናንተ ድርጊት በራሱ እግዚአብሔርን እንደመሳደብ አይቆጠርምን? ስለዚህ ክፉ ተግባራችሁ ዞር ብላችሁ አታስቡምን?

 

እነዚህ ወገኖች በዚህም ቦታ ሙሴን ማንሣታቸው የእግዚአብሔር ነገር ለእነርሱ እንደተራ ነገር ተደርጎ ስለሚቆጠር ነው፡፡“… ይህ ከግብጽ ያወጣን ሙሴ ምን እንደሆነ አናውቅምና”(የሐዋ.7፡40)ያሉት እነዚህ ወገኖች፣ የሙሴ ወዳጆች መስለው በመታየት በየትኛውም ሙግታቸው ላይ የሙሴን ስም መላልሰው ያነሡ ነበር፡፡

 

“ሕዝቡንና ሽማግሌዎችን ጻፎችንም አናደዱ”(ቁ.12) ይላል፡፡ በዚያ ዘመን የነበረው ሕዝቡ በቀላሉ የሚታለል ሕዝብ ነበር፡፡ አስቡት እስቲ እንዴት ወደዚህ ድንቅ ማዕረግ የደረሰ ሰው እግዚአብሔርን ሊሳደብ ይችላል? እግዚአብሔርን የሚሳደብ ኃጢአተኛ ቢሆን ኖሮ እንዴት በሕዝቡ ፊት እንዲህ ዓይነት ድንቃድንቅ ተአምራትን ሊያደርግ ይችላል? ነገር ግን አላዋቂና ሥርዐት አልበኛ ሕዝብ ለእነርሱ ክፉ ፈቃድ መፈጸም እንደ ደጀን ሆናቸው፡፡ “በሙሴ ላይ በእግዚአብሔርም ላይ የስድብን ቃል ሲናገር ሰምተነዋል” (ቁ.11) እና “ይህ ሰው በዚህ በተቀደሰው ስፍራና በሕግም ላይ የስድብን ነገር ለመናገር አይተውም”(ቁ.13) እንዲሁም “ይህ የናዝሬቱ ኢየሱስ ይህን ስፍራ ያፈርሰዋል ሙሴም ያስተላለፈልንን ሥርዐት ይለውጣል ሲል ሰምተነዋል”(ቁ.14) ብለው ነበር ቀሊል ልብ ያለውን ሕዝብ በእርሱ ላይ የቀሰቀሱበት፡፡ በዚህ ቦታ ሙሴ ያስተላለፈልንን ሥርዐት አሉ እንጂ እግዚአብሔር የሠጠንን ሥርዐት አላሉም፡፡ በጭፍን ጥላቻም በእርሱ ላይ ተነሣሥተው የእነርሱን ክፋት በእርሱ ላይ በመለጠፍ ሥርዐት አልበኛ ብለው ከሰሱት፡፡

 

ነገር ግን እግዚአብሔርን የሚሳደብ አንድም ሰብዕና የሌለው ሰው መሆኑን እንዲገለጥ “በሸንጎ የተቀመጡት ሁሉ ትኩር ብለው ሲመለከቱት እንደ መልአክ ፊት ሆኖ ፊቱን አዩት” ይህ ቅዱስ በሸንጎው ፊት እንዲህ ብለው ሲያሳጡት እንኳ ርጋታን ተላብሶ ነበር ክሱን ያደምጥ የነበረው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ በአንድ አጥፊ ላይ እውነተኛ ምስክሮች ምስክርነታቸውን ሲሰጡ እንዲህ ዓይነት ተአምር እንደተከሰተ ጽፎልን አናገኝም፡፡ ነገር ግን በቅዱስ እስጢፋኖስ ላይ የሚመሰክሩ ምስክሮች ሐሰተኞች ስለመሆናቸው እግዚአብሔር ያሳይ ዘንድ   ፊቱ እንደመልአክ ፊት እንዲበራ አደረገው፡፡

 

እኚህ አይሁድ ሐዋርያትን ስለ ክርስቶስ ዳግም እንዳይሰብኩ ከለከሉ  እንጂ ሐሰተኞች ምስክሮች አቁመው አልከሰሷቸውም ነበር፡፡ ይህን ቅዱስ ግን ሐሰተኛ ምስክሮችን አቁመው በሸንጎ ፊት ከሰሱት፡፡ ስለዚህም በሁሉ ፊት የእርሱ ጻድቅነት ይሟገታቸው ዘንድ ከፊቱ ብርሃን መንጭቶ ሲያበራ ታያቸው፡፡ ይህም ሽማግሌዎችንም ሳይቀር አስደንቁዋቸው ነበር፡፡

 

እርሱም  እንዲህ አለ፡-“ወንድሞችና አባቶች ሆይ ለአባታችን ለአብርሃም በካራን ሳይቀመጥ ገና በሁለት ወንዝ መካከል ሳለ ታየው” አለ፡፡(ም.7፡4) በዚህ ንግግሩ የእግዚአብሔር የተስፋ ቃል ከርሰታቸው፣ ከግርዘት፣ ከመሥዋዕት፣ ከቤተመቅደሱ በፊት እንዲኖር፣ ከእነርሱ በጎነት የተነሣ ግርዘትና ሕግ ለእነርሱ እንዳልተሰጣቸው ነገር ግን ምድሪቱ በአብርሃም መታዘዝ ምክንያት እንደተሰጠቻቸው እንዲገነዘቡ አድርጎአቸዋል፡፡ እንዲሁም መገረዛቸው ብቻውን የተስፋውን ቃል ለመቀበል እንደማያበቃቸው  አመለከታቸው፡፡ ከእነዚህ በተጨማሪም ለአማናዊው ሥርዐት ይህ ጥላ እንደሆነ እንዲሁም እግዚአብሔር ወደ አዘጋጀው አገርና ርስት ለመግባት ሲባል  አገርንና ርስትን ጥሎ በእርሱ ትእዛዝ መውጣት ሕግን ማፍረስ እንዳልሆነ ሲያስረዳ “በዚያን ጊዜ ከከለዳውያን አገር ወጥቶ በካራን ተቀመጠ”(ቁ.4)እንዳለ ማስተዋል እንችላለን፡፡

ይቀጥላል……

 

ኢይብቁል ብክሙ መሪር ሥርው /መራራ ሥር አይብቀልባችሁ/ /ዕብ.12፡15/

ዘገብርኤሏ


የአብርሃም ልጆች ነን የሚሉ ነገር ግን የአብርሃምን ሥራ የማይሠሩና የነቢዩ ዳዊት ልጆች ነን የሚሉ የእርሱን ፈለግ የማይከተሉ ዕብራውያንን ቅዱ ጳዉሎስ «መራራ ሥር አይብቀልባችሁ» ሲል መከራቸው፡፡ ዕብራውያን በእግዚአብሔር እናምናለን፤ የእሱ ልጆች ነን እያሉ ይመጻደቁ ስለነበሩ መልካም ሥራ በመሥራት ወደ እግዚአብሔር እንዳይቀርቡ የከለከላቸውን መራራውን ሥር እንዲያስወግዱ አሳሰባቸው፡፡ ሁሉን የሚያይና የሚያውቅ አምላከ ሰማይ ወምድር ኢየሱስ ክርስቶስ እነዚህን ውጫቸውን ያሳመሩ ነገር ግን ውስጣቸውን በኃጢአት ያሳደፉትንና በመራራ ሥር የተመሰለው ኃጢአት በውስጣቸው የበቀለባቸውን ጸሐፍትና ፈሪሳውያንን ሲገስጽ «እናንተ ግብዞች ጻፎች፤ ፈሪሳዉያን በውስጡ ቅድሚያና ስስት ሞልቶ ሳለ የጽዋውንና የወጭቱን ውጭ ስለምታጠሩ ወዮላችሁ፡፡» ብሏቸል፡፡ /ማቴ.23፡25/

ኃጢአትን በሐልዮ ጸንሶ በነቢብ መውለድ፣ በነቢብ ወልዶም በገቢር ማሳደግ መራራ ሥር ነው፡፡ /ማቴ.24፡16/ ይህም ማለት ኃጢአትን ማሰብ አስቦም ሥራ ላይ ማዋል በአጠቃላይ በኃጢአት መውደቅ በሰው ልቡና ውስጥ የሚበቅል መራራ ሥር ነው፡፡ በዚህም «ሐሞትና እሬትም የሚያበቅል ሥር አይሁንባችሁ» /ዘዳ.18፡19/ የተባለውም የሰው ልጅ በመራራ ሥር፣ በሐሞትና በእሬት የተመሰለውን ኃጢአት ከሕይወቱ ካላራቀ መራራ ገሀነመ ዕሳት እጣ ፈንታው ይሆናል፡፡
ከላይ የጠቀስናቸው ሐሳቦች በሙሉ መራራ ሥር የተባለው ኃጢአት መሆኑን የሚያረጋግጡ ናቸው፡፡ ስለሆነም እስኪ በሕይወታችን ውስጥ ሊነቀሉ የሚገባቸው ከእግዚአብሔር መንግሥት የሚለዩንን መራራ ሥሮች በዝርዝር እንመልከት፡፡

1.ዝሙት

ዝሙት አእምሮን የሚያጐድል፣ ሰላምን የሚነሣ፣ ጤንነትን የሚያሳጣ፣ ሕይወትን የሚያበላሽ፣ ጸጋ እግዚአብሔርን የሚያሳጣ /የሚገፍፍ/ በሰው ልቦና ውስጥ የሚበቅልና መነቀል ያለበት መራራ ሥር ነው፡፡ ብዙ ታላላቅ አባቶች ክብራቸውን ያጡት በዝሙት እንደሆነ መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡ ለምሳሌ፡- እስራኤላዊያን ከሞአብ ልጆች ጋር በማመንዘራቸው ብኤልፌጐር የሚባል ጣዖት እንዲያመልኩ አደረጓቸው፡፡ ከዚህም የተነሣ እግዚአብሔርን በማስቆጣታቸው 24 ሺሕ ሕዝብ በአንድ ቀን ተቀስፏል፡፡ /ዘፍ.22፡37፣ ዘኁ.27፡1/ «ኃጢአትን የሚዘራ መከራን ያጭዳል» እንደተባለው፡፡ /ምሳ.22፡1ዐ/
ዝሙት፣ ሴሰኝነትና አመንዝራነት ቅድስናን ከሚያሳጡ ታላላቅ ኃጢአቶች ውስጥ የሚቆጠሩ ናቸው፡፡
የሰው ልጅ በእነዚህ ኃጢአቶች እንዳይወድቅ እግዚአብሔር አምላክ ሁሉን አዋቂ ነውና አንድ ለአንድ በመወሰን ጸንቶ እንዲኖር ጋብቻን ባርኮ ቀድሶ ሰጥቶታል፡፡ «መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር፤ መኝታውም ንጹሕ ይሁን፣ ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል፡፡» እንዲል፡፡ /ዕብ.13፡4፣ 1ቆሮ.7፡1/ ዝሙት ከእግዚአብሔር መንግሥት የሚለይ መራራ ሥር ነው የተባለውም ለዚህ ነው፡፡ ሶምሶንም ጸጋውን እንዲገፈፍ ያደረገው ይህው በውስጡ የበቀለው መራራ ሥር ነው፡፡ /መሳ.17፡1/ ይህ ታላቅ ሰው ለእግዚአብሔር የተለየ ናዝራዊ ቢሆንም አንድ ናዝራዊ ማድረግ የሌለበትን የዝሙትን ተግባር ፈጽሞ በመገኘቱ ከክብሩ ተዋርዷል ኀይሉ ተነፍጎታል፡፡ /ዘኁ.6፡1/ ዛሬም ትእዛዛተ እግዚአብሔርን በመጣስና ዝሙት በመሥራት ከክብር እየተዋረድን ያለን ሰዎች ራሳችንን ልንመረምርና መራራውን ሥር በንስሐ በጣጥሰን በመጣል ወደ እግዚአብሔር ልንቀርብ ይገባል፡፡ ለሶምሶን እግዚአብሔር አምላክ ታላላቅ ውለታዎችን ቢውልለትም፤ እሱን ያስጨነቀው አምላክ ያደረገለት ውለታ ሳይሆን ከደሊላ በዝሙት የመውደቅ መንፈስ አእምሮውን አሳጥቶት ነበር፡፡ /መሳ.16፡17/ ይህች ሴት ቃሏን አጣፍጣ የዚህን የተመረጠ ሰው ሕይወት እንዳጠመደችው ዛሬም የብዙዎቹን ሕይወት በዝሙት የሚያጠምዱ እርኩስ መንፈስ ያደረባቸው መራራ ሥር የበቀለባቸው እንዳሉ ማስተዋል ይገባል፡፡
ከክብራችን እንዳንዋረድ የቅዱሳን አባቶቻችንን ፈለግ በመከተል ሥጋችንን ለነፍሳችን አስገዝተን መኖር ያስፈልጋል፡፡ ዓይኖቻችን ወደ ቅዱስ ሥጋውና ወደ ቅዱስ ደሙ የሚመለከቱ መሆን አለባቸው፡፡ «ልጄ ሆይ ወደ ጋለሞታ ሴት ልብህ አይባዝን በጐዳናዋ አትሳት፡፡ ወግታ የጣለቻቸው ብዙ ናቸውና፡፡» /ምሳ.7፡24/ በዝሙት ተወግተው ከወደቁት ወገኖች እንዳንደመር በየትኛውም ቦታ ጥንቃቄ ልናደርግ ያስፈልጋል፡፡

2.ትዕቢት

ሳጥናኤልን ያህል ታላቅ መልአክ ከክብሩ ያዋረደው ሌላው መራራ ሥር ትዕቢት ነው፡፡ ትዕቢት በመራራ ሥር የተመሰለውም ከኔ በላይ ማን አለ በማለት የማይገባውን ይገባኛል እያሰኘ ሌላውን የመናቅ፤ ራስን ከፍ ከፍ የማድረግ መራራ መንፈስ ስለሚያበቅል ነው፡፡ «አንተ የንጋት ልጅ አጥቢያ ኮከብ ሆይ አንተ ወደ ሰማይ ዐርጋለሁ፣ ዙፋኔንም ከሰማይ ከዋክብት በላይ ከፍ ከፍ አደርጋለሁ አልህ፡፡ ነገር ግን ወደ ሲኦል ወደ ጉድጓድም ጥልቅ ትወርዳለህ፡፡» /ኢሳ.14፡12-16/ ብሎ የተናገረለት ሳጥናኤል በትዕቢቱ ምክንያት ነው፡፡ «ትዕቢተኛ የሆነውና ልቡ የሚሳሳው ከእኔ ጋር አይተባበርም፡፡» /መዝ.3፡5/ ተብሎ የተነገረውን የእግዚአብሔርን ቃል ልናስብ ይገባል፡፡
ይሁን እንጂ ትናንት በቅድስት ቤተ ክርስቲያን እቅፍ ቅዱስ ሥጋውንና ቅዱስ ደሙን እየበላና እየጠጣ አድጎ በትዕቢት ምክንያት የበላበትን ወጭት ሰባሪ የሆነ ብዙ ነው፡፡ ክርስቲያን ነኝ እያለ በሀብቱ በጉልበቱ በእውቀቱ፣ በወገኑ የሚኩራራና የሚታበይም አለ፡፡ ይሁን እንጂ ሀብታሙ በደሃው ላይ፣ የተማረው ባልተማረው ላይ አሠሪ በሠራተኛው ላይ የሚታበይ ከሆነ ክርስቲያን ነው ሊባል ከቶ አይችልም፡፡ እውነተኛ የእግዚአብሔር ልጆች መገለጫ፤ ያለው የሌለውን መርዳት፣ የተማረውም ላልተማረው ደሃ ተበደለ ፍርድ ተጓደለ ማለት፣ ስለ ፍቅረ እግዚአብሔር ሲባል ራስን ዝቅ ማድረግ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን የማገልገል ጸጋ ቢሰጠንም በቸርነቱ መሆኑን ማወቅ ይኖርብናል እንጂ ልንታበይ አይገባም፡፡ በሰንበት ትምህርት ቤት፣ በሰበካ ጉባኤ፣ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የምናገለግል ሁሉ የምናቀርበው የአገልግሎት መስዋዕት በእግዚአብሔር ቸርነት መሆኑን ልንገነዘብ ይገባል፡፡ ልክ «… የታዘዛችሁትን ሁሉ ባደረጋችሁ ጊዜ የማንጠቅም ባሪያዎች ነን ልናደርገው የሚገባንን አድርገናል በሉ፡፡» እንደተባለ፡፡ /ሉቃ.17፡1ዐ/
ስለዚህ ፈሪሃ እግዚአብሔር ሊኖረን እንጂ ልንታበይ አይገባም፡፡ «እግዚአብሔርን መፍራት ባለጠግነት ክብር ሕይወትም ነው፡፡» /ምሳ.22፡4/ እንዳለ ጠቢቡ በምሳሌው፡፡

3. ማስመሰል

መመሳሰልና መስሎ መታየት፣ ለመመሳሰል መጣር የብዙዎች ችግር ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አንዳች ፍሬ ባገኝባት ብሎ ወደ አንዲት ዛፍ ሲጠጋ ፍሬ ያፈራች መስላ እንጂ አፍርታ ባለመገኘቷ ምክንያት ለዘላለሙ ፍሬ አይገኝብሽ ብሎ ረገማት፤ ወዲያውም ደረቀች፡፡ /ማቴ.21፡18/  ከዚህ ኀይለ ቃልም የምንረዳው በመስሎ መኖርና ሆኖ አለመገኘት የሚያመጣውን ርግማን ነው፡፡ ማስመሰል መራራ ሥር ነውና ሊነቀል ይገባዋል፡፡ ዛሬም ብዙ ሰው በአፉ የሃይማኖት ሰው ይመስላል፣ እውነታው ግን እንዲህ አይደለም፡፡ ብዙዎች ቤተ ክርስቲያን የሚሔዱ ጾም የሚጾሙ፣ ነገር ግን ከኃጢያት ያልተለዩ፣ በንስሐ መመለስን ችላ የሚሉ፣ ታቦት ሲነግሥ እልል ስለተባለ ብቻ እልል የሚሉ ከዚያ ሲወጡ ግን ኃጢአት ለመሥራት የሚጣደፉና በልባቸው የሸፈቱ ሰዎች የማስመሰሉን መራራ ሥር ከውስጣቸው በንስሐ ነቅለው መጣል አለባቸው፡፡ ሆኖ መገኘት እንጂ መስሎ መታየት አያድንምና፡፡ «ይህ ሕዝብ በከንፈሩ ያከብረኛል፣ ልቡ ግን ከኔ በጣም የራቀ ነው፡፡ የሰውም ሥርዓት የሆነ ትምህርት እያስተማሩ በከንቱ ያመልኩኛል፡፡» /ኢሳ.29፡13፣ ማቴ.5፡8/ እንደተባለው ዛሬም የብዙ ሰው አምልኮ የዚህ ትንቢት መፈጸሚያ ይመስላል፡፡ ስለዚህ ጥዋት ቤተ ክርስቲያን፤ ከሰዓት ቤተ ጣኦት በመሔድ ጊዜን በከንቱ ከማሳለፍ መቆጠብ ያሻል፡፡ ክርስቲያን ነኝ እያለ ጨሌውን፣ የዐውደ ነገሥቱን ጥንቆላ ማመን፣ መናፍስትን መጥራትና የመሳሰሉትን እየፈጸሙ መገኘት በልብ መሸፈት ነውና ልንመለስ ይገባል፡፡ «በሰማያት ያለው የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ እንጂ ጌታ ሆይ፤ ጌታ ሆይ፤ የሚሉኝ መንግሥተ ሰማያት የሚገቡ አይደሉም፡፡» /ማቴ.7፡21/ ተብሏልና፡፡
መስለው ለመኖር የሞከሩ ብዙ ሰዎች ሲጎዱ እንጂ ሲጠቀሙ አላየንም፡፡ ግያዝ ከኤልሳዕ ጋር መስሎ ሲኖር ልቡ ግን ወደ ገንዘብ ሸፍቶ ስለነበር በለምጽ ተመታ፡፡ /2ኛ ነገ.5፡2ዐ/ የይሁዳንም ታሪክ ስንመለከት ከሐዋርያት ጋር ተመሳስሎ እየኖረ ልቡናው በፍቅረ ንዋይ ተነድፎ እንደነበር ነው፡፡ እናም እነዚህንና የመሳሰሉትን የፍቅረ ንዋይ፣ የስስት፣ የእምነት ጎደሎነት ወዘተ መራራ ሥሮች በቶሎ በንስሐ መነቃቀል ያስፈልጋል፡፡
ካህኑም፣ ዲያቆኑም፣ ሰባኪውም፣ ዘማሪውም በአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ነኝ የሚል ሁሉም አገልግሎቱ ዋጋ የሚያገኘው ከእግዚአብሔር መሆኑን ከልብ በማጤንና ራሱን በመመርመር የጐደለውን ሊያስተካክል ይገባል፡፡ እያንዳንዷ ሥራችን የምትበጠርበት ጊዜ ይመጣልና፡፡ «መጻሕፍትም ተከፈቱ፤ ሌላ መጽሐፍም ተከፈተ፣ እርሱም የሕይወት መጽሐፍ ነው፡፡ ሙታንም በመጻሕፍት ተጽፎ እንደነበረ እንደሥራቸው መጠን ተከፈሉ፡፡ … እያንዳንዱ እንደሥራው መጠን ተከፈለ፡፡» እንዲል፡፡ /ራእ.2ዐ፡12/
ስለዚህ መልካም ዋጋ ለማግኘት መልካም ሥራ ለመሥራት መጣር ይገባል፡፡ «አምላካችሁ እግዚአብሔርን ተከተሉ እርሱንም ፍሩ ትእዛዙንም ጠብቁ ቃሉንም ስሙ እርሱንም አምልኩ ከእርሱም ጋር ተጣበቁ» /ዘዳ.13፡4/ ስለተባልን ለመልካም ሥራ እሺ እንድንል ያስፈልጋል፡፡ «እሺ ብትሉ፣ ለእኔም ብትታዘዙ፣ የምድርን በረከት ትበላላችሁ፤ እምቢ ብትሉ ግን ብታምጹ ሰይፍ ይበላችኋል፤ የእግዚአብሔር አፍ ይህንን ተናግሯል» ተብሏልና፡፡ /ኢሳ.1፡19/

4. ዓላማ ቢስነት

ዓላማ የሌለው ሰው ከየት ተነሥቶ ወዴት መሔድ እንዳለበት የማያውቅ፣ ካሰበበት የማይደርስ ነው፡፡ ማንም ወደነዳው የሚነዳ፣ በጭፍን የሚጓዝ ሰው ዓላማ ቢስ ሊባል ይችላል፡፡ ዓላማ የሌለው ሰው በጀመረውና በተሠማራበት ተግባር ላይ ጸንቶ አይቆይም፡፡ በተለይ ክርስቲያን ዓላማ ከሌለው በትንሽ ነገር የሚፈተን፣ ሥጋዊ ፍላጐቱ ካልተሟላለት የማያገለግል፣ የሚያማርር፣ በሆነ ባልሆነው የሚያኰርፍ፣ መንፈሳዊነትን ያዝ፣ ለቀቅ የሚያደርግ የጸሎቱ፣ የጾሙ ዋጋ ዛሬውኑ እንዲከፈለው የሚፈልግ ይሆናል፡፡ የሚያገለግልበትንም ዓላማ ያልተገነዘበ ሰው በየደቂቃው እንዲመሰገን ይፈልጋል፡፡ ሰዎች ዓላማቸውን እንዲስቱ በልባቸው ውስጥ የማዘናጋትን ተግባር የሚፈጽም ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስ ስለሆነ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል፡፡ ቅዱሳን አባቶች በተለያዩ ፈተናዎች ውስጥ ቢያልፉም ዓላማን የመሳት መራራ ሥር በውስጣቸው አልበቀለም፡፡ በሁሉም ጸንተው በመቆማቸው ለክብር አክሊል በቅተዋል፡፡
ሙሴ እስራኤልን በምድረ በዳ ይመራ በነበረበት ወቅት የተለያዩ ፈተናዎች ቢያጋጥሙትም ከዓላማው አልተዘናጋም፡፡ ይልቁንም ያህዌህ ንሲ /እግዚአብሔር ዓላማዬ ነው አለ እንጂ፡፡ /ዘዳ. 12፡15/
ዮሴፍ ጽኑ ዓላማ ስለነበረው የተዘጋጀለትን የዝሙት ግብዣ እምቢ አለ፡፡ /ዘፍ. 39/
ሶስና ልትሸከመው የማትችል የሚመስል ፈተና ቢያጋጥማት ንጽሕናዋን ክብሯን ጠብቃ፣ ለአምላኳ ታምና መኖርን ዓላማዋ ስላደረገች የመጣባትን ፈተና በጽናት፣ በታማኝነት፣ በንጽሕና በቅድስና ልታልፍ ችላለች፡፡ /መጽሐፈ ሶስና/  ኢዮብ ዓላማው እግዚአብሔር ስለነበር ይፈራረቅበት የነበረውን መከራ፣ ሥቃይና ችግር ሊያልፍ ችሏል፡፡ ወርቅ በእሳት እንደሚፈተን ሁሉ ተፈትኖ፣ ነጥሮ ታላቅነቱን አስመስክሯል፡፡ /ኢዮ.2፡10/ በአንጻሩ ደግሞ ዓላማቸውን የሚያስት መራራ ሥር በውስጣቸው በመብቀሉ ምክንያት የተጐዱ ከክብራቸው ያነሡ ጥቂቶች አይደሉም፡፡
ለምሳሌ ሳኦልን ብንመለከት እግዚአብሔር አምላክ ከሕዝበ እስራኤል ላይ ንጉሥ እንዲሆን ቢሾመውም የቅንዓት መንፈስ በውስጡ ስለበቀለ እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ተግባር ሲሠራ እናያለን፡፡ /1ኛሳሙ. 11፡9፣15፡35/
ዛሬም ትናንት የቤተ ክርስቲያን ልጆች የነበርን፣ እግዚአብሔር ከፍ ስላደረገን፣ ስለሾመን ዓላማችንን የዘነጋን አንታጣምና ራሳችንን ልንመረምር ይገባል፡፡ ከዓላማችን እንድንስት የሚያዘናጉ ነገሮች በርካቶች ናቸው፡፡ ሰው ለገንዘብ፣ ለሥልጣን፣ ለሓላፊ ጠፊ ሀብት ብሎ ዓላማውን ይስታል፡፡ ይሁዳ ምንም እንኳን ከሐዋርያት አንዱ ሆኖ ቢቆጠርም ዓላማው መንግሥተ ሰማያትን መውረስ ሳይሆን ገንዘብን ማሳደድ ስለነበረ አምላኩን እስከ መሸጥ ደረሰ፡፡ «እንጀራዬን የበላ በእኔ ላይ ተረከዙን አነሣ፡፡» ተብሎ የተነገረው ትንቢት ተፈጸመበት፡፡ /መዝ.4ዐ፡9/ ይሄው ዛሬ የነፍሰ ገዳዮችና የክፉዎች ተምሳሌት ሆኖ ይነገራል፡፡ ስለዚህ «ከመልካም ሽቱ መልካም ስም ይሻላል፡፡» እንደተባለ ስማችን በክፉ እንዳይጠራ በዓላማችን እንጽና፡፡ /መክ. 7፡1/ ዓላማችን መንግሥቱን ለመውረስ፣ ስሙን ለመቀደስ ይሁን፡፡ እንደ ዴማስ ወደ ዓለም የሚመለስ መራራ ሐሳብ በውስጣችን እንዳይበቅል ጥንቃቄ እናድርግ፡፡ /2ኛጢሞ. 4፡9/

5. የጥርጥር መንፈስ

«የሚጠራጠር ሰው በነፋስ የተገፋና የተነቃነቀ የባህርን ማዕበል ይመስላል፡፡ ሁለት ሐሳብ ላለው፣ በመንገድም ሁሉ ለሚወላውል ለዚያ ሰው ከጌታ ዘንድ አንዳች የሚያገኝ አይምስለው፡፡» /ያዕ. 1፡6/ በማለት እንደተነገረው ተጠራጣሪ ሰው ከጌታ አንዳች ነገር አያገኝም፡፡ በአሁኑ ወቅት ከጽናታችን እንድንናወጥ የሚያደርጉ ብዙ ነገሮች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ነገር ግን የተጠራበትን ዓላማ ጠንቅቆ የማያውቅ ክርስቲያን በጥርጥር ነፋስ ተነቅሎ ይገነደሳል፡፡ ስለዚህ ጊዜው ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚሻው በመሆኑ በማስተዋል መራመድ ያስፈልጋል፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት በመንፈስ ቅዱስ ገላጭነት ይመጣ ዘንድ ስላለው ክህደትና ሐሳዊ መሲህ «… የሚፈጥንን ጥፋት በራሳቸው ላይ እየተሳቡ የሚያጠፉ ኑፋቄን አሾልከው ያገባሉ፤ … በእነርሱም ጠንቅ የእውነት መንገድ ይሰደባል፡፡» /2ጴጥ.2፡1/ በማለት ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም የክርስቶስን አምላክነት የሚጠራጠርና የሚያጠራጥር፣ በቅዱሳን ላይ አፉን የሚከፍት ሐሳዊ መሲህ ቢነሣ የሚያስደንቅ መሆን የለበትም፡፡ ለምን ቢሉ ትንቢቱ ይፈጸም ዘንድ ግድ ነውና፡፡ ዮሐንስም ስለዚህ ነገር «አውሬው ታላቅ ነገርና ስድብን የሚናገርበት አፍ ተሰጠው … እግዚአብሔርንም ለመሳደብ ስሙንና ማደሪያውንም፣ በሰማይም የሚያድሩትን ሊሳደብ አፉን ከፈተ፡፡» ብሎ ጽፏል፡፡ /ራእ.13/ ስለዚህ በልባችን የሚበቅለውን የጥርጥር መንፈስ ከውስጣችን ነቅለን ልንጥል ያስፈልጋል፡፡ «ከራሳችሁ ጽናት እንዳትወድቁ ተጠንቀቁ፡፡ /2ጴጥ.3፡17/ እንደተባልነው ጥንቃቄ ልናደርግ ያስፈልጋል፡፡
በአጠቃላይ መራራ ሥር ኃጢአትና ክርስቲያናዊ ምግባር በአንድ ሰውነት ላይ ሊበቅሉ የማይገባቸው እንክርዳድና ፍሬ ናቸው፡፡ በመሆኑም በንስሐ መከር መለየት ይኖርብናል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም የመራራ ሥራ ፍሬዎችን የሥጋ ሥራ በማለት ገልጿቸዋል፡፡ «አስቀድሜ እንዳልኩ እንደዚህ ያሉትን የሚያደርጉ የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም ብሏል፡፡ ገላ. 5፡21» ስለዚህ ክርስቲያናዊ ሕይወት እንዲያብብ የክፋት ሥራ የሆኑ ኃጢአቶችን በንስሐ እና በተጋድሎ በተለይም ዝሙት፣ ትዕቢት፣ ማስመሰል፣ ዓላማ ቢስነትና የጥርጥር መንፈስ የመሰሉ መራራ ስሮች በጥንቃቄ መንቀልና ማራቅ ያስፈልገናል፡፡ መራራ ሥሮችን ነቅለን የመንፈስ ፍሬያትን በሰውነታችን እናበቅል ዘንድ የእግዚአብሔር ቸርነት የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

መስቀል ለእኛ ለኦርቶዶክሳውያን

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

መስከረም 28/2004 ዓ.ም.

ምን አልባት አንድ ሰው የእውነትን እውቀት ቢያስተምር በእውቀቱ ለመማረክ ከጠቢቡ ይልቅ አላዋቂው በጣም የቀረበ ነው፡፡ እርሱንም ወደዚህ እውቀት ለማምጣት ከጠቢቡ ይልቅ አላዋቂው በጣም ይቀላል፡፡ ይህን እውቀት እረኞችና ባላገሮች ፈጥነው ለመቀበል የበቁት እውቀት ነው፡፡ እነርሱ ለሁልጊዜውም አንዳች ጥርጣሬ በልቡናቸው ሳያሳድሩ እውቀቱን እንደ ጌታ ቃል አድርገው ተቀብለውታል፡፡ በዚህ መልክ ጌታችን የአሕዛብን ማስተዋልና ጥበብ አጠፋው፡፡ ይቺ የአሕዛብ ማስተዋልና ጥበብ አስቀድማ ራሱዋን አዋርዳለችና ለዘለዓለም ለምንም የማትጠቅምና የማትረባ አደረጋት፡፡ ይቺ ማስተዋልና ጥበብ ምንም እንኳ የእርሱዋን አቅምና ችሎታ በጌታችን ሥራ ላይ ለመግለጥ ብትሞክርም አልሆነላትም፡፡ ስለዚህም አሁን ራሱዋን ለማላቅ አልተቻላትም፡፡ ምክንያቱም በክርስቶስ የተገለጠው እውቀት እርሱዋን የሚሻ አይደለምና፡፡ ይህ አዲስ የተገለጠው እግዚአብሔርን የማወቅ መንገድ ከእርሱዋ በእጅጉ የላቀ ነው፡፡ እንዲህ ከሆነ ወደ ዚህ ወደ እግዚአብሔር የእውቀት ከፍታ ለመምጣት እምነትና የዋሃት ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡ እነዚህ ከውጭ በትምህርት ከምናገኛቸው ይልቅ ሊኖሩን የሚገቡ መንፈሳዊ ሀብታት ናቸው፡፡ ምክንያቱም “እግዚአብሔር የዚችን ዓለም ጥበብ ሞኝነት እድርጎአታል ብሎናልና፡፡

ነገር ግን “እግዚአብሔር የዚችን ዓለም ጥበብ ሞኝነት እንዲሆን አድርጐታል” ሲል ምን ማለቱ ነው? ምክንያቱም ሞኝነትን በእምነት ካለመቀበል ጋር አቆራኝቶ ነውና ያስተማረው፡፡ የዚህ ዓለም ጥበበኞች የሚባሉት በዚህ እውቀታቸው አብዝተው የሚመኩ ቢሆንም ጌታችን ግን እነርሱን ለመጋፈጥ ጊዜውን አላጠፋም ነበር፡፡ መልካም የሆነውን ነገር ፈጽማ ለይታ ማወቅ የተሳናት ይህች ጥበብ ምን ዓይነት ጥበብ ናት? ስለዚህ አስቀድማ የእርሱዋ ጥበብ የማይጠቅምና የማይረባ መሆኑን ከተረዳች በኋላ ጌታችን ደግሞ ሞኝነት እንደሆነ ገለጠው፡፡ ይህች ሰዋዊት ጥበብና ማስተዋል የእግዚአብሔርን ሕልውና በእውቀቱዋ ተደግፋ ማረጋገጥ አልተቻላትም፤ እንዴት ታዲያ ከዚህ በእጅጉ የሚልቀውንና የሚሰፋውን የእግዚአብሔርን ሥራ መረዳትና ማስረዳት ይቻላታል? ስለዚህም ከዚህ እንደምንረዳው የእግዚአብሔርን ጥበብ ለመረዳት የግድ እምነት እንጂ ብዙ ምርምርና ድካም አለማስፈለጉን ነው፡፡ በዚህ መልክ እግዚአብሔር አምላክ የዓለምን ጥበብ ሞኝነት እንዳደረጋት ማስተዋል እንችላለን፡፡

 

እርሱ በወንጌል ሞኝነት ዓለሙን ለማዳን ወድዶአል፡፡ ነገር ግን ሞኝነት ሲል በአላዋቂነት ማለቱ ግን አይደለም በወንጌል ሞኝነት ሲል በሰው ዘንድ እንደ ሞኝነት በሚቆጠር መልኩ ሲለን ነው፡፡ በእርሱ የተገለጠችው ጥበብ ታላቅ የሆነች ጥበብ ናት፤ ነገር ግን ለዓለሙ የገለጠባት መንገድ ግን ሞኝነት ይመስላል፡፡ ከእግዚአብሔር ሞኝነት የሚልቅ ጥበብ ፈጽሞ የለም፡፡ ከዓለሙም ሲያስተዋውቃት ሞኝነት በሚመስል መንገድ ነበር፡፡ ይህችን ጥበብ ወደ ዓለም ሲያገባት ለምሳሌ ልክ እንደ አፍላጠን አሪስጣ ጣሊስ፣ ሶቅራጠስ በፍልስፍና በተካኑት ወገኖች በኩል አልነበረም ፡፡ ነገር ግን በተናቁ ዓሣ አጥማጆች በኩል ነው እንጂ፡፡ እንዲህ ስለሆነም ድሉ እጅግ ታላቅና አንጸባራቂ ሆነ፡፡

ሐዋርያው በመቀጠል ስለመስቀሉ ኃይል ሲገልጽ “መቼም አይሁድ ምልክትን ይለምናሉ፣ የግሪክ ሰዎችም ጥበብን ይሻሉ፣ እኛ ግን የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን ይህም ለአይሁድ ማሰናከያ፣ ለአሕዛብም ሞኝነት ነው፤ የተጠሩት ግን አይሁድ ቢሆኑ የግሪክ ሰዎች ቢሆኑ የእግዚአብሔር ኃይልና የእግዚአብሔር ጥበብ የሆነው ክርስቶስ ነው፡፡” (ቁ.፳፪-፳፬) አለ፡፡

ለዚህ ኃይለ ቃል ሰፊ ትንታኔን መስጠት ይቻላል፡፡በዚህ ቦታ ሐዋርያው ሊገልጠው የፈለገው ነገር እንዴት እግዚአብሔር አምላክ ሰው ከሚያስበው በተቃራኒው መንገድ ሞትን ድል እንደነሣውና ወንጌል ከእግዚአብሔር ዘንድ የተሰጠች ስለመሆኑዋ ነው፡፡ ስለዚህ ሲናገር ምን አለ?፡- አይሁድን በክርስቶስ እመኑ ስላቸው እነርሱ ደግሞ የሞተውን አስነሡትና በአጋንንት ቁራኛ የተያዘውን ፈውሱትና አሳዩን እነዚህን ምልክቶችን ብታሳዩን በእርሱ እናምናለን፡፡ እኛ ግን በምላሹ ስንመልስላቸው እኛስ “የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብክላችኋለን” እንላቸዋለን፡፡ እንዲህ ዓይነት ቃላችን ፈቃዱ የሌላቸው ትእቢተኞችን ብቻ አይደለም የሚያሸሻቸው፣ ነገር ግን በእርሱ ለማመን ፈቃዱ ያላቸው አይሁድ እንኳ የሚያስበረግግ ቃል ነው፡፡ እንዲህ ሲባል ቃሉ ያን ያህል የሚያስበረግግ ቃል ሆኖ ግን አይደለም፡፡ ይልቁኑ የጠፉትን ወደ እርሱ የሚያቀርብና ለእግዚአብሔር ምርኮን የሚያመጣና ድል የሚነሣ ቃል ነበር፡፡

 

አሕዛብ ደግሞ ቃሉን በንግግር ጥበብ አሳምረን በፍልስፍና መንገድ እንድናቀርብላቸው ይሻሉ፡፡ እነርሱ እንዲህ እንዲቀርብላቸው ቢወዱም እኛ ግን ስለ መስቀሉ እንሰብክላቸዋለን፡፡ ስለዚህም በአይሁድ ዘንድ እንደ ደካሞች ተደርገን እንደተቆጠርን እንዲሁ በእነዚህም ዘንድ እንደሞኞች እንቆጠራለን፡፡ እኛን ከመስማት የሚመለሱት እነርሱ በጠየቁን መልክ ባለማቅረባችን ብቻ ግን አይለደም፤ እኛን ከመስማት የሚመለሱት፣ ነገር ግን እነርሱ ከጠየቁን በተቃራኒው አድርገን በማቅረባችንም ጭምር ነው እንጂ፡፡ ለእነርሱ ለእኛ የመዳን ምልክታችን መስቀል ስለመሆኑ በምክንያት አለመግለጻችን ብቻ አይደለም እኛን ከመስማት እንዲመለሱ የሚያደርጋቸው ነገር መስቀሉ ለእነርሱ የደካማነት ምልክት እንጂ የኃያልነት ምልክት አለመሆኑም ጭምር እንጂ፡፡ በእነርሱ ዘንድ ይህ ጥበብ ሳይሆን ሞኝነትን የሚያሳይ ተደርጎ ነው የሚቆጠረው፡፡

ስለዚህም እነርሱ ኃይልን የሚሰጣቸውን ምልክትንና ጥበብ ሲሹ የጠየቁትን አለማግኘታቸው ብቻ ሳይሆን እነርሱ ከሚመኙት ምልክት በተቃራኒ በማቅረባችንና ክርስቶስን እንዲከተሉት በመስበካችንም ይሰነካከላሉ፡፡ እንዴት ታዲያ እኛ የምንሰብከው የመስቀሉ ኃይል ከመረዳት ያለፈ አይሆን? አንድ በመከራ ውስጥ ላለና ከስቃዩ ለማረፍ መጠጊያ ለሚፈልግ ሰው እኛ እጅግ አደገኛ ወደሆነው የባሕር ማዕበል ውስጥ እርሱን የምንመራውና በዚያ ውስጥ የምናድነው መሆናችንን የገለጽንለት ብንሆን እንዴት እኛን አምኖን ደስ ብሎት ሊከተለን ይችላል? ወይም አንድ ሐኪም የታመመነውን ቁስለኛ ሰው ሕማሙን በመድኃኒት ሳይሆን ቁስሉን ራሱን ደግሞ በማቃጠል እንደሚያድነው እየማለ ቢነግረው እንዴት ሊቀበለው ይችላል? ይህ በእርግጥ ልዩ የሆነ ኃይል ነው፡፡ ስለዚህም ክርስቶስ ሐዋርያትን ወደ ዓለም ሁሉ ሲልካቸው ያለ ምልክት አልሰደዳቸውም፡፡ ነገር ግን ከሚታወቁት ምልክቶች በተቃራኒው የሆኑ ምልክቶችን ያደርጉ ዘንድ ነበር ሥልጣንን የሰጣቸው ፡፡

 

በሥጋው ወራት ጌታችን እንዲህ ዓይነት ከተፈጥሮአዊ ሥርዓት በወጣ መልኩ ምልክቶችን ያደርግ ነበር፡፡ ለምሳሌ ሲወለድ ጀምሮ ዐይነ ስውር በነበረው ላይ ኃይሉን በመፈጸም አሳይቶናል፡፡ የዚህን ሰው የታወሩትን ዐይኖች ጌታችን ሲፈውሳቸው ዐይነ ስውርነትን በሚያባብስ ጭቃ ቀብቶ ነበር፡፡ (ዮሐ.9፥6) በጭቃው ጌታችን ይህን እውር የሆነው ሰው እንደፈወሰው እንዲሁ በመስቀሉ ዓለሙን ወደ እርሱ አቀረበው፡፡ ተቃዋሚዎችን ድል መንሣት የማይቻለውን ኃይልን በማስታጠቅ ድል የሚነሣ አደረገው፡፡

እንዲህ ዐይነትን ተግባር በሥነፍጥረትም ላይ ፈጽሞት እናገኘዋለን፡፡ ፍጥረታትን ሲፈጥራቸው እነርሱኑ መልሶ በሚያጠፋ ነገር ነው ፈጥሮአቸው የምናገኘው፡፡ ለምሳሌ የባሕር ማዕበልን በአሸዋ በመገደብ ለኃይለኛው ማዕበል ደካማ የሆነው አሸዋ ይጠብቀው ዘንድ መሾሙን እናስተውላለን፡፡ ምድርን በውኃ ላይ አጸናት፡፡ ውኃን እጅግ ስስና ቀላል በሆነ ደመና እንዲቁዋጠር አደረገው፡፡ በነቢያትም በኩል በአነስተኛ የእንጨት ቅርፊት ከውኃ ውስጥ ዘቅጦ የነበረውን ብረት አወጣ፡፡ (2ነገሥ.6፥ 5-7) እንዲሁ በመስቀሉ ዓለሙን ወደ እርሱ አቀረበ፡፡ ታላቅ ስለሆነው ኃይልና ጥበብ አታስተውሉምን? እነሆ ከእኛ መረዳት በተቃራኒው በሆነ ኃይል እኛን ወደ እምነት ሲያቀርበን አትመለከቱምን? እንዲሁ መስቀልም ደካማ ሊመስለን ይችላል፤ ነገር ግን በእጅጉ ብርቱ መሆኑ ብቻ ሳይሆን ሰዎችን ወደራሱ የሚስብ ኃይል በላዩ እንዳደረበት ማስተዋል እንችላለን፡፡

ስለዚህ ቅዱስ ጳውሎስ እነዚህን ሁሉ በአእምሮ ውስጥ ሲያመላልሳቸው ቆይቶ በመደነቅና በመገረም “ከሰው ይልቅ የእግዚአብሔር ሞኝነት ይጠበባልና የእግዚአብሔርም ድካም ከሰው ይልቅ ይበረታል”(ቁጥ.፳፭) አለ፡፡ ከመስቀሉ አንጻር ሞኝነትናና ደካማነትን አስቀመጠ ነገር ግን አማናዊ የሆነውን ሞኝነትንና ደካማነት ሳይሆን የሚመስለውን ነገር ነበር የገለጠልን፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ ስለመስቀሉ ኃይል ሲሰብክ በተቃራኒ ጎራ ያሉትን ወገኖች አመለካከታቸውን ሳይጎዳ ነበር የሰበከው፡፡ ፈላስፎች በምክንያት ይህን ኃይል መረዳት እንደማይችሉ ነገር ግን በእነርሱ ዘንድ ሞኝነት የሚመስለው የመስቀሉ ነገር ታላቅ የሆነ ኃይል ያለው መሆኑን ነበር ያስገነዘባቸው፡፡ ስለዚህ ብዙ ወይም ጥቂት ወይም አንድ ተከታይ ያለው ጠቢብ ሰው የት አለ? ፕላቶና ተከታዮቹ እንዴት ያለ አድካሚ በሆነ መንገድ ጥበብን ማግኘት ሻቱ! እነርሱ ለእኛ ስለ መስመር፣ ስለማዕዘን(angle)፣ ስለ ነጥቦች፣ ስለቁጥሮች፣ ተመጣጣኝ ስለሆኑትና ስላልሆኑት ሒሳባዊ ቀመሮች ልክ እንደ ሸረሪት ድር እያወሳሰቡ አስተምረውን ነበር፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ግን እነዚህ ድሮች በዚህ ምድር ስንኖር አያስፈልጉንም ማለታችን ግን አይደለም ሆኖም ከዚህ ከሚልቀው ጋር ሲተያዩ እምብዛም አስፈላጊዎች አይሆኑም፡፡ ፈላስፋው ፕሉቶ ነፍስ ሕያዊት እንደሆነች ለማስረዳት እንዴት ደከመ! ሲወጣም ሲገባም ስለነፍስ ሕያዊነት ትንታኔ ለመስጠት ሞከረ ነገር ግን ስለነፍስ እርግጠኛውን ነገር ለማስተማር አልበቃም፡፡ ይባስ ብሎ በዚህ ጉዳይ ሰሚ አጣ፡፡

ነገር ግን መስቀል ባልተማሩት ሐዋርያት በኩል ብዙ ሰዎችን ወደ እርሱ አቀረበ፡፡ ዓለሙ ሁሉ ተገልብጦ ክርስቶስን ወደ መከተል ተመለሰ፡፡ የተለመዱትን ብቻ አልነበረም ሲያስተምሩ የነበሩት ነገር ግን ስለእግዚአብሔር፣ እውነተኛ ስለሆኑት አንድ ክርስቲያን ሊላበሳቸው ስለሚገቡ መልካም ምግባራት እንዲሁም በወንጌል ሕይወት እንዴት መመላለስ እንዲገባን በተጨማሪም ስለዓለም ምጽአት በሰፊው ሰብከዋል፡፡ በትህምርታቸውም የተከተሏቸውን ሁሉ ፈላስፎች አደረጉዋቸው፤ ያልተማሩትንም በጥበብ ቃል የሚያስተምሩ መምህራን አደረጓቸው፡፡ ወዳጄ ሆይ ከሰው ይልቅ የእግዚአብሔር ሞኝነት እንዴት እንደሚልቅ ተመልከት፡፡ ምክንያቱም በዚህ ታላቅ በሆነ በመስቀሉ በተገለጠው ኃይል ዓለሙ ሁሉ ድል ተነሣ፤ ብዙዎች የተሰቀለውን ክርስቶስን እየሰበኩ ብዙዎችን ለእርሱ ማረኩ፡፡ እነዚህ እየሰፉና ዓለምን እየከደኑዋት ሲመጡ በተቃራኒ ጎራ ያሉ ወገኖች ግን እየጫጩና እየጠፉ ሄዱ፡፡ ሕያው የሆነው ቃሉ ከሙታን ጋር ውጊያን ገጠመ ድል ነሣቸውም፡፡

ስለዚህም አንድ ፈላስፋ እኔን ሞኝ ሲል የእርሱን እጅግ የበዛውን ሞኝነቱን ይመለከታል፡፡ ምንም እንኳ እኔ በእርሱ አንደበት ሞኝ ብባልም መረጃዎች ግን የሚያሳዩት እኔ ከእርሱ ይልቅ ጠቢብ መሆኔን ነው፡፡ እርሱ እኔን ደካማ ቢል እንዲህ ባለበት ንግግሩ የእርሱን ደካማነት ይረዳል፡፡ ከዓሣ ማጥመድ የመጡት ሐዋርያት በእግዚአብሔር ጸጋ ለመፈጸም የተቻላቸውን ከአሕዛብ ፈላስፎች፣ ንግግር አዋቂዎችና፣ ገዥዎች ወይም በአጭሩ ዓለም ሁሉ ከዚህ ወደዚያ ብዙ ሺህ ጊዜ ቢታትር በእነርሱ ያደረውን ሀብት በድካማቸው ለማግኘት ቢጥሩ አይደለም ማግኘት ሐዋርያት የስተማሩትን ደግመው መናገር አይቻለውም፡፡ በመስቀሉ ያልተሰበከ ምን ነገር አለ? ስለነፍስ ሕያውነት ፣ ስለሥጋ ትንሣኤ ፣ ስለዚች ዓለም አላፊነት፣ ተስፋ ስለምናደረጋት ሕይወት፣ ሰዎች መላእክነትን ስለመምሰላቸው፣ ራስን ባዶ ስለማድረግ እንዲሁም ሌሎችም ወደ ፍጹምነት የሚያደርሱ አስተምህሮዎች የተላለፉበት በመስቀሉ ነው፡፡….

ከዚህ በላይ እኛ ምን ልንል እንችላለን ? ነገር ግን በተግባር እርስ በእርሳችን ያለንን ድንቅ የሆነ መተሳሳሰብን እናጠንክር ፡፡ የጽድቅም ብርሃን ደምቆ እንዲታይ እናድርግ፡፡ ሐዋርያውም እናንተን ለዓለም የምታበሩ ብርሃናት ናችሁ ይላችኋል(ፊልጵ.፪፥፲፭)፡፡ መንፈሳዊው ተግባር ከዓለማዊው ተግባር እንደመላቁ እግዚአብሔር አምላክ ከፀሐይም ከሰማይም ከውቅያኖስም በላይ ታላቅ ሥራን ለዚህች ምድር እንድንፈጽም ሓላፊነትን ሰጥቶናል፡፡ እኛ በሰማይ ላይ የምታበራውን ፀሐይንና ክበቡዋን አይተን እናደንቃለን፡፡ ይልቁኑ ከእርሱዋ በእጅጉ የሚልቀው ብርሃን በእኛ ውስጥ እንዳለ እናስተውል፡፡ ከዚህም ጎን ለጎን እኛ ይህን ብርሃን ካልሠራንበት የዚህ ብርሃን ተቃራኒ የሆነ ድቅድቅ ጨለማ እንደሚነግሥብንም ልብ እንበል፡፡ ጽኑ የሆነው ጨለማ ዓለምን ሲውጣት ዓለም በጭንቅ ውስጥ ትሆናለች፡፡ በእኛ ውስጥ ድቅድቅ ጨለማ ሰፍኖ ሲገኝ ነፍሳችን በጭንቅ ትያዛለች፡፡ ጨለማው በከሃዲያን ወይም በአሕዛብ ላይ ብቻ ያለ አይደለ ነገር ግን በእኛም መካከል ባሉት ክርስቲያናዊ እውቀቱና ሕይወቱ በሌላቸው ላይ ነግሦም ይታያል፡፡

 

ከመካከላችን አንዳንዶች ትንሣኤውን አይቀበሉም፣ አንዳንዶች ደግሞ በጥንቆላና በኮከብ ቆጣሪዎች የሚታመኑ እነርሱ ባሉዋቸውም የሚመሩ ወገኖች ናቸው፡፡ አንዳንዶች ደግሞ ከክፉ ይጠብቀናል ሲሉና አጋንንትንም እንስብበታለን በማለት አሸን ክታቦችን በአንገታቸው ላይ የሚያንጠለጠሉ ናቸው፡፡

ስለዚህም ጉዳይ ጦምን እንያዝ በውጊያውም ረዳት ሁኑኝ፡፡ በእናንተ ክርስቲያናዊ ምልልስ እነርሱን ወደዚህ ወደተቀደሰ ሕይወት ማምጣት ይቻላልና፡፡ እኔ ሁልጊዜ እንደማስተምረው አንድ ሰው ክርስቲያናዊ ስብዕናን አስመልክቶ ሌሎችን ከማስተማሩ አስቀድሞ ራሱን ሊያስተምር ይገባዋል እላለሁ፡፡ እርሱን የሚሰሙት ከቅድስና ሕይወት ወጥተው እንዳይመላለሱ አርዓያ ሊሆናቸው ይገባል፡፡ በዚህም መልክ በመመላለሰ አሕዛብ ስለእኛ በጎ የሆነ አመለካከት እንዲኖራቸው እናድርግ፡፡ ወንጌልን በሕይወታችን ለእነርሱ በመስበካችን ከእነርሱ የምንቀበለው መከራ ይኖራል ነገር ግን አላፊ ነው፡፡

ይህን በሕፃናት አታስተውሉትምን፡፡ አንዳንዴ ልጆች በአባታቸው እቅፍ ሳሉ በቁጣ የአባታቸውን ጉንጭ በጥፊ ሊመቱት ይችላሉ፤ ነገር ግን አባት ልጁ ቁጣውን በእርሱ ላይ በመግለጡ በልጁ አይቆጣም ይልቅኑስ በእርሱ ዘንድ እጅግ ጣፋጭ ይሆንለታል፡፡ ቁጣው ከልጁ ላይ ባለፈ ጊዜ ደግሞ አባት ይበልጥ ደስ ይለዋል፡፡ እንዲሁ እኛም ለኢአማንያን እናድርግ ልክ ልጅ እንዳለው አባት እንሁን፡፡ ይህን እንደስንቅ ይዘን ለእነርሱ የክርስቶስን ወንጌል እንስበክላቸው፡፡ ሁሉም አሕዛብ በእኛ ዘንድ እንደ ሕፃናት ናቸውና፡፡ እንዲህም እንደሆነ የእነርሱ አንዳንድ ጸሐፍት “ይህ ሕዝብ እንደ ሕፃን ነው ከአሕዛብም አንድም አረጋዊ ሰው የለም” ብለው ቃላችንን ያረጋግጡልናል፡፡ ሕፃናት የሚጠቅማቸውን ነገር ሊለዩ አይችሉም፤ አሕዛብን ሁል ጊዜ እንደ ሕፃናት ጨዋታ ወዳዶች ናቸው፡፡ በአፈር ላይ ይንደባለላሉ በከንቱ ነገር በቀላሉ ይወሰዳሉ ከንቱ በሆነም ነገር በፍቅር ይወድቃሉ፡፡ ለሕፃናት የሚጠቅም ነገርን ስንነግራቸው ጆሮ ሰጥተው አያዳምጡንም ከዚህ ይልቅ እኛ ስንናገር እነርሱ ይስቃሉ፡፡ አሕዛብም እንዲሁ ናቸው፡፡ እኛ ስለመንግሥተ ሰማያት ስንሰብክላቸው እነርሱ ይስቃሉ፡፡ ከሕፃናት አፍ በብዛት የሚወርደው ለሃጭ ምግቡ ላይ ሲያርፍ ምግቡን እንዲያበላሸው እንዲሁ ከአሕዛብ አንደበት የሚወጡ ቃላት ከንቱዎችና የረከሱ ናቸው፡፡

ለሕፃናት የሚስፈልጋቸውን ምግብ እንኳ ብንሰጣቸው ክፉ የሆነ ቃላት ከአንደበታቸው እያወጡ ሊነጫነጩብን ይችላሉ እኛም እነርሱን በመታገሥ እናሳልፋቸዋለን፡፡ ሕፃናት አንድ ሌባ ወደቤታቸው ገብቶ የቤቱ ቁሳቁሶችን እየወሰደ ቢያዩት ዝም ብለው ከመመልከትና እንደ ተባባሪ ወገን ሆነው ሲስቁ ከመገኘት ባለፈ እርሱን አይቃወሙትም፡፡ ነገር ግን እነርሱ ከሚጫወቱበት እቃ አንዱ የተወሰደባቸው እንደሆነ የወሰደባቸው ሰው ለመጉዳት ሲጥሩ ሲያለቅሱና በንዴት መሬቱን ሲጠበጥቡት እናስተውላቸዋለን፡፡ አሕዛብም እንዲሁ ናቸው፡፡ ሰይጣን ነፍሳቸውን የሚጠቅመውን መንፈሳዊ ሀብት ሲዘርፋቸው ከዚህም አልፎ ለሕይወታቸው አስፈላጊ የሆነውን ሲያሳጣቸው እያዩ ይስቃሉ፡፡ እንዳውም ከእርሱ ጋር እንደ ጓደኛ ሲተባበሩት ይገኛሉ፡፡ ነገር ግን አንድ ሰው ከእነርሱ እንደ ሕፃን መጫወቻ የተናቀን እቃን ሲወስድባቸው ቢመለከቱ ልክ እንደ ሕፃን ይጮኻሉ ያነባሉ፡፡ ሕፃናት ራቁታቸውን ስለመሆናቸው እንደማያስተውሉ አሕዛብም እንዲሁ ናቸው፡፡ ስለዚህም ሕጋዊው ተራክቦው እነርሱን ሲያሳፍራቸው ሕገወጡ መዳራት ግን አያሳፍራቸውም፡፡

እናንተ በዚህ ትምህርቴ ልትረኩና ደስታችሁን በእልልታ ልትገልጡልኝ ትችሉ ይሆናል ነገር ግን ከደስታችሁ ጋር በእነርሱ ተግባር ተስባችሁ እንዳትወሰዱ ለራሳችሁ ጥንቃቄን እንድታደርጉ ልመክራችሁ እወዳለሁ፡፡ ስለዚህም አዋቂዎች ትሆኑ ዘንድ እለምናችኋለሁ፡፡ እኛ እንደ እነርሱ ሕፃናት ከሆንን እንዴት አዋቂዎች እንዲሆኑ እነርሱን ማስተማር ይቻለናል? እንዴትስ እነርሱን ሞኝነት ከሆነው ከሕፃናዊ ድርጊታቸው መመለስ እንችላለን? ስለዚህ ተዋዳጆች ሆይ ወደ ክርስቶስ የእውቀቱ ከፍታ እንድንደርስና የመንግሥቱ ወራሾች እንድንሆን እራሳችንን አዋቂዎች እናድርግ፡፡ ሰው እንሁን፡፡ በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየስሱ ክርስቶስ ፍቅርና ርኅራኄ ለእግዚአብሔርና መንፈስ ቅዱስ ክብር ምስጋና ይሁን ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ አሜን፡፡