“አባታችን ሆይ” ክፍል አንድ

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

መግቢያ

አንባቢያን ሆይ ይህ ጽሑፍ የትርጉም ሥራ ሲሆን ትምህርቱም ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የማቴዎስን ወንጌል ሲተረጉም ከጻፈው ላይ የተወሰደ ነው፡፡ የዚህ ቅዱስ አባት ሥራዎች ብዙ ከመሆናቸው የተነሣ ታላቁ ጸሐፊ /The great author/ ተብሎ ነው በሥነ መለኮት ምሁራን የሚታወቀው፡፡ “አባታችን ሆይ” የሚለውን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ያስተማረውን የጸሎት ሥርዐት ይህ ቅዱስ እንዴት አድርጎ ድንቅ በሚባል መልኩ እንደተረጎመው ትመለከቱ ዘንድ እነሆ ብለናል፡፡


ግብዞችን አትምሰሉአቸው

ግን ስትጸልይ ወደ እልፍኝህ ግባና መዝጊያህንም ዘግተህ በሥውር ላለው አባትህ ጸልይ በሥውር የሚያይህ አባትህ በግልጽ ይከፍልሃል፡፡” /ማቴ.6÷1-6/

በዚህ ቦታ ላይ ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስ ጻፎችንና ፈሪሳውያንን ግብዞች ማለቱ አግባብነት ነበረው፡፡ ምክንያቱም ወደ እግዚአብሐር ቤት ለጸሎት በሚመጡበት ጊዜ የሰዎችን ቀልብ ለመሳብ ሲሉ ከሥርዓት የወጣ አለባበስን ይለብሱ ነበር እንጂ ለጸሎት ተስማሚ የሆነውን የትሕትና አለባበስን አይለብሱም ነበርና ነው፡፡

ለጸሎት ወደ አምላኩ የሚቀርብ ሰው ሌሎች ጉዳዮቹን ሁሉ ወደ ኋላ ትቶና ከሰው ዘንድም ምስጋናንና ክብርን ሳይሻ ጸሎቱን ተቀብሎ ወደሚፈጽምለት አምላኩ ብቻ ትኩረቱን ሊያደርግ ይገባዋል፡፡ ይህን መፈጸም ትተህ ዐይኖችህን የትም የምታንከራትት ከሆነ ከእግዚአብሐር ቤት በባዶ እጅህ ምንም ሳታገኝ እንድትመለስ ዕወቅ፡፡ ከእግዚአብሔር አምላክ ዘንድ ዋጋ ማግኘትና ማጣት በእጅህ የተሰጠ የአንተ እድል ፈንታህ ነው፡፡ ስለዚህ ከንቱ ውዳሴን የሚሹ ሰዎች ከእኔ ዘንድ አንዳች አያገኙም አላለም፡፡ ነገር ግን “ዋጋቸውን ተቀብለዋል” አለ፡፡

በእርግጥ ከእግዚአብሐር ዘንድ ሳይሆን እነርሱን ከመሰሉ ሰዎች ምስጋናና አድናቆትን አግኝተው ይሆናል፡፡ ይህ ለእነርሱ ዋጋቸው ነው፡፡ ነገር ግን ከእግዚአብሐር ዘንድ አይደለም፡፡ ምክንያቱም ለጸሎታቸው ብድራትን የጠበቁት ከእግዚአብሔር ሳይሆን ከሰዎች ነውና፡፡ ነገር ግን በዚህ ኃይለ ቃል እግዚአብሔር አምላክ ማንኛውንም እንደ ፈቃዱ ልመናና ጸሎት ብናቀርብ ልመናችንን ሊሰማን ጸሎታችንን ሊቀበል ቃል ኪዳን መግባቱም እናስተውላለን፡፡ ጌታችን ጻፎችና ፈሪሳውያን ለጸሎታቸው የመረጡት ሥፍራ ለከንቱ ውዳሴ የሚያጋልጥ መሆኑን ካስረዳ በኋላ እኛ ስንጸልይ ምን ማድረግ እንዳለብን አስተምሮናል፡፡
እንዲህም አለን “አንተ ግን ስትጸልይ ወደ እልፍኝህ ግባ መዝጊያህንም ዘግተህ በሥውር ላለው አባትህ ጸልይ፡፡” ምንድን ነው ታዲያ? እንዲህ ሲለን በቤተ ክርስቲያን ጸሎትን አታድርጉ ሲለን ነውን? አይደለም ነገር ግን እንዲህ ማለቱ በየትኛውም ቦታ ሆነን ጸሎትን ብናደርግ በፍጹም ተመስጦ ሆነን ማቅረብ እንዳለብን ሲያሳስብ ነው፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር በየትም ቦታ ማንኛውንም መልካም ሥራ ብንፈጽም ሁልጊዜም በማስተዋል ሆነን ብንፈጽማቸው የእርሱ ፈቃድ ነውና፡፡ ምንም እንኳን አንተ የእልፍኝህን በር ዘግተህ ብትጸልይ ይህን በማድረግህ ከሰው ዘንድ ምስጋናን ሽተህ ከሆነ የእልፍኝህን በር ዘግተህ በመጸለይህ ከእግዚአብሔር ዘንድ አንዳች ዋጋን አገኛለሁ ብለህ አትጠብቅ፡፡

ይህንን ግልጽ ለማድረግም “ለሰው ትታዩ ዘንድ” የሚለውን ቃል ጨመረበት፡፡ ስለዚህም አንተን የእልፍኝህን ደጅ ዘግተህ ትጸልይ ዘንድ ማዘዙ ልቡናህን ሰብስበህ ትጸልይ ዘንድ ነው እንጂ በርህን ዘግተህ መጸለይ ዋጋ ያሰጥሃል እያለህ አይደለም፡፡ የእግዚአብሐር ፈቃድ የቤትህን ደጅ ዘግተህ ትጸልይ ዘንድ ሳይሆን የልብህን ደጆች በመዝጋት ትጸልይ ዘንድ ነው፡፡

ማንኛውንም የትሩፋት ሥራዎችን ስትሠራ ከከንቱ ውዳሴ ነፃ መሆን መልካም ነው፡፡ በተለይ ደግሞ ስትጸልይ ራስህን ከከንቱ ውዳሴ መጠበቅ ይገባሃል፡፡ ከዚህ ውጪ ግን በጸሎታችን ሰዓት የምንቅበዘበዝና የምንባክን ከሆነና ከልባችን የማንጸልይ ከሆነ ለዚህ ክፉ ለሆነ በሽታ ማለትም ለከንቱ ውዳሴ እንጋለጣለን፡፡ እኛ በተመስጦ ሕሊናችንን ሰብስበን ካልሆነ የምንጸልየው እንዴት ጸሎታችንን እግዚአብሔር እንደሚሰማን እርግጠኛ እንሆናለን?

እንዲያም ሆኖ አንዳንድ ምዕመናን ከሥርዓት የወጣ ጩኸት በማሰማትና ያልተገባ ጠባይን በማሳየት የሌላውን ሰላም የሚያውኩ ከዚህም ባለፈ ራሳቸውን ለከንቱ ውዳሴ የሚያጋልጡ አሉ፡፡ በገበያ ቦታ እንኳ አንድ የእኔ ቢጤ ባልተገባ ጠባይ እና ለመስማት በማይመች ጩኸት ለአንዱ ባለጸጋ ልመና ቢያቀርብ ፈጥኖ ከፊቱ እንዲያባርረው በትሕትና በመሆን ቢለምነው ግን የባለጸጋውን ሆድ አባብቶ ያለውን እንዲሰጠው እንደሚያደርገው አትመለከትምን?

እኛም ስንጸልይ በማይገባና ፈር በለቀቀ ከሥርዐት በወጣ መልኩ አብዝተን በመጮኽ ሊሆን አይገባም፡፡ ነገር ግን በውጭ የምናሰማው አንዳች ጩኸት ሳይኖር ለከንቱ ውዳሴ ከሚያጋልጡ ያልተገቡ ጠባያት ርቀን አጠገባችን ያሉትን ሰዎች  ሳናውክ በፍጹም ትሕትና በውስጣዊ ማንነታችን ማለትም በነፍሳችን ወደ እግዚአብሐር ልንጮኽና ልመናችንን ልናቀርብ ይገባል፡፡

እንዲህ ስንል ሰው ከደረሰበት ታላቅ ኅዘን የተነሣ አምርሮ ሊጮኽ አይችልም ማለታችን ግን አይደለም፡፡ ቢሆንም አንድ ሰው ምንም እንኳ እጅግ ያዘነና የተከዘ ቢሆንም ይህን ታላቅ ኅዘን በነፍሱ ወደ እግዚአብሔር በመጮኽ ሊገልጸው ይችላል፡፡ ለምሳሌ ሙሴ ወደ እግዚአብሐር አምላኩ በነፍሱ አብዝቶ ቃተተ ጮኸም፤ ጩኸቱም ከእግዚአብሐር ዘንድ ተሰማች፤ በዚህም ምክንያት እግዚአብሐር ሙሴን “ለምን ትጮኽብኛለህ” አለው፡፡ /ዘጸአ.14÷15/ የነቢዩ ሳሙኤል እናት ሐና ከከንፈሩዋ የወጣ አንዳችን ድምፅ ሳይኖር በነፍሷ ግን የልቧን ኅዘን ወደ እግዚአብሐር ታመለክት ነበር፡፡ ልመናዋንም እግዚአብሐር ተቀበላት የልቧንም መሻት ሁሉ ፈጸመላት፡፡ አቤል እንኳን በሞቱና በደሙ ከእግዚአብሐር አምላክ ዘንድ ከመለከት ድምፅ ይልቅ ጠርታ የምትሰማ ጩኸትን ወደ እግዚአብሐር ጮኾ ነበር፡፡ /ዘፍ.4÷10/

ነቢዩ ኢዩኤልም በእግዚአብሔርም ፊት የልባችንን ኅዘን ለመግለጽ ልብሳችንን ሳይሆን ልበችንን ለጸሎት ልናዋርድ እንዲገባን ሲያስረዳ “ልባችሁን እንጂ ልብሳችሁን አትቅደዱ” /ኢዩ.2÷13/ ብሎናል፡፡

መዝሙረኛውም “አቤቱ አንተን ከጥልቅ ጠራሁ” /መዝ.129፥1/ ብሏል፡፡ ከልባችን ጥግ ከጥልቁ የሚወጣው ጩኸታችን ድንቅ የሆነ ምላሽን ይዞልን ይመጣል፡፡ በምድራዊው ቤተ መንግሥት ትንሽ የሆነ ኮሽታ ወይንም ሹክሹክታ የግቢውን ጸጥታ ምን ያህል እንደሚያውከው አትመለከትምን? እንዴት ታዲያ ምድራዊ ባልሆነው እጅግም አስፈሪ በሆነው ሰማያዊው ቤተ መንግሥት ስትገባ የበለጠ ፀጥታን ገንዘብህ ማድረግ ይጠበቅብህ ይህን!!

አንተ አሁን በምስጋና ከትጉሃን መላእክት ጋር ተቆጥረሃል፡፡ ከሊቃነ መላእክት ጋርም ማኅበርተኛ ሆነሃል፡፡ ከሱራፌል ጋር ዝማሬን ለእግዚአብሐር ለማቅረብ ታድመሃል፡፡ በሰማያት ያሉ መላእክት ሁሉ በመልካም ሥርዓት በመሆን ለእግዚአብሔር ይገዛሉ፡፡ እርሱንም በመፍራት ሆነው ድንቅ የሆነ ዝማሬአቸውንና ቅዳሴአቸውን ለፍጥረት ሁሉ ገዢ ለሆነው አምላክ ያለማቋረጥ ያቀርባሉ፡፡

አንተም ከእነርሱ ጋር እግዚአብሐርን በማመስገን ስሙን በመቀደስ እነርሱን ትመስሏቸው ዘንድ ከእነርሱ ጋርም በጥምቀት ማኅበርተኛ ሆነሃል፡፡ ስለዚህም በምትጸልይበት ጊዜ ለሰዎች ትታይ ዘንድ አትጸልይ ነገር ግን ወደ እግዚአብሐር ጸልይ፡፡ እርሱ በሁሉ ቦታ ይገኛልና እይታን ከፈለግህ በሁሉ ቦታ ያለ እርሱ ከሰው ይልቅ ያስተውልሃል፡፡ እርሱ በልብህ የታሰበውን እንኳ ያውቃል፡፡

በሥውር የሚያይህ አባትህ በግልጥ ይከፍልሃል፡፡” እንዲህ ሲል /Shall freely give thee “but shall reward thee”/  በነጻ ይሰጣሀል አላለም ነገር ግን እንደሚገባ ሆነህ በመጸለይህ ምክንያት በብድራት በግልጽ ይከፍልሃል ማለት ነው፡፡ አዎን እርሱ በአንተ ዘንድ እንደ ተበዳሪ ሆኖ ታየ፡፡ በዚህም አንተን ምን ያህል እንደወደደህና እንዳከበረህ አስተውል፡፡ እርሱ የማይታይ አምላክ እንደመሆኑ መጠን እንዲሁ እኛም ስንጸልይ በሥውር ላለው አባት ብለን እንጂ ከሰው ምስጋናን ለመቀበል ሽተን ሊሆን አይገባውም፡፡

በጸሎታችሁ አሕዛብን አትምሰሉአቸው

በመቀጠል ጸሎታችንን አንዴት ማቅረብ እንዳለብን ያስተምረናል፡፡ “አሕዛብም በመናገራቸው ብዛት እንዲሰሙ ይመስላቸዋልና ስትጸልዩ እንደነርሱ በከንቱ አትድከሙ” /ማቴ.6÷7/ አለ፡፡
ትመለከታለህ! አስቀድሞ ስለምጽዋት ሲያስተምር ወደ ከንቱ ውዳሴ የሚካተቱንን ነገሮች በማውጣት ከእነርሱ እንድንጠበቅ አዝዞን ነበር፡፡ ከእነዚህም ሌላ ግን ጨምሮ አላስተማረንም ወይንም ከድካማችን ካገኘነው እንጂ በአመፃ ካገኘነው ገንዘብ እንዳንመጸውት አስተማረን እንጂ ምጽዋቱ መቼ መፈጸም እንዳለበት ጊዜውን ለይቶ አላስተማረንም፡፡ ምክንያቱም “ስለጽድቅ የሚራቡ ብፁዓን ናቸው” በማለት ምጽዋታችን ምን መምሰል እንዳለበት አስቀድሞ አስተምሮ ነበርና ነው፡፡

ጸሎትን በተመለከተ ግን ደግሞ ደጋግሞ ነበር ያስተማረው፡፡ አስቀድሞ ጻፎችና ፈሪሳውያንን እንደወቀሳቸው ሁሉ “በከንቱ አትድከሙ” በማለት አሕዛብን ወቀሳቸው፡፡ እንዲህ የሚያደርጉ ወገኖችንም አሳፈራቸው፡፡ጌታችን በትምህርቱ የምንሳብባቸውንና እኛም ልንፈጽማቸው የምንጓጓላቸውን ነገሮች ጎጂነት ነቅሶ በማውጣት ደጋግሞ አስተምሮናል፡፡ ምክንያቱም እኛ ሰዎች ስንባል በውጫዊ ገጽታቸው አምረውና አሽብርቀው በሚታዩ ነገሮች በቀላሉ ስለምንሳብ በውጭ ሲታዩ ጻድቃን የሚመስሉን ግብዞች መስሎ መመላለስን ስለምንመርጥ ነው፡፡

“በከንቱ አትድገሙ” በማለት እንዲህ የሚያደርጉ ሰዎች እጅግ የዘቀጠ አስተሳሰብ እንዳላቸው ገለጠ፡፡ እኛ ከእግዚአብሔር ፈቃድ ውጭ ሥልጣንን፣ ክብርን፣ የጠላት ነፍስን ባለጸግነትን እንዲሁም ሌላም እኛን የማይመለከቱን ነገሮችን በጸሎት ብንጠይቅ በከንቱ እንደመድገም ይቆጠርብናል፡፡

ስለዚህም “አትምሰሏቸው ሳትለምኑት አባታችሁ የሚያስፈልጋችሁን ያውቃልና” አለን፡፡ እዚህ ላይ ጌታችን እንዲህ ሲል ጸሎታችሁን አታርዝሙት ማለቱ አይደለም የጌታችን ዋናው የትምህርቱ ትኩረት ጊዜን በተመለከተ አይደለም ነገር ግን አስቀድመን እንዳስቀመጥነው የማይገቡ ጸሎታትን በማድረግ በከንቱ መድከም አብዝተንና አርዝመን የምንጸልየውን ጸሎት ነው፡፡

የሚገባ ጸሎት ከሆነ ደጋግመን መጸለይ እንዲገባ “በጸሎት ጽኑ” ተብለን ታዘናል፡፡ በኤፌ.6÷18 ላይም በጸሎት መጽናት እንዳለብን ተቀምጦልናል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም “ፊታችሁን ልናይ በእምነታችሁም የጎደለውን ልንሞላ ሌሊትና ቀን ከመጠን ይልቅ እንጸልያለን” /1ኛተሰሎ.3÷9-10/ በማለት በተግባር እየፈጸመ እንደነበር እናስተውላለን፡፡

ጌታችን ከጨካኙ ዳኛ ዘንድ ፍርድ ተጓደለብኝ በማለት በተደጋጋሚ ደጅ የጠናችውን መበለት ምሳሌ በማድረግ /ሉቃ.18÷1/ እንግዳ ስለመጣበት እንጀራ በእኩለ ሌሊት ከወዳጁ ይለምን ዘንድ የሄደውን ሰው ትጋት በማውሳትና ያም ወዳጁ የተጠየቀውን የሰጠበት ምክንያት ስናስተውል ስለወዳጅነቱ ሳይሆን ስለንዝነዛው ብዛት እንደሆነ አብራርቶ ገልጾልናል፡፡ በዚህም ያለማቋረጥ መጸለይ እንደሚገባ አስትምሮናል፡፡ በእርግጥ አጭር ስንኞችን ደጋግሞና አርዝሞ መጸለይ ይገባል አንልም ይህም እንደማይገባ ሲያስረዳ “በጸሎታቸው ብዛት የሚሰሙ ይመስላቸዋልና እነርሱን አትምሰሉአቸው” ብሎናልና፡፡

“ባትለምኑትም አባታችሁ የሚያስፈልጋችሁን ያውቃል” ይላልና እርሱ የሚያስፈልገንን ካወቀ የእኛ መጸለይ ለምን አስፈለገ? ብሎ የሚጠይቅ ከእኛ መካከል አይጠፋም፡፡ አምላክን እንዲህ አድርግ ብለን አናዘውም ነገር ግን ከእርሱ ጋር የፍቃድ አንድነት ይኖረን ዘንድ ስለሚገባን ነው፡፡ /እግዚአብሔር ያለፈቃዳችን አንዳች ነገር ሊያደርግብን አይፈቅድም እርሱ ፈቃዳችንን ይጠይቃል/ ከዚህም በተጨማሪ ከእርሱም ጋር በጸሎት በምንመሠርተው የጠበቀ ግንኙነት ተጠቃሚዎች እንድንሆንና እንዲሆን የገዛ ኃጢአታችንን ዘወትር በማሰብ በትሕትና እንመላለስ ዘንድ ነው፡፡

“እናም ስትጸልዩ እንዲህ ብላችሁ ጸልዩ አባታችን ሆይ በሰማይ የምትኖር”/ማቴ.6÷9/

ይቀጥላል…

ቅዱስ እሰጢፋኖስ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ አስተምህሮ

ቀን ጥቅምት 17/2004 ዓ.ም.

በዲ/ን ሽመል መርጊያ

 

(የሐዋ.6፡8-ም.7፡53)

መግቢያ

በሐዋርያት ስብከት ቤተ ክርስቲያን ስትስፋፋ በትምህርታቸውና በተዐምራታቸው ተስበው ወደ ክርስትና እምነት የተመለሱ ከአይሁድና ከአሕዛብ ወገን የሆኑ ክርስቲያኖች መሬታቸውንና ጥሪታቸውን በመሸጥ  ያላቸውን ሀብት አንድነት በማድረግ በኢየሩሳሌም የአንድነት ኑሮን ይኖሩ ነበር፡፡ በሕብረትም የሐዋርያት ትምህርትን በመስማትና  በጸሎት ይተጉ እንዲሁም ማዕድን በመባረክ በጋራ ይመገቡ ነበር፡፡ መጽሐፍ ቅዱስም “አንድ ልብና አንዲትነፈስ አላቸው በማለት (የሐዋ.4፡32) ስለአንድነታቸው ፍጹምነት ይነግረናል፡፡

 

ነገር ግን በቁጥር እየበዙ ሲመጡ በመካከላቸው በማዕድ ምክንያት ልዩነት ተፈጠረ፡፡ ከይሁዲነት ወደ ክርስትና የተመለሱ ክርስቲያኖች በምግብ ክፍፍል ወቅት ከግሪክ የመጡትን ይጸየፉዋቸው፣ በተለይ ባልቴቶቻቸውን ቸል ይሉባቸው ስለነበር በማኅበሩ መካከል አለመስማማት ተፈጠረ፡፡ ይህም በሐዋርያት ዘንድ ተሰማ፡፡

 

ሐዋርያትም “የእግዚአብሔርን ቃል ትተን ማዕድን እናገለግል ዘንድ የሚገባ አይደለም”የሐዋ.6፡2) በማለት ማዕዱንና በውስጥ ያለውን አገልግሎት ያስተናብሩ ዘንድ ሰባት ሰዎች እንዲመረጡ የክርስቲያኑን ኅብረት ጠየቁ፡፡ ምዕመናኑም በአሳቡ ደስ ተሰኝተው መንፈስ ቅዱስና ጥበብ የሞላባቸውን ሰባት ክርስቲያኖችን መረጡ፡፡ ሐዋርያትም እጆቻቸውን ጭነው ረድእ ይሆኑአቸው ዘንድ ዲያቆናት አድርገው ሾሙአቸው፡፡

 

ከእነዚህም ዲያቆናት መካከል በቅድስና ሕይወቱ ለክርስቲያኖች ዓብነት የሆነው ሰማዕቱ ቅዱስ እስጢፋኖስ ይገኝበታል፡፡ እስጢፋኖስ የሚለው ቃል የግሪክ ቃል ሲሆን ትርጉሙም “አክሊል” ማለት ነው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስን ወደ ግእዝ በኋላም ወደ አማርኛ የመለሱት አባቶች በቀጥታ የግሪኩን እስጢፋኖስ የሚለውን ቃል ተጠቅመዋል፡፡ ቅዱስ እስጢፋኖስ ምንም እንኳ ስሙ የግሪክ ስም ይሁን እንጂ በትውልዱ አይሁዳዊ ነው፡፡ ወላጆቹ ይህንን ስም ሊሰጡት የቻሉት በፍልስጤም ጠረፋማ ከተሞች ይኖሩ ስለነበር የግርክ ባሕልና ቋንቋ ተጽእኖ አድሮባቸው ይሆናል ተብሎ ይገመታል፡፡

 

ቅዱስ እስጢፋኖስ በሐዋርያት ጥበቃ የነበረችውን ቤተ ክርስቲያን ከአምላክ ዘንድ ባገኘው የማስተማርና የፈውስ ሀብት ያገለግል ነበር፡፡ በእርሱም ታላላቅ ተኣምራት ይፈጸሙ ነበር፡፡ ስለዚህም ሕዝቡ ከፊት ይልቅ እጅግ እየበዛና በትምህርት እየጠነከረ መጣ፡፡ አይሁድም ይህን ተመልክተው በቅዱስ እስጢፋኖስ ላይ በቅናትና በጠላትነት ተነሡበት፡፡ ነገር ግን ከመንፈስ ቅዱስ ባገኘው ጥበብና ኃይል እነርሱን በቃልም በድርጊትም ይቃወማቸው ነበርና ሊረቱት አልተቻላቸውም፡፡ ስለዚህም እግዚአብርሔርን፣ ሙሴ ሲሳደብ ሰምተነዋል፣. ሙሴ የሠራልንን ሥርዐት ይለውጣል፣ በዚህ ቤተ መቅደስና በሕጉ ላይ የስድብን ቃል ይናገራል፣ ይህንንም ቤተ መቅደስ የናዝሬቱ ኢየሱስ አፍርሱ ብሎአል እያለ ያስተምራል አያሉ፣ ሕዝቡን፣ ሽማግሌዎችንና ጸሐፍትን በማናደድ ይዘው ከሸንጎ ፊት አቆሙት፡፡

 

ቅዱስ እስጢፋኖስን በሸንጎ ፊት ባቆሙት ጊዜም ፊቱ ልክ እንደ መልአክ ፊት ሆኖ በርቶ ነበር፡፡ እርሱም ለተከሰሰበት ነጥብ መልስ ሰጠ፡፡ ከአብርሃም እስከ ክርስቶስ ለእነርሱ የተሰጣቸውን በረከት በመቃወማቸው ከተስፋ ቃል እርቀው እንደተወገዱ ገለጠላቸው፡፡ ክርስቶስንም ባለመቀበላቸው ወቀሳቸው፡፡ በዚህም ምክንያት በቁጣ ተነሣስተው ከከተማ ውጭ በመውሰድ በድንጋይ ወግረው ገደሉት፡፡

 

ቅዱስ እስጢፋኖስ አይሁድ በድንጋይ እየወገሩት ሳለ ሰማያት ተከፍተው ክርስቶስን በአብ ቀኝ ቆሞ ተመለከተ፡፡ ይህንን ራእይ የክርስቶስን ትንሣኤን ለማይቀበሉት አይሁድ አሰምቶ ተናገረ፤ እነርሱ ከፊት ይልቅ በእርሱ ጨከኑ በድንጋይም ወገሩት፡፡ ነገር ግን ቅዱስ እስጢፋኖስ ጌታውን ክርስቶስን መስሎ ነበርና ልክ እንደ መምህሩ ክርስቶስ “አቤቱ ይህን ኀጢአት አትቁጠርባቸው” ብሎ በታላቅ ድምፅ ጮኾ  ነፍሱን ሰጠ፡፡ በቤተክርስቲያንም ታሪክ ስለክርስቶስ መስክሮ ሰማዕትነትን የተቀበለ የመጀመሪያው ዲያቆን ሆኖአል፡፡

 

በደማስቆ መንገድ ላይ ክርስቲያኖችን ያሳድድ የነበረ ሳውል በኋላም ቅዱስ ጳውሎስ ተብሎ ስያሜ የተሰጠው ሐዋርያ  ቅዱስ እስጢፋኖስ በድንጋይ በሚወግሩበት ወቅት በእርሱ ሞት ተስማምቶና ድንጋይን በእስጢፋኖስ ላይ ያነሡትን የአይሁድ ልብስ ይጠብቅ የነበረ ብላቴና ነበር፡፡ ነገር ግን ቅዱስ ጳውሎስ ሐዋርያ ከሆነ በኋላ የእስጢፋኖስን ቤተሰቦች አጥምቆአቸዋል፡፡ ይህ ደግሞ ድንቅ ነው፡፡  ቅድስት ቤተክርስቲያናችንም ይህን ቅዱስ የመታሰቢያ ቀን በመስጠት  ጥቅምት 17 የድቁና ማዕረግን በአነብሮተ ዕድ በሐዋርያት የተቀበለበትን፥  ጥር 1 ደግሞ ዕረፍቱን ታስባለች፡፡

 

ከዚህ በመቀጠል ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የሐዋርያት ሥራን በተረጎመበት በ15ኛው ድርሳኑ የሐዋ.6.8-ም.7፡53  ያለውን መሠረት አድርጎ የሰጠውን ትምህርት እንመለከታለን፡፡

 

ድርሳን 15 የሐዋርያት ሥራ ትርጓሜ በቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ትምህርት

 

ከሰባቱ ዲያቆናት መካከል አንዱ ብቻ የክብሩን አክሊል እንደደፋ ትመለከታለህን? ምንም እንኳ ለሁሉም የተሰጠው ሥልጣን አንድ ዓይነት ቢሆንም ታላቅ የሆነን ጸጋን ለራሱ እንዴት ገንዘቡ እንዳደረገ አስተውል፡፡ አንድም ተአምር ወይም ድንቅ ሳያደርግ በዛን ዘመን እንዴት በምዕመናኑ ዘንድ ታዋቂ እንደሆነ ተመልከት፡፡ ነገር ግን ሕዝቡን ወደ መምራት አልመጣም፡፡ ይህ የሚያሳየን በጥምቀት የምናገኘው ጸጋ ብቻውን ሕዝቡን ለመምራት በቂ እንዳልሆነ ነው፡፡ ምንዕመኑን ለማገልገል የሚነሣ ሰው አስቀድሞ ከጸጋው ጋር ሥልጣኑም ሊኖረው ይገባዋል፡፡ ምንም እንኳ በጥምቀት መንፈስ ቅዱስን የተቀበልን ብንሆንም  የእግዚአብሔርን መንጋ ለማገልገል ሌላ አጋዥ የሆነ የመንፈስ ቅዱስ ድጋፍ ያስፈልገናል፡፡ ከዚህም የምንረዳው ይህንኑ ነው፡፡

 

“የነጻ ወጪዎች ከተባለችው ምኩራብም ከቀሬናና ከእስክንድርያም ሰዎች ከኪልቅያና ከእሲያም ከነበሩት አንዳንዶቹ ተነሥተው እስጢፋኖስን ይከራከሩት ነበር”(ቁ.9) “ተነሥተው” የሚለው ቃል የሚያሳየው የእነርሱ ቁጣ ነው፡፡ እኛ በዚህ ብዙ ሆነን እንደተሰባሰብነው እንዲሁ የእስጢፋኖስ ጉባኤም  ነበር፡፡ በዚህ ቦታ የአይሁድን ሌላ ሴራ እናስተውላለን፡፡ ገማልያል በሐዋርያት ላይ ስህተትን እንዳይፈላልጉ ቢያስጠነቅቃቸውም በዚህ ቦታ ዘዴያቸውን ቀይረው እንደገና  በሐዋርያት ላይ በጠላትነት መነሣታችን በዚህ ቦታ ላይ እናስተውላለን፡፡

 

እናም “የነጻ ወጪዎች ከተባለችው ምኩራብም ከቀሬናና ከእስክንድርያም ሰዎች ከኪልቅያና ከእሲያም ከነበሩት አንዳንዶቹ ተነሥተው እስጢፋኖስን ይከራከሩት ነበር፡፡ ይናገርበት የነበረውንም ጥበብና መንፈስ ይቃወሙ ዘንድ አልቻሉም፡፡ በዚያን ጊዜ፡-በሙሴ ላይ በእግዚአብሔርም ላይ የስድብን ነገር ሲናገር ሰምተነዋል የሚሉ ሰዎችን አስነሡ፡፡”(ቁ.9-12)አለን፡፡ በዚህ እነዚህ ወገኖች  “በሙሴና በእግዚብሔር ላይ የስድብን ቃል ሲናገር ሰምተነዋል” ብለው በቅዱስ አስጢፋኖስ ላይ መነሣታቸውን እናስተውላለን፡፡ እንዲህም ማድረጋቸው ከእርሱ ስህተትን ለማግኘት እንዲመቻቸው ሊያናገሩት ስለፈለጉ ነበር፡፡

 

እርሱ ግን ከፊት ይልቅ በግልጥ ስለክርስቶስ ሰበከላቸው፡፡ በሚሰብክበትም ወቅት የእግዚአብሔርን ሕግ መሠረት አድርጎ ነበረ ወይም ሕጉን እየጠቀሰ ነበር የሰበከው፡፡ እርሱ በግልጥ በመስበኩ ምክንያትም እርሱን ለመወንጀል ሲባል የሐሰት ምስክሮችን ማሰባሰባቸውን ከንቱ አደረገባቸው፡፡ወደ ምኩራቡ የመጡት አይሁዳውያን አመጣጣቸው ከተለያየ ቦታ ነበር፡፡ እንደ አመጣጣቸውም የተለየዩ ምኩራቦችም የነበራቸው ይመስላሉ፡፡ አንዳንዶች ግን  ምልልሱ አሰልችቶአቸው መኖሪያቸውን በዚያው በኢየሩሳሌም አድርገው የሚኖሩም ናቸው፡፡ ምኩራቡዋም የነጻ ወጪዎች ምኩራብ መባሉዋ ከሮማውያን አገዛዝ ነጻ የሆነች ምኩራብ በመሆኑዋ ነበር፡፡ በዚህች ምኩራብ ብዙ የውጭ ሀገር ሰዎች ከትመውባት ይኖሩ ነበር፡፡ ስለዚህ በዚህች ከተማ ሕጉ የሚነበብባት ምኩራብ ይህቺ  ነበረች፡፡

 

“እስጢፋኖስን ተከራከሩት” አለ ወንጌላዊው፤ ተወዳጆች ሆይ በዚህ ኃይለ ቃል አይሁድ  ቅዱስ እስጢፋኖስን በግልጽ አስተማሪነቱ አይገባህም እያሉ ሳይሆን ይከራከሩት የነበሩት እኔ መምህር ልባል አይገባኝም እንዲል ነበር ጫና ይፈጥሩበት የነበሩት፡፡ በእርሱ የሚፈጸሙ ተአምራቶች በእርሱ ላይ በክፋት እንዲነሣሡበት ምክንያት ሆኖአቸው ነበር፡፡ ነገር ግን ከእርሱ ጋር በቃል ወደ መሟገት ሲመጡ አሳፍሮ ይመልሳቸው ነበር፡፡ ስለዚህም ሐሰተኛ ምስክሮችን ወደማሰባሰብ ተመለሱ፡፡

 

ነገር ግን “እስጢፋኖስን ይከራከሩት ነበር ይናገርበት የነበረውንም ጥበብና መንፈስ ይቃወሙ ዘንድ አልቻሉም፡፡” ተብሎ እንደተጻፈው  ለክርክራቸው ምላሽ ስላሳጣቸው ይህ ምክንያት ሆኖአቸው በቁጣ በመነሣሣት እርሱን ለመግደል አልሞከሩም፡፡ ነገር ግን ሐዋርያትን በመተው በእርሱ ላይ ብቻ ውንጀላዎችን በማቅረብ በዚህ መንገድ በሐዋርያትና በተከታዮቻቸው ላይ ሽብርን በመዝራት ጉባኤውን መበታተንን ነበር ዓላማቸው፡፡

 

ስለዚህም ሲከሱት “እንዲህ ብሎ ተናገረ” አላሉትም ነገር ግን  “ሕዝቡንና ሽማግሌዎችም ጻፎችም ቀርበውም ያዙት ወደ ሸንጎም አመጡትና፡- ይህ ሰው በዚህ በተቀደሰ ስፍራ  በሕግም ላይ የስድብን ነገር ለመናገር አይተውም”(ቁ.12-13) በማለት ነበር የከሰሱት፡፡” “የስድብን ነገር ለመናገር አይተውም” ሲሉም እንዲህ ማወክ የእለት ከእለት ተግባሩ አድርጎታል ሲሉ ነው፡፡

 

“ይህ የናዝሬቱ ኢየሱስ ይህን ስፍራ ያፈርሰዋል ሙሴም ያስተላለፈልንን ሥርዐት ይለውጣል ሲል ሰምተነዋልና የሚሉ የሐሰት ምስክሮችን አቆሙ፡፡”(ቁ.14)ሲሉም ክርስቶስን ሊነቅፉት ሽተው የናዝሬቱ ማለታቸውን እናስተውላለን ፡፡ እነዚህ ወገኖች “ቤተመቅደስን የምታፈርስ በሦስትም ቀን የምትሠራው ራስህን አድን”(ማቴ.27፡40) በማለት በክርስቶስ ላይ ሲሳለቁ የነበሩ ወገኖች ናቸው፡፡እነዚህ ወገኖች ምንም እንኳ አገራቸውን ጥለው የሚኖሩ ቢሆኑም ለሙሴና ለቤተመቅደሱ ያላቸው ክብር የተለየ ነበር፡፡ የእነርሱ ክስ ሁለት ገጽታ ነበረው፡፡ እርሱ ሥርዐቱን የሚለውጠው ከሆነ በእርሱ ምትክ ሌላ ሥርዐት ይተካልና ብለው ስለሰጉ ነበር፡፡ ለውጡ እንዴት ከቀደመው የተሻለና ከዕንቊ ይልቅ የከበሩ ጸጋዎች የሞሉት እንደሆነ አስተውል፡፡

 

“በሸንጎ የተቀመጡት ሁሉ ትኩር ብለው ሲመለከቱት እንደ መልአክ ፊት ሆኖ ፊቱን አዩት ፡፡”(ቁ.15) በቤተክርስቲያን አነስተኛ ማዕረግ ላይ ላለው ክርስቲያን እንኳ የፊት መልክ እንደ ፀሐይ አብርቶ መታየት የተለመደ መሆኑን ነው ከዚህ ምንባብ  የምናስተውለው፡፡ አንድ የምጠይቀው ጥያቄ አለኝ ይህ ዲያቆን ከሐዋርያት የሚያንስበት ነገ አለውን? ተአምራት ከመፈጸም አልተቆጠበም፣ በድፍረት ነበር ሲያስተምር የነበረው፡፡ መጽሐፉም “በሸንጎ የተቀመጡት ሁሉ ትኩር ብለው ሲመለከቱት” ይልና “እንደ መልአክ ፊት ሆኖ ፊቱን አዩት”ይላል (ዘጸአ.34፡30) ይህ የእርሱ ጸጋ ነው፤ ይህ የሙሴ ክብር ነው፤ እርሱ የሚናገረውን ሁሉ በመታዘዝ ይፈጽሙት ዘንድ እግዚአብሔር አምላክ ይህን ክብር ሰጥቶት ነበር፡፡ አዎን ዛሬም በሚወዱአቸውም በሚጠሉአቸውም ፊት አስገራሚና አስደናቂ  መንፈሳዊ ብርሃንን ከፊታቸው የሚፈልቅላቸው ቅዱሳን አሉ፡፡

 

በዚህ ቦታ የቅዱስ እስጢፋኖስን ቃል መስማት ለምን እንዳስፈለገ አስቀድሞ ተገልጦአል፡፡ ስለዚህም ከዚህ በመቀጠል “ሊቀ ካህናቱም ይህ ነገር እንዲህ ነውን አለ? (የሐዋ.7፡1) እንዲህ ዓይነት ጥያቄ ውስጥ አንዳች ታላቅ ተንኮል እንዳለ ማስተዋል ይቻላል፡፡ ስለዚህም ቅዱስ እስጢፋኖስ መልሱን ታላቅ በሆነ ብስለት ጀመረ “ወንድሞችና አባቶች  ሆይ ስሙ የክብር አምላክ ለአባታችን ለአብርሃም በካራን ሳይቀመጥ ገና በሁለት ወንዝ መካከል ሳለ ታየና ከአገርህና ከዘመዶችህም ወጥተህ ወደማሳይህ ወደ ማንኛውም ምድር ና አለው፡፡” አለ፡፡(ቁ.2-3) በዚህ መልሱ የእነርሱን ተንኮል ነቅሎ አጠፋው፡፡ በዚህም ስለምን ቤተመቅደሱ  ከእንግዲህ ምንም እንደማይጠቅም ገለጠላቸው፡፡ ሥርዐታቸውም ከእነርሱ ግምት ውጪ ምንም ጥቅም እንደሌለው በተዘዋዋሪ አስረዳቸው፡፡ እንዲሁም ስብከቱን ምንም የማስቆም ኃይሉ እንደሌላቸውና ደካማ በሆነው አካል ተጠቅሞ እግዚአብሔር ብርቱ የሆነውን ኃይሉን እንደሚገልጥ አሳየበት፡፡

 

ይህ የመግቢያ ንግግሩ ማግ ጠቅላላ የንግግሩን ይዘት እንዴት እንዲታታው አስተውል፡፡ ከዚህ በላይ ደግሞ እነዚህ ወገኖች እንዴት ታላቅ ደስታና ታላላቅ በረከቶችን ያመጡላቸውን አስካሁንም እየተቃረኑዋቸው እንደመጡ፣ አሁንም ድል ሊነሡት የማይችሉትን አምላክ እየተፈታተኑ እንደሆኑ መግለጡንም ልብ እንላለን፡፡

 

“የክብር አምላክ ለአባታችን ለአብርሃም በካራን ሳይቀመጥ ገና በሁለት ወንዝ መካከል ሳለ ታየና ከዚህ  ከአገርህና ከዘመዶችህም ወጥተህ ወደማሳይህ ወደ ማንኛውም ምድር ና አለው “ አለው፡፡ በዚያን ዘመን ቤተመቅደስ፣ መሥዋዕትም አልነበረም ነገር ግን የእግዚአብሔር ራእይ ብቻ ለአብርሃም የተገለጠለት ነበር፡፡ የእርሱም ቅድመ አያቶቹ ፋርሶች እንደነበሩ እርሱም በተቀመጠባትም ምድር እንግዳ ሆኖ እንደኖረ ያስረዳቸው፡፡በንግግሩ መጀመሪያ ላይ ቅዱስ እስጢፋኖስ “ የክብር አምላክ” ማለቱ መልካም ነበር፡፡ በዚህም እግዚአብሔር ለሰዎች ከሰጠው ክብር ውጪ እንዳደረጋቸው አስረዳቸው፡፡ “የክብር አምላክ” ሲል   “አብርሃምን ያከበረው አምላክ እኛም ይህን ክብር በእምነት እንድናገኝ  አበቃን” ሲላቸው ነው፡፡

 

ቅዱስ እስጢፋኖስ ከሥጋዊ ሥርዐትና ለቦታ ከሚሰጡት ክብር አውጥቶ እንዴት በውስጣቸው ጥያቄን እንደፈጠረባቸው አስተውል፡፡ “የክብር አምላክ” አለ እንዲህ ሲል እርሱ ከእኛ ዘንድ፣ ከመቅደሱም ለእርሱ የሚቀርበው ክብር፣ ክብሩን እንደማይጨምርለት፣ ይልቁኑ እርሱ ራሱ የክብራቸው ምንጭ እንደሆነ ለማሳየት በመፈለጉ ነበር እንዲህ ያላቸው፡፡ በተጨማሪም  ሴራ ሠርታችሁ እኔን ለዚህ ሸንጎ በማቅረባችሁ እግዚአብሔርን ያከበራችሁት እንዳይመስላችሁም እያላቸው ነበር፡፡

 

“ከዘመዶችህ” አለ፡፡ ስለምን የአብርሃም አባት ታራ ከካራን ወጣ ብሎ መጽሐፍ ቅዱስ ተናገረ? (ዘፍ.11፡1) ከዚህ የምንማረው ለአብርሃም በተገለጠለት ራእይ መሠረት የአብርሃምም አባት ከካራን ወጥቶ ከንዓን መግባቱን ነው፡፡ በዚህ ቦታ ደግሞ አብርሃምን  “ከዚህ  ከአገርህና ከዘመዶችህም ወጥተህ ወደማሳይህ ወደ ማንኛውም ምድርና አለው”  በአብርሃም ታላቅ መታዘዝ  የእነርሱን አለመታዘዝ በመግለጥ  የአብርሃም ልጆች ለመባል ምንም እንደማይበቁ ገለጠላቸው፡፡  “ከዘመዶችህ” በማለት ለእግዚአብሔር የማይመቹ ክፉዎች፣ ክፋታቸውንም ሊታገሥ ካልቻላቸው ትውልድ እንደሆኑ፣  አብርሃምም በዚያ ቢቆይ  ከክፋታቸው የተነሣ መልካም ፍሬን ሊያፈራ እንደማይችል ሲገልጥለት ነው፡፡

 

“በዚያን ጊዜ ከከለዳውያን አገር ወጥቶ በካራን ተቀመጠ፡፡ ከዚያም አባቱ ከሞተ በኋላ እናንተ ዛሬ ወደምትኖሩበት ወደዚች አገር አወጣው፡፡ በዚህችም የእግር መረገጫ  ጫማ ስንኳ የሚያህል ርስት አልሰጠውም ”(ቁ.4) እንዲህ በማለቱ በአእምሮአቸው ርስታችን ናት ብለው ከሚመኩባት አውጥቶ እንደሰደዳቸው እናስተውላለን፡፡ ሰጠው ቢላቸው ኖሮ ፍርዱ በእነርሱ ላይ ሳይሆን በእርሱ ላይ ይወድቅ ነበር፡፡ ስለዚህም ዘመዶቹንና ሀገሩን ጥሎ ከወጣ በኋላ ወደዚህ መጣ አላቸው፡፡  ከዛስ በኋላ ከንዓንን ለአብርሃም ርስት አድርጎ አልሰጠውምን? ሰጥቶታል ነገር ግን ይህ የሌላይቱ ርስት ጥላ ነበር፡፡

 

ቅዱስ እስጢፋኖስ ትምህርቱን “ርስት አልሰጠውም” ብቻ ብሎ ለማጠናቀቅ አልፈለገም “ነገር ግን ልጅ ሳይኖረው ለእርሱ ከእርሱም በኋላ ለዘሩ ይሰጠው ዘንድ ተስፋ ሰጠው፡፡” (ቁ.5) አለ፡፡ ከዚህ በመቀጠል የማይቻለው ሁሉ ለእርሱ የሚቻለው እግዚአብሔር ምን እንዳደረገ ገለጠላቸው፡፡ ከሩቁ አገር የሆነ ሰው እነሆ እግዚአብሔር እንዲህ አለው፡- አንተን የከንዓን አገር ገዢ አደርግሃለሁ፡፡ ነገር ግን ስለ እርሱ የተነገረውን መልሰን እንመርምረው፡፡ ተወዳጆች ሆይ እጠይቃኋለሁ በቅዱስ እስጢፋኖስ ላይ የጸጋው ብርሃን የታየው በምን ምክንያት ነው? ጸሐፊው ስለእርሱ ማንነት አስቀድሞ ሲጽፍ “ጸጋና ኃይል የተሞላ”(የሐዋ.6፡8)በማለት ማረጋገጫውን ሰጥቶአል፡፡

 

ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ መገለጥን ለእያንዳንዱ ለጥቅም ይሰጠዋል ለአንዱ ጥበብን መናገር ይሰጠዋልና፣ ለአንዱም በዚያው መንፈስ እውቀትን መናገር ይሰጠዋል፣ ለአንዱም በዚያው መንፈስ እምነት፣ ለአንዱ የመፈወስ ስጦታን …” (1ቆሮ.12፡8፣9)እንዲል አንድ ሰው የመፈወስ ጸጋ ያይደለ ሌላ ጸጋ ሊሰጠው ይችላል፡፡ “በሸንጎ የተቀመጡት ሁሉ ትኩር ብለው ሲመለከቱት እንደ መልአክ ፊት ሆኖ ፊቱን አዩት፡፡”(ቁ.15) ብሎ መናገሩ እንደእኔ ለቅዱስ እስጢፋኖስ  በመንፈስ ቅዱስ የተሰጠውን “ጸጋና ኃይሉን” ይመስለኛል፡፡ ልክ በርናባስን “ደግ ሰውና መንፈስ ቅዱስ እምነትም የሞላበት ነበረና፡፡” (የሐዋ.11፡24) እንደተባለው ዓይነት ማለቴ ነው፡፡ እውነተኞችና ንጹሐን ሰዎች ከምንም ነገር በላይ ሰዎች ይድኑ ዘንድ ይፈልጋሉ ፡፡ ይህ ጸጋም እጅግ ታላቅ የሆነ ጸጋ ነው፡፡

 

“በዚያን ጊዜ፡- በሙሴ ላይ በእግዚአብሔርም ላይ የስድብን ቃል ሲናገር ሰምተነዋል የሚሉ ሰዎችን አስነሡ፡፡”(ቁ.11) አለ፡፡ አስቅድመው ሐዋርያትን ሲከሷቸው ትንሣኤውን ይሰብካሉ ሕዝቡን ወደ ራሳቸው ስበዋል ብለው ነበር፡፡ በዚህ ግን ሕመማቸውን ከእነርሱ ላይ ባራቀላቸው ቅዱስ ላይ ክሳቸውን ያቀረቡት፡፡ (ቁ.4፡ 2) እነዚህ ወገኖች በተደረገላቸው ፈውስ የተነሣ ምስጋናን ሊያቀርቡ  እንጂ እርሱ ላይ በጠላትነት እንዲነሡ የሚያበቃቸው አልነበረም፡፡ እንዴት ታላቅ እብደት ነው! በዚህ ቦታ በሥራ የረታቸውን  በቃላቸው ሊረቱትን ሲሟገቱት እናስተውላለን፡፡ በክርስቶስ ላይ የፈጸሙትን በቅዱስ እስጢፋኖስም ላይ የደገሙት በቃል ብቻ ጉልበታቸውን ማሳየት ነው፡፡

 

እነዚህ ወገኖች ምንም ወንጀል ሳያገኙባቸው ያለምንም መረጃ ምንም የሚከሱበት ነጥብ ሳይኖራቸው ክርስቲያኖችን ሲይዙዋቸው አያፍሩም፡፡ እነርሱ ላይ ምስክር ኖሮት እነርሱን ወደ ፍርድ ወንበር የሚያመጣቸው እንዳልነበር አስተውሉ፡፡ ከሆነ ግን እነርሱ ተከራክረው ይረቱዋቸው ነበር፡፡ ነገር ግን ሐሰተኛ ምስክሮችን በእነርሱ ላይ ያስነሡባቸዋል፡፡ ምክንያቱም ሥራቸው ሕገወጥ እንዳይመስልባቸው ነበር፡፡ እነዚህ ወገኖች ክርስቶስን ሕግን ሽፋን አድርገው የሰቀሉት ወገኖች ናቸው፡፡

 

ቢሆንም የሐዋርያትን እንዲሁም የቅዱስ እስጢፋኖስን ስብከት ሰውን  እንዴት እየለወጠ እንደነበር አስተዋላችሁን? በዚህም ምክንያት ነው እነርሱ ላይ በቁጣ ከመነሣት አልፈው በድንጋይ እስከመውገር ደደረሱት፡፡ አሁንም እንዲሁ ናቸው፡፡ እንዲህም በሚፈጽሙበት ወቅት አንዱ ወዳጁን ወደ አንድ ቦታ ወስዶ አንደሚደረገው ዓይነት በየግላቸው የሚያደርጉት ዱለታ አይደለም፡፡ ነገር ግን  ከየአቅጣጫው ተሰባስበው ነበር ሴራቸውን ይጠነስሱ ይነበሩት፡፡ በሴራቸው ጠላቶቻቸውን ሳይቀር ያሳትፉ ምስክር ይሆኑላቸው ዘንድ ያግባቡ ነበር፡፡ ይህን ያህልም ደክመው የእስጢፋኖስን ጥበብ መቃወም አልተቻላቸውም፡፡(ቁ.10)

 

ከኢየሩሳሌም ብቻ ያሉት አይደሉም እርሱን ለመቃወም የተሰለፉት ነገር ግን ከሌሎችም አገራት የመጡትም ጭምር  ነበሩ፡፡ እኒህ ወገኖች “በሙሴ ላይ በእግዚአብሔርም ላይ የስድብን ቃል ሲናገር ሰምተነዋል”አሉ (ቁ.11) እናንተ በድርጊታችሁ እፍረትን የማታውቁ አይሁድ ሆይ የእናንተ ድርጊት በራሱ እግዚአብሔርን እንደመሳደብ አይቆጠርምን? ስለዚህ ክፉ ተግባራችሁ ዞር ብላችሁ አታስቡምን?

 

እነዚህ ወገኖች በዚህም ቦታ ሙሴን ማንሣታቸው የእግዚአብሔር ነገር ለእነርሱ እንደተራ ነገር ተደርጎ ስለሚቆጠር ነው፡፡“… ይህ ከግብጽ ያወጣን ሙሴ ምን እንደሆነ አናውቅምና”(የሐዋ.7፡40)ያሉት እነዚህ ወገኖች፣ የሙሴ ወዳጆች መስለው በመታየት በየትኛውም ሙግታቸው ላይ የሙሴን ስም መላልሰው ያነሡ ነበር፡፡

 

“ሕዝቡንና ሽማግሌዎችን ጻፎችንም አናደዱ”(ቁ.12) ይላል፡፡ በዚያ ዘመን የነበረው ሕዝቡ በቀላሉ የሚታለል ሕዝብ ነበር፡፡ አስቡት እስቲ እንዴት ወደዚህ ድንቅ ማዕረግ የደረሰ ሰው እግዚአብሔርን ሊሳደብ ይችላል? እግዚአብሔርን የሚሳደብ ኃጢአተኛ ቢሆን ኖሮ እንዴት በሕዝቡ ፊት እንዲህ ዓይነት ድንቃድንቅ ተአምራትን ሊያደርግ ይችላል? ነገር ግን አላዋቂና ሥርዐት አልበኛ ሕዝብ ለእነርሱ ክፉ ፈቃድ መፈጸም እንደ ደጀን ሆናቸው፡፡ “በሙሴ ላይ በእግዚአብሔርም ላይ የስድብን ቃል ሲናገር ሰምተነዋል” (ቁ.11) እና “ይህ ሰው በዚህ በተቀደሰው ስፍራና በሕግም ላይ የስድብን ነገር ለመናገር አይተውም”(ቁ.13) እንዲሁም “ይህ የናዝሬቱ ኢየሱስ ይህን ስፍራ ያፈርሰዋል ሙሴም ያስተላለፈልንን ሥርዐት ይለውጣል ሲል ሰምተነዋል”(ቁ.14) ብለው ነበር ቀሊል ልብ ያለውን ሕዝብ በእርሱ ላይ የቀሰቀሱበት፡፡ በዚህ ቦታ ሙሴ ያስተላለፈልንን ሥርዐት አሉ እንጂ እግዚአብሔር የሠጠንን ሥርዐት አላሉም፡፡ በጭፍን ጥላቻም በእርሱ ላይ ተነሣሥተው የእነርሱን ክፋት በእርሱ ላይ በመለጠፍ ሥርዐት አልበኛ ብለው ከሰሱት፡፡

 

ነገር ግን እግዚአብሔርን የሚሳደብ አንድም ሰብዕና የሌለው ሰው መሆኑን እንዲገለጥ “በሸንጎ የተቀመጡት ሁሉ ትኩር ብለው ሲመለከቱት እንደ መልአክ ፊት ሆኖ ፊቱን አዩት” ይህ ቅዱስ በሸንጎው ፊት እንዲህ ብለው ሲያሳጡት እንኳ ርጋታን ተላብሶ ነበር ክሱን ያደምጥ የነበረው፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ በአንድ አጥፊ ላይ እውነተኛ ምስክሮች ምስክርነታቸውን ሲሰጡ እንዲህ ዓይነት ተአምር እንደተከሰተ ጽፎልን አናገኝም፡፡ ነገር ግን በቅዱስ እስጢፋኖስ ላይ የሚመሰክሩ ምስክሮች ሐሰተኞች ስለመሆናቸው እግዚአብሔር ያሳይ ዘንድ   ፊቱ እንደመልአክ ፊት እንዲበራ አደረገው፡፡

 

እኚህ አይሁድ ሐዋርያትን ስለ ክርስቶስ ዳግም እንዳይሰብኩ ከለከሉ  እንጂ ሐሰተኞች ምስክሮች አቁመው አልከሰሷቸውም ነበር፡፡ ይህን ቅዱስ ግን ሐሰተኛ ምስክሮችን አቁመው በሸንጎ ፊት ከሰሱት፡፡ ስለዚህም በሁሉ ፊት የእርሱ ጻድቅነት ይሟገታቸው ዘንድ ከፊቱ ብርሃን መንጭቶ ሲያበራ ታያቸው፡፡ ይህም ሽማግሌዎችንም ሳይቀር አስደንቁዋቸው ነበር፡፡

 

እርሱም  እንዲህ አለ፡-“ወንድሞችና አባቶች ሆይ ለአባታችን ለአብርሃም በካራን ሳይቀመጥ ገና በሁለት ወንዝ መካከል ሳለ ታየው” አለ፡፡(ም.7፡4) በዚህ ንግግሩ የእግዚአብሔር የተስፋ ቃል ከርሰታቸው፣ ከግርዘት፣ ከመሥዋዕት፣ ከቤተመቅደሱ በፊት እንዲኖር፣ ከእነርሱ በጎነት የተነሣ ግርዘትና ሕግ ለእነርሱ እንዳልተሰጣቸው ነገር ግን ምድሪቱ በአብርሃም መታዘዝ ምክንያት እንደተሰጠቻቸው እንዲገነዘቡ አድርጎአቸዋል፡፡ እንዲሁም መገረዛቸው ብቻውን የተስፋውን ቃል ለመቀበል እንደማያበቃቸው  አመለከታቸው፡፡ ከእነዚህ በተጨማሪም ለአማናዊው ሥርዐት ይህ ጥላ እንደሆነ እንዲሁም እግዚአብሔር ወደ አዘጋጀው አገርና ርስት ለመግባት ሲባል  አገርንና ርስትን ጥሎ በእርሱ ትእዛዝ መውጣት ሕግን ማፍረስ እንዳልሆነ ሲያስረዳ “በዚያን ጊዜ ከከለዳውያን አገር ወጥቶ በካራን ተቀመጠ”(ቁ.4)እንዳለ ማስተዋል እንችላለን፡፡

ይቀጥላል……

 

ኢይብቁል ብክሙ መሪር ሥርው /መራራ ሥር አይብቀልባችሁ/ /ዕብ.12፡15/

ዘገብርኤሏ


የአብርሃም ልጆች ነን የሚሉ ነገር ግን የአብርሃምን ሥራ የማይሠሩና የነቢዩ ዳዊት ልጆች ነን የሚሉ የእርሱን ፈለግ የማይከተሉ ዕብራውያንን ቅዱ ጳዉሎስ «መራራ ሥር አይብቀልባችሁ» ሲል መከራቸው፡፡ ዕብራውያን በእግዚአብሔር እናምናለን፤ የእሱ ልጆች ነን እያሉ ይመጻደቁ ስለነበሩ መልካም ሥራ በመሥራት ወደ እግዚአብሔር እንዳይቀርቡ የከለከላቸውን መራራውን ሥር እንዲያስወግዱ አሳሰባቸው፡፡ ሁሉን የሚያይና የሚያውቅ አምላከ ሰማይ ወምድር ኢየሱስ ክርስቶስ እነዚህን ውጫቸውን ያሳመሩ ነገር ግን ውስጣቸውን በኃጢአት ያሳደፉትንና በመራራ ሥር የተመሰለው ኃጢአት በውስጣቸው የበቀለባቸውን ጸሐፍትና ፈሪሳውያንን ሲገስጽ «እናንተ ግብዞች ጻፎች፤ ፈሪሳዉያን በውስጡ ቅድሚያና ስስት ሞልቶ ሳለ የጽዋውንና የወጭቱን ውጭ ስለምታጠሩ ወዮላችሁ፡፡» ብሏቸል፡፡ /ማቴ.23፡25/

ኃጢአትን በሐልዮ ጸንሶ በነቢብ መውለድ፣ በነቢብ ወልዶም በገቢር ማሳደግ መራራ ሥር ነው፡፡ /ማቴ.24፡16/ ይህም ማለት ኃጢአትን ማሰብ አስቦም ሥራ ላይ ማዋል በአጠቃላይ በኃጢአት መውደቅ በሰው ልቡና ውስጥ የሚበቅል መራራ ሥር ነው፡፡ በዚህም «ሐሞትና እሬትም የሚያበቅል ሥር አይሁንባችሁ» /ዘዳ.18፡19/ የተባለውም የሰው ልጅ በመራራ ሥር፣ በሐሞትና በእሬት የተመሰለውን ኃጢአት ከሕይወቱ ካላራቀ መራራ ገሀነመ ዕሳት እጣ ፈንታው ይሆናል፡፡
ከላይ የጠቀስናቸው ሐሳቦች በሙሉ መራራ ሥር የተባለው ኃጢአት መሆኑን የሚያረጋግጡ ናቸው፡፡ ስለሆነም እስኪ በሕይወታችን ውስጥ ሊነቀሉ የሚገባቸው ከእግዚአብሔር መንግሥት የሚለዩንን መራራ ሥሮች በዝርዝር እንመልከት፡፡

1.ዝሙት

ዝሙት አእምሮን የሚያጐድል፣ ሰላምን የሚነሣ፣ ጤንነትን የሚያሳጣ፣ ሕይወትን የሚያበላሽ፣ ጸጋ እግዚአብሔርን የሚያሳጣ /የሚገፍፍ/ በሰው ልቦና ውስጥ የሚበቅልና መነቀል ያለበት መራራ ሥር ነው፡፡ ብዙ ታላላቅ አባቶች ክብራቸውን ያጡት በዝሙት እንደሆነ መጻሕፍት ያስረዳሉ፡፡ ለምሳሌ፡- እስራኤላዊያን ከሞአብ ልጆች ጋር በማመንዘራቸው ብኤልፌጐር የሚባል ጣዖት እንዲያመልኩ አደረጓቸው፡፡ ከዚህም የተነሣ እግዚአብሔርን በማስቆጣታቸው 24 ሺሕ ሕዝብ በአንድ ቀን ተቀስፏል፡፡ /ዘፍ.22፡37፣ ዘኁ.27፡1/ «ኃጢአትን የሚዘራ መከራን ያጭዳል» እንደተባለው፡፡ /ምሳ.22፡1ዐ/
ዝሙት፣ ሴሰኝነትና አመንዝራነት ቅድስናን ከሚያሳጡ ታላላቅ ኃጢአቶች ውስጥ የሚቆጠሩ ናቸው፡፡
የሰው ልጅ በእነዚህ ኃጢአቶች እንዳይወድቅ እግዚአብሔር አምላክ ሁሉን አዋቂ ነውና አንድ ለአንድ በመወሰን ጸንቶ እንዲኖር ጋብቻን ባርኮ ቀድሶ ሰጥቶታል፡፡ «መጋባት በሁሉ ዘንድ ክቡር፤ መኝታውም ንጹሕ ይሁን፣ ሴሰኞችንና አመንዝሮችን ግን እግዚአብሔር ይፈርድባቸዋል፡፡» እንዲል፡፡ /ዕብ.13፡4፣ 1ቆሮ.7፡1/ ዝሙት ከእግዚአብሔር መንግሥት የሚለይ መራራ ሥር ነው የተባለውም ለዚህ ነው፡፡ ሶምሶንም ጸጋውን እንዲገፈፍ ያደረገው ይህው በውስጡ የበቀለው መራራ ሥር ነው፡፡ /መሳ.17፡1/ ይህ ታላቅ ሰው ለእግዚአብሔር የተለየ ናዝራዊ ቢሆንም አንድ ናዝራዊ ማድረግ የሌለበትን የዝሙትን ተግባር ፈጽሞ በመገኘቱ ከክብሩ ተዋርዷል ኀይሉ ተነፍጎታል፡፡ /ዘኁ.6፡1/ ዛሬም ትእዛዛተ እግዚአብሔርን በመጣስና ዝሙት በመሥራት ከክብር እየተዋረድን ያለን ሰዎች ራሳችንን ልንመረምርና መራራውን ሥር በንስሐ በጣጥሰን በመጣል ወደ እግዚአብሔር ልንቀርብ ይገባል፡፡ ለሶምሶን እግዚአብሔር አምላክ ታላላቅ ውለታዎችን ቢውልለትም፤ እሱን ያስጨነቀው አምላክ ያደረገለት ውለታ ሳይሆን ከደሊላ በዝሙት የመውደቅ መንፈስ አእምሮውን አሳጥቶት ነበር፡፡ /መሳ.16፡17/ ይህች ሴት ቃሏን አጣፍጣ የዚህን የተመረጠ ሰው ሕይወት እንዳጠመደችው ዛሬም የብዙዎቹን ሕይወት በዝሙት የሚያጠምዱ እርኩስ መንፈስ ያደረባቸው መራራ ሥር የበቀለባቸው እንዳሉ ማስተዋል ይገባል፡፡
ከክብራችን እንዳንዋረድ የቅዱሳን አባቶቻችንን ፈለግ በመከተል ሥጋችንን ለነፍሳችን አስገዝተን መኖር ያስፈልጋል፡፡ ዓይኖቻችን ወደ ቅዱስ ሥጋውና ወደ ቅዱስ ደሙ የሚመለከቱ መሆን አለባቸው፡፡ «ልጄ ሆይ ወደ ጋለሞታ ሴት ልብህ አይባዝን በጐዳናዋ አትሳት፡፡ ወግታ የጣለቻቸው ብዙ ናቸውና፡፡» /ምሳ.7፡24/ በዝሙት ተወግተው ከወደቁት ወገኖች እንዳንደመር በየትኛውም ቦታ ጥንቃቄ ልናደርግ ያስፈልጋል፡፡

2.ትዕቢት

ሳጥናኤልን ያህል ታላቅ መልአክ ከክብሩ ያዋረደው ሌላው መራራ ሥር ትዕቢት ነው፡፡ ትዕቢት በመራራ ሥር የተመሰለውም ከኔ በላይ ማን አለ በማለት የማይገባውን ይገባኛል እያሰኘ ሌላውን የመናቅ፤ ራስን ከፍ ከፍ የማድረግ መራራ መንፈስ ስለሚያበቅል ነው፡፡ «አንተ የንጋት ልጅ አጥቢያ ኮከብ ሆይ አንተ ወደ ሰማይ ዐርጋለሁ፣ ዙፋኔንም ከሰማይ ከዋክብት በላይ ከፍ ከፍ አደርጋለሁ አልህ፡፡ ነገር ግን ወደ ሲኦል ወደ ጉድጓድም ጥልቅ ትወርዳለህ፡፡» /ኢሳ.14፡12-16/ ብሎ የተናገረለት ሳጥናኤል በትዕቢቱ ምክንያት ነው፡፡ «ትዕቢተኛ የሆነውና ልቡ የሚሳሳው ከእኔ ጋር አይተባበርም፡፡» /መዝ.3፡5/ ተብሎ የተነገረውን የእግዚአብሔርን ቃል ልናስብ ይገባል፡፡
ይሁን እንጂ ትናንት በቅድስት ቤተ ክርስቲያን እቅፍ ቅዱስ ሥጋውንና ቅዱስ ደሙን እየበላና እየጠጣ አድጎ በትዕቢት ምክንያት የበላበትን ወጭት ሰባሪ የሆነ ብዙ ነው፡፡ ክርስቲያን ነኝ እያለ በሀብቱ በጉልበቱ በእውቀቱ፣ በወገኑ የሚኩራራና የሚታበይም አለ፡፡ ይሁን እንጂ ሀብታሙ በደሃው ላይ፣ የተማረው ባልተማረው ላይ አሠሪ በሠራተኛው ላይ የሚታበይ ከሆነ ክርስቲያን ነው ሊባል ከቶ አይችልም፡፡ እውነተኛ የእግዚአብሔር ልጆች መገለጫ፤ ያለው የሌለውን መርዳት፣ የተማረውም ላልተማረው ደሃ ተበደለ ፍርድ ተጓደለ ማለት፣ ስለ ፍቅረ እግዚአብሔር ሲባል ራስን ዝቅ ማድረግ ነው፡፡ በቤተ ክርስቲያን የማገልገል ጸጋ ቢሰጠንም በቸርነቱ መሆኑን ማወቅ ይኖርብናል እንጂ ልንታበይ አይገባም፡፡ በሰንበት ትምህርት ቤት፣ በሰበካ ጉባኤ፣ በቤተ ክርስቲያን ውስጥ የምናገለግል ሁሉ የምናቀርበው የአገልግሎት መስዋዕት በእግዚአብሔር ቸርነት መሆኑን ልንገነዘብ ይገባል፡፡ ልክ «… የታዘዛችሁትን ሁሉ ባደረጋችሁ ጊዜ የማንጠቅም ባሪያዎች ነን ልናደርገው የሚገባንን አድርገናል በሉ፡፡» እንደተባለ፡፡ /ሉቃ.17፡1ዐ/
ስለዚህ ፈሪሃ እግዚአብሔር ሊኖረን እንጂ ልንታበይ አይገባም፡፡ «እግዚአብሔርን መፍራት ባለጠግነት ክብር ሕይወትም ነው፡፡» /ምሳ.22፡4/ እንዳለ ጠቢቡ በምሳሌው፡፡

3. ማስመሰል

መመሳሰልና መስሎ መታየት፣ ለመመሳሰል መጣር የብዙዎች ችግር ነው፡፡ ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አንዳች ፍሬ ባገኝባት ብሎ ወደ አንዲት ዛፍ ሲጠጋ ፍሬ ያፈራች መስላ እንጂ አፍርታ ባለመገኘቷ ምክንያት ለዘላለሙ ፍሬ አይገኝብሽ ብሎ ረገማት፤ ወዲያውም ደረቀች፡፡ /ማቴ.21፡18/  ከዚህ ኀይለ ቃልም የምንረዳው በመስሎ መኖርና ሆኖ አለመገኘት የሚያመጣውን ርግማን ነው፡፡ ማስመሰል መራራ ሥር ነውና ሊነቀል ይገባዋል፡፡ ዛሬም ብዙ ሰው በአፉ የሃይማኖት ሰው ይመስላል፣ እውነታው ግን እንዲህ አይደለም፡፡ ብዙዎች ቤተ ክርስቲያን የሚሔዱ ጾም የሚጾሙ፣ ነገር ግን ከኃጢያት ያልተለዩ፣ በንስሐ መመለስን ችላ የሚሉ፣ ታቦት ሲነግሥ እልል ስለተባለ ብቻ እልል የሚሉ ከዚያ ሲወጡ ግን ኃጢአት ለመሥራት የሚጣደፉና በልባቸው የሸፈቱ ሰዎች የማስመሰሉን መራራ ሥር ከውስጣቸው በንስሐ ነቅለው መጣል አለባቸው፡፡ ሆኖ መገኘት እንጂ መስሎ መታየት አያድንምና፡፡ «ይህ ሕዝብ በከንፈሩ ያከብረኛል፣ ልቡ ግን ከኔ በጣም የራቀ ነው፡፡ የሰውም ሥርዓት የሆነ ትምህርት እያስተማሩ በከንቱ ያመልኩኛል፡፡» /ኢሳ.29፡13፣ ማቴ.5፡8/ እንደተባለው ዛሬም የብዙ ሰው አምልኮ የዚህ ትንቢት መፈጸሚያ ይመስላል፡፡ ስለዚህ ጥዋት ቤተ ክርስቲያን፤ ከሰዓት ቤተ ጣኦት በመሔድ ጊዜን በከንቱ ከማሳለፍ መቆጠብ ያሻል፡፡ ክርስቲያን ነኝ እያለ ጨሌውን፣ የዐውደ ነገሥቱን ጥንቆላ ማመን፣ መናፍስትን መጥራትና የመሳሰሉትን እየፈጸሙ መገኘት በልብ መሸፈት ነውና ልንመለስ ይገባል፡፡ «በሰማያት ያለው የአባቴን ፈቃድ የሚያደርግ እንጂ ጌታ ሆይ፤ ጌታ ሆይ፤ የሚሉኝ መንግሥተ ሰማያት የሚገቡ አይደሉም፡፡» /ማቴ.7፡21/ ተብሏልና፡፡
መስለው ለመኖር የሞከሩ ብዙ ሰዎች ሲጎዱ እንጂ ሲጠቀሙ አላየንም፡፡ ግያዝ ከኤልሳዕ ጋር መስሎ ሲኖር ልቡ ግን ወደ ገንዘብ ሸፍቶ ስለነበር በለምጽ ተመታ፡፡ /2ኛ ነገ.5፡2ዐ/ የይሁዳንም ታሪክ ስንመለከት ከሐዋርያት ጋር ተመሳስሎ እየኖረ ልቡናው በፍቅረ ንዋይ ተነድፎ እንደነበር ነው፡፡ እናም እነዚህንና የመሳሰሉትን የፍቅረ ንዋይ፣ የስስት፣ የእምነት ጎደሎነት ወዘተ መራራ ሥሮች በቶሎ በንስሐ መነቃቀል ያስፈልጋል፡፡
ካህኑም፣ ዲያቆኑም፣ ሰባኪውም፣ ዘማሪውም በአጠቃላይ የቤተ ክርስቲያን አገልጋይ ነኝ የሚል ሁሉም አገልግሎቱ ዋጋ የሚያገኘው ከእግዚአብሔር መሆኑን ከልብ በማጤንና ራሱን በመመርመር የጐደለውን ሊያስተካክል ይገባል፡፡ እያንዳንዷ ሥራችን የምትበጠርበት ጊዜ ይመጣልና፡፡ «መጻሕፍትም ተከፈቱ፤ ሌላ መጽሐፍም ተከፈተ፣ እርሱም የሕይወት መጽሐፍ ነው፡፡ ሙታንም በመጻሕፍት ተጽፎ እንደነበረ እንደሥራቸው መጠን ተከፈሉ፡፡ … እያንዳንዱ እንደሥራው መጠን ተከፈለ፡፡» እንዲል፡፡ /ራእ.2ዐ፡12/
ስለዚህ መልካም ዋጋ ለማግኘት መልካም ሥራ ለመሥራት መጣር ይገባል፡፡ «አምላካችሁ እግዚአብሔርን ተከተሉ እርሱንም ፍሩ ትእዛዙንም ጠብቁ ቃሉንም ስሙ እርሱንም አምልኩ ከእርሱም ጋር ተጣበቁ» /ዘዳ.13፡4/ ስለተባልን ለመልካም ሥራ እሺ እንድንል ያስፈልጋል፡፡ «እሺ ብትሉ፣ ለእኔም ብትታዘዙ፣ የምድርን በረከት ትበላላችሁ፤ እምቢ ብትሉ ግን ብታምጹ ሰይፍ ይበላችኋል፤ የእግዚአብሔር አፍ ይህንን ተናግሯል» ተብሏልና፡፡ /ኢሳ.1፡19/

4. ዓላማ ቢስነት

ዓላማ የሌለው ሰው ከየት ተነሥቶ ወዴት መሔድ እንዳለበት የማያውቅ፣ ካሰበበት የማይደርስ ነው፡፡ ማንም ወደነዳው የሚነዳ፣ በጭፍን የሚጓዝ ሰው ዓላማ ቢስ ሊባል ይችላል፡፡ ዓላማ የሌለው ሰው በጀመረውና በተሠማራበት ተግባር ላይ ጸንቶ አይቆይም፡፡ በተለይ ክርስቲያን ዓላማ ከሌለው በትንሽ ነገር የሚፈተን፣ ሥጋዊ ፍላጐቱ ካልተሟላለት የማያገለግል፣ የሚያማርር፣ በሆነ ባልሆነው የሚያኰርፍ፣ መንፈሳዊነትን ያዝ፣ ለቀቅ የሚያደርግ የጸሎቱ፣ የጾሙ ዋጋ ዛሬውኑ እንዲከፈለው የሚፈልግ ይሆናል፡፡ የሚያገለግልበትንም ዓላማ ያልተገነዘበ ሰው በየደቂቃው እንዲመሰገን ይፈልጋል፡፡ ሰዎች ዓላማቸውን እንዲስቱ በልባቸው ውስጥ የማዘናጋትን ተግባር የሚፈጽም ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስ ስለሆነ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል፡፡ ቅዱሳን አባቶች በተለያዩ ፈተናዎች ውስጥ ቢያልፉም ዓላማን የመሳት መራራ ሥር በውስጣቸው አልበቀለም፡፡ በሁሉም ጸንተው በመቆማቸው ለክብር አክሊል በቅተዋል፡፡
ሙሴ እስራኤልን በምድረ በዳ ይመራ በነበረበት ወቅት የተለያዩ ፈተናዎች ቢያጋጥሙትም ከዓላማው አልተዘናጋም፡፡ ይልቁንም ያህዌህ ንሲ /እግዚአብሔር ዓላማዬ ነው አለ እንጂ፡፡ /ዘዳ. 12፡15/
ዮሴፍ ጽኑ ዓላማ ስለነበረው የተዘጋጀለትን የዝሙት ግብዣ እምቢ አለ፡፡ /ዘፍ. 39/
ሶስና ልትሸከመው የማትችል የሚመስል ፈተና ቢያጋጥማት ንጽሕናዋን ክብሯን ጠብቃ፣ ለአምላኳ ታምና መኖርን ዓላማዋ ስላደረገች የመጣባትን ፈተና በጽናት፣ በታማኝነት፣ በንጽሕና በቅድስና ልታልፍ ችላለች፡፡ /መጽሐፈ ሶስና/  ኢዮብ ዓላማው እግዚአብሔር ስለነበር ይፈራረቅበት የነበረውን መከራ፣ ሥቃይና ችግር ሊያልፍ ችሏል፡፡ ወርቅ በእሳት እንደሚፈተን ሁሉ ተፈትኖ፣ ነጥሮ ታላቅነቱን አስመስክሯል፡፡ /ኢዮ.2፡10/ በአንጻሩ ደግሞ ዓላማቸውን የሚያስት መራራ ሥር በውስጣቸው በመብቀሉ ምክንያት የተጐዱ ከክብራቸው ያነሡ ጥቂቶች አይደሉም፡፡
ለምሳሌ ሳኦልን ብንመለከት እግዚአብሔር አምላክ ከሕዝበ እስራኤል ላይ ንጉሥ እንዲሆን ቢሾመውም የቅንዓት መንፈስ በውስጡ ስለበቀለ እግዚአብሔርን የሚያሳዝን ተግባር ሲሠራ እናያለን፡፡ /1ኛሳሙ. 11፡9፣15፡35/
ዛሬም ትናንት የቤተ ክርስቲያን ልጆች የነበርን፣ እግዚአብሔር ከፍ ስላደረገን፣ ስለሾመን ዓላማችንን የዘነጋን አንታጣምና ራሳችንን ልንመረምር ይገባል፡፡ ከዓላማችን እንድንስት የሚያዘናጉ ነገሮች በርካቶች ናቸው፡፡ ሰው ለገንዘብ፣ ለሥልጣን፣ ለሓላፊ ጠፊ ሀብት ብሎ ዓላማውን ይስታል፡፡ ይሁዳ ምንም እንኳን ከሐዋርያት አንዱ ሆኖ ቢቆጠርም ዓላማው መንግሥተ ሰማያትን መውረስ ሳይሆን ገንዘብን ማሳደድ ስለነበረ አምላኩን እስከ መሸጥ ደረሰ፡፡ «እንጀራዬን የበላ በእኔ ላይ ተረከዙን አነሣ፡፡» ተብሎ የተነገረው ትንቢት ተፈጸመበት፡፡ /መዝ.4ዐ፡9/ ይሄው ዛሬ የነፍሰ ገዳዮችና የክፉዎች ተምሳሌት ሆኖ ይነገራል፡፡ ስለዚህ «ከመልካም ሽቱ መልካም ስም ይሻላል፡፡» እንደተባለ ስማችን በክፉ እንዳይጠራ በዓላማችን እንጽና፡፡ /መክ. 7፡1/ ዓላማችን መንግሥቱን ለመውረስ፣ ስሙን ለመቀደስ ይሁን፡፡ እንደ ዴማስ ወደ ዓለም የሚመለስ መራራ ሐሳብ በውስጣችን እንዳይበቅል ጥንቃቄ እናድርግ፡፡ /2ኛጢሞ. 4፡9/

5. የጥርጥር መንፈስ

«የሚጠራጠር ሰው በነፋስ የተገፋና የተነቃነቀ የባህርን ማዕበል ይመስላል፡፡ ሁለት ሐሳብ ላለው፣ በመንገድም ሁሉ ለሚወላውል ለዚያ ሰው ከጌታ ዘንድ አንዳች የሚያገኝ አይምስለው፡፡» /ያዕ. 1፡6/ በማለት እንደተነገረው ተጠራጣሪ ሰው ከጌታ አንዳች ነገር አያገኝም፡፡ በአሁኑ ወቅት ከጽናታችን እንድንናወጥ የሚያደርጉ ብዙ ነገሮች እንዳሉ ይታወቃል፡፡ ነገር ግን የተጠራበትን ዓላማ ጠንቅቆ የማያውቅ ክርስቲያን በጥርጥር ነፋስ ተነቅሎ ይገነደሳል፡፡ ስለዚህ ጊዜው ከፍተኛ ጥንቃቄ የሚሻው በመሆኑ በማስተዋል መራመድ ያስፈልጋል፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያት በመንፈስ ቅዱስ ገላጭነት ይመጣ ዘንድ ስላለው ክህደትና ሐሳዊ መሲህ «… የሚፈጥንን ጥፋት በራሳቸው ላይ እየተሳቡ የሚያጠፉ ኑፋቄን አሾልከው ያገባሉ፤ … በእነርሱም ጠንቅ የእውነት መንገድ ይሰደባል፡፡» /2ጴጥ.2፡1/ በማለት ተናግረዋል፡፡ በመሆኑም የክርስቶስን አምላክነት የሚጠራጠርና የሚያጠራጥር፣ በቅዱሳን ላይ አፉን የሚከፍት ሐሳዊ መሲህ ቢነሣ የሚያስደንቅ መሆን የለበትም፡፡ ለምን ቢሉ ትንቢቱ ይፈጸም ዘንድ ግድ ነውና፡፡ ዮሐንስም ስለዚህ ነገር «አውሬው ታላቅ ነገርና ስድብን የሚናገርበት አፍ ተሰጠው … እግዚአብሔርንም ለመሳደብ ስሙንና ማደሪያውንም፣ በሰማይም የሚያድሩትን ሊሳደብ አፉን ከፈተ፡፡» ብሎ ጽፏል፡፡ /ራእ.13/ ስለዚህ በልባችን የሚበቅለውን የጥርጥር መንፈስ ከውስጣችን ነቅለን ልንጥል ያስፈልጋል፡፡ «ከራሳችሁ ጽናት እንዳትወድቁ ተጠንቀቁ፡፡ /2ጴጥ.3፡17/ እንደተባልነው ጥንቃቄ ልናደርግ ያስፈልጋል፡፡
በአጠቃላይ መራራ ሥር ኃጢአትና ክርስቲያናዊ ምግባር በአንድ ሰውነት ላይ ሊበቅሉ የማይገባቸው እንክርዳድና ፍሬ ናቸው፡፡ በመሆኑም በንስሐ መከር መለየት ይኖርብናል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስም የመራራ ሥራ ፍሬዎችን የሥጋ ሥራ በማለት ገልጿቸዋል፡፡ «አስቀድሜ እንዳልኩ እንደዚህ ያሉትን የሚያደርጉ የእግዚአብሔርን መንግሥት አይወርሱም ብሏል፡፡ ገላ. 5፡21» ስለዚህ ክርስቲያናዊ ሕይወት እንዲያብብ የክፋት ሥራ የሆኑ ኃጢአቶችን በንስሐ እና በተጋድሎ በተለይም ዝሙት፣ ትዕቢት፣ ማስመሰል፣ ዓላማ ቢስነትና የጥርጥር መንፈስ የመሰሉ መራራ ስሮች በጥንቃቄ መንቀልና ማራቅ ያስፈልገናል፡፡ መራራ ሥሮችን ነቅለን የመንፈስ ፍሬያትን በሰውነታችን እናበቅል ዘንድ የእግዚአብሔር ቸርነት የቅድስት ድንግል ማርያም አማላጅነት አይለየን፡፡

 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

መስቀል ለእኛ ለኦርቶዶክሳውያን

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ

መስከረም 28/2004 ዓ.ም.

ምን አልባት አንድ ሰው የእውነትን እውቀት ቢያስተምር በእውቀቱ ለመማረክ ከጠቢቡ ይልቅ አላዋቂው በጣም የቀረበ ነው፡፡ እርሱንም ወደዚህ እውቀት ለማምጣት ከጠቢቡ ይልቅ አላዋቂው በጣም ይቀላል፡፡ ይህን እውቀት እረኞችና ባላገሮች ፈጥነው ለመቀበል የበቁት እውቀት ነው፡፡ እነርሱ ለሁልጊዜውም አንዳች ጥርጣሬ በልቡናቸው ሳያሳድሩ እውቀቱን እንደ ጌታ ቃል አድርገው ተቀብለውታል፡፡ በዚህ መልክ ጌታችን የአሕዛብን ማስተዋልና ጥበብ አጠፋው፡፡ ይቺ የአሕዛብ ማስተዋልና ጥበብ አስቀድማ ራሱዋን አዋርዳለችና ለዘለዓለም ለምንም የማትጠቅምና የማትረባ አደረጋት፡፡ ይቺ ማስተዋልና ጥበብ ምንም እንኳ የእርሱዋን አቅምና ችሎታ በጌታችን ሥራ ላይ ለመግለጥ ብትሞክርም አልሆነላትም፡፡ ስለዚህም አሁን ራሱዋን ለማላቅ አልተቻላትም፡፡ ምክንያቱም በክርስቶስ የተገለጠው እውቀት እርሱዋን የሚሻ አይደለምና፡፡ ይህ አዲስ የተገለጠው እግዚአብሔርን የማወቅ መንገድ ከእርሱዋ በእጅጉ የላቀ ነው፡፡ እንዲህ ከሆነ ወደ ዚህ ወደ እግዚአብሔር የእውቀት ከፍታ ለመምጣት እምነትና የዋሃት ያስፈልጋል ማለት ነው፡፡ እነዚህ ከውጭ በትምህርት ከምናገኛቸው ይልቅ ሊኖሩን የሚገቡ መንፈሳዊ ሀብታት ናቸው፡፡ ምክንያቱም “እግዚአብሔር የዚችን ዓለም ጥበብ ሞኝነት እድርጎአታል ብሎናልና፡፡

ነገር ግን “እግዚአብሔር የዚችን ዓለም ጥበብ ሞኝነት እንዲሆን አድርጐታል” ሲል ምን ማለቱ ነው? ምክንያቱም ሞኝነትን በእምነት ካለመቀበል ጋር አቆራኝቶ ነውና ያስተማረው፡፡ የዚህ ዓለም ጥበበኞች የሚባሉት በዚህ እውቀታቸው አብዝተው የሚመኩ ቢሆንም ጌታችን ግን እነርሱን ለመጋፈጥ ጊዜውን አላጠፋም ነበር፡፡ መልካም የሆነውን ነገር ፈጽማ ለይታ ማወቅ የተሳናት ይህች ጥበብ ምን ዓይነት ጥበብ ናት? ስለዚህ አስቀድማ የእርሱዋ ጥበብ የማይጠቅምና የማይረባ መሆኑን ከተረዳች በኋላ ጌታችን ደግሞ ሞኝነት እንደሆነ ገለጠው፡፡ ይህች ሰዋዊት ጥበብና ማስተዋል የእግዚአብሔርን ሕልውና በእውቀቱዋ ተደግፋ ማረጋገጥ አልተቻላትም፤ እንዴት ታዲያ ከዚህ በእጅጉ የሚልቀውንና የሚሰፋውን የእግዚአብሔርን ሥራ መረዳትና ማስረዳት ይቻላታል? ስለዚህም ከዚህ እንደምንረዳው የእግዚአብሔርን ጥበብ ለመረዳት የግድ እምነት እንጂ ብዙ ምርምርና ድካም አለማስፈለጉን ነው፡፡ በዚህ መልክ እግዚአብሔር አምላክ የዓለምን ጥበብ ሞኝነት እንዳደረጋት ማስተዋል እንችላለን፡፡

 

እርሱ በወንጌል ሞኝነት ዓለሙን ለማዳን ወድዶአል፡፡ ነገር ግን ሞኝነት ሲል በአላዋቂነት ማለቱ ግን አይደለም በወንጌል ሞኝነት ሲል በሰው ዘንድ እንደ ሞኝነት በሚቆጠር መልኩ ሲለን ነው፡፡ በእርሱ የተገለጠችው ጥበብ ታላቅ የሆነች ጥበብ ናት፤ ነገር ግን ለዓለሙ የገለጠባት መንገድ ግን ሞኝነት ይመስላል፡፡ ከእግዚአብሔር ሞኝነት የሚልቅ ጥበብ ፈጽሞ የለም፡፡ ከዓለሙም ሲያስተዋውቃት ሞኝነት በሚመስል መንገድ ነበር፡፡ ይህችን ጥበብ ወደ ዓለም ሲያገባት ለምሳሌ ልክ እንደ አፍላጠን አሪስጣ ጣሊስ፣ ሶቅራጠስ በፍልስፍና በተካኑት ወገኖች በኩል አልነበረም ፡፡ ነገር ግን በተናቁ ዓሣ አጥማጆች በኩል ነው እንጂ፡፡ እንዲህ ስለሆነም ድሉ እጅግ ታላቅና አንጸባራቂ ሆነ፡፡

ሐዋርያው በመቀጠል ስለመስቀሉ ኃይል ሲገልጽ “መቼም አይሁድ ምልክትን ይለምናሉ፣ የግሪክ ሰዎችም ጥበብን ይሻሉ፣ እኛ ግን የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብካለን ይህም ለአይሁድ ማሰናከያ፣ ለአሕዛብም ሞኝነት ነው፤ የተጠሩት ግን አይሁድ ቢሆኑ የግሪክ ሰዎች ቢሆኑ የእግዚአብሔር ኃይልና የእግዚአብሔር ጥበብ የሆነው ክርስቶስ ነው፡፡” (ቁ.፳፪-፳፬) አለ፡፡

ለዚህ ኃይለ ቃል ሰፊ ትንታኔን መስጠት ይቻላል፡፡በዚህ ቦታ ሐዋርያው ሊገልጠው የፈለገው ነገር እንዴት እግዚአብሔር አምላክ ሰው ከሚያስበው በተቃራኒው መንገድ ሞትን ድል እንደነሣውና ወንጌል ከእግዚአብሔር ዘንድ የተሰጠች ስለመሆኑዋ ነው፡፡ ስለዚህ ሲናገር ምን አለ?፡- አይሁድን በክርስቶስ እመኑ ስላቸው እነርሱ ደግሞ የሞተውን አስነሡትና በአጋንንት ቁራኛ የተያዘውን ፈውሱትና አሳዩን እነዚህን ምልክቶችን ብታሳዩን በእርሱ እናምናለን፡፡ እኛ ግን በምላሹ ስንመልስላቸው እኛስ “የተሰቀለውን ክርስቶስን እንሰብክላችኋለን” እንላቸዋለን፡፡ እንዲህ ዓይነት ቃላችን ፈቃዱ የሌላቸው ትእቢተኞችን ብቻ አይደለም የሚያሸሻቸው፣ ነገር ግን በእርሱ ለማመን ፈቃዱ ያላቸው አይሁድ እንኳ የሚያስበረግግ ቃል ነው፡፡ እንዲህ ሲባል ቃሉ ያን ያህል የሚያስበረግግ ቃል ሆኖ ግን አይደለም፡፡ ይልቁኑ የጠፉትን ወደ እርሱ የሚያቀርብና ለእግዚአብሔር ምርኮን የሚያመጣና ድል የሚነሣ ቃል ነበር፡፡

 

አሕዛብ ደግሞ ቃሉን በንግግር ጥበብ አሳምረን በፍልስፍና መንገድ እንድናቀርብላቸው ይሻሉ፡፡ እነርሱ እንዲህ እንዲቀርብላቸው ቢወዱም እኛ ግን ስለ መስቀሉ እንሰብክላቸዋለን፡፡ ስለዚህም በአይሁድ ዘንድ እንደ ደካሞች ተደርገን እንደተቆጠርን እንዲሁ በእነዚህም ዘንድ እንደሞኞች እንቆጠራለን፡፡ እኛን ከመስማት የሚመለሱት እነርሱ በጠየቁን መልክ ባለማቅረባችን ብቻ ግን አይለደም፤ እኛን ከመስማት የሚመለሱት፣ ነገር ግን እነርሱ ከጠየቁን በተቃራኒው አድርገን በማቅረባችንም ጭምር ነው እንጂ፡፡ ለእነርሱ ለእኛ የመዳን ምልክታችን መስቀል ስለመሆኑ በምክንያት አለመግለጻችን ብቻ አይደለም እኛን ከመስማት እንዲመለሱ የሚያደርጋቸው ነገር መስቀሉ ለእነርሱ የደካማነት ምልክት እንጂ የኃያልነት ምልክት አለመሆኑም ጭምር እንጂ፡፡ በእነርሱ ዘንድ ይህ ጥበብ ሳይሆን ሞኝነትን የሚያሳይ ተደርጎ ነው የሚቆጠረው፡፡

ስለዚህም እነርሱ ኃይልን የሚሰጣቸውን ምልክትንና ጥበብ ሲሹ የጠየቁትን አለማግኘታቸው ብቻ ሳይሆን እነርሱ ከሚመኙት ምልክት በተቃራኒ በማቅረባችንና ክርስቶስን እንዲከተሉት በመስበካችንም ይሰነካከላሉ፡፡ እንዴት ታዲያ እኛ የምንሰብከው የመስቀሉ ኃይል ከመረዳት ያለፈ አይሆን? አንድ በመከራ ውስጥ ላለና ከስቃዩ ለማረፍ መጠጊያ ለሚፈልግ ሰው እኛ እጅግ አደገኛ ወደሆነው የባሕር ማዕበል ውስጥ እርሱን የምንመራውና በዚያ ውስጥ የምናድነው መሆናችንን የገለጽንለት ብንሆን እንዴት እኛን አምኖን ደስ ብሎት ሊከተለን ይችላል? ወይም አንድ ሐኪም የታመመነውን ቁስለኛ ሰው ሕማሙን በመድኃኒት ሳይሆን ቁስሉን ራሱን ደግሞ በማቃጠል እንደሚያድነው እየማለ ቢነግረው እንዴት ሊቀበለው ይችላል? ይህ በእርግጥ ልዩ የሆነ ኃይል ነው፡፡ ስለዚህም ክርስቶስ ሐዋርያትን ወደ ዓለም ሁሉ ሲልካቸው ያለ ምልክት አልሰደዳቸውም፡፡ ነገር ግን ከሚታወቁት ምልክቶች በተቃራኒው የሆኑ ምልክቶችን ያደርጉ ዘንድ ነበር ሥልጣንን የሰጣቸው ፡፡

 

በሥጋው ወራት ጌታችን እንዲህ ዓይነት ከተፈጥሮአዊ ሥርዓት በወጣ መልኩ ምልክቶችን ያደርግ ነበር፡፡ ለምሳሌ ሲወለድ ጀምሮ ዐይነ ስውር በነበረው ላይ ኃይሉን በመፈጸም አሳይቶናል፡፡ የዚህን ሰው የታወሩትን ዐይኖች ጌታችን ሲፈውሳቸው ዐይነ ስውርነትን በሚያባብስ ጭቃ ቀብቶ ነበር፡፡ (ዮሐ.9፥6) በጭቃው ጌታችን ይህን እውር የሆነው ሰው እንደፈወሰው እንዲሁ በመስቀሉ ዓለሙን ወደ እርሱ አቀረበው፡፡ ተቃዋሚዎችን ድል መንሣት የማይቻለውን ኃይልን በማስታጠቅ ድል የሚነሣ አደረገው፡፡

እንዲህ ዐይነትን ተግባር በሥነፍጥረትም ላይ ፈጽሞት እናገኘዋለን፡፡ ፍጥረታትን ሲፈጥራቸው እነርሱኑ መልሶ በሚያጠፋ ነገር ነው ፈጥሮአቸው የምናገኘው፡፡ ለምሳሌ የባሕር ማዕበልን በአሸዋ በመገደብ ለኃይለኛው ማዕበል ደካማ የሆነው አሸዋ ይጠብቀው ዘንድ መሾሙን እናስተውላለን፡፡ ምድርን በውኃ ላይ አጸናት፡፡ ውኃን እጅግ ስስና ቀላል በሆነ ደመና እንዲቁዋጠር አደረገው፡፡ በነቢያትም በኩል በአነስተኛ የእንጨት ቅርፊት ከውኃ ውስጥ ዘቅጦ የነበረውን ብረት አወጣ፡፡ (2ነገሥ.6፥ 5-7) እንዲሁ በመስቀሉ ዓለሙን ወደ እርሱ አቀረበ፡፡ ታላቅ ስለሆነው ኃይልና ጥበብ አታስተውሉምን? እነሆ ከእኛ መረዳት በተቃራኒው በሆነ ኃይል እኛን ወደ እምነት ሲያቀርበን አትመለከቱምን? እንዲሁ መስቀልም ደካማ ሊመስለን ይችላል፤ ነገር ግን በእጅጉ ብርቱ መሆኑ ብቻ ሳይሆን ሰዎችን ወደራሱ የሚስብ ኃይል በላዩ እንዳደረበት ማስተዋል እንችላለን፡፡

ስለዚህ ቅዱስ ጳውሎስ እነዚህን ሁሉ በአእምሮ ውስጥ ሲያመላልሳቸው ቆይቶ በመደነቅና በመገረም “ከሰው ይልቅ የእግዚአብሔር ሞኝነት ይጠበባልና የእግዚአብሔርም ድካም ከሰው ይልቅ ይበረታል”(ቁጥ.፳፭) አለ፡፡ ከመስቀሉ አንጻር ሞኝነትናና ደካማነትን አስቀመጠ ነገር ግን አማናዊ የሆነውን ሞኝነትንና ደካማነት ሳይሆን የሚመስለውን ነገር ነበር የገለጠልን፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ ስለመስቀሉ ኃይል ሲሰብክ በተቃራኒ ጎራ ያሉትን ወገኖች አመለካከታቸውን ሳይጎዳ ነበር የሰበከው፡፡ ፈላስፎች በምክንያት ይህን ኃይል መረዳት እንደማይችሉ ነገር ግን በእነርሱ ዘንድ ሞኝነት የሚመስለው የመስቀሉ ነገር ታላቅ የሆነ ኃይል ያለው መሆኑን ነበር ያስገነዘባቸው፡፡ ስለዚህ ብዙ ወይም ጥቂት ወይም አንድ ተከታይ ያለው ጠቢብ ሰው የት አለ? ፕላቶና ተከታዮቹ እንዴት ያለ አድካሚ በሆነ መንገድ ጥበብን ማግኘት ሻቱ! እነርሱ ለእኛ ስለ መስመር፣ ስለማዕዘን(angle)፣ ስለ ነጥቦች፣ ስለቁጥሮች፣ ተመጣጣኝ ስለሆኑትና ስላልሆኑት ሒሳባዊ ቀመሮች ልክ እንደ ሸረሪት ድር እያወሳሰቡ አስተምረውን ነበር፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ ግን እነዚህ ድሮች በዚህ ምድር ስንኖር አያስፈልጉንም ማለታችን ግን አይደለም ሆኖም ከዚህ ከሚልቀው ጋር ሲተያዩ እምብዛም አስፈላጊዎች አይሆኑም፡፡ ፈላስፋው ፕሉቶ ነፍስ ሕያዊት እንደሆነች ለማስረዳት እንዴት ደከመ! ሲወጣም ሲገባም ስለነፍስ ሕያዊነት ትንታኔ ለመስጠት ሞከረ ነገር ግን ስለነፍስ እርግጠኛውን ነገር ለማስተማር አልበቃም፡፡ ይባስ ብሎ በዚህ ጉዳይ ሰሚ አጣ፡፡

ነገር ግን መስቀል ባልተማሩት ሐዋርያት በኩል ብዙ ሰዎችን ወደ እርሱ አቀረበ፡፡ ዓለሙ ሁሉ ተገልብጦ ክርስቶስን ወደ መከተል ተመለሰ፡፡ የተለመዱትን ብቻ አልነበረም ሲያስተምሩ የነበሩት ነገር ግን ስለእግዚአብሔር፣ እውነተኛ ስለሆኑት አንድ ክርስቲያን ሊላበሳቸው ስለሚገቡ መልካም ምግባራት እንዲሁም በወንጌል ሕይወት እንዴት መመላለስ እንዲገባን በተጨማሪም ስለዓለም ምጽአት በሰፊው ሰብከዋል፡፡ በትህምርታቸውም የተከተሏቸውን ሁሉ ፈላስፎች አደረጉዋቸው፤ ያልተማሩትንም በጥበብ ቃል የሚያስተምሩ መምህራን አደረጓቸው፡፡ ወዳጄ ሆይ ከሰው ይልቅ የእግዚአብሔር ሞኝነት እንዴት እንደሚልቅ ተመልከት፡፡ ምክንያቱም በዚህ ታላቅ በሆነ በመስቀሉ በተገለጠው ኃይል ዓለሙ ሁሉ ድል ተነሣ፤ ብዙዎች የተሰቀለውን ክርስቶስን እየሰበኩ ብዙዎችን ለእርሱ ማረኩ፡፡ እነዚህ እየሰፉና ዓለምን እየከደኑዋት ሲመጡ በተቃራኒ ጎራ ያሉ ወገኖች ግን እየጫጩና እየጠፉ ሄዱ፡፡ ሕያው የሆነው ቃሉ ከሙታን ጋር ውጊያን ገጠመ ድል ነሣቸውም፡፡

ስለዚህም አንድ ፈላስፋ እኔን ሞኝ ሲል የእርሱን እጅግ የበዛውን ሞኝነቱን ይመለከታል፡፡ ምንም እንኳ እኔ በእርሱ አንደበት ሞኝ ብባልም መረጃዎች ግን የሚያሳዩት እኔ ከእርሱ ይልቅ ጠቢብ መሆኔን ነው፡፡ እርሱ እኔን ደካማ ቢል እንዲህ ባለበት ንግግሩ የእርሱን ደካማነት ይረዳል፡፡ ከዓሣ ማጥመድ የመጡት ሐዋርያት በእግዚአብሔር ጸጋ ለመፈጸም የተቻላቸውን ከአሕዛብ ፈላስፎች፣ ንግግር አዋቂዎችና፣ ገዥዎች ወይም በአጭሩ ዓለም ሁሉ ከዚህ ወደዚያ ብዙ ሺህ ጊዜ ቢታትር በእነርሱ ያደረውን ሀብት በድካማቸው ለማግኘት ቢጥሩ አይደለም ማግኘት ሐዋርያት የስተማሩትን ደግመው መናገር አይቻለውም፡፡ በመስቀሉ ያልተሰበከ ምን ነገር አለ? ስለነፍስ ሕያውነት ፣ ስለሥጋ ትንሣኤ ፣ ስለዚች ዓለም አላፊነት፣ ተስፋ ስለምናደረጋት ሕይወት፣ ሰዎች መላእክነትን ስለመምሰላቸው፣ ራስን ባዶ ስለማድረግ እንዲሁም ሌሎችም ወደ ፍጹምነት የሚያደርሱ አስተምህሮዎች የተላለፉበት በመስቀሉ ነው፡፡….

ከዚህ በላይ እኛ ምን ልንል እንችላለን ? ነገር ግን በተግባር እርስ በእርሳችን ያለንን ድንቅ የሆነ መተሳሳሰብን እናጠንክር ፡፡ የጽድቅም ብርሃን ደምቆ እንዲታይ እናድርግ፡፡ ሐዋርያውም እናንተን ለዓለም የምታበሩ ብርሃናት ናችሁ ይላችኋል(ፊልጵ.፪፥፲፭)፡፡ መንፈሳዊው ተግባር ከዓለማዊው ተግባር እንደመላቁ እግዚአብሔር አምላክ ከፀሐይም ከሰማይም ከውቅያኖስም በላይ ታላቅ ሥራን ለዚህች ምድር እንድንፈጽም ሓላፊነትን ሰጥቶናል፡፡ እኛ በሰማይ ላይ የምታበራውን ፀሐይንና ክበቡዋን አይተን እናደንቃለን፡፡ ይልቁኑ ከእርሱዋ በእጅጉ የሚልቀው ብርሃን በእኛ ውስጥ እንዳለ እናስተውል፡፡ ከዚህም ጎን ለጎን እኛ ይህን ብርሃን ካልሠራንበት የዚህ ብርሃን ተቃራኒ የሆነ ድቅድቅ ጨለማ እንደሚነግሥብንም ልብ እንበል፡፡ ጽኑ የሆነው ጨለማ ዓለምን ሲውጣት ዓለም በጭንቅ ውስጥ ትሆናለች፡፡ በእኛ ውስጥ ድቅድቅ ጨለማ ሰፍኖ ሲገኝ ነፍሳችን በጭንቅ ትያዛለች፡፡ ጨለማው በከሃዲያን ወይም በአሕዛብ ላይ ብቻ ያለ አይደለ ነገር ግን በእኛም መካከል ባሉት ክርስቲያናዊ እውቀቱና ሕይወቱ በሌላቸው ላይ ነግሦም ይታያል፡፡

 

ከመካከላችን አንዳንዶች ትንሣኤውን አይቀበሉም፣ አንዳንዶች ደግሞ በጥንቆላና በኮከብ ቆጣሪዎች የሚታመኑ እነርሱ ባሉዋቸውም የሚመሩ ወገኖች ናቸው፡፡ አንዳንዶች ደግሞ ከክፉ ይጠብቀናል ሲሉና አጋንንትንም እንስብበታለን በማለት አሸን ክታቦችን በአንገታቸው ላይ የሚያንጠለጠሉ ናቸው፡፡

ስለዚህም ጉዳይ ጦምን እንያዝ በውጊያውም ረዳት ሁኑኝ፡፡ በእናንተ ክርስቲያናዊ ምልልስ እነርሱን ወደዚህ ወደተቀደሰ ሕይወት ማምጣት ይቻላልና፡፡ እኔ ሁልጊዜ እንደማስተምረው አንድ ሰው ክርስቲያናዊ ስብዕናን አስመልክቶ ሌሎችን ከማስተማሩ አስቀድሞ ራሱን ሊያስተምር ይገባዋል እላለሁ፡፡ እርሱን የሚሰሙት ከቅድስና ሕይወት ወጥተው እንዳይመላለሱ አርዓያ ሊሆናቸው ይገባል፡፡ በዚህም መልክ በመመላለሰ አሕዛብ ስለእኛ በጎ የሆነ አመለካከት እንዲኖራቸው እናድርግ፡፡ ወንጌልን በሕይወታችን ለእነርሱ በመስበካችን ከእነርሱ የምንቀበለው መከራ ይኖራል ነገር ግን አላፊ ነው፡፡

ይህን በሕፃናት አታስተውሉትምን፡፡ አንዳንዴ ልጆች በአባታቸው እቅፍ ሳሉ በቁጣ የአባታቸውን ጉንጭ በጥፊ ሊመቱት ይችላሉ፤ ነገር ግን አባት ልጁ ቁጣውን በእርሱ ላይ በመግለጡ በልጁ አይቆጣም ይልቅኑስ በእርሱ ዘንድ እጅግ ጣፋጭ ይሆንለታል፡፡ ቁጣው ከልጁ ላይ ባለፈ ጊዜ ደግሞ አባት ይበልጥ ደስ ይለዋል፡፡ እንዲሁ እኛም ለኢአማንያን እናድርግ ልክ ልጅ እንዳለው አባት እንሁን፡፡ ይህን እንደስንቅ ይዘን ለእነርሱ የክርስቶስን ወንጌል እንስበክላቸው፡፡ ሁሉም አሕዛብ በእኛ ዘንድ እንደ ሕፃናት ናቸውና፡፡ እንዲህም እንደሆነ የእነርሱ አንዳንድ ጸሐፍት “ይህ ሕዝብ እንደ ሕፃን ነው ከአሕዛብም አንድም አረጋዊ ሰው የለም” ብለው ቃላችንን ያረጋግጡልናል፡፡ ሕፃናት የሚጠቅማቸውን ነገር ሊለዩ አይችሉም፤ አሕዛብን ሁል ጊዜ እንደ ሕፃናት ጨዋታ ወዳዶች ናቸው፡፡ በአፈር ላይ ይንደባለላሉ በከንቱ ነገር በቀላሉ ይወሰዳሉ ከንቱ በሆነም ነገር በፍቅር ይወድቃሉ፡፡ ለሕፃናት የሚጠቅም ነገርን ስንነግራቸው ጆሮ ሰጥተው አያዳምጡንም ከዚህ ይልቅ እኛ ስንናገር እነርሱ ይስቃሉ፡፡ አሕዛብም እንዲሁ ናቸው፡፡ እኛ ስለመንግሥተ ሰማያት ስንሰብክላቸው እነርሱ ይስቃሉ፡፡ ከሕፃናት አፍ በብዛት የሚወርደው ለሃጭ ምግቡ ላይ ሲያርፍ ምግቡን እንዲያበላሸው እንዲሁ ከአሕዛብ አንደበት የሚወጡ ቃላት ከንቱዎችና የረከሱ ናቸው፡፡

ለሕፃናት የሚስፈልጋቸውን ምግብ እንኳ ብንሰጣቸው ክፉ የሆነ ቃላት ከአንደበታቸው እያወጡ ሊነጫነጩብን ይችላሉ እኛም እነርሱን በመታገሥ እናሳልፋቸዋለን፡፡ ሕፃናት አንድ ሌባ ወደቤታቸው ገብቶ የቤቱ ቁሳቁሶችን እየወሰደ ቢያዩት ዝም ብለው ከመመልከትና እንደ ተባባሪ ወገን ሆነው ሲስቁ ከመገኘት ባለፈ እርሱን አይቃወሙትም፡፡ ነገር ግን እነርሱ ከሚጫወቱበት እቃ አንዱ የተወሰደባቸው እንደሆነ የወሰደባቸው ሰው ለመጉዳት ሲጥሩ ሲያለቅሱና በንዴት መሬቱን ሲጠበጥቡት እናስተውላቸዋለን፡፡ አሕዛብም እንዲሁ ናቸው፡፡ ሰይጣን ነፍሳቸውን የሚጠቅመውን መንፈሳዊ ሀብት ሲዘርፋቸው ከዚህም አልፎ ለሕይወታቸው አስፈላጊ የሆነውን ሲያሳጣቸው እያዩ ይስቃሉ፡፡ እንዳውም ከእርሱ ጋር እንደ ጓደኛ ሲተባበሩት ይገኛሉ፡፡ ነገር ግን አንድ ሰው ከእነርሱ እንደ ሕፃን መጫወቻ የተናቀን እቃን ሲወስድባቸው ቢመለከቱ ልክ እንደ ሕፃን ይጮኻሉ ያነባሉ፡፡ ሕፃናት ራቁታቸውን ስለመሆናቸው እንደማያስተውሉ አሕዛብም እንዲሁ ናቸው፡፡ ስለዚህም ሕጋዊው ተራክቦው እነርሱን ሲያሳፍራቸው ሕገወጡ መዳራት ግን አያሳፍራቸውም፡፡

እናንተ በዚህ ትምህርቴ ልትረኩና ደስታችሁን በእልልታ ልትገልጡልኝ ትችሉ ይሆናል ነገር ግን ከደስታችሁ ጋር በእነርሱ ተግባር ተስባችሁ እንዳትወሰዱ ለራሳችሁ ጥንቃቄን እንድታደርጉ ልመክራችሁ እወዳለሁ፡፡ ስለዚህም አዋቂዎች ትሆኑ ዘንድ እለምናችኋለሁ፡፡ እኛ እንደ እነርሱ ሕፃናት ከሆንን እንዴት አዋቂዎች እንዲሆኑ እነርሱን ማስተማር ይቻለናል? እንዴትስ እነርሱን ሞኝነት ከሆነው ከሕፃናዊ ድርጊታቸው መመለስ እንችላለን? ስለዚህ ተዋዳጆች ሆይ ወደ ክርስቶስ የእውቀቱ ከፍታ እንድንደርስና የመንግሥቱ ወራሾች እንድንሆን እራሳችንን አዋቂዎች እናድርግ፡፡ ሰው እንሁን፡፡ በጌታችን በመድኃኒታችን በኢየስሱ ክርስቶስ ፍቅርና ርኅራኄ ለእግዚአብሔርና መንፈስ ቅዱስ ክብር ምስጋና ይሁን ዛሬም ዘወትርም ለዘለዓለሙ አሜን፡፡

 

 

ዘመነ ጽጌ

መሠልጠን ማለት ግን ምን ማለት ነው?!

በዲ/ን ቴዎድሮስ በየነ

 

ሥልጣኔ ሲተነተን አንድ ገጽታ፣ አንድ መልክ፣ አንድ ወጥ ሳይሆን ብዙ መልኮች፣ ብዙ ገጽታዎች እንዳሉት ማጤን ይገባል፡፡ ሥልጣኔ የሰው ልጅ አካባቢውን ለኑሮ እንዲስማማው፣ እንዲመቸው ለማድረግና ለሕይወቱ የተመቻቸ ሥፍራ ለማድረግ የዕለት ተዕለት ተግባር ውስጥ ቀስ በቀስ የተከሰተ ነው፡፡

በዚህ ረገድ ሥልጣኔ ጥንትም የነበረ፣ ዛሬም ያለ፣ ለወደፊትም የሚኖር የሰው ልጅ የተፈጥሮ እንቅስቃሴ ነው፡፡ ሆኖም ግን ስለ ሥልጣኔ ብይን ሲሰጥ፣ ስለ መግለጫው ሲነገር፣ ስለ ጥቅሙ ሲዘመር፣ ስለ ግቡ /መዳረሻው/ ሲታተት፤ ሥልጣኔ ከቁሳዊ ነገር መሟላትና ከሥጋዊ ድሎትና ምቾት ጋር ብቻ ሲያያዝ ይስተዋላል፡፡ ለዚህም ይመስላል የሥልጣኔን ክስተት በዓይን በሚታዩ፣ አብረቅራቂና ሜካኒካዊ በሆኑ ነገሮች ብቻ እንድናይ ከታች ጀምሮ በትምህርት ቤት እንድንማረው የሆነው፡፡ በሚዲያ ዘወትር እንድንሰማው የተደረገው፡፡ከበደ ሚካኤል ስለ ሥልጣኔ ምንነት ሲናገሩ እንዲህ ይላሉ፡፡

 

“ሰዎች ራሳቸውን ለማረምና ኑሯቸውን ለማሻሻል ሲሉ በሥጋና በመንፈስ ያፈሩት ከመጀመሪያ ጀምሮ አሁን ድረስ የተከማቸው የሥራ ፍሬ ሥልጣኔ ይባላል፡፡”

በእኚህ ኢትዮጵያዊ ጸሐፊ የሥልጣኔ ምንነት ገለጻ ውስጥ በዚህ ዘመን ሚዛን ላይ ያልወጡ ታላላቅ ቁምነገሮችን አምቆ ይዟል፡፡ ከነዚህም ውስጥ “በሥጋና በመንፈስ” በማለት ለሰው ልጅ የህላዌው መሠረት፣ የደስታው ምንጭ ሥጋዊ ፣/ቁሳዊ/ ነገር ብቻ እንዳልሆነ አስምረውበታል፡፡ መንፈሳዊም ፍሬም ሥልጣኔ እንደሆነ፡፡ ሥልጣኔ ከመጀመሪያ ጀምሮ አሁን ድረስ የተከማቸ የሥራ ፍሬ ነው ሲሉም፤ ሥልጣኔ የዛሬ ሦስት መቶ ወይም አራት መቶ ዓመት ክስተት ብቻ አይደለም ማለታቸው ነው፡፡

ዘመናዊ ሥልጣኔን ከምዕራባውያን ሥልጣኔ ጋር ብቻ አያይዞ የሥልጣኔ መልክና ገጽታ በምዕራባውያን መስታወት ብቻ የሚታይ እንዳልሆነም የጸሐፊው እይታ ያሳያል ፡፡

 

ዛሬ በብዙ ኢትዮጵያውያን ዘንድ ሥልጣኔ ማለት ምዕራባዊ መስሎ መቅረብ፣ የምዕራብ ቋንቋን መናገር፣ የምዕራባውያንን የአኗኗር ዘይቤ መያዝ ይመስላል፡፡ እስከ ቅርብ ጊዜ ድረስ በኢትዮጵያውያን ሠርግ ሲዘፈን እንደነበረው “የእኛ ሙሽራ ኩሪባቸው በእንግሊዝ አናግሪአቸው” የምዕራብ ቋንቋ መናገር የኩራት ምልክት፣ የሥልጣኔ ምልክት ነበር፡፡ ይህ ግን ስህተት እንደሆነ ኤቪሊንዎ የተባለ አንድ ምዕራባዊ ጸሐፊ ኢትዮጵያ ኋላቀር ነች እያሉ የሚተቹትን በነቀፈበት ጽሑፉ እንዲህ ይላል፡-

“የአንድን ኅብረተሰብ ትልቅነት የምትገምተው አውሮፓን ስላልመሰለ ወይም የ”ሰለጠኑ” አገራትን ስላልመሰለ ሳይሆን በራሱ እምነትና የእሴት ስልት ውስጥ የተቃረነ ነገር ሲሠራ ነው፡፡”

የዚህ መጣጥፍ ዐቢይ ጭብጥ ሥልጣኔ ከራስ እሴት አለመቃረን ነው የሚል ነው፡፡ ሃይማኖታዊ ትውፊታችን፣ ባህላችንና ታሪካችን የኢትዮጵያውያን እሴቶች ምንነትን ይነግሩናል፡፡ ከእነዚህ ውስጥ ዛሬ እዚህ ላይ የምናየው ስለ ከበረው የዳኝነት /ፍትሕ/ ሥርዓት እሴታችን ነው፡፡ በኢትዮጵያ ረዥም ዘመን ታሪካችን የዳኝነት ሥርዓት የተከበረ ነው፡፡ ፈረንጆች “the rule of law /ሕጋዊ ሥርዓት/” የሚሉትን የኢትዮጵያ ሕዝብ “የሕግ አምላክ” ይለዋል፡፡

በቆየው የኢትዮጵያ ባሕል አንድ ሰው ከመንገድ ላይ ባላጋራውን ካየ “በሕግ አምላክ ቁም” በማለት ብቻ ባላጋራውን አስቁሞ የነጠላዎቻቸውን ጫፍ ቋጥረው /ተቆራኝተው/ ያለ ፖሊስ አጀብ ወደ መረጡት ዳኛ ዘንድ ሄደው ፍርዳቸውን ይቀበሉ ነበር፡፡

“በቆረጡት በትር ቢመቱ፤ በመረጡት ዳኛ ቢረቱ፤ የእግዜር ግቡ ከብቱ፡፡” የሚባለውም ለዚህ ነው፡፡

ኢትዮጵያውያን በቀድሞ ዘመን “የተበደለ ከነጋሽ፤ የተጠማ ከፈሳሽ” ብለው፤ የተጠማ ውሃን እንደሚሻ ሁሉ የተበደለም ጉዳቱን ለንጉሡ አሰምቶ ትክክለኛ ፍርድ እንደሚያገኝ ያምኑ ነበር፡፡ በዚህም ምኞትና ሐሳቡን የፈጸሙ የመንፈስ ልዕልና ደረጃቸውን ያሳዩ ፈታሔ ጽድቅ /እውነተኛ ዳኞች/ በታሪኩ አይቷል፡፡ አጼ ዘርአያዕቆብ /15ኛው መቶ ክ/ዘ/፤ ልጃቸው የደሀ ልጅ ገድሎ በዳኞቻቸው ዘንድ በቀላል ፍርድ ስለ ተለቀቀ ይግባኙን ንጉሡ ወስደው የሞት በቃ ፈርደው እንዳስገደሉት ይታወቃል፡፡ ይህ ምንም ርትዕ ቢሆን፤ ከአብራክ በተከፈለ ልጅ ላይ ሞትን መፍረድ ሐቀኝነት ነው፡፡ በሌላ ዘመንና ቦታም ይህ ተመሳሳይ ታሪክ በትግራዩ ራስ ልዑል ሚካኤል ስሑል /18ኛው መ/ክ/ ተፈጽሟል፡፡ ሁለቱም ከግል ጥቅማቸው በተቃራኒ ቆመዋል፡፡ ይህ ነው ኢትዮጵያዊው መልካም እሴት፡፡ ሁለቱም መሪዎች የኢትዮጵያ ሕዝብ ፍትሕ ሲጓደል በብርቱ እንደሚያዝን፤ ምንም የተወሰደው ሀብት ዋጋው ያነሰ ቢሆን በዳኝነት መዛባት እጅግ አድርጎ እንደሚቆጭ ያውቃሉ፡፡ “በፍርድ ከሄደችው በቅሎዬ፤ ያለ ፍርድ የሄዳችው ጭብጦዬ ታሳዝነኛለች” የሚል ጽኑ የፍትሕ ጥማት እምነቱ እንደሆነ ያውቃሉ፡፡ እነርሱም የርትዕ ፍርድ ታላቅነት አሳዩት፡፡

ስለዚህም የአንድ ሥልጡን ማኅበረሰብ አንዱ መገለጫው ይህን ከመሰለ ባሕላዊ እሴቱ ጋር አለመጋጨቱ፤ አለመቃረኑ ነው፡፡ ስለ ሥልጣኔ ስናወራ ለሥጋ እርካታ መገለጫ የሆነችውን የአብረቅራቂ ቁስ ሙሌትን ብቻ ይዘን መጓዝ የለብንም፡፡ የከበሩ የባሕልና የታሪክ እሴቶቻችንም የሥልጣኔ ማነጸሪያዎች ናቸው፡፡ የሰው ልጅን ማንነትና ፍላጎት በቁሳዊ ነገር ብቻ መመዘንም፤ ሰውን ከሰውነት ደረጃ ማውረድ ነው፡፡ በዚህ መተማመን ከተደረሰ አንድ ሥልጡን ማኅበረሰብ ለመገንባት በምናደርገው ጉዞ ውስጥ ሥልጣኔን በግንጥል ጌጧ ሳይሆን በሙሉ ክብሯ እንረዳታለን ማለት ነው፡፡

ዛሬ ጊዜና ታሪክ በሰጡን ኃላፊነት ላይ ያለን ሁሉ “ደሀ ተበደለ ፍርድ ተጓደለ” የማንል ከሆነ፤ ከግል ጥቅም ይልቅ ለብዙኃኑ ጥቅም ካልቆምን? የሰው እንባ እሳት ነው ያቃጥላል ካላልን? ከራሳችን የእምነትና የእሴት ስሌት በተቃራኒ ስለቆምን በእውነት አልሰለጠንም፡፡

ውድ አንባቢዎች አፄ ዘርአያዕቆብና ራስ ልዑል ሚካኤል ስሑል በልባቸው ካለው የእምነትና የእሴት ስሌት በተቃራኒ ያልቆሙበት ምክንያት /ሠልጥነው የታዩበት ምሥጢር/ የሚከተሉት አራቱ ይመስሉኛል፡፡

1. እግዚአብሔር አለ፤ እሱ ይፈርዳል፤ በምንሰጠው ፍርድ እሱ ይመለከታል ብለው ማመናቸው፡፡

2.  ሕሊና አለ፤ እሱን ማምለጥ አይቻልምና ብለው ለሕሊናቸው በመገዛታቸው፡፡

3. ታሪክ አለ፤ ታሪክ ይፋረደናል፤ የምንሠራውን ነገር ለታሪክ ትተነው የምንሄድ ነን፤ ከታሪክ ማምለጥ አንችልም ብለው በጽናት መቆማቸውና፣

4.  ሕዝብ አለ፤ የተደረገውን ስለሚያውቅ ይመለከተናል፡፡ ይታዘበናል፡፡ ከእነዚህ ነገሮች ማምለጥ አንችልም ብለው በመንፈሳዊ ወኔ መቆማቸው ነው፡፡

ስለ እውነተኛ ዳኝነት ከቱባ ባሕላችን ውስጥ መዘን ስናጠና የምናገኘው የትልልቆቹን መሪዎች፣ የከበሩት አበውና፣ የሚደነቁት እመው ያልተዛባ ፍርድ ክዋኔ ምሥጢሩ፤ በምንሠራው ሥራ፤ በምንሰጠው ፍርድ እግዚአብሔር፣ ሕሊና፣ ታሪክና ሕዝብ አለ ብለው ማመናቸው ነው፡፡ ከሰፈር የዕቁብ ዳኝነት እስከ ሀገር ማስተዳደር፤ ከማኅበር ሙሴነት እስከ ቤተ ክርስቲያን መምራት የቻለ ሰው በሚያስተላልፈው ውሳኔና በሚሰጠው ፍርድ ውስጥ ከላይ ያየናቸውን አራቱን የባሕላችንን እሴቶች በልቡናው ጽላት ቀርጾ በእነርሱ መመራት ካልቻለ፡፡ ፍትሕ ትጨነግፋለች፡፡ እውነት ከምድሩ ትጠፋለች፡፡ ፍቅር ጓዟን ጠቅልላ ትበናለች፡፡ ክህደት ታብባለች፡፡ ማስመሰል ትነግሳለች፡፡ ውሸት ትወፍራለች፡፡ ሥልጣኔ ቅዥት ትሆናለች፡፡

ይቆየን…..

መስቀል ለእኛ ለኦርቶዶክሳውያን

በዲ/ን ሽመልስ መርጊያ
ቀን ፡ መስከረም 16/2004 ዓ.ም.

መስቀል ለእኛ ለኦርቶዶክስ ክርስቲያኖች ልዩ የሆነ መንፈሳዊ አንድምታ አለው ፡፡ በመስቀል እነሆ አሮጌው ሰዎችንን በመስቀልና ከጐኑ በፈሰሰው ውኃ ተጠምቀን በመቅበር አዲሱን ሰው ክርስቶስን ለብሰን ተነሥተናል(ኤፌ.4፥22-24)፡፡ በመስቀል እርግማናችን ተወግዶ የኃጢአት ስርየትን አግኝተናል ፡፡ በመስቀሉ ላይ ከተሰዋው ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙ በመመገብ ከሚያፈቅረን ከጌታችን ከመድኃኒታችን ከኢየሱስ ክርስቶስ ጋር ፍጹም የሆነ ተዋሕዶን መሥርተናል(ማቴ.26፥26) ፤ እርሱ በእኛ ፣ እኛም በእርሱ የሆንበት ሰማያዊ ማዕዳችን መስቀሉ ነው (ዮሐ.6፥56) ፡፡

በመስቀሉ በአዳምና በሔዋን መተላለፍ ምክንያት በእኛ ላይ ጸንቶ የነበረው የፍርድ ትእዛዝ ተሽሯል(ቆላ.2፥14)፡፡ በብሉይ ለሙሴና ለእስራኤል ዘሥጋ እግዚአብሔር አምላክ በምስክሩ ድንኳን ውስጥ ባለችው የቃል ኪዳኑ ታቦት ላይ  ሆኖ በደመና አምድ ይገለጥላቸው ነበር(ዘጸአ.33፥9) ፡፡ ቢሆንም ወደ ቅድስተ ቅዱሳን የምታገባዋ ጎዳና ተዘግታ ነበር ፡፡ ስለዚህ ቅዱስ ጳውሎስ “ካህናት አገልግሎታቸውን እየፈጸሙ ዘወትር በፊተኛይቱ ድንኳን ይገቡባታል በሁለተኛይቱ ግን ሊቀ ካህናት ብቻውን በዓመት አንድ ጊዜ ይገባባታል እርሱም ስለ ራሱና ስለሕዝቡ ኃጢአት የሚያቀርበውን ደም ሳይዝ አይገባም ፤ ፊተኛይቱም ድንኳን በዚህ ገና ቆማ ሳለች ወደ ቅድስት የሚወስደው መንገድ ገና እንዳልተገለጠ መንፈስ ቅዱስ ያሳየናል”(ዕብ.9፥6-) ብሎ ተናገረ ፡፡

እነሆ እግዚአብሔር በደመና አምድ የሚገለጥበት የሥርየት መክደኛው ወይም የምህረት ዙፋኑ የተባለው የቃል ኪዳኑ ታቦቱ የመስቀሉ ምሳሌ ነው ፡፡ ምንም እንኳ እግዚአብሔር አምላክ በደመና አምድ የሚገለጥበት ሥፍራ የሥርየት መክደኛ (mercy seat) የምህረት ዙፋን ይባል እንጂ የጌታ ምህረት ለአዳም ልጆች ገና አልተፈጸመላቸውም ነበር፡፡ ነገር ግን ወጣ ላለው ነገር ጥላ አለውና መስቀሉን ታቦቱ አድርጎ በእግዚአብሔርና በሰው ፣ በቅዱሳን መላእክትና በሰዎች መካከል የነበረውን የጥል ግርግዳ አፍርሶ እርቅን ከሰው ልጆች ጋር ፈጸመ ፡፡ የልዩነት መጋረጃው ተቀደደ መስቀሉንም ዙፋኑ በማድረግ በምህረት ለእኛ ታየ (ዕብ.4፥16) ፡፡

በመስቀሉ የእግዚአብሔር ልጅነትን ሥልጣን አገኘን(ዮሐ.1፥12) ፡፡ በመስቀሉ የርስቱ ወራሾች ፣ ቅዱስ ሕዝብና የመንግሥቱ ካህናት ተባልን(1ጴጥ.2፥9) ፡፡ በመስቀሉ አባ አባ የምንልበትን የልጅነትን መንፈስ ተቀበልን(ሮሜ.8፥15) ፡፡ በመስቀሉ የመንፈስ ቅዱስ ቤተመቅደሶች ተሰኘን(1ቆሮ.3፥16) ፡፡ በመስቀሉ አካላችን የሆነውን በጥምቀት የለበስነውን ክርስቶስን የምናገለግልበትን ልዩ ልዩ የመንፈስ ቅዱስ ጸጋዎችን ተቀበልን(ገላ.3፥27፣ 1ቆሮ.12፥4-11)፡፡ እነሆ እኛ አሁን በክርስቶስ አዲስ ፍጥረታት ተሰኝተናልና አገራችንም በሰማያት ነውና እሳትም መንፈስም በሆነው መንፈስ ቅዱስ ተጠምቀን እሳታዊያንና መንፈሳውያን የሆኑትን መላእክትን መስለናቸዋልና ለአዲሱ ተፈጥሮአችን የሚስማማ ሰማያዊ ማዕድ ተዘጋጀልን(ኤፌ.2፥10 ፤ ፊልጵ.3፥20፤ ማቴ.22፥31) ፡፡ ማዕዱም የጌታችን የመድኃኒታችን የኢየሱስ ክርስቶስ ቅዱስ ሥጋውን ክቡር ደሙን ነው፡፡ ይህ ሰማያዊ ማዕድ ለነፍሳችንም ለሥጋችንም ሕይወትና መድኃኒት ነው፡፡ በመስቀሉ ላይ በተሰዋው ቅዱስ ሥጋውና ክቡር ደሙም ከመለኮታዊ ርስት ተካፋዮች (2ጴጥ.1፥4) ፡፡ ስለዚህም ነው እኛ ኦርቶዶክሳውያን የጌታችን ቅዱስ ሥጋ ክቡር ደሙ ለሚፈተትበት የመስቀሉ አምሳል ለሆነው  የምህረት ቃል ኪዳን ታቦቱ ልዩ አክብሮትና ፍቅር ያለን ፡፡

እኛ ኦርቶዶክሳውያን መስቀሉን ከክርስቶስ ክርስቶስን ከመስቀሉ ነጣጥለን አንመለከትም፡፡ ክርስቶስንም ስናስብ በመስቀሉ ስለእኛ የተቀበለውን መከራ እናስባለን ፡፡ መስቀሉንም ስንመለከት እርሱን ዙፋን አድርጎ ባሕርያችንን ያከበረውን ክርስቶስን አናስተውለዋለን ፡፡ መስቀል ማለት ለአንድ ኦርቶዶክሳዊ ክርስቲያን ወንጌል ማለት ነው ፡፡ ከልደቱ እስከ ትንሣኤው መስቀሉን ጠቅሰን እንሰብካለን ፡፡ ይህ ነው የመስቀሉ ቃል ፡፡መስቀል ምንድን ነው ቢሉን ክርስቶስ ስለእኛ ድኅነት ሲል የተሰቀለበት የክብር ዙፋኑ ነው እንላቸዋለን ፡፡ ማን ነው እርሱ ቢሉን የባሪያውን መልክ ይዞ ከቅድስት ድንግል ማርያም የተወለደው እግዚአብሔር ቃል ነው ብለን መልስ እንሰጣቸዋለን ፡፡ ስለምን በመስቀል ላይ መዋል አስፈለገው ብለው ቢጠይቁን በአዳም መተላለፍ ምክንያት በእኛ ላይ የተፈረደውን የሞት ፍርድ በሞቱ ሽሮ ሕይወትን ሊሰጠን እንላቸዋለን፡፡ ሞቶ ቀረ ወይ ብለው ቢጠይቁን ደግሞ ”ሕያውን ከሙታን መካከል ስለምን ትፈልጉታላችሁ ተነሥቶአል”(ሉቃ.24፥5)እንላቸዋልን፡፡ የመስቀሉ ቃል ለእኛ ጥልቅ የሆነ ትርጉም አለው ፡፡

ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ የቆሮንቶስ መልእክትን በተረጎመበት በአራተኛው ድርሳኑ  ሐዋርያው ቅዱስ ጳውሎስ “የመስቀሉ ቃል ለሚጠፉት ሞኝነት ለእኛ ለምንድን ግን የእግዚአብሔር ኃይል ነውና ፡፡ የጥበበኞችን ጥበብ አጠፋለሁ ፣ የአስተዋዮችንም ማስተዋል እጥላለሁ ተብሎ ተጽፎአልና ፡፡ ጥበበኛ የት አለ ? ጻፊስ የታለ ? የዚች ዓለም መርማሪስ የት አለ ? እግዚአብሔር የዚችን ዓለም ጥበብ ሞኝነት እንዲሆን አላደረገውም? ” (1ቆሮ.1፥18-20) ብሎ የተናገረውን ኃይለቃል ሲተረጉም እንዲህ ይላል ፡፡ “በጽኑ ደዌ የተያዘና በጣር ላይ ላለ ሕመምተኛ ጤናማ የሆነ ምግብ አያስደስተውም ፤ ወዳጆቹንና ዘመዶቹን እንደታላቅ ሸክም ይቆጥራቸዋል ፡፡ ለእርሱ ያላቸውንም መቆርቆር ፈጽሞ አያስተውልም ፤ ይልቁኑ ሰላምን እንደሚነሡት ቆጥሮ ይጠላቸዋል ፡፡ እንዲህ ዓይነት ጠባይ በኃጢአት ምክንያት በነፍሳቸው በጠፉት ላይም ይታያል ፡፡

እነዚህ ወገኖች ወደ ድኅነት የምትወስዳቸውን ጎዳና ፈጽመው አያውቋትም ፡፡ ይህ ጤናማ ከሆነ ተፈጥሮ የሚመነጭ አይደለም ከተያዙበት በሽታ እንጂ፡፡ እነዚህ ወገኖች ልክ እንደ አእምሮ ሕመምተኛ ሰው ስለእነርሱ መዳን የሚያስቡላቸውን ይጠላሉ፡፡ ከዚህም አልፈው በእነርሱ ላይ ጥቃትን ለማድረስ ይነሣሣሉ፡፡ እንዲህ ዓይነት ጠባይ በኢአማንያንም ላይ የሚታይ ጠባይ ነው፡፡እነዚህ ወገኖች እነርሱን የሚያስቱዋቸውን ከመጠን በላይ ይወዱዋቸዋል እነርሱንም ለመገናኘት ይናፍቃሉ፡፡ እነዚህ ወገኖች መልካም ወዳጆቻቸውን ለይተው ለማወቅ አለመቻላቸው በሽታው በእነርሱ ላይ ምን ያህል እንደከፋ የሚያሳይ ልዩ ምልክት ነው፡፡ ይህ በአሕዛብም ላይ የሚታይ ነው ፡፡

ስለዚህ ወዳጆች ሆይ እንትጋ፡፡ አዎን ከቤተሰቦቻችንም በላይ ስለእነርሱ መዳን እንሥራ ስለእነርሱም አብዝተን እንጸልይ ፡፡ ምክንያቱም ለሁሉ ከመጣው ድኅነት ርቀዋልና ፡፡ሰዎችን ሁሉ ወደ ድኅነት ከማድረስ አንጻር አንድ ሰው ሰውን ሁሉ ከማፍቀሩ በላይ ቤተሰቡን ሊያፈቅር ሊያፈቅራት አይገባውም፡፡ ስለዚህ ለነገሮች ሁሉ ብልህ እንሁን ወይም እንደችሎታችን መጠን እንድከም፡፡ “የመስቀሉ ቃል በራሱ ኃይልና ጥበብ ሆኖ ሳለ “የመስቀሉ ቃል ለሚጠፉት ሞኝነት … ነውና” ተብሎ እንደተጻፈ ለእነርሱ ለጥፋት  ሆኖባቸዋልና እናልቅስላቸው፡፡

ነገር ግን ከመካከላችን አንዳንዶች መስቀሉ በአሕዛብ ሲዘበትበት ተመልክተው ስለመስቀሉ ቀንተው የአሕዛብን ፍልስፍና  በመጠቀም ፈላስፎችን ሊረቱ የሚተጉ ክርስቲያኖች ነበሩና እንዲህ ዓይነት ወገኖችን ቅዱስ ጳውሎስ ሊያጽናናቸው በመሻት የአሕዛብ ፍልስፍና ከንቱ እንደሆነ ለማስረዳት ሲል ቅዱስ ጳውሎስ እንዲህ ብሎ ተናገራቸው፡፡ ከሚጠፉት ወገኖች ዘንድ የሆኑ ግን ይህንን ታላቅ ምሥጢር መረዳት አልተቻላቸውም፡፡ ምክንያቱም ከእነርሱ አጠገብ ያሉት ፈላስፎችና ራሳቸው የአእምሮ ሕመምተኞች ናቸውና፤ ወደ ጤንነት የሚያመጣቸውን መድኅኒት ፈጽመው ጠልተውታልና፡፡

ነገር ግን ሰው ሆይ “የባሪያውን መልክ ይዞ ተገኘ”(ፊልጵ.2፥7) ይላልና ክርስቶስ የባርያውን አርዓያ ይዞ በመገኘቱ ስለእኛ ድኅነት በመስቀል ላይ መቸንከሩ እንዲሁም ሞትን ድል አድርጎ ስለመነሣቱ በአሕዛብ ፍልስፍና እንዴት ብለህ ማስረዳት ትችላለህ? ለእግዚአብሔር አምላክ አምልኮን ማቅረብ ፣ ለሰዎች ልጆች ስላለው ጥልቅ ፍቅር ማድነቅ ይገባሃል እንጂ አባት ወይም የልብ ወዳጅ ወይም ልጅ ለአባቱ የማያደርገውን ለአንተ አድርጎ በማግኘትህ በፍጹም ጥበብ የተሞላውን ተግባሩን እንደሞኝነት በመቁጠር በእርሱ ላይ ምላስህን ታንቀሳቅሳለህን? ደህና! ይህ ግን የሚያስገርም ነገር አይደለም፤ ወደ ድኅነት የሚመራቸውን ጉዳይ አለማስተዋላቸው በነፍሳቸው የመጥፋታቸው ምልክት ነው እንጂ ፡፡

ወገኔ ሆይ አጠገብህ ያሉ ኢአማንያን እውነት በሆነው በዚህ ጉዳይ ላይ ሲያፌዙ ብትመለከት እንግዳና አዲስ ክስተት እንደተፈጸመ ቆጥረህ ልትረበሽ  አይገባህም፡፡ ይህን ታላቅ ምሥጢር የሰዎችን የመረዳት አቅም ተጠቅመህ ማስረዳት አይቻልህም፡፡ እንዲህ ለማድረግ የሞከርኽ እንደሆነ ግን ውጤቱ ተቃራኒ ይሆንብሃል፡፡ እንዲህ ዓይነት ከሰው አእምሮ በላይ የሆነ ክርስቲያናዊ እውቀት በእምነት ብቻ የሚቀበሉት ነው፡፡ እስኪ ንገረኝ እግዚአብሔር ቃል እንዴት ሰው ሆነ? እንዴትስ ቅድስት ድንግል ማርያም ማኅፀን አደረ? ስለዚህ ጉዳይ በእምነት ከመቀበል ውጪ ሰዎችን በምክንያት ማስረዳት ይቻልሃልን?  እነዚህ ወገኖች በእምነት ይህን ካልተቀበሉት በቀር በዚህ ጉዳይ ላይ ማፌዛቸው አይቀርም፡፡ ስለዚህም ነው የእግዚአብሔርን ሥራ ሰዎች በአእምሮ ጠባያቸው   ተደግፈው ለመመርመር በመሞከራቸው የጥፋት ልጆች ናቸው የሚባሉት ፡፡

ስለምን ነገሬን ለማስረዳት እግዚአብሔርን ብቻ እንደ ምክንያት እጠቀማለሁ? ይህ ዓይነት ነገር እግዚአብሔር  በፈጠራቸው ሥነፍጥረታትም ላይ የሚታይ አይደለምን ? ነገሮችን ሁሉ በምክንያት ለማስረዳት ለምትጥር ለአንተ  አንድ ሰው  እንዴት ብርሃንን ለማየት እንደምንችል ሊያስረዳህ ቢሞክር እርሱን አይደለም ብለህ ምክንያትን በማቅረብ ልትከራከረው ትችላለህን? ፈጽሞ አትችልም፡፡ ይልቁኑ አንድ ሰው ብርሃንን ለመመለከት ዐይኑን መክፈት ብቻ ይበቃዋል በማለት እውነታውን ብቻ ከማስቀመጥ ባለፈ  ዝርዝር ጉዳዩን በምክንያት ማስረዳት አይቻልህም፡፡

ለእያንዳንዱ ነገር ምክንያቱ ሊገለጥ ይገባዋል ለሚል ሰው ስለምን በጆሮአችን መመልከት አልቻልንም? ወይም በዐይናችን መስማት አልቻልንም? ወይም ስለምን በአፍንጫችን ማየት  አልቻልንም? ወይም በዐይናችን ማሽተት አልቻልንም? ብለን ብንጠይቀው መልሱን ከመመለስ ይልቅ እኛን እንዳላዋቂ ቆጥሮ በእኛ ላይ ሊሳለቅብን ይችላል ፡፡ ነገር ግን እኛ በእርሱ ላይ መልሰን አንሳለቅበትምን? ምክንያቱም ለእነዚህ  የስሜት  ሕዋሳቶቻች ሁሉ ምንጩ አንዱ የአእምሮ ክፍል ነውና፡፡ እንዲሁም አንዱ አካል ከአንዱ አካል እጅግ ተዛምዶ ያለው በመሆኑ ስለምን አንዱ አካል የሌላውን አካል ተግባር መሥራት ይሳነዋል ? ብለን ጥያቄ ብናቀርብለት ለዚህ ጥያቄያችን አሳማኝ ምክንያትን ሊያቀርብንልን  አይችልም ፤ ወይም ለዚህ ድንቅ ለሆነ ተፈጥሮ ስለአተገባበሩ ትንታኔ መስጠት አይቻለውም ፡፡ እኛም ይህን ለማስረዳት ብንዳዳ እርሱ መልሶ በእኛ ላይ አያፌዝብንምን? ስለዚህ ይህን ሁሉ በቀላሉ ማከናወን የሚቻለውንና የጥበብ ባለቤት የሆነውን እግዚአብሔር ጉዳዩን እንተውለትና  እኛ የእርሱን ሥራ በአእምሮ ጠባያችን  ከመመርመር እንከልከል፡፡ ይህን በሁሉም የእግዚአብሔር ሥራዎች ላይ እናሳይ ፡፡  ከእኛ አእምሮ ጠባይ በላይ  ስለሆነው ሥራዎቹ እኛ ትንታኔ መስጠት አይቻለንም፡፡

የአሕዛብ ፈላስፎች ተሳልቆ ከአእምሮቸው የማስተዋል ማነስ የተነሣ አይደለም፡፡ ነገር ግን ከእነርሱ ሞኝነት የተነሣ ነው እንጂ፡፡ ምክንያቱም ታላቅ የሆነውን የእግዚአብሔርን ሥራ የሰው እውቀት ፈጽሞ ሊረዳው አይቻለውምና፡፡ተወዳጆች ሆይ እኔ “እርሱ ስለሰው ልጆች ድኅነት ተሰቀለ” ስል ፈላስፋው ደግሞ “ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል? እርሱን ለስቅላት ሲነዱት መከላከል ያልቻለና ጽኑ ሕማምን የተቀበለ እንዴት ከዚህ በኋላ ከሞት ተነሥቶ ሌሎችን ሊረዳ ይቻላል?፡፡ ይህን ማድረግ የሚቻለው ሆኖ ቢሆን ኖሮ ከሞት በፊት አድርጎት ባሳየን ነበር ብለው ይጠይቃሉ፡፡ ይህን በእርግጥ አይሁድም፡- “ሌሎችን አዳነ ራሱን ሊያድን አይችልም” ብለው ነበር፡፡ (ማቴ.27፥41-42) ይህ ፈላስፋ ደግሞ  “እርሱ ራሱን ማዳን ያልቻለ እንዴት ሌላውን ሊያድን ይችላል፤ ለዚህ ምንም ምክንያትን ልታቀርቡ አትችሉም፣ ለዚህ ምንም ምክንያት ሊኖራችሁ አይችልም ፤ ሊል ይችላል፡፡  አንተ ሰው ሆይ ያልከው በእርግጥ እውነት ነው፡፡ ምክንያቱም ይህ እኮ ከሰው አእምሮ በላይ የሆነ የእግዚአብሔር ጥበብ ነው፡፡ የመስቀሉ ኃይል በቃላት ሊገለጽ የማይችል እጅግ ግሩም ነው እንዴት ፍጥረታዊው አእምሮ ሊረዳው ይችላል፡፡

ሠለስቱ ደቂቅ ወደ እቶን እሳት ባይጣሉ ኖሮ በእነርሱ የተገለጠው የእግዚአብሔር ጠባቂነት አድንቆት ባልተቸረው ነበር፡፡ ወደ እቶን ሲጣሉ በእሳቱ ላይ በመረማመድ እሳቱን ድል እንደነሡት ታወቀ፡፡ የዮናስንም ታሪክ ስንመለከት ከሠለስቱ ደቂቅ በላይ የሚያስገርም ተአምር እንደተፈጸመ ልንመለከት እንችላለን፡፡ ዮናስ ምንም ግዙፍ በሆነው ዓሣ አንባሪ ቢዋጥም እርሱን ግን አልጎዳውም ነበር፡፡  እርሱ በዓሣ አንበሪው ባይዋጥ ኖሮ በእርሱ የተፈጸመው እጅግ አስገራሚ ተአምር ባልተደነቀ ነበር፡፡ እንዲሁ ነው በክርስቶስ የተፈጸመው፡፡ እርሱ ባይሞት ኖሮ ሙታን ከሞት እስራት እንደተፈቱና ወደ መንግሥቱ እንደፈለሱ ባልታመነ ነበር፡፡ ስለዚህም “ስለምን ክርስቶስ በመስቀል ላይ ሳለ ራሱን ከመስቀል ሞት አላዳነም ?” ብለህ አትናገር፡፡ እርሱ ሞትን ድል ሊነሣ ሊሞት ስለእኛ መዳን መሞትን መረጠ፡፡ እርሱ ከመስቀሉ ላይ ራሱን ሊያወርድ ያልቻለበት ምክንያት ችሎታ ስለሌለው አይደለም ፤ ስላልፈገ ነው እንጂ፡፡ ሞት ሊቋቋመው ያልቻለ እርሱን እንዴት እጆቹን የተቸነከሩት ችንካሮች  እርሱን አስረው ሊይዙት ይችላሉ ?

የክርስቶስ ዓላማ ለእኛ ለክርስቲያኖች በጣም የታወቀ ነው፡፡ እኛ እንደ ኢአማንያን አይደለንም ፡፡ ስለዚህም  ቅዱስ ጳውሎስ “የመስቀሉ ቃል ለሚጠፉት ሞኝነት ለእኛ ለምንድን ግን የእግዚአብሔር ኃይል ነውና ፡፡ የጥበበኞችን ጥበብ አጠፋለሁ ፣ የአስተዋዮችንም ማስተዋል እጥላለሁ ተብሎ ተጽፎአልና ፡፡ ጥበበኛ የት አለ? ጻፊስ የታለ? የዚች ዓለም መርማሪስ የት አለ ? እግዚአብሔር የዚችን ዓለም ጥበብ ሞኝነት እንዲሆን አላደረገውም? ” አለን (1ቆሮ.1፥18-20)  ቅዱስ ጳውሎስ ለዚህ ዓለም ፈላስፎች ምክንያትን በመደርደር ሊከራከራቸው አልሞከረም ፡፡ ነገር ግን ትምህርቱን ለማስረዳት ቅዱሳት መጻሕፍትን አንደ መረጃ ጠቀሰ እንጂ፡፡ ስለዚህም በድፍረትና በታላቅ ቃል “ጥበበኛ የት አለ ? ጻፊስ የት አለ ? የዚች ዓለም መርማሪስ የት አለ ? እግዚአብሔር የዚችን ዓለም ጥበብ ሞኝነት አላደረገውምን ?በእግዚአብሔር ጥበብ ምክንያት ዓለም በጥበቡዋ ስላላወቀች በስብከት ሞኝነት የሚያምኑትን ለራሱ ሊያድን የእግዚአብሔር በጎ ፈቃዱ ሆኖአልና” ብሎ ተናገረ፡፡ “የጥበበኞችን ጥበብ ያስተዋዮችን ማስተዋል አጠፋለሁ ተብሎ ተጽፎአልና” ፡፡

ቅዱስ ጳውሎስ “ጥበበኛ የት አለ ? ጻፊስ የት አለ ? በማለት የአይሁድ ምሁራንንም የአሕዛብ ፈላስፎችንም በዚህ ቦታ እንዳዋረዳቸው እንመለከታለን ፡፡ የትኛው የአሕዛብ ፈላስፋ ወይስ የአይሁድ መምህር ነው እኛን ወደመዳን እውቀት የመራና  እውነትን የገለጠልን ? ማንም የለም ፡፡ ከሰዎች ወገን ወደ ድኅነት ጎዳና የመሩን ከዓሣ አጥማጆቹ ሐዋርያት በቀር ከአይሁድ ምሁር ወይም ከአሕዛብ ጠቢብ ማንም የለም፡፡ ስለዚህ ቅዱስ ጳውሎስ  ነገሩን ሲያጠቃልልና የእነርሱን ትምክህት ሲያዋርደው “እግዚአብሔር የዚችን ዓለም ጥበብ ሞኝነት እንዲሆን አላደረገውም” ? አለ፡፡ ይህ ለምን እንደሆነ ምክንያቱንም አስቀመጠ ፡፡ “በእግዚአብሔር ጥበብ ምክንያት ዓለም በጥበቡዋ ስላላወቀች” አለ፡፡ ስለዚህ በመስቀሉ የእርሱን ጥበብ አሳየን፡፡ ሐዋርያው  “በእግዚአብሔር ጥበብ ምክንያት” ሲል ምን ማለቱ ነው ? በፈቃዱ ራሱን በሥነ ፍጥረቱ የገለጠበትን ጥበብ ማለቱ ነው፡፡ ከሚታየው ነገር ተነሥተው ለፈጠራቸው አምላክ አድናቆት እንዲኖራቸው በመሻት አስቀድሞ እግዚአብሔር ራሱን በሥነ ፍጥረቱ ገልጦ ነበር ፡፡

እንደ እውነቱ  ከሆነ የዚህ ሰማይ ተፈጥሮው ድንቅ አይደለምን ? የምድሪቱስ ስፋት የሚገርም አይደለምን ? እነዚህን የፈጠራቸው አምላክ በእውነት ኃያል አምላክ ነው ፡፡ ሰማያቱ በእርሱ መፈጠራቸው ብቻ አይደለም የሚደንቀው ነገር ግን በቀላሉ እነርሱን በመፍጠሩም ጭምር እንጂ ፡፡ የምትታየውንም እህቺ ምድርም በእርሱ መፈጠሩዋ ብቻ አይደለም የሚደንቀው ፣ ካለመኖር ወደ መኖር ማስገኘቱም ጭምር  እንጂ ፡፡ ስለዚህም ጉዳይ በነቢዩ ዳዊት አስቀድሞ “አቤቱ አንተ ከጥንት ምድርን መሠረትህ ሰማያትም የእጅህ ሥራ ናቸው ፡፡”(መዝ.101፥25) ተባለ፡፡  ኢሳይያስም “ሰማያትን እንደ መጋረጃ የሚዘረጋቸው ፣  እንደ ድንኳንም ለመኖሪያ የሚዘረጋቸው ፣ አለቆችንም እንዳልነበሩ የሚያደርጋቸው የምድርንም ፈራጆች እንደ ከንቱ ነገር የሚያደርጋቸው እርሱ ነው ፡፡”አለን (ኢሳ.40፥23)

በዚህ ጥበቡ ዓለም እግዚአብሔርን ለማወቅ ባለመፈለጉዋ ምክንያት ሞኝነት በሚመስል መልኩ ያም ማለት በወንጌል እምነት ወደ ራሱ ሊያቀርባቸው ወደደ ፡፡ የእግዚአብሔር ጥበብ ባለበት የሰው ጥበብ እንደ ምናምን ይቆጠራል፡፡ ከዚህ አስቀድሞ ግን ዓለምን እንዲህ ግሩምና ድንቅ አድርጎ የፈጠረ አምላክ ማንም  ሊቋቋመው የማይቻለው ብርቱ አምላክ እንደሆነና ከመረዳት ያለፈ ጥበብና እውቀት ያለው ፈጣሪ እንደሆነ በሥነ ፍጥረቱ ለማስረዳት ሞክሮ ነበር፡፡ ከዚህም ተነሥተን እርሱን ወደ መረዳት መድረስ ነበረብን፡፡ አሁን ግን በሥነፍጥረቱ እርሱን ማወቅ ስላልቻልን በምክንያት ሳይሆን በእምነት እኛን ለማዳን ፈቀደ ፡፡ ሐዋርያት ጠቢባን ስለነበሩ አልነበረም የተመረጡት ፤ እምነት ስላላቸው እንጂ፡፡ ስለዚህም እግዚአብሔርን በመመራመር ሳይሆን የእግዚአብሔርን የማዳን ሥራ በእምነት በመቀበላቸው ምክንያት በጥበባቸው ከአሕዛብ ጠቢባን በላይ አዋቂዎች ሆኑ፡፡ የእርሱ ሥራ ከሰዎች የማወቅ ችሎታ በላይ እጅግ ታላቅ ግሩም  ነው፡፡  ነገር ግን “እንዴት እግዚአብሔር የአሕዛብን ጥበብ አጠፋ ? ቢባል ከቅዱስ ጳውሎስና ከሌሎችም ሐዋርያት እንደተማርነው የአሕዛብን ጥበብና ማስተዋል የማይጠቅምና የማይረባ በማድረግ ነው፡፡ የምሥራቹን ወንጌል የሰው ልጅ እንዲሰማ በማድረግ ጠቢባን በእውቀታቸው እንዳይጠቀሙ ያልተማሩትም  ባለማወቃቸው እንዳይጎዱ አደረጋቸው ፡፡

ይቀጥላል……..

“ሊከተለኝ የሚወድ… መስቀሉን ተሸክሞ ይከተለኝ”

ቀሲስ ፋሲል ታደሰ
ቀን፡ መስከረም 13 / 2003 ዓ.ም.

መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የሰው ልጆችን ፍቅር ስለገለጠበት ሕማምና ሞቱ ለደቀመዛሙርቱ ባስተማረበት ወቅት ለእነርሱም “እኔን ሊከተል የሚወድ ራሱን ይካድ ጨክኖም መስቀሌን ተሸክሞ ይከተለኝ” ብሏቸዋል፡፡ አስቀድሞ “የሰው ልጅ ይሰቀል ዘንድ ይገባዋል” በማለት ነገረ ድኅነትን የሚፈጽምልን በዕፀ መስቀሉ እንደሆነ ተናግሯል፡፡ ጊዜው ሲደርስም በቀራንዮ መስቀል ላይ ዋለ በገዛ ፈቃዱ ስለ ሰው ልጆች መዳን ቅድስት ነፍሱን ከቅዱስ ሥጋው ለየ፡፡ በአካለ ነፍስ ወደ ሲዖል ወርዶ ነፍሳትን ወደ ገነት አሸጋገረ፤ የዲያብሎስንም ሥራ በመስቀሉ ድል ነሣ ሰላምን አደረገ፡፡ “በእኛ የነበረውን የሚቃወመንንም በትእዛዛት የተጻፈውን የዕዳ ጽሕፈት ደመሰሰው እርሱንም /ዲያብሎስ/ በመስቀሉ ጠርቆ ከመንገድ አስወግደታል እንደሚል /ቆላ. 2÷20/

ቅዱስ ዮሐንስ “ወበዝንቱ ተዐውቀ ፍቅሩ ለእግዚአብሔር የእግዚአብሔር ፍቅሩ በዚህ ታወቀ” በማለት እንደገለጸው አምላካዊ ፍቅሩን በሕማማተ መስቀሉ አሳይቶናል  /1ኛ ዮሐ.4÷10/፡፡ ሕግን የጣስን ቅጣትም የሚገባን የሰው ልጆች ሆነን ሳለ ነገር ግን ከቸርነቱ ብዛት “የሟቹን ሞት አልወድም” በማለት በዘለዓለም ሞት ተቀጥተን እንድንኖር አልወደደምና በሕማማተ መስቀሉ “ደዌያችንን ተቀበለ ሕማማችንን ተሸከመ ስለ እኛም ታመመ… በእርሱ ቁስል እኛ ተፈወስን” /ሕዝ.18÷32፣ ኢሳ.53÷4/፡፡

የእግዚአብሔር ፍቅር በመስቀል እንደተገለጠ ሁሉ የሰው ልጆችም እርሱን የመውደዳችን መገለጫ መስቀሉን በመሸከም መከተል እንደሆነ በአምላካዊ ቃሉ አስተምሮናል፡፡ ይህም ማለት እንደ ጌታችን ረጅምና ክብደት ያለው ዕፀ መስቀልን በትከሻችን ተሸክመን ቀራንዮ እንድንጓዝ ሳይሆን መከራ መስቀሉ ስለ እኛ ሲል የፈጸመልን መሆኑን በማመን እና ተከታዮቹ በመሆናችን የሚመጣብንን መከራ በመታገሥ መኖር እንደሚገባን ሲያመለክተን ነው፡፡ በዚህም መሠረት “መስቀል መሸከም” የተባለው በዓለም ስንኖር በክርስትና ምክንያት የሚገጥመንን መከራ ነው፡፡ “በዓለም ግን መከራ ትቀበላላችሁ ነገር ግን ጽኑ እኔ ዓለሙን ድል ነስቼዋለሁና” እንዲል /ዮሐ.16÷33/፡፡ በወቅቱ ይህ ቃል የተነገራቸው ቅዱሳን ሐዋርያት መስቀሉን በመሸከም ማለትም ስለ ክርስትና ኑሮ የመጣባቸውን መከራ በመታገሥ እና ድል በመንሳት ኑረዋል ለዚህም ነው፡፡ “መንግሥተ ሰማያት በብዙ መከራ እንገባ ዘንድ ያስፈልገናል” በማለት በቃልም በተግባርም የገለጹት /ሐዋ.14÷22/፡፡ የክርስትና ጉዞ እንደ ቀራንዮ ጉዞ መከራ የበዛበት ነው፡፡ ፈቃደ ሥጋን እየታገሱ ለፈቃደ ነፍስ እየኖሩ ዓለምን፣ ዲያብሎስን እየተዋጉ እስከ ሞት በመጽናት ተጉዘው የክብር አክሊል የሚቀዳጁበት ሕይወት ነውና “እስከ ሞት ድረስም የታመንህ ሁን የሕይወት አክሊልንም እሰጥሀለሁ” ተብሎ እንደተጻፈ /ራእ.2÷10/፡፡

መከራ ከየት ይመጣል?

1. ከዲያብሎስ ጥንተ ጠላታችን ዲያብሎስ የሰው ልጅን በኃጢአት መጣል ቋሚ ሥራው ነው፡፡ ይልቁንም የመስቀሉን ዓላማ የያዙ ክርስቲያኖችን ይከታተላል፡፡ በተለያዩ ወጥመዶችም ለመያዝ እና መከራ ለማጽናት ይሞክራል፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ “ጠላታችሁ ጋኔን የሚውጠውን ፈልጐ እንደሚያገሳ አንበሳ ይዞራልና” ሲል ቅዱስ ጳውሎስም “ሰልፋችሁ ከጨለማ ገዦች…. ከክፋዎች አጋንንት ጋር ነው” በማለት ውግያውን ገልጾታል፡፡ ቅዱስ ዮሐንስ በራእይ መጽሐፉም በሰይጣን አማካኝነት የተለያዩ መከራዎች እንደሚመጡ ሲያስረዳ እንዲህ ብሏል “ትቀበለውም ዘንድ ስላለህ መከራ አትፍራ እነሆ እንድትፈተኑ ሰይጣን ከእናንተ አንዳንዶችን ወደ እስር ቤት እንዲገቡ ያደርጋል….”/ራእ.2÷10/ ቅዱሳን ከዲያብሎስ የመጣባቸውን መከራ በመታገሥ ለክብር እንደበቁ ገድላት ምስክሮች ናቸው፡፡ “ክርስቶስን በመከራ ትመስሉት ዘንድ ደስ ይበላችሁ” እንደ ተባለው ቅዱስን የመጣባቸውን መከራ በጸጋ በመቀበል ጌታቸውን መስለዋል /1ኛ ጴጥ. 4÷13/፡፡

ጠላታችን ዲያብሎስ ፈቃደ ሥጋን በማስወደድ፣ በደካማ ጐናችን በመፈታተን፣ በሥጋዊ ምኞት ለመጣል መከራ ያመጣብናል፡፡ ለእኛ አብነት እንዲሆነን በተፈጸመው የገዳመ ቆሮንቶስ የዲያብሎስ ፈተና እንደምንገነዘበው “ዛሬም ለእኔ ብትሰግድ፣ ብትገዛ…” በማለት በምኞት ዓለም በማስጐምጀት ከእግዚአብሔር ሊያርቀን ይታገለናል፡፡ ስለሆነም ጌታችንን በክብር የምንመስለው መስቀሉን በመሸከም ከመሰልነው እንደሆነ በማስተዋል ከዲያብሎስ በተለያዩ መንገዶች የሚመጡብንን መከራዎች በመታገሥ እና ድል በመንሣት ለመኖር መዘጋጀት ይጠበቅብናል፡፡ መስቀሉን የመሸከም መገለጫም የሚደርስብንን የተለያየ መከራ መታገሥ እንደሆነም በማስታወስ፤ ክብሩን በማሰብ፤ ክርስቲያናዊ ፈተናን ለመቋቋም እንበርታ፡፡ “ካለው ክብር ጋር ሲመዛዘን መከራው ምንም እንዳይደለ እናውቃለን” እንደሚል /ሮሜ. 8÷18/፡፡


2.    በራሳችን ክፉ ምኞት
– አንዳንድ ጊዜ ከመንፈሳልነት ርቀን የምናውጠነጥነው ክፉ ምኞት በራሳችን ሕይወት ላይ መከራ ሲያመጣብን ይስተዋላል፡፡ ቅዱስ ያዕቆብ “በእናንተ ዘንድ ጥልና መጋደል ከወዴት ይመጣሉ? በሰውነታችሁ ውስጥ የሚሠራውን ዝሙት ከመውደድ የተነሣ ከዚህ አይደለምን….” በማለት ከራስ ክፉ ምኞት መከራ እንደሚመጣ ያስገነዝበናል፡፡ በመንፈስ ስንዝል ኃጢአት መጓዝ እንጀምራለን፡፡ አምኖን በገዛ ምኞቱ ተፈትኖ በዝሙት እንደወደቀ ሁሉ ዛሬም በራሳችን ክፉ ምኞት በመገፋፋት በኃጢአት በመውደቅ ዳግማዊ አምኖን እንዳንሆን ያስፈልጋል /2ኛ ሳሙ.13÷1/፡፡  በአብዛኛው ያለፈቃዳችን የምንሠራው ኃጢአት እንደሌለ ልናጤን ይገባናል፡፡ ይህንንም “ነገር ግን እያንዳንዱ በራሱ ምኞት ሲሳብና ሲታለል ይፈተናል” እንዲል /ያዕ 1÷14/፡፡

በመሆኑም ለክፉ ምኞት ተጋላጭ የሆነውን ኅሊናችንን በመግዛት፤ ለመልካም ሥራ መነሣሣት መታገል በራሱ መስቀል መሸከም መሆኑን ዘወትር ልንዘነጋ አይገባንም፡፡ በፈቃደ ሥጋ ለተዘፈቅንም ከዚህ ለመውጣት የሚደረገው ትግል ተገቢ መሆኑን በመረዳት መንፈሳዊ ተጋድሎውን ልናፀና ይገባልና፡፡ “ሰውነቱን በመከራ የሚያሰቃያትን አመስግኑት” /ኢሳ. 49÷7/ ተብሎ እንደተጻፈ የፈቃደ ሥጋ ምኞት የሆኑትን ዝሙት፣ ሱሰኝነትን፣ መዳራት… የመሳሰሉትን ድል ለመንሣት መታገል የሚያስመሰግን ተግባር ነው፡፡ ስለዚህም የሥጋን ሥራ በመንፈሳዊ ሥራ በመተካት ከራሳችን ምኞት ፈተና እንዳይጸናብን መንገዱን ለመዝጋት እየጣርን በጾም በጸሎት ረድኤተ እግዚአብሔርን አጋዥ እናድርግ፡፡ “እንደ እግዚአብሔር ፈቃደ መከራን የሚቀበሉ ሰዎችም መልካም ሥራን በመሥራት ለታመነ ፈጣሪ ነፍሳቸውን አደራ ይስጡ” ተብሏልና /1ጴጥ.4÷19/፡፡

3.    ካላመኑ ወገኖች- በክርስትና ኑሮ ላይ መከራ ከሚመጣበት አንድ ካለመኑ ወገኖች ነው፡፡ ከዘመነ አበው ጀምሮ በአምልኮተ እግዚአብሔር የዳኑ ሰዎች እግዚአብሔርን ከማያምኑ ወገኖች መከራ ሲመጣባቸው ኖሯል፡፡ የግብጹ ፈርዖን እሥራኤል ላይ መከራ ማጽናቱ እና ከዐሥሩ የቅስፈት ዓይነቶች አለመማሩ ያለማመኑ ውጤት ነው፡፡ በመሆኑም እሥራኤል ባሕረ ኤርትራን ሲሻገሩ ፍጻሜው ስጥመት ሆኗል፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትን አይሁድ ጣዖት አምላኪዎች እና ጠንቋዮች መከራ ያጸኑባቸው እንደነበር በሐዋርያት ሥራ ተመዝግቧል፡፡ ለምሳሌ ኤልማስ የተባለ ጠንቋይ ወንጌልን እንዳይሰብኩ ሲፈታተናቸው፤ ሌሎች ደግሞ መጽሐፎቻቸውን በማቃጠል የአገልግሎት እንቅፋት ሆነውባቸዋል፡፡ እንደዚሁም በማሳደድ እና በመግረፍም ሄሮድስና ሌሎችም ዐላውያን ነገሥታት መከራ ያመጡባቸው ነበር፡፡ /ሐዋ.13÷8፤19÷19/ ለዚህም ነው፡፡ “መከራ ተቀብለን ተንገላተን ወንጌልን ተናገርን” በማለት ቅዱስ ጳውሎስ መከራቸውን የገለጸው /1ኛ ተሰ.2÷2/ በተጨማሪም ስደት መራብ መጠማት ነቀፋ.. እና የመሳሰሉት በአገልግሎታቸው ጊዜ የተለመደ መከራ ስለመሆኑ እና ነገር ግን የቅዱሳን አበው ጭንቀት ከሌሎች ስለሚመጣው መከራ ሳይሆን የአብያተ ክርስቲያናት ሐሳብ ስለመሆኑ ለቆሮንቶስ ክርስቲያኖች በጻፈው መልእክቱ አስገንዝቧል/ 2ኛ ቆሮ.11÷28/፡፡ የዘመነ ሰማዕታት ቅዱሳን ሰዎች ኑሮም እንደሚያስረዳው በየዋሻው እምነታቸውን የገለጡበት እና ደማቸውን ስለ ክርስትና ያፈሰሱት እንደእነ ዲዮቅልጥያኖስ እና መሰሎቹ ካመጡባቸው መከራ የተነሣ መሆኑን የቤተ ክርስቲያን ታሪክ ማስረጃ ነው፡፡ በዘመናችንም በተለያዩ መንገዶች በኢየሱስ ክርስቶስ የባሕርይ አምላክነት ካላመኑ ወገኖች መከራ ሊመጣ ይችላል፡፡ አይሁድ የክርስቶስን መስቀል እንደቀበሩ፤ የቤተ ክርስቲያንን ትውፊትና ሥርዓተ ትምህርት ለመቅበር በመሯሯጥ በተዋሕዶ እምነታቸው የዳኑትን ምእመናን እና አገልጋዮችን የሚፈታተኑ ተረፈ አይሁድ በየዘመኑ ይነሣሉና፡፡ “በመጣባችሁ መከራ አትደነቁ” እንደተባለ፤ ስለ ሃይማኖት ከማያምኑ /ከተጠራጣሪዎች/ በሚመጣው ፈተና ሳንታወክ በመንፈሳዊ ሕይወት እና በተዋሕዶ ትምህርት ልንጸና ይገባናል፡፡

ከላይ የጠቀስናቸውን የመከራ ምንጮች መሠረት አድርገን በዘመናችን ስላለው መከራም ልናተኩር ይገባናል፡፡ በክርስትና ኑሮ ላይ እየተፈታተኑን የሚገኙትን የመከራ ዓይነቶች ከራሳችን እና ከውጪ ብለን ብንጠቁም ለመረዳት ግልጽ ይሆናል፡፡ ለአብነት ያህልም ከራሳችን ከሚመጡብን የወቅቱ ችግሮት ሁለቱን እንመልከት፡፡

1.    ዓለማዊነት- “ወንድሞች ሆይ ይህን ዓለም አትውደዱ፤ ዓለምን መውደድ ከእግዚአብሔር ጋር ጥል ነው፡፡” ይላል ነገር ግን ከሰይጣን ግፊት ወይም ከራሳችን ከደካማ ጐን የተነሣ በመውደቅ ለዓለም ምርኮኛ መሆን የተለመደ ሆኗል፡፡ ዓለማዊነት ስንልም በዓለም ውስጥ የሚገኝ የኃጢአት ተግባራት መፈጸምን ነው በዘመናዊነት እና በሥልጣኔ ሰበብ ብዙዎች ለዕውቀትና ለልማት የሚሆነውን በጐ ነገር ከመቀስም ይልቅ ኃጢአታዊ ተግባራት ላይ ሲያተኩሩ ይታያል፡፡ ለምሳሌ ከመጾም መብላትን፣ ከማስቀደስ መተኛትን፣ ከመዝሙር ዘፈንን፣ በሥርዐት ከመልበስ ፋሽን መከተልን… የመሳሰሉትን ማዘውተሩ በዓለማዊ ምኞት የመጠመድ መገለጫ ነው፡፡ በአንድ ወቅት እሥራኤል ከሞዓብ መንደርና ተግባር በመተባበራቸው በጣዖት አምልኮ በዘፈን እና በዝሙት ሲወድቁ ለቅስፈት ተዳርገዋል፡፡ ዛሬም ቢሆን በክርስትና ኑሮ የሚጓዙ ኦርቶዶክሳዊያን ዕውቀት፣ ገንዘብ እና ሀገር መለወጥ ሲገጥማቸው በጐውን ከመጠቀም ይልቅ የሥልጣኔ ትርጓሜ ባለመረዳት የክርስትና ሕይወትን በዓለማዊነት ሲለውጡ በአነጋገር፣ በአለባበስ በውሎ…. በመሳሰሉት ምዓባዊ ሥራ መሥራት እየተብራከተ መጥቷል /ዘኁ.21/፡፡ ስንቶቻችን ነን ከዓለማዊነት ሸክም ርቀን ስለ እግዚአብሔር ፍቅር መስቀሉን ተሸክመን ለመኖር የተዘጋጀን? ዛሬ ዛሬ ከዓለማዊነት የተነሣ ቤተ ክርስቲያንን መከተል ሳይሆን ቤተ ክርስቲያን እንደ እነርሱ ፍላጐት እንድትከተላቸው የሚፈልጉ አይጠፋም፡፡ ለሥርዐት ከመገዛት ይልቅ “ምን አለበት፣ ምን ችግር? አለው” በሚል ቃላት ተደልለው ለቀኖና ቤተ ክርስቲያን ቸልተኛ ከመሆን እስከ ኑፋቄ መድረስ እየተለመደ ነው፡፡ ስለዚህም ለሥጋ ሥራ የሚያተጋውን ዓለማዊነትን አርቀን ለመንፈስ ፍሬዎች የሚያበቃውን ነገረ መስቀሉን እየሰብን ጌታችንን በእውነት ልንከተለው ይገባናል፡፡

2.  ፍቅረ ንዋይ– ባለንበት ወቅት በፍቅረ እግዚአብሔር እንዳንጸና ከሚፈታተነን አንዱ ገንዘብ ወዳድ መሆን ነው፡፡ ይሁዳ እንደ ሌሎቹ ደቀመዛሙርት መስቀሉን ተሸክሞ እንዳይከተል ጠልፎ የጣለው ኃጢአት ፍቅረ ንዋይ መሆኑ የታወቀ ነው፡፡ ዛሬስ ለምን በዐሥራት አልታመንም? ሰንበትና በዓላትን አላከበርንም…? ብለን ራሳችንን ብንመረምር ያለኝ ይበቃኛል የሚለውን ምክር ወደ ጐን ትተን በፍቅረ ንዋይ መጠመዳችንን የሚያሳይ ነው፡፡ የሙስና መብዛት፤ አጭበርባሪነት መበራከት፤ በንግድና በተለያዩ ዘርፎች አታላይነት ከመጠን ማለፉ ፍቅረ ንዋይ ሲጸናወተን እንጂ ሌላ ምን ሊሆን ይችላል? ቅዱስ ጳውሎስ “ገንዘብ መውደድ የክፋት ሁሉ ሥር ነው” በማለት እንደ ገለጸው ለገንዘብ ሲባል በየቤቱ፣ በየቢሮው፣ እና በተለያዩ ቦታዎች የክፉ ሥራ መበራከት የሰላም መጥፋት የአደባባይ ምስጢር አይደለምን? /1ኛ ጢሞ.6÷10/

ከውጪያዊ አካላት የሚመጡብንን የክርስትና ሕይወት እንቅፋቶች ለመዘርዘር ይህ አጭር ጽሑፍ በቂ አይሆንም፡፡ ነገር ግን ለአብነት ያህል አንዱን እንመልከት-

ሀ.   የሐሰት ክስ /ስም ማጥፋት/– ዲያብሎስ የታወቀው እና ሥራውን የጀመረው በሐሰት ንግግር መሆኑ ይታወቃል፡፡ በዓለመ መላእክት “እኔ ነኝ ፈጣሪ” ማለቱ እና አዳምና ሔዋንን በሐሰት ትምህርት ማጥመድ የሐሰት አባትነቱን አረጋግጦለታል፡፡ ጥንትም ሆነ ዛሬ በሐሰት አባትነቱን አረጋግጦለታል፡፡ ጥንትም ሆነ ዛሬ በሐሰት አንደበት የግብር ልጆቹ የሆኑ ሐሳዋውያን እውነተኞች በሐሰት ሲከስሱ እና ስማቸውን ሲያጠፉ ይገኛሉ፡፡ በእግዚአብሔር ቃል ጸንተው እውነትን ይዘው የሚታገሉትን ከሚገጥማቸው ፈተና አንዱ ከሐሰተኞች የሚሰነዘር ስም ማጥፋት ዘመቻ መሆኑ እየተለመደ መጥቷል፡፡ በመሠረቱ አይሁድ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በሐሰት መክሰሳቸውን ያስተዋለ ክርስቲያን በዚህ ሊደነቅ አይገባውም፡፡ በዘመነ ብሉይ ሶስናን ብናስታውስ ያልፈጸመችውን እንደ ፈጸመችው አድርገው በሐሰት ከሰዋት ለፍርድ ያበቋት ረበናት ለጊዜው ስም ማጥፋቱ ቢሳካላቸውም እውነቱ ሲገለጥ ግን ውርደቱ እና ቅጣቱ በእነርሱ ላይ ሆኗል፡፡ ዛሬም በቤተ ክርስቲያን አገልግሎት የተጠመዱትን ከአባቶች እስከ ምእመናን በሚገኙ አገልጋዮች ላይ ስም ለማጥፋት የሚሯሯጡ ውሉደ ሐሰት ተበራክተዋል፡፡ ንስሐ ካልገቡ ፍጻሜያቸው እንደ ረበናቱ ይሆናል፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ “በሌላ ትፈርድ ዘንድ ማነህ? … እርሱን እግዚአብሔር ሊያቆመው ይችላልና” /ሮሜ.14÷4/ በማለት እንዳስተማረው ሐሰተኞች የፈረዱባቸው ወገኖች አጥፍተው እንኳን ቢሆን ንስሐ ገብተው እንደሆነ ምን እናውቃለን? በውኑ የአገልግሎት ማኅበራትን አባቶችን የቤተ ክርስቲያን ሓላፊዎችን… ለማዋረድ በመሞከርስ የሚገኘው ጥቅም ምን ይሆን?

አንዳንድ ጊዜ የምንታማበት ነገር እውነት ከሆነም የታማው /የተተቸው/ አካል ልቡ ያውቃልና ራሱን ሊመረምር ይገባል፡፡ ሆኖም ግን ሐሰተኞች /ሰዳቢዎች/ ሊገነዘቡ የሚገባው ለሃይማኖት በመቅናት ከሆነ አገላለጹ ይህ እንዳልሆነ ተረድተው ይልቁንም ክርስቲያን ከባቴ አበሳ መሆን በፍቅር እና በቅርበት ስሕተተኞችን በምክርና በጸሎት በማገዝ ቢሆን የዓመፃ ሳይሆን የእውነት መሆኑ ግልጽ ይሆናል፡፡

ማጠቃለያ

የክርስትና ኑሮ አልጋ በአልጋ እንዳልሆነ ከልብ ከተረዳን እውነትን የያዘ ሁሉ ፈተና ሲገጥመው “መስቀሉን ይሸከም” የሚለውን ቃል ሊያስተውል ይገባል፡፡ የሚገጥመንንም መከራ በሚከተሉት ነጥቦች ድል መንሣት እንችላለን፡፡

1.   ትዕግሥት “ኢዮብ ታገሠ እግዚአብሔርም ሰማው” /ያዕ.5÷11/ ተብሎ እንደተጻፈ ትዕግሥት ይኑረን፡፡ የማይፈተን የተባረከ ነው አልተባለም፤ በፈተና የሚጸና እንጂ፡፡ በመሆኑም ከጌታችን እና እርሱን መስለው ከተገኙ ከቅዱሳን በመማር መስቀሉን በትዕግሥት ተሸክመን ልንጓዝ ይገባል፡፡ ቅዱሳን ሐዋርያትን መከራ አጽንተውባቸው በሸንጐ ሲያቆሟቸው በትዕግሥት ተቀበሉት፡፡ “በሸንጐ ፊት ስለተናቁ ደስ ብሏቸው ወጡ” እንደሚል መከራን በጸጋ ተቀበሉ /ሐዋ. 5÷41/፡፡

2.  ፍቅር– “ከክርስቶስ ፍቅር ማን ይለየናል? መከራ ወይስ ጭንቀት” /ሮሜ 8÷35/ እንደተባለ ፍቅር ያለው መከራን ይታገሣል /1ኛ ቆሮ.13÷7/፡፡ ሊያስፈራን የሚገባ ከእግዚአብሔር መለየት እንጂ፤ በእግዚአብሔር መንገድ ሆነን የሚገጥመን መከራ መሆን የለበትም፡፡ የክርስትና ሕይወትም ሆነ ፍቅረ እግዚአብሔር ዋና መገለጫው መከራ መቀበል መስቀሉን ተሸክሞ በፍቅር መኖር ነውና፡፡ በመሆኑም በትክክለኛ መንገድ ዓላማውን ተረድቶ የመጣ አገልጋይ አስፈሪ ነገሮች እንኳን ቢገጥሙት ወደኋላ አይሸሽም፤ ቅዱሳን ሁሉን ትተው እንደተከተሉት ፍቅረ እግዚአብሔር ራስን እስከ መስጠት ያደርሳልና /ማቴ.19÷19/፡፡

3.    ጽናት- እያንዳንዱ አገልግሎት የራሱ የሆነ ችግር አለው፡፡ ውጤቱም ጽናቱ ላይ ነው “እያንዳንዱ በራሱ ድካም መጠን የራሱን ደመወዝ ይቀበላል” የተባለው እንዲፈጸምልን ጽናት ወሳኝ ነው፡፡ “በሁሉ እንገፋለን እንጂ አንጨነቅም፤… እንሰደዳለን እንጂ አንጣልም…” ብሎ ቅዱስ ጳውሎስ እንደተናገረው ለአገልግሎት ያለንን ቁርጠኝነት በጽናት ልንገልጽ ይገባናል፡፡

በአጠቀላይ የክርስትና ሕይወት መከራው ብዙ ዋጋውም እጅግ ብዙ ነውና በትዕግስት፣ በፍቅር፣ በጽናት ሆነን እንትጋ በመከራ ጽናት መስለነው መስቀሉን ተሸክመን እስከሞት ከተጓዝን ክብርን ያቀዳጀናልና፡፡ በሁሉም ስለ ስሜ የተጠላችሁ ትሆናላችሁ እስከ መጨረሻ የሚጸና ግን እርሱ ይድናል እንደሚል /ማቴ.10÷22/፡፡

ምንጭ፡- ሐመር 18ኛ ዓመት ቁጥር 6 መስከረም 2003

ወስብሐት ለእግዚአብሔር
adye abeba 2006

“በዚህች ዓመት ደግሞ ተዋት” ሉቃ.13÷6-9

ዲ/ን ተስፋሁን ነጋሽ

ጳጉሜ 3/2006 ዓ.ም.

adye abeba 2006

 

ጌታችንና መድኃኒታችን ፈጣሪያችንና አምላካችን እግዚአብሔር ወልድ /ኢየሱስ ክርስቶስ/ በመዋዕለ ሥጋዌው በምሳሌ አድርጐ ወንጌልን አስተምሯል፡፡ በምሳሌ ማስተማር ሊተላለፍ የተፈለገውን መልእክት ሲያስተላልፉት ምግብን በጣፈጠ መረቅ ፈትፍቶ እንደማጉረስ ያህል ይሆናልና፤ እንዲሁም አንድ መልእከት በምሳሌ ጣፍጦ በቋንቋ ዘይቤ ተውቦ ሲቀርብ ምሥጢሩ ልብን ይማርካል፡፡ ስለዚህ የሰው አእምሮ በሃይማኖት ልጓም ተስቦ ለምግባረ ጽድቅ እንዲዘጋጅ ጌታችን ለነጋዴው በወርቅ በዕንቁ፣ ለገበሬው በእርሻ በዘር፣ ለባልትና ባለሙያዎች በእርሾ በቡሆ፣….. ወዘተ እየመሰለ ያስተምር ነበር፡፡ ማቴ.4÷30፡፡

እኛም ጌታ በምሳሌ ካስተማራቸው ትምህርቶች መካከል ለወቅቱ የሚስማማውን መርጠን እንመለከታለን በሉቃ.13÷6-9 ላይ ይህንንም ምሳሌ መሰለ “ለአንድ ሰው በወይኑ አትክልት አጠገብ የተተከለች በለስ ነበረች ግን ፍሬ ሊፈልግባት ቢመጣ ምንም አላገኘም፡፡ ስለዚህ የወይን አትክልት ጠባቂዋን እነሆ ከዚህች በለስ ፍሬ ልፈልግ ሦስት ዓመት እየመጣሁ ምንም አላገኘሁምና ቁረጣት፤ ስለምን ደግሞ መሬቱን ታጐሳሉቁላለች? አለው፡፡” እርሱ ግን መልሶ ጌታ ሆይ ዙሪያዋን እስክኮተኩትላትና ፋንድያ እስካፈስላት ድረስ በዚህች ዓመት ደግሞ ተዋት፡፡ ወደ ፊት ግን ብታፈራ ደህና ነው፤ ያለዚያ ግን ትቆርጣታለህ አለው፡፡” ተብሎ ተጽፏል፡፡

ይህ ከላይ የተገለጸው ምሳሌ በሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን ሲተረጐም /ሲመሰጠር/ እንዲህ ነው፤ የወይን አትክልት የተባለች ኢየሩሳሌም ናት፣ አንድ ሰው የተባለ እግዚአብሔር ነው፣ በለስ የተባሉ ደግሞ ቤተ እስራኤል ናቸው፡፡ ነቢዩ ኢሳይያስ “እግዚአብሔር ለዘለዓለም አይራብም” ይላል ኢሳ.46÷25፡፡ ራሱ ጌታችንም “የእኔስ መብል የላከኝን ፈቃድ አደርግ ዘንድ ሥራውንም እፈጽም ዘንድ ነው፡፡” ብሏል ዮሐ.4÷35 ፡፡ ስለዚህ ሰማያዊያን መላእክትን እንዳይራቡ ያደረገ አምላክ እስራኤል ዘሥጋን ገበሬ በማያርስበት ዘር በሌለበት ዝናብ በማይጥልበት ምድረ በዳ መና ከሰማይ አውርዶ የመገበ ጌታ ተራበ ሲባል ያስገርማል! ግን ፍጹም አምላክ እንደመሆኑ ፍጹም ሰው ሆኗልና አልተራበም አንልም፤ በሥጋ ተርቧልና የዕፀ በለስ ፍሬን ፈለገ፡፡

ይኸውም የበለስ ውክልና ከተሰጣቸው ቤተ እስራኤል የሃይማኖትና የምግባር ፍሬን እንደፈለገ ያመለክታል፡፡ “በለስ ዘይቤ ቤተ እስራኤል እሙንቱ” ተብሏልና እግዚአብሔር አምላክ በብሉይ ኪዳን በቅዱሳን ነቢያት አድሮ የሃይማኖት /የምግባር/ ፍሬ ባገኝባቸው ብሎ ወደ እስራኤል ሔደ፤ ግን ምንም አላገኘም፡፡ እንዲያውም ሕዝቡ ቅዱሳን ነቢያትን በመጋዝ እየሰነጠቁ፣ በምሳር እየፈለጡ በማጥፋት ከዘመን ዘመን ወደተለያየ አዳዲስ ባዕድ አምልኮአቸው ሲገቡ አየ፡፡ ስለዚህ የበለስዋን ጠባቂ “ሦስት ዓመት እየመጣሁ ምንም ፍሬ አላገኘሁባትምና ቁረጣት” አለው፡፡ ሦስት ዓመት ያለው ዘመነ መሳፍንት፣ ዘመነ ነገሥታትና ዘመነ ካህናትን ነው፡፡ በዚህን ጊዜ የወይን ጠባቂዋ የተባለ መጋቤ ብሉይ ቅዱስ ሚካኤል “ተራድቼ ሥራ እስካሠራቸው ድረስ የዘንድሮን ይቅር በላቸው” እያለ መለመኑን ያጠይቃል፡፡

አንድም ሰው የተባለ አብ ቢሉ በልጁ ህልው ሆኖ፣ ወልድ ቢሉ ሰው ሆኖ ሃይማኖት፣ ምግባር ፍለጋ ወደ እስራኤል ሄደ፡፡ ሦስት ዓመት በመዋዕለ ስብከቱ እየተመላለሰ ሲያስተምራቸውም ምንም ፍሬ አላፈሩምና “ይህችን ዕፀ በለስ ቁረጣት” አለው፡፡ መጋቤ ሐዲስ ቅዱስ ገብርኤል ግን “ተራድቼ ሥራ እስካሠራቸው ድረስ ይቅር በላቸው፡፡” ብሎ ለመነ የጌታን ትምህርት ያልተቀበሉ አይሁድ ግን የንስሐን ፍሬ ለማፍራት በጄ የሚሉ አልሆኑም፡፡ በአንደበታቸው የአብርሃም ልጆች ነን ይላሉ፤ ነገር ግን የአብርሃምን ሥራ ሊሠሩ አልቻሉም፡፡ “ይህ ሕዝብ በከንፈሩ ያከብረኛል ልቡ ግን ከእኔ የራቀ ነው” እንዲል፡፡

ስለዚህ ጌታ ከዕፀ በለሷ ዛፍ ምንም የሚበላ ፍሬ ስላላገኘ ረገማት፡፡ አንድም ጌታችን የፈለገውን ባለማግኘቱ ጉባኤ አይሁድን ረገመ፡፡ “በአንጻረ በለስ ረገማ ለኃጢአት” እንዲል፡፡ ሊቁ ቅዱስ ዮሐንስ አፈወርቅ ስለዚህ ጉዳይ እስራኤል ከበረከት ይልቅ እርግማን እንዳገኛቸው አሕዛብ ደግሞ የእግዚአብሔርን ጸጋ እንዳገኙ ሲገልጽ “አሕዛብ በእግዚአብሔር ቸርነት አበባ ሰበሰቡ፤ በአይሁድ ዘንድ ግን እሾህ ተረፈ፡፡ ይኸውም የሃይማኖት ጉድለት ነው፡፡” ብሏል፡፡

ዛሬም ገበሬ ዘርን ዘርቶ አርሞና ኮትኩቶ ከአሳደገ በኋላ የድካሙን ፍሬ እንደሚጠብቅ ሁሉ፤ እግዚአብሔር አምላካችንም በድንቅ መግቦቱ ከአሳደገን ልጆቹ የምግባርና የሃይማኖት ፍሬን ይፈልግብናል፡፡ ግን ጌታ ወደ በለስ ሕይወታችን ቢመጣ ምን ያገኝ ይሆን? ፍሬ ወይስ ቅጠል? የእግዚአብሔር ቃል ግን ለንስሐ የሚገባውን ፍሬ እንድናፈራ ያዘናልና መንፈሳዊ ሕይወታችን እንዳይደክም፣ እንዳይጠወልግ፣ እንዳይደርቅና አላስፈላጊ ሆኖ ሲገኝ ደግሞ ወደ እሳት እንዳይጣል የንስሐን ፍሬ ልናፈራ ይገባናል፡፡ ሕይወት ያለ ንስሓ ክንፍ እንደሌላት ወፍ ናትና፡፡

በንስሓ ወደ እግዚአብሔር የሚመለሱ ሰዎች ግን ይቅርታን /ምሕረትን/ ያገኛሉ፡፡ እግዚአብሔር የሚመለከተው ያለፈ ማንነታችንን ሳይሆን የዛሬውንና የወደፊቱን ሕይወታችንን ነውና፡፡ ቅዱስ ያሬድ “ኢተዘኪሮ አበሳ ዚአነ ኢኃደገነ ፍጹመ ንማስን ኄር እግዚአብሔር ኃጢአታችንን በማሰብ እንጠፋ ዘንድ ከቶ አልተወንም ቸር አምላክ ነውና” እንዲል፡፡ አዎ! እኛ በንስሓ ከተመለስን አምላካችን በኃጢአታችን ላይ አያስኬደንም፤ እርሱ የኃጢአታችንን አድራሻ ክረምት በፈለቀው ባሕር ውስጥ ይጥለዋልና፡፡ ሚክ.7÷18፡፡

እኛ ሰዎች ልብ ካልን በአዲሱ የዘመን መለወጫ ከተፈጥሮ እንኳ ብዙ ነገር መማር እንችላለን፡፡ አዝርእት፣ እፅዋት፣ ታድሰው፣ ቅጠላቸው ለምልሞ በአበባ ተንቆጥቁጠው እናያለን፡፡ ጋራ ሸንተረሩ አረንጓዴ ለብሶ፣ አፍላጋት በየቦታው እየተንፎለፎሉ፤ አዕዋፍ በዝማሬ፣ እንስሳት በቡረቃ ሰማይ ምድሩን ልዩ ያደርጉታል፡፡ ታዲያ ግዑዛኑ ፍጥረታት ጽጌ መዓዛቸውን የአዲስ ዓመት መሥዋዕት አድርገው ሲያቀርቡ እኛስ ምን ይዘናል?

ሰው ሠራሽ ሆኖ መዓዛ የሌለውን፣ ፍሬ የማያፈራውንና አበባ መሰሉን ሳይሆን፣ እግዚአብሔር የፈጠረውን፣ ያለመለመውንና አብቦ መልካም መዓዛ የሚሰጠውን የተፈጥሮ አበባን እንሁን፡፡ ያን ጊዜ ዝንቦች ሳይሆኑ ንቦች ማርን ለማዘጋጀት ይቀስሙናል፡፡ ስለዚህ በሃይማኖት ብቻ ያይደለ በምግባርም እናብብ፡፡ ያን ጊዜ ከዘማሪው ክቡር ዳዊት ጋር “በቸርነትህ ዓመታትን ታቀዳጃለህ ምድረ በዳውም ስብን ይጠግባል የምድረ በዳ ተራራሮችም ይረካሉ” ብለን ለመዘመር እንበቃለን፡፡ መዝ.64÷11-13፡፡

በአጠቃላይ አዲስ ዘመን የአምላክ ስጦታ /በረከት/ ነው፡፡ ስለዚህ በምድር ላይ የሚኖር ማንኛውም ሰው ዘመኑ በፈጣሪ ምልጣን የተያዘና የተገደበ ነው፡፡ ቅዱስ ዳዊት “አቤቱ እኛ አፈር እንደሆንን አስብ፤ ሰው ዘመኑ እንደ ሣር ነው፡፡ እንደ ዱር አበባም ያብባል ነፋስ በነፈሰበት ጊዜ ግን ያልፋል” በማለት ሰው ካደገ በኋላ በሕመም ፀሐይነት ይደርቅና በሞት ነፋስነት ይወለዳል፡፡ ባለፈው ዓመት ብዙዎች ወደሞት መንደር ደርሰዋል፤ እኛም እንደነርሱ መንገደኞች መሆናችንን እንርሳ፡፡

ባለቅኔው፡-
“በሉ እናንተም ሒዱ የእኛም ወደዚያው ነው ወትሮም መንገደኛ ፊትና ኋላ ነው” እንዲል፡፡

ነቢየ እግዚአብሔር ኢሳይያስም በበኩሉ “ሣሩ ይደርቃል፤ አበባውም ይረግፋል፤ የአምላካችን የእግዚአብሔር ቃል ግን ለዘለዓለም ጸንቶ ይኖራል” በማለት የሰው ሁሉ ክብሩ ሥጋዊ ሕይወቱና ተድላ ደስታው አንድ ጊዜ፣ አንድ ወቅት ለምልሞና አምሮ የሚታይ ሆኖ ሳለ ያው ደግሞ ሳይቆይ የሚጠፋ መሆኑን ያመለክታል፡፡ ኢሳ.40÷8፡፡ ስለዚህ በአዲሱ ዘመን ራሳቸውን ለከፍተኛ ግብ የሚያዘጋጁ ሁሉ ወደ ተቀደሰ መንፈሳዊ ሕይወት ሊሸጋገሩ ይገባል፡፡ ከእግዚአብሔር የተሰጠን እድሜም የአጭር ጊዜ እንግዳ መሆናችንን ስለሚያስገነዝበን የምንሸኘውም እንዲሁ ባልታወቀ ጊዜ ውስጥ መሆኑን በመረዳት እውነተኛ ሃሳባችንና ሥራችንን ለተተኪው ትውልድ የማይረሳ አስመስጋኝ ቅርስ መሆን አለበት፡፡

እንዲህ ዓይነቱ መልካምነት ደግሞ ለክርስቲያን በአዲሱ ዘመን እንደሎተሪ ዕጣ የሚደርሰው ሳይሆን ራሱ ፈልጐ የሚሆነው ነው፡፡ ስለዚህ ይልቁንም በአሁኑ ዘመን በመጽሐፍ ቅዱስ የተጻፈው ሁሉ ፍጻሜ እያገኘ ባለበት ዘመን ፍቅር በጠፋበት ዘመን አብዛኛው ሕዝብ ለማይረባ ነገር ብሎ ደገኛ ሃይማኖቱን እየለቀቀ ወደ አልባሌ ቦታ ሲገባ የሕይወት ለውጥ ማምጣት ያስፈልጋል፡፡ እኛ በአዲሱ ዓመት የሕይወት ለውጥን ካሳየን የእግዚአብሔር ጸጋ በውስጣችን ሥራውን በመጀመር በአንድ ሰንሰለት ላይ በርካታ የሕይወት ለውጥን ያመጣልናል፡፡ ይህ የሕይወት ለውጥ በአዲሱ ዘመን ውስጥ ለመኖሩ ተግባራዊ መለኪያው ደግሞ ቀጣይነቱ፣ ፍጹም ተጋድሎውና ግልጽ መሆኑ ነውና ራሳችንን እንመርምር፡፡ 1ጢሞ.4÷7፡፡

ባለቅኔው፡-

“አዲስ ሰው ስትሆን ጽድቅን ሳታፈራ እንዲያው እንደታጠርክ በክፋት ወጋግራ አሮጌውን ሳትጥል አዲስ መደረቱ የዘመን ቅበላ ይቅር ምናባቱ!” እንዲል፡፡

የዚያች የወይን ጠባቂ “ወደፊት ብታፈራ ደህና ነው ያለበለዚያ ግን ትቆርጣታለህ” እንዳለ ለነፍሳችን አንድ ነገር ሳንይዝ፣ ዘመናችን እንዳያረጅና እንዳይቆረጥ ዛሬ ለበጐ ሥራ እነነሣ፡፡ መጥመቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ አሁንም “ምሳር በዛፎች ሥር ተቀምጧል፤ እንግዲህ መልካም ፍሬ የማያደርግ ዛፍ ሁሉ ይቆረጣል፤ ወደ እሳትም ይጣላል” ይላልና፡፡ ማቴ.3÷10 እነሆ ! ዛሬ ግን እንደ እግዚአብሔር ቸርነት አሮጌውን ዓመት አሳልፈን ለአዲሱ ዓመት በቅተናል፡፡ ስለዚህ አዲሱን ዓመት በመንፈሳዊ ሕይወታችን ጐልምሰን፣ ሁላችንም ለተቀደሰ ዓላማ ተሰልፈን፣ ከክፉ ምግባራችንም ተመልሰን የምንቀደስበት የምንባረክበት የሰላም፣ የጤናና የደስታ ዘመን ያድርግልን አሜን!!

Emebetachin-Eriget

«ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ ሞታ ለማርያም የዐጽብ ለኲሉ»

መ/ር ሳሙኤል ተስፋዬ

ነሐሴ 15/2003 ዓ.ም

Emebetachin-Erigetፆመ ፍልሰታ የእመቤታችን ዕረፍት፣ ትንሣኤና ዕርገቷ የሚታሰብበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ ወቅት ምእመናንን ከአካባቢያቸው ራቅ ብለው በተለያዩ ገዳማትና አድባራት በመሄድ አሊያም በአጥቢያቸው በመሰባሰብ እመቤታችን ለሐዋርያት በተለያዩ ጊዜያት ተገልጻ ሞትና ትንሣኤዋን የገለጸችበትን ሁኔታ ያስባሉ፡፡ ጌታም እናቱን መንበር አድርጎ ቀድሶ ማቁረቡን ይዘክራሉ በዚህ ወቅት በፆም በጸሎት ተወስነው የልጇን ቸርነት የድንግልን አማላጅነት ይማጸናሉ፡፡ ሁሉም እንደሚደረግላቸው ያምናሉ፡፡ የሱባኤው ወቅት ሲፈጸም «በእውነት ተነሥታለች» ብለው በደስታ የፆሙን ወቅት ይፈጽማሉ፡፡

 

 

ሞትና ትንሣኤዋ እንዴት ነው ቢሉ፡-
የእመቤታችን ቅድስት ድንግል ማርያምን ሞትና ትንሣኤ ነገረ ማርያም፣ ስንክሳር እና ተኣምረ ማርያም እንደሚያስረዱት፤ ጥር 21 ቀን ዐርፋለች፡፡ ሞቷ የሚያስደንቅ መሆኑን ታላቁ የቤተክርስቲያናችን አባት ቅዱስ ያሬድ  «ሞትሰ ለመዋቲ ይደሉ ሞታ ለማርያም የሐጽብ ለኲሉ፤ ሞት ለማናቸውም ሰው ሁሉ የተገባ ነው የማርያም ሞት ግን ሁሉን ያስደንቃል» በማለት ገልጾታል፡፡

ቅዱሳን ሐዋርያት የእመቤታችንን የከበረ ሥጋዋን ገንዘውና ከፍነው ለማሳረፍ ወደ ጌቴሴማኒ መካነ ዕረፍት (የመቃብር ቦታ) ይዘው ሲሄዱ አይሁድ በቅንአት መንፈስ ተነሣሥተው «ቀድሞ ልጇን በሦስተኛው ቀን ከሙታን ተነሣ፤ በዐርባኛው ቀን ወደ ሰማይ ዐረገ እንደገናም ተመልሶ ይህን ዓለም ለማሳለፍ ይመጣል  እያሉ ሲያውኩን ይኖራሉ፡፡ አሁን ደግሞ እርሷንም እንደ ልጇ ተነሣች፣ ዐረገች እያሉ ሲያውኩን ሊኖሩ አይደለምን) ኑ ተሰብሰቡና ሥጋዋን በእሳት እናቃጥላት» ብለው ተማክረው መጡ፡፡

ታውፋንያ የሚባል አይሁዳዊ የከበረ ሥጋዋን የተሸከሙበትን አጎበር (የአልጋ ሸንኮር) በድፍረት ያዘ፡፡ የእግዚአብሔር መልአክ በእሳት ሰይፍ ሁለት እጆቹን ቆረጣቸው፡፡ እጆቹ ተንጠልጥለው ከቆዩ በኋላ በእውነት የአምላክ እናት ናት በማለት ስለ አመነ እጆቹ ተመልሰው እንደነበሩ ሆነውለታል፡፡ ከዚህ በኋላ መልአከ እግዚአብሔር የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ  ከሐዋርያው ዮሐንስ ጋር ነጥቆ ወስዶ በገነት ከዕፀ ሕይወት ሥር አስቀመጠው፡፡ ቅዱስ ዮሐንስም ከጥቂት ጊዜ በኋላ ወደ ሐዋርያት ሲመጣ የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ በገነት መኖሩን ነገራቸው፡፡  ሐዋርያትም የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ አግኝተው  ለመቅበር በነበራቸው ምኞትና ጉጉት  ዮሐንስ አይቶ እኛ እንዴት ሳናይ እንቀራለን ብንጠየቅስ ምን እንመልሳለን በማለት በነሐሴ አንድ ቀን ሱባኤ ጀምረው ሲጾሙና ሲጸልዩ ከሰነበቱ በኋላ በ14 (በሁለተኛው ሱባኤ መጨረሻ) ጌታችን የእመቤታችንን ትኩስ የከበረ ሥጋ አምጥቶ ስለሰጣቸው በታላቅ ዝማሬ፣ በውዳሴ ወስደው ቀድሞ በተዘጋጀው መካነ ዕረፍት  በጌቴሴማኒ ቀበሯት፡፡

የእመቤታችን የቀብር ሥነ ሥርዐት በተፈጸመ ጊዜ ከ12ቱ ሐዋርያት አንዱ የሆነው ቅዱስ ቶማስ አልነበረም፡፡ ከሀገረ ስብከቱ በደመና ተጭኖ ወደ ኢየሩሳሌም ሲመጣ፣ እመቤታችን በተቀበረች በሦስተኛው ቀን  እንደ ልጇ ትንሣኤ ተነሥታ ስታርግ ያገኛታል፡፡ ቀድሞ የልጅሽን አሁን ደግሞ የአንቺን ትንሣኤ ሳላይ ቀረሁ ብሎ ቢያዝን እመቤታችን ከእርሱ በቀር ሌሎች ሐዋርያት ትንሣኤዋን እንዳላዩ ነግራው ቅዱስ ቶማስን አጽናናችው፡፡ ሄዶም ለሐዋርያት የሆነውን ሁሉ እንዲነግራቸው አዝዛው ለምልክት ይሆነው ዘንድ የተገነዘችበትን ሰበኗን ሰጥታው ወደ ሰማይ ዐርጋለች፡፡

ልበ አምላክ ቅዱስ ዳዊት የእመቤታችን ትንሣኤ አስቀድሞ በትንቢት መስታወትነት ታይቶት «ተንሥእ እግዚኦ ውስተ ዕረፍትከ አንተ ወታቦተ መቅድስከ፤ አቤቱ ወደ ዕረፍትህ ተነሥ አንተና የመቅደስህ ታቦት» (መዝ.131፥8)፡፡  ነቢዩ ዳዊት ይህን ቃለ ትንቢት  አስቀድሞ ክርስቶስ እንደሚነሣ ከገለጸ በኋላ ቀጥሎ የመቅደሱ ታቦት እናቱ ቅድስት ድንግል ማርያም እንደምትነሣ ይናገራል (ማቴ5፥35፤ ገላ 4፥ 26፤ ዕብ 12፥22፤ ራዕ 3፥12)፡፡

ወደ ቀደመ ነገራችን እንመለስና ቅዱስ ቶማስም ሐዋርያት ወደ አሉበት ኢየሩሳሌም በደረሰ ጊዜ «የእመቤታችን ነገር እነዴት ሆነ?»  ብሎ ቢጠይቃቸው፤ «እመቤታችንን እኮ ቀበርናት» ብለው ነገሩት፡፡ እርሱም ዐውቆ ምስጢሩን ደብቆ «አይደረግም ሞት በጥር በነሐሴ መቃብር  እንደምን ይሆናል?» አላቸው፡፡ ቅዱስ ጴጥሮስ አንተ መጠራጠር ልማድህ ነው፡፡ ቀድሞ የጌታን ትንሣኤ ተጠራጠርክ አሁንም አታምንም ብሎ  የእመቤታችን መካነ መቃብር ሊያሳዩት ይዘውት ሔዱ፡፡ መቃብሩን ቢከፍቱ የእመቤታችንን የከበረ ሥጋ አጡት፤ ደነገጡም፡፡ በዚህ ጊዜ ቅዱስ ቶማስ «አታምኑኝም ብዬ ነው እንጂ እመቤታችንስ ተነሥታ ዐርጋለች» ብሎ  የሆነውን ሁሉ ተረከላቸው፡፡ ከዚያም ምልክት እንዲሆን የሰጠችውን ሰበኗን አሳያቸው፡፡ እነርሱም ማረጓን አምነው ሰበኗን ለበረከት ከተከፋፈሉ በኋላ ወደየአህጉረ ስብከታቸው ሄዱ፡፡ በየሀገረ ስበከታቸውም ሕሙማንን ሲፈውሱበትና ገቢረ ተአምር ሲያደርጉበት ኖረዋል፡፡

በዓመቱ ትንሣኤሽን ቶማስ አይቶ እንዴት ይቅርብን ብለው ነሐሴ አንድ ቀን ጀምሮ ሱባኤ ገቡ፡፡ በሱባኤው መጨረሻ ነሐሴ 16 ቀን ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የለመኑትን ልመና ተቀብሎ እመቤታችንን መንበር፣ ቅዱስ ጴጥሮስን ንፍቀ (ረዳት) ቄስ)፣ ቅዱስ እስጢፋኖስን ገባሬ ሰናይ (ዋና) ዲያቆን አድርጎ ቀድሶ አቁርቦአቸዋል፡፡ ከዚህ በኋላ እመቤታችንን ሐዋርያት በግልጽ ትንሣኤዋን ዕርገቷን እያዩዋት ከጌታችን ጋር በክብር በይባቤና በመዝሙር ወደ ሰማይ ዐርጋለች፡፡ ቅዱስ ያሬድ በመዝሙሩ «እመቤታችን ድንግል ማርያም ከምድር ወደ ሰማይ ዐረገች በሰማይም ከልጇ ጋር በአብና በመንፈስ ቅዱስ ቀኝ ተቀመጠች»፡፡

የእመቤታችን ትንሣኤ፣ ዕርገት ልዩ የሆነበት ምስጢር
በመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት መሠረት ትንሣኤ ጊዜያዊና ዘለዓለማዊ በመባል ይታወቃል፡፡ ጊዜያዊ ትንሣኤ የሚባለው የእግዚአብሔር ከሃሊነት የሚገለጽበት ተኣምራዊ ሥራ ሆኖ በተወሰኑ ሰዎች ላይ ይፈጸምና ዳግም ሞትን የሚያስከትል ነው፡፡ ለምሳሌ ኤልያስ ያስነሣውን ወልደ መበለት (1ኛ ነገ 17፥8-24) ዐጽመ ኤልሳዕ  ያስነሣውን ሰው (2ኛነገ 13፥20፦21) ትንሣኤ ወለተ ኢያኢሮስን (ማቴ 9፥ 8-26) በዕለተ ስቅለት ከመቃብር ወጥተው በቅድስት ከተማ የታዩ ሙታን (ማቴ 27፥52-53) በቅዱስ ጴጥሮስ ጸሎትና ምልጃ የተነሣች ጣቢታን (ሐዋ ሥ 9፥36-41) እንዲሁም ትንሣኤ አልዓዛርን መጥቀስ ይቻላል፡፡

አልዓዛር ከሞተ በኋላ በአራት ቀን እንደተነሣ ወንጌላዊው ቅዱስ ዮሐንስ ጽፏል፡፡ «በታላቅ ድምፅ አልዓዛር ሆይ ወደ ውጭ ና ብሎ ጮኸ፡፡ የሞተውም እጆቹና እግሮቹ  በመግነዝ እንደተገነዙ ወጣ፤ ፊቱም በጨርቅ እንደተጠመጠመ ነበር፡፡ ኢየሱስም ፍቱትና ይሂድ ተውት አላቸው(ዮሐ 11፥43-44)፡፡  ኢየሱስ ክርስቶስ ሲያነሣውም ለማየት በመቃብሩ ዙሪያ የነበሩ አይሁድ ከሞተ በኋላ በአራት ቀን መነሣቱን ተመልክተው አደነቁ የአልዓዛር እኅቶችም  ተደሰቱ፡፡ አልዓዛር ግን ለጊዜው ቢነሣም ቆይቶ ተመልሶ ዐርፏል ወደፊት ትንሣኤ ዘጉባኤ ይጠብቀዋል፡፡

የቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ የክብርና የሕይወት ትንሣኤ ሲሆን ሁለተኛ ሞትን አያስከትልም ትንሣኤ ዘጉባኤንም አይጠብቅም፡፡ መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ የትንሣኤያችን በኩር ሆኖ በሞተ በሦስተኛው  ቀን ተነሥቷል፡፡ እናቱ እመቤታችንም በልጇ ሥልጣን፤  እንደ ልጇ ትንሣኤ በሦስተኛው ቀን ተነሥታ ትንሣኤ ዘጉባኤን ሳትጠብቅ በክብር ዐርጋለች፡፡  እንደዚህ ያለውን ትንሣኤ ከእርሷ በቀር ሌሎች ቅዱሳን ወይም ነቢያትና ሐዋርያት አላገኙትም በዚህም ሁኔታ የቅድስት ድንግል ማርያም ትንሣኤ ከማናቸውም ትንሣኤ ልዩ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ይህም ትንሣኤ ዘለዓለማዊ የሆነ ከዳግም ሞተ ሥጋ ነጻ የሆነ ትንሣኤ ነው፡፡

ስለ ቅድስት ድንግል ማርያም ከመቃብር መነሣት ነሐሴ 16 ቀን የሚነበበው መጽሐፈ ስንክሳር እንደሚያስረዳን አባቷ ዳዊት በገናውን እየደረደረ ጸሐፊው የነበረው ዕዝራም መሰንቆውን ይዞ ቅዱሳን መላእክት ነቢያትና ጻድቃን እያመሰገኗት በብሩህ ደመና ወደ ሰማይ ዐረገች ከዚያም በክብር ተቀመጠች፡፡ በዚያም ስፍራ ሁለተኛ ሞት ወይም ሐዘን ጩኸትና ስቃይ የለም የቀደመው ሥርዐት አልፎአልና (ራዕ 21፥4-5)፡፡

የእመቤታችን ዕርገትም በመጽሐፍ ቅዱስ ከተገለጸው ከእነ ሄኖክና ኤልያስ ዕርገት የተለየ ነው፡፡  ሄኖክ ወደ ሰማይ ያረገው በምድር ሳለ እግዚአብሔርን በእምነቱና በመልካም ሥራው ስለአስደስተና በሥራውም ቅዱስ ሆኖ ስለተገኘ ሞትን እንዳያይ ዐረገ፡፡ ወደፊት ገና ሞት ይጠብቀዋል ሞቶም ትንሣኤ ዘጉባኤ ያስፈልገዋል፡፡ «ሄኖክ ሞትን እንዳያይ በእምነት ተወሰደ እግዚአብሔርም ስለ ወሰደው አልተገኘም» (ዕብ 11፥5)፡፡

ነቢዩ ኤልያስም በእሳት ሠረገላ ተነጥቋል «እነሆ የእሳት ሠረገላና የእሳት ፈረሶች በመካከላቸው ገብተው ከፈሉአቸው፤ ኤልያስም በአውሎ ነፋስ ወደ ሰማይ ወጣ»  (2ኛ ነገ 2፥10)፡፡ ነቢዩ በእሳት ሠረገላም ቢነጠቅም ወደፊት ሞት ይጠብቀዋል፤ ትንሣኤ ዘጉባኤም ያስፈልገዋል፡፡

 

ኢትዮጵያዊው ሊቅ ቅዱስ ያሬድም በድርሰቱ ስለ ዕርገትዋ ጽፏል፡፡ በቃልዋ የታመነች በሥራዋም የተወደደች ቅድስት ድንግል ማርያምን መላእክት እያመሰገኗትና በመንፈሳዊ ደስታ እያጀቧት ወደ ሰማይ አሳረጓት ሲል በዘመረው መዝሙር አስረድቶናል፡፡
የእመቤታችን አማላጅነት የትንሣኤያችን በኲር የሆነው የአምላካችን ኢየሱስ ክርስቶስ ቸርነቱ ከሁላችን ጋር ይሁን አሜን፡፡