የ፳፻፲፩ ዓ.ም የአጽዋማት ባሕረ ሐሳባዊ ቀመር

በዲ/ን ታደለ ሲሳይ

በዘመናት ሁሉ የነበረው ያለውና የሚኖረው፣ ሁሉን የፈጠረ በሁሉም ያለ እግዚአብሔር ብቻ ነው፡፡ ለእርሱ በዚህን ጊዜ መኖር ጀመረ፣ በዚህን ጊዜ መኖር ያቆማል የማይባልለት የህልውናው መጀመሪያም ሆነ መጨረሻ የሌለው ዘለዓለማዊ ነው፡ “ተራሮች ሳይወለዱ ምድርም ዓለምም ሳይሠሩ ከዘላለም እስከ ዘለዓለም ድረስ አንተ ነህ”፡፡ “ኢየሱስም እውነት እውነት እላችኋለሁ አብርሃም ሳይወለድ እኔ አለሁ አላቸው፡፡”፣ ብሏል፡፡ በተጨማሪም፣ “ኢየሱስ ክርስቶስ ትናንትናና ዛሬ እስከ ዘለዓለም የሚኖር እርሱ ነውና” እንዲል /መዝ.89÷2፣ዮሐ. 8÷56-69 ዕብ.13÷8/፡፡

የሰው ልጅ ሐሳቡ፣ ንግግሩና ተግባሩ የሚከናወነው በጊዜ ነው፡፡ የጊዜያትና የዘመናት ቁጥርም ከሰው ልጅ ሕይወት ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ የጊዜያትና የዘመናት ቁጥርም ከሰው ልጅ ሕይወት ጋር የተቆራኘ ነው፡፡ ዘመን ማለት በኅሊና ሲመረመር የጊዜና የዕድሜን መጠንና ልክ የሚወስን መሆኑን መጽሐፈአቡሻኸር ያስረዳል፡፡  ይህ ዘመን የሚባለው የጊዜ ዕድሜ በስያሜው አጠራር መሠረት ኃላፊ፣ የአሁንና የትንቢት/የወደፊት/  ጊዜ ተብሎ በሦስት ክፍላተ ጊዜ ይመደባል፡፡ «ወፉካሬሁሰ ለዘመን በውስተ ልብ አርአያ ወሰን ውእቱ ለጊዜ ዕድሜ ወዝንቱሰ ጊዜ ዕድሜ ዘስሙ ዘመን ይትከፈል እመንገለ ስሙ ኅበ ሠለስቱ ክፍል ኀበ ዘኅለፈ ዘመነ ወኀበ ዘይመጽእ ወኀበ ዘሀሎሂ እንዲል[1]፡፡

ከጥንተ ፍጥረት እስከ ዳግም ምጽአት ድረስ ያለው ዘመን ሁሉ በእነዚህ ሦስት ጊዜያት ሲሠፈርና ሲቆጠር ይኖራል፡፡ ያለፈውንና የሚመጣውን ዘመን ቆጥሮና ሠፍሮ መረዳትና ማስረዳት  እንደሚገባ ሲገልጽ ደግሞ፣  “ተሰአሉ  ዘቀደሙ መዋዕለ ዘኮነ እምቅድሜክሙ እምአመ ፈጠሮሙ እግዚአብሔር ለእጓለ እመሕያው ዲበ ምድር እም አጽናፈ ሰማይ እስከ አጽናፈ ሰማይ ለእመ ኮነ ዝንቱ ነገር፤ እግዚአብሔር  ሰውን በምድር ላይ ከፈጠረው ጀምሮ ከሰማይ ዳር እስከ ዳርቻዋ ድረስ ከቶ እንዲህ ያለ ታላቅ ነገር ወይም እንደ እርሱ ያለ ተሰምቶ እንደሆነ ከአንተ በፊት የነበረውን የቀድሞው ዘመን ጠይቅ”  ተብሎ ተጽፏል /ዘዳ.4÷32 ፡፡

ልበ አምላክ ዳዊትም ያለፈውን ዘመን በማስታወስ “የድሮውን ዘመን አሰብሁ፤ የዘለዓለሙን ዓመታት አሰብሁ፤ አጠነጠንሁም” በማለት ተናግሯል /መዝ.76÷51/፡፡

ዳግመኛም ይህ ዓመታትን ቆጥሮ ዘመኑን ያወቀው ልበ አምላክ ዳዊት ሲጸልይ፣ “ንግረኒ ውኅዶን ለመዋዕልየ፤ የዘመኔን አነስተኛነት ንገረኝ” ብሏል/መዝ.101÷23፡፡ ክቡር ዳዊት የዘመኑን ቁጥር ሲያሰላ እየቀነሰ እንደሚሔድ ገብቶታል፡፡ ይህ ግን ከኃጢአቱ የተነሣ አይደለም፡፡ ይልቁንም ስለ እርሱ የተጻፈው ምሥክርነት “ዳዊትም በራሱ ዘመን የእግዚአብሔርን አሳብ ከገሰገሰ በኋላ አንቀላፋ”  ይላል/ሐዋ.13÷37/፡፡ ይህ ደግሞ ዘመንን ታረዝማለች፡፡ እንዲል /ምሳ.10÷27/

በመሆኑም ኦርቶዶክሳውያን አባቶቻችንን ሥርዓት ጠብቀን፣ ሕገ እግዚአብሔርን አክብረን፣ እግዚአብሔር ሠፍሮ የሰጠንን ዘመን እርሱ በገለጸልን አቆጣጠር እየተጠቀምን በየዓመቱ አጽዋማትን እንጾማለን፣ በዓላትን እናከብራለን፡፡ በመሆኑም እንደእስካሁኑ ሁሉ ዛሬም የ2011 ዓ.ም አጽዋማትንና በዓላትን እንደሚከተለው እናወጣለን፡፡

                                                                  መባጃ ሐመር
ለአጽዋማትና በዓላት ማውጫ ወሳኝ የሆነው ነጥብ መባጃ ሐመር ነው፡፡ መባጃ ሐመር መባጊያ ሐመር እየተባለም ይጠራል፡፡ መባጊያ ሐመር ሲሆን የበጋ መመላለሻ የሚል ትርጉም ይሰጣል፡፡ በሌላ በኩል መባጃ በራሱ ማቆያ፣ ማክረሚያ ተብሎ ይተረጎማል፡፡

ሐመር መርከብ፣ መጓጓዣ የሚለውን ትርጉም ያስገኛል፡፡ መባጃ ሐመር የመጥቅዕና የዕለታት ተውሳክ ድምር ሆኖ አጽዋማትና በዓላት የሚውሉበትን ቀን ያመለክታል፡፡ በሐመር የተመሰለውም አጽዋማትና በዓላት ወደ ላይና ወደታች የሚመላለሱበት ሥርዓት /መርከብ/ ስለሆነ ነው፡፡

በአጠቃላይ መባጃ ሐመር ማለት የአጽዋማትንና የበዓላትን መዋያ ወይም መግቢያ ቀን ለማወቅ የሚያገለግል ልዩ ቁጥር ማለት ነው፡፡ [2]

ከሰባቱ አጽዋማት መካከል አራቱ በመባጃ ሐመር መሠረት በየዓመቱ እየተቀያየሩ ወይም ቀመር እየተሠራላቸው የሚወጡ ሲሆን፣ ሦስቱ ግን ያለ መባጃ ሐመር በየዓመቱ በተመሳሳይ ወቅት ይባጃሉ፡፡

በመባጃ ሐመር የሚባጁት አራት አጽዋማት ዐቢይ ጾም፣ ጾመ ድኅነት፣ ጾመ ነነዌና ጾመ ሐዋርያት ሲሆኑ፣ ያለ ማባጃ ሐመር በየዓመቱ ቋሚ ጊዜ ይዘው የሚብቱት ሦስቱ አጽዋማት ደግሞ ጾመ ነቢያት፣ ጾመ ገሃድና ጾመ ማርያም /ፍልሰታ/ ናቸው፡፡

ከላይ በተመለከትነው መሠረት መባጃ ሐመር የአጽዋማትና የበዓላት ማስገኛ ልዩ ቁጥር ነው ካልን ቁጥሩ እንዴት እንደሚገኝ ማወቅ ያስፈልገናል፡፡ መባጃ ሐመርን ለማግኘት መጥቅዕንና በዓለ መጥቅዕ የዋለበትን ዕለት ተውሳክ እንደምራለን፡፡ ይቆየን

ተውሳክ
ተውሳክ ማለት ለአንድ ጾም ወይም ለአንድ ዕለት የተሰጠ ልዩ ቁጥር (ኮድ) ማለት ነው፡፡ በዚህ ቁጥር መሠረትም አጽዋማትንና በዓላትን ማውጣት ይቻላል፡፡

ተውሳክ ማለት ጭማሪ፣ ተጨማሪ ማለት ሲሆን ለበዓላትና ለአጽዋማት ማውጫ ያገለግላል፡፡[3] እንዲል፡፡

መጥቅዕ ማለት ነጋሪት ወይም ደወል ማለት ነው፡፡ ነጋሪት ሲመታ፣ ደወል ሲደወል ሕዝብ ይሰበሰባል፤ መልእክትም ይተላለፋል፡፡ በዓላትና አጽዋማትም በመጥቅዕ ይሰበሰባሉ፤ መዋያቸውንም በዚህ ማወቅ ይቻላል፡፡ በዚህም መሠረት መጥቅዕ ከዕለታት ተውሳክ ጋር ተደምሮ መባጃ ሐመርን ያስገኛል፡፡

      መባጃ ሐመር = መጥቅዕ + በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት ተውሳክ

መጥቅዕ= ያለፈው ዓመት መጥቅዕ + ጥንተ መጥቅዕ (ጥንተ መጥቅዕ በየዓመቱ የማይቀያየር ቁጥር ሲሆን ይኸውም 19 ነው፡፡)

መጥቅዕን በዚህ መንገድ ማግኘት ከቻልን፣ በዓለ መጥቅዕ እንዴት እንደሚገኝ አሁን እንመለከታለን፡፡

‹‹መጥቅዕ ሲበዛ ከመስከረም ንዛ፤ መጥቅዕ ሲያንስ ጥቅምትን ዳስ››

ይህ ታላቅ መልእክት ያለው የአባቶቻችን አባባል ሲሆን ለበዓለ መጥቅዕ ማውጫ የሚያገለግል ንግግራዊ ፎርሙላ ወይም ቀመር ነው፡፡ መጥቅዕ ሲበዛ ከመስከረም ንዛ ማለት በዓለ መጥቅዕን በጥቅምት አውል ማለት ሲሆን፣ መጥቅዕ ሲያንስ ጥቅምትን ዳስ ማለቱ መጥቅዕ ባነሰ ጊዜ በዓለ መጥቅዕን በጥቅምት አውለው ማለት ነው፡፡

መጥቅዕ በዛ የሚባለው ከዐሥራ አራት በላይ ሲሆን ነው፤ አነሰ የሚባለው ደግሞ ከዐሥራ አራት በታች ሲሆን ነው፡፡ በዚህም መሠረት መጥቅዕ ከዐሥራ አራት በላይ ከሆነ በዓለ መጥቅዕ በመስከረም ይውላል፤ መጥቅዕ ከዐሥራ አራት በታች ከሆነ ደግሞ በዓለ መጥቅዕ በጥቅምት ይውላል፡፡ ይህ ሁል ጊዜም ቢሆን የሚያገለግል ሕግ ነው፡፡ ለዚህም ነው አበው ‹‹መጥቅዕ ሲበዛ ከመስከረምንዛ፤ መጥቅዕ ሲያንስ ጥቅምትን ዳስ›› ያሉት፡፡

ለምሳሌ የ2011ን መባጃ ሐመር እንፈልግ፡፡

መባጃ ሐመርን ከመፈለጋችን በፊት ግን መጥቅዕን ማወቅ የግድ ነው፡፡ መጥቅዕን ለማወቅ ደግሞ የወንበርን ዓመታዊ ስሌት ማግኘት ያስፈልጋል፡፡ በመሆኑም፤

ወንበር = ቅልክ+ድልክ – 1

19

=5500+2011 -1

19

=395 ቀሪ 6-1

ወንበር =5

የ2011 ወንበር 5 ነው ማለት ነው፡፡

ከዚህ በመነሣት መጥቅዕን ለማግኘት፤

መጥቅዕ= ወንበር (ጥንተ መጥቅዕ)

= 5(19)

30

= 3 ቀሪ 5

መጥቅዕ = 5

መባጃ ሐመር = መጥቅዕ + በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት ተውሳክ

መጥቅዕ = 5

በዓለ መጥቅዕን ለማግኘት፤ መጥቅዕ ከዐሥራ አራት በታች ስለሆነ ጥቅምት ላይ በዓለ መጥቅዕ ይውላል፡፡ ስለዚህ ጥቅምት 5 ሰኞ በዓለ መጥቅዕ ሲሆን፤ ይህ በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት ሰኞ ተውሳኩ 6 ነው ማለት ነው፡፡

ስለዚህ፤

መባጃ ሐመር = መጥቅዕ + በዓለ መጥቅዕ የዋበት ዕለት ተውሳክ

መጥቅዕ = 5

በዓለ መጥቅዕ የዋለበት ዕለት = ሰኞ

የሰኞ ተውሳክ = 6

መባጃ ሐመር = 5 + 6 = 11

ስለዚህ የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር 11 ስለሆነ በዚህ መሠረት የ2011ን በዓላትና አጽዋማት ማውጣት ይቻላል፡፡

የመባጃ ሐመር ዋነኛ አገልግሎት ከአጽዋማት ተውሳክ ጋር እየተደመረ በዓላትንና አጽዋማትን ማስገኘት ነው፡፡ ስለዚህ የአጽዋማትንና የበዓላትን ተውሳክ ማወቅ ይጠበቅብናል፡፡በመሆኑም መባጃ  ሐመሩንና የበዓላትና የአጽዋማትን ተውሳክ በመጠቀም የ2011ን የበዓላትና የአጽዋማትን መግቢያ እናገኛለን፡፡

ጾመ ነነዌ
ጾመ ነነዌ የራሱ የሆነ ተውሳክ የለውም፡፡ የሚወጣውም ያለ ተውሳክ በመባጃ ሐመር ብቻ ነው፡፡

ሀ. በዓለ መጥቅዕ በመስከረም በሚውልበት ጊዜ ጾመ ነነዌ በጥር ይውላል፡፡

ለ. በዓለ መጥቅዕ በጥቅምት በሚሆንበት ጊዜ ጾመ ነነዌ በየካቲት ይውላል፡፡

ሐ. መጥቅዕ ከ፲፬(14) በላይ ሆኖ ከዕለት ተውሳክ ጋር ስንደምረው ከ፴(30) ከበለጠ ጾመ ነነዌ በየካቲት ይውላል፡፡

ከላይ የተዘረዘሩት አራት ነጥቦች መቼም ቢሆን የማይለወጡ ቋሚ ሕጎች ናቸው፡፡ በመሆኑም እነዚህን አራቱን በቃል አጥንቶ መያዝ ያስፈልጋል፡፡

ምሳሌ፡- ከላይ የተመለከትነውን የ2011 ዓ.ምን ጾመ ነነዌ እናውጣ፡፡

መጥቅዕ 5 ሲሆን በዓለ መጥቅዕ ጥቅምት ሰኞ ነው፡፡ መባጃ ሐመሩ ደግሞ 11 ነው፡፡ ከላይ በ‹‹ለ››እንደተመለከትነው በዓለ መጥቅዕ በጥቅምት በሚሆንበት ጊዜ ጾመ ነነዌ በየካቲት ይውላል ብለናል፡፡ በተጨማሪም ጾመ ነነዌ ተውሳክ ስለሌላት በመባጃ ሐመርብቻ ነው የምትወጣ ብለናል፡፡ ስለዚህ መባጃ ሐመሩ 11 ስለሆነ የካቲት 11 ቀን ጾመ ነነዌ ትገባለች ማለት ነው፡፡

ዐቢይ ጾም
የዐቢይ ጾምን ተውሳክ ለማግኘት ከጾመ ነነዌ ማግስት ጀምሮ እስከ ዐቢይ ጾም ያሉትን ቀናት መቁጠር ነው፡፡ እኒህም ቀናት ፲፬(14) ናቸው፡፡ በመሆኑም የዐቢይ ጾም ተውሳክ ፲፬(14) ነው ማለት ነው፡፡

ለምሳሌ በ2011 ዓ.ም ዐቢይ ጾም የገባው፤

የዐቢይ ጾም መግቢያ = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የዐቢይ ጾም ተውሳክ

መባጃ ሐመር = 11

የዐቢይ ጾም ተውሳክ = ፲፬(14)

የዐቢይ ጾም መግቢያ = 11 + 14 = 25

የካቲት 25 የዐቢይ ጾም መግቢያ ነው ማለት ነው፡፡

ደብረ ዘይት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ዐቢይ ጾም ያሉትን ቀናት ቆጥረን የዐቢይ ጾም ተውሳክ ፲፬(14) ነው ብለናል፡፡ የደብረ ዘይትን ተውሳክ ለማግኘትም በተመሳሳይ መልኩ ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ደብረ ዘይት ያሉትን ቀናት ስንቆጥር ፵፩(41) ቀናትን እናገኛለን፡፡ ለ፴(30) ሲካፈል ቀሪ (፲፩)11ን እናገኛለን፡፡ ስለዚህ የደብረ ዘይት ተውሳክ ፲፩(11) ነው ማለት ነው፡፡

ደብረ ዘይት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የደብረ ዘይት ተውሳክ

= 11 + 11

= 22

ከየካቲት ቀጥሎ ያለው ወር መጋቢት ስለሆነ መጋቢት 22 ደብረዘይት ነው ማለት ነው፡፡

ሆሣዕና
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ሆሣዕና ያሉት ቀናት ፷፪(62) ናቸው፡፡ እንደተለመደው ለ፴(30) ስናካፍለው ፪(2) ቀሪ እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የሆሣዕና ተውሳክ (፪)2 ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ሆሣዕና መግቢያ = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የሆሣዕና ተውሳክ

= 11 + 2

= 13

ሚያዝያ 13 በዓለ ሆሣዕና ነበር ማለት ነው፡፡

ስቅለት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ስቅለት ያሉት ቀናት ሥልሳ ሰባት ናቸው፡፡ ለሠላሳ ስናካፍለው ቀሪ ፯(7)ን እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የስቅለት ተውሳክ ፯/7/ ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ስቅለት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የስቅለት ተውሳክ

= 11 + 7

= 18

ሚያዝያ 18 ስቅለት ነው ማለት ነው፡፡

ትንሣኤ
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ትንሣኤ ያሉት ቀናት ሥልሳ ዘጠኝ ናቸው፡፡ ለሠላሳ ስናካፍለው ቀሪ ፱(9) እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የትንሣኤ ተውሳክ ፱ (9) ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ትንሣኤ = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የትንሣኤ ተውሳክ

= 11 + 9

= 20

ሚያዝያ 20 ትንሣኤ ነው ማለት ነው፡፡

ርክበ ካህናት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ርክበ ካህናት ያሉት ቀናት ፺፫(93) ናቸው፡፡ ለሠላሳ ስናካፍለውቀሪ ፫(3)ን እናገኛለን፡፡ በመሆኑም የርክበ ካህናት ተውሳክ ፫(3) ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ርክበ ካህናት = የ2011 መባጃ ሐመር + የርክበ ካህናት ተውሳክ

= 11 + 3

= 14

ግንቦት 14 ርክበ ካህናት ነው ማለት ነው፡፡

ዕርገት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ በዓለ ዕርገት ያሉት ቀናት ፻፰(108) ናቸው፡፡ ፻፰(108)ን ለ፴(30) ስናካ ፍለው ፫(3) ጊዜ ደርሶ ፲፰(18) ይቀራል፡፡ በመሆኑም የዕርገት ተውሳክ ፲፰(18) ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ዕርገት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የስቅለት ተውሳክ

= 11 + 18

= 29

ግንቦት 29 ዕርገት ነው ማለት ነው፡፡

ጰራቅሊጦስ
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ጰራቅሊጦስ ያሉት ቀናት ፻፲፰(118)ናቸው፡፡ ፻፲፰(118)ን ለ፴(30) ስናካፍለው ፫(3) ቀሪ ፳፰(28) ይሆናል፡፡

፳፰(28) የጰራቅሊጦስ ተውሳክ ይሆናል፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ጰራቅሊጦስ = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የጰራቅሊጦስ ተውሳክ

= 11 + 28

= 39

ለ፴(30) ሲካፈል 9 ቀሪ ይሆናል፡፡ ጰራቅሊጦስ ሰኔ 9 ነው ማለት ነው፡፡

ጾመ ሐዋርያት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ጾመ ሐዋርያት ያሉት ቀናት ፻፲፱(119) ናቸው፡፡ ፻፲፱ (119)ን ለ፴(30) ስናካፍለው ፫(3) ጊዜ ደርሶ ፳፱ (29) ይቀራል፡፡

፳፱(29) የጾመ ሐዋርያት ተውሳክ ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ጾመ ሐዋርያት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የጾመ ሐዋርያት ተውሳክ

= 11 + 29

= 40

40 ለ30 ሲካፈል 1 ቀሪ 10 ይሆናል፡፡

ስለዚህ ሰኔ 10 የጾመ ሐዋርያት መግቢያ ነው ማለት ነው፡፡

ጾመ ድኅነት
ከጾመ ነነዌ ማግስት እስከ ጾመ ድኅነት ያሉት ቀናት ፻፳፩(121) ናቸው፡፡ ፻፳፩(121) ለ፴(30) ሲካፈል ፬(4) ጊዜ ደርሶ ፩(1) ይቀራል፡፡ የጾመ ድኅነት ተውሳክ ፩(1) ነው ማለት ነው፡፡

በ2011 ዓ.ም፤

ጾመ ድኅነት = የ2011 ዓ.ም መባጃ ሐመር + የጾመ ድኀነት ተውሳክ

= 11 + 1

= 12

ሰኔ 12 የጾመ ድኅነት መግቢያ ዕለት ነው ማለት ነው፡፡

በአጠቃላይ የአጽዋማቱ ተውሳክ እንደሚከተለው ነው፡፡

አጽዋማት       ተውሳክ           የመዋያ ዕለት

ጾመ ነነዌ        = አልቦ (0)         የካቲት 11

ዐቢይ ጾም        = ፲፬(14)           የካቲት 26

ደብረ ዘይት       = ፲፩(11)          መጋቢት 22

ሆሣዕና          = ፪(2)             ሚያዝያ 13

ስቅለት           = ፯(7)             ሚያዝያ 18

ትንሣኤ          = ፱(9)             ሚያዝያ 20

ርክበ ካህናት      = ፫(3)             ግንቦት 14

ዕርገት           = ፲፰(18)          ግንቦት 29

ጰራቅሊጦስ       = ፳፰(28)          ሰኔ 9

ጾመ ሐዋርያት    = ፳፱(29)          ሰኔ 10

ጾመ ድኅነት       = ፩(1)            ሰኔ 12

ኢየዐርግና ኢይወርድ
እነዚህ አጽዋማት ምንም እንኳን በየዓመቱ የየራሳቸው ቀመራዊ ማውጫ ቢኖራቸውም ገደብ ግን አላቸው፡፡ ገደባቸውም በግእዝ ኢይወርድና ኢየዐርግ ሲባል፣ ኢይወርድ የታችኛው እርከን፣ ኢየዐርግ ደግሞ የላይኛው እርከን ነው፡፡ በአማርኛው ገደብ ልንለው እንችላለን፡፡ በዚህም መሠረት የአጽዋማት ገደብ የሚከተለውን ይመስላል፡፡

አጽዋማትና በዓላት          ኢይወርድ    ኢየዐርግ

ጾመ ነነዌ             ጥር 17             የካቲት 21

ዐቢይ ጾም           የካቲት 1             መጋቢት 5

ደብረ ዘይት          የካቲት 28            ሚያዝያ 2

ሆሣዕና             መጋቢት 19           ሚያዝያ 23

ስቅለት          መጋቢት 24           ሚያዝያ 28

ትንሣኤ            መጋቢት 26           ሚያዝያ 30

ርክበ ካህናት        ሚያዝያ 20             ግንቦት 24

ዕርገት             ግንቦት 5                ሠኔ 9

ጰራቅሊጦስ         ግንቦት 15               ሠኔ 19

ጾመ ሐዋርያት      ግንቦት 16               ሠኔ 20

ጾመ ድኅነት        ግንቦት 18               ሠኔ 22

ቋሚ የመግቢያ ጊዜ ያላቸው አጽዋማት
                               ጾመ ነቢያት
ጾመ ነቢያት በአራቱም ዘመናት ምን ጊዜም ኅዳር ዐሥራ አምስት እንዲጾም ተወስኗል፡፡

                                   ጾመ ገሀ  ድ
ጾመ ገሀድ የትክ ጾም ነው፡፡ ይህ ጾም ዓርብንና ሮብን የሚያሽር በዓል በዓርብና በሮብ ሲውል በትኩ በዋዜማው የሚጾም ጾም ነው፡፡ ለምሳሌ ጥምቀት ዓርብ ቢውል ሐሙስ ጾመ ገሀድ ይሆናል፡፡ ነገር ግን አበው ለጾም ማድላት አለብን በማለት ጾመ ገሀድ ምንጊዜም ጥምቀት በጾም ቀን ዋለም አልዋለም በዋዜማው እንዲጾም ወስነዋል፡፡

                                   ጾመ ፍልሰታ 
ሐዋርያት የእመቤታችንን ትንሣኤ ለማየት ይበቁ ዘንድ ሱባኤ ገብተው የጾሙት ጾም ሲሆን ምንጊዜም ነሐሴ አንድ ቀን ገብቶ ከሁለት ሱባኤ በኋላ የእመቤታችን ዕርገት ይፈጸማል፡፡

[1]  አቡሻኸር አንቀጽ 1 ገጽ 17 (የብራና ጽሑፍ)

[2] ዲ/ን ታደለ ሲሳይ ባሕረ ሐሳብ በቀላል አቀራረብ ገጽ 71

[3]  ዝኒ ከማሁ ገጽ 66